Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 346 through 360 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ በተቋሙ በተከሰተ ግጭት ምክንያት ተቋሙን ለቀው የሄዱ ተማሪዎችን በድጋሚ ለመቀበል ዝግጅቱን ያጠናቀቀ ሲሆን የተቋሙ መምህራንም ለተማሪዎች የማካካሻና የማካካሻ ስልጠናዎችን ለመስጠት መዘጋጀታቸው ተገልጿል።

    ደሴ (ወሎ ዩኒቨርሲቲ) – የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን የትርምስ ማዕከል ለማድረግ ጥቅመኞችና የፖለቲካ ቁማርተኞች ገንዘብ የጥፋት ተልዕኮ ፈጻሚ መልምለው መንቀሳቀስ ከጀመሩ ውለው አድረዋል። ይህም የጥፋት ተልዕኮ በአማራና በኦሮሚያ ክልል ያሉ ሁሉንም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለማንኳኳት ሞክሯል። ይህንኑ እኩይ ተግባር እልባት ለመስጠት የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኔስተር አጀንዳና ተልዕኮ ቀርጾ በሁለቱ ክልሎች በሚገኙ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ያሉ አካላትን የማወያየት ሥራ ሠርቷል።

    በዚሁ ውይይት በወሎ ዩኒቨርሲቲ በተማሪዎች መካከል የተከሰተው አለመግባባት በእርቀ ሰላም ተፈቶ ወደ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደቱ ተጀምሯል። የወሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን በዚህ የይቅርታና የፍቅር መድረክ ‘የሰላም መሠረቱ ይቅርታ ነው፣ በጋራ ስንሆን ብዙ ሀብት ያለን ህብር ነን፣ አባቶቻችን ቋንቋና ሀይማኖት ሳይገድቧቸው ኩርማን ዳቦ ተካፍለው ያስረከቡንን ሀገር ያልኖርንበትን ዘመን ታሪክ በመጥቀስ እርስ በርስ ከሚያጠፋፋና ሀገርን ከሚያፈርስ መጥፎ ታሪክ በመቆጠብ በይቅርታ ሀገርን የማዳን ሥራ መሥራት ይጠበቅብናል’ ሲሉ ገልጸዋል። ታላላቆችን የአማራና የኦሮሞ ሕዝቦች ለማጋጨት ገንዘብ መድበው የሚንቀሳቀሱ አካላት ተማሪዎች መጠቀሚያ መሆን የለባቸውም ያሉት የደሴ ከተማ ከንቲባ አቶ አበበ ገ/መስቀል የከተማ አስተዳደሩ የውጭ ተልዕኮ አንግበው የሚቀሳቀሱ አካላትን ከዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ ጋር በመተባበር የተቋሙን ሰላም ለማረጋገጥ እንደሚሠሩ ተናግረዋል።

    የፌደራል መንግሥት ተወካይ የሆኑት አቶ ብሩክ ከበደ በበኩላቸው በወቅቱ እየታየ ያለው ሁኔታ ሀገራችን ኢትዮጵያ በተስፋና በስጋት ውስጥ እንድትሆን አድርጓታል በማለት ሀገር በማፍረስ ላይ የተጠመዱ አካላት ያልኖርንበትን ዘመን ታሪክ እያመገሉ ከሚያጋጩ አካላት እኩይ ሴራ በመጠንቀቅ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር የማስቀጠል ታሪካዊ ኃላፊነት እንድወጡ ለተማሪዎች ጥሪ አስተላልፈዋል። አያይዘውም አቶ ብሩክ የፌደራል መንግሥት በአማራና በኦሮሚያ ክልል ያሉ 22ቱም ዩኒቨርሲቲዎች ሰላም እንዲጠበቅና ተማሪዎች በተመደቡበት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመልሰው ገብተው እንዲማሩ እየሠራ እንደሆነ ገልጸዋል። በዚህ የእርቅ ሥነ-ሥርዓት የሀይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች ተማሪዎችን ወደ አንድነት የሚያመጡ መልዕክቶችን አስተላልፈዋል። ወሎ ዩኒቨርሲቲ በተቋሙ በተከሰተ ግጭት ምክንያት ተቋሙን ለቀው የሄዱ ተማሪዎችን በድጋሚ ለመቀበል ዝግጅቱን ያጠናቀቀ ሲሆን የተቋሙ መምህራንም ለተማሪዎች የማካካሻ (tutor) ስልጠናዎችን ለመስጠት መዘጋጀታቸው ተገልጿል።

    ምንጭ፦ ወሎ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    በዲዛይን መዘግየት፣ የግንባታ ግብዓቶች በወቅቱ ባለመቅረባቸው እና በተቋራጮች እቅም ውሱንነት ምክንያት ግንባታው በተያዘለት ጊዜ ያልተጠናቀቀው ቡሬ የተቀናጀ አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ እስከ  የካቲት ወር መጨረሻ (2012 ዓ.ም.) ድረስ ሙሉ በሙሉ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ ነው።

    አዲስ አበባ (ንግድ እና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር) – ቡሬ የተቀናጀ አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ (Bure Integrated Agro-industry Park) ግንባታ 79 በመቶ መጠናቀቁን የኢንዱስትሪ ፓርኩ ሥራ አስኪያጅ አቶ ዳኛቸው አስረስ ገልጸዋል።

    በ1000 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈውና በሦስት ምዕራፍ የሚገነባው ይህ ኢንዱስትሪ ፓርክ የመጀመሪያው ዙር ግንባታ 79 በመቶ መጠናቀቁን የተናገሩት ሥራ አስኪያጁ፥ ለማጠናቀቅ ከተያዘለት ጊዜ 20 በመቶ መዘግየቱንም ተናግረዋል።

    በዲዛይን መዘግየት፣ የግንባታ ግብዓቶች በወቅቱ ባለመቅረባቸው እና በተቋራጮች እቅም ውሱንነት ምክንያት ግንባታው በተያዘለት ጊዜ ሳይጠናቀቅ ቀርቷል ያሉት አቶ ዳኛቸው፥ እስከ የካቲት 30 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ ሙሉ በሙሉ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ ነው ሲሉ ገልጸዋል።

    የውሃ፣ የመንገድና የሌሎች መሠረተ-ልማት ግንባታ እየተካሄደ መሆኑን የተናገሩት ኃላፊው፥ የመብራት ኃይል አቅርቦት ሥራ ባለመጀመሩ ፓርኩ ተገንብቶ እንደተጠናቀቀ ወደ ማምረት ሥራ ለመግባት እንቅፋት እንደሚሆንባቸውም ጠቅሰዋል።

    በንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የቆዳና ጨርቃ-ጨርቅ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ተካ ገብረኢየሱስ በበኩላቸው የፓርኩ የመጀመሪያ ዙር ግንባታ ሲጠናቀቅ ሥራ ለመጀመር የሚያስችል ኃይል ጊዜያዊ በሆነ አማራጪ እንደሚቀርብና በዘላቂነት ለኢንዱስትሪ ፓርኩ የሚያስፈልገውን ንዑስ ጣቢያ (sub-station) ለመገንባት ከቻይና መንግስት ጋር ስምምነት ተደርሷል ብለዋል።

    በ4.3 ቢሊየን ብር እየተገነባ ያለው ይህ ፓርክ ግንባታው ሲጠናቀቅ በሀገሪቱ ያለውን የገበያ ክፍተት ከመሙላቱም በተጨማሪ ከፍተኛ የሆነ የውጪ ምንዛሪ ያስገኛል ያሉት አቶ ዳኛቸው፥ ከፓርኩ ግንባታ ጎን ለጎን 7 የገጠር የሽግግር ማዕከላት ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል።

    ቡሬ የተቀናጀ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ፓርክ ሦስቱም የግንባታ ምዕራፎች ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት ሲጀምር ከ3 መቶ ሺህ እስከ 4 መቶ ሺህ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ እድል ይፈጥራል። ዘገባው የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ነው።

    ምንጭ፦ ንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ቡሬ የተቀናጀ አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ

    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እና አሞሌ ዲጂታል ዋለት ድርጅት የአዲስ አበባ ስታዲየም የትኬት ሽያጭን በጋራ ለማከናወን ስምምነት አደረጉ
    —–

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እና አሞሌ ዲጂታል ዋለት ድርጀት (ዳሸን ባንክ) [Amole Digital Wallet] የአዲስ አበባ ስታዲየም የትኬት ሽያጭን በዘመናዊ መንገድ ለማከናወን የሚያስችላቸውን ስምምነት በተወካዮቻቸው ተፈራርመዋል። በዚህም መሠረት የአዲስ አበባ ስታዲየም የመግቢያ ትኬቶች በሙሉ በአሞሌ የገንዘብ መቀበያዎች ማለትም በሁሉም የፖስታ ቤቶች፣ ሸዋ ሱፐር ማርኬት፣ ህዳሴ ቴሌኮም እና ዳሽን ባንክ (በሁሉም ቅርንጫፎች) እና አሞሌ በሚያዘጋጃቸው ሌሎች ተቋማት የሚከናወን ይሆናል።

    በዚህም መሠረት ስፖርት ክለቡ አዲስ አበባ ስታድየም ውስጥ ለሚያደርጋቸው ውድድሮች የእጅ በእጅ የትኬት ሸያጭ በየትኛዎቹም የስታዲየሙ በሮች እንደማይከናወን ክለቡ አስታውቋል።

    ክለቡ በተጨማሪ እንዳስታወቀው፥ የዓመት የስታዲየም ቅድመ-ክፍያ ሲከፍሉ የነበሩ 289 ደንበኞች አሁንም በቅድሚያ ቦታቸውን ማስከበር የሚችሉ ሲሆን ከዚህ ቀደም ለሁሉም በስታዲየሙ ለሚደረጉ ውድድሮች አጠቃላይ ሲጠየቅበት የነበረው የክፍያ ሂደትም ማስተካከያ ተደርጎበታል። ይህም የዓመት ክፍያ ከሁለቱ የከተማው ቡድኖች የደርሶ-መልስ ውድድር ውጪ የሚፈልጉትን ቡድን የዓመት ክፍያ መክፈል የሚያስችል ማሻሻያን ማድረግ ተችሏል።

    በመሆኑም የዓመት ክፍያው 9,000 (ዘጠኝ ሺህ) ብር ሲሆን ይህም የሁለቱንም ቡድኖች ሙሉ ጨዋታዎችን (30 ጨዋታዎች) ለመመልከት የሚያስፈልግ የብር መጠን ነው። ከዚህ ውስጥ የኢትዮጵያ ቡናን ጨዋታ ብቻ ለመመልከት የፈለገ ተመልካች የ14 ጨዋታዎች 4,200 (አራት ሺህ ሁለት መቶ) ብር የሚከፍል ሲሆን የሁለቱን የከተማው ደርቢ ጨዋታዎችን እንደ ማንኛውም ተመልካች ከአሞሌ የገንዘብ መቀበያዎች ገዝቶ የሚገባ ይሆናል። ከሌሎች የዓመት ክፍያ ከሌላቸው ቅድሚያ የሚሰጣቸው ይሆናል። ሁለቱም የከተማው ቡድኖች ጨዋታዎች በሁለቱ ክለቦች ስምምነት የሚፈፀም ይሆናል።

    በዚህም መሠረት የአዲስ አበባ ስታዲየም የመግቢያ ዋጋ የሚከተለው ይሆናል

    • ክቡር ትሪቡን፦ 300 ብር
    • ጥላ ፎቅ፦ 200 ብር
    • ከማን አንሼ ባለ ወንበር፦ 100 ብር
    • ከማን አንሼ ወንበር የሌለው፦ 50 ብር
    • ካታንጋ፦ 30 ብር
    • ሚስማር ተራ እና የንጋት ኮከብ፦ 20 ብር

    የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብዓመታዊ የክቡር ትሪቢዩን የመግቢያ ትኬቶች ከኅዳር 27 ቀን 2019 ዓ.ም. ጀምሮ ጀምሮ እየተሸጠ ይገኛል።

    ስለ አሞሌ ዲጂታል ዋለት ለማንበብ እዚህ ይጫኑ

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    አሞሌ ዲጂታል ዋለት

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ደረጃውን የጠበቀና ወቅቱን ያገናዘበ የቴክኖሎጂ ስልጠና ማዕከል ለማስገንባት የሚያስችለውን የመግባቢያ ስምምነት ከኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን፣ ዲዛይንና ሱፐርቪዥን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ጋር ጥቅምት 03 ቀን 2012 ዓ.ም. በተቋሙ መሰብሰቢያ አዳራሽ ተፈራርሟል።

