አሸናፊን የራሱ የሚያደርግ ብልህ ሕዝብ

Home Forums Semonegna Stories አሸናፊን የራሱ የሚያደርግ ብልህ ሕዝብ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #15160
    Anonymous
    Inactive

    [በዚህ ጽሑፍ ላይ አማራ ብዬ የጠቀስኩት ማኅበረሰብ በአሰፋ ጨቦ ትንታኔ መሠረት ሲሆን፥ ዘርን ሳይሆን የአባቶቻችንን ድል እና ኃያልነት የተቀበለውን፣ የማሸነፍ መንፈሱ የማይደረመስ ተራራ የሆነውን፣ በየሄደበት ሁሉ የአባቶቹን ድል አድራጊነት እያሰበ የበታችነትን እንቢ ያለውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ የሚመለከት ነው።]

    አሸናፊን የራሱ የሚያደርግ ብልህ ሕዝብ

    (ሙሉዓለም ጌታቸው)

    የዛሬ አንድ ወይም ሁለት ዓመት ፌስቡክ ላይ በአንድ የኦሮሞ አክቲቪስት ተጽፎ ብዙ ሰው የተለዋወጠው ጽሑፍ ነበር። ጽሑፉ ኦሮሞ ጀግኖቹን አሳልፎ የሚሰጥ ባህል አለው ብሎ ይከራከራል። አማራ* ደግሞ የሌላን ጀግና ሳይቀር የራሱ የማድረግ፣ የማጠጋጋት ባህል አለው ይላል። ይሄ ጽሑፍ ባሰብኩት ጊዜ ሁሉ ይገርመኛል። በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ በየትኛውም ዘርፍ አንቱታን ያተረፉ ጀግኖች አብዛኛው ከኦሮሞ ናቸው፤ ነገር ግን የሚያከብራቸው እና የሚወዳቸው አማራው ወይም ሌላው ብሔር ነው። በተቃራኒው በሕይወት በነበሩበት ዘመን ሳይቀር ከሃዲ፣ የአማራ ተላላኪ እያለ ሲሰድባቸው የነበሩትን ልክ ሲሸነፉ ወይም ሲመቱ የራሱ አድርጎ የመቀበል እና ሞታቸውን የእሱ የማድረግ ባህል ቢያንስ በእኔ ዕድሜ በማውቀው የኦሮሞ ማኅበረሰብ ውስጥ የሰረጸ ባህል ይመስላል።

    ኃይሌ ፊዳ ጎበና እየተባለ መከራውን እንዳየ እንደተሰደበ ደረግ ጭዳ አደረገው። አሁን ደግሞ ለብዙ የኦሮሞ የዘመኑ ጎበዞች ጃዋርን ጨምሮ ኃይሌ ፊዳ የኦሮሞ ጀግና እየተደረገ ሲቀርብ እና ለትግል ማነሳሻ ሲውል መመልከት የተለመደ ሆኗል። “The Ethiopian Revolution and Its Implication” በሚል ርዕስ በአሜሪካው የስለላ ተቋም ሲ.አይ.ኤ. (CIA) እ.ኤ.አ. በማርች 1977 (March 1977) ተዘጋጅቶ በጥብቅ ምስጢርነት ለአሜሪካው የሥራ አስፈጻሚው አካል የቀረበው ሰነድ መንግስቱ ኃይለማርያም ኦሮሞ እንደሆነ ከገለጸ በኋላ፥ በንጉሡ ወዳጆች ከስልጣን የሚፈነቀል ከሆነ “በኦሮሞነቴ” ወይም “ኦሮሞ” ስለሆንኩ ከስልጣን አባረሩኝ ብሎ ዘሩን ሊጠቀምበት እንደሚችል ትንቴውን ያቀርባል። “እንደዚህ ዓይነት አደጋ ካልገጠመው ግን ኦሮሞነቱን የማሳየት (ለስልጣን ሲል ማለቱ ነው) ዝንባሌ አይታይበትም” ይላል የስለላው ሰነድ። ተመልከቱ የሚሸነፍ ከሆነ በኦሮሞ የዘር ጉርጓድ ውስጥ ሊደበቅ ይችላል እያለን ነው (ሽንፈቱን እንጂ ድሉን ለኦሮሞ ለመስጠት ፈቃደኛ አልነበረም ማለቱ ነው)። ይሄ በዘመኑ ሳይቀር በራሳቸው የዓለም ትግል ሲሸነፉ ኦሮሞነታቸውን (ዘራቸውን) ለውድቀታቸው ሰበብ የማቅረብ ዝንባሌ እንዳለ ከማሳየቱ ባሻግር፥ ሲሸነፉ የራሱ የሚያደርጋቸው ማኅበረሰብ እንዳለ ይነግረናል።

    ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከአባታቸው መኮንን ጉዲሳ የተወለዱ ኦሮሞ ናቸው። በዓለም የተደነቁ፣ ዘመናዊ ኢትዮጵያን በዘመናዊ ተቋም የመሠረቱ፣ እጅግ አስደናቂ መሪ ናቸው። ኢትዮጵያ በእሳቸው ጊዜ የነበራትን ዝና ለመመለስ ቢያንስ 100 ዓመት በትንሹ ሊያስፍልጋት ይችላል፤ እሱም ጠንክረን ከሠራን። በርግጥ ፍጹም ሥልጣን የሚወዱ በመሆናቸው ፍጻሜያቸውን ክፉ አደረጉት። ንጉሡን የሚወዳቸው እና የራሱ ያደረጋቸው ግን ማነው? አማራው! በእሳቸው ዘመን ክፉኛ የተጨፈጨፉ ሁለት አመጾች አሉ። አንዱ የቀዳማይ ወያኔ ትግል በትግራይ ሲሆን ሌላኛው የጎጃም አመጽ ነው። የጎጃምን አመጽ ድባቅ የመቱበት ዘግናኝ ክስተት የታሪክ ጸሐፊዎች እንኳ ቃላት ያጡለት ነው። ግን ዛሬ ለሃውልታቸው መሠራት፣ ለስማቸው ክብር የሚቆመው ይሄው አማራው ነው። ምክንያቱም ጀግናን የራሱ የማድረግ ሥነ-ልቦና አለው። ሰቅለው ለገደሉት ለበላይ ዘለቀ እየዘፈነ ፥ ለእሳቸው ክብርና ዝና ዜማ ሲያወርድ ምንም አይጣላበትም። ድንቅ ሥነ-ልቦና። ኦሮሞው ደግሞ የመኮንን ጉዲሳን ሃውልት ሐረር ላይ አፍርሶ፣ ሰው ሀገር ላይ ሎንደን (London) ደግሞ የሳቸውን ያፈርሳል። ምክንያቱም ተሸናፊን እንጂ አሸናፊን የመቀበል ሥነ-ልቦና አላወረሱትም። የተቆረጠ የጡት ሃውልት ለልጆቹ ዘወትር እያሳየ፥ በባዶ እግሩ የሚሄድ ከእሱ በምንም የማይሻለው አማራ አደረገው ይላቸዋል። ልጅ በውስጡ ፍርሃት ይሰርጽበታል። የተሸናፊው ዘር አባል መሆኑ በራሱ የሚፈጥርበት የሥነ-ልቦና ቀውስ ቀላል አይደለም። ከዛ ሕይወቱን በጥላቻ መነጽር መመልከት ይጀምራል። ጥላቻ ደግሞ የሽንፈት ዋስታና ነው።

