Search Results for 'ልደቱ አያሌው'

Home Forums Search Search Results for 'ልደቱ አያሌው'

Viewing 11 results - 1 through 11 (of 11 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    ሚያዝያ 11 ቀን፥ 2013 ዓ.ም.
    አቶ ልደቱ አያሌው
    ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን
    አዲስ አበባ

    ጉዳዩ:- በድጋሚ አቤቱታ ማቅረብን ይመለከታል

    በቅድሚያ በእኔ በአመልካቹ ላይ በተደጋጋሚ እየደረሰ የሚገኘውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት መፍትሄ እንዲያገኝ መሥሪያ ቤታችሁ እያደረገ ስላለው ያልተቋረጠ ጥረት ልባዊ ምስጋናየን አቀርባለሁ። ሆኖም በእኔ ላይ እየተፈፀመ የሚገኘው የሰብዓዊ መብት ጥሰት አሁንም ያልተቋረጠና ለሕይወቴ አስጊ በሆነ ደረጃ ተጠናክሮ የቀጠለ በመሆኑ፥ ይሄንን አቤቱታ በድጋሚ ለማቅረብ ተገድጃለሁ።

    የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በሀገሪቱ የተፈጠረውን የፖለቲካ ቀውስ ሰበብ በማድረግ በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንድውል ከተደረገበት ከሐምሌ 17 ቀን፥ 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በሀገሪቱ ሕግና የሕግ የበላይነት የለም ሊያስብል በሚባል ደረጃ በርካታና ተከታታይ የሰብዓዊ መብት መብት ጥሰት በእኔ ላይ እየተፈፀመ ይገኛል። ለማስታወስ ያህል…

    1. ሕጋዊ ነዋሪነቴ ተመዝግቦ የሚገኘው በአዲስ አበባ ከተማ ሆኖ እያለ፥ እንድታሰር የተደረገው ግን ያለ አግባብ በኦሮሚያ ክልል ነው።
    2. በስልክ ተጠርቼና ለፌደራሉ ፖሊስ ኮሚሽን በእራሴ ፈቃድ እጄን ሰጥቼ በቁጥጥር ስር ከዋልኩ በኋላም በሕጉ መሠረት በ48 ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት እንድቀርብ አልተደረገም።
    3. በቁጥጥር ስር ከዋልኩ በኋላ ያለምንም ፍርድ ቤት ትዕዛዝ በስልክና በኢንተርኔት አማካይነት ያደረኳቸው የግል የመልዕክት ልውውጦች በሕገ-ወጥ መንገድ እንዲበረበሩና በሲዲ እንዲቀዱ ተደርገዋል። የግል ማስታወሻወቼና ረቂቅ የፅሁፍ ሰነዶቸ ሳይቀሩ በፖሊስ ተወስደዋል።
    4. በቁጥጥር ውስጥ ውዬ ገና ክስ እንኳ ባልተመሠረተብኝ ወቅት የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኛ ነን የሚሉ ሰዎች ወንጀለኛ እንደሆንኩ አድርገው ሰፊ የስም ማጥፋት ዘመቻ እንዲያካሂዱብኝ ተደርጓል።
    5. በምርመራ ወቅትና የምርመራ ፋይሌ ከተዘጋ በኋላም የዋስ መብት ተከልክዬና ክስ ሳይመሠረትብኝ በጊዜ ቀጠሮ ሰበብ ከሁለት ወራት በላይ ለሆነ ጊዜ በሕገ-ወጥ መንገድ በእስር ቤት እንድቆይ ተደርጓል።
    6. በፍርድ ሂደቱ ወቅት በግልፅ እንደታየው፥ በቢሾፍቱ ከተማ አመፅ አስነስተሀል፤ ሕገ-ወጥ መሣሪያ ታጥቀህ ተገኝተሀል፤ መንግሥትን በሕገ-ወጥ መንገድ አፍርሰሀል የሚሉ የፈጠራ ክሶች እንዲቀርቡብኝ ተደርጓል።
    7. “መንግሥትን በሕገ-ወጥ መንገድ አፍርሰሀል” በሚል የተከሰስኩበት ወንጀል አዲስ አበባ በሚገኝ የፌደራሉ ፍርድ ቤት መታየት ሲገባው ያለ አግባብ በአዳማ ከተማ የሚገኘው የኦሮሚያ ክልል ጥቅላይ ፍርድ ቤት በውክልና እንዲያየው ተደርጓል። ይህም መሆኑ የፍርድ ሂደቱ በማልናገረው ቋንቋ እንዲካሄድና ብዙ ውጣ ውረድ እንዲደርስብኝ አድርጓል።
    8. በፍርድ ሂደቱ ወቅት ለሁለት ጊዜ ያህል የዋስ መብት በፍርድ ቤት ቢፈቀድልኝም ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ በመጣስ ለሁለት ወራት ያህል በእስር አቆይቶኛል። ከዋስትና መብቴ ጋር በተያያዘም ፍርድ ቤት ለአምስት ጊዜ የሰጣቸው የተለያዩ ትዕዛዞች በፖሊስ እምቢተኝነት ሳይፈፀሙ ቀርተዋል።
    9. ለሕይወት አስጊ የሆነ ከፍተኛ የልብ ህመም ያለብኝ ሰው መሆኔ እየታወቀም የኮቪድ ወረረሽኝ ተጠቂ ከሆኑ ሰዎች ጋር በአንድ ጠባብ ግቢ ውስጥ ታስሬ ለረጅም ጊዜ እንድቆይ ተደርጓል።
    10. ከአምስት ወራት መታሰር በኋላ የዋስ መብቴ ተጠብቆ ከተፈታሁ ከጥቂት ቀናት በኋላም እኔንና የትግል ጓደኞቼን ከሀገሪቱ የፖለቲካ ሂደት ለማግለል ሲባል አባል የሆንኩበት የፖለቲካ ፓርቲ በሕገ-ወጥ መንገድ እንዲሰረዝና ህልውናውን እንዲያጣ ተደርጓል።
    11. ከእስር ቤት ወጥቸ አስቸኳይ የቀዶ ጥገና የሕክምና እርዳታ ለማግኘት ወደ ውጭ ሀገር ለመጓዝ ለሁለት ጊዜ ያደረኩት ሙከራም ምንም አይነት የፍርድ ቤት እገዳ ባልተጣለብኝና እንዲያውም ጉዳዩን ይመለከት የነበረው ፍርድ ቤት ወደ ውጭ ሀገር ሄጀ የመታከሜን አስፈላጊነት በማመን ረዥም ቀጠሮ ሰጥቶኝ እያለ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት መሥሪያ ቤት በሕግ ባልተሰጠው ሥልጣን ባደረገብኝ ሕገ-ወጥ ክልከላ ምክንያት ከሀገር የመውጣት ሕገ- መንግሥታዊ መብቴ ተጥሷል።
    12. ይህ የተጣለብኝ ሕገ-ወጥ እገዳ እንዲነሳልኝ ለማድረግ የተለያዩ ጉዳዩ የሚመለከታቸውን የመንግሥት ባለ ስልጣናት ቀጠሮ ይዤ ለማነጋገር በተደጋጋሚ ብሞክርም ባለስልጣናቱ ሊያናግሩኝ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ሙከራዬ ሳይሳካ ቀርቷል።
    13. መሥሪያ ቤታችሁ ባደረገው ጥረት ምክንያት የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት መሥሪያ ቤት በእኔ ላይ ምንም ዓይነት የጉዞ ክልከላ እንዳላደረገ የሚክድ ደብዳቤ ለመሥሪያ ቤታችሁ ከፃፈ በኋላም ለሦስተኛ ጊዜ ከሀገር ለመውጣት ያደረኩት ሙከራ የኢሚግሬሽን ዜግነትና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ ክልከላ ስላደረገብኝ ጉዞዬ ሳይሳካ ቀርቷል። የጉዞ ፓስፖርቴም በመሥሪያ ቤቱ ባልደረቦቼ ተወስዶብኛል።
    14. የኢሚግሬሽን መሥሪያ ቤት ለምን የጉዞ ክልከላ እንዳደረገብኝና እንደቀማኝ በማግስቱ ዋናው መሥሪያ ቤት ድረስ ሄጄ ለመጠየቅ ባደረኩት ሙከራ የፌዴራሉ ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል ባቀረበው ጥያቄ መሠረት በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውዬ ምርመራ እስከሚካሄድብኝ ድረስ የፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የአራዳ ምድብ አንደኛ ችሎት የካቲት 4 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. በዋለው ችሎት ወደ ውጭ እንዳልጓዝ እገዳ የጣለብኝ ስለመሆኑ ተነግሮኛል።

    ከእነዚህ ከዚህ በላይ ከተዘረዘሩት ተደጋጋሚ የመብት ጥሰቶች በግልፅ መረዳት እንደሚቻለውና በእኔ በኩል እንደምገነዘበውም መንግሥት በእኔ ላይ ይህን ሁሉ የመብት ጥሰት እየፈፀመ የሚገኘው የፈፀምኩት ወንጀል ስላለ ሳይሆን መብቴን በሕገ-ወጥ መንገድ በመጣስና በመገደብ ከፖለቲካ ተሳትፎ ውጭ እንድሆን ስለፈለገ ነው።

    እኔ አመልካቹ የአለፈ ታሪኬ እንደሚያሳየው ለሃያ ስምንት ዓመታት በሀገሪቱ ፖለቲካ በነበረኝ ተሳትፎ ስድስት ጊዜ በሕገ-ወጥ መንገድ በፈጠራ ክስ የታሰርኩ ቢሆንም አንድም ጊዜ በወንጀለኝነት ተፈርዶብኝ አያውቅም። የኢትዮጵያ ህዝብ በግልፅ እንደሚያውቀው በዚህ የረጅም ጊዜ የፖለቲካ ተሳትፎዬ ስታገል የኖርኩት በሀገሪቱ ዘላቂ ሰላም፣ እርቅና የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን ሲሆን፤ በአንፃሩም ሕገ-ወጥነትን፣ አመጽንና የኃይል አማራጭን በግልፅና በድፍረት በማውገዝ የምታወቅ ሰላማዊ የፖለቲካ ሰው ነኝ። ሆኖም መንግሥት ከላይ በተገለፀው ሁኔታ በፈጠረብኝ ተከታታይ ሕገ-ወጥ ጫና ምክንያት በአሁኑ ወቅት ከፖለቲካ ተሳትፎዬ ሙሉ በሙሉ ለመገለል የተገደድኩ ሲሆን ከዚያም በላይ ያለብኝን ከፍተኛ የልብ ህመም ወደ ውጭ ሀገር ሄጀ መታከም ባለመቻሌ ምክንያት በህይወት የመኖር ዕድሌ ከፍተኛ አደጋ ላይ ወድቋል። በአጠቃላይም እየደረሰብኝ ባለው ተደጋጋሚ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ምክንያት ለከፍተኛ የጤና መታወክ፣ የሞራል ውድቀት፣ የገንዘብና የጊዜ ብክነት ተዳርጊያለው።

    ይህ ሁሉ በተደጋጋሚ የተፈጸመብኝ በደል አልበቃ ብሎም እኔ አመልካቹ ፈጽሞ ባልተነገረኝና በማላውቀው ሁኔታ፣ ምንም ዓይነት ጥያቄ ባልቀረበልኝና ምርመራ ባልተካሄደበት ሁኔታ፣ ከዚያም በላይ ተፈልጌ የጠፋሁ ወንጀለኛ የሆንኩ በሚያስመስል ሁኔታ የጉዞ እገዳ የተጣለብኝ ስለመሆኑ የአራዳ ፍርድ ቤት ሰጠ የተባለው ትዕዛዝ አሁንም በእኔ ላይ የፈጠራ ክስ እንደገና በመመሥረት እንድታሰርና ሕይወቴ አደጋ ውስጥ እንዲወድቅ እየታሰበና ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ነው።

    በአንድ ሰው የደረሰ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በሁሉም ሰው ላይ እንደደረሰ ጥሰት የሚቆጠር መሆኑን ታሳቢ በማድረግና በእኔ ላይ እየተፈፀመ ያለው ተደጋጋሚ መቋጫ ያጣ የሰብዓዊ መብት ጥሰትም የፖለቲካና ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ ሕገ-መንግሥታዊ መብቴን ከመጣስም በላይ በሕይወት ለመኖር ያለኝን የማይገሰስ ሰብዓዊ መብቴን አደጋ ላይ የጣለ መሆኑን ግምት ውስጥ በማስገባት፥ መሥሪያ ቤታችሁ በጉዳዩ ልዩ ትኩረት በመስጠት ምርመራ እንዲያካሂድልኝና አስቸኳይ መፍትሔ እንዳገኝ እንዲያግዘኝ በድጋሚ በአክብሮት እጠይቃለሁ።

    ከሰላምታ ጋር!
    ልደቱ አያሌው

    ግልባጭ፦
    ለመገናኛ ብዙሀን

    አቶ ልደቱ አያሌው ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የጻፉት ደብዳቤ

    Anonymous
    Inactive

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ያለችበት የሕልውና አደጋ በአቶ ልደቱ አያሌው እይታ

    ስንብት፥ ለመሰንበት
    ልደቱ አያሌው
    የካቲት 29 ቀን 2013 ዓ.ም.

    ሀገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ የሕልውና አደጋ ውስጥ ትገኛለች። ብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ የሆነ የዕውቀት፣ የአቅምና የቅንነት ድክመት ያለበት በመሆኑ ሀገሪቱ የገጠማትን ችግር ከማቃለልና ከመፍታት ይልቅ፥ የበለጠ እያባባሰውና እያወሳሰበው ይገኛል። በዚህም ምክንያት ሀገራችን ሕልውናዋን የሚፈታተን አሳሳቢ የእርስ በርስ ግጭት ውስጥ ከመግባቷም በላይ፥ ከኤርትራና ከሱዳን መንግሥታት ግልጽ ወረራ ተፈጽሞባታል። ከታሪኳና ከማንነቷ በተቃራኒም ይህንን ግልጽ ወረራ  ለመቀልበስ የሚያስችል አቅምና ወኔ ያጣች ደካማ ሀገር ሆናለች። ይህ ክስተት ሀገሪቱ ምን ያህል በሂደት ውስጣዊ አንድነቷ እየተዳከመ እንደመጣና ወደ መበታተን አደጋ ውስጥ እየገባች ስለመሆኑ አንድ ማሳያ ነው።

    ብልጽግና ፓርቲ እያራመደ በሚገኘው የተሳሳተ የውጭ ግንኙነት ምክንያትም ሀገራችን ለከፍተኛ የዲፕሎማሲ ጫና ተጋላጭ በመሆን ብሔራዊ ጥቅሞቿንና ሉዓላዊነቷን በአግባቡ ማስከበር የማትችልበት ሁኔታ ውስጥ ገብታለች። ‘በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ’ እንዲሉም ሀገራዊ ሕልውናችንን በሚፈታተን መጠን ኢኮኖሚያችን ወደ ጥልቅ ቀውስና ኪሣራ ውስጥ እየገባ ይገኛል።

    ይህ ሁሉ እየሆነ ያለው በብዙ የሕይወት መሥዋዕትነት የተገኘውና የዛሬ ሦስት ዓመት ገደማ ተጀምሮ የነበረው የለውጥ ሂደት በአመራር ድክመትና በአምባገነናዊ ባህርይ ምክንያት እንዲከሽፍ በመደረጉ ነው። በሥልጣን ላይ የሚገኘው ብልጽግና ፓርቲ ለለውጡ መምጣት ምክንያት የሆኑትን ፖለቲካዊ ችግሮች ሕጋዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ሰላማዊ በሆነ አግባብ ከመፍታት ይልቅ አማራጭ ሀሳቦችን በማፈን፣ በፖለቲካ ተቀናቃኞቹ ላይ የስም ማጥፋት ዘመቻ በማካሄድና የፈጠራ ክስ በመመሥረት፣ በሕገ-ወጥ መንገድ ተቀናቃኞቹን በማሰርና ‘ለሕልውናዬ ስጋት ናቸው’ ብሎ የሚፈራቸውን የፖለቲካ ድርጅቶች ሕጋዊ ዕውቅና በመሠረዝ ጭምር ካለፈው የ27 ዓመቱ የኢሕአዴግ ሥርዓት የባሰ እንጂ የተሻለ አለመሆኑን በተግባር አሳይቷል። ባጭሩ፥ ሀገራችን ከእንግዲህ በብልጽግና ፓርቲ ወይም በዶ/ር ዐቢይ አሕመድ እየተመራች ከአንድ ቀውስ ወደ ሌላ የባሰ ቀውስ የመሸጋገር እንጂ ወደ በጎና የተሻለ ሥርዓታዊ ለውጥ የመሸጋገር ዕድል እንደሌላት በማያሻማ ሁኔታ ግልጽ ሆኗል።

    እኔም ሆንኩ አባል የሆንኩበት ፓርቲ፥ በአንድ በኩል የተጀመረው የለውጥ ሂደት ስኬታማ እንዲሆን ከተፈለገ ምን ዓይነት መዋቅራዊ ለውጦች በቅደም ተከተል መካሄድ እንዳለባቸው፤ በሌላ በኩል ደግሞ በአመራር ብቃት ማነስ ምክንያት የተጀመረው የለውጥ ሂደት ከከሸፈ በሀገራችን አጠቃላይ ሕልውና ላይ ሊያስከትል የሚችለው አደጋ ምን ያህል ከባድና አደገኛ እንደሚሆን የሚያሳስብ የሀሳብ ትግል ላለፉት ሦስት ዓመታት ስናካሂድ ቆይተናል።

    ነገር ግን የወቅቱ የሀገራችን ፖለቲካ በዕውቀት፣ በምክንያታዊነትና በሐቀኝነት የሚካሄድ ሳይሆን ብሔርተኝነት፣ ጽንፈኝነት፣ ሤረኝነት፣ ጥላቻና ውሸት የነገሠበት በመሆኑ ጩኸታችን የቁራ ጩኸት ሆኖ ቀርቷል። ሆኖም ቀደም ብለን ስናቀርበው የነበረው ስጋት ከተራ ሟርተኝነት ሳይሆን፥ ከተጨባጭ የፖለቲካ ግምገማ፣ ግንዛቤና ትንታኔ የመነጨ ስለነበር እንደፈራነው የለውጥ ሂደቱ ከሽፎ አሁን ሀገሪቱ ወደባሰና ውስብስብ የሕልውና አደጋ ውስጥ ገብታለች።

    የለውጥ ሂደቱን መክሸፍ ተከትሎ ሀገራችን ወደ ከፍተኛ የእርስ በርስ ጦርነት የገባችና በውጭ ኃይሎች ወረራ ሥር የወደቀች ቢሆንም፥ ግብዞቹ የብልጽግና አመራሮችና የእነርሱ የፕሮፓጋንዳ ሰለባ የሆኑ ተከታዮቻቸው ግን ዛሬም ጭምር ሀገሪቱ ወደላቀ የብልጽግና ጎዳና እየገሰገሰች እንደሆነ ሊነግሩን ሲደፍሩ እያየን ነው። ብልጽግና ፓርቲ የከሸፈን የለውጥ ሂደት ተከትሎ የሚካሄድ ሀገራዊ ምርጫ፥ የተጨማሪ ቀውስ ምንጭ ከመሆን ባለፈ ለሀገሪቱ መዋቅራዊ የፖለቲካ ችግሮች የሚያስገኘው ምንም ዓይነት አዎንታዊ ፋይዳ የሌለ መሆኑን መገንዘብ ተስኖት የሥልጣን ቅቡልነት ልባስ ለመደረብ ሲል ብቻ ትርጉም የለሽ ምርጫ ለማካሄድ እየተጣደፈ ይገኛል። ይህም ሀገሪቱ ወደባሰና ከቁጥጥር ውጭ ወደሆነ የፖለቲካ ቀውስ ልትገባ ትችላለች የሚል ተጨማሪና ምክንያታዊ ስጋት ፈጥሯል።

    በእኛ በኩል ውጤታማ ሽግግር ባልተካሄደበትና አንጻራዊ ሰላምና መረጋጋት ባልተፈጠረበት ሁኔታ በችኮላ ወደ ምርጫ ውስጥ መግባት አደገኛና ኃላፊነት የጎደለው ውሳኔ ነው የሚል የጠነከረ አቋም ያለን ቢሆንም፥ ምርጫው መካሔዱ የማይቀር ከሆነ ግን ቢያንስ በምርጫው ሂደት ሊፈጠር የሚችልን አደጋ ለመቀነስ በሚያስችል አግባብ በምርጫው ተሳታፊ ለመሆን በዝግጅት በማድረግ ላይ ነበርን።

    ነገር ግን ከሁሉም ነገር በላይ ሀሳብን አብዝቶ የሚፈራውና ከሀገሪቱ ደኅንነት በላይ ለራሱ የሥልጣን የበላይነት ሰፍሳፋ የሆነው የወቅቱ መንግሥት በመጭው ምርጫም ሆነ በቀጣዩ የትግል ሂደት ተሳትፎ እንዳይኖረን ስለፈለገና ስለወሰነ በሕገ-ወጥ መንገድ ፓርቲያችን እንዲሰረዝና ከትግሉ ሜዳ እንዲወገድ አድርጓል።

