Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 271 through 285 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን እህተ ማርያም በሌሎች ወንጀሎችም በመጠርጠሯ ምርመራውን እያጠናከረ መሆኑን ገለጸ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ራሷን ንግሥተ ነገሥት (እህተ ማርያም) እያለች በምትጠራው ትዕግሥት ፍትህአወቅ ላይ የአስቸኳይ አዋጁን ከመጣስ በተጨማሪ በሌሎች ወንጀሎችም በመጠርጠሯ ምርመራውን እያጠናከረ መሆኑን ገለጸ።

    በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የልዩ ልዩ ወንጀል ዲቪዥን ምርመራ ኃላፊ ኢንስፔክተር በድሉ ግርማ ትዕግሥት ፍትህአወቅ (እህተ ማርያም) ላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እምነቴንና ቀኖናዬን አቃላለች መገልገያ አልባሳቴን ያለ አግባብ ጥቅም ላይ አውላለች በሚል ያቀረበችው ክስም በምርመራው እየታየ እንደሆነ ገልጸዋል።

    ግለሰቧ ሃይማኖትም ሆነ ማኅበር ለመመሥረት ከኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዲሪ) የሰላም ሚኒስቴር ተገቢውን ፈቃድ ሳታገኝ ርትዕት ተዋሕዶ የሚል ሃይማኖት መሥርታ ተከታዮቿን አላግባብ እየሰበሰበች የነበረበት ሂደትም እየተመረመረ ነው ተብሏል።

    ተጠርጣሪዋ የትዳር አጋሯ በትራፊክ አደጋ እንደሞተ ብትገልጽም የሟች ቤተሰቦች ይህ ስለመሆኑ ምንም ማስረጃ ባለመኖሩ ተጨማሪ ምርመራ ይደረግልን ማለታቸውም ምርመራው የሚያተኩርበት ሌላ ጭብጥ መሆኑንም ኢንስፔክተሩ ገልጸዋል።

    በተጠርጣሪዋ ቤት የተገኘው አስከሬንም ለምርመራ ወደ ሆስፒታል መላኩንም ኢንስፔክተር በድሉ ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    —–
    ሌሎች ዜናዎች፦

    እህተ ማርያም

    Anonymous
    Inactive

    ቅኔ ነው ሀገር ― የሦስት ሙዚቃዊ ዘመናት አንጋፋ እና ወጣት ድምፃውያንን እንዲሁም ታላላቅ የሙዚቃ ሊቃውንትን ያገናኘ ልዩ ኦርኬስትራዊ ኅብረ ዝማሬ!!!

    • ከ1950ዎቹ እና 60ዎቹ አንጋፋ ድምጻውያን መካከል አንዱ የሆነው ጥዑመ ልሳኑ ድምጻዊ ታደለ በቀለ (ከሥራዎቹ በጥቂቱ፦ “አላስቀየምኳትም”፣ “ዉብ ዓይናማ” /ከሒሩት በቀለ ጋር/፣ “ሸንኮርዬ” /ከወይንሸት ሙሉነህ ጋር/)፣
    • ከ1970ዎቹ እና 80ዎቹ የወጣትነት ዘመናቸው እስከ ዛሬ ዝናቸው እንደተጠበቀ እዚህ የደረሱት ድምጻውያኑ ንዋይ ደበበ (ከብዙ ሥራዎቹ በጥቂቱ፦ “የፍቅር ገዳም”፣ “አልዋሽም”፣ “ብትከዳኝ ታዘብኳት”፣ “ማዕበል ነው”፣ “ሸጊት ከሐረር፣ ሸጋው ከሐረር” /ከሀመልማል አባተ ጋር/) እና ጸጋዬ እሸቱ (ከብዙ ሥራዎቹ በጥቂቱ፦ “ሰንደቅ ዓላማ”፣ “ያይኔ አበባ”፣ “አላስገድድሽም”፣ “አንቺ ቅናተኛ”፣ “እናት ወደር የላት”፣ “ለሰርጓ ተጠራሁ”)፣
    • ከ1990ዎቹ አይረሴ አልበሞቹ ጀምሮ እስከ ዛሬ ተወዳጅ የኾነው ድምጻዊ ኃይልዬ ታደሰ (ከብዙ ሥራዎቹ በጥቂቱ፦ “ሁሌ ሁሌ”፣ “እንደአፍሽ ያድርገው”፣ “እሷን ብቻ”፣ “በዘመኔ”፣ “ልትሄድ ነው”፣ “ይሞታል ወይ”)፣
    • የሙዚቃ ልኬት በልዩ አጨዋወት እና ድንቅ ብቃት የታየበት እንዲሁም ብዙዎች ለመስማት የጓጉለት ሠርፀ ፍሬስብሐት (በኢትዮጵያን አይድል [Ethiopian Idol] ውድድር ላይ እጅግ ላቀ ባለ የዳኝነት ሙያው አንቱታን ያተረፈ)፣
    • ከወጣቶቹ፣ ከዘመነኞቹ ከወደፊት የሙዚቃ ተስፋዎቹ ከሚካኤል ለማ ደምሰው፣ ከየማርያም ቸርነት (የሚ)፣ ከማኅሌት ነጋሽ ፣ ከማስተዋል ዕያዩ እና ከይድነቃቸው ገለታ ጋር በአንድነት “ቅኔ ነው ሀገር” የተሰኘ ድንቅ ኅብረ ዝማሬ አቅርበዋል።

    ድርሰት፣ ቀረፃ፣ ቅንብር፣ ፕሮዳክሽን እና ዳይሬክቲንግ በያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት መምህሩ በወጣቱ ድንቅ ሙዚቀኛ በኢዩኤል መንግሥቱ ውብ ሆኖ ተሰናድቷል።

    የሙዚቃው የድምጽ ውኅደት በታላቁ ሙዚቀኛ በአበጋሱ ክብረወርቅ ሺዎታ ተከውኗል።

    በሙዚቃ መሣሪያ ተጫዋችነት፥ ዶ/ር ዕዝራ አባተ፣ ረ/ፕ ኃይሉ ዓለማየሁ፣ የያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ዳይሬክተር ሰላማዊት አራጋው፣ ታዋቂው ሳክስፎኒስት አክሊሉ ወልደ ዮሐንስ (ጆኒ)፣ ኤፍሬም ውብሸት፣ ዳዊት ፍሬው ኃይሉ፣ ኢዩኤል መንግሥቱ፣ ለታሪክ ጥላሁን ፣ ሚሊዮን አብርሀም፣ ቴዎድሮስ አበራ፣ ዳዊት ቦስኮ እና ሌሎች በርካታ የሙዚቃ መሣሪያ ተጫዋቾች በሥራው ላይ ግሩም አጨዋወት ተሳትፈዋል።

    ሀገር ሰምና ወርቅ ያላት ቅኔ ናት። የቅኔዋን “ወርቅ” የምናገኘው፣ “ሰው በሌለበት ሰው ሆነን ስንገኝ ነው፤” ሰውነት፣ ሀገር መውደድ፣ ሰው ሆኖ መገኘት… የዘመናችን እና የወቅቱ ትልቅ “የመሆን አለመሆን” (to be or not to be) ‘ሐምሌታዊ’ (ሼክስፒሪያን) ጥያቄ ስለመሆኑ ኅብረ ዝማሬው ይነግረናል።

    ይህን ምርጥ የትብብር ውጤት የሆነውን ሙዚቃ ለማድመጥ/ ለመመልከት (ምነው ሸዋ ቲዩብ) እዚህ ጋር ይጫኑ

    ሠርፀ ፍሬስብሐት እንደጻፈው

    ቅኔ ነው ሀገር

    Anonymous
    Inactive

    የፖሊስ የዘፈቀደ እስር በአስቸኳይ ሊቆም እና የታሰሩትም ሊለቀቁ ይገባል
    Police Should Immediately Stop Arbitrary Arrests and Release those Detained

    አዲስ አበባ (የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን) – [በትላንትናው ዕለት (ግንቦት 5 ቀን 2012 ዓ.ም.)] በአዲስ አበባ ከተማ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ሳያደርጉ የተገኙ ሰዎች በፖሊስ እየታሰሩ ከመሆናቸው ጋር በተያያዘ በሚዲያዎች የወጡ ዘገባዎችንና ለኮሚሽኑ የቀረቡ አቤቱታዎችን ተከትሎ የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ የሚከተለውን ብለዋል።

    የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ የኮቪድ 19 ስርጭትን ለመከላከል አስፈላጊ የጤና መመርያ ሲሆን ሕብረተሰቡም ሊከተለው የሚገባ ነው። በእርግጥም የአስቸኳይ ጊዜ ደንቡ ማንኛውም ሰው እንደ ገበያ ቦታዎች፥ ሱቆች ፣ የትራንስፖርት አገልግሎቶች ባሉ የሕዝብ አገልግሎት መስጫ ቦታዎች እና በሌሎች ሕዝብ በሚበዛባቸውና የአካል መራራቅን መጠበቅ በማይቻልባቸው አካባቢዎች የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ማድረግ እንዳለበት ይደነግጋል። ከዚህ ውጪ ግን በየትኛውም ቦታ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ሳያደርጉ የተገኙ ሰዎች ላይ ሁሉ የሚደረግ የዘፈቀደ እስር ከሕግ ውጭ ከመሆኑም በላይ ለነገሩ ሁኔታ ተመጣጣኝ ያልሆነ እርምጃ እና የታለመለትን አላማ የሚቃረን በመሆኑ በአስቸኳይ ሊቆም ይገባል፤ በዚህ ሁኔታ የታሰሩ ሰዎችም በአስቸኳይ ሊፈቱ ይገባል።

    [የኮሮናቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝ ስርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠርና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ በመጋቢት ወር 20212 ዓ.ም. የወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማስፈፀሚያ ደንብን የፌዴራል ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ሚያዝያ 3 ቀን 2012 ዓ.ም. ይፋ ማድረጉ ይታወሳል። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም ከሚያዝያ ወር ጀምሮ ለአምስት ወራት ተግባራዊ እየሆነ እንደሚቆይ ተነግሯል።]

    ADDIS ABABA (Ethiopian Human Rights Commission) – Responding to media reports and complaints of arrests by police in the city of Addis Ababa on 13th May 2020 for not wearing face masks, Chief Commissioner of the Ethiopian Human Rights Commission (EHRC) Dr. Daniel Bekele said:

    Covering nose and mouth are recommended health measures to prevent the spread of COVID-19 and the public needs to follow these critical health directives. Indeed, the Emergency Regulations impose an obligation to wear face covering in public service areas such as markets, shops, transport services or other public spaces with large number of people where social distancing is not possible. Otherwise, arbitrary arrest of people on the streets is outside the regulation, disproportionate and counter-productive measure which should stop immediately and all those detained should be released immediately.

    [In the first week of April 2020, Ethiopia has declared a state of emergency in the country to help curb the spread of the coronavirus pandemic. The state of emergency is reported to stay in action for five months from its declaration.]

    Semonegna.com

    የፖሊስ የዘፈቀደ እስር በአስቸኳይ ሊቆም ይገባል

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ ኤጀንሲ ለ18 ወራት የሚበቃ የመድኃኒት ክምችት መኖሩን ገለጸ
    ለለይቶ ማቆያዎች የሕክምና ቁሳቁሶች ተሟልቶ እየቀረበ እንደሚገኝ ተጠቁሟል

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ ኤጀንሲ ለ18 ወራት የሚበቃ የመድኃኒት ክምችት ለመያዝ እየሠራ መሆኑ ተገለጸ። በፌደራልና በክልል ደረጃ ለሚገኙ ለይቶ ማቆያዎች የሕክምና ቁሳቁሶች ተሟልቶ እየቀረበላቸው እንደሚገኝም ተጠቁሟል።

    በኤጀንሲው የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር ወ/ሮ አድና በሬ በተለይ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለጹት፥ ኤጀንሲው በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ሳቢያ በሀገሪቱ የመድኃኒት አቅርቦት እጥረት እንዳይከሰት ከወዲሁ ለ18 ወራት የሚበቃ የመድኃኒት ክምችት ለመያዝ እየሠራ ይገኛል።

    እንደ ዳይሬክተሯ ማብራሪያ፤ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነው የመድኃኒት አቅርቦት ከውጭ የሚገባ በመሆኑ በሀገሪቱ የመድኃኒት አቅርቦት እጥረት አንዴ ከተከሰተ የአቅርቦት ሰንሰለቱን ለመመለስ ጊዜ ስለሚወስድ ችግሩን በፍጥነት ለመቅረፍ አዳጋች ያደርገዋል። ኤጀንሲው ችግሩን ከግምት ውስጥ በማስገባት ቫይረሱ ወደ ሀገሪቱ ቢገባ በመድኃኒት አቅርቦቱ ላይ ሊያሳድር የሚችለውን ተጽኖ ታሳቢ በማድረግ፥ ኮሚቴ ተቋቁሞ በመጋዘን ምን ያህል የመድኃኒት ክምችት እንዳለ፤ ከወርሃዊ ፍጆታው አንጻር በመጋዘንና በመጓጓዝ ላይ ያለው መድኃኒት ለምን ያህል ጊዜ እንደሚበቃ፣ መጠናቸውን፣ የትኛው መድኃኒት ቀድሞ መግባት እንዳለበት፣ እስከ መቼ መድኃኒቶቹ ወደ አገር ውስጥ ሊገቡ እንደሚችሉ ቀደም ብሎ ጥናት ተደርጓል።

    ወ/ሮ አድና ኮሚቴው ቫይረሱ በሀገሪቱ ከተከሰተ በኋላም ከተመላላሽ ታካሚዎች ባሻገር በተለይ ተከታታይ መድኃኒት የሚወስዱ ወገኖች እጥረት እንዳያጋጥማቸው፣ በመጋዘንና በመጓጓዝ ላይ ያለው መድኃኒት ለነዚህ ወገኖች አቅርቦት ሳይቆራረጥ ምን ያህል ጊዜ ሊያስኬድ ይችላል የሚለው ላይም በድጋሚ ጥናት ማካሄዱን ተናግረዋል።