    በቅርቡ ቤት ውስጥ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በእናቱ አማራ ነው እያለች አንድ ዘመዳችን በደስታ ትፈነድቃለች። ጠቅላዩ ብዙም አልቆየም፤ በOBN ላይ ቀርበው በእናታቸውም በአባታቸውም ኦሮሞ እንደሆኑ ገለጹ። ይሄውልሽ ተሳስተሻል ስላት፥ እሱ ነው የተሳሳተው አለችኝ። ቀጥላም የሰላም ኖቤል ሽልማት ሲቀበል አስተዋዋቂዋ በእናቱ አማራ እንዲሁም በአባቱ ኦሮሞ እያለች የተናገረችውን አሳየችኝ። ይሄ እኮ እሱ የተናገረው ሳይሆን እነሱ በስማ በለው ጽፈው ያቀረቡት ነው። ደግሞ ካስተዋልሽው በእናቱ አማራ ስትል እኮ ሳቀ። ይሄም የሚጠቁምሽ ነገር አለ ስላት፥ “ችግር የለውም እኔ ነው ብያለው፤ ነው!” አለችኝ። ይሄ አሸናፊን፣ ጀግናን የራስ የሚያደርግ፣ የሚቀበል ሥነ-ልቦና እንዲሁ በከንቱ የመጣ አይደለም፤ ሲገነባ የቆየ እንጂ። በእውቀቱ ስዩም ኢትዮጵያውያን ‘እኛ በዚህ ነገር አንደኛ ነን’ የማለት ሥነ-ልቦና አለን ይላል። “ለምሳሌ እኔ የቤቱ ሦስተኛ ልጅ ብሆንም ለሰው ስናገር ግን” ይላል፥ “ከቤታችን ሦስተኛ በመሆን አንደኛ ነኝ ብዬ ነው” በማለት የባህላችንን ራስን ከፍ የማድረግ ድንቅ ሥነ-ልቦና ይገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ነገ ቢገደል ወይም አንድ ነገር ቢያደርጉት ኦሮሞ ስለሆነ ተገደለ ብለው አሁን የምታይዋቸው እሱን የሚቃወሙ የኦሮሞ ጎበዞች የራሳቸው ጀግና ያደርጉታል። እሱም ይሄን ሥነ-ልቦና ጠንቅቆ ስለሚያውቅ ሥልጣኑ ባልጸናበት ወቅት “ከቡራዩ ጠቅላያችን ተነካ ብለው ወጣቶች ሲመጡ፥ ኦሮሞ መምራት አይችልም እያሉ” ምናምን እያለ ሆዳቸውን እያባባው ነበር። በበታችነት ሥነ-ልቦና ትልቅ ሀገር መገንባት እንደማይቻል ጠንቅቆ የሚያውቀው አብይ ይሄን “rhetoric” ብዙ አልገፋበትም። ደካማ አድርጎ ራሱን ዘወትር የሚስል ማንም፥ በዙሪያው ባሉ ሊከበር እንደማይችል ያውቃል’ና፤ በተለይ በፖለቲካ። አብይ ጠንክሮ ሲወጣ፣ ኮስታራ መሪ ሲሆን፣ ቀጥ ለጥ አድርጎ ሲገዛ ሲሰድቡት የነበሩ የአማራ አክቲቪስቶች ሳይቀሩ መልሰው በፍቅሩ እያበዱለት ነው። አማራው የተቀረጸበት እና ያደገበት ሥነ-ልቦና ከጀግንነት እና ከቆራጥነት ጋር እጅግ የተሳሰረ ነው። ባለፉት 30 ዓመታት በኦሮምኛ የተዘፈኑ እና የአማርኛ (በተለይ የባህል) ዘፈኖችን ቁጭ ብላችሁ አነጻጽሩ። አሁን የምናገረው እንደ ጉድ ይታያችኋል።