    በእኔ ላይም በባለቤትነት በሚቆጣጠራቸውና ለልዩ ተልዕኮ ባቋቋማቸው የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ቅጥረኞቹን አሰማርቶ ሰፊ የስም ማጥፋት ዘመቻ በማካሄድ፣ የዛቻና ማስፈራራት ድርጊት በመፈጸም፣ የፈጠራ ክስ በመመሥረትና በሕገ-ወጥ መንገድ በማሰር የትግል ተሳትፎዬን ለመገደብ ሞክሯል። ይህም አልበቃ ብሎት በፖለቲካ መድረኩ ላይ ብቻ ሳይሆን በሕይወትም እንዳልኖር ስለፈለገ፥ ያለምንም ሕጋዊ ድጋፍ ያለብኝን ከፍተኛ የልብ ሕመም ወደውጭ ሀገር ሄጄ እንዳልታከም እገዳ ጥሎብኛል። ይህ ሕገ-ወጥ እገዳ እንዲነሳልኝ የተለያዩ የመንግሥት ተቋማትንና ባለሥልጣናትን ለማነጋገርና ለመማጸን ያደረግኩት ጥረትም ስኬታማ ሳይሆን ቀርቷል። በዚህም ምክንያት ከፍተኛ የልብ ቀዶ ጥገና ሕክምና ለማድረግ የነበረኝ ቀጠሮ በመስተጓጎሉ በእያንዳንዱ ሰዓትና ዕለት ሕይወቴ ለዕልፈት ሊጋለጥ በሚችልበት አደጋ ውስጥ እገኛለሁ። በዚህ ድርጊቱም የወቅቱ መንግሥት አምባገነናዊ ብቻ ሳይሆን ምን ያህል ኢ-ሰብአዊ መሆኑን በተግባር አሳይቷል። በርግጥም ሥርዓቱ ከግለሰብ ግድያ ጀምሮ እስከ የሕዝብ ጅምላ ጭፍጨፋ ከሚደርስ ቀውስ የፖለቲካ ትርፍ ለመቃረም የሚጥር ኃይል በመሆኑ በእኔ ላይ ይህንን ማድረጉ እምብዛም አያስደንቅም።

    ሰሞኑን የምገኝበትን አሳሳቢ የጤና ሁኔታ በተመለከተ ከሐኪም ጋር ባደረግሁት ምክክርም ለሕመሜ አስተማማኝ ሕክምና እስካገኝ ድረስ በአካሌም ሆነ በአዕምሮዬ ላይ ምንም ዓይነት ጫናና ውጥረት የሚፈጥር ሥራ እንዳልሠራና በቂ ረፍት እንዲኖረኝ ከባድ ማስጠንቀቂያና ምክር ተሰጥቶኛል። ጤናዬ ከሚገኝበት አሳሳቢ ደረጃ (risk) አኳያ በሕይወት ለመሰንበት የምፈልግ ከሆነ፥ ለጊዜው ያለኝ ብቸኛ አማራጭ ይህንን ማድረግ እንደሆነ ተነግሮኛል።

    ሀገራችን የምትገኝበትን እጅግ አሳሳቢ ሁኔታ ግምት ውስጥ በማስገባት በእኔ በኩል አስቸኳይ የሕክምና እርዳታ አግኝቼና ጤናዬ ተስተካክሎ በትግሉ ሂደት የጎላ ተሳትፎ እንዲኖረኝ ከፍተኛ ፍላጎት የነበረኝና አሁንም ያለኝ ቢሆንም የሕክምና እርዳታ እንዳላገኝ ራሳቸውን በፈጣሪ ቦታ ሊተኩ በሚፈልጉ ገዥዎች በመከልከሌ ምክንያት ይህንን ምኞቴን ማሳካት የማልችልበት እንቅፋት ገጥሞኛል። ስለሆነም ተገቢውን የሕክምና እርዳታ አግኝቼ ጤናዬ እስኪመለስ ድረስ በሕይወት የመሰንበት ዕድሌን ለመሞከር ስል ከማንኛውም ዓይነት የትግል እንቅስቃሴ (ገንዘብ ወይም ምክር ከማዋጣት ባለፈ) ራሴን ለጊዜው ለማቀብ የተገደድኩ ስለመሆኑ በከፍተኛ ቁጭትና ሐዘን እገልጻለሁ።

    በዚህ ጉዳይ ላይ የሚሰማኝ ቁጭትና ሐዘን ልብን የሚሰብር የሆነብኝ ያለምክንያት ሳይሆን፥ ሀገራችን ከመቼውም ጊዜ በላይ የሕልውና አደጋ ውስጥ በገባችበትና ዋጋ የሚከፍልላት ዜጋ በሚያስፈልጋት በአሁኑ ወቅት ከአቅሜ በላይ በሆነ የጤና ችግር ምክንያት ራሴን ከትግሉ ሜዳ ለማግለል መገደዴ ያልጠበቅሁትና ከፍላጎቴ ውጭ የሆነ መጥፎ ገጠመኝ ስለሆነ ነው።

    የሆነው ሆኖ ይህንን መጥፎ አጋጣሚ እንደ አንድ ጊዜያዊ ስንብት ልቁጠረውና ስለ ዛሬዋ ኢትዮጵያ ሕዝቡ ግንዛቤ ሊወስድ ይገባዋል ብዬ በማምንባቸው በሚከተሉት ስምንት ነጥቦች ዙሪያ የሚሰማኝን በመግለጽ ለመሰናበት ልሞክር።

    1. ከእንግዲህ በብልጽግና ፓርቲ የሚባባስ እንጂ የሚፈታ ችግር የለንም

    በአሁኑ ወቅት ሀገራችን ለገጠማት የሕልውና አደጋ በአስተሳሰብና በመዋቅር ደረጃ ዋናዎቹ ተጠያቂ ምክንያቶች የጽንፈኝነት ፖለቲካ፣ ብሔርተኝነትና የፖለቲካ አመራር ድክመቶች ናቸው። ስለሆነም ለወቅቱ የለውጥ ሂደት መክሸፍ ዋናው ተጠያቂ የእነዚህ መዋቅራዊ ድክመቶች ሰለባ የሆነው የቀድሞው ኢሕአዴግ፣ የአሁኑ ብልጽግና ፓርቲ ነው።

    ብልጽግና ፓርቲ በእጁ የገባውን ወርቃማ የለውጥ ዕድል በአግባቡ መጠቀም ሳይችል የቀረበት ተጨማሪ ምክንያትም ፓርቲው ከሀገሪቱ ጥቅምና ደኅንነት በላይ ለራሱ የፖለቲካ ሥልጣን የበላይነት ቅድሚያ በመስጠት ውስጣዊ አንድነቱን በማዳከሙና ወደ የእርስ በርስ የሥልጣን ሽኩቻ ውስጥ በመግባቱ ነው። የፓርቲው ውስጣዊ ክፍፍል በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች እየተፈጠሩ ላሉ የእርስ በርስ ግጭቶችና በትግራይ ክልል ለተከሰተው ጦርነት ዋናው ምክንያት ሲሆን፥ ውስጣዊ ችግሩ አሁንም የተሻለ ትኩረት አግኝቶ ካልተፈታ በስተቀር ሀገሪቱን ለባሰ ቀውስና ጦርነት የሚዳርጋት ይሆናል። የራሱን ውስጣዊ ችግር መፍታት ያልቻለና ከራሱ የፖለቲካ ሥልጣን በላይ የሀገሪቱን ጥቅም ማስቀደም የተሳነው ደካማ ገዥ ፓርቲ የለውጥ ሂደቱን ስኬታማ ሊያደርግም ሆነ ሀገሪቱን ከጥፋት ሊታደጋት አይችልም።

    ቀደም ሲል ብልጽግና ፓርቲ ይህንን መሠረታዊ ድክመቱን አምኖ በመቀበልና በማረም ራሱንም ሆነ ሀገሪቱን ከጥፋት ሊታደጋት ይችላል የሚል ግምት (ምናልባትም የሞኝነት) የነበረን ቢሆንም ግምታችን ስህተት እንደነበር ያለፉት ሦስት ዓመታት ሂደት በተግባር አሳይቶናል። በዚህም ምክንያት ብልጽግና ፓርቲ እንደ ፈጣሪውና አሳዳጊው ህወሓት ሁሉ፥ ከመሞት መዳን ያለመቻል መዋቅራዊ ችግር ያለበት ግትርና ጀብደኛ ድርጅት እንደሆነ መገንዘብ ችለናል። ምክንያቱም ብልጽግና ፓርቲ አምባገነን የሆነው አምባገነን እንዲሆን ያስገደዱት ነባራዊ ሁኔታዎች ስላሉ ሳይሆን በራሱ ፍላጎትና ውሳኔ አምባገነን መሆንን የመረጠ ድርጅት ስለሆነ ነው።

    ከይቅርታ ጋር፥ እዚህ ላይ በከፍተኛ ድፍረትና ርግጠኛነት ልናገር የምችለው፥ የ21ኛዋን ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያን በ16ኛው ክፍለ ዘመን የማክያቬሊ የፖለቲካ ሤራ ስልት (conspiracy theory) እና የንግርት አምልኮት ለመግዛት እየሞከረ ያለው ብልጽግና ፓርቲ አሁን በያዘው አቅጣጫ መጓዝ ከቀጠለ ራሱንም ሆነ ሀገሪቱን የማፍረስ እንጂ ወደ ዘላቂ ለውጥ የማሸጋገር ሚና ከቶውንም ሊኖረው አይችልም። በአሁኑ ወቅት ትግራይ ውስጥ የገባንበትን ከባድ ጦርነት፣ በኤርትራናና በሱዳን መንግሥት የተፈጸመብንን ወረራ፣ በሕዳሴ ግድብ ምክንያት ከግብጽና ከሱዳን ጋር የገባንበትን ፍጥጫ፣ በተለያዩ የሀገሪቱ ክልሎች እየተፈጸመ የሚገኘውን የሕዝብ መፈናቀልና የጅምላ ጭፍጨፋ፣ በገዥው ፓርቲና በበርካታ ተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል የሚታየውን ፍጥጫ፣ ከዓለም አቀፉ ኅብረተሰብ እየደረሰብን ያለውን ከባድ ተጽዕኖ፣ የኮሮና ወረርሽኝ እያስከተለብን ያለውን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ቀውስ፣ ከፊታችን እየመጣ ያለውን ሁለንተናዊ ኢኮኖሚያዊ ውድቀትና ሌሎች ተመሳሳይ ፈተናዎቻችንን በጥቅሉ ደምረን ስናያቸው እንኳንስ ብልጽግና ፓርቲ ብቻውን ሆኖ ሁላችንም ተባብረን በአንድነት ብንቆም የወቅቱን የሀገሪቱን ፈተና በቀላሉ መወጣት አዳጋች ነው። ስለሆነም የውስጥ ችግራችንን ፈተን በአንድነት እስካልቆምን ድረስ በብልጽግና ፓርቲ የተናጠል ጥረት ችግራችን ፍጹም ሊፈታ እንደማይችል መገንዘብ ያስፈልጋል።

    1. ወቅቱ ኢትዮጵያውያን በአስተሳሰብና በሞራል ዝቅታ ላይ የምንገኝበት ነው

    የምንገኝበት ወቅት ኢትዮጵያውያን ከመቼውም ጊዜ በላይ ጭካኔን፣ ጅምላ ግድያን፣ የሤራ ፖለቲካን፣ የጥላቻ ንግግርን፣ ውሸትንና የግለሰብ አምልኮትን እየተለማመድን የምንገኝበት ነው። እነዚህን እኩይ ተግባራት በፊት አውራሪነት እያለማመደን የሚገኘው መንግሥት ሲሆን፥ ጋሻጃግሬዎቹ ደግሞ ሀይማኖተኛ፣ ብሔርተኛና ምሁራን ነን ባይ “ልሂቃን” መሆናቸውን እያየን ነው።

    በርግጥም ወቅቱ የ“ዝቅታችን” ወቅት ነው። ለአንድ “ህወሓት” የተባለ አምባገነናዊ የሆነና በሕዝብ ትግል ከሥልጣን ለተወገደ ኃይል ባለን ገደብ የለሽ ጥላቻ ምክንያት ዓይነልቦናችን ታውሮ የዛሬ ገዥዎቻችን በሕዝብና በሀገር ላይ እየፈጸሙት ያለን የዛሬ ግፍና በደል ፈጽሞ ማየትና መረዳት ተስኖናል። የወቅቱ ገዥዎቻችን ለራሳቸው የሥልጣን የበላይነት ሲሉ በሀሰትና በአስመሳይነት በጥብጠው የሚግቱንን ሥልታዊ ፕሮፓጋንዳ፣ በሀገር ጥቅምና በሕግ ማስከበር ሰበብ እየፈጸሙት ያለን በውጤቱ ሀገር በታኝ የሆነ የሤራና የበቀል ተግባር መገንዘብ ተስኖን እንደ ሕዝብ የአዲስ አምባገነናዊ ኃይል አዋላጅና ወላጅ ሆነናል። እወደድ ባይና ደካማ በሆነው የብልጽግና ፓርቲ አመራርና ተከታዮቹ በሆኑት የኅብረተሰብ ክፍሎች መካከል ያለው የጋራ አጀንዳ፥ በዋናነት ህወሓትን በመጥላትና በመበቀል ዙሪያ የተቃኘ ቢሆንም፥ ዋናውና የጋራ መገለጫቸው የሆነው ባሕርያቸውና ግብራቸው ግን የህወሓት አውዳሚ አመለካከትና ውርስ (legacy) አራማጅና አስቀጣይ መሆን ነው። እነዚህ ግብዝ ኃይሎች በህወሓት መንገድ መጓዝ ህወሓት በከፋፋይ አጀንዳው ያዳከማትን ሀገር ለይቶላት እንድትፈርስ ከማድረግ ያለፈ ውጤት እንደማያመጣ መገንዘብ ተስኗቸዋል። ይህም በራሱ ኢትዮጵያውያን ከሌሎችም ሆነ ከራሳችን ያለፈ ስህተትና ውድቀት የመማር አቅማችን እጅግ አናሳ መሆኑን ያሳያል።

    በአጠቃላይም ወቅቱ ኢትዮጵያውያን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በራሳችን ታሪክ፣ አንድነት፣ ሉዓላዊነት፣ ሰላም፣ የወደፊት ዕድገትና ጥቅም ላይ ራሳችን ጦርነት ያወጅንበት ወቅት ነው ማለት ይቻላል። በአጭሩ የራሱን ፍላጎትና ዘለቄታዊ ጥቅም የማያውቅ ግብዝ ሕዝብ ሆነናል። ከገባንበት ዝቅጠት ጥልቀትና ስፋት አኳያም አንዳንዶች “ኢትዮጵያውያን እርስ በርስ ተጨራርሰን ከምንጠፋ በስምምነት ተለያይተን መኖር የምንችልበት ዕድል ይኖር ይሆን?” ብለው ራሳቸውን ለመጠየቅ የተገደዱበት ወቅት ላይ ደርሰናል። ኢትዮጵያውያን እንደ “ሕዝብ” በዚህ ዓይነት የአስተሳሰብና የሞራል ዝቅታ ላይ እንደምንገኝ ተገንዝበን ስክነትና ብስለት ወደተላበሰ የፖለቲካ አቅጣጫ በፍጥነት ካልገባን በስተቀር ሀገራችንን ከገጠማት የመፈራረስ አደጋ ልንታደጋት አንችልም። እጅግ አማላይና መሠሪ በሆነው የሥርዓቱ የፕሮፓጋንዳ ስልት ሰለባ በመሆን፣ ወይም በአድር ባይነት፣ ወይም በጥቅመኝነትም ሆነ በማንኛውም ሌላ ምክንያት የወቅቱን ሥርዓት እየደገፍን የምንገኝ ዜጎች በታሪክና በትውልድ ፊት የየራሳችን የተጠያቂነት ድርሻ እንደሚኖርብን ተገንዝበን፥ ሥርዓቱን መቃወምና መታገል ቢያቅተን እንኳን ቢያንስ ዝም በማለት የሀገሪቱ ጥፋትና ውድቀት ቀጥተኛ ተጋሪ ከመሆን ልንቆጠብ ይገባል።

    1. በይስሙላ ምርጫ የሚፈታ ችግር የለንም

    ነጻና ፍትሐዊ ምርጫ ለማካሄድ የሚያስችል ውጤታማ የሽግግር ሂደት ባላካሄድንበት ሁኔታ የሚካሄደው የዘንድሮው ሀገራዊ ምርጫ ሂደትም ሆነ ውጤት የሀገሪቱን የፖለቲካ ቀውስ የበለጠ የማባባስ እንጂ የመፍታት አንደምታ አይኖረውም። ምርጫው ሳይጀመር ያለቀና ውጤቱም ሀገሪቱን ወደ ባሰ ቀውስ ማስገባት ወይም አምባገነናዊነትን ማጽናት መሆኑ አስቀድሞ የታወቀ ነው። ይህ ምርጫ ብልጽግና ፓርቲ በማንኛውም መንገድ አሸናፊ ሆኖ በሥልጣን ላይ ለመቀጠል ወስኖና ተዘጋጅቶ የገባበት ምርጫ ስለሆነ፥ የዚችን ደሃ ሀገር በጀት ከማባከን ያለፈ ፋይዳ አይኖረውም። በአጭሩ መጭው ምርጫ ነጻና ፍትሐዊ እንደማይሆን ሳይሆን እንዳልሆነ የቅድመ ምርጫው ሂደት በማያሻማ ሁኔታ አሳይቷል። የወቅቱ የፖለቲካ ችግር በዘላቂነት ሊፈታ የሚችለው በአንጻራዊነት ነጻ፣ ገለልተኛና ጠንካራ የዴሞክራሲ ተቋማትን ለመገንባት፣ ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች በነጻነትና በእኩልነት ምርጫ የሚወዳደሩበትን ሁኔታ ለማመቻቸት፣ ብሔራዊ መግባባትና ዕርቅን ለማስፈን፣ ብሎም ሕገ-መንግሥታዊ ማሻሻያ ለማድረግ በሚያስችል ሁሉን አቀፍ በሆነ የሽግግርና የሀሳብ ግብይት ሂደት (national dialogue) ነው እንጂ በተለመደው ዓይነት የታይታ የምርጫ ግርግር አይደለም።

    ወደ መዋቅራዊና ዘላቂ ለውጥ ለመግባት ከተፈለገ መፍትሔው የችኮላ ምርጫ ማካሄድ ሳይሆን በቅድሚያ ከፖለቲካ ጉዳይ ጋር በተያያዘ በመላው ሀገሪቱ የታሠሩ የፖለቲከኛ እስረኞችን መፍታት፣ ዜጎች ላይ የሚደረግ አፈናና ግድያን ማስቆም፣ የሀገሪቱ ሕግጋትና ተቋማት ሀገር ጠቀም በሆነ አግባብ እንዲሻሻሉ ማድረግና ቢያንስ ዶ/ር ዐቢይ ወደ ሥልጣን በመጡባቸው በመጀመሪያዎቹ ጥቂት ሳምንታት የታየው ዓይነት የዕርቅና የመቻቻል መንፈስ በሀገሪቱ እንዲሰፍን ማድረግ ያስፈልጋል።

    1. ልዩ ትኩረት አዲስ አበባ ከተማን ለማሸነፍ

    በተግባር እየተፈጸመ ከሚገኘው ግልጽ ድርጊት እንደምንረዳው ብልጽግና ፓርቲ ነጻና ፍትሐዊ በሆነ ምርጫ ተወዳድሮ በማሸነፍ ሳይሆን በአፈናና በኃይል በሥልጣን ላይ ለመቀጠል የወሰነ አምባገነን ኃይል ነው። ገዥው ፓርቲ የሚጠላቸውንና የሚፈራቸውን የፖለቲካ ፓርቲዎች ከፖለቲካ መድረኩ በማስወገድና የፓርቲ አመራሮችን በማሰር በወሰደው እርምጃ መጭው ምርጫ ነጻና ፍትሐዊ እንዳልሆነ ከወዲሁ በተግባር አረጋግጧል። ሆኖም ምርጫው በታሰበበት ጊዜ የሚካሄድ ከሆነ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ራሳቸውን ከሂደቱ ከማግለል ይልቅ አቅማቸውና ሁኔታው በፈቀደላቸው መጠን በምርጫው ተሳታፊ ቢሆኑ የተሻለ ይሆናል እላለሁ።

    ነገር ግን በቂ ዝግጅት አድርገውና የገዥውን ፓርቲ ሁለንተናዊ ተጽዕኖ በብቃት ተቋቁመው በሀገር ደረጃ መንግሥት ለመሆን በሚያስችል መጠን ምርጫውን ለማሸነፍ የሚኖራቸው ዕድል እጅግ ጠባብ መሆኑን በመገንዘብ ሙሉ ትኩረታቸውን አዲስ አበባ ከተማን ለማሸነፍ ማድረግ ይኖርባቸዋል። አዲስ አበባ ከተማን አሸንፎ ለመረከብም አንድነት ተኮር የሆኑ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የመተባበር ጉዳይ ምንም ዓይነት ቅድመ ሁኔታ ሊቀርብበት የማይገባና ምትክ የለሽ እርምጃ መሆኑን መገንዘብ አለባቸው። ግለሰብን በመጥላት የሀገርን ጥቅም ጥያቄ ውስጥ ማስገባት ከማንኛውም ኃላፊነት ከሚሰማው ፓርቲ የማይጠበቅ ተግባር ቢሆንም ምናልባት የእኔ ለጊዜውም ቢሆን ከምርጫውና ከትግሉ ሂደት ገለል ማለት ለተቃዋሚው ጎራ መተባበር አንድ ጥሩ አጋጣሚ ሊሆን እንደሚችል እገምታለሁ።

