Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 406 through 420 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ኩባንያዎች አባል ኩዊንስ ሱፐርማርኬት እጅግ ዘመናዊ የሆነውን የቀራኒዮ ፕላዛ ቅርንጫፍ ሱፐርማርኬቱን አስፈላጊዎቹን ሕጋዊ መስፈርቶች አሟልቶ በማደራጀት ማክሰኞ ሐምሌ 16 ቀን 2011 ዓ.ም. ሁሉን በአንድ ባቀፈውና ማራኪ በሆነው በኮልፌ ቀራኒዮ ፕላዛ ቅጥር ጊቢው አስመረቀ።

    በዚሁ የምረቃ ሥነ ስርዓት ላይ ዶ/ር አረጋ ይርዳው የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ዋና ሥራ አስፈጻሚ እና የዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ባደረጉት ንግግር፤ በዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያላቸው ደንቦችን መሠረት ባደረገ ዲዛይን የተሠራው፤ ኩዊንስ ሱፐርማርኬት አካሄዱም ለደምበኞች ቀላልና ምቹ የግብይት ሁኔታ ለማስፈን ትኩረት የሠጠ ነው ብለዋል።

    ሱፐርማርኬቱ በሚገኝበት በቀራንዮ ፕላዛ፣ የዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚ፣ በዓይነቱ ልዩ የሆነ የነዳጅ ጣቢያ/ማደያና የተሽከርካሪ እጥበትና መለስተኛ ጥገና አገልግሎት መስጫ እና በትንሹ ከ150 በላይ መኪኖች ማቆሚያ፣ የእርሻ ምርቶች መሸጫ፣ ካፌና ሱቅ፣ ባንክ፣ እና ሁለገብ አዳራሽ መኖሩን የገለጹት ዶ/ር አረጋ፥ እነዚህ በአንድ አካባቢ መደራጀታቸው ደንበኞቹን በአንድ የንግድ ማዕከል በርካታ አገልግሎቶች እንዲያገኙ የሚያስችል በመሆኑ፣ሱፐርማርኬቱን ልዩ ያደርገዋል ብለዋል።

    ለኩዊንስ ኩባንያ መቋቋምና በዚህ ደረጃ መስፋፋት ምክንያት ለሆኑት ለሚድሮክ ኢትዮጵያ ሊቀ-መንበርና ባለሀብት ለሼህ ሙሐመድ ሁሴን አሊ አል-አሙዲ በቅድሚያ ምስጋና ያቀረቡት ዶ/ር አረጋ፥ በዛሬው ቀን በመካከላችን ለተገኙት ወንድማቸው ለሼህ አብደላ ሁሴን አሊ አል-አሙዲ ምስጋና አቀርባለሁ ብለዋል።

    እንዲሁም፣ የቀራኒዮ ቅርንጫፍ ፕሮጀክት በዚህ ለገበያ አመቺ በሆነ ቦታ እንዲገነባ ለረዱን የኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ አስተዳደር አመራሮች እና የሚመለከታቸው ሠራተኞች፣ በአካባቢው የሚገኙ ነዋሪዎች፣ መብራት ኃይል፣ የቴሌፎንና የውሃ ተቋማት፣ የአዲስ አበባ የመንገድ ሥራዎች ተቋም፣ የአካባቢው የፖሊስ እና የፀጥታ ኃላፊዎች እና ሌሎችም ላደረጉልን መተባበር ከፍተኛ ምስጋና አቅርባለሁ ብለዋል።

    ዶ/ር አረጋ በዚሁ ንግግራቸው፥ የኩዊንስ ቀራኒዮ ቅርንጫፍ ፕሮጀክት ለቅድመ መደበኛ አገልግሎት ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ፣ ለሥራ ማስኬጃ እና ለሽያጭ የሚያገለግሉ ዕቃዎች (መደርደሪያዎች፣ ማቀዝቀዣዎች፣…) ግዢ፣ የሲስተም ዝርጋታ ወጪን ጨምሮ፣ ለሸቀጣ ሸቀጥ አቅርቦት ጠቅላላ ወጪ 59.3 ሚሊዮን ብር መሆኑን አስረድተው፤ ሕንፃው በ37.7 ሚሊዮን ብር ወጪ መገንባቱንና የኤልፎራ አግሮ ኢንዱስትሪ ንብረት በመሆኑ፣ ኩዊንስ በኪራይ እንደሚገለገልበት አስታውቀዋል።

    የሪቴል ግሩፕ ፕሪንሰፓል ኦፕሬሽን ኦፊሰር ወ/ሮ ታህሳሥ ወንድምነህ በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር ኩዊንስ ሱፐርማርኬት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኀበር ሰኔ 25 ቀን 2002 ዓ.ም. 46 ቋሚ እና 5 ኮንትራት፣ በድምሩ 51 ሠራተኞች በመያዝ የተቋቋመ መሆኑን አስታውሰው፥ ኩባንያው የአግሮ ኢንዱስትሪ ውጤቶችን (የዶሮ፣ የወተት እና የሥጋ ተዋጽዖዎችን)፣ የእርሻ ምርቶችን (ሰብሎች፣ አትክልት፣ ፍራፍሬ እና አበባዎች)፣ የባሕር ምግቦች (ዓሣ)፣ የንጽህና መጠበቂያ ምርቶች (ሣሙና….) የታሸጉ ምርቶች፣ መጠጦች እና ሌሎች የፋብሪካ ውጤቶችን (የጽሕፈት መሣሪያዎችን፣ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎችን እና የቤት ውስጥ የመገልገያ ዕቃዎች) በችርቻሮ እና በጅምላ በመሸጥ እና በማከፋፈል ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

    ወ/ሮ ታህሳሥ በዚሁ ንግግራቸው፤ ኩባንያው በአሁኑ ጊዜ የካፒታል መጠኑ ወደ ብር 23,786,000፣ የሠራተኞቹ ብዛት ወደ 142 (132 ቋሚ እና 10 ኮንትራት) ማደጉን አመልክተው፤ ዓመታዊ ሽያጩም ሥራ ሲጀምር ከነበረው ከብር 12,192,000 ወደ ብር 157,000,000 ማደጉን አሰታውቀዋል።

    አያይዘውም ኩባንያው ቅርንጫፎቹን ወደ ሰባት በማሳደግ ጥራት ያላቸውን ምርቶች በበቂ ሁኔታ በማቅረብ ላይ እንደሚገኝ እና ተጨማሪም አንድ የዳቦ ማምረቻና መሸጫ በመቻሬ ቅርንጫፍ በማቋቋም ለሠራተኞችና ለኀብረተሰቡ አገልግሎት በመስጠት ላይ መሆኑን አስረድተው፤ ሱፐርማርኬቱ ለ50 ተጨማሪ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩንና ዓመታዊ ሽያጩም ብር 75,000,000 እንደሚሆን፤ የኩባንያውን ዓመታዊ የሽያጭ መጠንንም በግማሽ በማሳደግ አስተዋጽዖ እንደሚያደርግ አሰታውቀዋል።

    ወ/ሮ ታህሳሥ ለኩዊንስ ኩባንያ መቋቋምና በዚህ ደረጃ መስፋፋት ምክንያት ለሆኑት ለሚድሮክ ኢትዮጵያ ሊቀመንበርና ባለሀብት ለክብር ዶ/ር ሼህ ሙሐመድ ሁሴን አሊ አል-አሙዲ፣እንዲሁም፣ የቀራኒዮ ቅርንጫፍ ፕሮጀክት በዚህ ለገበያ አመቺ በሆነ ቦታ እንዲገነባ የፕሮጀክት ሀሳብ በማቅረብ፣ አስፈላጊውን በጀት በመመደብ፣ በፕሮጀክቱ ሂደትም ያልተቋረጠ የዕለት ተዕለት ክትትል በማድረግ፣ የቅርብ አመራር በመስጠት እና አቅጣጫ በማስያዝ ፕሮጀክቱ በአጥጋቢ ሁኔታ እንዲጠናቀቅ ላበቁት ለዶ/ር አረጋ ይርዳው የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ቺፍ ኤግዚኪዩቲቭ ኦፊሰር እና ፕሬዚዳንት፤ ከፍተኛ ምስጋና አቅርበዋል።

    በዚሁ የምረቃ ሥነ-ሥርዓት ላይ ለፕሮጅክቱ መሳካት አሰተዋጽኦ ያበረከቱ ድርጅቶችና ግለሰቦች፤ የተዘጋጀላቸውን ሠርቲፊኬት ከዕለቱ የክብር እንግዳ ከሼህ አብደላ ሁሴን አሊ አል-አሙዲ እጅ ተቀብለዋል።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ፤ የኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ሥራ አስፈጻሚ ተወካይና ሌሎች ከፍተኛ የሥራ አመራሮች፣ የሚድሮክ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እና ደንበኞች በተገኙበት ተካሂዷል።

    ምንጭ፦ ሚድሮክ ኢትዮጵያ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    ኩዊንስ ሱፐርማርኬት


    Anonymous
    Inactive

    ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ሐምሌ 20 ቀን 2011 ዓ.ም. በሚሊኒየም አዳራሽ አስመረቀ

    የትምህርት ጥራትን ማጠናከርና ማሻሻል ቀጣይነት ያለዉ ሥራ ስለሆነ በዚህ ጉዳይ መንግሥት ብቻ ሳይሆን የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና ማህበረሰቡ የበኩላቸዉን ሃላፊነት ሊወጡ ይገባል ተባለ።

    ይህን ያሉት የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ፕሮፌሰር ሂሩት ወልደማርያም ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ሐምሌ 20 ቀን 2011 ዓ.ም. በሚሊኒየም አዳራሽ ባስመረቀበት ወቅት በክብር እንግድነት ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት ነው።