    ሁለቱን ተቋማት ወክለው የመግባቢያ ሰነዱን የፈረሙት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሽፈራ ተሊላና የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን፣ ዲዛይንና ሱፐርቪዥን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ኢንጂነር ነገደ አባተ ናቸው።

    የቴክኖሎጂ ስልጠና ማዕከሉ ግንባታ በሁለት ምዕራፍ ተከፍሎ የሚከናወን ሲሆን፥ በምዕራፍ አንድ የግንባታ ጥናትና የዲዛይን ሥራዎች፣ በምዕራፍ ሁለት የህንጻ ግንባታ ቁጥጥር እና የውል አስተዳደር ሥራዎች የሚከናወኑ ይሆናል።

    የስልጠና ማዕከሉ ግንባታ የሚከናወነው አዲስ አበባ ኮተቤ በሚገኘው 16.9 ሄክታር መሬት ላይ ነው። ግንባታው የሚከናወነው የከተማውን ሕግና የህንጻ ግንባታ ስታንዳርድ እንዲሁም ማስተር ፕላን መሠረት በማድረግ መሆኑንም በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ወቅት ተገልጿል።

    የማዕከሉ ሕንጻ ግንባታ አጠቃላይ ወጪ በአማካሪ ማሀንዲሱ ጨረታ ከወጣ በኋላ የሚወሰን ሲሆን፥ የማዕከሉ ማስተር ፕላን ለማዘጋጀት፣ ለዲዛይንና ኮንትራት አሰተዳደር ሥራዎች ከ37 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ይደረግበታል።

    የቴክኖሎጂ ማዕከሉ የመማሪያ ክፍል፣ የአስተዳደር ህንጻ፣ ቤተ-መፅሐፍት፣ የምርምርና የልህቀት ማዕከል፣ መኝታ ቤቶች፣ ልዩ ልዩ የስፖርት ማዘውተሪያ ሜዳዎችና የማሰራጫ (distribution) ሥራዎች ሠርቶ ማሳያ የሚኖረው ይሆናል።

    የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሽፈራ ተሊላ በፌርማ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የሚገነባው የስልጠና ማዕከል ተቋሙ የጀመራቸውን የለውጥ ሥራዎች በቴክኖሎጂ በመደገፍ የተቋሙን አገልግሎት አሰጣጥ ቀልጣፋ፣ ጥራት ያለውና አስተማማኝ ለማድረግ፣ የአቅም ውስንነቶችንና የመረጃ ከፍተቶች ለመሙላት ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል።

    ዋና ሥራ አስፈጻሚው አክለውም የኦፕሬሽንና የቢዝነስ ሥራዎችን ለማቀላጠፍ፣ የከፍተኛ ቮልቴጅ እቃዎችን ጥራት ለመፈተሽና ለማረጋገጥ፣ የማሰራጫ (distribution) መስመሮችን ለመቆጣጠር የሚያስችል ስካዳ ሲስተም (SCADA system) ተግባራዊ ለማድረግም ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል።

    የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን፣ ዲዛይንና ሱፐርቪዥን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ኢንጅነር ነገደ አባተ በበኩላቸው የስልጠና ማዕከሉ አቅም ያላቸው ባለሞያዎችን ለመፍጠር የሚያስችልና ለሌሎች ተቋማትም ማሳያ በመሆኑ በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ በትኩረት እንደሚሰሩ ተናግረዋል።

    የስልጠና ማዕከሉ ግንባታ የጥናትና የዲዛይን ሥራዎችን ሙሉ ለሙሉ ከተጠናቀቁ በኋላ የሚጀመር መሆኑን በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ተጠቁሟል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት

    Semonegna
    Keymaster

    ብርሃን ባንክ የ10ኛ ዓመት የምሥረታ ክብረ በዓሉን ሲያከብር ለኢትዮጵያ ልብ ህሙማን ሕፃናት መርጃ ድርጅት የ3 ሚሊዮን ብር እንዲሁም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የአጥንት ህክምና ክፍል የ2 ሚሊዮን ብር ድጋፍ አድርጓል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ብርሃን ባንክ የ10ኛ ዓመት የምሥረታ ክብረ በዓሉን ህዳር 16 ቀን 2012 ዓ.ም. በተለያዩ ሥነ-ሥርዓቶች በስካይላይት ሆቴል በደማቅ ሁኔታ አክብሯል። በዝግጅቱ ባንኩ ለአገልሎት ክፍት ከሆነበት ከከፈረንጆች ጥቅምት (October) ወር 2009 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ዛሬ ያሉ የተለያዩ ዋነኛ ስኬቶቹን በማወደስ፣ የወደፊት ጊዜያትን ደግሞ በጠንካራ አቅም ሊጓዝ እንዳቀደ ነው ያስረዳው። የእለቱ ዝግጅት በሦስት ዋና ዋና የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ያነጣጠረ ሆኖ በተለያዩ መርሃግብሮች በስኬት ተጠናቅቋል።

    ከተለያዩ የህትመት እና ኤሌክተሮኒክስ ሚዲያ ተቋማት ተጋብዘው በቀረቡ የሚዲያ አካላት በተዘጋጀው የባንኩ የዲሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ እና የባንኩ ፕሬዚዳንት በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ እስከ 11፡45 ድረስ ተከናውኗል። በማስከተልም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ወንበሮቻቸውን እንደያዙ በመድረኩ ላይ በእውቅ የሙዚቃ ተጫዋቾች አማካኝነት ድንቅ የሆነ የቫዮሊን የሙዚቃ ኮንሰርት ለታዳሚያኑ ቀርቧል። ይህንንም ተከትሎ በአርቲስት ሃረገወይን አሠፋ የመድረክ አጋፋሪነት ለእንግዶቹ የሚቀርበው የአዳራሽ ውስጥ ዝግጅቱ በይፋ ተጀመረ። አርቲስት ሃረገወይን የባንኩን የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ካቀረበች እና አጠር ያለ የ10 ዓመታት የባንኩን የአመሰራረት አፅመ ታሪክ በአጭሩ አቅርባ መድረኩን እንዲረከቧት እና የእለቱን የክብር እንግዶች ወደ መድረክ እንዲጋብዙ የባንኩን ፕሬዚዳንት አቶ አብሃም አላሮን ወደ መድረኩ ጋበዘች።

    የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አብሃም አላሮ የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክት እንዲያስተላልፉ የብሔራዊ ባንክ ገዥ የሆኑትን ይናገር ደሴ (ዶ/ር) ወደ መድረክ ጋብዘው ገዥው ባንኩ በርካታ ባለአክሲዮኖችን በመያዝ ቀዳሚው የንግድ ባንክ መሆኑን ገልፀው ለመላው የባንኩ ማህበረሰብ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክታቸውን አቅርበዋል። በማስከተልም የቀረበው የባንኩ የዲሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ጉማቸው ኩሴ የእንኳን አደረሳችሁ እና እንኳን ደስ ያላችሁ መልክት ሲሆን፥ ሰብሳቢው በመልዕከታቸው የባንኩን ስኬቶች በማወደስ ቀጣይ ሥራዎችን በተሻለ አቅም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ እምነታቸውን ገልፀዋል። ይህ ዝግጅት እንዲህ ባለው መልኩ ቀጥሎ በባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ አብርሃም አላሮ አጠር ያለ የኢትዮጵያ ባንኮችን ታሪክ እና እድገት እንዲሁም ብርሃን ባንክ በ10 ዓመታት ዕድሜው ያሳየውን የአፈፃፀም ጉዞን የሚያሳይ ጥናት ቀርቧል። ፕሬዚዳንቱ ባንኩ ከምሥረታው ጀምሮ በተለያዩ ልኬቶች ያስመዘገባቸው ስኬቶቹ እጅግ አመርቂ እና ፍሬያማ የሚባሉ መሆናቸውን አብራርተው በቀጣይም እነኚህ ስኬቶቹ በላቀ መልኩ አሸብርቀው እንደሚቀጥሉ ያላቸውን እምነት ገልፀዋል።

    በማስከተል የቀረበው ለባንኩ መመሥረት እንዲሁም በተለያዩ መንገዶች ባንኩን ከምሥረታው ጀምሮ ላገዙ መሥራቾች፣ አመራሮች እንዲሁም ላለፉት አስር ዓመታት በባንኩ ላገለገሉ ሠራተኞች የእውቅና እና የምስጋና ስጦታዎችን የማበርከት ሥነ-ሥርዓት ነበር። ከምስጋና የምስክር ወረቀት (certificate) ጀምሮ 13 ሠራተኞቹን ጨምሮ ለተለያዩ ባለድርሻዎች በወርቅ በተሠሩ ስጦታዎች ተበርክቶላቸዋል። ይህንኑ መርሀ ግብር ተከትሎ ብርሃን ባንክ ለኢትዮጵያ ልብ ህሙማን ሕፃናት መርጃ ድርጅት የ3 ሚሊዮን ብር እንዲሁም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የአጥንት ህክምና ክፍል 2 ሚሊዮን ብር ድጋፍ አድርጓል። ይህንኑ ስጦታ የማዕከላቱ ተጠሪዎች ዶክተር ሄለን በፈቃዱ (የልብ ሕሙማን ህፃናት ድርጅትን በመወከል) እና ዶክተር ብሩክ ላምቢሶ (የአጥንት ህክምና ክፍልን በመወከል) ከባንኩ የዲሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ እጅ ተቀብለዋል። ይሀንን ስጦታ ሲቀበሉም ድጋፉ በሚደረግላቸው እና የህክምና ወጪዎቻቸውን መሸፈን በማይችሉ አቅመ ደካማ ህፃናት እና አረጋውያን ስም አመስገነው ገንዘቡን ሙሉ በሙሉ ለታለመለት ዓላማ እንደሚያውሉ ከምስጋና ጋር ቃል ገብተዋል።

    በዝግጅቱ መጨረሻ ላይም የባንኩ ቀጣይ የንግድ ምልክት ወይም መለያ ምልክት ሆኖ የሚያገለግለውን አዲስ አርማ ለታዳሚያን ተዋውቆ የዕለቱ ዝግጅት በእራት መርሀ ግብር በደማቅ ሁኔታ ተገባዷል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ብርሃን ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    የሲዳማ ሕዝበ ውሳኔ ጊዜያዊ ውጤትን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ
    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ
    ህዳር 13 ቀን 2012 ዓ.ም
    ሀዋሳ

    የደቡብ ብሄር ብሄረሰቦች ሕዝቦች ክልል ምክር ቤት ኅዳር 12 ቀን 2011 ዓ.ም. ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባቀረበው ጥያቄ መሠረት የሲዳማ ዞን በክልልነት የመደራጀት ጥያቄ ሕዝብ ውሳኔ ኅዳር 10 ቀን 2012 ዓ.ም. ተካሂዷል።

    የሕዝበ ወሳኔው አፈፃፀም ተአማኒ፣ ሰላማዊ እና ፍትሃዊ አንዲሆን ለማድረግ ቦርዱ እስከ ሕዝብ ውሳኔው ድምጽ መስጫ ዕለት ድረስ በርካታ ተግባራትን ሲያከናውን ቆይቷል። ቦርዱ የሕዝበ ውሳኔውን ጥያቄ የማስፈፀም ኃላፊነቱን መወጣት የጀመረው ሂደቱ ፍትሃዊ፣ ሰላማዊ እና ተአማኒ እንዲሆን እንዲሁም በሲዳማ ዞን እና በሀዋሳ ከተማ የሚኖሩ ዜጎች ያለ አድልዎ ፍላጎታቸውን የሚገልፁበት አሠራር ለመዘርጋት የሚያስችል የሲዳማ ሕዝብ ውሳኔ አፈፃፀም መመሪያ በማጽደቅ ነው።