    ኤጀንሲው በጥናቱ መሠረት የመድኃኒቶቹን የአገልግሎት ዕድሜ ታሳቢ በማድረግ ለ18 ወራት የሚበቃ የመድኃኒት ክምችት ለመያዝ እየሠራ እንደሚገኝ ገልጸው፥ በተለይ የስኳር፣ የደም ግፊት፣ የአስም፣ የልብ ህመምተኞች በተከታታይ ከሚወስዷቸው መድኃኒቶች በተጨማሪ ኤችአይቪ (HIV) በደማቸው የሚገኝባቸው ወገኖች የሚወስዷቸው የፕሮግራም መድኃኒቶችን ለ18 ወራት የሚበቃ ክምችት ለመያዝ ታሳቢ ተደርጎ ግዢ እንዲፈጸም፣ በመጓጓዝ ላይ ያሉት በወቅቱ እንዲገቡና በመጋዘን ተከማችተው ያሉ መድኃኒቶችም በወቅቱ ወደ ጤና ተቋማቱ ተልከው ለህመምተኞች እንዲደርስ የማድረግ ሥራ እየተሠራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

    ወ/ሮ አድና የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በጤና ቀውስነቱ እስከመቼ ድረስ እንደሚቀጥል ስለማይታወቅ የመድኃኒት አቅርቦት እጥረቱ ተከስቶ ችግር ውስጥ ከመገባቱ በፊት የመድኃኒት ክምችቱን ማሳደግ ላይ መሠራቱ ዘርፈ ብዙ ጥቅም እንዳለው ጠቁመው፥ ቀደም ሲል በውል የታሰሩ የመድኃኒት ግዢዎች በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ዋጋ ከመጨመር ባለፈ በውሉ መሠረት ድርጅቶቹ ለማቅረብ እያመነቱ በመሆኑ በተፈለገው መጠን መድኃኒቶቹን ለማከማቸት እንቅፋት ሊፈጥር እንደሚችል ተናግረዋል።

    በተያያዘ ዜና የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ ኤጀንሲ የኮሮና ቫይረስ በሀገሪቱ ከተከሰተ ጊዜ ጀምሮ ወረርሽኙን ለመከላከል የሚያስችሉ የሕክምና ግብዓቶችን እያሠራጨ እንደሚገኝ ዳይሬክተሯ ገልጸው፥ ኤጀንሲው የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በሚያቀርበው ጥያቄ መሠረት በፌዴራልና በክልል ደረጃ ለሚገኙ ለይቶ ማቆያዎች ሙሉ ለሙሉ የሕክምና ቁሳቁሶችን አሟልቶ እያቀረበ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ ኤጀንሲ Ethiopian Pharmaceuticals Supply Agency EPSA

    Anonymous
    Inactive

    “ሕግ አክባሪው የትግራይ ሕዝብ፣ የህወሓትን ውሳኔ አይቀበለውም” ― አቶ ነብዩ ስሁልሚካኤል የትግራይ ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – ህወሓት የዘንድሮውን ምርጫ በክልል ደረጃ አካሂዳለሁ ብሎ ያወጣው መግለጫ ሕገ መንግሥቱን የሚጣረስ በመሆኑ ሕግ አክባሪው የትግራይ ሕዝብ በምንም መልኩ የማይቀበለው መሆኑን የትግራይ ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ነብዩ ስሁልሚካኤል አስታወቁ።

    የትግራይ ብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ነብዩ ስሁልሚካኤል ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንዳስታወቁት፥ ምርጫ የማካሄድ ሥልጣን ያለው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሆኖ ሳለ ህወሓት በክልል ደረጃ ምርጫ አካሂዳለሁ ማለቱ የሕገ መንግሥቱን ድንጋጌ የሚጥስ ከመሆኑም ባለፈ ሕግ አክባሪው የትግራይን ሕዝብ የማይመጥ ነው። ሕዝቡ ይህንን ሕገ መንግሥቱን የሚንድ ተግባር አይቀበልም።

    «የህወሓት መግለጫው ከሕገ መንግሥት ያፈነገጠ ብቻ ሳይሆን የምርጫ ቦርድ ኃላፊነትን የዘነጋና አልፎ ተርፎም እውቅና መስጠት ያልፈለገ መግለጫ ነው» ያሉት አቶ ነብዩ፥ ይህም ሕገ መንግሥትና አገርን መናድ በመሆኑ በወንጀል ሕጉ የሚያስጠይቅ መሆኑንን አስገንዝበዋል።

    የትግራይን ሕዝብ አስተዳድራለሁ የሚለው ህወሓት እያደረገ ያለው ተግባር ይህንን ጨዋ ሕዝብ ደረጃ የማይመጥንና የሥልጣንን ጥማትን ለማርካትና ወንበርን ለመጠበቅ ብቻ የሚሄድበት መንገድ ነው ሲሉም ተናግረዋል።

    በአሁኑ ወቅት ትግራይ ውስጥ ሥርዓት አለ ለማለት በጣም አስቸጋሪ መሆኑን የጠቀሱት ኃላፊው፥ በክልሉ ምርጫ ለማካሄድ በሚል ዝግ የሆኑ የካድሬዎች ስብሰባ እየተካሄዱ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ይህም ደግሞ በክልልም ሆነ በአገር ደረጃ የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሚጥስ መሆኑን አመልክተዋል። “ይህም የሚያሳየው ራሳቸው ላወጁት አዋጅ እንኳን ተገዢ አለመሆናቸውን ነው” ብለዋል።

    በሌላ በኩል እንደ አገር የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መጥቶ እያለ፤ በቫይረሱ የተየዙ ሰዎችን ውጤት እንደ አገር መረጃ እየተላለፈ ባለበት ሁኔታ የክልሉ ጤና ቢሮ በተናጠል መረጃ ማውጣቱ የህወሓትን አመራሮች ምን ያህል ለሕዝብም ሆነ ለአገር ደኅንነት የማያስቡ መሆናቸውን እንደሚያመላክት አስረድተዋል። “የትግራይ ሕዝብ እንዲህ ዓይነት የመንግሥት አገልግሎት አይመጥነውም፤ አይገባውምም” ብለዋል። በአሁኑ ወቅት ሕዝቡ በማኅበራዊ ሚዲያና በሌሎች መንገዶች የህወሓትን ተግባር እየኮነነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።

    መንግሥትን የሚመራው ብልጽግና ፓርቲ የምርጫ ጊዜው ከማራዘም ባለፈ የሕዝብና የአገር ግዛት አንድነትን እንዲሁም ሕገ መንግሥቱን የማስጠበቅ ኃላፊነት እንዳለበት አስታውሰው፤ ሕገ መንግሥቱን ለመናድና በአቋራጭ ወደ ሥልጣን ለመምጣት ብሎም አገር የሚበጠብጡ አካላትን ሕግን መሠረት በማድረግ እርምት የሚወሰድባቸው መሆኑን አስታውቀዋል። “የአገርና የሕዝብን ደኅንነትን በማስቀደም ሕጋዊና ተመጣጣኝ እርምጃ ይወስዳል” ብለዋል።

    ምንጭ፦ አዲስ ዘመን / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የትግራይ ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ነብዩ ስሁልሚካኤል Nebiyu Sihul Mikael

    Anonymous
    Inactive

    የጤና ሳይንስ ምሩቃን በሀገር ውስጥ ተወዳዳሪ እንዲሆኑና ከሀገር ውጭ ሲወጡ ደግሞ በተማሩበት የሙያ መስክ ጥራት ያለውን ሥራ መሥራት እንዲችሉ የሚያበቃ የሥርዓተ ትምህርት ክለሳና የስልጠና ፕሮግራም ደረጃ ማሳደግ እንደሚገባ ተጠቁሟል።

    በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሰጡ የጤና ሳይንስ ትምህርቶችን ጥራት ለማሳደግ የሚያስችል ውይይት ተካሄደ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር Jhpiego ከተሰኘ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት ጋር የጤና የሰው ኃይል ልማት ማሻሻያ ፕሮግራም (Health Workforce Improvement Program /HWIP/) ላይ የቪዲዮ ውይይት (webinar) አድርጓል።

    በውይይቱ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ በሀገራችን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በጤና ሳይንስ የሚመረቁ ምሁራን በሀገር ውስጥ ተወዳዳሪ እንዲሆኑና ከሀገር ውጭ ሲወጡ ደግሞ በተማሩበት የሙያ መስክ ጥራት ያለውን ሥራ መሥራት እንዲችሉ የሚያበቃ የሥርዓተ ትምህርት ክለሳና የስልጠና ፕሮግራም ደረጃ ማሳደግ ይገባል ብለዋል።

    ለዚህም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የትምህርት ጥራት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ገልጸው እንዲህ ዓይነት መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እገዛም አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመዋል። በጤና ዘርፍ በየዓመቱ መሰልጠን ያለባቸውን ቁጥር አጥንቶ መመጠን፣ ኢ-ለርኒንግን (e-learning) ማጠናከር፣ የትምህርት መርሃግብሮች ዕውቅና አሰጣጥ (programs accreditation) ላይ መሥራት፣ የመርሃግብር ደረጃ ማውጣትና ተግባራዊ ማድረግ ከዩኒቨርሲቲዎች ይጠበቃል ብለዋል።

    የተወሰኑ ዩኒቨርሲቲዎች የራሳቸው ሆስፒታል እና የጤና ማዕከላት ሲኖራቸው የሌላቸው ደግሞ ተማሪዎቻቸውን በአከባቢያቸው ከሚገኙ የጤና ማዕከላት ጋር በመቀናጀት ያሰለጥናሉ ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፥ ስለሆነም በጤና ዘርፍ ያሉ አመራሮችን፣ መምህራንን እና የጤና ባለሙያዎችን አቅም መገንባትና ግብዓት ማሟላት ለጥራት የራሱ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመዋል።

    ፕሮጀክቱ የ5 ዓመት መሆኑን እና በጤና ዘርፍ የሚወጡ ተማሪዎች ጥራት እንዲኖራቸው መሥራትና፣ ለጤና ዘርፍ ትምህርት ጥራት የሚያስፈልጉ አስፈላጊ ግብዓቶችንና ቴክኒካዊ ምክረሃሳቦችን በማቅረብ ተግባራዊ እንዲረግ መሥራት ዋና ዓላማቸው መሆኑን የገለፁት የJhpiego ዳይሬክተር ዶ/ር ተግባር ይግዛው የጤና ሳይንስ ትምህርትን ጥራትን ለመደገፍ እንደሚሠሩ ገልጸዋል።

    የ39.5 ሚሊየን ዶላር ፕሮጀክቱን ተግባዊ ለማድረግም በጤና ትምህርት ዘርፍ በሚደረጉ ድጋፎች ላይ ከሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር መሥራት እንደሚፈልጉ ገልጸዋል። በተለይ ለጾታ እኩልነት ቦታ እንደሚሰጡም ጠቁመዋል።

    ዶ/ር ተግባር ፕሮጀክቱ በኢትዮጵያ የጤና ዘርፍ ውስጥ የሚከሰቱትን ወሳኝ የሰው ኃይል ችግሮች ለመቅረፍ የሚያስችሉ መንገዶችን ለማመቻቸት ከጤና ሚኒስቴር ጋር በትብብር ስምምነት የሚሠራ መሆኑን ገልጸው፥ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እና ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ተባብሮ በመሥራትም የኢትዮጵያን የጤና ባለሙያዎች ጥራት፣ የአገልግሎት አሰጣጥና ብቃት ለማሻሻል እና የጤና የሰው ኃይል አስተዳዳሪዎች ችሎታን ለመገንባት በተቋም እና ግለሰቦች አቅም ግንባታ ላይ ትኩረት አድርጎ ይሠራል ብለዋል።

    በውይይቱ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ቅድሚያ ተሰጥቶ ቢሠራበት የሚሏቸውን ሀሳቦች አንስተዋል። በዚህም በሚኒስቴሩ በኩል ከድርጅቱ ጋር በጋራ የሚሠራባቸው መስኮች ተለይተው እና የትግበራ ዕቅድ አውጥተው ወደሥራ እንደሚገቡ ተጠቁሟል።

    በውይይቱ ዩኒቨርሲቲዎችን ዓለምአቀፋዊ ማድረግ ላይ የሚሠራውን ሥራ ለማገዝ ዕውቅና መስጠት (accreditation) መጀመር እንዳለበትና በተለይ የሕክምና ትምህርት ላይ ቀድሞ መጀመር ጥቅሙ ከፍተኛ መሆኑም ተመላክቷል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የጤና ሳይንስ ትምህርት

    Anonymous
    Inactive

    ቀጣዩ ሀገራዊ ምርጫን በተመለከተ ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ የሰጠው ወቅታዊ የአቋም መግለጫ
    የባለሙያዎቹ የባለአደራ መንግሥት (Caretaker Government of Technocrats) ይቋቋም!