    የአንድነት ኃይሉ ምንም ዓይነት ድምጽ ሊባክን በማይችልበት ሁኔታ እርስ በርስ ላለመፎካከር አስቀድሞ ካልተስማማ በስተቀር፥ ብልጽግና ፓርቲና አጋሮቹ (በፓርቲም ሆነ በግል የሚወዳደሩ) አዲስ አበባን የማሸነፍ ዕድል እንደሚኖራቸው መገንዘብ ያስፈልጋል። ብልጽግና ፓርቲና አጋሮቹ አዲስ አበባን የማሸነፍ ዕድል ካገኙም የአዲስ አበባ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን የመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ጥቅምና ሕልውና አደጋ ውስጥ እንደሚገባ መገንዘብ ያስፈልጋል። በተጨማሪም በምርጫ 97 ሲሆን እንደታየው “ምርጫው ስለተጭበረበረ ያሸነፍነውን ወንበር ወይም ምክር ቤት አንረከብም” በሚል የተሠራው ታሪካዊ ስህተት በዘንድሮውም ምርጫ እንዳይደገም ፓርቲዎች ከወዲሁ በጉዳዩ ላይ መተማመንና መወሰን ይኖርባቸዋል።

    1. መፍትሔው ሁሉን አቀፍ የሆነ የሽግግር ሂደት መፍጠር ነው

    በአሁኑ ወቅት ሀገራችን በሁለት የጎረቤት ሀገራት (በኤርትራና ሱዳን) ሉዐላዊነቷ ተደፍሮ የግዛት ወረራ ተፈጽሞባታል። ይህ ወረራ ከማንኛውም ውስጣዊ ችግሮቻችን በላይ ቅድሚያ ትኩረት ሊሰጠውና በአስቸኳይ ሊቀለበስ የሚገባው ነው። ይህንን ማድረግ ሳንችል ኢትዮጵያውያን እንደ ሀገርና ሕዝብ የነጻነት ታሪክም ሆነ ሉዐላዊ ሕልውና አለን ብለን መናገር አስቸጋሪ ይሆናል። የወቅቱ መንግሥት በሀገር ውስጥ እየተፈጸመ ያለውን ብሔር ተኮር ጭፍጨፋ ማስቆምም ሆነ የሀገሪቱን ሉዓላዊነት ማስከበር ስላለመቻሉ የሚያቀርበው ማንኛውም ምክንያትም ተቀባይነት ሊኖረው አይገባም። የወቅቱ መንግሥትም ሆነ መንግሥትን በዋናነት የሚመሩት ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ እነዚህን ሁለት ቁልፍና መሠረታዊ የአንድ መንግሥት ኃላፊነቶች በአግባቡ መወጣት ስላልቻሉ ከእንግዲህ የሚኖራቸው ብቸኛ አማራጭ ችግሩን ለመፍታት የሚያስችል ሀገራዊ የሀሳብ ግብይት ሂደት (national dialogue) መጀመርና ሁሉን ዐቀፍ የሆነ የሽግግር ሂደት ማካሄድ ነው።

    የወቅቱ መንግሥት ቀደም ሲል በኢሕአዴግ ስም፣ አሁን ደግሞ በብልጽግና ፓርቲ ስም ሕዝባዊ ይሁንታ ሳይኖረው ለ30 ዓመታት በሥልጣን ላይ ያለ ኃይል ነው። ይህ መንግሥት የሀገሪቱን መሠረታዊ ፖለቲካዊ ችግሮች መፍታት ካለመቻሉም በላይ ይበልጥ እያባባሰውና እያወሳሰበው ይገኛል። ስለሆነም የወቅቱ ብልጽግና ፓርቲ በአንድ በኩል የሀገሪቱን አንድነትና ሉዓላዊነት ማስከበር ባልቻለበት ሁኔታ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ነጻና ፍትሐዊ ምርጫ አካሒዶ የሕዝብ እውነተኛ ውክልና ለማግኘት በሐቅ ባልተዘጋጀበት ሁኔታ የሀገሪቱን የፖለቲካ ሥልጣን በቋሚ ርስትነት ይዞ ሊቀጥል አይገባውም።

    ገዥው ብልጽግና ፓርቲ ከግለሰብ በላይ የሆነ ሚና አለኝ ብሎ የሚያምንና ድክመቱ የኔ ሳይሆን የመሪዎቼ ወይም የመሪዬ ነው ብሎ የሚያስብ ከሆነም ሀገሪቱ ለይቶላት ከመፍረሷ በፊት መሪዎቹን ወይም መሪውን የመቀየር ርምጃ ሊወስድ ይገባዋል። ይህንን ማድረግ ካልቻለ ግን ለሀገሪቱ ውድቀት ፓርቲውም እንደ ድርጅት ተጠያቂ ይሆናል።

    ከዚህ ውጭ በአንድ ሀገር የዘር ጭፍጨፋን ማስቆምና የውጭ ወረራን መከላከል ያልቻለ ማንኛውም መንግሥት በሥልጣን ላይ መቀጠል የሚችልበት ሕጋዊ፣ ፖለቲካዊም ሆነ ሞራላዊ ምክንያት የለም። ከዚህ በተጻራሪ የዘር ጭፍጨፋን ማስቆምና ሀገሪቱን ከውጭ ወራሪ መከላከል ያልቻለ መንግሥት፥ “ሌላ አማራጭ የለንም” በሚል ሰበብ በሥልጣን ላይ ሊቀጥል የሚችለው ኢትዮጵያ ሕልውናዋን ከጥፋት አድኖ የሚያስቀጥላት ትውልድና ዜጋ ያልፈጠረች መካን ሀገር መሆኗን አምነን ከተቀበልን ብቻ ይሆናል።

    በተጨማሪም በቅርቡ ትግራይ ክልል ውስጥ የገባንበት ጦርነት የሀገሪቱን አንድነት ከፍተኛ ጥያቄ ውስጥ የሚጥልና ከኛ ዘመንም አልፎ ምናልባትም ለልጅ ልጆቻችን የሚተርፍ ጣጣ የሚያስከትል አሳሳቢ ክስተት ነው። ስለሆነም ይህ ችግር በዘላቂነት በጦርነት ሊፈታ እንደማይችል በመገንዘብ ከሥልጣን ጥያቄ፣ ከበቀል፣ ከስሜትና ከጀብደኝነት በራቀ አተያይ ለችግሩ አስቸኳይ ሰላማዊና ፖለቲካዊ መፍትሔ መፈለግ ይኖርበታል።

    1. ሀገሪቱን ከሕልውና አደጋ መታደግ የሚችል ጠንካራ ፓርቲ መፈጠር አለበት

    ኢትዮጵያውያን ሁልጊዜም በሀገሪቱ በጎ የፖለቲካ ለውጥ እንዲመጣ የምንመኝና የምንፈልግ ቢሆንም ይህንን የሁልጊዜ ምኞታችንን ዕውን ለማድረግ የሚያስችል ጠንካራና ለመርህ ታማኝ የሆነ ፓርቲ መፍጠር እስካሁን አልቻልንም። ዛሬም እንደ ትናንቱ የሥርዓቱን ድክመቶችና ጥፋቶች ስንቆጥር የምንውል የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች፣ ምሁራን፣ ጋዜጠኞችና አክቲቪስቶች ብንኖርም ያለጠንካራ ፓርቲ መኖር ሀገሪቱን ከጥፋት መታደግም ሆነ ዘላቂ ለውጥ ማምጣት እንደማይቻል መገንዘብ የቻልን አይመስልም። በምሬት፣ በጩኸትና በውግዘት ብቻ ሊመጣ የሚችል ዘላቂ ለውጥ እንደማይኖር ተገንዝበን ለመጭው ትርጉም የለሽ ምርጫ ከምንሰጠው ትኩረት በላይ ለሀገሪቱ ችግሮች የሚመጥን ጠንካራና ታማኝ ፓርቲ በመፍጠር ሥራ ላይ ማተኮር አለብን። በተለይም አንድነት ተኮር የሆነው የፖለቲካ ኃይል ከመቼውም ጊዜ በላይ በተዳከመበትና በተበታተነበት ሁኔታ ኢትዮጵያን ከጥፋት ለመታደግ የሚያስችል አስተማማኝ ለውጥ ማምጣት እንደማይቻል በመገንዘብ አዲሱ ትውልድ ዋና ተዋናይ የሚሆንበት ጠንካራና ታማኝ ፓርቲ መፍጠር ቀዳሚና ለነገ የማይባል አጀንዳችን መሆን ይገባዋል እላለሁ። ይህንን ማድረግ ካልቻልን “አማራጭ የለም” በሚል ሰበብ አምባገነኖችና የሀገርን ሕልውና አደጋ ላይ የሚጥሉ ፓርቲዎች ወይም መሪዎች ሁልጊዜም በሥልጣን ላይ የሚቀጥሉበትን ዕድል እንፈጥራለን።

    1. የቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረት ለሰላም

    የወቅቱ የሀገራችን ፖለቲካዊ ሁኔታ በብዙ ውጥረቶች የተሞላና በቀላሉ ተሰባሪ ነው። በዚህ ምክንያት ውጤታማ በሆነ የሽግግር ሂደት ሳይታለፍ የሚካሄደው መጪው ምርጫ ሀገራችንን ወደ ባሰ ግጭትና ትርምስ ሊያስገባ የሚችልበት ሰፊ ዕድል አለ። ይህ ስጋት በቂ መነሻ ምክንያት ያለው መሆኑን በመረዳት ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች የምርጫ ሂደቱ ወደ ግጭትና ብጥብጥ እንዳያመራ የማድረግ የጋራ ኃላፊነት አለባቸው። ይህንን በመገንዘብ ከፍተኛ ጥንቃቄ የተሞላበትና የሰከነ ሰላማዊ የምርጫ ቅስቀሳ ሊያካሒዱ ይገባል። አሁን ከምንገኝበት እጅግ ከባድና ውስብስ የፖለቲካ ሁኔታ አንጻር የሰላም እጦት የሀገሪቱን ሕልውና የሚፈታተን አደጋ ይዞብን ሊመጣ ስለሚችል፥ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምርጫውን አሸናፊ ለመሆን ከመሥራት በላይ ለሰላም መኖር የቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረት መስጠት ይኖርባቸዋል።

    በአግባቡ ካልተጠቀምንበትም በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ ያለው ማኅበራዊ ሚዲያ የብሔራዊ ደኅንነታችን ዋና የአደጋ ምንጭ ሊሆን ይችላል። ይህንን እውነታ በመገንዘብ ማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚ የሆኑ ዜጎቻችን በምርጫው ወቅት የሚኖራቸው ሚና ለሰላም ቅድሚያ በሚሰጥ የኃላፊነት ስሜት ሊካሄድ ይገባዋል። በአጠቃላይ ሀገራችን በአሁኑ ወቅት በውስጥም በውጭም ከፍተኛና አሳሳቢ ውጥረት ውስጥ የምትገኝ መሆኑን በመገንዘብ ለሰላም መኖር የቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረት መስጠት ግዴታችን መሆኑን መገንዘብ ያስፈልገናል።

    1. ሕገ-መንግሥቱ ሳይሻሻል የፖለቲካ ችግራችን አይፈታም

    የወቅቱ የሀገራችን የፖለቲካ ችግር የሀገራዊ ብሔርተኞችንና የንዑስ ብሔር ብሔርተኞችን የተካረረ የፖለቲካ ቅራኔ በአንጻራዊነት በሚያቻችል አግባብ የወቅቱን ሕገ-መንግሥት ከማሻሻል ባነሰ ሌላ የመፍትሔ ርምጃ ሊፈታ አይችልም። ሕገ-መንግሥቱ እስካልተሻሻለ ድረስ ከማንነት ጋር በተያያዘ በአሁኑ ወቅት የተነሱትም ሆነ ወደ ፊት ባልተቋረጠ ሁኔታ ሊነሱ የሚችሉ ጥያቄዎች የሀገሪቱን ሰላምና ሕልውና እያወኩ መቀጠላቸው አይቀርም። ይህ ችግር ዘላቂ መፍትሔ እስካላገኘ ድረስም የሀገሪቱ ሰላም፣ አንድነት፣ ሕልውናና የኢኮኖሚ እጥረት በዘላቂነት መፍትሔ ሊያገኝ አይችልም።

    ከዚህ ግንዛቤ ጋር በተያያዘ በኔ በኩል ለውይይት መነሻ የሚሆን የሕገ-መንግሥት አማራጭ ረቂቅ ሰነድ በመጽሐፍ መልክ በማሳተም ላይ እገኛለሁ። የሕገ-መንግሥቱ መሻሻል ለሀገሪቱ የፖለቲካ ችግሮች መፈታት የሚኖረውን ምትክ የለሽ አዎንታዊ አስተዋዕፆ የምትገነዘቡ መገናኛ ብዙኃን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ምሁራንና ዜጎች በረቂቅ ሰነዱ ላይ ውይይት በማድረግ ትችት እንድታቀርቡበትና እንድታዳብሩት፣ ከተቻለም ሰነዱን በመጭው ምርጫም ሆነ በቀጣዩ የትግል ሂደት የጋራ የትግል አጀንዳ አድርጋችሁ እንድትጠቀሙበት በዚህ አጋጣሚ ጥሪዬን አቀርባለሁ።

    በመጨረሻም ከአቅም በላይ በሆነ የጤና ምክንያት ቢሆንም ሀገራችን ከመቼውም ጊዜ በላይ ዋጋ የሚከፍልላት ዜጋ በሚያስፈልጋት በአሁኑ ወቅት ለጊዜውም ቢሆን ከትግል ተሳትፎዬ ለመታቀብ በመገደዴ፥ የትግል አጋሮቼንና የዐላማ ደጋፊዎቼን ሁሉ ከልብ ይቅርታ እጠይቃለሁ። ይህንን የምለው ከእኔ ብዙ እንደምትጠብቁና ለእኔ ለራሴ እንደሆነብኝ ሁሉ ለእናንተም ይህ ክስተት ድንገተኛ መርዶ እንደሚሆንባችሁ ስለምገነዘብ ነው። ወደፊት የጤና ሁኔታዬ ተሻሽሎ እስከመጨረሻው በፖለቲካ ሂደቱ ለመቀጠል ለራሴ የገባሁትን ቃል ለመፈጸም ፈጣሪ ዕድል እንደሚሰጠኝ ተስፋ እያደረግኹ ሀገራችን ኢትዮጵያ መልካሙ ሁሉ እንዲገጥማት ያለኝን ልባዊ ምኞት በዚህ አጋጣሚ እገልጻለሁ።

    ልደቱ አያሌው

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ያለችበት የህልውና አደጋ በአቶ ልደቱ አያሌው እይታ

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ጋዜጣዊ መግለጫ
    ኦሮሚያ ክልል፡ የዋስትና መብትን በተቀላጠፈ መንገድ ስለማረጋገጥ

    የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሰበታ ልዩ ችሎት ለአራት ወራት ያህል በእስር በቆዩት በአቶ ለሚ ቤኛ እና በአቶ ዳዊት አብደታ ጉዳይ የዋስትና መብታቸውን በማረጋገጥ የሰጠውን ትክክለኛ ውሳኔ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) እውቅና እየሰጠ፣ የኦሮሚያ ክልል መንግሥት ሥራ አስፈጻሚና የፍትሕ አካላት በተመሳሳይ መልኩ የሌሎችንም ተጠርጣሪዎች የዋስትና መብት መከበሩን እንዲያረጋግጡ ጥሪ ያቀርባል።

    ኢሰመኮ መስከረም 12 ቀን 2013 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፥ በፍርድ ቤት የዋስትና መብት ተፈቅዶላቸውና የዋስትና ሁኔታውን አሟልተው ከእስር እንዲለቀቁ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ የሰጠላቸው ሰዎች በእስር እንዲቆዩ መደረጉ ፍትህን የሚያጓድልና ሰብአዊ መብቶችን የሚጥስ ተግባር መሆኑን በመግለጽ፥ በፍርድ ቤት የዋስትና መብት ተከብሮላቸዉ በእስር ላይ የነበሩ ሰዎች በአስቸኳይ ከእስር እንዲፈቱ ማሳሰቡ ይታወሳል።

    በዚሁ መሠረት ኮሚሽኑ በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ፖሊስ ጣቢያዎች በእስር ስለሚገኙ ሰዎች ሁኔታ ሊወሰድ የሚገባውን እርምጃ ለሚመለከታቸው የክልሉ ኃላፊዎች በማሳወቅ ክትትሉን የቀጠለ ሲሆን፤ በተለያዩ ቦታዎች አበረታች አርምጃዎች የተወሰዱ ቢሆንም አሁንም ድረስ በተለይ የዋስትና መብት ተፈቅዶላቸው በእስር የሚገኙ ሰዎች አሉ። ከእነዚህ መካከል የአቶ ልደቱ አያሌው እና የዶ/ር ሁሴን ከድር ጉዳይ አፋጣኝ እልባት የሚሻ መሆኑን ኮሚሽኑ ያሳስባል።

    ከሐምሌ 18 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በቢሾፍቱ ከተማ በእስር ላይ ለሚገኙት አቶ ልደቱ አያሌው ፍርድ ቤት በዋስትና እንዲፈቱ ተደጋጋሚ ትዕዛዝ ቢሰጥም፤ ውሳኔው ተግባራዊ ሳይሆን ቀርቶ በክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ተጨማሪ ክስ የተመሠረተባቸው ሲሆን፤ አሁንም በድጋሚ ያቀረቡት የዋስትና መብት ጥያቄ ላይ ውሳኔ ለመስጠት ለኅዳር 18 ቀን 2013 ዓ.ም. ቀጠሮ መሰጠቱ ይታወቃል። በኢሰመኮ ምርመራ መሠረት በአቶ ልደቱ ላይ የቀረቡት ክሶች የዋስትና መብት የማያስከለክሉ ከመሆኑም በተጨማሪ፣ ኢሰመኮ የተመለከተው የጤንነታቸው ሁኔታ ማስረጃዎች የዋስትና መብት ጥያቄውን በአፋጣኝ ተግባራዊ ማድረግን አስፈላጊነት ያስረዳል። ስለሆነም የአቶ ልደቱ አያሌው የዋስትና መብት በአስቸኳይ ሊፈቀድ የሚገባ ነው።

    በሌላ በኩል ከሐምሌ 4 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በእስር ላይ የሚገኙት ዶ/ር ሁሴን ከድር የአጋርፋ ወረዳ ፍርድ ቤት ጥቅምት 11 ቀን 2013 ዓ.ም. የዋስትና መብት ፈቅዶላቸዉ ከእስር እንዲለቀቁ ትዕዛዝ ከመስጠቱም በተጨማሪ፥ የፌደራል ዐቃቤ ሕግ ጥቅምት 13 ቀን 2013 ዓ.ም. ከፖሊስ በቀረበለት የተጠርጣሪው የምርመራ መዝገብ ላይ በሰጠው ውሳኔ ክስ ለማቅረብ የሚያበቃ ማስረጃ አለማግኘቱን ጠቅሶ የምርመራ መዝገቡን ዘግቷል። ይሁንና ውሳኔው ተግባራዊ ሳይሆን ቀርቶ ፖሊስ ለኮሚሽኑ እንዳሳወቀው በተጨማሪ ወንጀል በመጠርጠራቸው አሁንም በእስር ላይ ናቸው፡፡ ዶ/ር ሁሴን ከድር አብዛኛውን የእስር ጊዜ የቆዩት በአጋርፋ እስር ቤት ሲሆን፤ ጥቅምት 27 ቀን 2013 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ ከተማ ተወስደው አሁንም በኦሮሚያ ፖሊስ ቁጥጥር ስር እንደሚገኙ ኢሰመኮ የተረዳ ቢሆንም፤ ወደ አዲስ አበባ ከመጡ ወዲህ ከቤተሰቦቻቸው አለመገናኘታቸው ኮሚሽኑን አሳስቦታል። ስለሆነም ዶ/ር ሁሴን ከድር በአስቸኳይ በቤተሰባቸው ሊጎበኙ የሚገባ ከመሆኑም በተጨማሪ፤ ሊያስከስስ የሚችል አሳማኝ ክስ ካለ በአፋጣኝ ሊቀርብ፣ አሊያም ከእስር ሊለቀቁ ወይም የዋስትና መብታቸው በአስቸኳይ ሊከበር ይገባል። የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ እንደገለጹት “የዋስትና መብት በሕገ መንግሥቱና ኢትዮጵያ በተቀበለቻቸው የሰብአዊ መብቶች ስምምነቶች የተረጋገጠ መሠረታዊ መብት እንደመሆኑ፥ በሕግ በግልጽ ከተመለከቱ ሁኔታዎች በስተቀር የዋስትና መብት በተቀላጠፈ አሠራር ተግባራዊ ሊደረግ የሚገባው ነው።” አክለውም “በዚህ ረገድ ፍርድ ቤቶች የተከሳሾችን የዋስትና መብት የሚያረጋግጡ ውሳኔዎችን እየወሰኑ መሆናቸው የሚበረታታ ተግባር ነው” ብለዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን

    የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን

    Anonymous
    Inactive

    የምንገኝበት የፖለቲካ ቀውስ፣ ፈጣን ፖለቲካዊ መፍትሔ ይፈልጋል!
    ከኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ሥራ አስፈፃሚ የተሰጠ መግለጫ

    በኢትዮጵያ ሕዝብ የረዥም ጊዜ መራራ ትግል 2010 ዓ.ም ላይ የመጣው ለውጥ ሕዝቡ ከነበረው ተስፋ በተቃራኒ የመክሸፍ አደጋ አጋጥሞታል።