    ሚኒስትሯ አክለውም ከፍተኛ ትምህርትን የማስፋፋት፣ የጥራትና ፍትሀዊነት ሂደት ዉስጥ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ዓይነተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ። በተለይም ተደራሽነትን ከማስፋት አንጻር መንግሥት ባዘጋጀዉ የሕግ ማዕቀፍ በመደገፍ ከ1993 ዓ.ም. ጀምሮ በርካታ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተቋቁመዉ ለዜጎች ሰፊ የትምህርትና የሥራ ዕድል ከፍተዋል። እነዚህ ተቋማት በትምህርት ፈላጊዎች እንደጥሩ አማራጭ ስለታዩና ተቀባይነትም ስላገኙ በአሁኑ ወቅት በዘርፉ የተሰማሩ ተቋማት ብዛት ከ200 በላይ ደርሷል፤ በዚህም በከፍተኛ ትምህርት ከሚማሩት ጠቅላላ ተማሪዎች ውስጥ ከ20 በመቶ በላይ የሚሆኑትንም ያስተናግዳሉ ብለዋል።

    ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ለ36ኛ ጊዜ ተማሪዎቹን ባስመረቀበት በዚህ ዝግጅት የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በማኅበረሰብ አገልግሎትና በጥናትና ምርምር ላይ እያሳዩ ያሉት መልካም ጅምር ሊበረታታ ይገባል ሲሉ ፕሮፌሰር ሂሩት ጨምረው ተናግረዋል።

    በመጨረሻም ፕሮፌሰር ሂሩት ወልደማርያም እንዳሉት፥ የአገሪቱ ኢኮኖሚ እያደገ በሄደ ቁጥር የሚፈለገዉ የሰዉ ኃይልም በቁጥርና በጥራት እየጨመረ ይሄዳል። ለዚህም የወቅቱን የእድገት እርምጃና የሥራ ገበያ ፍላጎት የሚመጥን የማስተማር፣ የምርምርና ማኅበረሰብ አቀፍ አገልግሎት ማስፋፋት አስፈላጊ ነው ብለዋል። አክለውም፥ የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ይሄንን ተገንዝበው የፕሮግራም አድማሳቸውንና አገልግሎታቸውን የአገሪቱን የአሁንና መፃኢ የሰው ኃይል ፍላጎት ባገናዘበና ጥራቱን ባስጠበቀ መልኩ በማሻሻል አጋርነታቸውን አጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል ሲሉ አስምረውበታል።

    ሚኒስትሯ በቆይታቸውም ከፍተኛ ውጤት ላስመዘጉ ተመራቂዎች የሜዳሊያና ዋንጫ፣ እንዲሁም የሚድሮክ ኢትዮጵያ ግሩፕስ ባለቤት በሆኑት በሼህ ሁሴን አሊ አላሙዲን ስም በተሰየመው የሕይወት ዘመን አገልግሎት ሽልማት ዘርፍ ተሸላሚ ለሆኑ 4 ግለሰቦች የምስክር ወረቀት አበርክተዋል፡፡

    ዶ/ር አረጋ ይርዳዉ የዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንትና የሚድሮክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ በበኩላቸው፥ ተማሪዎች በቆይታው ያካበበቱትን ዕውቀትና ልምድ ለአገራቸው በሚጠቅም መልኩ ሊያውሉት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

    ዩኒቨርሲቲው በአገራችን የመጀመሪያው የግል ዩኒቨርሲቲ በመሆን በመንግሥት ዕዉቅና ተሰጥቶት ላለፉት ሦስት አስርት ዓመታት በተለያዩ የትምህርት ደረጃዎችና መስኮች ለዜጎች ተደራሽነትንና ህትሃዊነትን ለማስፋት በሚደረገው ጥረት የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – አድማስ ዩኒቨርሲቲ በኢትዮጵያ የጥራት ደረጃዎች ኤጀንሲ የተዘጋጁት ስታንዳርዶች በተገቢው መልክ በመፈፀም በ2012 ዓ.ም. በተቋም ደረጃ አይ ኤስ ኦ የምስክር ወረቀት (ISO Certificate) ለማግኘት የሚያስችለውን ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ገለጸ።

    የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ብሩ አስማረ እንደገለጹት፥ ዩኒቨርሲቲው የትምህርት አሰጣጥ ጥራት ደረጃውን በማሳደግ ለዚሁ ተገቢ የሆነ እውቅና ለማግኘት የሚያስችለው ብቃት ላይ ይገኛል።

    በቴክኒክና ሙያ ኮሌጀች የትምህርት ሥልጠና ጥራት ለማስጠበቅና በየሙያ ደረጃው የሥርዓተ ትምህርት ክለሳ አድርጓል ያሉት ምክትል ፕሬዚዳንቱ የማስልጠኛ መሳሪያዎች (Training Teaching and Learning Materials /TTLM) ዝግጅት በሁሉም የብቃት አሃዶች ማዘጋጀቱንና የትብብር ሥልጠናን አፈፃፃምን የሚያሻሻሉ የተለያዩ ተገባራት እያከናወነ መሆኑን አስረድተዋል።

    አቶ ብሩ አስማረ አያይዘውም የምዘና ሥርዓቱን ለማጠናከርና በዩኒቨርሲቲው የሚተገበረውን የተከታታይ ማጠቃለያና ተቋማዊ ምዘና ዝግጅትና አፈፃፃም ደረጃውን የጠበቀ እንዲሆን መደረጉንም አስረድተዋል።

    በኢትዮጵያ የደረጃ ኤጀንሲ (Ethiopia Standard Agency) የተዘጋጁ የጥራት ምዘናዎችን (stadards) ማለትም የስርዓተ ትምህርት (Curriculum Requirement ES. 6259-1: 2018)፣ የመሣሪያዎች ማሽነሪዎች (Tools, Machines and Equipment Requirement ES 6259-8: 2018)፣ የምዘናና የማሰልጠኛ መሣሪያዎች (Assessment & Instructional Materials ES 6299-9: 2011 ) እና የመሳሰሉትን ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን አቶ ብሩ ገልጸዋል።

    ምክትል ፕሬዚዳንቱ አያይዘውም በዩኒቨርሲቲው የሚስጠውን የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠና በምርምር ለማገዝ እንዲቻል የተለያዩ ጥናቶች በማካሄድ ያሉ ችግሮችን የመለየት ሥራ በየጊዜው እየተካሄደ መሆኑን ጠቁመዋል።

    በጥቅምት ወር 1990 ዓ.ም. “አድማስ የቢዝነስ ማሰልጠኛ ማዕከል” በሚል ሥራውን የጀመረው ይህ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም፥ በፍጥነት ራሱን በማሳደግ በሚያዝያ ወር 1991 ዓ.ም. የኮሌጅነት ደረጃ አግኝቶ ስሙን “አድማስ ኮሌጅ” ብሎ በመሰየም ሥራውን አስፋፋ። ቀጥሎም በመጋቢት ወር 1999 ዓ.ም. “አድማስ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ” በሚል ስም የትምህርትና የስልጠና ተግባሩን አሳደገ። የከፍተኛ ትምህርት አዋጅ ቁጥር 650/2009 የሚጠይቃቸውን አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅቶች በሙሉ በማሟላት በሐምሌ ወር 2006 ዓ.ም. የሙሉ ዩኒቨርሲቲ ደረጃን አግኝቶ “አድማስ ዩኒቨርሲቲ” ተባለ።

    አድማስ ዩኒቨርሲቲ የዘንድሮን ተመራቂዎችን ጨምሮ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ከ70 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በተለያዩ የትምህርት ዘርፎችና እርከኖች አስመርቋል።

    በአሁኑ ወቅትም በውጭ/ጎረቤት ሀገራት ሶማሌላንድና ፑንትላንድ በሚገኙት ካምፓሶቹ ያሉትን ጨምሮ በጠቅላላው ከ20 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ተቀብሎ እያስተማረ ነው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አድማስ ዩኒቨርስቲ የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ብሩ አስማረ


    Anonymous
    Inactive

    አድማስ ዩኒቨርስቲ 6 ሺህ 8 መቶ 48 ተማሪዎችን ተማሪዎች አስመረቀ
    —–

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)፦ አድማስ ዩኒቨርስቲ በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያስተማራቸውን 6 ሺህ 8 መቶ 48 ተማሪዎች ተማሪዎች ሐምሌ 14 ቀን 2011ዓ.ም. አስመረቀ።

    ዩኒቨርስቲው በአዲስ አበባ ሚሊኒየም አዳራሽ በተከናወነ ሥነ-ስርዓት ያስመረቃቸው ተማሪዎች በዲግሪና በቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ዲፕሎማ በመደበኛና ተከታታይ መርሃ ግብር ትምህርታቸውን ተከታትለው ያጠናቀቁ ናቸው። የዩኒቨርስቲው ሬጅስትራር ኃላፊ አቶ ተፈሪ ክብረት እንደገለጹት ተመራቂዎቹ 3 ሺህ 121 በዲግሪ፣ 1 ሺህ 668 በደረጃ-3፣ እና 2 ሺህ 59 በደረጃ-4 በቴክኒክና ሙያ የትምህርት ዘርፎች ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ናቸው።

    ተመራቂዎቹ በዲግሪ በአካዉንቲንግና ፋይናንስ፣ በቢዝነስ ማኔጅመንት፣ በሆቴል ማኔጅመንት፣ በማርኬቲንግ ማኔጅመንት እና በኮምፒዩተር ሳይንስ የተመረቁ ሲሆን በቴክኒክና ሙያ ደግሞ በኢንፎርሜሽን ኮምኒኬሽን ቴክኖልጂ፣ ሆቴሌና በቢዝነስ ፋይናንስ ዘርፎች የሰለጠኑ መሆናቸውን ኃላፊው ገልጸዋል።

    በሥነ ስርዓቱ ላይ የዩኒቨርስቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ሞላ ፀጋይ እንደገለጹት ዩንቨርስቲው በአገሪቷ የተማረ የሰው ኃይል ለማፍራት በምታደርገው ጥረት ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ ይገኛል። ዩኒቨርስቲው እያደረገ ያለውን የማኅበረሰብ አቀፍ አገልግሎትም አጠናክሮ እንደሚቀጥል ፕሬዚዳንቱ አክለዋል።