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ወደ ተሻለ የዴሞክራሲ ሥርዓት የምትሸጋገረውና መጪው ምርጫ ብሩህ ተስፋ የያዘ የሚሆነው አሳታፊ፣ ሁሉን አቀፍ ሀገራዊ ጉባዔ በማድረግ ብቻ ነው። ጉባዔው በአንድ በኩል ሀገራችን ያንዣበበባትን የኮሮና ወረርሽኝን እንዴት ልታልፍ እንደምትችል ምክክር እንዲደረግ የሚያስችል ሲሆን፣ በሌላ በኩል ቀጣዩ ምርጫ መቼ ይሁን? በምን ቅርጽ ይካሄድ? እስከ ምርጫው ድረስ ሀገራችንን ማንና እንዴት ይምራት? ለሚሉት አንገብጋቢ ጥያቄዎች ምላሽ የሚገኝበት መድረክም ነው። ይህን ዓይነቱን ጉባዔ ፍሬያማ ለማድረግ በሀገሪቱ የሚንቀሳቀሱ ዋና ዋና የፖለቲካና የሲቪክ ባለድርሻዎች እንዲሳተፉበት ማድረግ የግድ ይላል።

    ይሁን እንጂ፣ ገዢው ፓርቲ እንደዚህ ዓይነቱ ሀገራዊ ጉባዔ እንዲደረግ ሁኔታዎችን ከማመቻቸት ይልቅ፥ በሀገራችን ውስጥ ተፅዕኖ ያላቸውን የፖለቲካ ድርጅቶች በማግለል የተወሰኑ የፖለቲካ ድርጀቶችን ብቻ መርጦ ስብሰባ አድርጓል። በዚህ ሂደት ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲን ጨምሮ፣ ሌሎች ለገዢው ፓርቲ ብርቱ ተፎካካሪ የሆኑ የፖለቲካ ድርጅቶች እንዳይሳተፉ አድርጎ፣ ቅንነትና ታማኝነት የጎደለው፣ ጠቃሚ ሃሳቦች በተሟላ መልኩ ያልተንሸራሸሩበት፣ ለሃቀኛ ሽግግር ያልቆረጠ ስብሰባ እንዲሆን አድርጎታል።

    በዚህም ሳቢያ በሀገራችን መጻኢ ዕድል ላይ ጥቁር ዳመና እንዲያንዣብብ እየሆነ ነው። ኢትዮጵያን ወደ ሚቀጥለው የተሻለ ደረጃ ከማስፈንጠር አንፃር ማንም ልጅ፣ ማንም የእንጀራ ልጅ ስላልሆነ፣ የማግለል አካሄድ ለሀገራችን ስለማይበጅ በአፋጣኝ ሊቆም ይገባል።

    በኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት የመንግሥት የሥራ ዘመን 5 ዓመት ብቻ እንደሆነና፣ የስልጣን ዘመኑ ከማለቁ ከወራት በፊት [ብሔራዊ] ምርጫ መደረግ እንዳለበት የደነገገ ቢሆንም፥ በበሽታ፣ በጦርነት፣ በተፈጥሮ አደጋ ወይም በሌላ እክል ምርጫውን ማካሄድ ሳይቻል ቢቀር ምን መደረግ እንዳለበት ምንም መፍትሄ አላስቀመጠም። ይህም አሁን ባለው የኮሮና ወረርሽኝ ሳቢያ ምርጫን በተመለከተ ትልቅ ሀገራዊ ተግዳሮት ፈጥሯል።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ በሚያዝያ 24 እና 25 ቀን 2012 ዓ·ም. ባደረገው አስቸኳይ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ስብሰባ፣ የምርጫውን መራዘም አስመልክቶ ገዢው ፓርቲ አግላይ በሆነው ስብሰባ ያቀረባቸውን 4 አማራጮች በጥልቀት ከሕግና ከፖለቲካ አግባብነት አንፃር እያየ መርምሯል።

    ኮሚቴው በገዢው ፓርቲ የቀረቡት አማራጮች ሀገሪቷን ከተጋረጡባት ተግዳሮቶች የማይታደጓት ብቻ ሳይሆኑ፣ በከፊል ሕጋዊ መሠረትም የሌላቸው መሆኑንም ተገንዝቧል። ስለሆነም፣ አማራጭ ሀገራዊ መፍትሄ ለማስቀመጥ ውይይትና ክርክር ከማድረጉ በፊት አራት መስፈርቶች እንደ ቅድመ-ሁኔታ አስቀምጧል። እነዚህም፡-

    1. የኢትዮጵያን ሀገራዊ አንድነት፣ ሠላምና ደኅንነት የሚያስቀጥል መሆን እንዳለበት፣
    2. መፍትሔው ሀገራዊ ተግዳሮቱን እንደ ክፍተት በመጠቀም የማንንም የስልጣን ጥም እውን ለማድረግና ለማስፈፀም መዋል እንደሌለበት፣
    3. ለዴሞክራሲያዊ ሽግግርና ሥርዓት ግንባታ እንቅፋት መሆን እንደሌለበት፣
    4. የባልደራስን ጨምሮ ከማንኛቸውንም የፖለቲካ ድርጅት ፍላጎትና አመለካከት የፀዳ መሆን እንዳለበት፣
    5. ለመሰል ሀገራዊ ተግዳሮት ዓለም-አቀፍ ተሞክሮ ግምት ውስጥ መግባት እንዳለበት የሚሉት ናቸው።

    እነዚህን መስፈርቶች መመዘኛ አድርጎም፣ በገዢው ፓርቲ በኩል የቀረቡት «አማራጮች»ም ሆኑ በተቃራኒው ኢትዮጵያን ማፍረስ የሚሹ ኃይሎች የተሰባሰቡበት ያቀረቡት «የሽግግር መንግሥት እንመሥርት» ጥያቄ ለሀገሪቱ እንደማይበጁ ጥርት አድርጎ ማየት ችሏል።

    በአንጻሩ በአውሮፓ፣ በእስያ፣ በላቲን አሜሪካና በአፍሪካ ያሉትን መሰል ተሞክሮዎች ግምት ውስጥ ሲገቡ፣ ከመስከረም 30 ቀን 2013 ዓ.ም. በኋላ ለኢትዮጵያ የሚበጃት «የባለሙያዎች የባለአደራ መንግሥት» ወይም በእንግሊዘኛ አጠራሩ “Caretaker Government of Technocrats” ነው ብሎ በፅኑ አምኗል።

    ይህ የባለሙያዎች የባለአደራ መንግሥት ከየዘርፉ በሚመለመሉ ምሁራንና ባለሙያዎች የሚቋቋም ሲሆን፣ አዋጪነቱም ተፈትኖ የታየ ብቻ ሳይሆን፣ ገዢው ፓርቲም ይሁን ተቃዋሚ ፓርቲዋች ሀገራዊ ተግዳሮቱን በመጠቀም ለስልጣን ሽሚያ እንዳይጋበዙና ሀገር እንዳትጎዳ ዋስትና ይሰጣል።

    የባለሙያዎቹ የባለአደራ መንግሥት፡-

    1ኛ. የባለሙያዎቹ የባለአደራ መንግሥት በሕይወት ዘመናቸው የፖለቲካ ድርጅት አባላት ባልነበሩ ምሁራንና ባለሙያዎች የሚቋቋም ይሆናል፣
    2ኛ. የባለሙያዎቹ የባለአደራ መንግሥት አባላትና ሹመኞች በቀጣይ በሚደረገው ምርጫ ውስጥ ምንም ዓይነት ተሳትፎ እንዳይኖራቸው ገደብ የሚጣልባቸው ይሆናል፣
    3ኛ. የባለሙያዎቹ የባለአደራ መንግሥት አባላትና ሹመኞች ከምርጫ በኃላ በሚቋቋመው መንግሥት የፖለቲካ ሹመት እንዳይሰጣቸው የአንድ የምርጫ ዘመን ገደብ የሚጣልባቸው ይሆናል፣
    4ኛ. የባለሙያዎቹ የባለአደራ መንግሥት አባላት በፖለቲካ፣ በሲቪክ ባለድርሻ አካላት ተሳትፎና በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ታዛቢነት የሚመረጡ ይሆናል፣
    5ኛ. የባለሙያዎቹ የባለአደራ መንግሥት አባላት ከሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ ካሉ ኢትዮጵያውያን ምሁራን መካከል ይመረጣሉ፣

    የባለሙያዎቹ የባለአደራ መንግሥት ኃላፊነት፡-

    1. የሀገር ሉዓላዊነትን መጠበቅ፣
    2. የሀገር ጸጥታን ለማስጠበቅ ሕግና ሥርዓትን ማስከበር፣
    3. ለነጻ ምርጫ የሚያስፈልጉ ነጻ የመንግሥት ተቋማትን መገንባት፣
    4. የመንግሥትን የዕለት ተዕለት ሥራ መምራት፣
    5. ከምርጫው በፊት፣ ለሀገራዊ እርቅና መግባባት ሁሉም የፖለቲካ ድርጅቶች የሰላም ቃል ኪዳን እንዲያደርጉ ሁኔታዎችን ማመቻቸት፣
    6. ኢትዮጵያዊያን ሀገራዊ ቃል ኪዳን (citizen’s covenant) እንዲገቡ ሁኔታዎችን ማመቻቸት፣
    7. የባለሙያዎቹ የባለአደራ መንግሥት የሥራ ዘመን ከሁለት ዓመት ያልበለጠ ይሆናል።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ
    ሚያዚያ 26ቀን 2012 ዓ·ም.
    አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ!

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ

    Anonymous
    Inactive

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ብሔራዊ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ መግለጫ

    ለመላው የአማራ ሕዝብ፣
    ለድርጅታችን አባላትና ደጋፊዎች፣
    ለመላው ኢትዮጵያውያን!

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ብሔራዊ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ሚያዝያ 26 እና 27 ቀን 2012 ዓ.ም. ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ የሀገራችንን ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊና ምጣኔ ሀብታዊ አውዶችን በጥልቀት በመገምገም፤ የአማራ ሕዝብን ወቅታዊ አቋምና ዘላቂ ጥቅሞችን፤ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶችና ኃይሎች ፍላጎቶችን እና የቀረቡ አማራጮችን በፅሞና በመመርመር፤ በዚህም መሠረት፦

    • ለሰላማዊና ጠንካራ ሀገራትና መንግሥታት እንኳን የሚያዳግቱ ግዙፍና አሳሳቢ ብሔራዊ ተግዳሮቶች የተደቀኑብን መሆኑን በማመን፤
    • የዴሞክራሲያዊ ውድድር፣ የልሂቃን ውይይትና ድርድር ባህል ባልዳበረበት በጥልቅ በተከፋፈለ ብሔራዊ ማኅበረሰብ ውስጥ እንደምንገኝ በመገንዘብ፤
    • የኢትዮጵያ ቀጣይ ሁኔታ በምርጫ ወይም በይስሙላ ማሻሻያዎች ብቻ እንደማይወሰን፣ የአሸናፊዎችና የጉልበተኞች ጫናም ዘላቂ ሰላም እንደማያመጣ በማመን፤
    • ከምንም ከማንም በላይ የአማራን ሕዝብ ሰላም፣ ደኅንነትና ዘላቂ ጥቅሞች መከበርና የሀገራችንን ህልውና ቀጣይነት በማስቀደም፤

    አብን እነዚህንና ሌሎችንም ተጓዳኝ ታሳቢዎችን በማድረግ ሀገራችን ከገባችበት አጣብቂኝ በአስተማማኝ ልትወጣ የምትችልባቸውን መንገዶች በተመለከተ የሚከተሉትን አቋሞች ወስዷል።

    1ኛ. የሽግግር ጊዜ (transitional period) አስፈላጊነት
    ንቅናቄያችን አብን ሌሎች በሀገራችን የሚገኙ የፖለቲካ ድርጅቶችና ተቋማት ላቀረቧቸው አማራጭ ሃሳቦች ክብር ያለው ቢሆንም አሁን ለገባንበት ፖለቲካዊ ቀውስ አዲስ የሽግግር መንግሥት (transitional government) መፍትሄ ይሆናል የሚል እምነት የለውም።

    ከዚህ ይልቅ የተወሰነ የሽግግር ጊዜ መፍጠር የተሻለ አማራጭ መሆኑን እንገነዘባለን። ምክንያቱም የሕዝባችንና የሀገራችን ዕጣፈንታ በአስተማማኝ መሠረት ላይ እንዲቆም ሁኔታዎችን በማመቻቸት፣ ነባራዊ ውጥረቶችና ክፍተቶች እንዲረግቡና የጥሞናና ውይይት መንፈስ እንዲሰፍን ያስችላል። የሽግግር ጊዜ ያላሰለሰ ሕዝባዊ ውይይት፣ ልሂቃዊ ምክክርና ድርድር እንዲደረግና ሊያሠራ የሚችል ብሔራዊ መግባባት እንዲፈጠር ዕድል ይሰጣል።

    2ኛ. የመንግሥት-መር (state-led) ሽግግር አስፈላጊነት
    አብን ከገባንበት ብሔራዊ አጣብቂኝ ለመውጣት የሀገርን ሉዓላዊነት፣ የዜጎችን ሰላምና ደኅንነት፣ የሕግን የበላይነት በማስከበር ረገድ ኃላፊነቱን በብቃት የሚወጣ አካል መኖር እንዳለበት ያምናል። አዲስ የሽግግር መንግሥት መፍጠር በሀገራችን ወቅታዊ የፖለቲካና የኃይል አሰላለፍ አውድ ሊሳካ እንደማይችል ይገነዘባል።

    ስለዚህም ምንም እንኳን ላለፉት ሁለት ዓመታት ገደማ የታየው መንግሥት መሩ የለውጥ ሂደት የከሸፈና የማያሰራ እንደነበር ብንረዳም፣ ምርጫው እስኪካሄድ ድረስ በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት መቆየትና የሽግግር ሂደቱን መምራት ለሕዝባችንና ሀገራችን ሰላምና ደህንነት ካሉት አማራጮች በአንፃራዊነት የተሻለው ነው ብለን እናምናለን።

    3ኛ. የመዋቅራዊና ሁሉን አካታች ሽግግር ሂደት አስፈላጊነት
    አብን የአማራ ሕዝብና የሌሎች ወንድም ህዝቦች መሠረታዊ ጥያቄዎች ሥርዓታዊና መዋቅራዊ በመሆናቸው በዋነኝነት የሚፈቱት በልሂቃን መካከል በሚደረግ ውይይትና ድርድር ከሚመነጭ ፖለቲካዊ መፍትሄ መሆኑን ያምናል።

    ብሔራዊ ፖለቲካችን ከጥሬ የስልጣን ትግል ወደ ዘላቂ ሰላም እንዲሻገር ከታሰበ ከአጭር ፖለቲካዊ ትርፍ ይልቅ ዘላቂ የሀገርና የሕዝብ ጥቅምን ያማከለና አዲስ ቅርፅና አቅጣጫ ያለው ሰፊና የማያቋርጥ የድርድርና እርቅ ሂደት ያስፈልጋል። በተለይም የሀገሪቱን ሕገ-መንግሥት ማሻሻል፣ አጠቃላይ መዋቅራዊና ተቋማዊ ለውጦችን ማድረግ ያሻል። ከሁሉም በላይ በአሳሳቢ ሁኔታ እየወደቀ የመጣውን ምጣኔ ሀብታችንን እንዲያንሰራራ ማድረግ የግድ ነው። ለዚህም ተፎካካሪ ፓርቲዎችን፣ ሲቪክ ማኅበራትንና ሌሎችንም ባለድርሻ አካላትን ያካተተና ለሕዝብ ተወካዮች ተጠሪ የሆነ የብሔራዊ ውይይት ኮሚሽን እንዲቋቋም ድርጅታችን አብን ይጠይቃል።

