ኢትዮ ቴሌኮም 4000 የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የ16 ሚሊዮን ብር የገንዘብ ድጋፍ መርሐ ግብር ይፋ አደረገ

Home Forums Semonegna Stories ኢትዮ ቴሌኮም 4000 የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የ16 ሚሊዮን ብር የገንዘብ ድጋፍ መርሐ ግብር ይፋ አደረገ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #13156
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ኢትዮ ቴሌኮም በዩኒቨርሲቲ የሚገኙ ተማሪዎች የድጋፍ መርሐ ግብርን በ2006 ዓ.ም. የጀመረ ሲሆን የተጠቃሚዎችም ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በ2011 በጀት ዓመት መጨረሻ በ13 ዩኒቨርስቲዎች ለ840 ተማሪዎች ድጋፍ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን ይህ ድጋፍ የሚኖረውን ጠቀሜታ ታሳቢ በማድረግ  በመላው ሀገሪቱ በሚገኙ 45 ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የሚማሩ አራት ሺህ (4000) ተማሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የድጋፍ መርሐ ግብር አዘጋጅቶ ጥሪ የተደረገላቸው የመንግሥት ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንቶች፣ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎችና ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት በተገኙበት ታኅሣሥ 21 ቀን 2012 ዓ.ም.  ይፋ አድርጓል። ለዚህም ፕሮጀክት የሚውል በዓመት ብር 16 ሚሊዮን ብር መድቧል።

    ­­­­­­­­­ኢትዮ ቴሌኮም ማኅበራዊ ኃላፊነቱን (corporate social responsibility) ለመወጣት ትኩረት ሰጥቶ እየሠራባቸው ከሚገኙ ጉዳዮች መካከል የትምህርት ዘርፍ አንዱ ሲሆን ከዚህም ውስጥ በመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ለሚገኙና ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ተማሪዎች ወርኃዊ የገንዘብ ድጋፍ ያደርጋል።

    ኩባንያው በትምህርት ዘርፍ በተለያዩ አካባቢዎች ድጋፍ ለሚሹ ከአሥራ አራት ሺህ በላይ ተማሪዎች የምገባ፣ የትምህርት ቁሳቁስና የኪስ ገንዘብ ድጋፍ እንዲሁም በያዝነው 2012 በጀት ዓመት በመላው ሀገሪቱ በሚገኙ 93 ትምህርት ቤቶች ለሚማሩ 32,974 ተማሪዎች ለእያንዳንዳቸው የአንድ ደርዘን ደብተር ድጋፍ እንዲሁም ከአምስት ሺህ በላይ ለሚሆኑ ተማሪዎች የዩኒፎርምና ቦርሳ ድጋፍ አድርጓል።

    ከዚሁ በተጨማሪ ኢትዮ ቴሌኮም ሴቶች በኢኮኖሚው መስክ ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ ከአዲስ አበባ ክፍለ ከተሞች ለተውጣጡ አንድ መቶ ሴቶች የፋሽን ዲዛይን ሥልጠና እንዲወስዱ ሙሉ ወጪውን በመሸፈን ድጋፍ አድርጓል። የሥልጠና ዕድሉ የተመቻቸው ሴቶች በትምህርት፣ በሥራ እንዲሁም በአጠቃላይ የምጣኔ ሀብት (የኢኮኖሚ) መስኮች ያለባቸውን ተጽእኖ ከግምት በማስገባት ሴቶችን ማስተማር እና በኢኮኖሚ በማብቃት ራሳቸውን እንዲችሉና ልጆቻቸውን ማስተማር እንዲችሉ እገዛ ለማድረግ ነው።

    ኩባንያው በተለይ ከ2011 በጀት ዓመት ጀምሮ በተደራጀ መልኩ ማኅበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት ለዋና ሥራ አስፈጻሚ ተጠሪ የሆነ የሥራ ክፍል በማደራጀት ማኅበረሰባችን ድጋፍ የሚሻባቸውን የትኩረት መስኮች በመለየት የማኅበራዊ ኃላፊነት ሥራዎችን አጠናክሮ በመሥራት ላይ ይገኛል። በዚህም ረገድ:-

    • በሰብዓዊ እና ማኅበረሰብ አቀፍ ድጋፎች ለሴቶች፣ ለአረጋውያን፣ ለሕፃናት፣ ለአካል ጉዳተኞች፣ ለጎዳና ተዳዳሪዎች እና ለመሳሰሉት የማኅበረሰብ ክፍሎች ድጋፍ አድርጓል፤
    • በአረንጓዴ ልማትና በአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ “በአረንጓዴ ኢትዮጵያ ፕሮጀክት” አማካኝነት በመላ ሀገሪቱ ከ17 ሺ በላይ ሠራተኞችን በማሳተፍ ከ1.5 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ተክሎ እንክብካቤ በማድረግ ላይ ይገኛል፤
    • ኢትዮ ቴሌኮም ሸገርን ለማስዋብ ፕሮጀክት ካደረገው የገንዘብ ድጋፍ በተጨማሪ ከቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ እስከ ብሔራዊ ቤተመንግሥት የመንገድ ላይ መብራቶች ድጋፍ በማድረግ አዲስ አበባ ከተማ ውብና ጽዱ ለማድረግ የበኩሉን አስተዋፅኦ በማድረግ ላይ ይገኛል። ከዚህም ጋር በተያያዘ ኩባንያው ሌሎች የሀገራችን ከተሞች ጽዱና አረንጓዴ አካባቢን ለመፍጠር የሚያደርጉትን ጥረት በመደገፍ ላይ ይገኛል፤ ለወደፊትም ይህንኑ አጠናክሮ ይቀጥላል፤
    • በተጨማሪም ኩባንያው ለሌሎች የመንግሥት ፕሮጀክቶችም በሄልዝ ኔት (Health Net)፣ በወረዳ ኔትና (Woreda Net) በስኩል ኔት (School Net) ፕሮጀክቶች አማካኝነት ድጋፉን እያደረገ ይገኛል፡

    ማኅበራዊ ኃላፊነትን የመወጣት ባህል ኩባንያው ብቻ ሳይወሰን በሠራተኞቻችንም በበጎ ፈቃደኝነት የሚሠራ ሲሆን፥ በዚህም ረገድ በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ ሠራተኞቻችን በየአካባቢያቸው በጤና፣ በሰብዓዊነት፣ በትምህርት፣ በአካባቢ ጥበቃ እና በመሳሰሉት ዘርፎች ከፍተኛ አስተዋፅኦ በማድረግ ላይ ይገኛሉ።

    በዩኒቨርሲቲ እንዱስትሪ ትስስር፣ በተመራቂ ተማሪዎች የኤክስተርንሺፕ (externship) እና በተለያዩ ዩኒቨርሲቲ መምህራን የጥናት ፕሮጀክቶች ላይ ኢትዮ ቴሌኮም በሀገራችን ከሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በመተባበር እንደሚሠራ ይታወቃል። በቀጠይም ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በቅንጅት ማኅበረሰቡን የሚጠቅሙ ፕሮጀክቶች ላይ በመሳተፍ የሀገራችን ዜጎች ከሁለቱ ተቋማት የሚጠቀሙበትን ሁኔታዎች በጋራ እንደሚያመቻች ኩባንያው በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል።

    ምንጭ፦ ኢትዮ ቴሌኮም/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ኢትዮ ቴሌኮም

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.