    ከዚሁ ዜና ጋር በተያያዘም፥ አድማስ ዩኒቨርሲቲ መቐለ ካምፓስ ሰኔ 29 ቀን 2011ዓ.ም. በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች በድግሪና በቴክኒክና ሙያ መርሃ ግብሮች ያሰለጠናቸውን 1 ሺሕ 300 ተማሪዎች አስመርቋል። በተመሳሳይ መልኩ ዩኒቨርስቲው 1 መቶ 41 በድግሪ እና 302 ደግሞ በደረጃ-4 በቴክኒክና ሙያ በቢሾፍቱ ካምፓስ የሰለጠኑ ተማሪዎችን አስመርቋል።

    አድማስ ዩኒቨርሲቲ የዘንድሮን ተመራቂዎችን ጨምሮ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ከ70 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በተለያዩ የትምህርት ዘርፎችና እርከኖች አስመርቋል።

    በአሁኑ ወቅትም በውጭ ሶማሌላንድና ፑንትላንድ በሚገኙት ካምፓሶቹ ያሉትን ጨምሮ በጠቅላላው ከ20 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ተቀብሎ እያስተማረ ነው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    Semonegna
    Keymaster

    «በ1950ዎቹ ዓመታት መጨረሻ ጋሽ ጥላሁንን፤ አለማየሁ እሸቴን እና ታምራት ሞላን የመሳሰሉ እንቁዎች ሰምቼ ከሙዚቃ ፍቅር ያዘኝ» ድምፃዊ የግጥምና ዜማ ደራሲ እንዲሁም የሙዚቃ አቀናባሪ አንጋፋዉ አርቲስት አያሌዉ መስፍን። ከሁሉ ከሁሉ የአዲስ አበቤ ፍቅረኛሞች ቀጠሮአቸዉ አያሌዉ መስፍን ሙዚቃ ቤት ጋር እንደነበር የሚያስታዉስ ያስታዉሰዋል።

    ድምፃዊ የግጥምና ዜማ ደራሲ እንዲሁም የሙዚቃ አቀናባሪ ነው፤ አንጋፋዉ አርቲስት አያሌዉ መስፍን። ወሎ የሙዚቃ ባለ ኃብቶችን የሙዚቃ ምሁራንን፤ ያፈራች ሃገር መሆንዋ አብዛኞች ይመሰክሩላታል። ወሎ ካፈራችዉ አያሌዉ መስፍን ከመሳሰሉ ከያኒዎች መካከል በባህል ሙዚቃ ገናና ስምን የተከለዉ የማሲንቆዉ ቀንድ፤ በማሞካሸት የጥበብ ጀማሪ አሰፍዬ አባተ ይባል የነበረዉ፤ አንጋፋዋ ድምፃዊ ማሪቱ ለገሰ፤ አለማየሁ እሸቴ፤ ኃብተሚካኤል ደምሴ ከአብዛኞቹ የጥበብ እንቁዎች እጅግ ጥቂቶቹ ናቸዉ።

    ወሎ ከያኒዎችን ብቻ ሳይሆን አራቱን የኢትዮጵያ የሙዚቃ ቅኝቶች ያፈራች እንደሆነችም ይነገርላታል። «በ 50 ዎቹ ዓመታት መጨረሻ ጋሽ ጥላሁንን፤ አለማየሁ እሸቴን እና ታምራት ሞላን የመሳሰሉ እንቆዎች ሰምቼ ከሙዚቃ ፍቅር ያዘኝ» ያለን አንጋፋዉ አርቲስት አያሌዉ መስፍን፤ ስለአገር ፍቅር ስለፍትህ፤ ስለአንድነት ስለፍቅር አዚሞአል፤ ገጥሞአልም። በተለይ በሙዚቃዎቹ ከኢትዮጵያ ጦር ሠራዊት ጋር በጋራ የሃገር ድንበርን ማስከበሩ ይነገርለታል። በደረሳቸዉ ግጥሞች በርካታ ከያንያን ተወዳጅ ዜማቸዉን ለአድማጭ ጆሮ አድርሰዉ ታዋቂ ሆነዋል። ከሁሉ ከሁሉ የአዲስ አበቤ ፍቅረኛሞች ቀጠሮአቸዉ አያሌዉ መስፍን ሙዚቃ ቤት ጋር እንደነበር የሚያስታዉስ ያስታዉሰዋል።

    ምን እሱ ብቻ! እንዲህ እንደአሁኑ የእጀታ ስልክ (ሞባይል) ኖሮ፤ የኢንተርኔት አገልግሎት ከሞላ ጎደል ተስፋፍቶ «ሜሴጅ አድግ አድርጊልኝ» በማይባልበት በዝያ ዘመን ከክፍለሃገር የመጡ ኢትዮጵያዉያን አያሌዉ ሙዚቃ ቤት መገናኛቸዉ ነበር። የመዲናዋም ወጣቶች ቢሆኑ በአያሌዉ ሙዚቃ ቤት በራፍ ግራና ቀኝ ከቆመዉ ነጎድጓድ ድምፅን ከሚተፋዉ አምፕሊፋየር «አልያም የድምፅ ማጉያ » በተለይ አዲስ ሙዚቃ ተለቀቀ ከተባለ አካባቢዉ ላይ ቆመዉ ማድመጫቸዉ ነበር፤ የሆነ ሆነና አንጋፋዉ ሙዚቀኛ አያሌዉ መስፍን የት ይሆን? የሙዚቃዉን መድረክ ተዉዉ እንዴ?

    ስለአገር ፍቅር ስለፍትህ፤ ስለአንድነት ስለፍቅር አዚሟል

    አዘጋጆች፦ አዜብ ታደሰ እና ተስፋለም ወልደየስ (ዶይቸ ቬለ)
    —–
    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    አርቲስት አያሌዉ መስፍን


    Semonegna
    Keymaster

    ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ ተቀብሎ ያሰለጠናቸውን 198 ተማሪዎች ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ አስመረቀ
    —–

    ፍቼ (ሰሞነኛ) – ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ ተቀብሎ ያሰለጠናቸውን 198 ተማሪዎች ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ቅዳሜ ሀምሌ 6 ቀን 2011 ዓ.ም በታላቅ ድምቀት አስመርቋል። በምርቃት ሥነ-ስርዓቱ ላይ የተለያዩ ጥሪ የተደረገላቸዉ እንግዶችና ከፍተኛ ባለስልጣናት ተገኝተዋል።

    በምርቃት መርሀግብሩ ላይ የተገኙት የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ ለተመራቂዎች ባስተላለፉት መልዕት ‛ከጀግናው ጀነራል ታደሰ ብሩ መገኛና ከየዋኋ እናት አበበች ጎበና አገር የምትመረቁ ተማሪዎች በጀግንነት ሀገርን ማሻገር፣ በየዋህነት ሁሉን ማቀፍ መርሀችሁ ሊሆን ይገባል’ ብለዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት በበኩላቸው ‛መማር ለራስ ብቻ መኖርና መለወጥ ሳይሆን ለሀገራችን ህዝብ ችግር መፍትሄ መፈለግ ነው’ በማለት የዕለቱ ተመራቂዎች የሀገራቸውን ችግር የሚፈቱ ብርቱ ዜጎች እንዲሆኑ አበክረው ተናግረዋል።

    የዕለቱ የክብር እንግዳም በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ልማት ዘርፍ አስተባባሪ የሆኑት ዶ/ር ግርማ አመንቴ ሲሆኑ በዕለቱ ባስተላለፉት መልዕክት ‛በዓለም ላይ ያለምንም ድንበር ከሀገራችሁ ጀምሮ በየትኛዉም ቦታ የመሥራትና ማንኛዉንም ዕድሎች በመለየትና በመጠቀም በምክንያታዊነት፤ ከስሜታዊነት የወጡ ዉሳኔዎችን በመዉሰድ ለዓለም ትልቅ አስተዋጽኦ የምታደርጉ ዜጎች ለመሆን ራሳችሁን ማዘጋጀት ይጠበቅባችኋል’ ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲው ከተቋቋመ ጊዜ ጀምሮ ለሦስት ዓመታት በሁለት ኮሌጆች፥ ማለትም በቢዝነስና ኢኮኖሚክስ እንዲሁም በእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ኮሌጆች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች በታላቅ ድምቀት አስመርቋል።

    በምርቃት ሥነ-ስርዓቱ ላይ የተለያዩ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና ከፍተኛ ባለስልጣናት ተገኝተዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    Semonegna
    Keymaster

    ‘በሕገ-ረቂቁ እንዲካተቱ ያቀረብናቸው ማሻሻያዎች አልተካተቱም፤ ሃሳቦቻችንና አስተያየቶቻችን ያልተካተቱበትን ሰነድ ለመቀበል እንቸገራለን’ በማለት የተወሰኑ የተፎካካሪ ፓርቲ ተወካዮች መድረኩን ረግጠው መውጣታቸውን የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስታውቋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግ፣ ፍትህና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኢትዮጵያ ምርጫና የፖለቲካ ፓርቲዎች ሕገ-ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ ከተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ከተለያዩ ማኅበራት ተወካዮች ጋር ተወያይቷል።

    ‘በሕገ-ረቂቁ እንዲካተቱ ያቀረብናቸው ማሻሻያዎች አልተካተቱም፤ ሃሳቦቻችንና አስተያየቶቻችን ያልተካተቱበትን ሰነድ ለመቀበል እንቸገራለን’ በማለት የተወሰኑ የተፎካካሪ ፓርቲ ተወካዮች መድረኩን ረግጠው መውጣታቸውን የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስታውቋል።