    4ኛ. መሠረታዊ የሕዝባችንን ጥያቄዎች በተመለከተ

      • ሀ. የኮቪድ-19 ወረርሽኙ በቁጥጥር ስር ከዋለ በኋላ አሁን በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ምርጫ ከመካሄዱ አስቀድሞ በመሠረታዊ የሕዝቦች ጥያቄዎች ላይ ቅርፅ ያለውና ተቋማዊ የሆነ ብሔራዊ ውይይት (national dialogue) እንዲጀመር ለማድረግ ዋስትና እንዲሰጥ ንቅናቄያችን አበክሮ ይጠይቃል።
      • ለ. የሕዝብና ቤት ቆጠራን በተመለከተ፣ ንቅናቄያችን የ1999 ዓ.ም. ብሔራዊ የሕዝብና ቤት ቆጠራ ሳይንሳዊ ያልሆነና ሸፍጥ የተሞላብት የሕዝባችንን ቁጥር በእጅጉ የቀነሰ በዚህም ፖለቲካዊ ውክልናውን እና ምጣኔ ሀብታዊ ተጠቃሚነቱን ያሳጣ በመሆኑ ውጤቱ ሙሉ በሙሉ እንዲሰረዝ፤ ለተከሰቱት ጉዳቶች ፍትኃዊ ማካካሻ (restorative justice) እንዲደረግና ቀጣዩም ቆጠራ ሳይንሳዊና ገለልተኛ በሆነ ተቋም እንዲካሄድ ይጠይቃል።
      • ሐ. የሕገ መንግሥት ማሻሻያን በተመለከተ፤ አሁን ያለው ሕገ መንግሥት ሕዝባችንን የማይወክልና በሂደትም ቅቡልነትን ያላተረፈ፣ በአማራ ጠል ትርክት ላይ የተመሠረተ፣ ለሀገር አንድነትና ህልውና የማይበጅ፣ እንደዚህ ያለ ፈታኝ ወቅት ሲያጋጥም እንኳን በአግባቡ ሊያሻግር የማይችል በመሆኑ ከቀጣዩ ምርጫ በፊት የሕገ-መንግሥት ለውጥ ወይም ማሻሻያ እንዲደረግ ይጠይቃል።
      • መ. የሀገራችንንና ሕዝባችንን የሰላምና ደኅንነት ዋስትና በተመለከተ፤ መንግሥት ባለፉት ዓመታት ሕግና ሥርዓት በማስከበር ረገድ ያሳየው ድክመት ተገቢ አለመሆኑንና በፍፁም መቀጠል እንደሌለበት በማመን፤ የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶች ማስከበር ከመንግሥት ግንባር ቀደም ኃላፊነቶች መካከል መሆኑን በመገንዘብ፤ ሀገራችን ባለችበት የስጋት ሁኔታ የዜጎችን ሰላምና ደኅንነት ለማረጋገጥ የተለየ ዝግጁነት እንዲደረግ አበክሮ ይጠይቃል።

    አብን በሕዝባችን ትግል የተሸነፉ ቋሚ የአማራ ሕዝብና የኢትዮጵያ ጠላቶችና ግብረ አበሮቻቸው ሀገራችንን ለማተራመስና እንደገና የጭቆና መንበራቸውን ለመመለስ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ አጥብቆ እንደሚታገለው በአፅንኦት ያረጋግጣል።

    ንቅናቄያችን ከላይ የገለፃቸውን አቋሞች በተመለከተ ከመንግሥትና ከተለያዩ የሀገራችን የፖለቲካ ኃይሎች ጋር ንግግሮችንና ተግባራዊ እንቅስቃሴዎችን እያደረገ መሆኑን እያሳወቀ የተከበረው የአማራ ሕዝብ፣ የድርጅታችን አባላት፣ ደጋፊዎችና መላው ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን በአሁኑ ወቅት የተደቀነብንን ብሔራዊ አደጋ በማጤን ላቀረብናቸው አማራጭ ኃሳቦች ስኬት ከጎናችን እንድትሰለፉ በአክብሮት ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

    አንድ አማራ ለሁሉም አማራ! ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ!
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ብሔራዊ የሥራ ኮሚቴ
    አዲስ አበባ፣ ሸዋ፣ ኢትዮጵያ
    ሚያዝያ 29 ቀን 2012 ዓ.ም.

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)

    Anonymous
    Inactive

    ከአብሮነት ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት (አብሮነት) የተሰጠ መግለጫ
    ስልጣንን በሕገ-ወጥ መንገድ ለማራዘም የሚደረግ ሙከራ በአስቸኳይ ይቁም!

    ሀገራችን በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር ሆና የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ከፍተኛ ጥረት እያደረገች በምትገኝበት በአሁኑ ወቅት ገዥው ብልፅግና ፓርቲ ግን የስልጣን ዘመኑን በሕገ-ወጥ መንገድ ለማራዘም የሚያስችለውን ጥረት ለሕዝብ ይፋ ባልሆነ መንገድ እያደረገ ስለመሆኑ መረጃዎች እየደረሱን ነው። ገዥው ፓርቲ በአገሪቱ ሕገ-መንግሥት ከተሰጠው ስልጣንና መብት ውጭ በሦስት አማራጮች ስልጣኑን ለማራዘም እየሞከረ እንደሚገኝ ታውቋል።
    እነዚህ አማራጮችም፤-

    1. በዓመቱ መጨረሻ ላይ የአገሪቱ ፓርላማ እንዲበተን ማድረግና በ6ወር ጊዜ ውስጥ ሀገራዊ ምርጫ እንዲካሄድ ማድረግ፤
    2. የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን እንደገና በማራዘም የመንግሥትን የሥራ ዘመን ለማራዘም መሞከር፤
    3. የአገሪቱን ሕገ-መንግሥት በማሻሻል የመንግሥትን የሥራ ዘመን ለተወሰነ ጊዜ ማራዘም የሚሉ ናቸው።

    ከእነዚህ አማራጮች ውስጥ በየትኛው መንገድ የመንግሥትን ስልጣን ለማራዘም እንደሚቻልም ገዥው ፓርቲ ከራሱ መዋቅሮችና በዙሪያው ከሚገኙ የሕግ ባለሙያዎች ጋር እየመከረ እንደሆነ ታውቋል።

    አብሮነት ከዚህ ቀደም ደጋግሞ ለመግለፅ እንደሞከረው ከመስከረም 30 ቀን 2013 ዓ.ም. በኋላ ለአንድም ቀን በስልጣን ላይ የሚገኘውን መንግሥት ዕድሜ ለማራዘም የሚያስችል ምንም ዓይነት ድንጋጌ በሀገራችን ሕገ-መንግሥት ውስጥ የለም። በሕገ-መንግሥቱ አንቀፅ 58/3 እና አንቀፅ 72/3 መሠረት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የጠቅላይ ሚኒስትሩ የሥራ ዘመን አምስት ዓመት ብቻ ስለመሆኑ በግልፅ ተቀምጧል። አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ወይም ምርጫ ማካሄድ የማይቻልበት አስገዳጅ ሁኔታ ሲገጥም የመንግሥትን ዕድሜ እንዴት ማራዘም እንደሚቻል ሕገ-መንግሥቱ ምንም ዓይነት ድንጋጌ አላስቀመጠም። ስለሆነም ብልፅግና ፓርቲ እንዲህ ዓይነት ሕገ-መንግሥታዊ ቀውስ እንዲከሰት ምክንያት የሆኑትን የሕገ-መንግሥቱን አርቃቂዎች እና ለሕገ-መንግሥቱ ክፍተት መታየት ምክንያት የሆነውን ኮሮና ቫይረስን “ከመርገም” ውጭ በሕጋዊ መንገድ የስልጣን ዘመኑን ለአንድም ቀን የሚያራዝምበት ምንም ዓይነት መብትና ስልጣን በሕገ-መንግሥቱ አልተሰጠውም።

    በሕገ-መንግሥቱ አንቀፅ 60 ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን በትነው በ6ወር ጊዜ ውስጥ ምርጫ እንዲያካሂዱ ስልጣን የተሰጣቸውም በሕገ-መንግሥቱ የተቀመጠውን አምስት ዓመት የመንግሥት የስልጣን ዘመን ለመጨረስ ነው እንጂ ከአምስት ዓመት በላይ የመንግሥትን የሥራ ዘመን ለማራዘም አይደለም። እንዲያውም በሕገ-መንግሥቱ አንቀፅ 60/1 ላይ በግልፅ እንደተቀመጠው በጠቅላይ ሚኒስትሩ ውሳኔ ድጋሜ ምርጫ መካሄድ የሚችለው በስልጣን ላይ ያለው መንግሥት የሥራ ዘመን ከመጠናቀቁ በፊት ብቻ ነው። ስለዚህ ይህ ሕገ-መንግሥታዊ ድንጋጌ በሕግ የተሰጠን የሥራ ዘመን ለማጠናቀቅ ከመቻል ጋር እንጂ የሥራ ዘመንን ከማራዘምና የመንግሥት የሥራ ዘመን ካለቀ በኋላ ከሚካሄድ ምርጫ ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የለውም።

    በሕገ-መንግሥቱ አንቀፅ 93/1፣ ሀ እና ለ ላይ በግልፅ እንደተደነገገውም የመንግሥትን የስልጣን ዘመን ለማራዘም ተብሎ ሊታወጅ የሚችል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የለም። አሻሚና አከራካሪ ባልሆነ መንገድ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ለምን ዓይነት ጉዳዮች ሊታወጅ እንደሚችል ሕገ-መንግሥቱ በዝርዝርና በግልፅ ስላስቀመጠ መንግሥት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማዎጅ ስልጣኑን ለአንድም ቀን ለማራዘም የሚያስችለው ሕጋዊ መብትና ስልጣን የለውም።

    እንደ ሦስተኛ አማራጭ እየታየ ያለው ሕገ-መንግሥቱን አሻሽሎ የመንግሥትን የሥራ ዘመን ለማራዘም መሞከርም ሕጋዊነትን የተከተለ አሠራር አይደለም። አንድ በስልጣን ላይ የሚገኝ መንግሥት የራሱን የስልጣን ዘመን ለማራዘም ሲል በሥራ ላይ ያለውን ሕገ-መንግሥት የሚያሻሽል ከሆነ፣ እንዲህ ዓይነቱ ድርጊት እንደ አንዳንድ አምባገነን የአፍሪካ መሪዎች በዓለም ፊት መሳቂያ እና መሳለቂያ የሚያደርግ የአምባገነኖች ድርጊት እንጂ ሕጋዊ አሠራር ተደርጎ ሊቆጠር አይችልም። እንዲህ ዓይነቱ የስልጣን ዘመንን ለማራዘም ሲባል ሕገ-መንግሥትን ለማሻሻል የመሞከር እርምጃም ከሕግ መኖርና አስፈላጊነት መሠረታዊ መርህ ጋር የሚጋጭ ሕገ-ወጥ ተግባር ነው። በእንዲህ ዓይነቱ ሂደትም ማንኛውም የፖለቲካ ኃይል የሕዝብ ቅቡልነት ሊያገኝ አይችልም። እንዲህ ዓይነቱን ከባድ ሀገራዊ ጉዳይ አሳታፊና ሕጋዊ ባልሆነ መንገድ ለመወሰን መሞከርም ሀገራችን በአሁኑ ወቅት ምን ያህል ሁለንተናዊ የህልውና ፈተና ውስጥ እንደምትገኝ አለመረዳት ነው። ይህም እንደተለመደው የገዥውን ፓርቲ ከሀገር ጥቅም ይልቅ የራሱን ስልጣን የማስቀደም ኃላፊነት የጎደለው ፍልጎት የሚያሳይ ነው።

    ስለዚህ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ የሕገ-መንግሥቱ አርቃቂዎች በሠሩት ስህተት እና በኮሮና ቫይረስ ወደ ሀገራችን መግባት ምክንያት በአሁኑ ወቅት በሀገራችን የመንግሥት የሥራ ዘመንን አስመልክቶ ሕገ-መንግሥታዊ ቀውስ (constitutional crisis) መፈጠሩን አምኖ መቀበል ያስፈልጋል። እንዲህ ዓይነት ሕገ-መንግሥታዊ ቀውስ በአንድ አገር ሲፈጠር ደግሞ ለችግሩ መፍትሄ መስጠት የሚቻለው በመደበኛ የሕግ አሠራር ሳይሆን ከመደበኛ የሕግ አሠራር ውጭ (extra-constitutional) በሆነ መንገድ ነው። እንዲህ ዓይነቱን መፍትሄ ለመስጠትም በተለየ ሁኔታ በሕግ መብት የተሰጠው የፖለቲካ ፓርቲ ወይም መንግሥታዊ ተቋም ስለሌለ የተፈጠረውን ሕገ-መንግሥታዊ ቀውስ እንዴት እንፍታው? በሚለው ጥያቄ ተነጋግሮ የመፍትሄ አቅጣጫ የሚያስቀምጥ ሁሉን አቀፍ ሀገራዊ የምክከር ሂደት (national dialogue) መጥራት ያስፈልጋል። ከመስከረም 30 ቀን 2013 ዓ.ም. በኋላ በሀገራችን በሕጋዊም ይሁን በይስሙላ ምርጫ የተመረጠ መንግሥት ስለማይኖር የወደፊቱን የአገሪቱን ዕጣ-ፈንታ በመወሰን ረገድ ገዥው ብልፅግና ፓርቲ ከማንኛችንም በአገሪቱ ከምንገኝ ፓርቲዎች የተለየ መብትና ስልጣን ስለሌለው በጉዳዩ ላይ ምንም ዓይነት ውሳኔ ብቻውን መወሰን አይችልም። ገዥው ፓርቲ ይህንን ማድረግ ከሞከረ በሀገራችን ከፍተኛ የፖለቲካ ቀውስ እና ትርምስ ሊፈጠር እንደሚችል ቆም ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል።