    ከእንግዲህ በሀገራችን እውነተኛ ዴሞክራሲ እውን እንዲሆን፣ የዜጎች ሰብዓዊና ፖለቲካዊ መብቶች እንዲከበሩ፣ የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን፥ በእርግጠኝነት ደጋግሞ ቃል በመግባት ከፍተኛ የሕዝብ ድጋፍ አግኝቶ የነበረው የዶ/ር ዐቢይ አህመድ መንግሥት ለሕዝብ የገባቸውን ቃሎች ሁሉ በማጠፍ የለየለት አምባገነናዊ መንግሥት መሆን ጀምሯል።

    በዚህም ምክንያት የሀገራችንን ሰላምና መረጋጋት ክፉኛ የሚፈታተንና የሀገሪቱን አጠቃላይ ህልውና አደጋ ላይ ሊጥል የሚችል ከፍተኛ የፖለቲካ ውጥረትና ቀውስ በሀገራችን ተከስቷል። በብዙ ዜጎች ከፍተኛ መስዋዕትነት የተገኘው ለውጥ መክሸፉና ሀገሪቱ ተመልሳ በሌላ አምባገነናዊ ሥርዓት ስር መውደቋ እጅግ ልብ የሚሰብር አሳዛኝ ክስተት ቢሆንም፥ የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ሀገራችንን ከውድቀት ለማዳን ዛሬም ዕድሉ በእጃችን ነው ብሎ ያምናል።

    ይህ ከውድቀት የመዳን እድል እውን ሊሆን የሚችለውም በአንድ ገዥ ፓርቲ የበላይነትና ፈላጭ ቆራጭነት፣ ወይንም ባለፉት 27 ዓመታት ያየነው ዓይነት ውጤቱ አስቀድሞ የሚታወቅ የይስሙላ ምርጫ በማካሄድ አይደለም።

    በኢዴፓ እምነት ከዚህ አሳሳቢ የህልውና አደጋ ወጥተን ወደ ተሻለ ሁኔታ ለመሸጋገር ቢያንስ የሚከተሉት አራት ተጨባጭ እርምጃዎች ሊወሰዱ ይገባል ብለን እናምናለን፤

    1. በሀገራችን የሕግ የበላይነት የመጥፋት ችግር እጅግ አሳሳቢ ወደ ሆነ የከፋ ደረጃ እየተሸጋገረ ነው። በኢዴፓ አመራር በአቶ ልደቱ አያሌው እና በሌሎችም የፖለቲካ ሰዎች ላይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሲሆን እንደታየው ሰዎች በፈጠራ ክስ ያለአግባብ የሚንገላቱበትና የፍርድ ቤቶች ውሳኔና ትዕዛዝ የማይከበርበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ያለ ፍርድ ቤት ነፃነት በአንድ ሀገር ላይ የሕግ የበላይነት ሊከበር ስለማይችል ፍርድ ቤቶችን ለፖለቲካ ጉዳይ ለመጠቀም፤ እና የፍርድ ቤቶችን ውሳኔ በመጣስ እየተፈፀመ ያለው ሕገ-ወጥ ድርጊት በአስቸኳይ መቆም አለበት።
    2. በአሁኑ ወቅት የኢዴፓ/አብሮነት፣ የኦፌኮ፣ የኦነግና የባልደራስ ከፍተኛ ዓመራሮች፣ እንዲሁም በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች /በተለይም በኦሮሚያ ክልል/ ከፖለቲካ ጋር በተያያዘ በእስር ላይ ስለሚገኙ በሀገራችን ከፍተኛ የፖለቲካ ውጥረት ነግሷል። ይህ አሳሳቢ ውጥረት ወደ ሌላ አሳሳቢ ደረጃ ከመሸጋገሩ በፊት ሁሉም ከፖለቲካ ጉዳይ ጋር በተያያዘ በእስር ላይ የሚገኙ ዜጎች ያለምንም ቅድመ-ሁኔታ በአስቸኳይ መፈታት አለባቸው።
    3. ሀገራችን በዚህ ዓይነት የፖለቲካ ውጥረት ውስጥ ሆና በፍፁም ሀገራዊ ምርጫ ለማካሄድ መታሰብ የለበትም። ከአሁን ጀምሮ እስከሚቀጥለው ሀገራዊ ምርጫ ድረስ ሀገሪቱ እንዴት ትተዳደር? ምርጫው ከመካሄዱ በፊት በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል የተፈጠረውን ውጥረት ለማርገብ ምን ዓይነት ውይይት እና ድርድር ይካሄድ? ከክልልነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ በደቡቡ የሀገራችን ክፍል ያለው የፖለቲካ ውጥረት እንዴት ይርገብ? ሀገሪቱ ቋሚ መንግሥት እስከሚኖራት ድረስ የኢኮኖሚ ደህንነቷን የሚያስጠብቅ ምን ዓይነት እርምጃ ሊወሰድ ይገባል? ያልለየለትን የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ስርጭት በተመለከተ ምን ልናደርግ ይገባል? በሚሉትና በመሳሰሉ መሠረታዊ ጥያቄዎች ዙሪያ መፍትሄ ማመንጨት የሚያስችል አንድ ሁሉን አቀፍ የውይይትና የድርድር ሂደት /national dialogue / በአስቸኳይ መጀመር አለበት።
    4. በአሁኑ ወቅት በፌደራሉ መንግሥትና በትግራይ ክልል መካከል እየታየ ያለው ተገቢ ያልሆነና አሳሳቢ ፍጥጫ በአስቸኳይ መቆም አለበት። ጉዳዩ ከሀገሪቱ ሰላምና አንድነት ጋር በተያያዘ ከፍተኛ እንደምታ ያለው እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ በመሆኑ ያለምንም ቅድመ-ሁኔታ በውይይትና በድርድር መፈታት አለበት።

    በአጠቃላይ እነዚህ መሠረታዊ ጥያቄዎች በአግባቡ መመለስ ሳይችሉ ከቀሩና በሀገሪቱ ላይ የሚታየው ውጥረት የበለጠ ተባብሶ በዜጎችና በሀገር ላይ ለሚደርሰው ለማንኛውም የከፋ ጉዳት ዋናው ተጠያቂ ብልፅግና ፓርቲ መሆኑን እንገልፃለን። ከማንም በላይ የጉዳዩ እና የሀገሪቱ ባለቤት ሕዝቡ ነውና ከፍ ሲል የዘረዘርናቸው ጥያቄዎች በአስቸኳይ ተገቢ ምላሽ አግኝተው ሀገራችን ከውድቀት እንድትድን ሁሉም ሀገር ወዳድ ዜጋ በብልፅግና ፓርቲ ላይ ሕጋዊ እና ሰላማዊ ተፅዕኖ እንዲያደርግ ኢዴፓ ጥሪውን ያቀርባል።

    የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ
    ጥቅምት 3 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ

    የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ)

    Anonymous
    Inactive

    በማንኛውም ዜጋ ላይ የሚፈፀም ኢፍትሃዊነት በሁላችንም ላይ እንደተፈፀመ ይቆጠራል
    አንዱዓለም አራጌ

    ከዚህ ቀደም በጣም በአመዛኙ የፓርቲዬን አቋም ካልሆነ በስተቀር እምብዛም የግል አቋሜን አንፀባርቄ አላውቅም።

    ብዙውን ጊዜ ተቋሞቻችን ሕጸጻቸውን እያረሙ ሁላችንም የምንደገፍባቸው ተቋማት እንዲሆኑ እድልም ሆነ ጊዜ መስጠት ተገቢ መሆኑን አምናለሁ። ይሁን እንጂ፥ ትናንት የኢትዮጵያ ሕዝብ በነፍስና በስጋው ተወራርዶ መራር ሕዝባዊ ትግል ያደረገው ዝቅ ብለን የምንመለከተውን ዓይነት ግፍ ለማስተናገድ አለመሆኑ እሙን ነው።

    በ1993 ዓ.ም በጊዮርጊስ የጊዜ ቀጠሮ ፍርድ ቤት በተለያዩ ሁለት ችሎቶች፣ በተመሳሳይ ዕለት፣ በተመሳሳይ ሰዓት የተፈፀሙ ሁለት ውሳኔወችን ለማስታወስ እወዳለሁ። አንደኛው ችሎት በሀቪየስ ኮርፐስ (habeas corpus) ክስ አማካኝነት፣ እነአቶ ታምራት ታረቀኝን ካሰረበት አምጥቶ ለፍርድ ቤቱ ያቀርብ ዘንድ ፓሊስን ፍርድ ቤት በተደጋጋሚ ቢያዝም፥ ትዕዛዙ ባለመፈፀሙ በወቅቱ የፍትህ ሚንስትር የነበሩት አቶ ወረደወልድ ወልዴ ታስረው እንዲቀርቡ ባዘዘው መሠረት ታስረው ቀረቡ። ፍርድ ቤቱም የአንድ ወር እሥራት ፈረደባቸው። በሌላ ደግሞ የዳኛ ብርቱካን ሚደቅሳ ችሎት አቶ ስዬ አብርሃ ቀርበው የወ/ት ብርቱካን ችሎት አርነት ሰደዳቸው። ይሁን እንጂ ለቤታቸው ሊበቁ የተገባቸው አቶ ስዬ አብርሃ በአፈሙዝ አስገዳጅነት ወህኒ እንዲወርዱ ተገደዱ። ሚኒስትር ወረደወልድ ወልዴ ደግሞ ሳይገባቸው ለሞቀ ቤታቸው በቁ።

    ይህን የሃያ ዓመት ታሪክ ያለምክንያት አላነሳሁትም። ከእልህ አስጨራሽ ሕዝባዊ ትግል በኋላ የለውጥ ሽራፊ ለማየት ብንጓጓም ከሃያ ዓመት በኋላ ተመሳሳይ ለከት ያጣ ግፍ እያስተናገድን ነው። በ”ለውጡ” የመጀመሪያ ወራት ሕዝቡ የተራበ አንጀቱን አስሮ ይስቅ የነበረው፣ ድጋፉንም የቸረው ከእንግዲህ በፍትህ፣ በእውነትና በእኩልነት የምጠግብበት ዘመን ጠባ ብሎ በማመኑ ይመስለኛል። ከፈጣሪ በታች ተስፋችን በእጃችን መሆኑ የቀትር ያህል ግልፅ ቢሆንም፣ ከሃያ ዓመት በኋላ ተመሳሳይ የፍትህን መጨንገፍን ሳይ ጥልቅ ሀዘን አልተሰማኝም ብል ግን እውነቱን አልናገርም።

    በቅርቡ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ሥራ አስፈፃሚ አባል ወ/ሮ ሂሩት ክፍሌ ፍርድ ቤት የዋስትና መብቷን ቢያከብርላትም፥ ፓሊስ ላለመልቀቅ ያሳየውን ዳተኝነት እናስታውሳለን። በተመሳሳይ የአሥራት ቴሌብዥን ጋዜጠኞችንም እንዲሁ በመከራ መልቀቁ የቅርብ ጊዜ ትውስታችን ነው።

    ዛሬ ብዕሬን እንዳነሳ ያደረገኝ ጉዳይ የአቶ ልደቱ አያሌው ጉዳይ ነው። ስለአቶ ልደቱ ከእኔ በላይ ብዙ ነገሮችን አጣቅሶ ማቅረብ የሚችል ሌላ ማን እንዳለ በእውነት አላውቅም። በፓርቲዬም ላይ ቢሆን በተደጋጋሚ ምን ያደርጉ እንደነበር ፈፅሞ ዘንግቼው አይደለም። አቋማቸው ከአቋሜ ስለገጠመም አይደለም። ይልቅስ አቶ ልደቱ እራሳቸውን መከላከል በማይችሉበት በዚህ ሁኔታ አንዳች አሉታዊ ጉዳይ አንስቼ እሞግታቸው ዘንድ ፈፅሞ ህሊናዬ አይፈቅድልኝም።

    በተወሰነ መልኩ የቀደመውን ለአንባቢ ያስታወስኩትም ቢሆን፥ የቆምኩበትን የሀሳብ ማዕዘን ለማሳየት ይረዳኝ ዘንድ ግድ ሆኖብኝ እንጂ ምቾት ተሰምቶኝ አይደለም። ይልቅስ ከላይ ከፍ ብዬ ከጠቀስኳቸው ወገኖቻችንም በከፋ ሁኔታ የ“ፓሊስ ጢባጢቤ” መጫወቻ ሆነው ሳይ፥ እርሳቸውን የወጋ ጦር እኔንም እንደወጋኝ ተሰምቶኛል። በተለያየ ደረጃ የሚገኙ የኦሮሚያ ክልል ፍርድ ቤቶች የዋስትና መብታቸው ተከብሮ ከእስር እንዲለቀቁ ቢያዙም በፓሊስ እንቢተኝነት ግን በእስር ላይ ይገኛሉ። ውርደቱ፣ መረገጡ፣ ንቀቱና ኢፍትሃዊነቱ፣ የኢፍትሃዊነትን ስቃይ ለምናውቅ ዜጎች ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያውያን ሁሉ ነው። በማንኛውም ዜጋ ላይ የሚፈፀም ኢፍትሃዊነት በሁላችንም ላይ እንደተፈፀመ የሚጠራጠር ካለ እርሱ ፍፁም ማስተዋል የጎደለው ነው።

    በኢትዮጵያችን እየታየ ያለው ለከት ያጣ ግፍ ቅስም የሚሰብርና በምንም ዓይነት መንገድ ልንታገሰው የማይገባ ኢፍትሃዊ ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያን ያዋረደ ወደር-አልባ የነውረኝነት ተግባርም ነው።

    በፈጣሪ እንደምትታመኑ ደጋግማችሁ የነገራችሁን ወገኖች፥ በሚፈፀመው ግፍ ፈጣሪ የሚደሰትበት ይመስላችኋል? የሚሠራውን ኢፍትሃዊነት በአስቸኳይ እስካላስቆማችሁ የፈጣሪም ሆነ የሕዝብም ቁጣ እሩቅ እንደማይሆን ለመናገር ነቢይነትን አይጠይቅም።

    Free Lidetu Ayalew
    አንዱዓለም አራጌ

    አቶ አንዱዓለም አራጌ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ምክትል መሪ ሲሆኑ፤ ከዚያ በፊት ደግሞ የቀድሞው የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት እና ፕሬስ ሴክሬተሪ ነበሩ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    አቶ አንዱዓለም አራጌ

    Anonymous
    Inactive

    ግልፅ ደብዳቤ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት ለክብርት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ
    ነጋችንን እንዳንፈራ ሕግ ተርጓሚው ይፈራ!

    ክብርት ፕሬዝደንት፥ እንደሚያውቁት የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ባለፉት 20 ዓመታት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ በጭፍን ከመደገፍ እና ከመቃወም ወጥቶ በምክንያት መቃወም እና መደገፍ የፖለቲካ ባህል፣ አስተሳሰብ እንዲገነባ የራሱን ሚና ሲጫወት የቆየ ፓርቲ ነው። ይሄ ስልጡን የፖለቲካ ባህል እንደምንፈልገው ፍሬ ባያፈራም ቀላል የማይባል የፖለቲካ ባህል ለውጥ ጭላንጭል አይተናል ብለን እናስባለን። ይህን አዲስ ባህል የፈጠረ ፓርቲ ግን ለሱ የሚመጥነውን ያህል ክብር ሊሰጠው ቀርቶ በየዘመኑ የመጡ ገዥዎች አና ጽንፈኛ ፖለቲከኞች በሴራ አላላውስ ብለውታል።

    ኢዴፓ ከለውጡ በፊት ባሉት ሁለት ዓመታት እና ከለውጡ ማግስት ባሉ ሁለት ዓመታት የተቀነባበረ በሚመስል ደረጃ ፓርቲያችንን የማዳከም እና ከፖለቲካው መድረክ እንዲገለል የማድረግ ከፍተኛ ደባ እየተሠራበት ይገኛል። ይህን በፓርቲው ህልውና ላይ የተቃጣውን መሠረተ ሰፊ የማፍረስ እርምጃ በተለያዩ መድረኮች እያሸነፍን እዚህ ብንደርስም፥ አሁንም ድረስ በግፍ የተነጠቅነውን የፓርቲውን ቢሮዎች፣ ንብረቶች ገንዘቦች እና ሰነዶች ለማስመለስ በፍትህ አደባባይ እየታገልን ነው። አሁንም በቢሮክራሲ ውጣ ውረድ እየተንገላታን ነው፤ ባለፉት አራት ዓመታት በፓርቲያችን ህልውና ላይ እየደረሰ ያለውን ፈተና እየታገልን ባለንበት ሁኔታ ይባስ ብሎ የአርቲስት ሃጫሉን ሞት ተከትሎ ሌላ የፖለቲካ ጫና እየደረሰብን ይገኛል። ይኸውም የፓርቲያችን ብሔራዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ልደቱ አያሌው ያለጥፋታቸው የፖለቲካ ጥቃት ሰለባ እንዲሆኑ ተፈርዶባቸዋልል። አቶ ልደቱ በወንጀል ድርጊት ውስጥ መሳተፋቸው በተጨባጭ ማስረጃ እስከተረጋገጠባቸው ድረስ አይያዙ አንልም፤ ለሕግ የበላይነት ሲታገል የኖረ ፓርቲ በዚህ ረገድ ምንም ብዥታ የለበትም። ነገም ከነገ ወዲያም ማንም በፖለቲካ ፓርቲ አመራርነትና አባልነት ስም ከሕግ ማምለጥ አለበት ብለን አናምንም፤ ነገር ግን ፖሊስ እርቸውን አስሮ ማስረጃ ሲፈልግ ሲታይ፣ ማስረጃ ማቅረብ ተስኖት ፍርድ ቤት ልቀቅ ብሎ ሲወስን እምቢኝ ካለ የታሰረው ወንጀል ሠርቶ ሳይሆን ለምን የተለየ አሰብክ ተብሎ እንደሆነ ድርጊቱ ያሳብቃል። ከዚህ በተጨማሪ አቶ ልደቱ መንግሥት ላይ የሰላ ትችት በማቅረባቸውና በመቃወማቸው ብቻ እንደታሰሩ በፍትህ ሂደቱ ላይ የታዩትን ህጸጾች ስለታዘብኩ ነው ለእርስዎ አቤት ማለቴ። አቶ ልደቱ የሃጫሉን ሞት ተከትሎ ሁከት በተቀሰቀሰበት ሰዓት የፌዴራል ፖሊስ ለህይወትህ ያሰጋሃል ብሎ አጅቦ ከቢሾፍቱ ወደ አዲስ አበባ አምጥቷቸዋል። ይሄ ሆኖ ሳለ በፖሊስ የተከሰሱበት እና የተጠረጠሩበት ወንጀል የቢሾፍቱ ከተማ ወጣቶችን አደራጅተሃል፣ በገንዘብ ረድተሃል እና አስተባብረሃል ቢሆንም ተጨባጭ ማስረጃ ፖሊስ ለፍርድ ቤት ሊያቀርብ አልቻለም። በኋላም የተሰጠውን የምርመራ ግዜ በመጨረሱና አቃቢ ሕግም ተጨማሪ የምርመራ ግዜ ባለመጠየቁ ፍርድ ቤቱ በነፃ አሰናብቷቸዋል። ነገር ግን ይህንን የፍርድ ቤት ውሳኔ ሰምቶ ፖሊስ መልቀቅ ሲገባው፥ ከ17ቀናት በላይ በሕገ-ወጥ መንገድ አስሮ ሲያሰቃያቸው ቆይቷል። እኛም በፍትህ ሂደቱ ተስፋ ቆርጠን፣ አቶ ልደቱም ጠበቆቻቸውን አሰናብተው ፌደራል ላይ አካልን ነፃ የማውጣት ክስ ልንመሠርት ስንዘጋጅ ደግሞ ሌላ ክስ አዳማ ላይ ተከፈተባቸው።

    ይሄ ክስ በመጀመሪያው የቢሾፍቱ ከተማ የክስ መዝገብ ላይ ሕገ-ወጥ ሽጉጥ ተገኝቶባቸዋል ተብሎ ማስረጃ ቀርቦበት ውድቅ የተደረገ የክስ ጭብጥ ነው። የሆነው ሆኖ በሕገ-ወጥ መሣሪያ በመያዝ በሚል ምሥራቅ ሸዋ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቢከሰሱም ፍርድ ቤቱ የአቃቢ ሕግንና የጠበቆቻችንን የሕግ ክርከር መርምሮ አቶ ልደቱን በ100,000 (አንድ መቶ ሺህ) ብር ዋስትና ውጭ ሆነው እንዲከራከሩ ወሰነ። እኛም 100,000 (አንድ መቶ ሺህ) ብር አስይዘን ማስፈቻ ትዕዛዝ ለፖሊስ ብንወስድም አሁንም ፖሊስ ትዕዛዙን አልፈፅምም አለ። እኛም ትዕዛዙን ለሰጠው ፍርድ ቤት አቤት ብለን መልስ ሊነገረን ለበነጋታው ቀጠሮ ይዘን መጣን። ነገር ግን ማታ የአቶ ልደቱ ዋስትና እንደታገደ በመገናኛ ብዙኃን ሰማን። በዚህ ሁኔታ አቶ ልደቱ ከልብ ህመም ጋር ተያይዞ የልብ ቀዶ ጥገና ባደረጉበት አሜሪካ ቀጠሮአቸው እንዲያልፍ ተደርጎ፥ ከዚህ በተጨማሪ ካለባቸው የአስም ህመም የተነሳ ለኮሮና ተጋላጭ መሆናቸው በሐኪሞችም በፍርድ ቤቶቹም ታምኖበት ጭምር ውጭ ሆነው እንዲከራከሩ የተደረገው ጥረት በፖሊስ እምቢተኝነት ህይወታቸው አደጋ ውስጥ እንዲወድቅ ተደርጓል። በሂደቱ ሁሉ አቶ ልደቱ እያቀረቡት ያለው ቅሬታ ሁሉ ተቀባይነት እያጣ፣ የፍርድ ቤት ውሳኔ እየተሻረ የፖለቲካ ውሳኔ አሸናፊ እየሆነ ይገኛል። አሁንም እንደቀጠለ ነው። እና በፍትህ አደባባይ አቶ ልደቱ ደግመው ደጋግመው ነፃ ቢሆኑም ፖሊስ አለቅም ማለቱን ሳይ ነው የአቶ ልደቱ እስር ሕግ ጥሰው ሳይሆን በፖለቲካ እስር ነው ብዬ በእርግጠኝነት መናገሬ፤ እንጂማ ሁለቴ ያሸነፈ አይደለም አንድ ግዜም ያሸነፈ ቤቱ እስር ቤት አይሆንም ነበር። ይሄ የሚያሳየው የፍትህ ሥርዓቱ ላይ የበዛ የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት መኖሩን ነው።