    ሀጫሉ ሁንዴሳ ከሌላው ዘፈኝ በተለየ ይሄ በጣም የገባው አዋቂ ዘፋኝ ነበር። ኦሮሞ ተገፋ፤ ጡት አስቆረጠ፤ ተኮረኮመ የሚሉ ዘፈኖች እምብዛም የሉትም። የአድዋ ድል ሲመጣ እነ ግርማ ጉተማ ይሄ ድል እኛን አይመለከተንም፤ እነ ጸጋዬ አራርሳ እኛ ለሌላ ቅኝ ግዛት የተዳረግንበት ነው ብለው በድል ቀን ሲያለቃቅሱ ሀጫሉ ግን ፈረሱ ላይ ጉብ ብሎ ባለፉት 28 ዓመታት ባልተለመደ መልኩ ይሄ ድል ከማንም በላይ የኛ ነው እያለ መስቀል አደባባይ ወጣ። የአድዋ ተራራ ሄደን ትግራይ የኛ ናት ያልነው ኦሮሞዎች ነን አለን። ታሪክ ብዙ ነገሩ ተረት ነው። ዋናው ቁም ነገር የሰው ልጅ እጅግ ኢ-ምክንያታዊ ስለሆነ ተረትም ተነገረው ታሪክ ‘አንተ እኮ ልዩ ነህ፤ አሸናፊ ነህ’ ከተባለ የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት የአልያንስ ኃይሎች (the Allies) ጀርመንን ወደ አመድነት ከቀየሯት በኋላ አንድ የጀርመን ፖለቲከኛ ለጀርመኖች ያለው ነገር ነበር። “አገራችንን ከፈሏት። ሕንጻዎቻችንን አፈራረሱት። ስልጣኔያችንን አመድ አደረጉት። ጀርመናዊ አዕምሮአችንን ግን ከኛ መውሰድ አልቻሉም” ነበር ያለው። ጀርመን ዛሬ ካፈረሰቻት እንግሊዝ በተሻለ የኢኮኖሚ ቁመና ላይ ትገኛለች። በአውሮፓ ሕብረት በኩል ትልቅ ኢምፓየር ሆና ብቅ ብላለች። እዚህ ላይለመድረስ ከአራት አስርት ዓመታት በላይ አልፈጀባትም። አይሁዶችንም በተመሳሳይ መመልከት ነው። ከናዚ (Nazi) በኋላ የመጡት የጀርመን መሪዎች ብዙዎቻችን እንደምንገምተው በናዚ በተፈጸመ በደል ክፉኛ የሚጸጸቱ አልነበሩም። ይልቁስ ያን ሁሉ ተዓምር ጀርመን መሥራቷ ኩራት የወጠራቸው፣ ድጋሚ ኃያል ሀገር እንደሚሆኑ ለአፍታም ያልተጠራጠሩ ሕዝቦች ነበሩ። Paul Berman የተባለ አሜሪካዊ ጸሐፊ  “Power and the Idealist” ብሎ በጻፈው ድንቅ መጽሐፍ መጸጸት የጀመረ ትውልድ የመጣው ጀርመን በድጋሚ በኢኮኖሚ ከአበበች በኋላ በመጣው ትውልድ ነው ይላል። ዛሬ ለገጠማቸው ከስደተኛ ጋር ለተያያዘ መጠነ ሰፊ ችግር የጸጸት ሥነ-ልቦና ያለውን አስተዋጽኦ ያብራራል። ጄኔቫ (Geneva) እያለው አለቃዬ አይርሻዊ (Irish) ነበር። እንግሊዞች እንደ እኛ የበደሉት የለም ይለኛል። ለብዙ ዘመን እንግሊዝ እንዲህ አደረገን እያልን የተበዳይነት ፖለቲካ (victim politics) ስንሠራ ኖርን። ከእንግሊዝ ተላቀን እንኳ አዕምሮአችን ከእነሱ ነጻ አልወጣም ነበር። የገነቡትን ሃውልት ማፍረስ ሥራችን አደረግን። ወይ መልሰን የራሳችንን ሃውልት አላቆምን። መንገዶቹንም ሃውልቱን በማፍረስ ከትላንት የተሻለ ውብ አላደረግናቸውም፤ አስቀየሙ እንጂ። በኋላ ግን ባነንን አለ። ያኔ ነው ማደግ እና መለወጥ የጀመርነው። ከታሪካችን ጋር ታረቅን። የእንግሊዝን ድል የእኛ ድል አድርገን መቀበል እና መተረክ ጀመርን አለኝ። ከዚያ በብዙ ነገር ለመመንደግ ጊዜ አልፈጀብንም አለኝ።