    ስለሆነም፦

    1ኛ. በአሁኑ ወቅት ዋናውና ቀዳሚው ትኩረታችን የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን መከላከልና መቆጣጠር መሆን ስላለበት ቢያንስ እስከ ነሃሴ መጨረሻ 2012 ዓ.ም. ድረስ ብልፅግና ፓርቲ የተፈጠረውን ሕገ-መንግሥታዊ ቀውስ በተመለከተ ምንም ዓይነት አጀንዳ ይዞ እንዳይነጋገርም ሆነ የተናጠል ውሳኔ እንዳያስተላልፍ፤

    2ኛ. የትግራይ ክልላዊ መንግሥት በዘንድሮው ዓመት በተናጠል ምርጫ ለማካሄድ ማሰቡ ሕገ-መንግሥታዊ ውሳኔ አይደለም። በሀገሪቱ ሕገ-መንግሥት መሠረት በፌደራልም ሆነ በክልል ደረጃ ምርጫ ለማካሄድ ብቸኛ መብት የተሰጠው የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ መሆኑን በመገንዘብ የትግራይ ክልላዊ መንግሥትም ሆነ ህወሓት ከዚህ ዓይነቱ ሕገ-ወጥ ድርጊታቸው እንዲቆጠቡ፤

    3ኛ. ብልፅግና ፓርቲ ይህንን አጀንዳ በሚመለከት በድብቅ የሚፈፅማቸውን ተግባራት ሁሉም ተቃዋሚ ፓርቲዎች በንቃት እንዲከታተሉ፣ ገዥው ፓርቲ ይህንን አጀንዳ በተመለከተ ሕገ-ወጥ እርምጃ መውሰዱን የሚቀጥልበት ከሆነም ተቃዋሚ ፓርቲዎች አመቺ የመገናኛ መንገድ ፈጥረው በአስቸኳይ መመካከር እንዲችሉና በጉዳዩ ላይ የራሳቸውን አቋም እንዲይዙ፣ ከዚህ በኋላም በሀገራችን ጉዳይ አንዳችን ጋባዥ ሌላችን ተጋባዥ የምንሆንበት ምክንያት እንደሌለ ተገንዝበን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከገዥው ፓርቲ ጋር የምናደርገው ማንኛውም ግንኙነትና ድርድር በእኩልነት መንፈስ ብቻ እንዲሆን የሚያስችል አቋም እንድንይዝ፤

    4ኛ. የኢትዮጵያ ሕዝብ ላለፉት 29 ዓመታት በአፈናና በይስሙላ ምርጫ በስልጣን ላይ የኖረው ገዥው ፓርቲ ከመስከረም 30 ቀን 2013 ዓ.ም. በኋላ ለአንድም ቀን በስልጣን ላይ ሊቀጥል የሚችልበት ምንም ዓይነት ሕጋዊ መብት የሌለው መሆኑን ተገንዝቦ በሕገ-ወጥ መንገድ ስልጣን ላይ ለመቆየት የሚደረገውን ጥረት አጥብቆ እንዲቃወም፣ መቃወምም ብቻ ሳይሆን የገዥውን ፓርቲ ሕገ-ወጥ እርምጃ በጠንካራ ሕጋዊና ሰላማዊ ትግል ለማስቆም እንዲዘጋጅ አብሮነት ጥሪውን ያቀርባል።

    አብሮነት ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት (አብሮነት)
    ሚያዚያ 21 2012 ዓ.ም
    አዲስ አበባ

    አብሮነት ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት

    Anonymous
    Inactive

    የምንሰጠው ሕጋዊና ፖለቲካዊ አማራጭ ከወቅታዊው የኮሮና ወረርሽኝ የሚታደገን፣ ሀገረ-መንግሥቱን የሚያስቀጥልና ወደ ተረጋጋ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የምናደርገውን ሽግግር የሚያግዝ ሊሆን ይገባል! ― የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)

    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ የአቋም መግለጫ

    የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከባድ ጉዳት እያደረሰ እንደሆነ ይታወቃል። ወረርሽኙ በሰዎች ጤና እና ደኅንነት ላይ ካደረሰው እና እያደረሰ ካለው ጉዳት ባልተናነሰ የዓለምን እና የሀገራትን ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ መስተጋብሮች እና ሥርዓትን ከባድ አደጋ ውስጥ ከቷል። ወረርሽኙ በሀገራችን ኢትዮጵያ እስከካሁን ያስከተለው ጉዳት ከሌሎች ሀገሮች ጋር ሲነጻጸር አስከፊ የሚባል ባይሆንም የደቀነው አደጋ ግን ከፍተኛ መሆኑ እርግጥ ነው። በሌሎች ሀገር ከታየው ተሞክሮ አንፃር ወረርሽኙ ድንገት በከፍተኛ ቁጥር ዜጎችን ሊያጠቃ እና የጤና ሥርዓት ቀውስ ውስጥ ሊከተን የሚችልበት አደጋ አሁንም አለ። የጎረቤት ሀገሮች (ሱዳን፣ ጅቡቲ እና ሶማሊያ) የኮሮና ቫይረስ ስርጭት በፍጥነት መዛመት የጀመረበትና በተለይ ከጅቡቲ ጋር ካለን የቀረበ የኢኮኖሚ ትስስር አንፃር በምሥራቁ የሀገራችን ክፍል ላይ የደቀነው ስጋት ከፍተኛ እንደሆነ ግልጽ ነው።

    ወረርሽኙን ለመቆጣጠር የሚወሰዱ እርምጃዎች በሀገራችን ኢኮኖሚ ላይ የሚያሳርፉት ጫና ከአሁኑ እየታየ ነው። ወረርሽኙ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚያደርሰው ጫናም በወጪ እና ገቢ ንግድ ዘርፍ ላይ ጫና እያሳደረ ሲሆን ይህም በቶሎ ወደቀድሞ ሁኔታው የሚመለስ አይሆንም። የበረሀ አንበጣ በኢትዮጵያ የግብርና ምርት ላይ እንደዚሁም የአገር ውስጥ ጥቅል ምርት ዕድገት ላይ የሚያሳድረው አሉታዊ ተጽዕኖ ከፍተኛ ነው። በተጨማሪም በኮሮና ምክንያት ከፍተኛ የኢኮኖሚ መቀዛቀዝና እስከ ሰኔ ድረስ ከሁለት ሚሊዮን በላይ የሚደርሱ ዜጎች የሥራ ዋስትና የማጣት ስጋት/አደጋ እንዳንዣበበባቸው በቅርቡ ተገልጿል። በአጠቃላይ ቫይረሱ በኢኮኖሚው ላይ የሚያስከትለው መጠነ ሰፊ መቀዛቀዝና የአገራዊ ጥቅል አመታዊ ምርትና እድገት ማሽቆልቆል ሀገራችን ላይ የከፋ ጉዳት ማስከተሉ አይቀሬ ነው።

    በሀገራችን ነባራዊ ሁኔታ የወረርሽኙ ተጽዕኖ ከኢኮኖሚ እና ማኅበራዊ ጫና በተጨማሪ በፖለቲካው ዘርፍም በታሪካችን አጋጥሞን የማያውቅ ሁኔታ ውስጥ ከቶናል።

    ከወረርሽኙ በተጨማሪ ከዚህ ቀደም የነበሩ የውስጥ ፖለቲካዊ ችግሮች እና በዓባይ ወንዝ ላይ እየገነባን ካለነው የታላቁ የሕዳሴ ግድብ ጋር በተያየዘ ከሌሎች ሀገሮች የተደቀነብን አደጋ በፍፁም በቀላሉ የሚታይ አይደለም። በተለይም ከግድቡ የውሃ ሙሌት ጋር ተያይዞ የሚመጣው ተጽዕኖ እየጨመረ እንደሚሄድ ይጠበቃል።

    የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ምክንያት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ነሐሴ 23 ቀን 2012 ዓ.ም ሊደረግ ታስቦ የነበረውን 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ማካሄድ እንደማይችል መጋቢት 22 ቀን 2012 ዓ.ም አስታውቋል። ምርጫው በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ መካሄድ አለመቻሉ አሁን በሥልጣን ላይ ያለው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የክልል ምክር ቤቶች የሥራ ዘመን ከተጠናቀቀ በኋላ ሀገርን ማን ያስተዳድራል የሚል ሕገ-መንግሥታዊ ጥያቄ አስነስቷል። በዚህም ምክንያት የተለያዩ አካላት ለዚህ ጉዳይ መፍትሄ ነው የሚሉትን ሀሳብ እያቀረቡ ይገኛሉ።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በዚህ ጉዳይ ላይ ከሕግ ባለሙያዎች ጋር በተለይም ከሕገ-መንግሥት ጠበቆች (constitutional lawyers) ጋር ሰፊ ውይይት አድርጓል። ባለሙያዎቹ የተፈጠረውን ሕገ-መንግሥታዊ ክፍተት በሕገ-መንግሥታዊ አግባብ እንዴት ሊፈታ ይችላል የሚለውን የወቅቱ ትልቅ ጥያቄ ጊዜ ሰጥተው እንዲመክሩበት የከፍተኛ የባለሙያዎች ጉባዔ (high level panel of experts) በማቋቋም ለአንድ ወር ያህል ጉዳዩን ሲያስጠናና ምክክር ሲያስደርግበት ቆይቷል። ኢዜማ ከገባንበት የፖለቲካ አጣብቂኝ ለመውጣት ልንከተለው የሚገባው የመፍትሔ ሀሳብ የሚከተሉትን ታሳቢዎች ከግምት ያስገባ መሆን እንዳለበት በጽኑ ያምናል፤

    1. አገራችን ከምትገኝበት የሕግም የፖለቲካ አጣብቂኝ በአጭር ጊዜ ለመውጣት የሚረዳ መሆን እንዳለበት፣
    2. ተቋማዊ አሠራሮችን ከማጎልበት አንፃር የተሻለ ዕድል የሚፈጥር መሆን እንዳለበት፣
    3. አጠቃላይ ችግሩ በአጭር ጊዜ ፈቶ አገራችን ወደተረጋጋ የምርጫ ሂደት ለመግባት የሚያስችል መሆን እንዳለበት፣
    4. ከወጪም ከጊዜም አንፃር አገሪቱን ብዙ ዋጋ የማያስከፍል የተሻለው አማራጭ ላይ ትኩረት መደረግ እንዳለበትና በፍጥነት የተቀያየሩት የአገራችንንና የቀጠናውን ጂኦ-ፖለቲካዊና የደኅንነት ስጋቶች በሚገባ ከግምት ውስጥ ያስገባ መሆን እንዳለበት።

    ኢዜማ ከላይ የገለፅናቸውን ሀገራዊ ፈተናዎች ለማለፍ ሕዝብን አስተባብሮ ሊመራ የሚችል ጠንካራ መንግሥት እንደሚያስፈልገን ያምናል። ለዚህም እንደፓርቲ ልንከተለው የሚገባን የመፍትሄ ሀሳብ ይህንን የሚያረጋግጥ መሆን እንደሚገባው በፅኑ ይረዳል። ለዚህም ይረዳ ዘንድ የፓርቲያችንን የሕግ ባለሙያዎች ጨምሮ በሌሎች አካላትም የቀረቡትን የመፍትሔ ሀሳቦች እንደሚከተለው ተመልክተናቸዋል።

    1. ከሕግ አማራጭ ውጪ የፖለቲካ መፍትሄ በሚል በተለያዩ አካላት የቀረበ የመፍትሄ ሀሳብ

    በዋናነት በዚህ ረገድ የቀረበው ሀሳብ አሁን በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት የሥልጣን ዘመን ከመስከረም 25 ቀን 2013 ዓ.ም. በኋላ የሚያበቃ በመሆኑ እና ሕገ-መንግሥቱም ከመስከረም 25 ቀን 2013 ዓ.ም. በፊት መንግሥት በሥልጣን ላይ የሚቆይበትን ሁኔታ ክፍተት ስለማይሰጥ በፖለቲካ ፓርቲዎች ንግግር ላይ የተመሠረተ የሽግግር መንግሥት ሀገሪቱን ሊመራ ይገባል የሚል ነው። ይህ መፍትሄ ሀሳብ አሁን ያሉትን የፖለቲካ ፓርቲዎች የእርስ በርስ ግንኙነት እና የቁጥር ብዛት ከግምት ያላስገባ በመሆኑ ተግባራዊ ለማድረግ የማይቻል ነው። ከዚህም በላይ እንደ ሀገር ያሉብንን ከላይ የጠቀስናቸውን ፈተናዎች ተጋፍጦ ለማለፍ የሚያስፈልገንን ጠንካራ የመንግሥት መዋቅር የሚፈጥር አይደለም። ይህም የገባንበትን ችግር ከመፍታት ይልቅ ወደባሰ ሀገራዊ ቀውስ ሊከተን የሚችል አማራጭ ያደርገዋል።

    1. በሕገ-መንግሥቱ ማዕቀፍ ሥር ያሉ አማራጮች

    2.1. በኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 60/1 እና 3 መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን በትነው በ6 ወር ውስጥ ምርጫ ማድረግ፦ ይሄ አማራጭ በ6 ወር ውስጥ ሊፈጠሩ የሚችሉ እና ሕግ ማውጣት የሚያስፈልጋቸው ድንገተኛ የሀገር እና ሕዝብን ደኅንነት እና ጥቅም አደጋ ውስጥ ሊከቱ የሚችሉ ሁኔታዎች ከግምት የማያስገባ፣ የፌደራል መንግሥትን እንጂ ሥልጣናቸው አብሮ የሚጠናቀቀውን የክልል ምክር ቤቶች ተመሳሳይ ችግር ያላገናዘበ አማራጭ በመሆኑ የምንፈልገውን ጠንካራ መንግሥት የሚፈጥር አማራጭ ሆኖ አላገኘነውም።

    2.2. በኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 93 መሠረት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጅ እና ምርጫውን ማራዘም፦ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የመንግሥትን የሥልጣን ዘመን ለማራዘም የተቀመጠ አንቀጽ አይደለም። አስቸኳይ ግዜ ማዋጅም በቀጥታ የመንግሥትን ሥልጣን ማራዘምን አያስከትልም። እንዲሁም በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጥላ ስር የሚደረግ ምርጫን ነፃ እና ፍትሃዊ ማድረግ አይቻልም።