    ክብርት ፕሬዝደንት፥ የፍትህ ተቋሙ በእርስዎ መመራት ሲጀምር በፍትህ መጓደል ላለፉት 27 ዓመታት ፍዳውን ሲያይ የነበረው ዜጋ እፎይ ይላል ብዬ በግሌ ተስፋ አድርጌ ነበር፤ ሕግ ተርጓሚው ከሕግ አስፈፃሚው ተፅዕኖ ወጥቶ የሚገባውን ክብር እና የሚወስነውም ውሳኔ በአስፈጻሚው አካል ሳይሸራረፍ ተፈፃሚ ይሆናል ብዬም ነበር። ፍትህ እና ርትዕ በእርስዎ አመራር ይሰፍናል ብዬ በእርስዎ የቀደመ ልምድ ፍፁም ተማምኜ የነበረ ቢሆንም እየሆነ ያለው የተገላቢጦሽ ነው። ፍትህ ከቀደመው ጊዜ በባሰ ችግር ውስጥ መውደቁን እኔ በግሌ በዚች ሁለት ወር በተግባር ባየሁት ነገር አረጋግጫለሁ። እርስዎ የተሰጠዎትን ኃላፊነት ያለምንም ፍርሃት እና ይሉኝታ ለመወጣት ከሞከሩ የፍትህ ሥርዓቱ ወደ መስመር ውስጥ መግባቱ አይቀርም፤ ግን ክብርት ፕሬዝደንት ለተቋማዊ ለውጥና ከታሪክ ተጠያቂነት ለመዳንም የበኩልዎን ይወጡ።

    ክብርት ፕሬዝደንት፥ ዜጋ በፍትህ ሥርዓቱ ተስፋ ሲቆርጥ ለሥርዓት አልበኝነት መንገድ ይከፈታል፤ የሞራል ልዕልና ቦታ አጥቶ ፍትህ በየአደባባዩ ትረገጣለች፤ ዜጋ በራሱ መንገድ ፍትህን ይፈልጋል፤ ፍትህን በራሱ ህሊና ተመርቶ ለመስጠት ይገደዳል። ያኔ እንደ ሀገር ዜጋው ወጥቶ የመግባት፣ ሠርቶ ሀብት ንብረት የማፍራት መብቱ አደጋ ውስጥ ይወድቃል። ስለዚህ እርስዎ የሚመሩት ተቋም ክብርና ሞገሱን ካጣ የሀገር ክብር እና ሞገስ ጠፍቶ እንደ ሀገር የመኖር ህልውናችንም አደጋ ውስጥ ይወድቃል። የመንግሥት መኖር ምልክት የሆነው ሕግና ሥርዓት ጠፍቶ ባለፈው እንዳየነው በየአካባቢው የደቦ ፍርድ ይነግሳል። አቶ ልደቱስ በፖለቲካው ባላቸው ተደማጭነት እና ተሰሚነት ድምፅ የሚሆናቸው ብዙ ነው። በዚህ ሁኔታ ተራው ዜጋ ምን ያህል በፍትህ ሥርዓቱ ፍዳውን ሊያይ እንደሚችል ተገንዝበውታል? ለእርስዎ ተቋም ክብር የሚመጥን የፍትህ ሥርዓት አለ ብለው ያምናሉ? አይመስለኝም ፍትህ እና ርትዕ እንዲሰፍን፣ እንዳይጓደል የበለጠ ሥራ በመሥራት የዳኞችን ክብር ያስመልሱ። ዳኞች የሚፈርዱት ፍርድ በአስፈፃሚው አካል ሲደፈጠጥ ማየት ያሳፍራል፣ ያሸማቅቃል ነገን እንድፈራ ያደርጋል። ነጋችንን እንዳንፈራ ሕግ ተርጓሚው ይፈራ! ስለዚህ ክብርት ፕሬዝደንት፥ ጉዳዩ የአቶ ልደቱን ጉዳይ የፍትህ መጓደል ብቻ አድርገው አይቁጠሩት። በህይወት የመኖር እና ያለመኖር የመብት ጥያቄ ነው እያቀረበ ያለው። በፍርድ ቤት ውሳኔ ሳይሆን በአስፈፃሚው ጡንቻ በህይወቱ ላይ አንድ ነገር ቢደርስስ ማን ነው ተጠያቂው? በተለይ የሃጫሉን ሞት ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል የታዘብኩት ዜጎች ወደ ፍትህ ሳይቀርቡ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ እየተጉላሉ መሆኑን ነው። በየማጎሪያው እየተሰቃዩ ነው፤ የፍትህ ያለ እያሉ ነው። አሁንም እደግመዋለሁ ወንጀል የፈፀመ አይታሰር አልልም፤ ግን ከሕገ-መንግሥቱ ድንጋጌ ውጭ ዜጎች መጉላላት የለባቸውም፤ የተፋጠነ ፍትህ ይሰጣቸው፤ ሰብዓዊ መብታቸው ይጠበቅላቸው። ይህን በሁለት ወር ውስጥ የታዘብኩት ነው። ይህ የሚያሳየው የፍትህ መጓደል በሌሎች ክልሎች ላይም ቀላል በማይባል ደረጃ ችግሩ መኖሩን ነው። በቢሾፍቱና አዳማ ዋስትና ተፈቅዶላቸው ከወር በላይ ፖሊስ አለቅም በማለቱ በእስር የሚማቅቁ ብዙ ዜጎች እንዳሉ ያገኘኋቸው የሕግ ባለሙያዎች አጫውተውኛል። ፍትህ ተጠምተው በየእስር ቤቱ የሚሰቃዩ ብዙዎች ናቸው። ለፍትህ መከበር ሁሉም ሊጮህ ይገባል። ፍትህ በጉልበተኞች ጫማ ሲደፈጠጥ ሥርዓት አልበኝነት ይነግሳልና!

    ክብርት ፕሬዝደንት መዓዛ፥ ይህችን ግልፅ አቤቱታዬን ሰምተው በፍትህ ሥርዓቱ ላይ ነፍስ ይዘሩበታል፤ በየማጎሪያ ካምፑ ያሉ የብዙ ዜጎችን እንባ ያብሳሉ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። አመሰግናለሁ።

    ከከበረ ሰላምታ ጋር!
    አዳነ ታደሰ
    የኢዴፓ ፕሬዝደንት

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የጠቅላይ ፍርድ ቤት ክብርት ፕሬዝደንት መዓዛ አሸናፊ

    Anonymous
    Inactive

    የሀገር ሰላምና መረጋጋት፣ የዜጎች ሰብዓዊ-መብትና ክብር ከሁሉም ይቀድማል፤ ብሔራዊ መግባባት እና ውይይት በአስቸኳይ!
    ከአብሮነት ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት (አብሮነት) የተሰጠ መግለጫ

    በቅድሚያ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ እንኳን ለ2013 ዓ.ም አዲስ ዓመት በሰላም አደረሳችሁ በማለት መልካም ምኞቱን ይገልፃል። አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የጤና፣ የፍቅር፣ የመተሳሰብ፣ የመከባበር፣ የመግባባት፣ የሀገራችንን ዘርፈ ብዙ ችግሮች በመወያየት፣ በመነጋገርና በእርቅ የምንፈታበት ዘመን እንዲሆንልን ይመኛል።

    አብሮነት ላለፉት 27 ዓመታት በሀገራችን ተንሰራፍቶ የነበረው የህወሓት/ኢህአዴግ አፋኝ አገዛዝ ሥርዓት “የለውጥ ኃይል” በሚባለው የብልጽግና የሪፎርም አካሄድ ከተተካ ባለፍነው ሁለት ዓመት ከግማሽ ያህል ጊዜ የሀገራችንን አጠቃላይ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ሁኔታዎች፥ በአጠቃላይ ወቅታዊ ጉዳዮችን በተለይ በአዲሱ ዓመት መባቻ ገምግሟል።

    በአጠቃላይ የሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ግምገማው አብሮነት የሀገራችን ሕዝብ በሪፎርሙ ጅማሬ የተገባውን ቃል እና የፈነጠቀውን የፖለቲካ ምህዳር መሻሻል ተከትሎ የቋጠረው ተስፋ፣ ያሳደረው እምነት በጊዜ ውስጥ እየሟሸሸ፣ በሀገሪቱ የሚታየው ሁኔታ ከቁጥጥር ውጪ እየሆነ “የሽግግሩ መንግሥት” የሀገሪቱ ፍኖተ-ካርታ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በበዓለ ሲመታቸው ያደረጉት ንግግር ነው ከተባለው ጋር በከፋ ተቃርኖ ውስጥ ገብቷል። የሕግ የበላይነትን አክብሮ ስለማስከበር፣ የዜጎች ሀሳብን በነፃ መግለጽና መቀበል መብት፣ “አሸባሪዎች እኛ ነን” በማለት ይቅርታ ጠይቀው የሽብር ሕጉን ያወገዙበትና በዚህ ሕግ የታሰሩ ፍርደኞች የተፈቱበት፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት የፖለቲካ ፓርቲዎችን ተሳትፎ ያበረታቱበት፣ የሰብዓዊ መብት መከበር ለጥያቄ የሚቀርብ አይሆንም የተባለበት… ሌሎች አዎንታዊ ቃል-ኪዳኖች በፈጣን ሁኔታ ተቀልብሰው [ቀድሞ] ወደ ነበርንበት፣ ሲያልፍም ከድጡ ወደ ማጡ ሊያስብል በሚችል ወደ ከፋ ደረጃ መድረሳችንን ተረድቷል።

    በሀገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ የሚታየው ሁለንተናዊ ምስቅልቅል፣ ያጋጠሙን ፈተናዎች ከውስጥም ከውጪም እየገዘፉ፣ እየሰፉና እየተወሳሰቡ መጥተው ከመንግሥት የቁጥጥር አቅም በላይ በመሆናቸው ችግሮቹን የብልጽግና መንግሥት በተናጠል ሊሸከማቸውም ሆነ ሊያስተካክላቸው ከሚቻለው በላይ ሆነዋል፤ መፍትሄውም አብሮነት ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ሲያቀነቅነው የነበረው “በሁሉን-አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ሕገ-መንግሥታዊና መዋቅራዊ ለውጥ የሚመጣበትን ሥርዓት የመዘርጋት ፖለቲካ መፍትሄ እንጂ በምርጫም ሆነ ሌላ ከብልጽግና ብቻ በሚቀርብ መፍትሄ አያገኝም። ከአማራጭ መፍትሄዎች አንዱ የሽግግርና እርቅ መንግሥት ነው” የሚለው አቋሙ ትክክልና ዛሬ የበለጠ ግልጽ መሆኑን አረጋግጧል።

    በመሆኑም አብሮነት ሰላማዊ ትግሉን አጠናክሮ የመቀጠል ዓላማና ተልዕኮውን አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትና ለዚህም ግንኙነቱን በማጽናት፣ ማጠናከርና በማስፋት ለመሥራት ቃልኪዳኑን አድሷል። ወደ ወቅታዊ ሁኔታዎች ስንገባ አብሮነት የፖለቲካ ፓርቲዎችን እንቅስቃሴና የፖለቲካ እስረኞችን፣ የሀገራችን ቀጣይ ምርጫና የትግራይ ምርጫ፣ በአዲስ አበባ የሚፈጸመውን ዘርፈ ብዙ ሕገ-ወጥ ተግባራት፣ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ እና በሀገራችን በጎርፍና በዜጎች ላይ በሚፈጸም ጥቃት እየደረሰ ያለውን አደጋ፣ የሚመለከቱ ጉዳዮችን ገምግመናል።

    የፖለቲካ ፓርቲዎችን እንቅስቃሴ በሚመለከት፥ ከጅምሩ ታይቶ የነበረው የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሕጋዊና ሰላማዊ መንገድ ተደራጅተው እንዲንቀሳቀሱ የማበረታታት አካሄድ ተቀልብሶ ፓርቲዎች በሕጋዊ መንገድ በነፃነት ተንቀሳቅሰው ብቃት ያላቸው ተፎካካሪ ሆነው ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የሚያደርጉት አስተዋጽኦ በሕግ ማስከበር ስም በገዢው ፓርቲ እንዲገደብ ተደርጓል።

    ለዚህም እንደቅድመ 2010 ከገዢው ፓርቲ በሀሳብ የሚለዩትን፣ የሚተቹና የሚቃወሙትን፣ በገዢ ፓርቲውና መንግሥት ባለሥልጣናት በተጨባጭ የሚፈጸሙ ሕገ-ወጥ ተግባራት እንዲቆሙ፣ እንዲስተካከሉና አጥፊዎች በሕግ እንዲጠየቁ የሚጠይቁትን፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችንና አባላት በፈጠራ ውንጀላ ማሰርና ማሰቃየት፣ ትናንት ከተወገዘው ባልተናነሰ፥ እንዲያውም በከፋ ሁኔታ እየተፈጸሙ ነው። በዚህም ከሰላማዊ ታጋይነታቸው ውጪ የማይታሙት የአብሮነት ከፍተኛ አመራሮች በፈጠራ ውንጀላ ለእሥራትና ሥቃይ ተዳርገዋል።

    በፖለቲካ ሀሳብ ጥራታቸውና ነገሮችን አስቀድመው አርቀው በማስተዋላቸው የሚታወቁት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ያለምንም ማስረጃ ተሰቃይተው በነፃ ተለቀዋል፤ ትናንት የብልጽግና ፓርቲ አባል እንዲሆኑ ተጠይቀው ያልተቀበሉት የሰላማዊ አማራጭ መፍትሄ ሀሳብ አፍላቂ እውቁ ፖለቲከኛ አቶ ልደቱ አያሌው በተጠረጠሩበት ወንጀል ፖሊስ ማስረጃ ሊያቀርብ ባለመቻሉ ነፃ መሆናቸው በፍርድ ቤት ቢረጋገጥም ለህይወታቸው አስጊ የልብ ህመምተኛ በመሆናቸው የቅርብ የሐኪም ክትትል እንደሚያስፈልጋቸው ማስረጃ አቅርበውም የፍትህ ሥርዓቱን ግምት ላይ በጣለ፣ ሰብዓዊነትን በረገጠ አሳፋሪ ሁኔታ ዛሬም በከፍተኛ ስቃይ ውስጥ ይገኛሉ። አዲስ አበባ ውስጥ በማስረጃ አስደግፎ እንዲያቆም ችግሩን አደባባይ ያወጣው፣ በቀዳሚነት የታገለው የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ሊቀ-መንበሩን ጨምሮ ከፍተኛ አመራሮችም የዚሁ ፈጠራ ወንጀል ሰለባ ከመሆን አልፈው በተወገዘው “የፀረ-ሽብር ሕግ” እንዲከሰሱ ተበይኖባቸዋል። በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ከፖለቲካ አመለካከታቸውና አቋማቸው ጋር በተያያዘ ጉዳይ ክስ ሳይመሠረትባቸው፣ በትምህርት ቤቶች ጭምር ታስረው ይገኛሉ የሚሉ መረጃዎች በስፋት ይቀርባሉ።

    አብሮነት ኮሮና ቫይረስ /ኮቪድ-19 ወረርሽኝ ከመከሰቱ አስቀድሞም “የሀገራችን ነባራዊና ወቅታዊ ሁኔታ በሀገራችን ነፃ፣ ዲሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ምርጫ ማካሄድ አያስችልም፤ ምርጫ ቢደረግ የሀገሪቱን ችግሮች ከሚያባብስ በቀር መፍትሄ አይሆንም፤ ያሳለፍናቸው ተደጋጋሚ ምርጫዎች ለውስብስብ ችግራችን መፍትሄ አላመጡም፤ በቀጣይም ምርጫ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ቢደረግ ለውጥ አያመጣም፤ ለሀገራችን ዘላቂና አስተማማኝ መፍትሄው ሕገ-መንግሥታዊና መዋቅራዊ ለውጥ ነው፤ ይህ ፖለቲካዊ መፍትሄ ማለት ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ነው” የሚል ግልጽ አቋም መውሰዱ ይታወቃል። ይህንን አቋም የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መከሰት አግዞት ሀገራዊ ምርጫው እንዲራዘም ተደርጓል። ይሁን እንጂ ብዙ ፓርቲዎች የእኛን የብሔራዊ መግባባት ውይይት መፍትሄ ሀሳብ ቢቀበሉትም ገዢው የብልጽግና ፓርቲ/መንግሥት ባለመቀበላቸው መንግሥት ዕድሜውን በሕገ- መንግሥት ትርጉም ስም ላልተወሰነ ጊዜ ሲያራዝም፣ ህወሓት ደግሞ ሕገ-መንግሥትን ማክበር በሚል የብሔራዊ ምርጫ ቦርድየፌደሬሽን ምክር ቤትም ሆነ አስፈጻሚው እንዳይደረግ ቢወስኑም፣ ቢያሳስቡም፤ እምቢኝ በማለት ምርጫ በክልሉ አካሂዷል። ለዚህ ችግር ምላሽ ይሆናል፣ የውጥረቱን ጊዜ ያሳጥራል በሚል ይመስላል መንግሥት ከሰሞኑ ምርጫው በዚህ ዓመት ይደረጋል ሲል እየሰማን ነው፤ አንዳንድ እንቅስቃሴዎችም እየታዘብን ነው።

    አብሮነት መንግሥት በሕገ- መንግሥት ሥም ዕድሜውን ያለገደብ ማራዘሙም ሆነ ህወሓት /የትግራይ ክልል መንግሥት ያቀረብነውን የብሔራዊ መግባባት ውይይት ቢቀበልም፥ ተግባራዊ ለማድረግ ከመታገል ይልቅ የተናጠል ምርጫ ማድረጉ ትክክል አይደለም፤ የሁለቱም – ብልጽግና እና ህወሓት – የእልህ አካሄድ የሀገሪቱን ፖለቲካ ወደ ከፋ ውጥረት ከማሸጋገር ያለፈ ሰላማዊና ዘላቂ አስተማማኝ መፍትሄ ሊያመጡ አይችሉም ብሎ ያምናል።

    የሀገራችንና የአፍሪካ ዋና ከተማ በሆነችው አዲስ አበባ የሚፈጸሙት ዘርፈ-ብዙ ሕገ-ወጥ ተግባራት ካለፈው ጥፋት በቀጠለ ስህተት እና በዕውቀትና የፖለቲካ ዓላማ መሠረት አድርጎ በተነደፈ ስልት በስፋት እየተካሄደ ነው። በተለይ የመሬት ወረራና የኮንድሚኒየም ቤቶች ዝርፊያ ጎልተው ከወጡና አደባባይ ከዋሉ በርካታ ወራት ተቆጥረዋል። ዛሬ አቤቱታ አቅራቢዎች ቢበራከቱም የመጀመሪያው በማስረጃ የተደገፈ አቤቱታ አቅራቢዎች – የባልደራስ አመራሮች – ዛሬ ወህኒ ተጥለዋል። ችግሩ መፍትሄ አላገኘም፤ ጥያቄዎች አልተመለሱም፤ በቀረቡት ማስረጃዎች መሠረት የከንቲባ ሹም ሽር ከመደረግ ያለፈ አጥፊዎች ለሕግ አልቀረቡም፤ በቀጣይም ይህን ለማስተካከል ቁርጠኝነት ስለመኖሩ አመላካች እርምጃዎች አልታዩም፤ ይልቁንም በነበረው መሠረት ለማስቀጠልና “‹በከተማዋ የባለቤትነት ጥያቄ” ላይ የሚደረገው ሽኩቻ ሲባባስ እንጂ ለማስቆም የሚደረግ ጥረት አልተስተዋለም። በመሆኑም ችግሩ ወደ ከፋ ደረጃ እንዳያድግና በፍጥነት እንዳይስፋፋ፥ ብሎም ጥፋትና ስርቆቱን እንዳያባብስ አብሮነት ሥጋት ገብቶታል። አፋጣኝ ሕጋዊ የእርምት እርምጃ በመውሰድ የሕግ የበላይነት ማስከበር፣ ከተማይቱንም በግልጽ የአስተዳደራዊ ባለቤት ለሆኑት ነዋሪዎቿ ማስረከብ እንደሚያስፈልግ በጽናት ያምናል።