    ከዚህ በተጓዳኝ የሕዝብ ወሳኔውን የአፈፃፀም የጊዜ ሰሌዳ በማዘጋጀት ለሚመለከታቸው የክልሉ እና የዞን መስተዳደር አካላት እንዲደርስ ለሕዝብም ይፋ እንዲሆን ተደርጓል። ቦርዱ በሕዝብ ውሳኔው እቅድ አፈፃፀም ከክልሉና የዞኑ መስተዳደር አካላት ጋር በርካታ ውይይት እና ስምምነቶችን አድርጓል። በዚህም መሠረት ለሕዝብ ውሳኔ ማስፈፀሚያ የሚያስፈለገውን በጀት በክልሉ መንግሥት እንዲፈቀድ ተደርጓል። ሕዝብ ውሳኔው በሰላማዊ ሁኔታ ለማስፈፀም አስፈላጊ ሁኔታዎችን የክልሉ ምክር ቤት አስቀድሞ እንዲፈጽም በጠየቀው መሠረት የሕዝቡ ውሳኔ የሲዳማ ዞን በክልልነት እንዲደራጅ የሚል ከሆነ በዞኑ ውስጥ የሚኖሩ ሌሎች ብሔረሰቦች መብት ጥበቃንና አዲስ በሚፈጠረው እና ነባሩ ክልል መሃከል የሚኖረውን የሃብት ክፍፍል የሚወሰንበት አስተዳደርና በሕግ ማእቀፍ አውጥቶ አቅርቧል።

    በቅድመ ሕዝበ ውሳኔ ዝግጅት በቦርዱ ባለሞያዎች የመስክ ጥናት አካሂደው የድምፅ መስጫ ጣቢያዎችን መረጃ አደራጅተዋል። በዚህም መሠረት ለሕዝበ ውሳኔው ማስፈጸሚያ 1692 ምርጫ ጣቢያዎች የተቋቋሙ ሲሆን ከድምጽ ሰጪዎች ምዝገባ በኋላ ተጨማሪ 169 የድምፅ መስጫ ጣቢያዎች ተደራጅተዋል። የሕዝብ ወሳኔው አፈፃፀም ሰላምና ደኅንነት ለማስጠበቅ እንዲያስችል የክልሉ፣ ከዞኑ፣ ከሀዋሳ ከተማ እንዲሁም የፌደራል የጸጥታ ተቋማት እና አስተዳደር ተቋማት የሕዝበ ውሳኔው ፀጥታ ዕቅድ አዘጋጅተው አቅርበዋል። የዕቅዱንም አፈጻጸም ቦርዱ በጋራ ሲከታተል ቆይቷል። ከቅድመ ሕዝበ ውሳኔ ዝግጅት እስከ ድኅረ ሕዝበ ውሳኔ የነበረው የፀጥታና ደኅንነት ሁኔታ በዚህ ዕቅድ መሠረት በጋራ ኮሚቴ በየጊዜው እየታየ ሰላማዊ ሕዝበ ውሳኔ ለማካሄድ ተችሏል።

    ሕዝበ ውሳኔውን በገለልተኝነትና በሕግ መሠረት የሚያስፈፅሙ 6843 አስፈፃሚዎችን ከአዲስ አበባ ከተማ እና ኦሮሚያ ክልል አከባቢዎች በመመልመል በዞኑ ያሰማራ ሲሆን ሁሉም አስፈጻሚዎች ሕዝበ ውሳኔውን እንዴት እንደሚያስፈጽሙ ስልጠና ተሰጥቷቸዋል። ስልጠናውም ቀድመው የአሰልጣኞች ስልጠና በወሰዱ 20 አሰልጣኞች ለ5 ቀናት የተከናወነ ሲሆን ሁሉም አስፈጻሚዎች የታተመ የማስፈጸሚያ መመሪያ (manual) እንዲኖራቸው ተደርጓል።

    የመራጮች ምዝገባ በዞኑ እና በሀዋሳ ከተማ መስተዳድር ለሚኖሩ ማንኛውም ሕጋዊ መስፈርቱን ለሚያሟሉ ዜጎች ክፍት ሆኖ ከጥቅምት 27 እስከ ህዳር 06 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ ምዝገባው ተካሂዶ 2,280,147 ድምጽ ሰጪዎች ተመዝግበዋል።

    የድምጽ ሰጪዎች ሕዝበ ውሳኔው ድምጻቸውን ለመስጠት እንዲመዘገቡ ለመቀስቀስ በሬዲዮና በቴሌቪዥን የተለያዩ የምዝገባ መስፈርቶችን የሚገልጹ እንዲሁም ስለድምጽ አሰጣጡ የሚያብራሩ መልእክቶች ተላልፈዋል። በድምጽ ሰጪዎች ምዝገባና ድምጽ አሰጣጥ ሂደቱ የዜጎች መብት እንዳይገደብ እና የሂደቱን ሰላማዊነት ለማረጋገጥ የሚያግዙ የተለያዩ ተግባራት ተከናውነዋል። ከነዚህም መካከል የመጀመሪያው የቦርዱ አመራር አባላት በሀዋሳበይርጋለም፣ በወንዶ ገነት፣ በበሌላ፣ በመዘዋወር የድምጽ ሰጪዎች ምዝገባና ድምጽ ሰጪዎች ድምጽ አሰጣጥ ሂደት ክትትል በማድረግ የታዩ ጉድለቶች እና የአሠራር ዝንፈቶች እንዲስተካከሉ ያደረጉ ሲሆን፣ በተጨማሪም ዜጎች በድምጽ ሰጪዎች ምዝገባ እንዲሁም በድምጽ መስጠት ሂደቱ የታዘቧቸውን ግድፈቶች በቀጥታ ለቦርዱ ለማሳወቅ እንዲችሉ የቀጥታ የስልክ መስመሮች ተዘጋጅተው ለመገናኛ ብዙኃን እና ማኅበራዊ ሚዲያ ይፋ ተደርጓል። በደረሱት ጥቆማዎችም መሠረት የተለያዩ የማስተካከያ እርምጃዎች እንዲሁም መረጃዎች ሲሰጡ ቆይተዋል።

    በቦርዱ አባላት በተደረጉ ጉብኝቶች እና ቀደም ብሎ ከዞኑ እና ከክልል መስተዳድር ተቋማት ጋር በተደረጉ ተከታታይ ግንኙነቶች በሕዝበ ውሳኔው ሂደት በርካታ ማስተካከያዎች የተደረጉ ሲሆን ከነዚህም ጥቂቶቹ፦

    • የአካባቢ ሚሊሻ አባላት የምርጫ ጣቢያዎችን ጸጥታ አጠባበቅ ምንም አይነት ሚና እንዳይኖራቸው ተደርጓል፤
    • በሕዝበ ውሳኔው አፈጻጸም ያልተገባ ጣልቃ ገብነት የፈጸሙ ሰዎች በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርጓል፤
    • በሕዝበ ውሳኔው መራጮች ምዝገባ እና ድምጽ መስጠት ሂደት ሁለቱም አማራጮችን የሚወክሉ ወኪሎች አንዲገኙ ጥረት ተደርጓል፤
    • የተጓደሉ የሕዝበ ውሳኔ ማስፈጸሚያ ቁሳቁሶች በፍጥነት እንዲሟሉ ተደርጓል።

    የሕዝበ ውሳኔውን ሂደት ሰላማዊ ፣ ፍትሃዊነት እና ግልጽነቱን ለማረጋገጥ፣ እንዲሁም ለወደፊት መሻሻል ላለባቸው አሠራሮች ትምህርት ለመውሰድ ለ128 የሲቪል ማኅበራት ታዛቢዎች እና 74 የአገር ውስጥና የውጪ ሚዲያ ጋዜጠኞች ሂደቱን እንዲታዘቡና እንዲዘግቡ የሚያስችል እውቅና ተሰጥቷል። በተጨማሪም ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ጋር በመነጋገር የኮሚሽኑ 20 ታዛቢዎች ሕዝበ ውሳኔውን እንዲታዘቡ ተደርጓል። በኢትዮጵያ መንግሥት ሕዝበ ውሳኔውን እንዲታዘቡ ፍቃድ የተሰጣቸው የአሜሪካን መንግሥት ወኪሎችና ዲፕሎማቶች ሕዝበ ውሳኔን እንዲታዘቡ አስፈላጊው ድጋፍ ተደርጓል።

    የድምጽ ሰጪዎች ምዝገባ ከተጠናቀቀበት እስከ ድምጽ መስጫው ቀን ባሉት ጥቂት ቀናት ቦርዱ የድምጽ መስጫ ቁሳቁሶችን ያሰራጨ ሲሆን በዚህም ሂደት 3000 የድምጽ መስጫ ሳጥኖች እና 2.5 ሚሊዮን በላይ (መጠባበቂያን ጨምሮ) የድምጽ መስጫ ወረቀቶች እንዲሁም የተለያዩ ቅጾችና ቁሳቁሶች ስርጭት ተከናውኗል።

    በሕዝበ ውሳኔው ሂደት ጸጥታ እና ደኅንነት አስመልክቶ ቦርዱ ሂደቱን በሚመራበት ወቅት የተለያዩ መንገዶችን በመጠቀም መረጃ በመሰብሰብ፣ በሀዋሳ ከተማ እንዲሁም በሌሎች ወረዳዎች የሚገኙ ምርጫ ጣቢያዎች የመስክ ጉብኝት አድርጓል። ከአስተዳደር ወሰን ጋር በተያያዘ እና ቀድሞ ግጭት በነበረባቸው የተወሰኑ ቀበሌዎች ከማኅበረሰብ ክፍሎች የቀረቡ አቤቱታዎችን በማዳመጥ የቦርድ አመራር አባላት በቦታው በመገኘት የመስክ ቅኝቶችን አድርገው ከቀበሌ አስተዳደሮች ጋርም ውይይት አድርገዋል። ከውይይቱም በተጨማሪ የሲዳማ ዞን እና የደቡብ ክልል የጸጥታ አካላት፣ የፌደራል ፓሊስ እንዲሁም የመከላከያ ሰራዊትን ያካተተ የፀጥታ ችግሮችን በጋራ የሚያይ መድረክ በማቋቋም ሂደቱ ሰላማዊ እንዲሆን ተደርጓል።

    ኅዳር 10 ቀን 2012 ዓ.ም. የተከናወነው የድምጽ መስጠት ሂደት ሰላማዊ እና ጉልህ የሎጄስቲክስ ችግር ያልታያበት ሲሆን አንዳንድ ቦታዎች ላይ የመራጮች ቁጥር ከፍተኛ በመሆኑ ሰልፎች ከመኖራቸው በስተቀር በታቀደበት ሁኔታ ተጠናቋል። በዕለቱ የቦርድ አመራር አባላት የመስክ ጉብኝቶችን ያካሄዱ ሲሆን የምርጫ ቆጠራውም በዕለቱ ተጠናቆ በየምርጫ ጣቢያዎቹ ተለጥፏል። በዕለቱ ከመራጮች የሚመጡ ጥቆማዎችንም መሠረት በማድረግ የተለያዩ እርምት እርምጃዎች ሲከናወኑ ውለዋል።

    በዚህም መሠረት በአጠቃላይ ከተመዘገበው 2,280,147 መራጭ 2,277,063 ሰው ድምጹን ሰጥቷል። ይህም የምርጫ ቀን የድምጽ መስጠት ተሳትፎ (voter turnout) 99.86 በመቶ መሆኑን ያሳያል። ሲዳማ በነባሩ ክልል ውስጥ እንዲደራጅ ጎጆ ምልክትን የመረጠ ሰው ብዛት 33,463 ሲሆን የሲዳማ በክልልነት መደራጀትን ሻፌታን የመረጠ ሰው ብዛት 2,225,249 ነው። በውጤቱም ሻፌታ የመረጠው 98.51 % ሲሆን ጎጆን የመረጠው 1.48 % ነው። ። በሂደቱ የዋጋ አልባ ድምጽ ቁጥር 18,351(0.01%) ነው። የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 47/2/ እና /3/ ማንኛውም ብሄር ብሄረሰብ ወይም ሕዝብ የራሱ ክልል የመቋቋም መብት አለው በማለት በሚደነግገው መሠረት፥ የሲዳማ ሕዝበ ውሳኔ ሕጋዊና ሰላማዊ በሆነ ሁኔታ ተፈጽሟል። የዞኑ ነዋሪዎች በነፃ ፈቃዳቸው በሰጡት ውሣኔ መሠረት ሲዳማ ክልል ሆኖ መደራጀት የሚያስችለውን ድምፅም በዚህ ውሳኔ አግኝቷል።