    እንዲካተቱ ያቀረብናቸው ማሻሻያዎች ሳይካተቱ ሕገ-ረቂቁ እንዳይጸድቅ ሲሉ የተፎካካሪ ፓርቲ ተወካዮቹ ቋሚ ኮሚቴውን አሳስበዋል።

    የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ወይዘሮ የሺእመቤት ነጋሽ በበኩላቸው መሠረታዊ ማሻሻያዎች የተደረገባቸው አሥራ ሦስት ነጥቦች በሕገ-ረቂቁ መካተታቸውን ገልጸው፣ የብዙሃኑን የተፎካካሪ ፓርቲ ሃሳብና አስተያየት አካተናል ብለዋል።

    ማሻሻያዎቻችን አልተካተቱም ያሉ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች እስከ ሐምሌ 22 ቀን 2011 ዓ.ም. ድረስ ለቋሚ ኮሚቴው በጽሑፍ ማቅረብ እንደሚችሉም ወይዘሮ የሺእመቤት አሳውቀዋል።

    በውይይቱ ላይ የመንግሥት ሠራተኞች ለምርጫ በዕጩነት ከተመዘገቡበት ጊዜ ጀምሮ የምርጫ ሂደቱ እስኪጠናቀቅ ድረስ ከሥራ ገበታቸው በጊዜያዊነት እንደሚለቁና ደመወዝና ጥቅማ-ጥቅማቸውም እንደማይከር በሚዘረዝረው ረቂቅ-ሕግ አንቀጽ 33 ላይ ሰፋ ያለ ውይይት ተደርጎበታል።

    በደመወዙ ኑሮውን መደጎም ያልቻለን የመንግሥት ሠራተኛ ለምርጫ በዕጩነት ከተመዘገበበት ጊዜ ጀምሮ ደመወዙና ጥቅማ-ጥቅሙ አይከበርም ማለት ወደ ምርጫ አትግቡ ከማለት ለይተን አናየውም ብለዋል የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች ተወካዮቹ።

    የመንግሥት ሠራተኞች በሥራ ኃላፊነት ያገኙትን ስልጣን፣ የመንግሥትንና የሕዝብን ሃብትና ንብረት ለምርጫው አገልግሎት እንዳያውሉት ለማስቻል እንደሆነ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወይዘሪት ብርቱካን ሚዴቅሳ ተናግረዋል።

    ረቂቅ ሕጉ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ምሥረታ ጀምሮ እስከ የመሥራች ቁጥር አባላት ድረስ አዳዲስ አሠራሮችን እንዳካተተም ተገልጿል።

    አንድ ሃገር-አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲ ለመመሥረት ቢያንስ አስር ሺህ እንዲሁም አንድ የክልል ፓርቲ ለመመሥረት ደግሞ ቢያንስ አራት ሺህ አባላት እንደሚያስፈልጉ በረቂቅ ሕጉ ተጠቅሷል።

    ሃገር አቀፍም ሆነ የክልል ፓርቲ ለመመሥረት ሃገሪቱ ያለችበት ተጨባጭ ሁኔታ የተጠቀሰውን የመሥራች ቁጥር አባላት ለማሟላት እንደሚቸገሩ የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎቹ ተናግረዋል።

    መቶ ሚሊዮን ሕዝብ ባለበት ሃገር የተጠቀሰውን የመሥራች ቁጥር አባል ማሟላት አስቸጋሪ እንደማይሆን ወይዘሪት ብርቱካን ሚዴቅሳ አብራርተዋል።

    በግንቦት ወር 2011 ዓ.ም. 107 የነበሩ የተፎካካሪ ፓርቲዎች ቁጥር አሁን ላይ 137 እንደደረሰ ወይዘሪት ብርቱካን ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    [caption id="attachment_11503" align="aligncenter" width="600"]የተፎካካሪ ፓርቲ ተወካዮች የተፎካካሪ ፓርቲ ተወካዮች[/caption]


    Anonymous
    Inactive

    አዲሱ የአምለሰት ሙጬ ፊልም ‹‹ ምን አለሽ? ›› የሚል ርዕስ ተሰጥቶታል። ይህ ቃል ላልቶ እና ጠብቆ ሲነበብ የተለያየ ትርጉም ይሰጣል። ደግነቱ ላልቶም ጠብቆም ቢነበብ የፊልሙ ርዕስ ነው። ሁለቱም ትርጉም የፊልሙ ጭብጥ ነው። ይሄ ቃል ሌላም ማብራሪያ እንድንሰጥ ያስገድደናል።

    ዋለልኝ አየለ (አዲስ ዘመን ዕለታዊ ጋዜጣ)

    ከብዙ መገናኛ ብዙኃን እና ድረ-ገጾች አንድ ያስተዋልኩት ነገር “የፊልሙን ኢንዱስትሪ አንድ ደረጃ ከፍ የሚያደርግ” የሚል አገላለጽ ነበር። ይህ ፊልም ሦስት ዓመታት እና አምስት ሚሊዮን ብር ወስዷል። የፊልሙ ባለቤት ራሷ ታዋቂ ብትሆንም የታዋቂው ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) ሚስት መሆኗ ይመስላል ፊልሙን ገና ሳይታይ ዝነኛ አድርጎታል። ምክንያቱም ሌሎች ፊልሞች ከመታየታቸው በፊት እንዲህ ስማቸው ሲጠራ ስላልሰማን ነው። ማን ያውቃል ሲታይ ደግሞ እንደተባለውም የፊልሙን ኢንዱስትሪ ከፍ የሚያደርግ ቢሆንስ? ለመሆኑ በፊልሙ ውስጥ ምን አለ ይሆን?

    ስለ ‹‹ ምን አለሽ? ›› ፊልም ባለፈው ሰኞ ሐምሌ 8 ቀን 2011 ዓ.ም. ለመገናኛ ብዙኃን ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል። የፊልሙ ደራሲ፣ ዳይሬክተር እና ፕሮዲዩሰር አርቲስት አምለሰት ሙጬ ማብራሪያ ሰጥታለች።

    ፊልሙ ‹‹ ምን አለሽ? ›› የሚል ርዕስ ተሰጥቶታል። ይህ ቃል ላልቶ እና ጠብቆ ሲነበብ የተለያየ ትርጉም ይሰጣል። ደግነቱ ላልቶም ጠብቆም ቢነበብ የፊልሙ ርዕስ ነው። ሁለቱም ትርጉም የፊልሙ ጭብጥ ነው። ይሄ ቃል ሌላም ማብራሪያ እንድንሰጥ ያስገድደናል።

    መርካቶ አካባቢ ‹‹ምን አለሽ ተራ›› የሚባል ሰፈር እንዳለ እናውቃለን። የዚህ ፊልም መቼት ደግሞ መርካቶ ነው። የሆነው በአጋጣሚ ሳይሆን ታስቦበት ነው። ‹‹ምን አለሽ ተራ›› ይህን ስያሜ ያገኘው ቦታው የገበያ ቦታ ስለሆነና እዚያ የሄደ ሰው ምንም እንደማያጣ ስለሚታወቅ ነው። ለመሆኑ የፊልሙ መቼት ለምን መርካቶ ሆነ?

    መርካቶ ማለት ትንሿ ኢትዮጵያ ማለት ነው። ከየትም የመጣ ሰው የሚገናኝበት ነው፤ የታታሪ ሰዎች መገኛ ነው፤ የሥራ ቦታ ነው። የፊልሙ ባለቤቶች የተጠቀሙትን ገለጻ ስንጠቀም ደግሞ መርካቶ እንዲህ ነው።

    ‹‹ሙስሊም ሲሰግድ የክርስቲያኑ በር ላይ አንጥፎ ነው፤ ክርስቲያን ታቦት ሲያወጣ ሙስሊሙ መንገድ እየጠረገለት ነው›› የፊልሙ ባለቤት የሆነችው የአምለሰት ሙጬ ባለቤት ደግሞ ‹‹ራጉኤል አይደል ወይ የአንዋር ጎረቤት›› የሚለው ዘፈኑ የበለጠ ግልጽ አድርጎታል። መርካቶ በእነዚህ ምክንያቶች ለፊልሙ መቼት ተመረጠ። የአፍሪካ ትልቁ የገበያ ማዕከል ነው፤ የአገሪቱ ታታሪ ሠራተኞች መዳረሻ ነው።

    የፊልሙ ጭብጥ ደግሞ ከዚህ ጋር ይሄድልናል። ዋና ገጸ ባህሪዋ ሯጭ ናት፤ ድህነትን በሩጫ ማሸነፍ እንዳለብን ታምናለች፡ ፡ ጠንክሮ በመሥራት ከድህነት ለመላቀቅ ሩጫ እንደሚያስፈልግ ታምናለች። በሯጯ እምነት ድህነት ያለው ጭንቅላት ውስጥ ነው፤ የመሥራት ወኔ ካለ የትኛውም ነገር ይሠራል። ሩጫ ያለው ደግሞ መርካቶ ነው። መርካቶ ውስጥ ያለ ነጋዴ ልብ ብለን ብናይ ቁጭ ብሎ የሚዝናናበትና የሚተኛበት ጊዜ የለውም፤ ሁሌም ሥራ ላይ ነው።

    ሩጫ የተመረጠበት ሌላም ምክንያት አለው። የፊልሙ ዋና ዓላማ ኢትዮጵያን ማስተዋወቅ ነው። ኢትዮጵያን ለማስተዋወቅ ደግሞ ሩጫ ጥሩ ሽፋን ሆኖ ተገኝቷል፤ ምክንያቱም ኢትዮጵያ በሩጫ ስለምትታወቅ። በፊልሙ ውስጥ ሦስት ነገሮች መታወቅ እንዳለባቸው አምለሰት ተናግራለች፤ ድህነት፣ አኩሪ ታሪክ እና ሩጫ። ከአኩሪ ታሪካችን እና የሩጫ ዝናችን ጋር ድህነት እየተፎካከረ ይገኛል፤ ‹‹ይህን ድህነት በሩጫ ማሸነፍ አለብን!›› የደራሲዋ እምነት ነው።