    የኮቪድ-19/ኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በሚመለከት በተለይ ከወረርሽኙ መከሰትጋርተያይዞ ተጥሎ የነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መነሳትን ተከትሎ በሕብረተሰቡ ላይ እየታየ ያለው መዘናጋት አብሮነትን አሳስቦታል። መንግሥት በአዋጁ መነሳት ሕብረተሰቡ እንዳይዘናጋ በቂ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን መሥራት ባለመቻሉ ሕብረተሰቡ ወረርሽኙ የለም የተባለ ይመስል ከፍተኛ መዘናጋት ውስጥ ገብቷል። ሕብረተሰቡ የበሽታው መከላከያ የሆኑትን እርምጃዎች ሁሉ በመተው እራሱን ለበሽታው በሚያጋልጡ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በማስገባቱ በሽታው የበለጠ እንዳይስፋፋ አብሮነትን አስግቶታል። በመሆኑም መንግሥትም ሆነ ሕብረተሰቡ የወረርሽኙን አደገኛነት በመገንዘብ ለበሽታው የሚመጥን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ በአንክሮ ያሳስባል።

    በሀገራችን በጎርፍ እየደረሰ ያለውን አደጋ፣ በተለያዩ የሀገራችን ክልሎች/አካባቢዎች ከመጠን በላይ በጣለው ዝናብ የአዋሽ ወንዝ፣ የኦሞ ወንዝ፣ የባሮ ወንዝ፣ የአባይ ገባር ወንዞች ከመሙላታቸው በተጨማሪ ከግድቦች በተለቀቀ ውሃ ከ580,000 በላይ ዜጎች ለጉዳት ተዳርገዋል፤ ከዚህ ውስጥ ግማሽ ያህሉ ተፈናቅለዋል። በሌላ በኩል በተለያዩ አካባቢዎች (ኦሮሚያ ክልል፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፣ ደቡብ ክልል/ኮንሶ…) በዜጎች ላይ ጥቃት እየተፈጸመ ነው፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በአሰቃቂ መንገድ እየተገደሉና በሺዎች ህይወታቸውን ለማትረፍ ከቀዬአቸው እየተፈናቀሉ ነው። በመንግሥት በኩል ለመከላከል በቂ ዝግጅት፣ አደጋው ከደረሰም በኋላ በቂ ክትትልና ድጋፍ ያለመደረጉን፣ እንዲሁም በቀጣይ ሊደርሱ ለሚችሉ አደጋዎች በቂ የመከላከል ዝግጅት እየተደረገ ያለመሆኑን፣ ከአካባቢው የሚደርሱን መረጃዎች ያመለክታሉ። በሌላ በኩል የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በዚህ ልክ በሀገራችን በደረሰው አደጋና ጉዳት ምንም ሳይሉ በጎረቤት ሀገር ሱዳን በደረሰው ሀዘናቸውን ገልጸዋል፣ እንዳይቀጥልም ከጎናቸው እንደሚቆሙ ቃል ገብተዋል። ዜጎች በማያውቁት በተፈጸመባቸው ጥቃት ለሞት ተዳርገዋል፤ እየተዳረጉም ነው። በተረፉት ዜጎቻችን የደረሰው አደጋን ተከትሎ የሚመጣው የጤናና ምግብ ችግር፣ እንዲሁም ሊደርስ የሚችለው አደጋ በአንድ በኩል፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ዝምታና “የራሷ እያረረባት፣ የሰው ታማስላለች” አካሄድ በሌላው፣ በእጅጉ ያሳስበናል። ስለዚህ መንግሥት በራሱ እና ሕዝቡንና ዓለምአቀፍ ማኅበረሰቡን በማስተባበር በአፋጣኝ እንዲደርስላቸው ያስፈልጋል።

    በመጨረሻ ገዢው ፓርቲ /መንግሥት በአፈናና የሸፍጥ ፖለቲካ በተመሳሳይ መንገድ እየተጓዘ በፕሮፖጋንዳና ባዶ የተስፋ ቃላት ጋጋታ ፣ የተለየ ውጤትም ሆነ ችግሮቻችን መፍታት እንደማይችል በተደጋጋሚ ተመልክተናል። ስለዚህ አብሮነት ችግሮቻችንን በአስተማማኝና ዘላቂ መንገድ ለመፍታት፣ ሃቀኛ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ለነገ የማይባል ተግባር እንደሆነ ያምናል፤ ገዢው ፓርቲ ለዚህ ያለውን ከፍተኛ ኃላፊነት እንዲወጣ በአጽንኦት ጥሪ ያደርጋል።

    ለዚህ እንዲረዳም፡-

    1ኛ/ በፖለቲካ አመለካከታቸው ከገዢው ፓርቲ በመለየታቸውና በሀገሪቱ ለሚታዩት ችግሮችና በሕዝብና ሀገር ሀብት ላይ እየደረሰ ያለውን በደል በማስረጃ አስደግፈው ተቃውሞ በማሰማታቸውና ጥያቄ በማቅረባቸው ብቻ የታሰሩ የፖለቲካና የኅሊና እስረኞች በአስቸኳይ እንዲፈቱ፤

    2ኛ/ ለ27 ዓመታት አንድ ሆነው ሕዝባችን ሲያሰቃዩ የነበሩትና ዛሬ በሥልጣን ጥያቄና ያለፈውን በማስቀጠል ስልት ላይ ባለመስማማታቸው በተለያዩት በህወሓት እና በብልጽግና ፓርቲዎች መካካል ትናንትም ሆነ ዛሬ በሚደፈጥጡት ሕገ-መንግሥትና አምስት ጊዜ ባጭበረበሩት ምርጫ ሥም የሚታየው መካረርና ፍጥጫ በአስቸኳይ ተገትቶ፥ ለብሔራዊ መግባባት ውይይት ችግሮቻቸው እንዲፈታ የፖለቲካ ቁርጠኝነታቸውን እንዲያረጋግጡ፤

    3ኛ/ የሀገራችን ችግሮች ምንጭ ምርጫ ባለመሆኑ፥ በምርጫም የሚፈቱ ያለመሆናቸው ባለፉት አምስት ምርጫዎች በመረጋገጡ፥ ለሕገ-መንግሥታዊና መዋቅራዊ የፖለቲካ መፍትሄ ምርጫ ለማድረግ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችም ሆነ እንዲደረግ የሚደረጉ ግፊቶች በአስቸኳይ ቆመው ሁሉንም ወገኖች የሚያሳትፍ የውይይት መድረክ እንዲመቻች ለዚህም ሁሉም ዜጋ አስፈላጊውን ተፅዕኖ በመንግሥት ላይ እንዲያሳርፍ፤

    4ኛ/ መንግሥትም ሆነ ሕብረተሰቡ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን በመከላከል ረገድ እያሳዩ ያሉትን ቸልተኝነት በማቆም አስፈላጊውን የመከላከል ጥንቃቄና የመለየት ምርመራ እንዲያደርጉ፣ ለተጠቂዎች አገልግሎት ማቅረቡንና የግንዛቤ ማሳደግ ተግባራት በስፋት እንዲያከናውኑ፤

    5ኛ/ በሀገራችን በተፈጥሮና ሰው-ሠራሽ ምክንያት ጎርፍ እያደረሰ ላለው ከፍተኛ አደጋ መንግሥት “የራሷ እያረረባት የሰው ታማስላለች” ከሚያስብል አካሄድ ወጥቶ በዜጎች ህይወት፣ ሥቃይ፣ የንብረት ውድመትና ቀጣይ ህይወት ላይ ትኩረት እንዲያደርግ፤

    6ኛ/ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች እንደየቱም ክልል ነዋሪ የከተማቸው አስተዳዳራዊ ባለቤት መሆናቸው እንዲረጋገጥ፣ በከተማዋ የባለቤትነት መብት የሚደረገው በብልጽግና ውስጥ ጭምር የሚደረገው ሽኩቻ እንዲቆም፣ የተበዘበዘውና የተዘረፈው የከተማዋ ሀብት በሕግ ተመልሶ ለከተማዋ ልማት እንዲውል፣ አጥፊዎች ለሕግ እንዲቀርቡ፣ እንዲደረግ፤

    7ኛ/ በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች በዜጎች ላይ የደረሰው ጥቃት በገለልተኛ ወገን በአስቸኳይ እንዲጣራና ተገቢው ካሳ እንዲደረግላቸው፥ እንዲሁም አጥቂዎችና ተባባሪዎቻቸው በሕግ እንዲጠየቁ እንዲደረግ፣ ለጥቃቱ ሰለባዎች አስፈላጊው የዕለት ደራሽ ዕርዳታና የማቋቋሚያ ድጋፍ በአስቸኳይ እንዲደርሳቸው፤ ለዚህ ተፈጻሚነትም የፖለቲካ ፓርቲዎች ጅምሩ የብሔራዊ መግባባት ውይይት እንዳይነጠቅና በገዢው ፓርቲ እጅ እንዳይወድቅ፣ ከላይ ያቀረብናቸው እንዲፈጸሙ በልዩነታችን ውስጥ በሀገራዊ ጉዳዮች በቅድሚያ በሕግ የበላይነትን በማክበርና ማስከበር ለሰላምና መረጋጋት፣ ለሰብዓዊ መብት መከበር ተባብረን እንድንቆም ጥሪያችንን እናቀርባለን፤ ለተግባራዊነቱ ያለንን ቁርጠኝነት እናረጋግጣለን።

    ከአሳታፊ ሁሉን አቀፍ ሃቀኛ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ውጪ የቱም አንድ ፓርቲና ከብሔራዊ መግባባት ውይይት በፊት የሚደረግ የይስሙላ ምርጫ ለሀገራችን ችግሮች ዘላቂና አስተማማኝ መፍትሄ አያመጣም።

    ከሁሉም በፊት መንግሥት የሕግ የበላይነት በማክበርና በማስከበር በሃቀኛ ሕዝባዊ ተሳትፎ የሀገራችን ሰላምና መረጋጋት፣ የዜጎችን የመኖር ሰብዓዊ መብት የማረጋገጥ ኃላፊነቱን ይወጣ፤ ከሥልጣኑ ይልቅ ለሀገርና ሕዝብ ጉዳይ ቅድሚያ ይስጥ።

    አብሮነት ለኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት (አብሮነት)
    መስከረም 07 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ

    ብሔራዊ መግባባት እና ውይይት

    Anonymous
    Inactive

    ግልፅ ደብዳቤ ለኢንጂነር ታከለ ኡማ (ቢደርስም ባይደርስም)
    ወንድማገኘሁ አዲስ

    ሰላምታዬንና አክብሮቴን በማስቀደም የተከበሩ ሚኒስትር ኢንጂነር ታከለ ኡማ፥ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በጥናት ደረስኩበት ብሎ ይፋ ላደረገው ሰነድ በሰጡት መልስ የተገነዘብኩት እንደ አንድ ተራ ዜጋ ላቀርብልዎት እወዳለሁ።

    ሲጀመር የሰጡት ርዕስ ራሱ ችግር እንዳለበት ይሰማኛል። ማስረጃ አጠናቅሬያለሁ ያለ ድርጅት መግለጫ ከማውጣቱ ሰነዱን ለሚመለከታቸው አቅርቦ ይመሩት የነበረው ፅሕፈት ቤት መልስ ስላልሰጠ። ኢዜማ ከዚህ ቢሮ መልስ አግኝቶ ቢሆን ኖሮ አንደኛ መልሱን ሪፖርቱ ላይ ያካትት ነበር፤ አሳማኝ የሆኑ ጉዳዮች ከቀረቡም ፓርቲው ከሪፖርቱ ላይ የተወሰኑትን እንዲያርም ወይም እንዲያሻሽል ዕድሉ ክፍት ይሆን ነበር ብዬ አምናለሁ።

    በመቀጠልም ምላሽ ለመስጠት ተገቢው ቦታ ባልገኝም ሲሉ ተገቢው ቦታ ለመሆኑ የቱ ነው? ሰነዱ በቀጥታ ከሚመለከታቸው ግለሰቦች አካላት እርስዎና እርስዎ ይመሩት የነበረው ተቋም በመሆናቸው መልስ እንዳይሰጡ ቦታ ምክንያት ይሆናል ብዬ አላስብም ።

    በመቀጠልም የመሬት ወረራን በተመለከተ ስልጣን ላይ ከወጣንበት የመጀመሪያ ቀን ጀምሮ እስከ መጨረሻዋ ቀን ድረስ ጠንካራ እርምጃዎች ስንወስድበት የነበረ ጉዳይ ነው ብለዋል።  ለእርስዎ አድልተን ያሉትን ብንቀበል እንኳን “የመሬት ወረራውን አስቆሙት ወይ? የኮንዶሚኒየሙን አድሎአዊ እደላ አስወገዱት ወይ ነው?” ጥያቄው በራስዎ አንደበት የሀይማኖት ተቋማት ሳይቀሩ በኢ-መደበኛ አደረጃጀቶች ሲወረሩና በመንግሥት አካላት ሲፈርሱ በተነሳብዎት ተቃውሞ ምክንያት እርስዎ ራስዎ ይቅርታ አልጠየቁም ወይ? ከፍተኛ የሆነ የመሬት ወረራ እንዳለ በይፋ አልተናገሩም ወይ? ባለፉበት ባገደሙበት ሁሉ የከተማዋን መሬት ለግለሰቦችና ለተቋማት ሲያድሉ አልነበር ወይ?

    ሌላው ክቡር ኢንጂነር ታከለ ኡማ፥ የተፈናቀሉትን አርሶ አደሮች በመታከክ እንደ ህወሀቶቹ የቀን ጅቦች ብሄርዎን ዋሻ ለማድረግ የሄዱበት መንገድ በጣም ከእርስዎ በጭራሽ ያልጠኩት ነበር። ለመሆኑ የትኛው የኢዜማ የመግለጫው ክፍል ላይ ነው “የተፈናቀሉት ገበሬዎች የመኖሪያ ቤት ተጠቃሚ አይሆኑ” የሚለው። ማነው በቃለ መጠይቁስ ላይ “ለተፈናቀሉት ቤት አይሰጥ” ያለው? በእርስዎ የስልጣን ዘመን በገፍ ቤት የታደላቸው በሺዎች የሚቆጠሩት የኦሮሚያ ባለስልጣናት የተፈናቀሉ አርሶ አደሮች ነበሩ ወይ? እስከ ልጅ ልጅ የሚሰጠው መሬት ፍትሀዊ ነበር ወይ? ለስፖርት ክለቦች የታደለውስ? ይህ ሁሉ እየሆነ ያለው እኮ “በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ድሆች ከዛሬ ነገ አንገታችንን ማስገቢያ፣ ልጆቻችንን ማሳረፊያ ቤት ልናገኝ ነው” በማለት ቤትን የህልውናቸውና የተስፋቸው ጥግ አርገው እየጠበቁ ሳለ ነው።

    “እኛ ሕጋዊ እርምጃ ስንወስድ የዛሬ ተችዎቻችን የሰብዓዊ መብት ተነካ፤ ዜጎች ተፈናቀሉ ብለው ዘመቻ የከፈቱብን አካላት ናቸው” ብለዋል። በመጀመሪያ ደረጃ እርምጃ ሲወሰድ የሰብዓዊ መብት መከበር አለበት የሚለው ዓለም-አቀፋዊ መርህ እንደተጠበቀ ሆኖ ‘ዘመቻ’ ላሉት ቃል ግን ይቅርታ ያድርጉልኝና ማፈር ይኖርብዎታል። ለእርስዎም ሆነ ለመንግሥትዎ የኢዜማን ያክል ዕድል የሰጠ አንድም ድርጅት የለም። መወቀስ ካለበትም በሰጣችሁ ሰፊ ዕድልና በታገሳችሁ ልክ መሆን አለበት፤ ምንም እንኳን ሁለቱም ምክንያታዊ ናቸው ብዬ ባምንም።

    ሌላው እጅግ አስገራሚ የሆነው ደሞ “አንድም ቀን ለተናቀሉት የመቆርቆር ስሜት አሳይቶ የማያውቅ ድርጅት” ሲሉ የጠቀሱት ለመሆኑ ኢዜማ የጠቀሷቸው ዜጎች ሲፈናቀሉ ህልው ፓርቲ ነበር ወይ? ያፈናቀላቸው እኮ የራስዎ ድርጅት የዛሬው የኦሮሚያ ብልጽግና የትናንቱ ኦህዴድ ነበር! ተረሳ ክቡር ሚኒስትር? አርበኞች ግንቦት 7 (አግ7) እንዲሁም ከስመው ኢዜማን የመሠረቱት እኔ የማቃቸው ፓርቲዎች እና ግለሰቦች ሁሉ እናንተ ስታፈናቅሉ እነሱ ከተፈናቃዮች ጎን ሆነው ድምፃቸውን ሲያሰሙ የነበሩ መሆናቸውን አስረግጬ መናገር እችላለሁ። እንደ አንድ ለወገኑ እንደሚቆረቆር ኢትዮጲያዊ እኔም ከእነሱ ባለሁበት ያቅሜን ስጮህ ነበር። ለምን ይዋሻል ኢንጂነር?!

    “የአርሶ አደሮችን ጉዳይ ለተቀባይነት ማግኛ” በማለት የፃፉት እና “መጀመሪያ ላይ በሀሰተኛ መረጃ ሀገር ማፍረስ እንጂ አይገነባም” ላሉት ደሞ ትንሽ ማለት አለብኝ። ለመሆኑ ኢዜማ እርስዎ ባሉት መልኩ ተቀባይነት ማግኘት እንደሚቻል ጠፍቶት ነው በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ደጋፊዎቹን ያጣው? ሌላው ቢቀር በእናት ድርጅትዎ መዋቅር በአብዛኛው ኦሮሚያና እርስዎ ሲያስተዳድሯት በነበረችው በአዲስ አበባ ከተማ በፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች ላይ ሲደርሱ የነበሩት የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በማስጮህ ብቻ ተከታይን ማፍራት አይቻልም ብለው ያስባሉ? ይልቅስ ከላይ እንደጠቀስኩት የተፈናቃዮችን ልብ በፀረ-ኢዜማ ትርክት ለማነፅና ጭፍን ተከታይ ለማፍራት የኳተኑት እርስዎ ራስዎ ነዎት። በነገራችን ላይ፥ ለሀገር ሰላምና መረጋጋት ዕድል መስጠት ከመንግሥታዊ ኢ-ሕገመንግሥታዊ ተግባራት ጋር ማበር አይደለም።

    ክቡር ኢንጂነር፥ አሁን ላይ በደንብ የገባኝ ከስልጣን ሲወርዱ፣ በሀሳብ መሟገት ሲያቅታቸውና ፖለቲካ ፊት ስትነሳቸው “ብሔርን መደበቂያ ዋሻ” ማድረግ በስፋት እየተዛመተ ያለ አስፈሪ ፖለቲካዊ ባህል መሆኑን ነው። እርስዎም ይሄን መንገድ በመከተል የእነ ሀይለመስቀል ሸኚን ፣ የእነ አቦይ ስብሀትን የእነ ልደቱ አያሌውን ዱካ እንደተከተሉ ተረድቻለሁ።

    የአሿሿምዎ ሂደት አጠያያቂነት እንደተጠበቀ ሆኖ ክቡር ሚኒስትር፥ እርስዎ የታላቋ አዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ነበሩ። ሲያስተዳድሯት የነበረችው አዲስ አበባ ማለት የ AU፣ የ ECA እና የመሳሰሉት ታላላቅ ዓለም-አቀፋዊ ድርጅቶች መቀመጫና በዓለም ላይ 3ኛዋ ወይም 4ኛዋ የዲሎማሲና የፖለቲካ ከተማ እንደሆነች ዓለም የሚያውቀው ሀቅ ነው። አሁንም ቢሆን ሚኒስትር እንጂ እንደኔ አክቲቪስት አይደሉም። ቢሆን ደስ የሚለኝ ‘ቀረበ’ የተባለውን ሰነድ በሚገባ ፈትሸው ተመጣጣኝ በሆነ አግባብ መልስ ቢሰጡ ነበር። ሰነዱን በሙሉም ሆነ በከፊል ወይም በተወሰነ ደረጃ ተቀብለው፥ ያም ካልሆነ ተቃውመው የነበሩበትንና ያሉበትን ወንበር የሚመጥን አጸፋ ይሰጣሉ ብዬ ጠብቄ ነበር። በእኔ በኩል ያደረጓቸውን በጎ ተግባራት በዜሮ የማጣፋ ሰው አይደለሁም። የዛሬው መልስዎ ስሜቴን በእጅጉ ቢበርዘውም ለበጎ ለበጎዎቹ ሥራዎችዎ ዛሬም ክብር እሰጣለሁ። ይሁን እንጂ በቀረበብዎ ክስ እና በሰጡት መልስ ምክንያት የተደበቀውን “ኢንጂነር ታከለ ኡማን” ማየቴን ደሞ አልሸሽግዎትም። አሁን ለደረስኩበት ግንዛቤ ትልቁ ግብአቴ ደግሞ እርስዎ ራስዎ የነገሩንን ጭምር በመካድዎ ነው። ይሄ ሁሉ ሆኖም የነበሩበትንና ያሉበትን ደረጃ የሚመጥን መልስ ካለ ለመስማት አሁንም ፍቃደኛ ነኝ።