    የሕዝበ ውሳኔው ሂደት ሰላማዊና ተአማኒ እንዲሁም ከፍተኛ የሕዝብ ተሳትፎ የታየበት ነው። ሕዝበ ውሳኔው ዜጎች መብታቸውን በሰላማዊ መንገድ ተግባራዊ ያደረጉበት እና በሀገራችን የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ አንድ እርምጃ ነው ብሎ ቦርዱ ያምናል። በውጤቱ መሠረትም በሕገ-መንግስቱ አንቀጽ 47/3/መ ላይ እንደተጠቀሰው የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል ምክር ቤት እና በሲዳማ ዞን አስተዳደር የሕዝቡን ድምጽ ባከበረ፣ ሰላማዊ እና ግልጽ በሆነ መልኩ እንዲሁም ሽግግሩን ጊዜን በጠበቀ ሁኔታ በማከናወን የስልጣን ርክክቡን በአግባቡ አከናውነው ይህንን ሕዝበ ውሳኔ ውጤት እንደሚያስፈጽሙ ቦርዱ የጸና እምነት አለው።

    ያጋጠሙ ተግዳሮቶች
    የሕዝበ ውሳኔው አፈፃፀም ሰላማዊና ሕጋዊ መሆኑ በዚህ ሂደት የተገኘ በጎ ውጤት ሲሆን፥ ለዝግጅት ከነበረው አጭር ጊዜም አንጻር የቦርዱ አፈጻጸም የተሳካ ነው ብሎ ያምናል። የአፈፃፀም ሂደቱ ጠቃሚ ትምህርት የተገኘበት መሆኑን ያህል ተግዳሮቶች የነበሩበት በመሆኑ ለቀጣይ ትምህርት ይሆን ዘንድ የሚከተሉትን ማንሳት ተገቢ ይሆናል፤

    • የሕግ ማዕቀፍ እንዲወጣ (የአነስተኛ ቡድኖች መብት ጥበቃ፤ የሀብት ክፍፍል) በቦርዱ የቀረበው ጥያቄ በክልሉ ምክር ቤት የተሰጠው ምላሽ መዘግየት፤
    • የሕዝበ ውሳኔው ቅስቀሳ ሂደት የአንድን ወገን አማራጭ ብቻ የቀረበበት መሆኑ እና የሕዝበ ውሳኔውን ሂደት እንዲታዘቡ የክልሉ መንግሥት ወኪሎች እንዲመድብ በተደጋጋሚ ጥያቄ ቢቀርብለትም አለመመደቡ፤
    • የድምጽ መስጫ ጣቢያዎችን ለመወሰን የሚያስፈልገው የሕዝብ ቁጥር የተሟላ መረጃ አለመኖር፤
    • በተወሰኑ የሀዋሳ ከተማን የገጠር አካባቢ ድምፅ መስጫ ጣቢያዎች የማይመለከታቸው ሰዎች መገኘት፣ በድምፅ ሰጪዎች ላይ በአንዳንድ ጣቢያዎች ተፅእኖ የማሳደር ሁኔታ መታየት፤
    • በአንዳንድ ቦታዎች በድምፅ ሰጪዎች ብዛት ምክንያት የድምጽ መስጫ ጣቢያዎች መጨናነቅ መከሰቱ፤
    • በሕዝበ ውሳኔው ውጤት አገላለጽ ላይ ከሀዋሳ ከተማና ከዞኑ መስተዳድር ተቋማት ኃላፊዎች በቦርዱ ይፋዊ መግለጫ ከመሰጠቱ በፊት አስቀድሞ የመገመት (projection) እና የመግለጽ ችግር መታየቱ፤
    • በአንዳንድ የድምጽ መስጫ ጣቢያዎች በሕግ የተቀመጠን የምርጫ ጣቢያ መክፈቻ እና መዝጊያ ሰዓት አለመጠበቅ እንደዋና ተግዳሮት የሚጠቀሱ ሲሆን (ማለትም የክልሉ የጸጥታ ተቋማት፣ የደቡብ እዝ የአገር መከላከያ ሠራዊት) የሕዝበ ውሳኔ ቁሳቁስ ማጓጓዝ፣ የአካባቢ ጸጥታ እና ደኅንነትን በመጠበቅ፣ የአስፈጻሚዎች ስምሪትን እንዲሁም ድምጽ የተሰጠባቸውን ሰነዶችን ጥበቃ በማድረግ እጅግ የሚመሰገን ድጋፍ ማድረጋቸው እና በሕዝበ ውሳኔው ሂደት ከፍተኛ ቅንጅት መኖሩ እንደትልቅ ስኬት የሚነሳ ነው።

    ምስጋና
    በሲዳማ የክልልነት የመደራጀት ሕዝበ ውሳኔ እስካሁን በአገራችን ከነበረው ልምድ የተለየ እና መጀመሪያው ቢሆንም ሰላማዊ እና ሕጋዊ በሆነ ሁኔታ ሊፈጸም ችሏል። ይህንን ሕዝበ ውሳኔ ስኬታማ ለማድረግ ቦርዱ ከተለያዩ አካላት፣ ተቋማት እና ግለሰቦች ድጋፍ አግኝቷል። በዚህም መሠረት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለሚከተሉት ተቋማትና ግለሰቦች ምስጋናውን ያቀርባል።

    • በሕዝበ ውሳኔው በሰላማዊ እና ሥነ ሥርዓት ባለው ሁኔታ ለተሳተፉት የሲዳማ ዞን ነዋሪዎች በሙሉ፣
    • ከመኖሪያ አካባቢያቸው ርቀው በመሄድ ባልተሟላ አንዳንዴም በአስቸጋሪ ሁኔታ ሕዝበ ውሳኔውን ላስፈጻሙ የሕዝበ ውሳኔው አስፈጻሚዎች እና ሥራውን በማስተባበር ለደከሙ የቦርዱ ሠራተኞች፣
    • ለሕዝበ ውሳኔው አስፈጻሚዎች ምልመላ ድጋፍ ያደረጉልን፣ የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር ከንቲባ ፣ ለአዲስ አበባ ሴቶችና ሕጻናት ቢሮ፣ የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ፣ የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ፣ ለኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ
    • ለደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ምክር ቤት፣ ለደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስዳድር እና የርዕሰ መስተዳድሩ ሕህፈት ቤት፣
    • ለሲዳማ ዞን ምክር ቤት፣
    • ለሲዳማ ዞን አስተዳደር፣
    • ለሀዋሳ ከተማ ከንቲባ ጽሕፈት ቤት፣
    • ለኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሃገር መከላከያ ሠራዊትና ለአገር መከላከያ ሠራዊት ደቡብ እዝ፣
    • ለፌደራል ፓሊስ፣
    • ለደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ፓሊስ ኮሚሽን፣
    • ለሲዳማ ዞን ፓሊስ፣
    • ለሀዋሳ ከተማ ፓሊስ፣
    • ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን
    • ሕዝበ ውሳኔውን ለመታዘብ ለተሳተፉ ሲቪል ማኅበራት፣
    • የተለያዩ እገዛዎችንን ላደረጉልን የአሜሪካን የልማት ድርጅት (USAID/IFES) እና የተባበሩት መንግሥታት የልማት ድርጅት (UNDP)፣
    • ለአዲስ ፓርክ

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የሲዳማ ሕዝበ ውሳኔ

    Anonymous
    Inactive

    72 ኪሎ ግራም የምትመዝነው ETRSS-1 ሳተላይት በቻይና መንግሥት ድጋፍና በኢትዮጵያ መንግሥት በጀት የተገነባች ሲሆን፥ ለግብርና፣ ለማዕድን ፍለጋ፣ ለአካባቢ ጥበቃ፣ ለአየር ንብረት ለውጥ ክትትል/ ምርምርና ለመሳሰሉት ጥቅም ላይ ትውላለች።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ኢትዮጵያ የመጀመሪያዋን የመሬት ምልከታ ሳተላይት ታህሳስ 10 ቀን 2012 ዓ.ም. (በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር) ላይ ከቻይና ዋና ከተማ ቤይጂንግ 400 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኘው የቻይና ሳተላይት ማስወንጨፊያ ጣቢያ ወደ ህዋ ትመጥቃለች። ጉዳዩን በማስመልከት የኢፌዴሪ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ ጌታሁን መኩሪያ (ዶ/ር ኢንጂ.) እና የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ ቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት ጀነራል ዳይሬክተር ሰለሞን በላይ (ዶ/ር) ኅዳር 12 ቀን 2012 ዓም መግለጫ ሰጥተዋል። [ከአንድ ሳምንት በፊት ይህ ዜና በተዘገበበት ጊዜ ቀኑና ሰዓቱ ታህሳስ 7 ቀን 2012 ዓ.ም. ከጠዋቱ 12 ሰዓት ከ21 ደቂቃ ተብሎ የነበረ ሲሆን vኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ጌታሁን መኩሪያ (ዶ/ር ኢንጂ.) በትዊተር ገጻቸው ቀኑ ወደ ታህሳስ 10 ቀን 2012 ዓ.ም. መዛወሩን አስታውቀዋል]።

    ETRSS-1 የተሰኘችው ይህች ሳተላይት በቻይና መንግሥት ድጋፍና በኢትዮጵያ መንግሥት በጀት የተገነባች ሲሆን፥ ከቻይና መንግሥት የጠፈር ኤጀንሲ ጋር በትብብር የማምጠቅ ሥራው ይከናወናል። 72 ኪሎ ግራም (~159 ፓውንድ) የምትመዝነው ETRSS-1 ሳተላይት ለግብርና፣ ለማዕድን ፍለጋ፣ ለአካባቢ ጥበቃ፣ ለአየር ንብረት ለውጥ ክትትል/ ምርምርና ለመሳሰሉት ጥቅም ላይ ትውላለች።

    መግለጫ በሚሰጡበት ጊዜ፥ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ ጌታሁን መኩሪያ (ዶ/ር ኢንጂ.) ኢትዮጵያ የመጀመሪዋን ሳተላይት ለማምጠቅ ዝግጅቷን ማጠናቀቋ ወሳኝ ጊዜ ላይ እንደምትገኝ ማሳያ ነው ብለዋል። የሳተላይቷ ቁጥጥር ሙሉ ለሙሉ በኢትዮጵያ እና በኢትዮጵያውያን የዘርፉ ባለሙያዎች የሚከናወን እንደሚሆን ተናግረዋል። ይህንን ለማድረግም ከአዲስ አበባ ከተማ ወጣ ብሎ በተቋቋመው እንጦጦ ኦብዘርቫቶሪና የምርምር ማዕከል (Entoto Observatory and Research Center) ቅጥር ግቢ ውስጥ የመቆጣጠሪያ ጣቢያ ግንባታው ተጠናቅቋል። ይህ ጣቢያ የሳተላይቷ ደኅንነት ክትትል የሚደረግበትና ከሳተላይቷ የሚገኙ መረጃዎች የሚሰበሰቡበት ነው።

    የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ ቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት ጀነራል ዳይሬክተር ሰለሞን በላይ (ዶ/ር) በበኩላቸው በሳተላይቷ ግንባታ ከንድፍ ጀምሮ ኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች መሳተፋቸውንና በሀገር ውስጥ ከሚገኙም ሆነ ከውጭ አገራት ከመጡ ምሁራን እና ባለሙያዎች መካከል የዕውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግር የተገኘበት መሆኑን ተናግረዋል።

    ETRSS-1 ሳተላይት  ከተወነጨፈች በግማሽ ሰዓት ውስጥ ከመሬት 700 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኝ ህዋ ላይ ቦታዋን ትይዛለች። የሳተላይቷ ግንባታ 2008 ዓ.ም. ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በነበሩበት ጊዜ የተፈረመና 2009 ዓ.ም. ላይ የተጀመረ ነው።

    የሳተላይቷ መምጠቅ ኢትዮጵያ ለሳተላይት ምስል ግዢ በዓመት የምታወጣውን ከ350 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የሚያስቀር ነው።

    ምንጭ፦ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ETRSS-1 satellite

    Semonegna
    Keymaster

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ የደሴ ግቢ ተማሪዎች የአቋም መግለጫ

    ደሴ (ወሎ ዩኒቨርሲቲ) – አገራችን ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ምድረ ቀደምት ከሚባሉት ጥቂት ሃገራት አንዷ መሆኗ ኣሌ የማይባል ሃቅ ነው። በየዘመናቱ የመጡ ወራሪዎችን መክታና አሳፍራ በመመለሷ ከአፍሪካ በቅኝ ግዛት ካልተገዙ ሁለት ሃገራት አንዷ ነች። የዚህ ዋናው ሚስጢሩ የጥንት አባቶቻችንና እናቶቻችን በዘር፣ በጎጥ፣ በሃይማኖትና ሌሎች ልዩነቶች ሳይከፋፍሉ በአንድነት በመንቀሳቀሳቸው ነው። ነገር ግን ከተወሰኑ ዓመታት በፊት ጀምሮ ለኢትዮጵያ ሃገራችን እድገትና ብልጽግና ጸር የሆኑ አካላት የውስጥ ጥቅመኞችንና ሆድ-አደሮችን በመያዝ አገራችንን የትርምስ ቀጠና ለማድረግ ሌት ከቀን መሥራት ከጀመሩ ውለው አድረዋል::