    የ‹‹ ምን አለሽ? ›› ቃል መንታ ትርጉሞች

    ቃሉ ጠብቆ ሲነበብ፤ ‹‹ምንድን ነው ያለሽ? ምን ይዘሻል? ምን ይኖርሻል…?›› (“What do you have?”) የሚሉ ትርጉሞች ይሰጠናል። እንደተባለው ፊልሙ የኢትዮጵያን ታሪክ እና ዝና ማስተዋወቅ ነው፤ ይህን ታሪክና ዝና ሲያስተዋወቅ ኢትዮጵያ ‹‹ምን አላት? በውስጧ ምን ይገኛል? እነማን አሉባት?›› የሚለውን ይመልሳል። በፊልሙ ውስጥ ከ400 በላይ ተዋናዮች መሳተፋቸው ደግሞ ይሄን እንደሚያሳይ ይነግረናል።

    ቃሉ ላልቶ ሲነበብ ‹‹ምን ጠየቀሽ?›› (“What did he ask you?”) የሚል ትርጉም ይሰጠናል። ይሄ ጥያቄ ለኢትዮጵያ ይሆናል። ዓለም ምን አለሽ(ምን ጠየቀሽ) ተብላ ትጠየቃለች። ዓለም ስለኢትዮጵያ ምን እንደሚል ይነገርበታል ማለት ነው። ስለድህነቷም ይሁን ስለአኩሪ ታሪክ፣ ወግ እና ባህሏ አገራት ምን እንደሚሉ እናይበታለን።

    ድምፃዊ አብነት አጎናፍር በአንድ ወቅት ከሸገር ኤፍ ኤም ጋር ባደረገው ቃለመጠይቅ ሲናገር፤ ‹‹ለካ አያውቁንም›› የሚለውን ዘፈኑን የሠራው ውጭ አገር ሄዶ ስለኢትዮጵያ ምንም የማያውቁ አጋጥሞት ነው። አብነትና ጓደኞቹ በሆነ አጋጣሚ ታሰሩ፤የታሰሩበትም ከየት እንደመጡ ተጠየቁ፤ ‹‹ከኢትዮጵያ›› ቢሉም ይችን አገር ሊያውቁላቸው አልቻሉም። የተራራ ስም ቢጠሩ፣ የዓድዋን ታሪክ ቢጠቅሱ፣የአትሌት ስም ቢደረድሩ ምንም ሊያውቁላቸው አልቻሉም፤ ‹‹እኛ ግን የእነርሱን የልደት ቀን ሳይቀር እናውቃለን›› ያለው አብነት በዚህ ቁጭት ተነሳስቶ ‹‹ለካ አያውቁንም›› የሚለውን ዘፈን ሠርቷል። ምናልባት አምለሰትም ይሄ አጋጥሟት ይሆን?

    ‹‹ ምን አለሽ? ›› ፊልም ከውጭ ባለሙያዎች ጋር ነው የተሠራው። ይህም የይዘትና የቴክኒክ ዘመናዊነት እንዲኖረው አድርጓል። በይዘት በኩል ደራሲዋ እንደተናገረችው፤ የሥራ ትጋትን ለማሳየት ከውጭዎቹ የተወሰደው ነገር የጊዜ አጠቃቀም ነው። እነርሱ ጋ እያንዳንዷ ደቂቃ ዋጋ አላት፤ ይሄን ከእነርሱ ተሞክሮ ተወስዶ ተሠርቷል።

    በቴክኒካል ጉዳይ ሆሊውድ የሚጠቀማቸው ዘመናዊ መሳሪያዎችን ተጠቅሟል፤ መጠቀም ብቻ አይደለም፤ አዳዲስ ተዋንያን የእንዲህ ዓይነት ዘመናዊ መሳሪያዎችን አጠቃቀም እንዲለምዱ ተደርጓል።

    በሌላ በኩል በሚያስፈልግበት ጉዳይ ሁሉ የባለሙያ ድጋፍ ተደርጎበት ነው። ዋና ገጸ ባህሪዋ ሯጭ እንደመሆኗ የአትሌቲክስ ባለሙያ ያስፈልገዋል፤ ይሄንንም ተጠቅሟል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ከፍተኛ ሚና እንደነበረው በመግለጫው ላይ ተነግሯል። ከአልባሳት ድጋፍ ጀምሮ፣ ምን ዓይነት ልብስ በምን ሁኔታ እንደሚያስፈልግ የሙያ ድጋፍ አድርጓል። ፊልሞች እንዲህ በሚመለከተው ባለሙያ ድጋፍ ሲሠሩ ስነ ምግባሩንና ሙያውን የጠበቀ ይሆናሉና ቢለመድ እንላለን!

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ምን አለሽ? አምለሰት ሙጬ


    Anonymous
    Inactive

    ባህር ዳር (አብመድ)፦ ሰኞ ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ሹመታቸው የጸደቀላቸው የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ተመስገን ጥሩነህ ለምክር ቤት አባላትና ለሕዝቡ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    እንደ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝደንትነት ለመጀመሪያ ጊዜያቸው ንግግር ያደረጉት አቶ ተመስገን በመልዕክታቸው የወሰንና የማንነት ጥያቄዎች ለግጭት ምክንያት ሳይሆኑ በሕግ እንዲመለሱ እንደሚሠሩ ገልጸዋል።

    በተጨማሪም የኢኮኖሚ ዕድገቱም ትኩረት ይሰጠዋል ብለዋል። ከዚህ ጋር በተያያዘም ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለመኖሪያ ቤቶች ግንባታ እና ለኢንቨስትመንት ዕድገትም አትኩሮት እንደሚሰጥ አስገንዝበዋል።

    አቶ ተመስገን ጥሩነህ አስከትለውም “የሕግ የበላይነትን ማስፈንም ለነገ የምንለው ጉዳይ አይሆንም” ብለዋል ለአማራ ክልል ሕዝብ ባስተላለፉት መልዕክት።

    ለመሆኑ አቶ ተመስገን ጥሩነህ ድንቁ ማን ናቸው?

    አቶ ተመስገን ጥሩነህ ምሥራቅ ጎጃም ዞን ብቸና ወረዳ ወይራ ቀበሌ ነው የተወለዱት። ከታችኛው የመንግሥት መዋቅር እስከ ፌዴራል ከፍተኛ የኃላፊነት ቦታዎችም አገልግለዋል።

    በትምህርት ደረጃ የ1ኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በትውልድ ቀያቸው በጎተራ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተከታትለዋል፤ የመለስተኛና 2ኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ደግሞ በብቸና በሚገኘው የበላይ ዘለቀ ትምህርት ቤት ነው ያጠናቀቁት። የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከማይክሮሊንክ ኮሌጅ በሶፍትዌር ዘርፍ እና የሁለተኛ ዲግሪቸያውን ደግሞ እንግሊዝ ሀገር ከሚገኘው ግሪንዊች ዩኒቨርሲቲ (University of Greenwich) በለውጥ አመራርና አስተዳደር ተከታትለዋል።

    ርዕሰ መስተዳድር ተመስገን ጥሩነህ ድንቁ በ አማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት እና በፌደራል መንግስት ደረጃ በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች አገልግለዋል።

    በአማራ ክልል የርዕሰ መስተዳድሩ የፀጥታ እና ቴክኖሎጂ አማካሪ፣ የአማራ ገጠር መንገዶች ባለስልጣን ምክትል ሥራ አስኪያጅ፣ የአማራ ገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የምሥራቅ ጎጃም ዞን ዋና አስተዳዳሪ፣ የአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር በመሆን ሠርተዋል።

    ፌደራል መንግስት ደረጃ የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ (Information Network Security Agency) ዋና ዳይሬክተር እና የኢትዮ-ቴሌኮም ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ በመሆንም አገልግለዋል።

    አቶ ተመስገን የሀገር መከላከያ ሠራዊት መረጃ ዋና መምሪያ፣ የኤሌክትሮኒክስ እና የቴክኒካል መረጃ መምሪያ ኃላፊ በመሆንም አገልግለዋል። በመከላከያ ሠራዊት ውስጥም እስከ ሻለቃነት ማዕረግ ደርሰዋል።

    የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት ኤጀንሲ መሥራች ከመሆን ባለፈ በዚሁ መሥሪያ ቤት ከመምሪያ ኃላፊነት እስከ ዋና ዳይሬክተርነትም አገልግለዋል። እስከ ዛሬ ድረስ ደግሞ በሚኒስትር ማዕረግ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ በመሆን ሲያገለግሉ ቆይተዋል።

    ምንጭ፦ የአማራ መገናኛ ብዙሀን ድርጅት (አብመድ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አቶ ተመስገን ጥሩነህ


    Anonymous
    Inactive

    [ ትዕግስት ሚልኬሳ እና ባሏ የማገጠባት ሴትየ በኢትዮጵያውያን ዓይን ]

    ሴትየዋ በሞባይል ፈንታ ሽጉጥ ይዛ ገብታ ቢሆንስ… ቪዲዮ በመቅረጽ ፈንታ ጥይት ተኩሳ ቢሆንስ…?
    (ጋዜጠኛ መላኩ ብርሃኑ)

    በሰንሰለት ድራማ ተዋናይዋ ትዕግስት ሚልኬሳ ጉዳይ ሙሉ ቀን ሲጻፍ የዋለውን “ትንተና” ባላውቅም የአንዳንዶችን አስተያየት ግን በአለፍ አገደም አየሁት። ብዙዎች በተለይ ሴቶች የተዋናይቷን ድርጊት “ያለ እና የሚኖር” መሆኑን እያረጋገጡ “ለቀቅ አድርጓት’ ሲሉ አይቻለሁ። በተበዳይዋ ሚስት ላይ የነገር እስክስታ የወረዱት ግን ይበዛሉ። ይህች ሴት ባሏንና አንዲት አብራው የተኛችን ሴት ድንገት ስታገኛቸው እንኳን ቪዲዮ መቅረጽ ቀርቶ አልጋ ላይ እያሉ ባገኘችው ነገር ብትገላቸው ጭምር ሕግ በጊዜው የነበረችበትን የስነ ዐዕምሮ ሁኔታ (state of mind) ከግንዛቤ በማስገባት ቅጣት ከማቅለል ነጻ እስከመልቀቅ ሊደርስ የሚችል ፍትህ ሊሰጣት እንደሚችል ግን ማወቅ ያስፈልጋል።

    የተዋናይቷን (ትዕግስት ሚልኬሳ) ጉዳይ ዝርዝሩን ስለማናውቅ (ሚስት እንዳለው አታውቅም ነበር፣ በመጠጥ ሃይል ተገፋፍታ ነበር፣ ስሜት ፈትኗት ነበር፣… ምናምን የሚሉ ተገማች ግምቶችን ከግምት አስገብተን) ለጊዜው እንለፈውና….