    ኢትዮጵያኖች ራሳቸውን ከድል አድራጊ እና ከትልቅ ነገር ማጠጋጋት ነበር ታሪካቸው። ይሄ ተራ ጉራ የሚመስለው ሞኝ ይኖራል። በቅርብ ያገኘሁት አንድ ሸምገል ያለ ጥቁር አሜሪካዊ ዳኛ ጋር ስናወራ ለብዙ ጊዜ በራሴ እጠራጠር ነበር አለኝ። ውስጤ ውስጥ “ትችላለህ፣ አትችልም” የሚል ከባድ ትግል ነበር። ብዙ ምሳሌ እና እኔን የሚመስሉ አርአያ የሉኝም። ቀለሜ ያለመቻል ምሳሌ ሆኖ አሜሪካ ውስጥ ቆሟል። ይሄ የውስጥ ትግል ለእኔ አሰልቺ ነበር አለኝ። ኢትዮጵያኖች “ፑሽኪንን” ኢትዮጵያዊ ነው ሲሉ ለኢትዮጵያ ሥነ-ጽሑፍ ያበረከተው ነገር ኖሮ አይደለም። ነገ ለሚወለዱት፣ ከዛም ለሚሰደዱት ልጆቻቸው ‘የትም ሄደክ በሄድክበት ሀገር ካሉ ዜጎች በላይ አንተ የመብለጥ አቅም አለህ፤ አንተ ልዩ ነህ’ የሚል ታሪክ እየነገሩት ነው። ይሄ ትርክት ነው ነገ ልዩ የሚያደርገው። አስጨናቂውን የሕይወት ትግል አሸናፊ የሚያደርገው። የውብሸት ወርቃለማሁ ልጅ ዶ/ር ዳግማዊ ውብሸት በአሜሪካ ውስጥ ካሉ ስምንት ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ በሆነው Cornell University የእንግሊዘኛ ሥነ-ጽሑፍ አስተማሪ ነው። በአንድ ቃለ-መጠይቁ ላይ ወደ አሜሪካ ሲመጣ እንግሊዘኛ ካለመቻሉ በላይ አንብብ ሲባል ተማሪዎቹ በሳቅ ይወድቁ እንደነበረ ይገልጻል። “እነሱ ሲስቁ ጣልያንን ማሸነፋችን ትዝ እያለኝ፥ ‘ምናለ በሉኝ በራሳችሁ ቋንቋ እናንተን ካልበለጥኩ’ እያልኩ ለውስጤ እነገረው ነበር” ይላል። እንዳለውም በCornell University ታሪክ በእድሜ ትንሹ የእንግሊዘኛ ሥነ-ጽሑፍ ፕሮፌሰር ሆነ። ይሄ ተራ ዩኒቨርሲቲ አይደለም። አይደለም አስተማሪ ለመሆን ተማሪ ለመሆን እራሱ አስደናቂ አዕምሮ ሊኖርህ ይገባል። በነገራችን ላይ ከዚሁ ዩኒቨርሲቲ በኮምፒውተር ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በቅርብ በዶክትሬት ዲግሪ የተመረቀች የመጀመሪያዋ ጥቁር፥ ኢትዮጵያዊት ናት። ዶ/ር ረድኤት አበበ ትባላለች። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንደሚባለው የአሜሪካ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ተወዳዳሪ የምክትል ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን (Joe Biden) የሽግግር ካቢኔ መሪ ከታዋቂው ዬል ዩኒቨርሲቲ (Yale University) እና ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ (Harvard University) የተመረቀው ዮሐንስ አብርሃም የተባለ ኢትዮጵያዊ መሆኑን ታውቃላችሁ። ይሄ ማለት ጆ ባይደን ካሸነፈ በዋይት ሀውስ (White House) ውስጥ ካሉት ትልልቅ ስልጣኖች ቁልፉ ቦታን የሚይይዘው ኢትዮጵያዊው ዮሐንስ አብርሃም ይሆናል ማለት ነው። ደግሞም አምናለው በእኛ የእድሜ ዘመን ውስጥ ከኦባማ ቀጥሎ የአሜሪካ ጥቁር ፕሬዝዳንት የሚሆነው ኢትዮጵያዊ ሊሆን ይችላል። ብዙ ድንቅ ኢትዮጵያውያን በሪፖብሊካንም ሆነ በዲሞክራቶች የፓርቲ መስመር የስልጣን መሰላሉን እየወጡ እየተመለከትን ነው።