    በዚህ መጥፎ ተግባር ሕይወታቸውን እያጡ ላሉ ወገኖቻችን ነብስ ይማር እያልን ይህ መጥፎ ተግባር በአስቸኳይ ይቆም ዘንድ የሚከተለውን ባለ 8 ነጥብ የአቋም መግለጫ አውጥተናል።

    1. ዩኒቨርሲቲዎች የዕውቀት ማዕድ የሚቀርብባቸው የምርምርና የቴክኖሎጂ ፈጠራ ማዕከላት በመሆናቸው የብጥብጥ ቀጠና ለማድረግ የሚደረገውን እንቅስቃሴ አጥብቀን እናወግዛለን፣
    2. እኛ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ዓለም-ዓቀፍ እውቀታችን እንዲጎለብትና እንዲሰፋ በአዕምሮ ልማት ላይ የማይነጥፍ ድጋፍን እንጂ በብሔር፣ በሃይማኖትና በፖለቲካ ልዩነት እርስ በርስ ሊያፋጁን የሚጥሩትን መንግሥት ከጐናችን ሆኖ እርምጃ እንዲወሰድልን እንጠይቃለን።
    3. በርካታው የኢትዮጵያ ሕዝብ ለዘመናት በተለያየ ምክንያት ወደ ሰሜን፣ ደቡብ ምዕራብ እና ምሥራቅ ሲንቀሳቀስ የቆየ በመሆኑ እንደሰርገኛ ጤፍ ለመለየት በማይቻልበት መልኩ ተዋሕዶና ተጋምዶ የሚገኝ በመሆኑ ሊከፋፍሉን ቢሞክሩም ሳይሳካላቸው ቆይቷል። ከተወሰኑ ዓመታት ጀምሮ ከፍተኛ ተቋማት ውስጥ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ማዕከል ተደርጐ እየተሠራ በመሆኑ በየዓመቱ ሕይወታቸው እየተቀጠፈ ያሉ ንፁሃን የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እየተበራከተ መጥቷል። ይህንን መጥሮ ተግባር እኛ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በብሔር፣ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ ወዘተ… ሳንከፋፈል በአንድነት ቁመን እንድንጓዝ ጥሪ እናስተላልፋለን።
    4. የእምነት ተቋማት የአምልኮ ቦታ ብቻ ሳይሆኑ ለረዥም ዘመናት የዕውቀት፣ የምርምር፣ የፈጠራ፣ የፍልስፍና እና የጥበብ ማዕከላት በመሆናቸው የታሪካችንና ማንነታችን አሻራዎች በመሆናቸው ቤተ እምነቶትን ማቃጠል፣ ማፍረስ፣ መዝረፍ እንዲሁም አገልጋዮቻቸውን እጅግ ኢ-ሰብዓዊና ሰይጣናዊ በመሆነ መልኩ መግደል የተለመደ እየሆነ መጥቷል። ይህ ዘግናኝ ተግባር ለእኛ የሃገር ተረካቢዎች የአዕምሮ ጠባሳ በመሆኑ መንግሥት ከእኛ ጋር በመሆን በአስቸኳይ እንዲያስቆምልን ጥሪ እናስተላልፋለን።
    5. ለፀጥታ አካላት – አለመታደል ሆነና ጠረፍና ዳር ድንበር መጠበቅ የነበረባቸው ቢሆንም እነሆ በዩኒቨርሲቲዎች ተበትነው እየጠበቁን ይገኛሉ። ለዚህ መልካም ተግባራቸው እያመሰገን ለቀጣይ ግን ተቋማት እራሳቸውን ችለው ፀጥታቸውን እንዲያስከብሩ የስልጠናና የሙያ ድግፍ በማድረግ “አሳን ማብላት ሳይሆን አሳን እንዴት ማጥመድና መብላትን” እንድታስተምሩን እንጠይቃለን!
    6. በወሎ ዩኒቨርሲቲ የኮምቦልቻ ግቢ አጣልቶ- እና አጋጭቶ-አደሮችን አንሰማም በማለት ግቢያችሁን ከአካባቢው ማኅበረሰብ፣ የፀጥታ ኃይል፣ መምህራንና ሰራተኞች ከላይ እስከታች ካለው የውስጥም የውጭም አመራር ጋር በመሆን በተለይም ሁሉም ተማሪና የተማሪ አመራሮች በአንድ በመሥራታችሁ በዚህ መልካም ተግባራችሁ አጠናክራችሁ እንድትቀጥሉ በጐነትን፣ መልካምነትንና አርዓያነትን ማድነቅ ስለሚገባን በእናንተ የኮራንና የእናንተን ፈለግ ለመከተል ቃል እንገባለን።
    7. በተፈጠረው ግጭት ፈርታችሁ ወደ ቤተሰብ የሄዳችሁ ተማሪዎች እንዲሁም ይህን ግጭት ለተራ ፖለቲካዊ ትርፍ ለመጠቀም ባሰቡ አካላት ተቀስቀሳችሁ ከግቢ የወጣችሁ ተማሪዎች እስከ ሰኞ ህዳር ኅዳር 15 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ ወደ ትምህርት ገበታችሁ ትመለሱ ዘንድ ጥሪ እናስተላልፋለን።
    8. በመጨረሻም ይህንን ችግር ለመፍታት ሌት ከቀን ደከመን ሰለቸን ሳትሉ እልባት እንዲያገኝ ለጣራችሁ የደሴ እናቶች፣ የዩኒቨርሲቲው አመራሮች፣ የጸጥታ አካሎች እንዲሁም ተማሪዎች በጣም እናመሰግናለን። በዚህ አጋጣሚ ለወደፊቱም የዘወትር ድጋፋችሁንና ምክራችሁን አትለዩን እያልን ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ከነአንድነታቸው አጥብቆ ይባርክ እንላለን።

    እናመሰግናለን።
    ወሎ ዩኒቨርሲቲ የደሴ ግቢ ተማሪዎች

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ የደሴ ግቢ ተማሪዎች የአቋም መግለጫ

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) ምክር ቤት የግንባሩ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የመራለትን የፓርቲውን ውህደት አፀደቀ። የምክር ቤቱ ስብሰባ በህዳር 11 ቀን 2012 ዓ.ም. ውሎው ኢህአዴግና አጋር ድርጅቶችን በማዋሃድ አንድ አገር አቀፍ ፓርቲ (የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ) ለመመሥረት በተጀመረው እንቅስቃሴ ላይ ትኩረት አድርጎ ከተወያየ በኋላ ነው ያጸደቀው።

    ኢህአዴግ በሥራ አስፈጻሚ ደረጃ ግንባሩ ከአጋሮቹ ጋር እንዲዋሃድና ህብረ-ብሔራዊ ፓርቲ እንዲሆን ሰሞኑን በአብላጫ ድምጽ በመወሰን ለምክር ቤቱ መምራቱ ይታወሳል። ውህዱ ፓርቲ “የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ” የሚለውን ስያሜ ተሰጥቶት ለኢህአዴግ ምክር ቤት እንዲቀርብ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው ከስምምነት መድረሱም ይታወሳል። ምክር ቤቱም ህዳር 11 ቀን ባካሄደው ስብሰባው ግንባሩና አጋር ድርጅቶቹ እንዲዋሃዱ ውሳኔውን አሳልፏል።

    የኢሕአዴግ ምክር ቤት ዛሬ የፖርቲውን ውሕደት አጽድቋል። በአዲሱ የብልጽግና ፓርቲ አማካኝነት ሁሉም የታላቋ ኢትዮጵያ ዜጎች የሚሳተፉበት ጠንካራ፣ አካታችና እውነተኛ የፌደራል ሥርዓት ለመፍጠር ቆርጠን ተነሥተናል። ጸንተንም እንታገላለን።ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በትዊተር/ፌስቡክ ገጻቸው ላይ

    የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ አባል አቶ ፍቃዱ ተሰማ የህዳር 11 ቀን የምክር ቤቱን ውሎ በማስመልከት ለኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) እንደተናገሩት፥ ምክር ቤቱ በፓርቲው ውህደት ዙሪያ ተወያይቶ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል። አቶ ፍቃዱ እንደገለጹት ምልዓተ ጉባዔው ተሟልቶ ከመከረ በኋላ ውህደቱን በሙሉ ድምጽ ነው ያጸደቀው።

    በውይይቱ ላይ የኢህአዴግ ኦዲትና ቁጥጥር ኮሚሽንም የውህደቱን አስፈላጊነት፣ ሕጋዊ አሠራርና ከደንቡ ጋር የተገናኙ ጉዳዮችን በተመለከተ ዝርዝር ጥናት ማቅረቡን ነው የገለጹት።

    በኮሚሽኑ ጥናት ውጤት መሠረትም ኢህአዴግ አገራዊ ለውጡን ለመምራትና መሠረት ለማስያዝ፣ እንዲሁም ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ የውህደቱ አስፈላጊነት ላይ ከስምምነት ተደርሷል። የውህደቱ ሂደትም ሕገ-ደንቡና ስርዓቱን የተከተለ መሆኑ ተረጋግጦ ምክክር ከተደረገበት በኋላ መጽደቁን አብራርተዋል።

    ምክር ቤቱ በሁለተኛ ደረጃ የተመለከተው የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ መርሀ-ግብርን (ፕሮግራምን) ሲሆን፤ ፓርቲው በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በማኅበራዊና በውጭ ግንኙነት ላይ የሚከተላቸውን አቅጣጫዎች በሰፊው መመልከቱን አብራርተዋል።

    ቀደም ብሎ የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ፓርቲው በመተዳደርያ ደንቡ ላይ በአገሪቷ ለሚገኙ ቋንቋዎች በሙሉ እውቅና መስጠቱ ይታወሳል። ውህዱ ፓርቲም አማርኛን ጨምሮ አፋን ኦሮሞ፣ ሶማልኛ፣ ትግርኛ እና አፋርኛ ቋንቋዎች ለሥራ ቋንቋነት የተመረጡ መሆኑንም ማስታወቁ ይታወሳል።

    የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ በፕሬዝዳንትና ምክትል ፕሬዝዳንት የሚመራ ሲሆን፤ ይህም ከዚህ ቀደም የነበረውን ሊቀ-መንበርና ምክትል ሊቀ-መንበር የሚሉትን ስያሜዎችን ይተካል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ

    Semonegna
    Keymaster

    ‘አገር የሆነች ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅ የመንግሥት ግዴታ መሆኑን’ በማሳሰብ ማኅበረ ቅዱሳን ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) ደብዳቤ ጻፈ። የደብዳቤው ሙሉ መልዕክት እንደሚከተለው ይነበባል።

    ለክቡር ዶክተር ዐቢይ አህመድ
    የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዲሪ) ጠቅላይ ሚኒስትር
    አዲስ አበባ
    ጉዳዩ፡- በተለያዩ አካባቢዎች በቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሱ ያሉ ጥቃቶች እንዲቆሙ ስለመጠየቅ

    ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሆይ፡- አስቀድመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኢትዮጵያ የሀገር ግንባታ የነበራትን ታላቅ ሚና ተገንዝበው ለቤተ ክርስቲያናችን አንድነትና ሰላም ያረጉትን አስተዋጽኦ ሳናመሰግን አናልፍም።

    ይሁንና በአሁኑ ወቅት ይህን ደብዳቤ ለእርስዎ ለመጻፍ ያነሳሳን ዐቢይ ጉዳይ በሀገራችን በየጊዜው ድንገት በሚፈጠሩ ሁከቶችና ብጥብጦች ሁሉ ምክንያት ተፈልጎ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም ካህናቶቿና ተከታዮቿ ምእመናን የአደጋ ሰለባ እንዲሆኑ እየተደረገ መምጣቱ በከፍተኛ ደረጃ አሳሳቢና አፋጣኝ መፍትሔ በመንግሥት ሊሰጠው የሚገባው ሆኖ አግኝተነዋል።