    (ስለመልካም ስነምግባር እና ለትዳር ስለምንሰጠው ከፍ ያለ ዋጋ ብለን ) ሰው እንውቀስ ከተባለ ከልጅቷ ይልቅ ከፍ ባለ መጠን መወቀስ ያለበት ልጁ ነው ብዬ አስባለሁ። አንድ ወንድ ባለትዳር ሆኖ ፣ በጋራ ቤታቸው፣ ከሚስቱ ጋር በሚተኛበት አልጋ ላይ ሌላ ሴት ይዞ ተኝቶ ከተገኘ አስቀድሞ ትዳሩን በራሱ አፍርሶታል ማለት ይቀላል። አስቀድሞ መለያየት ሲቻል አትሊስት ሚስቱን በዚህ ያህል መጠን ሞራሏን ሊጎዳው አይገባውም ነበር።

    ነገሩ ከሆነ ዘንዳ እንግዲህ……

    (የሕግ ባለሙያዎች’ከህሊና ዳኝነት’ ጋር ስላለው ጉዳይ እዚህ ጋ ያግዙኝና ) በኢትዮጵያ የፍትህ ስርዓት አንድ ሰው ድንገት የራስ ህሊናን መቆጣጠር በማይቻልበት ሁኔታ ውስጥ ሆኖ ፣ በዚያ ተነሳሽነት ወንጀል ከፈጸመና ይህንን በበቂ ሁኔታ በማያወላዳ ማስረጃ ማረጋገጥ ከቻለ በነጻ የሚሰናበትበት ዕድል ሰፊ ነው።

    ለዚህ ደግሞ ራሴ በቅርብ የማውቀው አንድ ማስረጃ ላቅርብ። (ታሪኩ “ፍቅርና ወንጀል” በሚለው ቅጽ አንድ መጽሃፌ ውስጥ የተካተተ ረጅም የፍቅር እና የወንጀል ታሪክ ነው)

    አዲስ አበባ ውስጥ ሸራተን አካባቢ በአነድ ከብት ማርቢያ ግቢ ውስጥ ሁለት በስጋ የሚዛመዱ ሰራተኞች ግድግዳቸው በተያያዘ የቆርቆሮ ዛኒጋባዎች ውስጥ ይኖሩ ነበር።አንደኛው ሚስት አለችው። አንዱ ላጤ ነው። በአንድ የሃምሌ ወር ሌሊት (ቀኑ 12 ነው) ባለትዳሩ ሰውዬ ከሚስቱ ዕቅፍ ወጥቶ እንደተለመደው ላሞች ለማለብ ወደበረት ሄደ። አንድ ሰዓት ባልሞላ ጊዜ ዝናብ ስራ አላሰራ ሲለው ላስቲክ ራሱ ላይ ጣል ለማድረግ ፈለገና ያንኑ ለመውሰድ ተመልሶ ያልተሸጎረውን የቤቱን በር ገፋ አድርጎ ገባ። አልጋው ላይ ያየው ያልጠበቀው ትዕይንት ግን አቅሉን አሳተው። ዘመድየው ከላይ ሚስቱ ከታች “መርፌና ክር” ሆነዋል። (ከዚህ ቀደምም ይህንኑ ‘ባል ሲወጣ ውሽሜ ገባ’ አይነት ነገር የተላመዱት ይመስላል)

    በዚህ የተደናገጠው ባል ‘አረ አንተ ማነህ እግዚሃርን የማትፈራ?’ አለና ምላሽ ሲያጣ ጎንበስ ብሎ ባገኘው የብረት ዱላ ሁለቱንም እዛው በተኙበት ቀጥቅጦ አስቀራቸው። ወንድየው ዘመዱ መሆኑን ያወቀው ከገደለው በኋላ ነው። ከዚያም ሄዶ እጁን ለፖሊስ ሰጠ።

    አስታውሳለሁ… እኔ ስጠይቀው “የዕውነት አምላክና ቅዱስ ሚካዔል ረድተውኝ እንጂ መች እደርስባቸው ነበር” ነው ያለው።

    ጉዳዩን ሲያይ የቆየው ፍርድ ቤት ባል ያልጠበቀው ክስተት በገዛ አልጋው ላይ ተከስቶ እጅ ከፍንጅ ሲገጥመው የሚሰማውን ብስጭት እና ራስን ለመቆጣጠር ያለመቻል የስሜት ሁኔታ ከግምት በማስገባት፣ በዚህ ቅጽበት ለፖሊስ ወደማመልከት እና ጥፋተኛን በሕግ ወደማስቀጣት ቀና ሃሳብ ሊመጣ የሚችልበት ዕድልም ቀልብም እንደማይኖረው በማሰብ ፣ ወንጀሉ በአስገዳጅ የዐዕምሮ ሁኔታ ውስጥ ሆኖ የፈጸመው በመሆኑ ወዘተ የሚል ትንታኔ ሰጥቶ ሰውየውን ከወራት እስር በኋላ በነጻ አሰናብቶታል።

    እና ምን ለማለት ነው …

    ሴትየዋ በዚያ የብስጭት ቅጽበት ውስጥ ሆና እንኳን ቪዲዮ ቀርጻ ማሰራጨት ቀርቶ ሁለቱንም ባገኘችው ነገር ‘ሲጥ’ ብታደርጋቸው ጭምር ህጉ በዚያ ቅጽበት ያላትን የህሊና ሁኔታ ከግምት በማስገባት ነጻ ሊያደርጋት ይችል እንደነበር ማሰብ ይበጃል። ያደረገችውን ብታደርግ (በጊዜው እኛም ብንሆን የሚሰማንን እና የምንሆነውን አናውቅምና) አይፈረድባትም ለማለት ያህል ነው። አንዳንዴ የብስጭት ደረጃችንን ስንገልጽ ” የማደርገውን አላውቅም ነበር” እንል የለ? እንደዚያ መሆኑ ነው።

    በግሌ ሴትየዋ የነበራት የሚገርም መረጋጋት እና የጤናማ ሃሳብ ሚዛኗ ያለመዛባቱ ሁኔታ በጣም አስደንቆኛል። ወደሌላ ወንጀል እና ሃሳብ አለመግባቷም ቢያንስ ለሰዎቹም ጠቅሟቸዋል። በትንሹም በትልቁም ወንጀል ፈጽመው ‘ሰይጣን አሳሳተኝ’ ለሚሉ ሰዎች ይህች ሴት ምሳሌ ትሆናለች። ሰይጣን ሁለተኛ አጠገቧም አይደርስ ከዚህ በኋላ ! ቂቂቂቂ

    (የሕግ ባለሙያዎች ትንታኔያችሁ ይጠበቃል!!)
    ጋዜጠኛ መላኩ ብርሃኑ

    ትዕግስት ሚልኬሳ


    Semonegna
    Keymaster

    ክበቡ የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል እንዲሁም ተዛማጅ እሴቶችን በማስተዋወቅ ቀደም ሲል በኢትዮጵያ የነበረውን ፍቅር፣ ሰላምና አብሮ የመኖር እሴት ለመጪው ትውልድ ለማስረከብ ጠንክሮ እንደሚሠራ እምነታቸው መሆኑን የድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ተናግረዋል።

    ድሬ ዳዋ (ሰሞነኛ) – “ቋንቋችንን፣ ባህላችንን፣ እሴቶቻችንንና ታርካችንን ጠብቀን ለመጪው ትውልድ ማስረከብ የአሁኑ ትውልድ ግዴታ ነው።” በሚል መሪ ቃል የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል ማበልፀጊያ ክበብ በድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ ተቋቁሟል። በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል ክበብ ምሥረታ ቀደም ብለው ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ያሬድ ማሞ፣ የኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል ክበብ ፕሬዝዳንት ተማሪ ገሊማ፣ የተማሪዎች ህብረት ፕሬዝዳንት ተማሪ ጥበቡ ሙሉጌታ እንዲሁም የ2011 ዓ.ም የተማሪዎች ምረቃ ኮሚቴ ሰብሳቢ ተማሪ ቢቅላ ጋሮምሳ የክበቡን መመሥረት በማብሰር መርሃ ግብሩን ይፋ አድርገዋል።

    ክበቡ የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ እና ባህልን በማስተዋወቅ ቀደም ሲል በኢትዮጵያ የነበረውን ፍቅርና ሰላም እንዲሁም አብሮ የመኖር እሴት ለመጪው ትውልድ ለማስረከብ ጠንክሮ እንደሚሠራ እምነታቸው መሆኑን የድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ያሬድ ማሞ ተናግረዋል። ዶ/ር ያሬድ አያይዘውም ክበቡ ለሌላ ዓላማና እኩይ ተግባር እንደማይውል ሙሉ እምነታቸው መሆኑን በመግለጽ፤ ግንባር ቀደም ክበብ በመሆኑ ሌሎች ብሔሮችም ተመሳሳይ ጥያቄ ይዘው ቢመጡ ክበቡ እነሱን የማገዝ ሃላፊነት እንዳለበት አሳስበዋል። በመጨረሻም ዶ/ር ያሬድ ተማሪዎቻችን ከተለያዩ ብሔር ብሔረሰብ በመምጣታቸው የራሳቸውን ቋንቋና ባህል ለማስተዋወቅ ክበብ ለመመሥረት ቢፈልጉ ዩኒቨርሲቲው እኩል ድጋፍ እንደሚያደርግም ገልፀዋል።