    ወደ ቀደመ ነገሬ ልመለስ እና – የኦሮሞ ባህል ይሄን ነገር ካልመረመረ የብዙ አቅመ ድኩማን መደበቂያ እና የሽንፈት ታሪክ ወራሽ ልጆች መፈልፈያ ይሆናል። እስቲ ተመልከቱ – ብርሃነመስቀል አበበ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የአብይ ደጋፊ እና ደንበኛ የኢትዮጵያዊነት አቀንቃኝ ነበር። በአቅም ማነስ ከስልጣን ሲባረር ግን ኦሮሞነቱ ትዝ አለው። የወጣለት የኦሮሞ የመብት አቅንቃኝ ሆነ። ኦሮሞዎቹም ዓይንህን ለአፈር ብለው መስኪድ እንደገባ ውሻ እንዳላባረሩት፥ በአቅም ማነስ ተባሮ ሲመጣ ጀግና አድርገው ተቀበሉት። በተመሳሳይ አማራን እንይ፤ ልክ እንደ ብርሃነመስቀል አበበ ሲባረሩ አማራ ጉያ ውስጥ ለመደበቅ የፈለጉ ሰዎች በቅርብ ታሪካችን ነበሩ። ለምሳሌ ታምራት ላይኔ አንዱ ነው። አማራው ግን ከታምራት ላይኔ ይልቅ መለስ ዜናዊን ይወዳል። በተመሳሳይ ልደቱ አያሌውም ከፖለቲካው መድረክ ሲገለል፥ አማራ ስለሆንኩ ነው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ የጠላኝ አለ። ዶ/ር ብርሃኑ እኮ የተደነቀ አዋቂ ሰው ነው። ምን ዓይነት ጅል ቢሆን ነው የድጋፍ ማዕከሉ የሆነውን የአማራን ሕዝብ የሚጠላው? የአማራ ሕዝብ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋን እንደሚያፈቅር ለማወቅ በአማራ ክልል እሱ የተገኘባቸውን ሠልፎች እና ስብሰባዎች ማየት ነው። ከልደቱ ይልቅ የአማራው ሕዝብ የብርሃኑ አመለካከት ይስበዋል። ሽንፈት፣ውድቀትን በዘር ቅርፊት ማሳበብ አማራው አምርሮ የሚጸየፈው ነገር ነው። ተሸንፈህ ከመጣ አማራነትህ ይነጠቃል።

    አጼ ቴዎድሮስ በመጀመሪያ በአማራው ሕዝብ እጅግ የተጠላ መሪ እንደነበረ ታሪክን ማገላበጥ ብቻ በቂ ነው። እነ ዮፍታሔ እና ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን ግን ቴዎድሮስን በጀግንነት ካባ አዲስ ሰው አድርገው አቀረበቱ። የቋራ ሰው እየተባለ፣ የኮሶ ሻጭ ሲባል ሲሰደብ የከረመው ቴዎድሮስ ህልሙ እና ጀግንነቱ ለሕዝቡ ተብራርቶ በአዋቂዎች ሲቀርብለት አማራ የሆነው በፍቅር አበደለት። ጀግና እና ዘመን ተሻጋሪ አዋቂን የሱ እንኳ ባይሆን እንደምንም የራሱ የማድረግ ባህል አለውና።