    ክቡር ሚኒስትር፥ ስንብቴን አስቀድሜ እያቀረብኩ ደብዳቤዬን ከማጠናቀቄ በፊት እርስዎ ወይም ይመሩት የነበረው አስተዳደር ስለተሞገታችሁ ብቻ ሀገር እንደማትፈርስ በርግጠኝነት ልነግርዎ እወዳለሁ። ይልቅስ ሀገር የሚያፈርሰው የዜጎችን ድምፅ ለማፈን ይመሩት የነበረው ተቋም እየወሰደ ያለው ኢ-ሕገመንግሳታዊና ኢ-ዴሞክራሲያዊ እርምጃ ነው። የኢዜማ መግለጫዎች መታገድ የከንቲባ አዳነች አቤቤ ሳይሆን የእስዎ የሁለት ዓመታት የከንቲባነት ዘመን ውጤት ነው። የክብርት ከንቲባዋን ውጤት ደሞ ሰነባብተን እናየዋለን።

    አክባሪዎ ወንድማገኘሁ አዲስ

    ተያያዥ ጉዳዮች፦

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ግልፅ ደብዳቤ ለኢንጂነር ታከለ ኡማ

    Semonegna
    Keymaster

    አቶ ልደቱ አያሌው ለፍርድ ቤት ያቀረበው የሕግ መከራከሪያ ነጥብና የፍትህ ሥርዓቱን ውድቀት ያሳየበት ልብ የሚነካ ንግግር*

    ክቡር ፍርድ ቤት፥

    ለመጀመሪያ ቀን በዚህ ችሎት ላይ ስገኝ ከችሎቱ ጀርባ የተፃፈውንና “ተልዕኳችን የሕግ የበላይነትን በማስከበር አርዓያ መሆን ነው” የሚለውን ሳነብ እና ከአሁን ቀደም በተመሳሳይ ሁኔታ ተከስሼ ነፃ ያወጡኝ ፍርድ ቤቶች በመሆናቸው እውነተኛ ፍትህ ከዚህ ችሎት አገኛለሁ ብዬ ተስፋ አድርጌ ነበር። ዛሬ ግን በዚህ ችሎት ፊት የተገኘሁት ሕጋዊ ግዴታዬን ለመወጣትና ለችሎቱ ያለኝን አክብሮት ለመግለፅ እንጂ፥ ፍትህ አገኛለሁ ብዬ ተስፋ በማድረግ አይደለም። ክቡር ፍርድ ቤት፥ ይህንን ማለት የተገደድኩት በሚከተሉት ምክንያቶች ነው።

    1ኛ. ለፖሊስ ተጨማሪ የጊዜ ቀጠሮ የሚሰጠው በምርመራ ሂደቱ ላይ ያሉት ለውጦች በዳኞች እየተመዘኑ ቢሆንም፥ እስካሁን በቀረብኩባቸው አራት ችሎቶች ጉዳዩን ያዩት አራት የተለያዩ ዳኞች በመሆናቸው ምንም ዓይነት የምርመራ ውጤት ለውጥ በሌለበት ሁኔታ ተከታታይ የጊዜ ቀጠሮ እየተሰጠብኝ ያለው ከሕጉ መንፈስ ውጭ በመሆኑ፤

    2ኛ. ለከፍተኛ ሕክምና ወደ ውጭ አገር ለመሄድ ቀጠሮ እንዳለኝ፣ በአሁኑ ወቅትም ከፍተኛ የልብ ህመም ታማሚ እንደሆንኩ፣ ከህመሜ ጋር በተያያዘም በኮቪድ-19 ቫይረስ ብጠቃ ህይወቴ አደጋ ውስጥ ሊወድቅ እንደሚችል የሕክምና መረጃ አቅርቤ እያለና በፖሊስ የቀረበብኝ ክስ የዋስትና መብት የማያስከለክል ሆኖ እያለ ያለ አግባብ የዋስ መብት ተከልክያለሁ። ክቡር ፍርድ ቤት፥ ከምገኝበት አሳሳቢ የጤና ችግር በእስር ላይ ከምገኝበት ለኮሮና እጅግ ተጋላጭ የሆነ እስር ቤት አንፃር የተከለከልኩት የዋስትና መብት ሳይሆን የሰው ልጅ መሠረታዊ መብት የሆነውን በህይወት የመኖር መብቴን ነው። ይህም የሚያሳየው ገና ወንጀለኛ ተብዬ ሳይፈረድብኝ የሞት ፍርድ የተፈረደብኝ መሆኔን ነው፤

    3ኛ. በዚህ በተከበረው ፍርድ ቤት ፊት አሁን እየተከራከርን ያለነው አንድ መንግሥት እና አንድ ዜጋ አይደለንም። በሕጉ መሠረት ከሳሽና ተከሳሽ ነን። ክቡር ፍርድ ቤቱ ለከሳሽና ለተከሳሽ መብት መከበር እኩል መቆም ሲገባው ሁል ጊዜ የከሳሽን ምክንያታዊ ያልሆነ ጥያቄ እየተቀበለ፥ በተቃራኒው ደግሞ የእኔን በመረጃ የተደገፈ ጥያቄ ውድቅ እያደረገ አድሏዊነት እየፈፀመብኝ በመሆኑ፤

    4ኛ. በአጠቃላይ በሀገር ደረጃ ያለውን ሁኔታ ስናይም፥ ፍትህ እየተሰጠ ያለው ከችሎት አደባባይ ሳይሆን ከአራት ኪሎ ቤተ-መንግሥት መሆኑን እያየን ነው። በወቅቱ የፖለቲካ ቀውስ ምክንያት በእስር ላይ የምንገኘው ዜጎች በብዙ ሺዎች የምንቆጠር ሆኖ እያለ፥ ልክ ሁላችንም አንድ ዓይነት ወንጀል እንደሠራንና ጉዳያችን በአንድ ዳኛና ችሎት ብቻ እየታየ እንደሆነ ሁላችንም የዋስ መብት ተነፍገን በተደራራቢ የጊዜ ቀጠሮ መብታችን በጅምላ እየተጣሰ ነው።

    ክቡር ፍርድ ቤት፥ እኛ ፍትህ የምንጠብቀው ከፍርድ ቤት እንጂ ከሳሻችን ከሆነው የአራት ኪሎ መንግሥት አይደለም። የአራት ኪሎ መንግሥት ኃላፊነት ሕግ ማስፈፀም ነው እንጂ ሕግ መተርጎም አይደለም። ክቡር ፍርድ ቤት፥ በአጠቃላይ እነዚህ ከላይ የጠቀስኳቸው አራት ነጥቦች የሚያሳዩት የሕግ ሳይሆን የፖለቲካ እስረኞች መሆናችንን ነው። አሁን በመጨረሻ ፖሊስ “የሽግግር መንግሥት ጥያቄ በማቅረብ መንግሥትን የመገልበጥ ሙከራ አድርጓል” በሚል ክስ ሲያቀርብብኝ መታየቱ ይህንን የሚያረጋግጥ ነው።

    በዚህ ሁኔታ እውነተኛ ፍትህ ይገኛል ብዬ ስለማልጠብቅ በጊዜ ቀጠሮ እየተመላለስኩ እኔና ጠበቃዬ አጉል ከምንጉላላ፥ ውድ የሆነው የፖሊስ እና የፍርድ ቤት ጊዜም ያለ አግባብ ከሚባክን- መቋጫ የሌለው የፖሊስ የጊዜ ቀጠሮ ጥያቄ እንዲቋረጥና ጉዳዩ የፖለቲካ ውሳኔ ሲሰጠውና ፖሊስ “ምርመራዬን ጨርሻለው” ባለ ጊዜ ከእስር ቤት ወደ ችሎት እንድቀርብ እንዲወሰን በታላቅ አክብሮት እጠይቃለሁ።

    ምንጭ፦ ሀብታሙ አያሌው

    * አቶ ልደቱ አያሌው የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ምክር ቤት ሲሆኑ፥ ሐምሌ 17 ቀን 2012 ዓ.ም. ፓርቲው በፕሬዝደንቱ አቶ አዳነ ታደሰ በኩል፥ አቶ ልደቱ አያሌው የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ በቁጥጥር ስር እንዳዋላቸውና ቢሾፍቱ (ደብረ ዘይት) ከተማ በሚገኝ ፖሊስ ጣቢያ ውስጥ እንደታሰሩ ገልጾ ነበር። ይህንንም አስመልክቶ ፓርቲው ሐምሌ 21 ቀን 2012 ዓ.ም. ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቶ ነበር።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    አቶ ልደቱ አያሌው

    Anonymous
    Inactive

    [በዚህ ጽሑፍ ላይ አማራ ብዬ የጠቀስኩት ማኅበረሰብ በአሰፋ ጨቦ ትንታኔ መሠረት ሲሆን፥ ዘርን ሳይሆን የአባቶቻችንን ድል እና ኃያልነት የተቀበለውን፣ የማሸነፍ መንፈሱ የማይደረመስ ተራራ የሆነውን፣ በየሄደበት ሁሉ የአባቶቹን ድል አድራጊነት እያሰበ የበታችነትን እንቢ ያለውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ የሚመለከት ነው።]

    አሸናፊን የራሱ የሚያደርግ ብልህ ሕዝብ

    (ሙሉዓለም ጌታቸው)

    የዛሬ አንድ ወይም ሁለት ዓመት ፌስቡክ ላይ በአንድ የኦሮሞ አክቲቪስት ተጽፎ ብዙ ሰው የተለዋወጠው ጽሑፍ ነበር። ጽሑፉ ኦሮሞ ጀግኖቹን አሳልፎ የሚሰጥ ባህል አለው ብሎ ይከራከራል። አማራ* ደግሞ የሌላን ጀግና ሳይቀር የራሱ የማድረግ፣ የማጠጋጋት ባህል አለው ይላል። ይሄ ጽሑፍ ባሰብኩት ጊዜ ሁሉ ይገርመኛል። በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ በየትኛውም ዘርፍ አንቱታን ያተረፉ ጀግኖች አብዛኛው ከኦሮሞ ናቸው፤ ነገር ግን የሚያከብራቸው እና የሚወዳቸው አማራው ወይም ሌላው ብሔር ነው። በተቃራኒው በሕይወት በነበሩበት ዘመን ሳይቀር ከሃዲ፣ የአማራ ተላላኪ እያለ ሲሰድባቸው የነበሩትን ልክ ሲሸነፉ ወይም ሲመቱ የራሱ አድርጎ የመቀበል እና ሞታቸውን የእሱ የማድረግ ባህል ቢያንስ በእኔ ዕድሜ በማውቀው የኦሮሞ ማኅበረሰብ ውስጥ የሰረጸ ባህል ይመስላል።

    ኃይሌ ፊዳ ጎበና እየተባለ መከራውን እንዳየ እንደተሰደበ ደረግ ጭዳ አደረገው። አሁን ደግሞ ለብዙ የኦሮሞ የዘመኑ ጎበዞች ጃዋርን ጨምሮ ኃይሌ ፊዳ የኦሮሞ ጀግና እየተደረገ ሲቀርብ እና ለትግል ማነሳሻ ሲውል መመልከት የተለመደ ሆኗል። “The Ethiopian Revolution and Its Implication” በሚል ርዕስ በአሜሪካው የስለላ ተቋም ሲ.አይ.ኤ. (CIA) እ.ኤ.አ. በማርች 1977 (March 1977) ተዘጋጅቶ በጥብቅ ምስጢርነት ለአሜሪካው የሥራ አስፈጻሚው አካል የቀረበው ሰነድ መንግስቱ ኃይለማርያም ኦሮሞ እንደሆነ ከገለጸ በኋላ፥ በንጉሡ ወዳጆች ከስልጣን የሚፈነቀል ከሆነ “በኦሮሞነቴ” ወይም “ኦሮሞ” ስለሆንኩ ከስልጣን አባረሩኝ ብሎ ዘሩን ሊጠቀምበት እንደሚችል ትንቴውን ያቀርባል። “እንደዚህ ዓይነት አደጋ ካልገጠመው ግን ኦሮሞነቱን የማሳየት (ለስልጣን ሲል ማለቱ ነው) ዝንባሌ አይታይበትም” ይላል የስለላው ሰነድ። ተመልከቱ የሚሸነፍ ከሆነ በኦሮሞ የዘር ጉርጓድ ውስጥ ሊደበቅ ይችላል እያለን ነው (ሽንፈቱን እንጂ ድሉን ለኦሮሞ ለመስጠት ፈቃደኛ አልነበረም ማለቱ ነው)። ይሄ በዘመኑ ሳይቀር በራሳቸው የዓለም ትግል ሲሸነፉ ኦሮሞነታቸውን (ዘራቸውን) ለውድቀታቸው ሰበብ የማቅረብ ዝንባሌ እንዳለ ከማሳየቱ ባሻግር፥ ሲሸነፉ የራሱ የሚያደርጋቸው ማኅበረሰብ እንዳለ ይነግረናል።

    ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከአባታቸው መኮንን ጉዲሳ የተወለዱ ኦሮሞ ናቸው። በዓለም የተደነቁ፣ ዘመናዊ ኢትዮጵያን በዘመናዊ ተቋም የመሠረቱ፣ እጅግ አስደናቂ መሪ ናቸው። ኢትዮጵያ በእሳቸው ጊዜ የነበራትን ዝና ለመመለስ ቢያንስ 100 ዓመት በትንሹ ሊያስፍልጋት ይችላል፤ እሱም ጠንክረን ከሠራን። በርግጥ ፍጹም ሥልጣን የሚወዱ በመሆናቸው ፍጻሜያቸውን ክፉ አደረጉት። ንጉሡን የሚወዳቸው እና የራሱ ያደረጋቸው ግን ማነው? አማራው! በእሳቸው ዘመን ክፉኛ የተጨፈጨፉ ሁለት አመጾች አሉ። አንዱ የቀዳማይ ወያኔ ትግል በትግራይ ሲሆን ሌላኛው የጎጃም አመጽ ነው። የጎጃምን አመጽ ድባቅ የመቱበት ዘግናኝ ክስተት የታሪክ ጸሐፊዎች እንኳ ቃላት ያጡለት ነው። ግን ዛሬ ለሃውልታቸው መሠራት፣ ለስማቸው ክብር የሚቆመው ይሄው አማራው ነው። ምክንያቱም ጀግናን የራሱ የማድረግ ሥነ-ልቦና አለው። ሰቅለው ለገደሉት ለበላይ ዘለቀ እየዘፈነ ፥ ለእሳቸው ክብርና ዝና ዜማ ሲያወርድ ምንም አይጣላበትም። ድንቅ ሥነ-ልቦና። ኦሮሞው ደግሞ የመኮንን ጉዲሳን ሃውልት ሐረር ላይ አፍርሶ፣ ሰው ሀገር ላይ ሎንደን (London) ደግሞ የሳቸውን ያፈርሳል። ምክንያቱም ተሸናፊን እንጂ አሸናፊን የመቀበል ሥነ-ልቦና አላወረሱትም። የተቆረጠ የጡት ሃውልት ለልጆቹ ዘወትር እያሳየ፥ በባዶ እግሩ የሚሄድ ከእሱ በምንም የማይሻለው አማራ አደረገው ይላቸዋል። ልጅ በውስጡ ፍርሃት ይሰርጽበታል። የተሸናፊው ዘር አባል መሆኑ በራሱ የሚፈጥርበት የሥነ-ልቦና ቀውስ ቀላል አይደለም። ከዛ ሕይወቱን በጥላቻ መነጽር መመልከት ይጀምራል። ጥላቻ ደግሞ የሽንፈት ዋስታና ነው።

    በቅርቡ ቤት ውስጥ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በእናቱ አማራ ነው እያለች አንድ ዘመዳችን በደስታ ትፈነድቃለች። ጠቅላዩ ብዙም አልቆየም፤ በOBN ላይ ቀርበው በእናታቸውም በአባታቸውም ኦሮሞ እንደሆኑ ገለጹ። ይሄውልሽ ተሳስተሻል ስላት፥ እሱ ነው የተሳሳተው አለችኝ። ቀጥላም የሰላም ኖቤል ሽልማት ሲቀበል አስተዋዋቂዋ በእናቱ አማራ እንዲሁም በአባቱ ኦሮሞ እያለች የተናገረችውን አሳየችኝ። ይሄ እኮ እሱ የተናገረው ሳይሆን እነሱ በስማ በለው ጽፈው ያቀረቡት ነው። ደግሞ ካስተዋልሽው በእናቱ አማራ ስትል እኮ ሳቀ። ይሄም የሚጠቁምሽ ነገር አለ ስላት፥ “ችግር የለውም እኔ ነው ብያለው፤ ነው!” አለችኝ። ይሄ አሸናፊን፣ ጀግናን የራስ የሚያደርግ፣ የሚቀበል ሥነ-ልቦና እንዲሁ በከንቱ የመጣ አይደለም፤ ሲገነባ የቆየ እንጂ። በእውቀቱ ስዩም ኢትዮጵያውያን ‘እኛ በዚህ ነገር አንደኛ ነን’ የማለት ሥነ-ልቦና አለን ይላል። “ለምሳሌ እኔ የቤቱ ሦስተኛ ልጅ ብሆንም ለሰው ስናገር ግን” ይላል፥ “ከቤታችን ሦስተኛ በመሆን አንደኛ ነኝ ብዬ ነው” በማለት የባህላችንን ራስን ከፍ የማድረግ ድንቅ ሥነ-ልቦና ይገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ነገ ቢገደል ወይም አንድ ነገር ቢያደርጉት ኦሮሞ ስለሆነ ተገደለ ብለው አሁን የምታይዋቸው እሱን የሚቃወሙ የኦሮሞ ጎበዞች የራሳቸው ጀግና ያደርጉታል። እሱም ይሄን ሥነ-ልቦና ጠንቅቆ ስለሚያውቅ ሥልጣኑ ባልጸናበት ወቅት “ከቡራዩ ጠቅላያችን ተነካ ብለው ወጣቶች ሲመጡ፥ ኦሮሞ መምራት አይችልም እያሉ” ምናምን እያለ ሆዳቸውን እያባባው ነበር። በበታችነት ሥነ-ልቦና ትልቅ ሀገር መገንባት እንደማይቻል ጠንቅቆ የሚያውቀው አብይ ይሄን “rhetoric” ብዙ አልገፋበትም። ደካማ አድርጎ ራሱን ዘወትር የሚስል ማንም፥ በዙሪያው ባሉ ሊከበር እንደማይችል ያውቃል’ና፤ በተለይ በፖለቲካ። አብይ ጠንክሮ ሲወጣ፣ ኮስታራ መሪ ሲሆን፣ ቀጥ ለጥ አድርጎ ሲገዛ ሲሰድቡት የነበሩ የአማራ አክቲቪስቶች ሳይቀሩ መልሰው በፍቅሩ እያበዱለት ነው። አማራው የተቀረጸበት እና ያደገበት ሥነ-ልቦና ከጀግንነት እና ከቆራጥነት ጋር እጅግ የተሳሰረ ነው። ባለፉት 30 ዓመታት በኦሮምኛ የተዘፈኑ እና የአማርኛ (በተለይ የባህል) ዘፈኖችን ቁጭ ብላችሁ አነጻጽሩ። አሁን የምናገረው እንደ ጉድ ይታያችኋል።

    ሀጫሉ ሁንዴሳ ከሌላው ዘፈኝ በተለየ ይሄ በጣም የገባው አዋቂ ዘፋኝ ነበር። ኦሮሞ ተገፋ፤ ጡት አስቆረጠ፤ ተኮረኮመ የሚሉ ዘፈኖች እምብዛም የሉትም። የአድዋ ድል ሲመጣ እነ ግርማ ጉተማ ይሄ ድል እኛን አይመለከተንም፤ እነ ጸጋዬ አራርሳ እኛ ለሌላ ቅኝ ግዛት የተዳረግንበት ነው ብለው በድል ቀን ሲያለቃቅሱ ሀጫሉ ግን ፈረሱ ላይ ጉብ ብሎ ባለፉት 28 ዓመታት ባልተለመደ መልኩ ይሄ ድል ከማንም በላይ የኛ ነው እያለ መስቀል አደባባይ ወጣ። የአድዋ ተራራ ሄደን ትግራይ የኛ ናት ያልነው ኦሮሞዎች ነን አለን። ታሪክ ብዙ ነገሩ ተረት ነው። ዋናው ቁም ነገር የሰው ልጅ እጅግ ኢ-ምክንያታዊ ስለሆነ ተረትም ተነገረው ታሪክ ‘አንተ እኮ ልዩ ነህ፤ አሸናፊ ነህ’ ከተባለ የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት የአልያንስ ኃይሎች (the Allies) ጀርመንን ወደ አመድነት ከቀየሯት በኋላ አንድ የጀርመን ፖለቲከኛ ለጀርመኖች ያለው ነገር ነበር። “አገራችንን ከፈሏት። ሕንጻዎቻችንን አፈራረሱት። ስልጣኔያችንን አመድ አደረጉት። ጀርመናዊ አዕምሮአችንን ግን ከኛ መውሰድ አልቻሉም” ነበር ያለው። ጀርመን ዛሬ ካፈረሰቻት እንግሊዝ በተሻለ የኢኮኖሚ ቁመና ላይ ትገኛለች። በአውሮፓ ሕብረት በኩል ትልቅ ኢምፓየር ሆና ብቅ ብላለች። እዚህ ላይለመድረስ ከአራት አስርት ዓመታት በላይ አልፈጀባትም። አይሁዶችንም በተመሳሳይ መመልከት ነው። ከናዚ (Nazi) በኋላ የመጡት የጀርመን መሪዎች ብዙዎቻችን እንደምንገምተው በናዚ በተፈጸመ በደል ክፉኛ የሚጸጸቱ አልነበሩም። ይልቁስ ያን ሁሉ ተዓምር ጀርመን መሥራቷ ኩራት የወጠራቸው፣ ድጋሚ ኃያል ሀገር እንደሚሆኑ ለአፍታም ያልተጠራጠሩ ሕዝቦች ነበሩ። Paul Berman የተባለ አሜሪካዊ ጸሐፊ  “Power and the Idealist” ብሎ በጻፈው ድንቅ መጽሐፍ መጸጸት የጀመረ ትውልድ የመጣው ጀርመን በድጋሚ በኢኮኖሚ ከአበበች በኋላ በመጣው ትውልድ ነው ይላል። ዛሬ ለገጠማቸው ከስደተኛ ጋር ለተያያዘ መጠነ ሰፊ ችግር የጸጸት ሥነ-ልቦና ያለውን አስተዋጽኦ ያብራራል። ጄኔቫ (Geneva) እያለው አለቃዬ አይርሻዊ (Irish) ነበር። እንግሊዞች እንደ እኛ የበደሉት የለም ይለኛል። ለብዙ ዘመን እንግሊዝ እንዲህ አደረገን እያልን የተበዳይነት ፖለቲካ (victim politics) ስንሠራ ኖርን። ከእንግሊዝ ተላቀን እንኳ አዕምሮአችን ከእነሱ ነጻ አልወጣም ነበር። የገነቡትን ሃውልት ማፍረስ ሥራችን አደረግን። ወይ መልሰን የራሳችንን ሃውልት አላቆምን። መንገዶቹንም ሃውልቱን በማፍረስ ከትላንት የተሻለ ውብ አላደረግናቸውም፤ አስቀየሙ እንጂ። በኋላ ግን ባነንን አለ። ያኔ ነው ማደግ እና መለወጥ የጀመርነው። ከታሪካችን ጋር ታረቅን። የእንግሊዝን ድል የእኛ ድል አድርገን መቀበል እና መተረክ ጀመርን አለኝ። ከዚያ በብዙ ነገር ለመመንደግ ጊዜ አልፈጀብንም አለኝ።