    2.3. በኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 83 እና 84 መሠረት የሕገ-መንግሥት ትርጉም ከፌደሬሽን ምክር ቤት መጠየቅ፦ በዚህ አማራጭ መሠረት የሕገ-መንግሥት ትርጉም ሥራ የሚሠራው የሕገ-መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ በሙሉ ነፃነት እና ያለማንም ጣልቃ ገብነት የተመራለትን ጉዳይ በመመርመር የውሳኔ ሀሳብ አቅርቦ የፌደሬሽን ምክር ቤት ውሳኔ የሚሰጥ ከሆነ ያ ውሳኔ ምን ሊሆን እንደሚችል በእርግጠኝነት ማወቅ አይቻልም። አሁን ካለንበት አጣብቂኝ ክብደት አንጻር ጉዳዩን መዳረሻ ውጤቱ አስቀድሞ በእርግጠኝነት ለማይታወቅ እና ምናልባትም መልሶ እዚህ ከተጠቀሱት አማራጮች መካከል አንደኛውን እንድንከተል ሊያደርግ ለሚችል ሂደት መስጠት ተገቢ ሆኖ አላገኘነውም።

    2.4. በኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 104 እና 105/2 መሠረት የሕገ-መንግሥት ማሻሻያ ማድረግ፦ ይህ አማራጭ በሕገ-መንግሥቱ ውስጥ በግልጽ የተቀመጠ የማስፈጸሚያ ሥነ ሥርዓት ያለው እና አሁን ለገባንበት አጣብቂኝ የማያዳግም ምላሽ የሚሰጥ ሆኖ አግኝተነዋል።

    ምንም እንኳን ኢዜማ በሕገ-መንግሥቱ ውስጥ ሊሻሻሉ የሚገባቸው በርካታ አንቀጾች እንዳሉ በፅኑ ቢያምንም፥ አሁን ያለንበት ወቅት ሁሉን አቀፍ ሕገ-መንግሥታዊ ማሻሻያ ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል አይደለም። አሁን ለገባንበት ሕገ-መንግሥታዊ አጣብቂኝም ቀልጣፋ ምላሽ የሚሰጥ አይደለም። በኢዜማ እምነት ሁሉን አቀፍ ሕገ-መንግሥታዊ ማሻሻያ ለማድረግ ሀገራዊ መረጋጋት፣ በሕዝብ የተመረጠ መንግሥት እና ሰፊ ሕዝባዊ ተሳትፎ የሚጠይቅ ነው። እንዲሁም በከፍተኛ በጥንቃቄ ሊሠራ እንደሚገባው ሀገራዊ ጉዳይ በዚህ ወቅት ሊከወን አይገባም ብለን እናምናለን። ሆኖም አሁን የገጠመንን አጣብቂኝ ለመሻገር የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤቱን የሥራ ዘመን እና ምርጫ የሚደረግበትን ወቅት የሚደነግገው አንቀጽ 58ን ጊዜውን ጠብቆ ምርጫ ለማድረግ የማያስችል ድንገተኛ እና ከአቅም በላይ የሆነ ችግር በሚያጋጥምበት ጊዜ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከ1 ዓመት ላልበለጠ ጊዜ ምርጫውን ማራዘም እና ምርጫው እስኪደረግ ድረስ ዘላቂ ውጤት ያላቸውን እና በቀጣይ ምርጫውን አሸንፎ ሥልጣን በሚይዘው መንግሥት ላይ ተጨማሪ ኃላፊነትን የሚጥሉ ተግባራትን ከመከወን በከለከለ መልኩ የመንግሥትን ቀጣይነት በግልፅ የሚደነግግ አድርጎ በማሻሻል ቀጥተኛ፣ ሕገ-መንግሥታዊ፣ የማያዳግም እና ተቀባይነት ያለው መፍትሄ መስጠት አስፈላጊ ሆኖ አግኝተነዋል።

    በኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 105/2 ሀ እና ለ መሠረት የሕዝብ ተወካዮች እና የፌደሬሽን ምክር ቤቶች በጋራ ስብሰባ በ2/3ኛ ድምፅ ማሻሻያውን ሲያጸድቁ እንዲሁም ከክልል ምክር ቤቶች ውስጥ 2/3ኛ ክልሎች (6 ክልሎች) በአብላጫ ድምፅ ሲያጸድቁት በሕገ-መንግሥቱ ምዕራፍ 3 ስር ከሚገኙት እና አንቀጽ 104 እና 105 ውጪ ያሉትን የሕገ-መንግሥት አንቀጾች ማሻሻል እንደሚቻል ተደንግጓል። በዚሁ መሠረት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤቱን የሥራ ዘመን እና ምርጫ የሚደረግበትን ወቅት የሚደነግገው አንቀጽ 58/3 ከላይ በተገለጸው መሠረት ማሻሻል የተሻለ መፍትሄ እንደሆነ እናምናለን።

    ይህ መፍትሄ ተግባራዊ ከተደረገ በሥራ ላይ ያለውን ሕገ-መንግሥት ተከትሎ የሚፈፀም በመሆኑ ሕገ ምንግሥታዊ ጥያቄ የሚያስነሳ አይሆንም። እንዲሁም በቅርቡ ልናደርገው ከምናስበው ምርጫ እና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ አንፃርም አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል ብለን እናምናለን። በዚህ አማራጭ ላይ በተለያዩ አካላት የሚነሳው ጥያቄ በዚህ የወረርሽኝ ወቅት በአንቀጽ 104 ድንጋጌ መሠረት ህዝብን ለማወያየት አያስችልም የሚል ሲሆን ይህንን ክፍተት ግን ሕዝቡን በወኪሎቹ አማካኝነትና በተለያዩ የቴክኖሎጂ አማራጮች በማወያየት መሸፈን ይቻላል።

    ከዚህ ቀደም በሕገ-መንግሥቱ ውስጥ የጋራ የታክስ እና የግብር ሥልጣንን የሚደነግገው አንቀጽ 98 እና የሕዝብ ቆጠራን በሚመለክት የሚካሄድበት የጊዜ ገደብን የሚደነግገው አንቀጽ 103/5 በሕገ-መንግሥቱ የተጠቀሰውን የማሻሻያ ሥነ ሥርዓት ሙሉ በሙሉ ሳይከተሉ ለየብቻ በተለያየ ጊዜ ማሻሻያ ተደርጎባቸው እንደነበር የሚታወስ ሲሆን፥ አሁን መደረግ ያለበት ማሻሻያ ግን የሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ 104 እና 105/2 ያስቀመጡትን ድንጋጌዎች በሙሉ አሟልቶ ሊሆን እንደሚገባው እናምናለን።

    ይህ የሕገ-መንግሥት ማሻሻያ ተግባራዊ የሚደረግ ከሆነ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በተጨማሪ የክልል ምክር ቤቶችንና የፌድሬሽን ምክር ቤትንም የሥልጣን ዘመን በሚያራዝም መልኩ መተግበር አለበት።

    የፓርቲያችን እምነት የሕገ-መንግሥቱን አንቀጽ 58/3 ማሻሻል የተሻለ አማራጭ ነው የሚል ቢሆንም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከላይ በተራ ቁጥር 2.3 ላይ የጠቀስነውን አማራጭ በመውሰድ የሕገ-መንግሥቱን አንቀጥ 54/1፤ 58/3 እና 93 ላይ ትርጉም እንዲሰጥ ለፌደሬሽን ምክር ቤት እንደመራው ታውቋል። ምንም እንኳን ኢዜማ ይህንን አማራጭ የተሻለ አማራጭ ነው ብሎ ባያምንም አማራጩ ተግባራዊ የሚደረግ ከሆነ የሕገ-መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔው ሕገ-መንግሥቱን በሚተረጉምበት ወቅት ከመንግሥትም ሆነ ከሌላ ማንኛውም አካል ተፅዕኖ ነፃ ሆኖ ተግባሩን ማከናወን አለበት። የሕገ-መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ በሚያቀርበው የውሳኔ ሀሳብ የፌደሬሽን ምክር ቤት የሚያጸድቀው ትርጉም የመንግሥትን ሥልጣን በማንኛውም መልኩ የሚያራዘም ከሆነ ማራዘሚያውን እጅግ ቢገፋ ከ1 ዓመት እንዳይበልጥ ማድረግ አለበት። ውሳኔው በዚህ የማራዘሚያ ወቅት ሥልጣን ላይ የሚቆየው መንግሥት ዘላቂ ውጤት ያላቸውን እና በቀጣይ ምርጫውን አሸንፎ ሥልጣን በሚይዘው መንግሥት ላይ ተጨማሪ ኃላፊነትን የሚጥሉ ተግባራትን ከመፈፀም እንዲቆጠብ የሚያስገድድ መሆንም አለበት።

    በአጠቃላይ እንደሀገር የሚወሰዱ ማንኛውም አማራጮች አሁን ያለንበትን አስቸጋሪ እና ፈታኝ ወቅት ከግምት ያስገቡ፣ የሀገር መረጋጋት፣ ሰለም እና ቀጣይነትን የሚያረጋግጡ፣ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ሂደቱን የሚያስቀጥሉ እንዲሁም አሁን ከገባንበት ሕገ-መንግሥታዊ አጣብቂኝ በአስተማማኝ ሁኔታ የሚያስወጡን መሆን እንዳለባቸው ኢዜማ ለማሳሰብ ይወዳል። በተጨማሪም በተመሳሳይ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የሚወሰኑ ውሳኔዎች የተለያየ አመለካከት ካላቸው የፖለቲካ ኃይሎች ጋር በሚደረግ ውይይት መዳበራቸው መፍጠር የምንፈልገውን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንድንለማመድ በር የሚከፍት እና ሁሉንም ኃይሎች የባለቤትነት ስሜት እንዲሰማን የሚያደርግ በመሆኑ የፖለቲካ ፓርቲዎች በተመሳሳይ ሀገራዊ ጉዳይ ላይ በቂ እና ቀጣይነት ያለው ውይይት የምናደርግበት መድረክ እንዲመቻች ጥሪ እናቀርባለን።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
    ሚያዝያ 28 ቀን 2012 ዓ.ም
    አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)

    Anonymous
    Inactive

    የኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝን ምላሽ ለመስጠት ከ220 በላይ የሕክምና መስጫ እና ለይቶ ማቆያ ማዕከላት ዝግጁ ተደርገዋል

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በሀገራችን የኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝን ምላሽ ለመስጠት ከአንድ መቶ ሺህ በላይ ሰዎችን ሊይዙ የሚችሉ ከ220 በላይ የሕክምናና የለይቶ ማቆያ ማዕከላት ተዘጋጅተዋል።

    በኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የሕብረተሰብ ጤና ድንገተኛ አደጋ ማስተባበሪያ ማዕከል የኮቪድ-19 የተቋማት ዝግጁነት ክፍል አስተባባሪ አቶ ኢሳያስ መሠለ እንደገለጹት፥ የኮሮና ቫይረስ በቻይና ዉሃን ከተማ (Wuhan) ከተከሰተ ጀምሮ በሀገራችንም የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ተሠርተዋል። ከዚህም ውስጥ የኮሮና ቫይረስ የተገኘባቸውን ሰዎች የሕክምና መስጫ ማዕከል (treatment centers)፣ የበሽታውን ምልክት የሚያሳዩ ሰዎች የላብራቶሪ ምርመራ ተደርጎላቸው ውጤታቸው እስኪታወቅ ተለይተው የሚቆዩበት (isolation centers) እንዲሁም ከመጋቢት 14 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ማንኛውም ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባ ግለሰብ ለ14 ቀናት ለይቶ ማቆያ መግባት እንዳለበት በተላለፈው ውሳኔ መሠረት የለይቶ ማቆያ ቦታዎችን (quarantine centers) መለየትና ዝግጁ ማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎች ናቸው።

    በዚህም መሠረት ይህ መረጃ እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ በአዲስ አበባና በክልሎች ሙሉ በሙሉ ለኮሮና ቫይረስ ህሙማን አገልግሎት እየሰጠ የሚገኘውን የኤካ ኮተቤ ሆስፒታል ጨምሮ ከ10,000 በላይ ሰዎች የሕክምና አገልግሎት መስጠት የሚችሉ ከ40 በላይ ማዕከሎች (treatment centers) ዝግጁ የሆኑ ሲሆን ከ15,000 በላይ ሰዎችን አገልግሎት መስጠት የሚችሉ ከ100 የሚበልጡ የለይቶ ማቆያዎች (isolation centers) እንዲሁም የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎችን ጨምሮ ከ80 በላይ የለይቶ ማቆያዎች (quarantine center) ተዘጋጅተዋል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘም የኮቪድ-19 ብሔራዊ የድንገተኛ ማዕከል የኢንፌክሽን መከላከልና መቆጣጠር የውሀ፣ ሳኒቴሽንና ሀይጅን (sanitation and hygiene) ክፍል አስተባባሪ ወ/ሮ ኢክራም ሬድዋን እንደተናገሩት፥ ለኮሮና ቫይረስ (የኮቪድ-19) በሽታ በተዘጋጁ የለይቶ ማቆያ እና ሕክምና ማዕከላት ያሉ የውሀ ሳኒቴሽንና ሀይጅን እንዲሁም ኢንፌክሽንን ከመከላከልንና መቆጣጠር አንፃር ያሉ ክፍተቶችን በመለየት ለመሙላት እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ይህም ከውሀ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር፣ ከውሀ ልማት ኮሚሽን እና ከአጋር ድርጅቶች በተደረጉ ድጋፎች ሲሆን፥ የውሀ መቆራረጥና እጥረት ያለባቸውን ተቋማት ክፍተት መሙላት፤ የውሀ አቅርቦት መቆራረጥን ለመቀነስ የውሀ ታንከሮችና ፓምፖችን መግጠም፣ ውሀን በከባድ መኪና (truck) ማቅረብ እንዲሁም የእጅ መታጠቢያ እጥረት ባለባቸው የለይቶ ማቆያ እና ሕክምና ማዕከላት ከእጅ ንክኪ የጸዱ በእግር መከፈት የሚችሉ ተንቀሳቃሽ የእጅ መታጠቢያዎች እንዲተከሉ ተደርጓል።