    በምስረታው ላይ ታዋቂ ሰዎች፣ አባገዳዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፎበታል። የኦሮሞን ባህል ከማስተዋወቅ አንጻርም የኦሮሞ ባህላዊ ምግቦች ቅምሻ ሥነ-ስርዓትና የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች አለባበስ ትዕይንትም ተካሂዷል። በእለቱ የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ፣ ባህልና ታርክ ላይ የተመሠረተ ጥናታዊ ጽሁፍ በዶ/ር ተሾሜ ኤጌሬ የጅማ ዩኒቨርሲቲ የኦሮሞ ገዳ እንስቲትዩት ኤክስክዩቲቭ ዳይሬክተር፡ በአፋን ኦሮሞ ቋንቋና ታርክ ጥናታዊ ጽሁፍ አቅርቦ በተሳታፊዎች ሰፊ ውይይት ተካሂዶበታል።

    የዩኒቨርሲቲው የአፋን ኦሮሞ ቋንቋና ባህል ክበብ ፕሬዝዳንት እና መሥራች ተማሪ ገልማ ብዱ እንደተናገረው ክበቡ ኃይማኖት ተኮር ነገሮችን ከማንፀባረቅና ከማንኛውም የፖለቲካ አመለካከት የፀዳመሆኑን በመግለጽ የኦሮሞን ቋንቋ እና ባህል ከሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች ጋር በማዋሀድ ልምድ ልውውጥ በማድረግ በልዩነታችን ውስጥ ውበት አንድነታችን የሚጠናከርበትና የሚካሄድበት ክበብ ነው ብሏል። በክበቡም የሌሎች ብሄር ብሄረሰቦች ተወላጆች አባል ሆነው መሳተፍና አኩሪ የኢትዮጵያዊነት መልካም ባህላቸውን ማበልጸግ እንደሚችሉ ተናግረዋል።

    በዩኒቨርሲቲው የተማሪዎች ህብረት ስር ክበባትን ማደራጀት በሚፈቅደው መመሪያ መሰረት የኦሮምኛ ቋንቋና ባህልን ለማበልፀግ እንደ አንድ ክበብ የኦሮምኛን ቋንቋና ባህል ክበብ ሚያዝያ 5 ቀን 2011 ዓ.ም. ተመሥርቷል። የክበቡም ምሥረታ በአፍራን ቀሎ ባንድ ጣዕመ ዜማ፣ መነባነብ በገጣሚ እና ደራሲ ሲሳይ ዘለገሃሬ እና በዩኒቨርሲቲያችን ተማሪዎች ቀርቧል። በዩኒቨርሲቲያችን እስታዲየም ከአዲስ አበባ በተጋበዙ ታዋቂ የኦሮምኛ ዘፋኞች፣ የቀድሞ የአፍራን ቀሎ መሥራቾችና ዘፋኞች ተገኝቷል። እንዲሁም የማነቃቂያ ንግግሮች፣ የዕውቅና እና የስጦታ ሥነ-ስርዓቶችም ተካሂዷል።

    ምንጭ፦ ድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል


    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በግንቦት ወር በይፋ ተመሥርቶ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር አብሮ ለመሥራት በሩ ክፍት መሆኑን ከገለፀ በኋላ የኢትዮጵያ ራዕይ ፓርቲ፥ የከምባታ ሕዝብ ኮንግረስ (ከሕኮ) ተከትሎ ራሱን አክስሞ ኢዜማን የተቀላቀለ ሁለተኛ ፓርቲ ሆኗል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ከተመሠረተ 11 ዓመታትን ያስቆጠረው የኢትዮጵያ ራዕይ ፓርቲ (ኢራፓ) ሐምሌ 8 ቀን 2011 ዓ.ም. በጠራው አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ መክሰሙን አስታወቀ።

    ኢራፓ ሐምሌ 8 ቀን 2011 ዓ.ም. በራስ ሆቴል ባካሄደው አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባዔ መክሰሙንና የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህን (ኢዜማ) መቀላቀሉን የኢራፓ ፕሬዝዳንት አቶ ተሻለ ሰብሮ አስታውቀዋል። ፓርቲው በጠቅላላ ጉባዔው ላይ 8 ነጥቦችን የያዘ የአቋም መግለጫውም ይፋ አድርጓል።

    ኢራፓ በአቋም መግለጫው፥ ኢትዮጵያ ያለችበትን ችግር ለመፍታትና ከምንጩ ለማድረቅ መንግሥት፣ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎችና መላው የሀገሪቱ ሕዝቦች በመቻቻል፣ በትዕግስትና በአብሮነት መሥራት እንዳለባቸው ገልጿል። “ጣት መቀሳሰሩን ወደ ጎን በመተው የምክክርና የድርድር መድረኮች ተዘጋጅተው ተቀራርቦ መነጋገር ይገባል” ሲል ፓርቲው ጥሪውን አቅርቧል።

    ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሲዳማ ዞን ክልል የመሆን ጥያቄን ሕዝበ ውሳኔ አስመልክቶ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    በጠቅላላ ጉባኤው መገባደጃ ላይ ኢዜማን በመወከል ንግግር ያደረጉት የኢዜማ መሪ ብርሃኑ ነጋ (ፕ/ር)፣ ኢዜማ የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች ይፈጥሯቸው ከነበሩ ህብረቶች በተለየ መልኩ ራሳቸውን ያከሰሙ ድርጅቶች በምርጫ ወረዳ የተዘረጉ መዋቅሮችን በመቀላቀል እንደአዲስ ፓርቲ የተመሠረተ ፓርቲ መሆኑን አስታውሰው፤ “ትንሽ ፓርቲ ውስጥ ትልቅ ከመሆን ትልቅ ፓርቲ ውስጥ ትንሽ ሰው መሆን ይሻላል” ሲሉ በመሠረታዊ መርኾች የተስማሙ የፖለቲካ ድርጅቶች አንድ ላይ ሆነው ሰፊ ድንኳን ያለው ጠንካራ ድርጅት የማቆምን አስፈላጊነትን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ራዕይ ፓርቲ አባላት በሚኖሩበት አካባቢ በተደራጁ የኢዜማ ምርጫ ወረዳ መዋቅሮች ውስጥ በንቃት እንዲሳተፉ ጥሪ ያደረጉት የኢዜማ መሪ፣ የሚያጋጥሙ ችግሮችን በሰከነ ውይይት እና በዴሞክራሲያዊ መንገድ የመፍታት ባሕል አዳብረን ኢዜማን ታሪክ የሚሠራ ድርጅት እናደርገዋለን ብለዋል።

    የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ለአማራ ሕዝብ ህልውና እና ለሀገር እንድነት አስፈላጊውን መስዋትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆኑን ገለፀ

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ ግንቦት 1 እና 2 ቀን 2011 ዓ.ም. በይፋ ተመሥርቶ ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር አብሮ ለመሥራት በሩ ክፍት መሆኑን ከገለፀ በኋላ ኢራፓ፣ የከምባታ ሕዝብ ኮንግረስ (ከሕኮ) ተከትሎ ራሱን አክስሞ ኢዜማን የተቀላቀለ ሁለተኛ ፓርቲ ሆኗል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)


    Semonegna
    Keymaster

    ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሲዳማ ዞን ክልል የመሆን ጥያቄን ሕዝበ ውሳኔ አስመልክቶ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግስት ምክር ቤት የሲዳማ ዞን መስተዳደር ምክር ቤት ውሳኔን መሰረት በማድረግ በህዳር 11 ቀን 2011 ዓ.ም. የሲዳማ ዞን የክልልነት ጥያቄን ለመወሰን ሕዝበ ውሳኔ እንዲደራጅለት ለኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ ጥያቄ ማቅረቡ ይታወሳል።

    በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድን እንደ አዲስ የማደራጀት፣ የምርጫ ቦርድ ስልጣንና ተግባር የሚወስነውን ሕግ የማርቀቅ እና በተወካዮች ምክር ቤት የማጸደቅ፣ የምርጫ ህጎችን የማሻሻል፣ ተቋማዊ ለውጦችን የማከናወን እንቅስቃቄ ሲደረግ ቆይቷል። ከነዚህ ተቋማዊ ለውጦች መካከል የቦርዱን ማቋቋሚያ አዋጅ መሰረት አድርጎ የተከናወነው የምርጫ ቦርድ አባላት መረጣ ዋነኛው ነው።

    በዚህም መሰረት ከዚህ የቦርድ አባለት መረጣ ሰፊ ምክክርና ከፍተኛ ጥንቃቄ ተደርጐበት ከተለየ በኋላ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኔ 06 ቀን 2011 ዓ.ም. ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ ተጨማሪ አራት የቦርድ አባላት ሹመት ተከናውኖ ቦርዱ አባላት ተሟልተውለት ሥራውን ጀምሯል።

    ቦርዱ ተሟልቶ ሥራ በጀመረበት ባለፈው አንድ ወር በእንጥልጥል የሚገኙ እና አስቸኳይ ናቸው ያላቸው ጉዳዮች ላይ ውሳኔ በመስጠት ላይ ይገኛል።

    በቦርዱ አለመሟላት ምክንያት በእንጥልጥል ከቆዮት ጉዳዮች አንዱ ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች ሕዝቦች ክልል ምክር ቤት ለቦርዱ የቀረበው የሲዳማ ዞን የክልልነት ጥያቄን ሕዝበ ውሳኔ ማደራጀት ነው።

    ቦርዱ ሥራ ከጀመረ አንስቶ የሲዳማ ዞን ክልልነትን የሚመለከቱ በተለያዩ ጊዚያት የቀረቡትን ጥያቄዎች ከመመልከቱም በላይ ከክልሉና የዞን መስተዳድር አመራሮች ጋር በጉዳዩ ላይ ውይይት አድርጓል።