    ኢትዮጵያኖች ራሳቸውን ከድል አድራጊ እና ከትልቅ ነገር ማጠጋጋት ነበር ታሪካቸው። ይሄ ተራ ጉራ የሚመስለው ሞኝ ይኖራል። በቅርብ ያገኘሁት አንድ ሸምገል ያለ ጥቁር አሜሪካዊ ዳኛ ጋር ስናወራ ለብዙ ጊዜ በራሴ እጠራጠር ነበር አለኝ። ውስጤ ውስጥ “ትችላለህ፣ አትችልም” የሚል ከባድ ትግል ነበር። ብዙ ምሳሌ እና እኔን የሚመስሉ አርአያ የሉኝም። ቀለሜ ያለመቻል ምሳሌ ሆኖ አሜሪካ ውስጥ ቆሟል። ይሄ የውስጥ ትግል ለእኔ አሰልቺ ነበር አለኝ። ኢትዮጵያኖች “ፑሽኪንን” ኢትዮጵያዊ ነው ሲሉ ለኢትዮጵያ ሥነ-ጽሑፍ ያበረከተው ነገር ኖሮ አይደለም። ነገ ለሚወለዱት፣ ከዛም ለሚሰደዱት ልጆቻቸው ‘የትም ሄደክ በሄድክበት ሀገር ካሉ ዜጎች በላይ አንተ የመብለጥ አቅም አለህ፤ አንተ ልዩ ነህ’ የሚል ታሪክ እየነገሩት ነው። ይሄ ትርክት ነው ነገ ልዩ የሚያደርገው። አስጨናቂውን የሕይወት ትግል አሸናፊ የሚያደርገው። የውብሸት ወርቃለማሁ ልጅ ዶ/ር ዳግማዊ ውብሸት በአሜሪካ ውስጥ ካሉ ስምንት ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ በሆነው Cornell University የእንግሊዘኛ ሥነ-ጽሑፍ አስተማሪ ነው። በአንድ ቃለ-መጠይቁ ላይ ወደ አሜሪካ ሲመጣ እንግሊዘኛ ካለመቻሉ በላይ አንብብ ሲባል ተማሪዎቹ በሳቅ ይወድቁ እንደነበረ ይገልጻል። “እነሱ ሲስቁ ጣልያንን ማሸነፋችን ትዝ እያለኝ፥ ‘ምናለ በሉኝ በራሳችሁ ቋንቋ እናንተን ካልበለጥኩ’ እያልኩ ለውስጤ እነገረው ነበር” ይላል። እንዳለውም በCornell University ታሪክ በእድሜ ትንሹ የእንግሊዘኛ ሥነ-ጽሑፍ ፕሮፌሰር ሆነ። ይሄ ተራ ዩኒቨርሲቲ አይደለም። አይደለም አስተማሪ ለመሆን ተማሪ ለመሆን እራሱ አስደናቂ አዕምሮ ሊኖርህ ይገባል። በነገራችን ላይ ከዚሁ ዩኒቨርሲቲ በኮምፒውተር ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በቅርብ በዶክትሬት ዲግሪ የተመረቀች የመጀመሪያዋ ጥቁር፥ ኢትዮጵያዊት ናት። ዶ/ር ረድኤት አበበ ትባላለች። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንደሚባለው የአሜሪካ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ተወዳዳሪ የምክትል ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን (Joe Biden) የሽግግር ካቢኔ መሪ ከታዋቂው ዬል ዩኒቨርሲቲ (Yale University) እና ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ (Harvard University) የተመረቀው ዮሐንስ አብርሃም የተባለ ኢትዮጵያዊ መሆኑን ታውቃላችሁ። ይሄ ማለት ጆ ባይደን ካሸነፈ በዋይት ሀውስ (White House) ውስጥ ካሉት ትልልቅ ስልጣኖች ቁልፉ ቦታን የሚይይዘው ኢትዮጵያዊው ዮሐንስ አብርሃም ይሆናል ማለት ነው። ደግሞም አምናለው በእኛ የእድሜ ዘመን ውስጥ ከኦባማ ቀጥሎ የአሜሪካ ጥቁር ፕሬዝዳንት የሚሆነው ኢትዮጵያዊ ሊሆን ይችላል። ብዙ ድንቅ ኢትዮጵያውያን በሪፖብሊካንም ሆነ በዲሞክራቶች የፓርቲ መስመር የስልጣን መሰላሉን እየወጡ እየተመለከትን ነው።

    ወደ ቀደመ ነገሬ ልመለስ እና – የኦሮሞ ባህል ይሄን ነገር ካልመረመረ የብዙ አቅመ ድኩማን መደበቂያ እና የሽንፈት ታሪክ ወራሽ ልጆች መፈልፈያ ይሆናል። እስቲ ተመልከቱ – ብርሃነመስቀል አበበ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የአብይ ደጋፊ እና ደንበኛ የኢትዮጵያዊነት አቀንቃኝ ነበር። በአቅም ማነስ ከስልጣን ሲባረር ግን ኦሮሞነቱ ትዝ አለው። የወጣለት የኦሮሞ የመብት አቅንቃኝ ሆነ። ኦሮሞዎቹም ዓይንህን ለአፈር ብለው መስኪድ እንደገባ ውሻ እንዳላባረሩት፥ በአቅም ማነስ ተባሮ ሲመጣ ጀግና አድርገው ተቀበሉት። በተመሳሳይ አማራን እንይ፤ ልክ እንደ ብርሃነመስቀል አበበ ሲባረሩ አማራ ጉያ ውስጥ ለመደበቅ የፈለጉ ሰዎች በቅርብ ታሪካችን ነበሩ። ለምሳሌ ታምራት ላይኔ አንዱ ነው። አማራው ግን ከታምራት ላይኔ ይልቅ መለስ ዜናዊን ይወዳል። በተመሳሳይ ልደቱ አያሌውም ከፖለቲካው መድረክ ሲገለል፥ አማራ ስለሆንኩ ነው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ የጠላኝ አለ። ዶ/ር ብርሃኑ እኮ የተደነቀ አዋቂ ሰው ነው። ምን ዓይነት ጅል ቢሆን ነው የድጋፍ ማዕከሉ የሆነውን የአማራን ሕዝብ የሚጠላው? የአማራ ሕዝብ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋን እንደሚያፈቅር ለማወቅ በአማራ ክልል እሱ የተገኘባቸውን ሠልፎች እና ስብሰባዎች ማየት ነው። ከልደቱ ይልቅ የአማራው ሕዝብ የብርሃኑ አመለካከት ይስበዋል። ሽንፈት፣ውድቀትን በዘር ቅርፊት ማሳበብ አማራው አምርሮ የሚጸየፈው ነገር ነው። ተሸንፈህ ከመጣ አማራነትህ ይነጠቃል።

    አጼ ቴዎድሮስ በመጀመሪያ በአማራው ሕዝብ እጅግ የተጠላ መሪ እንደነበረ ታሪክን ማገላበጥ ብቻ በቂ ነው። እነ ዮፍታሔ እና ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን ግን ቴዎድሮስን በጀግንነት ካባ አዲስ ሰው አድርገው አቀረበቱ። የቋራ ሰው እየተባለ፣ የኮሶ ሻጭ ሲባል ሲሰደብ የከረመው ቴዎድሮስ ህልሙ እና ጀግንነቱ ለሕዝቡ ተብራርቶ በአዋቂዎች ሲቀርብለት አማራ የሆነው በፍቅር አበደለት። ጀግና እና ዘመን ተሻጋሪ አዋቂን የሱ እንኳ ባይሆን እንደምንም የራሱ የማድረግ ባህል አለውና።

    በምድር ላይ እንደእሱ ዓይነት ጠቢብ የለም ብሎ መጽሐፍ ቅዱስ የሰበከለትን ሰሎሞን የተባለ ሌጀንድ የኢትዮጵያ ጠበብት ሲመለከቱት ጊዜ አላጠፉም። ኢትዮጵያዊ አጋቡት። በዓለም ታሪክ የዓለምን ፖለቲካ በመቀየር ፈጽሞ አቻ የሌለው የPlato “The Republic” መጽሐፍ ድንቅ ሕዝብ እና ታላቅ ሀገር በፈላስፋ ይመራል በሚል አስደናቂውን መጽሐፍ ይዘጋል። አባቶቻችን ይሄን ለመረዳት ከባድ የሆነን መጽሐፍ ያነበቡ ስለነበሩ ፥ በኢትዮጵያ ታሪክ የሚነግሰውን ሁሉ ከፈላስፋው ሰሎሞን ወልደ ዳዊት ጋር ሲያዛምዱት ቆዩ። ኢትዮጵያኖች ልጆቻችሁን አዎ ልዩ ናችሁ እያላችሁ አሳድጓቸው። አንብበው፣ ተመራምረው አዋቂ ሲሆኑ ሁሉን በራሳቸው ይደርሱበታል። እስከዛ ግን ይሄን ሥነ-ልቦና ፈጽማችሁ አትንጠቋቸው። እነሱን እዚህ አሜሪካ እንደሚወለደው ከአንጎላ በመርከብ ከመጣው ጥቁር አሜሪካዊ ጋር የተገዢነት ሥነ-ልቦና አታላብሷቸው። ጥቁሩን ሁሉ ነጻ የሚያወጣው ኢትዮጵያዊው እሱ መሆኑን ከልጅነቱ ጀምራችሁ ስበኩት።

    በመጨረሻም በአንድ አፈ-ታሪክ ምሳሌ ጹሑፌን ልዝጋ። ጅብ አህያን ለብዙ ጊዜ ሲፈራት ይኖር ነበር። ለዚህ ዋናው ምክንያት ደግሞ የአህያ ጆሮ ቀንድ እየመሰለው ነው። አህያ ጅብን መወዳጀት ስለምትፈልግ ለብዙ ጊዜ እንዲቀርባት ትሻ ነበር። አንድ ቀን ግን ለምን እንደሚሸሻት ጨክና ጠየቀችው። እሱም ቀንዶቿን እጅግ እንደሚፈራው ለዛም እንደሚሸሻት ነገራት። በመገረም “ይሄ እኮ ቀንድ አይደለም፤ ጆሮዬ ነው፤ ስጋ እንጂ አይዋጋም አለችው።” ከዚያ ቀን ጀምሮ አባራሪ እና ተባራሪ ቦታ ተለዋወጡ። ኢትዮጵያኖች ታሪኮቻችን፣ ድሎቻችን፣ ሃውልቶቻችን፣ ሃይማኖታችን ጅብ ከሆኑ ጠላቶቻችን መጠበቂያ ጋሻዎቻችን፣ ምሽጎቻችን ናቸው። ይሄን አጥተን ከመኖር ሁላችን ማለቅን መምረጥ ይሻለናል። ጆን ስቱዋርት ሚል (John Stuart Mill) እንዳለው “የተደሰተ አሳማ ከመሆን የተከፋ ሰው መሆን ይሸላል፣ ጅል ሆኖ ከመደሰት ሶቅራጦስን ሆኖ ዕድሜ ልክን ማዘን ይሻላል።” ለልጆቻችን የባርነትን፣ የተሸናፊነትን ሥነ-ልቦናን ከምናወርስ ሁላችን ቀድመን ማለቅ ይሻለናል። አባቴ ጀግና ነው እያለ ካላባት ያደገ ልጅ በፈሪ አባት ካደገ ልጅ በላይ በራስ መተማመኑ ኃያል ነው።

    * በዚህ ጽሑፍ ላይ አማራ ብዬ የጠቀስኩት ማኅበረሰብ በአሰፋ ጨቦ ትንታኔ መሠረት ሲሆን፥ ዘርን ሳይሆን የአባቶቻችንን ድል እና ኃያልነት የተቀበለውን፣ የማሸነፍ መንፈሱ የማይደረመስ ተራራ የሆነውን፣ በየሄደበት ሁሉ የአባቶቹን ድል አድራጊነት እያሰበ የበታችነትን እንቢ ያለውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ የሚመለከት ነው።

    አማራ ብዬ የጠቀስኩት...

    Anonymous
    Inactive

    ብርሃኑ ነጋ የመረጠውን ሕይወት ለመምረጥ የጨዋ ልጅ መሆን ይጠይቃል፣ የህሊና ሰው መሆን ይጠይቃል፣ ራስን ማክበር ይጠይቃል። የብርሃኑ ነጋን ፅናትና የአቋም ሰውነቱን መካድ ነውር ነው! እሱን በፍርሃትና በአቋም የለሽነት ማማት ብልግና ነው። እሱን በዘርና በጎሳ ጉሊት መመደብ ውለታ ቢስነት ነው!

    የነጋ ቦንገር ልጅ!
    («ዘውድዓለም ታደሠ»)

    የልደቱ አያሌው ድብን ያልኩ አድናቂ ስለሆንኩና ብርሃኑ በልደቱ ጉዳይ የወሰደው አቋም አግባብነት ያለው (fair) ነው ብዬ ስለማላምን ትንሽ አዝኜበታለሁ። ሆኖም ግን እውነት እውነት ነችና ስለብሬ [ብርሃኑ ነጋ] የማልክዳቸው ሃቆች አሉ! (ስለእሱ የሰማኋቸውን “ሴራዎችን” (conspiracies) እዚህ ጋር አላነሳቸውም።)

    ብርሃኑ ነጋ እንደብዙዎቹ ፖለቲከኞቻችን ‘ፖለቲካ ክፍት የሥራ ቦታ ነው’ ብሎ ወደተመታው የኢትዮጵያ ፖለቲካ አልተቀላቀለም። በደርግ ዘመን ብዙዎች በወላጆቻቸው ሽካ ከብሔራዊ ውትድርና አምልጠው ማታ ማታ ገዳም ሰፈር ከቆነጃጅት ጋር ቡጊ ቡጊ ሲጨፍሩ ብሬ በዚያ እድሜው የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ሆኖ በአገሩ ጉዳይ ከሞት ጋር ሌባና ፖሊስ ይጫወት ነበር። (የሚወዳት እህቱንም አጥቷል።)

    በኢህአዴግም ግዜ ከመለስ፣ ከታምራትና ከበረከት ጋር ባለው ልዩ ወዳጅነት (special friendship) ተሞዳሙዶ ቢያሻው ስልጣን፣ ቢያሻው መሬት ሸምቶ፣ ቢያሻው ሚኒስትር፣ ቢያሻው ቀጭን ኢንቨስተር ሆኖ ዘንጦ መኖር ሲችል ላመነበት ነገር ጎምበስ ቀና ሳይል የተቃዋሚውን ጎራ ተቀላቅሏል።

    ምንም እንኳ በየትኛውም ዓለም ቢሄድ እጁን ስመው የሚቀበሉት ምርጥ ምሁር ቢሆንም ከምቾቱ ይልቅ ወደወህኒ ወርዶ ሞት ተፈርዶበታል። እስር ቤት ውስጥ የረሃብ አድማ አድርጓል። በስተርጅና ዘመኑም እንዳቅሚቲ የትጥቅ ትግል ለማድረግ ተሟሙቷል። በተደጋጋሚ በርሃ ወርዷል። የፖለቲካ አኪያሄዱን ወደድነውም ጠላነውም በሚችለው አቅም ለአገሩ ህዝብ ድምፅ ሆኗል! ይሄ የማይካድ ሃቅ ነው!

    ከግማሽ ምእተ-ዓመት በላይ የሃብት ማማ ላይ ከተቀመጠ ቤተሰብ ተወልዶ፣ ዩኒቨርሲቲ ደሞዙን ለምስኪን ተማሪዎች እየሰጠ አስተምሮ፣ እድሜውን ሙሉ ባለሰባት ኮከብ (seven-star) ሆቴል እንደፓፍ ዳዲ አምስት ቺኮች አቅፎ መዝናናት እየቻለ ያሻው አገር ሄዶ በዕውቀቱ ተከብሮ መሥራት እየቻለ፣ በአፍሪካ ገናና የሆነ የጦር ኃይል አለኝ የሚልን ኃይል በጦርነት አሸንፋለሁ ብሎ በወኔ የተነሳ፣ ቤተሰቡን ጥሎ በእስር የማቀቀ፣ አገሩ ላይከፍተኛ ዕውቅና እንዳለው ግለሰብ (VIP standard) መኖር ሲችል በአሸባሪነት ተፈርጆ ብላክ ሊስት (black list) ውስጥ የገባ አንድ ሰው ባፈላልግ ያገኘሁት ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋን ብቻ ነው!

    አሁን ደግሞ ብሬ በተጋዳላይ ታርጋ የሚንቀሳቀስ ፓርቲውን አክስሞ አዲስ ፓርቲ በማቋቋም ከመጀመሪያው “ሀ” ብሎ (from the scratch) ሊነሳ ነው። ይህን ሁሉ የሚያደርገው ለምንድን ነው? ለሀብት እንዳንል እንኳን እሱ ዘር ማንዘሩም ሃብታም ነው። ለስልጣን እንዳንል ገና ድሮ በቀላሉ ማግኘት ይችል ነበር! እና ለምንድነው ህይወቱን እንዲህ በከባድ ወጥ ውረዶች የተሞላ (tragedy) ያረገው?… መልሱ ቀላል ነው። ብሬ (ብርሃኑ ነጋ) የአቋም ሰው ነው! ብሬ ላመነበት ነገር ከገገመ ገገመ ነው! አዲዮስ!

    እኔ ከላይ እንደነገርኳችሁ ‘ለብሬ እሰዋለታለሁ፣ ብርሃኑ ነጋ ያማልዳል፣…’ ምናምን የምል አድናቂው አይደለሁም። ነገር ግን አክባሪው ነኝ። ፅናትና የአቋም ሰውነቱን መካድ ነውር ነው! እሱን በፍርሃትና በአቋም የለሽነት ማማት ብልግና ነው። እሱን በዘርና በጎሳ ጉሊት መመደብ ውለታ ቢስነት ነው!

    […] የባቄላ ፍሬ የምታህል ዛኒጋባ ቤት ሳትኖርህ ቫንዳም፣ ቫንዳም መጫወት፣ የምታጣው ነገር ሳይኖር ኃላፊነት (risk) መውሰድና ከባዱን የሕይወት መንገድ መምረጥ’ኮ ያለና የነበረ ነው። ነገር ግን ሁሉ ሞልቶልህ ብርሃኑ ነጋ የመረጠውን ሕይወት ለመምረጥ የጨዋ ልጅ መሆን ይጠይቃል፣ የህሊና ሰው መሆን ይጠይቃል፣ ራስን ማክበር ይጠይቃል! ይኸው ነው!

    ረጅም ዕድሜ ለነጋ ቦንገር ልጅ!

    [ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እና አቶ አንዱአለም አራጌ የኢትዮጵያ ዜጎች ማህበራዊ ፍትህ ፓርቲ መሪና ምክትል መሪ በመሆን ተመረጡ። ግንቦት 2 ቀን 2011 ዓ.ም. በተካሄደው ምርጫ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ 912 ድምፅ በማግኘት የፓርቲው መሪ በመሆን ተመርጠዋል። በተመሳሳይ አቶ አንዱአለም አራጌ የፓርቲው ምክትል መሪ በመሆን ተመርጠዋል። እንደዚሁም አቶ የሺዋስ አሰፋ 722 ድምፅ በማግኘት ሊቀመንበር ሆነው ሲመረጡ፥ ዶ/ር ጫኔ ከበደ ምክትል ሊቀመንበር በመሆን ተመርጠዋል። — ሰሞነኛ ኢትዮጵያ]

    ብርሃኑ ነጋ የኢትዮጵያ ዜጎች ማህበራዊ ፍትህ ፓርቲ


     

Viewing 11 results - 1 through 11 (of 11 total)