    በተጨማሪም ለሁሉም ለይቶ ማቆያ እና ሕክምና ማዕከላት የኢንፌክሽን መከላከልና መቆጣጠር ባለሙያ እና በአዲስ አበባ ለሚገኙ የለይቶ ማቆያ እና ሕክምና ማዕከላት የፀረ-ተህዋሲያን ኬሚካል ርጭት ባለሙያዎች ተመድበዋል። ለነዚህ ባለሙያዎችም የኮቪድ-19 የኢንፌክሽን መከላከልና መቆጣጠር ስልጠና የተሰጠ ሲሆን፥ ባለሙያዎቹም በአጠቃላይ የሚከናወኑ ተግባራት ኢንፌክሽንን ከመከላከልና መቆጣጠር አንጻር በአግባቡ እየተካሄዱ መሆናቸውን በየዕለቱ ይከታላሉ ብለዋል።

    በአጠቃላይ በሽታውን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ከሚሠሩ ሥራዎች ባሻገር ሕብረተሰቡ የሚያደርጋቸው ጥንቃቄዎች ለበሽታው ያለመስፋፋት ወሳኝ በመሆናቸው ሕብረተሰቡ ሳይዘናጋ የሚተላለፉ መልዕክቶችን እና መከላከያ መንገዶችን ተግባራዊ በማድረግ የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል።

    ለተጨማሪ መረጃ በስልክ መስመር 8335 ወይም በ952 በመደወል ወይም የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የኢሜል አድራሻ ephieoc@gmail.com በመጠቀም ወይም ባሉበት ክልል በተዘጋጁ ነፃ የስልክ መስመሮች በመደወል ሪፖርት እንዲያደርጉ ወይም በአካባቢው ለሚገኙ ጤና ተቋማት በስልክ እንዲያሳውቁ ኢንስቲትዩቱ ይጠይቃል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    EPHI NDMC new website for COVID-19 ለይቶ ማቆያ ማዕከላት

    Semonegna
    Keymaster

    79ኛውን የአርበኞች የድል በዓል በማስመልከት ፕሬዝደንት ሣህለወርቅ ዘውዴ ያስተላለፉት መልዕክት

    ውድ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ፥

    እንኳን ለ79ኛው የድል ቀን በሰላም አደረሰን። በመላው ዓለም በተከሰተው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ስጋት የተነሳ እንደለመድነው በአርበኞች ሀውልት ዙሪያ አንድ ላይ ተሰባበስበን በዓሉን ማክበር አልቻልንም። ሆኖም ግን የእነዚያን የቁርጥ ቀን የኢትዮጵያ ልጆችን ዘመን የማይሽረው ተጋድሎ በመንፈስ አድምቀነው እንደምንውል እምነቴ ጽኑ ነው።

    የዓለም የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ጮራ የሆነውን የአድዋ በዓልን የዛሬ ሁለት ወር አክብረናል። [ዛሬ] ደግሞ በተመሳሳይ የኩራትና የአይበገሬነት ከፍታ እንዲሁም መንፈስ ላይ የሚያስቀምጠንን የሚያዝያ 27 የድል በዓልን አስበን እንውላለን። ይህን ቀን ስናስታውስም ብዙ የታሪክ ሰበዞች ተከታትለው ይቀመጣሉ። አድዋ ላይ ያላሰቡትን ውርደት የተከናነቡት ፋሽስቶች ቂማቸውን ለመወጣት ቀን ሲቆጥሩ ከርመዋል። የታጠቁትን መሣሪያ ተማምነው የጠነሰሱትን ባርነት በኢትዮጵያ ምድር ላይ ለማንገስ ተማምለው ድንበር ጥሰው ገቡ። መጀመሪያ ገደማ ያሰቡት የሰመረላቸው መሰላቸው። በኢትዮጵያውያን ላይ ያዘነቡት የሞት መዓት እድሜ ልካቸውን ከዚህች ምድር የሚነቅላቸው እንደሌለ ዋስትና አድርገው ወሰዱት። በከተማውና በገጠሩ የሞት ነጋሪት ጎሰሙበት።

    ብዙም ሳይቆይ ግን ታሪክ ተገለበጠ። ኢትዮጵያውያንን በቅኝ ግዛት ለማንበርከክ የተመመው የፋሽቶች ሠራዊት የወጠነውን ሳይጨርስ ግማሽ መንገድ ላይ ቀረ። ኢትዮጵያውያን እናትና አባት አርበኞች የሞሶሎኒን የአደባባይ ድንፋታ እና የሠራዊቱን እብሪት የጠዋት ጤዛ አደረጉት። የአድዋውን ቂም ለመበቀል ከ40 ዓመታት በኋላ የተወጠነው ዘመቻ በድጋሚ በአድዋ መንፈስ መና ቀረ።

    ውድ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ፥

    ይህ የኢትዮጵያውያን በጨለማ ውስጥ ብርሃን መፈለግን፣ በመከራ ውስጥ ተባብሮ ማንሰራራትን፣ በጭንቅ ጊዜ ተስፋ ማድረግን በተለይ አሁን ለምንገኝበት ሁኔታ እጅግ በጣም አስፈላጊያችን ስንቅ ነው ብየ አምናለሁ። የአድዋ እና የአርበኞችን ድል መንፈስ እየታደሰ የሚቀጥል ህያው መንፈስ ማድረግ አለብን። ለዘላቂ የሀገራችን ጥቅሞች ልናውላቸው ይገባናል። በታላቁ የሕዳሴ ግድብ ያሳየነውን አንድነትና ታላቅ ህልም በሌሎችም ላይ እናባዛው። ዛሬ በተለያየ መልኩ የተደቀኑብንን ፈተናዎች ድል ለመንሳት እናውላቸው።

    የኮሮና ወረርሽኝ የደቀነብን አደጋ ከማይታይ ጠላት ጋር የሚደረግ ጦርነት ነው። የቫይረሱ ተለዋዋጭ ሁኔታ ሥራችንን ሁሉ ዱካውን ያጠፋ ጠላት ያህል ፈታኝና ውስብስብ አድርጎብናል። መመሪያ አክብረን፣ የሚጠበቅብንን ተወጥተን እስከተፋለምነው ድረስ ለመቆጣጠር ያለንን ዕድል ያሰፋዋል። ከወረርሽኙ በኋላ የሚኖረውን ሁኔታ ከአሁኑ የተሻለ ለማድረግም የቤት ሥራችንን መጀመር ይኖርብናል፤ ዛሬ ያልሠራንበትን ነገ አናገኘውምና።

    የኢትዮጵያን የድህነትና የርሃብ ታሪክ ጨርሶ ለመለወጥ ተስፋ ሰጪ ሁኔታ ላይ እንገኛለን። ተቻችለን፣ ተደማምጠን እና ተከራክረን የሀገራችንን ተስፋ ለማለምለም ቆርጠን እንነሳ። ይህን ስናደርግ የእነዚያ አይበገሬ ኢትዮጵያውያን አሻራ ህያው ሆኖ ከትውልድ ወደ ትውልድ ይሸጋገራል። ያለንበትን ተስፋ ሰጪ ሁኔታ ለዘላቂ እድገት እናውለው።የአድዋም ሆነ የአርበኞች ድል ከዚህ ውጭ የመጣ አይደለምና።

    መልካም የአርበኞች የድል በዓል

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    79ኛውን የአርበኞች የድል በዓል በማስመልከት ፕሬዝደንት ሣህለወርቅ ዘውዴ ያስተላለፉት መልዕክት

    Anonymous
    Inactive

    ከሚያዝያ 23 እስከ 25 ቀን 2012 ዓ.ም. በወቅታዊ ሀገራዊ እና ክልላዊ ጉዳዮች ላይ ለመወያየት ተሰብስቦ የነበረው የህወሓት ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ስብሰባውን ሲያጠናቅቅ ባለ አምስት ነጥብ ውሳኔዎችን አሳልፏል።

    ከህወሓት ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ

    የህወሓት ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ከሚያዝያ 23 እስከ 25 ቀን 2012 ዓ.ም. በክልላችንና በሀገራችን እንዲሁም በንዑስ ቀጣናው የተከሰቱ ፖለቲካዊ ጉዳዮችን በስፋት በመመርመር የውሳኔ ሃሳቦችን አሳልፏል። ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በክልላችን እየተከናወኑ ያሉ የሰላምና የልማት፣ የመልካም አስተዳደር፣ የክልላችንና የሕዝባችን ድኅንነት የመታደግ ሥራዎችን እንዲሁም የኮረናን ወረርሽኝ ለመመከት የተሠሩ ሥራዎች በሚመለከት በዝርዝር የተወያየበት ሲሆን፣ እስካሁን የታዩ ጥንካሬዎችን ጠብቆ ለማቆየትና የታዩ ጉድለቶችን ለማረም የተሠሩ ሥራዎችን በመመርመር ውሳኔዎችን አሳልፏል። በክልላችን ያሉ ወይም የሚኖሩ ፈተናዎች ለመመከት አሁንም ወሳኙ ውስጣዊ ጥንካሬያችን መሆኑን በድጋሚ በማረጋገጥ በዚህ ረገድ የተጀመሩ እንቅስቃሴዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ስምምነት ላይ ተደርሷል።

    የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በሦስት ቀን ስብሰባው በስፋት ከመከረባቸው ጉዳዮች ዋነኛው በሀገር ደረጃ በብልፅግና ፓርቲ እየተካሄደ መጥቶ አሁን በመጨረሻ ደረጃ ላይ የደረሰውን ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓት የመናድ ዘመቻ የሚመለከተው አጀንዳ የጎላ ትኩረት የተሰጠው ነበር። ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በዝርዝር ተወያይቶ እንዳስቀመጠው የብልፅግና ፓርቲ ቀድሞውኑም ለማከናወን ሙሉ ፈቃደኝነት ያላሳየበትን ሀገራዊ ምርጫ የCOVID-19 ወረርሽኝ መከሰትን እንደመልካም አጋጣሚ በመቁጠር በአንድ ሰው የሚመራ አምባገነን ሥርዓትን ለመትከልና ከሕገ-መንግሥታዊ መንገድ ውጪ የሥልጣን ዕድሜን ለማራዘም የተጀመረውን ጥረት አጠናክሮ ቀጥሎበታል። ባለፉት ጥቂት ቀናት በግልፅ እንደታየው የፓርቲዎችን ሃሳብ ለመቀበል በሚል በተጠራ የይስሙላ መድረክ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያለቀለት ያሉትን ሃሳብ ማጠናቀቂያ ክፍል ምን ሊመስል እንደሚችል በግልፅ አመላክተዋል።

    የህወሓት ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ይህ ያለበቂ ዝግጅትም ሆነ ያለግልፅ አጀንዳ የተጠራውና ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሕግ ውጭ በሥልጣን ለመቀጠል ያላቸውን ፍላጎት ያሳዩበት መድረክ ተከትሎ በፓርላማው የተጀመረውና ሕግን ያላግባብ በመተርጎም የብልፅግና ፓርቲን ሕገ-ወጥ የስልጣን ዕድሜ የማራዘም እንቅስቃሴ ፍፁም ተቀባይነት እንደሌለው በድጋሚ አስምሮበታል። አሁንም ሥልጣን ላይ ባለው ኣካል የተጀመረውና ሕገ-መንግሥትን መተርጎም በሚል ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓት የመናድ የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ እንደተደረሰ ግልፅ ሆኗል።

    በዚህም መሠረት የህወሓት ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የሚከተሉተን ውሳኔዎች አሳልፏል።

    1. የብልፅግና ፓርቲ ሕገ-መንግሥቱን ለመተርጐም በሚል ሰበብ የተጀመረው ገሀድ የወጣ እንቅስቃሴ በአስቸኳይ እንዲያቆም። ሕገ-መንግሥታዊ ትርጓሜ የሚያስፈልገው ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓት ባስቀመጠው ግልፅ መስፈርት መሠረት አሻሚ ሁኖ ለተገኙ አንቀፆች እንጂ የአንድን ስብስብ የሥልጣን ዕድሜ ከሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓት ውጭ ለማራዘም ሊሆን አይችልም። በመሆኑም ይህንን ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓት ሙሉ በሙሉ ለማፍረስ እየተደረገ ያለው ጥድፍያ በአስቸኳይ ቆሞ አሁንም የኮረና ወረርሽኝን በተቀናጀ መልኩ ለመከላከልም ሆነ ሀገራዊ ምርጫን ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓቱ በሚፈቅደው ማእቀፍ ውሰጥ በመሆን ለማከናወን በሚቻልባቸው መንገዶች ላይ ሁሉም ፓርቲዎች በሙሉ የባለቤትነት መንፈስ እንዲሳተፉ ተደርጎ ሀገርን ከለየለት የጥፋት አደጋ ለመታደግ እንዲቻል መድረክ እንዲመቻች ይጠይቃል።
    2. የእንደዚህ ዓይነቱ መድረክ አስፈላጊነት እንደተጠበቀ ሆኖ የብልፅግና ፓርቲ ነፃና ግልፅ ምርጫ የመምራት ምንም ዓይነት ሞራላዊ ብቃት የሌለው በመሆኑ ይህንን ለማስፈፀም የሚችል የተለየ አደረጃጀት የመፍጠር አስፈላጊነት ላይ ስምምነት ላይ ተደርሶ የሀገርን ሉዓላዊነትና ሰላም ለማስከበር አስፈላጊነት በቂ ትኩረት በሰጠ መልኩ ምርጫውን ለማከናወን የሚያስችል ዝግጅት እንዲጀመር ጥሪውን ያቀርባል።
    3. ይህ ሳይሆን ቀርቶ ወትሮውኑም ገዢውን ፓርቲ በሕገ-ወጥ መንገድ አፍርሶ ራሱን በወራሽነት ያስቀመጠው የብልፅግና ፓርቲ ከመስከረም 25 ቀን 2012 ዓ.ም. በኋላ በሥልጣን ላይ ለመቆየት የሚያስችለው ጠባብም ቢሆን ዕድል የማይኖር በመሆኑ የሀገሪቱ ችግር ለመፍታት ወደሚከብድ ችግር የምትገባበት ዕድል መፈጠሩ የማይቀር ይሆናል። ህወሓት እንደዚሁ ዓይነቱ ክስተት ሊፈጥረው የሚችለውን ትርምስ ለማስወገድ በሚደረጉ ሀገራዊ ጥረቶች ውስጥ ድርሻውን በቀናነት ለመጫወት ዝግጁ ቢሆንም የትግራይ ሕዝብ በመስዋዕትነቱ በተከለው ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓት የተረጋገጠለትን ራስን በራስ የማስተዳደር መብት እንደዋዛ እንዲጣልበት አይፈቅድም። ለዚህም ሲባል ከትግራይ ሕዝብና ለትግራይ ሕዝብ ራስን በራስ የማስተዳደር መብት ሙሉ ዕውቅና ከሚሰጡ የፖለቲካ ኃይሎች ጋር በመሆን ክልላዊ ምርጫን ጨምሮ ይህንኑ የሕዝባችንን መብት ከትርምስ ለመታደግ የሚያስችሉ ሥራዎችን በክልል ደረጃ ለማድረግ ዝግጅት እንዲደረግ ወስኗል። ይህ እንቅስቃሴ የፀረ ኮረና ወረርሽኝ ዘመቻችንን እንዲሁም ተቀባይነት ያላቸውን ሕገ-መንግሥታዊ መርሆዎችን ባሟላ መልኩ የሚፈፀም ይሆናል።
    4. የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የተወካዮች ምክር ቤት እንዲሁም የፌደሬሽን ምክር ቤት አባላት ህልውናቸው ያረጋገጠውን ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓት በጠራራ ፀሀይ ለማፍረስ የሚደረገውን እኩይ ተግባር በማስቆም ከታሪክ ተጠያቂነት ራሳቸውን እንዲያርቁ በዚህ አጋጣሚ የህወሓት ሥራ አስፈፃሚ ጥሪውን ያቀርባል።
    5. በመጨረሻም ህወሓት ሆነ የትግራይ ሕዝብ የሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓታችን ያረጋገጠውን ሕብረ-ብሔራዊ ፌዴራላዊ ሥርዓት ለማዳን በሚደረገው ርብርብ መሰል አጀንዳ ከሚያራምዱ ብሔር ብሔረሰቦችም ሆነ የፖለቲካ ኃይሎች ጋር ለመታገል ዝግጁ መሆናችንን አሁንም በድጋሚ ማረጋገጥ እንፈልጋለን።