    በየትኛውም ዓለም የሚኖሩ የእምነት ተቋማት ለሀገር ግንባታና ዕድገትም ያላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑ ግልጽ ነው። እንደዚሁ ሁሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኢትዮጵያ የሀገረ መንግሥት ግንባታ የማይተካ ሚና እንደ ነበራት ግልጽ ነው። በሥነ ጥበብ፣ በኪነ ሕንፃ፣ በሥነ ሥዕል፣ በሥነ ጽሑፍ፣ በሕግ ቀረጻና ሀገራዊ ክብርና እሴትን በማስጠበቅ ከፍተኛ ሚና የተጫወተች መንፈሳዊ ተቋም ናት። በረከታቸው ይደርብንና በሕይወት የተለዩን ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በተለያዩ ጽሑፎቻቸውና አባባሎቻቸው እንዳስቀመጡት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥነ ጽሑፍ ከነፊደሉ፣ ነጻነት ከነክብሩ፣ ዘመን ከነቀመሩ፣ ሀገር ከነድንበሩ፣ አንድነት ከነጥብዓቱ ያስረከበች የኢትዮጵያ ባለውለታ ናት። ቀደም ሲል በክቡርነትዎም አንደበት እንደተነገረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሀገር ባለውለታ ከማለት ይልቅ ራሷን ሀገር አድርጎ መግለጽ የውለታዋን ታላቅነት በተሻለ ሁኔታ ያሳያል። ይህን የምታደርገው ደግሞ የሀገሪቱን ከፍተኛ ቁጥር የያዘ ሕዝብ የምትመራ እንደመሆኗ እንደ ሀገር ስለምታስብና ለሀገር ልማትና እድገት ትኩረት ሰጥታ ስለምትሠራ መሆኑን ለመረዳት አያስቸግርም ።

    ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር፡-

    ቤተ ክርስቲያን ለሀገር ያበረከተችው አስተዋጽኦና ውለታ ይህ ሆኖ ሳለ ወርቅ ላበደረ ጠጠር እንዲሉ እየተፈጸመባት ያለው ግፍ ከበጎነቷ በተቃራኒ ከመሆኑም በላይ ከጊዜ ወደ ጊዜ በይዘቱ እየባሰና እየጨመረ በዐይነቱም ለመናገር እስከሚሰቀጥጥ ድረስ ዘግናኝ እየሆነ መጥቷል። ይህ ግፍ የተጀመረው ዛሬ ባይሆንም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ እያጋጠሙ ያሉ ተደጋጋሚና ቀን ቆጥረው የሚፈጸሙ ጥቃቶች በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተበረታቱባት ይገኛሉ። በተለይም ጽንፍ የረገጠው የዘውግ ፖለቲካ ርእዮተ ዓለምና ኢትዮጵያን በጠላትነት የፈረጁ “የውጭ አካላትን” ሽፋን ያደረገ እንቅስቃሴ ግብ ቤተ ክርስቲያንን የማጥፋትና ለሀገር አንድነትና ነጻነት ያላትን ሚና መቀነስ እንደሆነ ግልፅ እየሆነ መጥቷል። ከሀገራዊ የለውጥ እንቅስቃሴ ጋር ተያይዘው የመጡ የብዙ አካላት ፍላጎቶችም እንዲህ ዐይነት ቀውሶች እንዲፈጠሩ አስተዋጽኦ እንዳላቸውም እንረዳለን። በሀገር ውስጥም የወደፊቷ ኢትዮጵያ ምን መምሰል አለባት በሚለው ሃሳብ ላይ ዋልታ ረገጥ የሆነ አመለካከት በሚያራምዱ አካላት መካከል ያለው ውጥረትም ቀላል እንዳልሆነ እንገምታለን።

    ይህም ሁሉ ሆኖ መንግሥት ችግሩን ለመፍታትና ምላሽ ለመስጠት ያሳየውን በጎና ቅን ሙከራዎችን ግን ሳንጠቅስ አናልፍም። ነገር ግን አሁንም ቤተ ክርስቲያን የጥፋት መልእክተኞች የጥቃት ዒላማ ሆና ትገኛለች። በዚህ ረገድ የሕግ የበላይነት ኖሮ ፍትሕ ማግኘት አለመቻል ከመንግሥትም በቂ ከለላ ሳታገኝ መቅረቷ በኦርቶዶክሳውያን አእምሮ ብሶትና እሮሮ ያስነሳ በመንግሥትም ላይ ትልቅ ጥርጣሬን የሚያጭር እየሆነ መጥቷል። ለዚህም በምሳሌነት ቀደም ያለውን እንኳ ትተን የቅርቡን ብናይ በሲዳማ የክልልነት ጥያቄ በተነሳው ውዝግብና ከአክቲቪስት ጃዋር መሐመድ ጥበቃ መነሣት ውዝግብ ጋር ተያይዞ በተቀሰቀሰው ረብሻ በቤተ ክርስቲያን፤ በአገልጋዮችና በምእመናን የተፈጸመውን ጥቃትና የደረሰውን ዕልቂት ማስታወስ ይበቃል። በአጠቃላይ ሐምሌ 28 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ በጅግጅጋና አካባቢው ከተፈጸመው ጥቃት እስከ አሁን ቤተ ክርስቲያን ብዙ መከራን አስተናግዳለች። እርስዎ ከመጡ ጀምሮ በተረጋገጠ መረጃ መሠረት በትንሹ 25 አብያተ ክርስቲያን ተቃጥለዋል። ጅግጅጋ፣ ጅማ፣ ሲዳማ፣ ከሚሴ፣ ምሥራቅና ምዕራብ ሐረርጌ፣ ምሥራቅና ደቡብ ምዕራብ ሸዋ፣ ባሌና አርሲ በተፈጸሙ ጥቃቶች በመቶዎች የሚቆጠሩ ካህናትና ምእመናን በአሰቃቂ ሁኔታ በድንጋይ ተቀጥቅጠው፣ በእሳት ተቃጥለውና በገጀራ ተቆራርጠው ሕይወታቸውን አጥተዋል። በመቶዎች የሚቆጠሩ ከፍተኛ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል። ሕፃናትንና አሮጊቶችን ጨምሮ ብዙ ሴቶች ተደፍረዋል። የብዙ ክርስቲያኖች ቤቶች ተቃጥለዋል። በሺዎች የሚቆጠሩ ከቀያቸውና ከሀብት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል። በተለያዩ የሥነ ልቡና ጫናዎች ውስጥ ወድቀው በፍርሃትና በሥጋት የሚኖሩት ቁጥራቸው ቀላል አይደለም።

    ቀደም ሲልም የቤተክርስቲያን መቃጠልና ጥቃት ይቁም ብለው የተሰባሰቡና ለክቡርነትዎ ቀርበው ሃሳባቸውን ገልጸው እርስዎም በሰጡት ምላሽ ከክልሎች ጋር በመወያየት ችግሮችን ለመፍታት ብዙ ጥረቶች ተደርገዋል። ብዙ ክልሎችም አዎንታዊ ምላሽ ሰጥተዋል። የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ግን ጉዳዩ ላይ ትኩረት አልሰጠም፤ ፍላጎትም አላሳየም። አሁን እንደሚታዩት አብዛኞቹ ችግሮች የተፈጸሙትና በመፈጸምም ላይ የሚገኙት በዚሁ ክልል ውስጥ ነው። ይህን የምንጠቅሰው ስለማያውቁት ሳይሆን እንዲህ ዐይነቶች ጥቃቶች እየተፈጸሙ በአጥፊዎች ላይ አስተማሪ ርምጃ ሳይወሰድ ሲቀርና የዜጎች የደኅንነት ዋስትና አለመረጋገጥ ምን ማለት እንደሆነ ምንስ ያህል ከባድ እንደሆነ በኋላ የሚያስከትለውም አደጋ ከባድ እንደሆነ ለማሳሰብ ጭምር ነው።

    በያዝነው ወርኃ ኅዳር ደግሞ የጥቃት ዒላማ ተረኛ የሆኑት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ናቸው። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ብዙ ፍላጎቶች የሚስተናገዱባቸው፣ የሀሳብ ፍጭቶች የሚካሔዱባቸውና፣ ማኅበራዊ መስተጋብሮች የሚፈጸሙባቸው የልሕቀት ማእከላት ናቸው። በአግባቡ ከተያዙ ሀገርን ከድህነት የሚያወጡና ለሀገር ፈውስ የሚሆኑ ሊቃውንት የሚወጡባቸው፣ በአግባቡ ካልተያዙና ለጥፋ መልእክተኞች መሣሪያ ከሆኑ ግን ሀገርን የሚያጠፉ ትምህርትን በአግባቡ ያልተጠቀሙበት የጥፋት ዐርበኞች የሆኑ ትውልዶች የሚፈሩባቸው እንደሚሆኑ የታመነ ነው። ይህን እውነት ከግንዛቤ አስገብተን ስንመለከተው ለሀገር የሚበጅ፣ በሥነ ምግባር የታነጸ፣ ለሕዝብ የሚቆረቆር የተማረ ዜጋ ማፍራት የሚቻለው ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የተረጋጋ የመማር ማስተማር ከባቢያዊ ሁኔታ መፍጠር ከቻሉ ብቻ ነው። በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ላይ አጥልቶ የሚታየው የጥቃት ድባብ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እንዲማሩ ልጆቻቸውን የላኩ ወላጆችንም ሆነ ተማሪዎችን በተረጋጋ መንፈስ እንዲኖሩ የሚፈቅድ አይደለም። በአንዳንድ ቦታ አልፎ አልፎ እየተከሰቱ ያሉ አደጋዎችና ሁከቶች ወላጆችን ለከፍተኛ ሥጋትና ጭንቀት እየዳረጋቸው ነው። በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እየተፈጸመ ያለው ጥቃትም ሃይማኖትን ማእከል ያደረገ መሆኑ ደግሞ ጉዳዩን የበለጠ አሳሳቢ ያደርገዋል። ስለሆነም መንግሥት በአጥፊዎች ላይ ርምጃ አለመውሰድን እንደ “ትዕግሥት” በመቁጠር ቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃት በዝምታ መመልከቱ ብዙ ዋጋ የሚያስከፍል ነውና የዜጎችን የመኖር መብትና የደኅንነት ዋስትና ማረጋገጥን መንግሥት በአግባቡ እንዲተገብረው እንጠይቃለን። ሰሞኑን እንደተመለከትነው ጥቃቶችና ግጭቶችን በእንጭጩ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሳይወጡ መቆጣጠር እየተቻለ ከትኩረት ማነስ ምክንያት ይህንን ማድረግ ባለመቻሉ በምሥራቅና ምዕራብ ሐራርጌ ምእመናንና አብያተ ክርስቲያናት በሁለት ቀናት ብቻ የደረሰውን ጥፋት ዘርዝረን የማንጨርሰው ሆኖብናል።

    በመሆኑም በተለይም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች እየተፈጸሙ ያሉ ጥቃቶች በሚዲያ እንደተገለጸው ከመንግሥት አቅም በላይ ካልሆኑ በአጭር ጊዜ ችግሮቹ እልባት እንዲያገኙ መደረግ አለበት፣ ካልተቻለ ደግሞ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለተወሰነ ጊዜ ተዘግተው የማረጋጋት ሥራዎችን ሠርቶ እንደገና ማስጀመር እንደ አማራጭ መፍትሔ መታየት ይገባዋል ብለን እናምናለን። ከዚህም በተጨማሪ ጥቃቶችን እየፈጸሙና እያስፈጸሙ ባሉ አጥፊዎች ላይ አስተማሪ ርምጃ በግልጽና ሁሉንም ዜጋ በሚያሳምን መልኩ መውሰድ ለዜጎች ደኅንነት ማረጋገጥ ለነገ የማይባል ጉዳይ መሆኑን መግለጽ እንወዳለን። ችግሩ አልፎ አልፎ ከኦርቶዶክሳውያን ውጭ የሚገኙትንም የሚያካትት ቢሆንም አሁን ግልፅ ሆኖ ግን የሚታየው ኦርቶዶክሳውያኑ ላይ እጅግ ያነጣጠረ የሰፋና የከፋም ነው። አስቸኳይ መፍትሔ ካልተገኘለትም ‘’ኦርቶዶክሳውያኑ በሁሉም አካባቢ የጥቃት ዒላማ ተደርገን እየተቆጠርን ያለነው እኛን ነን’’ በማለት የራሳቸውን ደኅንነት የማስጠበቅ ግዴታ ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ። ይህ ደግሞ ከፍተኛ መተላለቅንም ሊያስከትል ይችላል። አንዳንድ የመንግሥት ሚዲያዎች አደጋዎችን በትክክል እንደመዘገብ እውነትን ማስተባበልና የተሳሳተ መረጃ ማስተላለፋቸው ደግሞ አሳዛኝ ከመሆኑም በላይ ሆነ ተብሎ የሚወሰድ ርምጃና በአብዛኛውም ምእመንም ዘንድ መንግሥታዊ ሽፋን ያለው ተደርጎ እንዲወሰድ አድርጎታል። በአጠቃላይ የችግሮቹ ሂደት ከመንግሥት ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ጉዳዮች ከመፈጠራቸው በፊት መንግሥት አስፈላጊውን ሁሉ እንዲያደርግ በተለይም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ላይ እየተፈጸሙ ያሉ ጥቃቶች በአስቸኳይ መፍትሔ እንዲሰጣቸው እየጠየቅን በጉዳዩ ዙሪያ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማትም ሆኑ ሃይማታዊ ተቋማት ሊሳተፉባቸው በሚገባቸው ኃላፊነቶች ሁሉ የድርሻችን ለመወጣት ዝግጁ መሆናችንን በዚሁ አጋጣሚ ለመግለጽ እንወዳለን።

    እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ!!!
    ማኅበረ ቅዱሳን (EOTCMK)

    ማኅበረ ቅዱሳን

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የአገሪቱን ስፖርት በበላይነት እንዲመራ፣ እንዲከታተልና እንዲደግፍ የፌዴራል መንግሥት የአስፈጻሚ አካላት ስልጣንና ተግባር ለመወሰን በወጣው አዋጅ ቁጥር 1097/2011 እንዲሁም የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽንን ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን በወጣው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር አንቀጽ 9 መሠረት ብሔራዊ የስፖርት ምክር ቤት እንደገና ማቋቋም አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል።

    በዚህም ህብረተሰቡ በስፖርት ተጠቃሚ እንዲሆንና በስፖርታዊ እንቅስቃሴ ባህሉ የዳበረና ሁለንተናዊ ስብዕናው የተሟላ ዜጋ እንዲሆን በሚደረገው ርብርብ የዘርፉን የባለድርሻ አካላት ሚናና ድርሻ ማሳደግ ዓላማ ያደረገና በቀጣይ የሀገሪቱ የስፖርት ልማት ዘርፍ ትልቅ ኃላፊነት የተሰጠው ብሔራዊ የስፖርት ምክር ቤት መሥራች ጉባኤ ህዳር 4 ቀን 2012 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ ሆቴል ተካሂዷል።

    ይህ ብሔራዊ የስፖርት ምክር ቤት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ደመቀ መኮንን ሰብሳቢነትና የበላይ ጠባቂነት የሚመራ ሲሆን፣ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ሂሩት ካሳው በምክትል ሰብሳቢነት ይመሩታል። ይህም በስፖርት ልማት ዘርፍ በበላይነት በመምራት ተቀራርቦና ተቀናጅቶ ለመሥራት የሚያግዝና የስፖርት ልማት ዘርፉ የተሻለ አሠራርና አደረጃጀት ኖሮት ህብረተሰቡ ከስፖርት ዘርፍ ተጠቃሚ እንዲሆን ያስችላል ተብሎ ይጠበቃል።

    በመሥራች ጉባኤው መክፈቻ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት ክቡር አቶ ኤልያስ ሽኩር የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ለእንግዶች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። እንዲሁም ክብርት ዶ/ር ሂሩት ካሳው የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ያስተላለፉት መልዕክት ይህ በእንደገና የተመሠረተው ብሔራዊ ምክር ቤት ለሀገሪቱ ስፖርት ልማት ዘርፍ ቀጣይ ዕጣ ፈንታ ላይ ታላቅ ኃላፊነት የተሰጠው ነው በማለት ጥልቅ ሀሳቦችን በማስቀመጥ አስገንዝበዋል።

    እንዲሁም የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር አቶ ደመቀ መኮንን በዳግም ለተመሠረተው ምክር ቤት የሥራ መመሪያና ቀጣይ አቅጣጫ ያስቀመጡ ሲሆን፣ የስፖርት ኢንዱስትሪው በቃላት ሊነገር በማይችለው በላይ የሕዝባችንን ፍላጎትና ጥያቄ መመለስ ያለበት ነው። በመሆኑም የስፖርት ዘርፉ በሰው ኃይልና በቁሳቁስ እንዲጠናከር፣ ተወዳዳሪና ብቁ ስፖርተኞች በማፍራት በመዝናኛ ስፖርትነት፣ ለአብሮነትና ሀገርና ሕዝብ ታላቅነት ያስጠበቀ እንዲሆን በተወዳዳሪነትና ዓለም-አቀፍ ተሳታፊነት እንዲኖረን በተሻለ አደረጃጀትና አመራር የማጠናከር አቅም የማኖር ተግባር ከስፖርት ምክር ቤቱ የሚጠበቅ ነው ብለዋል።

    በዕለቱ ለውይይት የቀረበው ጥናታዊ ጽሑፎች ርዕስ በኢትዮጵያ የስፖርት አመጣጥና አጀማመር እንዲሁም ሀገር-አቀፍ የስፖርት ሪፎርም ፕሮግራም በተከበሩ በአቶ ሀብታሙ ሲሳይ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ናቸው። በተሰጣቸው ሰዓት ገለፃና ማብራሪያ ከሰጡ በኋላ በተሳታፊዎች ውይይት ተደርጓል።

    በመሥራች ጉባኤው ላይ ከብሔራዊ ክልል ፕሬዝዳንቶች፣ ከከተማ አስተዳደር ከንቲባዎች፣ ከብሔራዊ ክልል የስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነሮች፣ የስፖርት ፌዴሬሽኖች ፕሬዝዳንቶችና የጽሕፈት ቤት ኃፊዎች እንዲሁም የስፖርቱ ደጋፊና አፍቃሪ ቤተሰቦች መሳተፋቸው ታውቋል።

    ምንጭ፦ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ብሔራዊ የስፖርት ምክር ቤት

    Semonegna
    Keymaster

    ዲላ፥ ኢትዮጵያ (ዲዩ) – ዲላ ዩኒቨርሲቲ (ዲዩ) ሪፈራል ሆስፒታል ከኦርቢስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ እና ከደቡብ ክልል ጤና ቢሮ ጋር በመተባበር የዓይን ህክምና ማዕከል በመገንባት በዲላ ከተማ እና አካባቢው ለሚገኝ ማኅበረሰብ የተለያዩ የዓይን ችግር (የትራኮማ፣ የዓይን ማየት ችግር፣ የሞራ ግርዶሽ) ያለባቸው ሰዎችን ቀዶ ህክምና አገልግሎት መስጠት ጀምረ።

    የዓይን ህክምና ክፍል አስተባባሪ የሆኑት አቶ ቢንያም እስጢፋኖስ፥ ዲላ ዩኒቨርሲቲ ሪፈራል ሆስፒታል ለአስር ዓመታት በአንድ ክፍል ውስጥ በቂ ባልሆነ የዓይን ህክምና እየሰጠ በመሆኑ ይርጋለም፣ ሀዋሳ እና አዲስ አበባ ሲላኩ (“ሪፈር” ሲደረጉ) በሽተኞች፣ በተለይም ከገጠሩ አከባቢ የሚመጡ ህክምና ፈላጊዎች ለተለያዩ ችግሮች ይጋለጡና ለእንግልት ይዳረጉ ነበር። በዚህ ምክንያት ከኦርቢስ ኢንተርናሽናል ጋር በመተባበር ህንፃውን ለማቋቋም ግንባታው ለአንድ ዓመት ሲገነባ እንደነበረና አሁን የሞራ ግርዶሽ ህክምና (cataract surgery) እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።

    የጌዴኦ ዞን፣ ቡርጅና አማሮ የመስክ አስተባባሪ የሆኑት አቶ ተመስገን ጌታቸው፥ “ከዚህ በፊት ለተለያዩ ነገሮች መጋለጥ ይኖራል፤ አሁን ግን ኦርቢስ ኢንተርናሽናል ስለተቋቋመ እነዚህ ችግሮች ሁሉ ይቀረፍላቸዋል፤ ጊዜያቸውንም ይቆጥባሉ፤ በጊዜም ህክምናውን ያገኛሉ ብለዋል።” ኦርቢስ ዓለምአቀፍ ኘሮጀክት የሥራ ድርሻው አስፈላጊ የህክምና እቃዎችን የማሟላት እገዛና የባለሙያውን ክኅሎት ለመጨመር ድጋፍ ማድረግ ሲሆን ሌሎች ነገሮች ሆስፒታሉ የሚችል መሆኑን አቶ ተመስገን ገልጸዋል።

    ለጊዜው ኦርቢስ ኢንተርናሽናል ለጊዜው የባለሙያዎች አቅም ግንባታ ስልጠና የመስጠት ተግባር እያከናወነ ቢሆንም የተለያዩ የዓይን ችግር ያለባቸው ሰዎችን የትራኮማ፣ የዓይን ማየት ችግር ያለባቸው የሞራ ግርዶሽ ቀዶ ህክምና በተጓዳኝነት መስጠት በመጀመሩ ሥራው ከተጀመረ በ5 ቀናት ውስጥ ከ200 በላይ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ቀዶ ጥገና እንደሚያገኙ ይጠበቃል። ህክምናው ከተጀመረ ጀምሮ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ህመምተኞች ለተለያዩ የዓይን በሽታዎች ምርመራ ተደርገው ከ140 በላይ የሞራ ግርዶሽ ቀዶ ህክምና መሠራቱን ተገልጿል።

    ህክምናው በቅርበት በዲላ ሪፈራል ሆስፒታል መከፈቱ ከዚህ በፊት በዓመት 3 ጊዜ ብቻ የነጻ ህከምና እንደሚሰጥና ሀዋሳ እና ይርጋለም በመመላለስ የህክምና፣ የትራንስፖርት እና የመኝታ ወጪ ብቻ ከ3 ሺህ ብር በላይ ይወጣ የነበረው ከመቅረቱም ባሻገር የነፃ ህክምና ሳይመላለሱ በአንድ ቀን አገልግሎት ማግኘት መቻላቸው ታካሚዎችና አስታማሚዎች እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ ዲላ ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዲላ ዩኒቨርሲቲ የዓይን ህክምና

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – በእነ ይልቃል ጌትነት (ኢንጂነር) የተቋቋመው የኢትዮጵያዊያን ሀገር አቀፍ ንቅናቄ (ኢሀን) ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሕጋዊ የምዝገባ የምስክር ወረቀት ማግኘቱን ተከትሎ ፓርቲው የወደፊቱን ትግል የትኩረት ነጥቦች አስመልክቶ ጥቅምት 27 ቀን 2012 ዓ.ም. በጽሕፈት ቤቱ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል።

    የኢትዮጵያውያ ሀገር አቀፍ ንቅናቄ በመግለጫው የፓርቲውን ራዕይ፣ ዓላማ፣ ተልዕኮ፣ ሀገራዊ እይታና የሚመራበትን ርዕዮተ-ዓለም በተመለከተ ማብራሪያ ሰጥቷል። በተጨማሪም በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች – ማለትም ሰሞኑን በሀገራችን ማንነትን መሠረት ባደረገ የተፈፀመውን ጥቃት እና የአዲስ አበባ ከተማን የባለቤትነት ጥያቄና የፖለቲካ ምርጫን በተመለከተ ያለውን አቋም ይፋ አድርጓል።

    ‘ነፃነት ከሌለ ምርጫ የለም። ሕዝባዊ አስተዳደር ለመትከልና የተለያዩ የፖለቲካ ሀሳብ አማራጮች ለሕዝብ አቅርቦ ሕዝቡ የፈለገውን እንዲመርጥ በቅድሚያ የዜጎችን ሙሉ ነፃነት ማክበርና ማስከበር ያስፈልጋል። ነፃነት ማለት በራሱ የአማራጮች መኖር ማለት ነው። ስለሆነም ነፃነት በሌለበት ምርጫ ሊኖር አይችልም። ለሕዝባዊ አስተዳደር እውን መሆን የዜጎችን ሙሉ ነፃነት ማስከበር የማይታለፍ ቅድመ-ሁኔታ ነው’ የሚለው የጋዜጣዊ መግለጫው ተቀዳሚ መልዕክት ነበር።