    በምድር ላይ እንደእሱ ዓይነት ጠቢብ የለም ብሎ መጽሐፍ ቅዱስ የሰበከለትን ሰሎሞን የተባለ ሌጀንድ የኢትዮጵያ ጠበብት ሲመለከቱት ጊዜ አላጠፉም። ኢትዮጵያዊ አጋቡት። በዓለም ታሪክ የዓለምን ፖለቲካ በመቀየር ፈጽሞ አቻ የሌለው የPlato “The Republic” መጽሐፍ ድንቅ ሕዝብ እና ታላቅ ሀገር በፈላስፋ ይመራል በሚል አስደናቂውን መጽሐፍ ይዘጋል። አባቶቻችን ይሄን ለመረዳት ከባድ የሆነን መጽሐፍ ያነበቡ ስለነበሩ ፥ በኢትዮጵያ ታሪክ የሚነግሰውን ሁሉ ከፈላስፋው ሰሎሞን ወልደ ዳዊት ጋር ሲያዛምዱት ቆዩ። ኢትዮጵያኖች ልጆቻችሁን አዎ ልዩ ናችሁ እያላችሁ አሳድጓቸው። አንብበው፣ ተመራምረው አዋቂ ሲሆኑ ሁሉን በራሳቸው ይደርሱበታል። እስከዛ ግን ይሄን ሥነ-ልቦና ፈጽማችሁ አትንጠቋቸው። እነሱን እዚህ አሜሪካ እንደሚወለደው ከአንጎላ በመርከብ ከመጣው ጥቁር አሜሪካዊ ጋር የተገዢነት ሥነ-ልቦና አታላብሷቸው። ጥቁሩን ሁሉ ነጻ የሚያወጣው ኢትዮጵያዊው እሱ መሆኑን ከልጅነቱ ጀምራችሁ ስበኩት።

    በመጨረሻም በአንድ አፈ-ታሪክ ምሳሌ ጹሑፌን ልዝጋ። ጅብ አህያን ለብዙ ጊዜ ሲፈራት ይኖር ነበር። ለዚህ ዋናው ምክንያት ደግሞ የአህያ ጆሮ ቀንድ እየመሰለው ነው። አህያ ጅብን መወዳጀት ስለምትፈልግ ለብዙ ጊዜ እንዲቀርባት ትሻ ነበር። አንድ ቀን ግን ለምን እንደሚሸሻት ጨክና ጠየቀችው። እሱም ቀንዶቿን እጅግ እንደሚፈራው ለዛም እንደሚሸሻት ነገራት። በመገረም “ይሄ እኮ ቀንድ አይደለም፤ ጆሮዬ ነው፤ ስጋ እንጂ አይዋጋም አለችው።” ከዚያ ቀን ጀምሮ አባራሪ እና ተባራሪ ቦታ ተለዋወጡ። ኢትዮጵያኖች ታሪኮቻችን፣ ድሎቻችን፣ ሃውልቶቻችን፣ ሃይማኖታችን ጅብ ከሆኑ ጠላቶቻችን መጠበቂያ ጋሻዎቻችን፣ ምሽጎቻችን ናቸው። ይሄን አጥተን ከመኖር ሁላችን ማለቅን መምረጥ ይሻለናል። ጆን ስቱዋርት ሚል (John Stuart Mill) እንዳለው “የተደሰተ አሳማ ከመሆን የተከፋ ሰው መሆን ይሸላል፣ ጅል ሆኖ ከመደሰት ሶቅራጦስን ሆኖ ዕድሜ ልክን ማዘን ይሻላል።” ለልጆቻችን የባርነትን፣ የተሸናፊነትን ሥነ-ልቦናን ከምናወርስ ሁላችን ቀድመን ማለቅ ይሻለናል። አባቴ ጀግና ነው እያለ ካላባት ያደገ ልጅ በፈሪ አባት ካደገ ልጅ በላይ በራስ መተማመኑ ኃያል ነው።

    * በዚህ ጽሑፍ ላይ አማራ ብዬ የጠቀስኩት ማኅበረሰብ በአሰፋ ጨቦ ትንታኔ መሠረት ሲሆን፥ ዘርን ሳይሆን የአባቶቻችንን ድል እና ኃያልነት የተቀበለውን፣ የማሸነፍ መንፈሱ የማይደረመስ ተራራ የሆነውን፣ በየሄደበት ሁሉ የአባቶቹን ድል አድራጊነት እያሰበ የበታችነትን እንቢ ያለውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ የሚመለከት ነው።

    አማራ ብዬ የጠቀስኩት...

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.