    የህወሓት ማዕከላይ ኮሚቴ ጽ/ቤት
    ሚያዝያ 26 ቀን 2012 ዓ.ም.

    ምርጫ በኢትዮጵያ ― የኢትዮጵያ ብሔራዊ እና ክልላዊ ምርጫዎች ― ሰሞነኛ ዜናዎችና መረጃዎች

    የህወሓት ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የሚከተሉተን ውሳኔዎች

    Anonymous
    Inactive

    “የጃዋርና የልደቱ ትልቁ ችግር ሕዝብን በኪሳቸው እንደያዙት ሳንቲም ሲፈልጉ ሊያስቀምጡት፣ ሲፈልጉ ደግሞ አውጥተው ሊጠቀሙበት፣ ደፍነው ለጅምላ ግዢ፣ ዘርዝረው ለችርቻሮ ሊያውሉት የሚችሉት አድርገው መቁጠራቸው ነው።”

    ሕዝብ እኮ ስልጣን የራበው ሁሉ እየነቀለ የሚጥደው የቦና ጎመን አይደለም (በድሉ ዋቅጅራ)

    የጃዋርን እና የልደቱን ውይይት አየሁት፤ ሰማሁት። ላየው የቀሰቀሰኝ ዋና ነጥብ አንድ ላይ ያመጣቸውን ጉዳይ የማወቅ ጉጉት ነበር። አገኘሁት። ያቀረቡበት መንገድ ነው ልዩነቱ፤ የጃዋር በፖለቲከኛ (ብስለትና መሰሪነት)፣ የልደቱ በወታደር (ጉልበትና ማስፈራራት) ከመቅረቡ በስተቀር፤ ‹መስከረም 30 የመንግሥት ሕጋዊ ተቀባይነት ስለሚያበቃ፣ መንግሥት እኛ የምንለውን የማይቀበል ከሆነ ሕዝቡ ከእኛ ጋር ቆሞ መንግሥት እንዲቃወም፣ እንዲታገል› ነው።

    በጎው ነገራቸው ―
    “መንግሥት ከተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በሁኔታው ላይ መወያየትና መስማማት አለበት” የሚለው ነው። በእርግጥ መንግሥት ይህን ማድረግ አለበት፤ ይህ ሕዝብ በኮሮና ድቀቱ ላይ፣ በፖለቲካ ምክንያት የሚፈጠር ነውጥን የሚሸከም ትከሻ አይደለም፤ የሚሰማ ጆሮ የለውም።

    የጃዋርና የልደቱ ትልቁ ችግር ሕዝብን በኪሳቸው እንደያዙት ሳንቲም ሲፈልጉ ሊያስቀምጡት፣ ሲፈልጉ ደግሞ አውጥተው ሊጠቀሙበት፣ ደፍነው ለጅምላ ግዢ፣ ዘርዝረው ለችርቻሮ ሊያውሉት የሚችሉት አድርገው መቁጠራቸው ነው። ሕዝቡን እውን ቢያውቁት የትላንቱን ውይይታቸውን ይዘውለት ለመቅረብ ባልደፈሩ ነበር። በተለይ አዚህ ላይ የልደቱ ድፍረት ለከት አልነበረውም። ከመስከረም 30 በኋላ መንግሥት ስብሰባ እንኳን ለመምራት፣ መብት እንደሌለው ሲናገር፣ ስለራሱ ሀገር የሚያወራ ፈጽሞ አይመስልም፤ በወረርሽኝ ምክንያት ምርጫ ስለተራዘመበት መንግሥት ሳይሆን፣ ሀገር ለቅቄ እወጣለሁ ያለበትን ቀን ስላላከበረ ቅኝ ገዢ የሚያወራ ነው የሚመስለው። የሚገርመው ከወራት በፊት ልደቱ “ተቃዋሚ ፖርቲዎችን 10 ሺህ ፊርማ እንዲያሰባስቡ መጠየቅ፣ ፓርቲዎችን ማዳከምና እንዳይመሠረቱ ማድረግ ነው…” ባለበት አፉ ዛሬ 100 ሚሊየን ሕዝብ ከጎኑ እንደሆነ በሙሉ ልብ ሲናገር መስማት ጤንነቱን ያጠራጥራል፤ .. ሕዝብ እኮ ስልጣን የራበው ሁሉ እየነቀለ የሚጥደው የቦና ጎመን አይደለም።

    ውይይታቸውን ልብ ላለ የልደቱና የጃዋር ልዩነት (ምንም እንኳን ጃዋር የፓርቲያቸውን የመፍትሄ ሀሳብ ግልጽ ባያወጣውም) ለችግሩ የሚያቀርቡት የመፍትሄ ሀሳብ ላይ ነው። በግሌ የጃዋር ፓርቲ የሽግግር መንግሥትን እንደመፍትሄ የሚያቀርብ አይመስለኝም። ዶ/ር መረራ እና ጃዋር እራሱ የፖለቲካ ሳይንስ ተማሪዎች በመሆናቸው እውቀታቸውን ተጠቅመው የተሻለ ሀሳብ ሊያቀርቡ ይችላሉ ብዬ እገምታለሁ።

    የልደቱ “የሽግግር መንግሥት” ሀሳብ ግን እንዳለው ቀድሞም በቀዳማዊ ኢህአዴግ መውደቅ ፍትጊያ (2009/10 ዓ.ም.) የነበረ፣ ዛሬም ከኮረና ጋር ያለ ነው። ልደቱ ከፍተኛ የስልጣን ፍላጎት ያለው ይመስለኛል፤ በሌላ በኩል ደግሞ የ97ቱ ምርጫ ሕዝባዊ ቅቡልነቱን እንዳወረደውና የሚፈልገውን የስልጣን እርካብ እንደማያስረግጠው ያውቃል። በመሆኑም ፓርቲዎች በመዋጮ የሚያቋቁሙት የሽግግር መንግሥት ነው ብቸኛ የማርያም መንገዱ። ይኸው ነው።

    በርካታ ሀገሮች በኮሮና የተነሳ ምርጫ አራዝመዋል፤ የትኛው ሀገር ነው የሽግግር መንግሥት የመሠረተው? የሽግግር መንግሥት የተወሰነ ጊዜ ተሰፍሮለት የሚመሠረት ነው። አሁን ያጋጠመው ችግር ወረርሽኝ ነው፤ 6 ወር ወይም ዓመት ሊወስድ ይችላል፤ አናውቅም።

    ለሁለቱም ―
    ፖለቲከኛ መሆን ካሻችሁ ሕዝቡን እወቁት፤ አክብሩት። አክብሮታችሁ ቀርባችሁ ከማወቃችሁ ይሁን። ሕዝብን የማያከብር ፖለቲከኛ ሕዝብን ሊመራ አይችልም። ሕዝብን አክብሩ። ሕዝብ ጉልበት ስትፈልጉ የምትገዙበት የሚስጢር ኪሳችሁ ሳንቲም፤ ስልጣን ሲርባችሁ እየነቀላችሁ የምትጥዱት የጓሮአችሁ ጎመን አድርጋችሁ አትኩጠሩት።

    በድሉ ዋቅጅራ

    የጃዋርና የልደቱ

    Anonymous
    Inactive

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ መከሰትን ተከትሎ 111 የንጽህና መጠበቂያ አምራቾች ዘርፉን ተቀላቅለዋል

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በሀገሪቱ ከተከሰተ በኋላ ለ111 የንጽህና መጠበቂያ አምራቾች ፍቃድ መስጠቱን የኢትዮጵያ ምግብና መድኃኒት ባለሥልጣን (የቀድሞው የኢትዮጵያ የምግብ መድኃኒትና ጤና ክብካቤ አስተዳደር ባለስልጣን (EFDA)) አስታወቀ።

    የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ሄራን ገርባ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደገለጹት፥ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በኢትዮጵያ ከተከሰተ በኋላ በሕብረተሰቡ ዘንድ የንጽህና መጠበቂያ ቁሶች ፍላጎት ጨምሯል። በወቅቱ የፍላጎቱና የምርት መጠን ባለመመጣጠኑ በተለይም የሳኒታይዘር እና የአልኮል ምርት እጥረት አጋጥሞ ነበር።

    ችግሩን ለመፍታት ባለስልጣን መሥሪያ ቤቱ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት በዘርፉ ከተሰማሩና ፍላጎት ካላቸው አምራቾች ጋር ውይይት ማካሄዱንም አስታውሰዋል። በዚህም አምራቾች ሳኒታይዘር እና አልኮል በስፋትና በጥራት እንዲያመርቱ የሚያስችል ስምምነት ተደርጎ ወደ ሥራ የገቡበት ሁኔታ መኖሩን ነው ዋና ዳይሬክተሯ የተናገሩት።

    ባለስልጣኑም አምራቾቹ ደረጃውንና ጥራቱን የጠበቀ ሳኒታይዘር እና አልኮል በስፋት እንዲያመርቱ ለማስቻል የሚያግዝ ጊዜያዊ መመሪያ አውጥቶ ተግባራዊ አድርጓል።

    ዳይሬክተሯ እንዳሉት፥ መመሪያው አምራቹ ስለምርቱ ሁኔታና ጠቀሜታ የሚያቀርበው የቅድመ ተግባር ሀሳብ (proposal) በአጭር ጊዜ ተቀባይነት እንዲኖረው የሚያስችልና የፍቃድ አሰጣጥ ሂደቱም ፈጣን እንዲሆን የሚያግዝ አሠራርን በውስጡ አካቶ የያዘ ነው። በዚህ መሠረት ዘርፉን በመቀላቀል የጥራትና የግብአት መስፈርቱን ላሟሉ 111 አምራች ፋብሪካዎች ወደምርት እንዲገቡ ፈቃድ መሰጠቱን ወ/ሮ ሄራን አስታውቀዋል።

    “ፋብሪካዎቹ በአሁኑ ወቅት የሳኒታይዘር እና የአልኮል ምርቶቻቸውን በጥራትና በሚፈለገው መጠን በማምረት ለሕብረተሰቡ እያቀረቡ ይገኛሉም” ብለዋል ወ/ሮ ሄራን።

    የምርቶቹን የጥራትና የደረጃ ሁኔታ ለመከታተልም በጊዜያዊነት የተዘጋጀው መመሪያ የቅኝት ሥራን የሚያከናውኑ አካላት ቅንጅታዊ አሠራርን ዝርዝር ሁኔታ ጭምር የሚዳስስ ነው። የቅኝት ሥራውን ከባለስልጣን መሥሪያ ቤቱ ሙያተኞች በተጨማሪ ከአዲስ አበባ የምግብ መድኃኒትና ጤና ክብካቤ ባለስልጣን እና ከጸጥታ አካላት የተወጣጣ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ የሚሠሩበት ሁኔታም ተፈጥሯል።

    ወ/ሮ ሄራን እንደገለጹት፥ የቅኝት ሥራው በገበያ ስፍራዎች፣ በሸቀጣሸቀጥ መሸጫ ሱቆች፣ በሱፐር ማርኬቶችና በመድኃኒት ቤቶች የሚከናወን ነው። በተከናወነው የቅኝት ሥራም አጠራጣሪና ከደረጃ በታች የሆኑ፣ እውቅናና የንግድ ፈቃድ የሌላቸው እንዲሁም የጥራት ደረጃቸው ዝቅተኛ የሆኑ ምርቶችን በፍተሻ መያዝ ተችሏል።

    “በዚህም ባለስልጣኑ እነዚህን ምርቶች ከገበያ የመሰብሰብና የማስወገድ ሥራ እና አቅራቢዎቹንም ተጠያቂ የማድረግ ተግባር አከናውኗል” ይላሉ ወ/ሮ ሄራን። በቁጥጥር ሥራው እርምጃ ከተወሰደ በኋላ የተወሰኑ አምራቾች የምርት ጥራታቸውን በማሻሻል በአዲስ መልክ ወደ ምርት ለመግባት እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውንም አመልክተዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ

Viewing 15 results - 271 through 285 (of 730 total)