    አዲስ አበባ ከተማን በተመለከተ ደግሞ፥ አዲስ አበባ ከተማ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን የጋራ ምልክታችን እንደሆነች፤ የአዲስ አበባ ሕዝብ ራስን በራስ የማስተዳደር መብቱ የተጠበቀ ሆኖ አዲስ አበባ የኢትዮጵያ ዋና ከተማ ስለሆነች፣ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን የጋራ ምልክት ሆና እንድትቀጥል ኢሀን ጠንክሮ እንደሚሠራ አስታውቋል። አዲስ አበባ የኢትዮጵያን ፖለቲካና ኢኮኖሚ በተመለከተ ያላትን ታሪካዊ ድርሻ እንድትወጣ የኢትዮጵያዊያን ሀገር አቀፍ ንቅናቄ በሙሉ አቅሙ እንደሚሠራም ጋዜጣዊ መግለጫው አትቷል።

    በመጨረሻም ሰሞኑን በኦሮሚያ ክልል፣ በድሬድዋ ከተማ እና በሀረር ከተማ ማንነትን መሠረት ባደረገ መልኩ በዜጎች ላይ የተፈፀመው ዘግናኝ ጭፍጨፋ በገለልተኛ አካል ተጣርቶ ለሕዝብ ይፋ እንዲደረግ የኢትዮጵያዊያን ሀገር አቀፍ ንቅናቄ አበክሮ እንደሚንቀሳቀስ፤ እንዲህ ዓይነቱን ዓይን ያወጣ አስነዋሪ ተግባር ለፖለቲካ ፍላጎት ሲባል ማለባበስና ማድበስበስ በንፁሀን ሕይወት መሳለቅ ከመሆኑም በላይ ለሀገራችን ሰላምና መረጋጋት ላይ ትልቅ ደመና ያዘለ ጥፋት በመሆኑ፣ ፓርቲው ጉዳዩን ከምንጩ ጀምሮ ማጥራትና የማያዳግም እርምጃ መውሰድ ከሀገር ደኅንነት /national security issue) ጋር የተያያዘ ከባድ ታሪካዊ ኃላፊነት ነው ብሎ እንደሚያምን በጋዜጥዊ መግለጫው አስታውቋል።

    የኢትዮጵያዊያን ሀገር አቀፍ ንቅናቄ የሥራ አስፈፃሚ አባላት፦

    1. ኢ/ር ይልቃል ጌትነት – ሊቀመንበር
    2. አቶ ወረታው ዋሴ – ምክትል ሊቀመንበር እና የሕዝብ ግንኙነት
    3. ወ/ሮ መዓዛ መሐመድ – የውጭ ግንኙነት ኃላፊ
    4. አቶ አወቀ ተዘራ – የአደረጃጀት ጉዳይ ኃላፊ
    5. አቶ እስክንድር ጥላሁን – የጥናትና ስትራቴጂ ኃላፊ
    6. አቶመሳይአማዶ – የሕግጉዳይኃላፊ
    7. ወ/ሪትምዕራፍይመር – የፋይናንስጉዳይኃላፊ
    8. አቶቴዎድሮስአሰፋ – የአባላትመረጃናደኅንነትጉዳይኃላፊ
    9. ወ/ሪትወይንሸትሞላ – የሴቶችናየወጣቶችጉዳይኃላፊናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያዊያን ሀገር አቀፍ ንቅናቄ

    Anonymous
    Inactive

    ጎንደር (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ጥቅምት 29 ቀን 2012 ዓ.ም. 251 የህክምና ዶክተሮችን አስመርቋል። በዚሁ ዕለት ዩኒቨርሲቲው ተላላፊና ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ዘርፍ እያደረገ ያለው ምርምር አበረታች ውጤቶችን ማስመዝገቡን አስታውቋል።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አስራት አጸደወይን እንደተናገሩት ዩኒቨርሲቲው በህክምናው ዘርፍ ከአጋር አካላት ጋር በተባበር በአባላዘር፤ በወባ በሽታ፤ በሳንባ ምች እና ተላላፊና ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች (communicable and noncommunicable diseases) ዙሪያ ምርምሮችን በማካሄድ ተስፋ ሰጪ ውጤቶች አስመዝግቧል። የምርምር ውጤቶቹም በዓለም አቀፍ ደረጃ ሲሠራባቸው የቆዩ የህክምና መመሪያዎችን እስከ ማስቀየር የደረሱ ተጽዕኖ ፈጣሪ ለመሆን መብቃታቸውንም ፕሬዝዳንቱ ገልጸዋል።

    “የምርምር ውጤቶቹ የህክምና ጊዜን በማሳጠር በመርፌ ይሰጡ የነበሩ ህክምናዎችን በአፍ በሚሰወዱ መድኃኒቶች በመተካትና የህሙማንን ስቃይ፤ እንግልትና የህክምና ወጪንም ለመቀነስ አስችለዋል” ብለዋል ዶ/ር አስራት።

    በየዓመቱም በጤናው ዘርፍ ብቻ ከ150 በላይ የምርምር ውጤቶች በታወቁ ዓለም አቀፍ ጆርናሎች ጭምር ለህትመት የበቁበት ሁኔታን መፍጠር እንደተቻለ ተናግረዋል።

    ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ዘንድሮ ለ36ኛ ጊዜ በህክምናው ዘርፍ ካስመረቃቸው 251 ዶክተሮች መካከልም 64ቱ ሴቶች መሆናቸውን ገልጸው፥ ምሩቃኑ በህክምናውና በምርምሩ ዘርፍ የሚጠበቅባቸውን ሁሉ እንዲያበረክቱ ጠይቀዋል። የዕለቱ ተመራቂዎች ለሙያቸውና ለገቡት ቃል-ኪዳን ታማኝ በመሆን ከግል ጥቅም ይልቅ ሕዝብን በማገልገል ፍጹም አዛኝና ሩህሩህ በመሆን ለህክምናው ሥነ-ምግባር ተገዥነታቸውን በተግባር እንዲያረጋግጡም መክረዋል።

    የዕለቱ የክብር እንግዳ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዲኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ በበኩላቸው “የህክምና ሳይንስ ትምህርት ክቡር የሆነውን የሰው ሕይወት የሚታደግ የተከበረ ሙያ ነው” ብለዋል። “ተማራቂዎች ለዚህ የደስታ ቀን ትደርሱ ዘንድ እውቀት ላቀበሏችሁ መምህራን፤ ለዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብና ለወላጆቻችሁ ብሎም ከእናንተ ብዙ ለምትጠብቀው ውድ ሀገራችሁ ድርብ ኃላፊነት አለባችሁ” ሲሉ አሳስበዋል።

    “ትምህርት የሁሉም መሠረት በመሆኑ ሀገርንና ወገንን ወደ እድገት ለማሻገር በተማርኩት ሙያ ለማገልገል ዝግኙ ነኝ” ያለችው ከዕለቱ ተመራቂዎች መካካል በከፍተኛ ማዕረግ የወርቅ ሜዳልያ ተሸላሚ የሆነችው ዕ ዶክተር ነጻነት ሃይሉ ነች። የሀገሪቱን ስር የሰደዱ የጤና ችግሮች ለመፍታት በጤናው ዘርፍ ምርምሮችን በማካሄድ የበኩሏን አስተዋጽኦ ለማድረግ የረጅም ጊዜ ህልሟ መሆኑንም ተናግራለች።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ በዩኒቨርሲቲው በምርምርና በህክምናው ዘርፍ የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ሀኪሞችና ተመራማሪዎች የእውቅና የምስክር ወረቀት ተሰጥቷል።

    የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በአሁኑ ወቅት በጤናው ዘርፍ 26 የመጀመሪያ፤ 37 የሁለተኛና 6 የሦስተኛ ዲግሪ እንዲሁም 10 የስፔሻሊቲ የትምህርት ፕሮግራሞች ሲኖሩት፤ ዩኒቨርሲቲው በጠቅላላው (በአምስቱ ካምፓሶቹ) 87 የመጀመሪያ፤ 137 የሁለተኛና 29 የሦስተኛ ዲግሪ ፕሮግራሞች አሉት። በጠቅላላው ከ45,000 በላይ ተማሪዎችን እያስተማረ ሲሆን፣ 8,300 ሠራተኞች አሉት።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ጎንደር ዩኒቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive

    አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከአፍረካ ምርጥ 10 ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ መሆን የቻለው ባሳየው ጥረትና መሻሻል ነው- ፕ/ር ጣሰው

    አዲስ አበባ (ኤፍ.ቢ.ሲ) – አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከአፍረካ ምርጥ 10 ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ መሆን የቻለው በየጊዜው ባሳየው ጥረት እና መሻሻል መሆኑን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሃና ገለፁ።

    አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአሜሪካው ግዙፍ የሚዲያ ድርጅት “U.S. News & World Report” ባወጣው ዘገባ  በአፍረካ ካሉ ምርጥ 10 ዓለማቀፋዊ ዩኒቨርሲቲዎች (Best Global Universities in Africa) አንዱ ሆኖ መመረጡን ተከትሎ ጥቅምት 27 ቀን፥ 2012 ዓ.ም. መግለጫ ሰጥቷል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሃና በመግለጫው፥ ዩኒቨርሲቲው በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት በ1950 ዓ.ም. መቋቋሙን ገልፀዋል። ዩኒቨርሲቲው ሲመሠረት የመቀበል አቅሙ 33 ተማሪዎችን ብቻ ሲሆን፥ ዛሬ ላይ የቅበላ አቅሙን እስከ 50 ሺህ ማድረሱን አስታውቀዋል።

    እንዲሁም ዩኒቨርሲቲው 13 ካምፓሶች፣ 10 ኮሌጆች፣ 2 የቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩቶች፣ 12 የምርምር ኢንስቲቲዩቶች እና 2 የማስተማሪያና የከፍተኛ ሕክምና መስጫ ሆስፒታሎችን በመያዝ በተለያዩ የትምህርት መርሃ ግብሮች ማለትም በ73 የትምህርት መስኮች የመጀመሪያ ዲግሪ መርሃ ግብር፣ በ345 የድኅረ ምረቃ መርሃ ግብሮች፣ በ90 የጥናትና ምርምር መስኮች የዶክትሬት መርሃ ግብሮችን እያከናወነ እንደሚገኝም አስታውቀዋል።

    ይህንን ተከትሎም ዩኒቨርሲቲው በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ዓለም አቀፋዊ እውቅናዎችን እና ደረጃዎችን አግኝቷል ያሉት ፕሮፌሰር ጣሰው፥ ከነዚህም የቅርብ የሆኑት በአውሮፓውያኑ በ2014 ከአፍሪካ ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች 18ኛ ደረጃ፣ በ2015 ከአፍሪካ ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች የ16ኛ ደረጃን እግኝቶ ነበር ብለዋል።

    በያዝነው በአውሮፓውያኑ በ2019 ደግሞ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከአፍሪካ ምርጥ ዓለማቀፋዊ ዩኒቨርሲቲዎች በ10ኛ ደረጃ ሆኖ ሊመዘገብ መቻሉንም ነው ፕሮፌሰር ጣሰው የገለፁት።

    አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እዚህ ደረጃ የደረሰው በየጊዜው ባሳየው ጥረት እና መሻሻል እንዲሁም በሚያደርገው ጥናትና ምርምር ኢትዮጵያ ከምትፈልገው የተማረ የሰው ኃይል ፍላጎት ጋር ለማጣጣም በተደረገው ጥረት መሆኑንም አስታውቀዋል።

    አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ኩራት ነው ያሉት ፕሮፌሰር ጣሰው፥ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ትንሿ ኢትዮጵያ ነው፤ ዩኒቨርሲቲው ሌሎች ኢትዮጵያውያን ዩኒቨርስቲዎችን በያዘው የእድገት እና የመሻሻል ጉዞ ላይ የመውሰድ ግዴታ አለበትም ብለዋል።

    የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአድሚኒስትሬሽን እና የተማሪዎች አገልግሎት ምክትል ፕሬዚዳንት ዶክተር ማቲዎስ ኢንሰርሙ በበኩላቸው፥ ኢትዮጵያ ካስመዘገበችው እድገት በተጨማሪ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ እዚህ ደረጃ የደረሰው ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር ባለው ተልኮ ነው ብለዋል።

    አፍሪካ ውስጥ የሚገኙ ምርጥ ዓለማቀፋዊ ዩኒቨርሲቲዎችን ደረጃ እና ዝርዝር ለማየት እዚህ ጋር ይጫኑ

    ምንጭ፦ ኤፍ.ቢ.ሲ. / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

     አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከአፍረካ ምርጥ 10 ዩኒቨርሲቲዎች


Viewing 15 results - 346 through 360 (of 730 total)