    እንደሚታወቀው የሲዳማ ዞን የክልልነት ሕዝበ ውሳኔ የማደራጀት ጥያቄ ከክልሉ ምክር ቤት ለቦርዱ የደረሰው ህዳር 12/2011 ዓ.ም. ሲሆን በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 47/3/ለ/ ለክልሉ የተሰጠው “ጥያቄው ከደረሰበት ቀን ጀምሮ በአንድ ዓመት” የሚለው የማደራጀት ጊዜ ገደብ ለቦርዱም ተግባራዊ የሚደረግ ነው።

    በመሆኑ በሕግ መንግስቱ የተጠቀሰው የጊዜ ገደብ ሊጠናቀቅ በቀሩት 5 ወራት ውስጥ ሕዝበ ውሳኔውን ለማከናወን የመጀመሪያ ደረጃ ዝግጅት እያደረገ ይገኛል።

    ሕዝበ ውሳኔ የሚከናወነው የሕዝብን ፍላጐትና ውሳኔ ህጋዊ እና ነፃ በሆነ አግባብ መሰጠቱን ለማረጋገጥ ነው። በመሆኑም ቦርዱ ተገቢና በቂ ዝግጅት አድርጐ ሕዝበ ውሳኔውን ማካሄድ ይችል ዘንድ የሚያደርጋቸው ዝግጅቶች፦

    • የሕዝበ ውሳኔ አካሄድ የሚመራበት የሥነ-ስርዓት መመሪያ ማዘጋጀት
    • የሕዝበ ውሳኔ አጠቃላይ ጊዜ ሰሌዳና በጀት ማዘጋጀት
    • በሕዝበ ውሳኔ ዝግጅትና ድምፅ መስጠት ሂደት ስለሚኖረው የፀጥታ አጠባበቅ ሁኔታ ግብረ ኃይል ማደራጀትና ዕቅድ ማፅደቅ
    • ገለልተኛ የምርጫ አስፈፃሚዎች መመልመል፣ ማሰልጠንና ማሰማራት
    • ከባለድርሻ አካላት ጋር የጋራ መድረክ ማዘጋጀት፣ የድርጊት መርሃ ግብር ማውጣት
    • በሕዝበ ውሳኔ አፈፃፄም ሂደቱ ላይ የጋራ ምክክር መርሃ ግብሮችን አውጥቶ መተግበር
    • የሰነድና ቁሳቁስ ዝግጅትና ህትመት ሥራዎች ማከናወን
    • ድምፅ መስጫ ወረቀቶችና ፖስተሮች ማዘጋጀት፣ ማሳተም፣ ማሰራጨት
    • ሕዝበ ውሳኔ ድምጽ ማሰጠት
    • ቆጠራና ውጤት ማሳወቅ

    ሲሆኑ በሌላ በኩል ሂደቱ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላትም የሚጠበቅባቸውን ዝግጅት ማድረግ ይኖርባቸዋል።

    በዚህም መሰረት፦

    1. የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ምክር ቤት ከክልሉ መንግስትና ከዞኑ መስተዳደር ጋር በመመካከር በአሁኑ ወቅት የክልሉም የዞኑም አስተዳደር ዋና ከተማ ሆና የምታገለግለው የሀዋሳ ከተማ የሕዝበ ውሳኔው ውጤት የሲዳማን ክልል መሆን የሚያረጋግጥ ቢሆን በከተማዋ ላይ ሁለቱ አካላት የሚኖራቸውን መብትና ከዚህ ጋር በተያያዘ የሚነሱ የሃብት ክፍፍል ጥያቄዎችን የሚያስተናግዱበትን አሠራር አዘጋጅተው ለቦርዱ እንዲያሳውቁ፤
    2. በአዋጅ 532/1999 አንቀጽ 107 በተጠቀሰው የትብብር ድንጋጌ መሰረት የሕዝበ ውሳኔው ጸጥታና ደኅነትን (electoral security) ማስጠበቅን አስመልክቶ የፌደራል ፓሊስ፣ የክልሉ ፓሊስና የዞኑ ፓሊስ በትብብር የሚሠሩበትን ዝርዝር እቅድ እንዲያወጡና ከቦርድ ጋር ተባብረው እንዲሠሩ፤
    3. የደቡብ ክልል ምክር ቤት በሲዳማ ዞን የሚኖሩ የተለያዩ የሌሎች ብሄር ብሔረሰብ አባላት ከሕዝበ ውሳኔው በኋላ የሚኖራቸውን ህጋዊ የመብቶች ጥበቃ አስመልክቶ ግልጽ አስተዳደራዊና ህጋዊ ማእቀፍ እንዲያዘጋጅና ለቦርዱ እንዲያሳውቅ ምርጫ ቦርድ የወሰነ ሲሆን፥ ከዚህም በተጨማሪ የሚመለከታቸው አካላት ከላይ የተጠቀሱት ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ምላሽ እስከ ሐምሌ 19 ቀን 2011 ዓ.ም. በጽሁፍ እንዲያሳውቁ ወስኗል፤
    4. በዚህ አጋጣሚ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሕገ መንግስቱና በምርጫ አዋጁ የተሰጠውን ኃላፊነት ዓለም አቀፍ የምርጫ መሰረታዊ መርሆዎች ጋር በማጣመር ኃላፊነቱን ለመወጣት ከፍተኛ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ለመግለጽ ይወዳል።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ
    ሐምሌ 10/2011 ዓ.ም.

    የሲዳማ ዞን ክልል የመሆን ጥያቄን ሕዝበ ውሳኔ አስመልክቶ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ


    Semonegna
    Keymaster

    የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን) ማዕከላዊ ኮሚቴ ላለፉት 10 ተከታታይ ቀናት ባካሄደዉ ስብሰባ ሀገራዊ የስላምና ፀጥታ ሁኔታን ከአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታ ጋር በማገናዘብ ገምግሟል።

    ከደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን) ማዕከላዊ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ

    ድርጅታችን የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን) ባለፉት 28 ዓመታት የደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦችን አስተባብሮ በመምራት በክልሉ ዉስጥ የልማት፤ የሰላም፤ የዴሞክራሲ ድሎችን አስመዝግቧል። በሀገራችን ከሚገኙ ብሔሮች ብሔረሰቦች 70 በመቶዉ ይዞ የተደራጀ ነዉ። የደቡብ ብሔሮች፤ ብሔረሰቦችና፤ ሕዝቦች ክልል ሕዝቦችን በህብረ-ብሔራዊ አንድነት እየመራ የሚገኝ ዲሞክራሲያዊና ሕዝባዊ ድርጅት ነው። ይህም ክልላችን የብዝሀነት ማዕከል፤ የአብሮነትና የአንድነት ማሳያ እንዲሆን አድርጓል።

    ደኢህዴን ለሕዝቦች እንድነትና ለሀገር ግንባታ ግንባር ቀደም ሚናዉን የተወጣና እየተወጣ የሚገኝ ድርጅት ሲሆን ሀገራችን የገጠማትን ተግዳሮቶች ለመፍታት መፍትሄ የሚሆኑ ዉሳኔዎችን ያስተላለፈና ስኬቶችን ያስመዘገበ ድርጅት እንደሆነም ገምግሟል። በሀገራችን ያጋጠሙ ችግሮችን ለማለፍ በተደረጉ ትግሎች ከእህት ድርጅቶች ጋር በመሆን የራሱን ጉልህ ሚና የተወጣ ድርጅት ነዉ። በሀገራችን ኢትዮጵያ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ያገጠሙ ችግሮችን ለመፍታት በተደረጉ ትግሎች ሠላማዊ የስልጣን ሸግግር ለማድረግ ታሪካዊ ኃላፊነት ተወጥቷል። ስለሆነም ድርጅታችን ሀገራዊ ለዉጡ እዉን እንዲሆን ግንባር ቀደም ሚና የተወጣና ታሪካዊ ዉሳኔ ያስተላለፈ ድርጅት እንደመሆኑ ለቀጣይነቱም ግንባር ቀደም ሚናዉን እንዲወጣ ማዕካላዊ ኮሚቴዉ አጽንዖት ሰጥቷል።

    የደኢህዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ላለፉት 10 ተከታታይ ቀናት ባካሄደዉ ስብሰባ ሀገራዊ የስላምና ፀጥታ ሁኔታን ከአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታ ጋር በማገናዘብ ገምግሟል።

    አሁን ሀገራችን ያለችበት ሁኔታም በዝርዝር አይቷል። ሁኔታዉን ለመቀየር ሁሉንም ሕዝቦች በማረባረብ ሠላማችንን ማስከበር ከቻልን ግን ብሩህ ተስፋ እንዳለን በአፅንዖት አይቷል።

    የሠላምና የፀጥታ ሁኔታዉ ከመቼዉም ጊዜ በላይ ለመንግስት ብቻ የሚተዉ ሳይሆን የነቃ የሕዝብ ተሳትፎ ጭምር የሚጠይቅ መሆኑን በመገንዘብ ድርጅቱ ሕዝብን በማስተባበር የክልሉን ብሎም የሀገሪቱን የሠላምና የፀጥታ ሁኔታ አስተማማኝ ለማድረግ ግንባር ቀደም ሆኖ እንደሚታገል አስምሮበታል።

    ዛሬም ዋነኛዉ ጠላት ድህነትና ኃላቀርነት መሆኑን የገመገመዉ ማዕከላዊ ኮሚቴዉ ይህንን ሁኔታ ለመቀየር የሚደረገዉን ትግል የሚፈታተኑ ሁኔታዎች መግጠማቸዉን አይቷል። የልማትና መልካም አስተዳደር ስራዎች ትኩረት ማነስ የስራ አጥነትና ድህነት የኑሮ ዉድነት የወጣቶችና የሴቶች ተሳትፎና ተጠቃሚነት ዛሬም ያልተሻሻለ መሆኑን፡ ዘላቂ ሠላም የማረጋገጥና የሕዝቦችን ደህንነት የማረጋገጥ ጉዳይ ትኩረት የሚሹ ተግባራት መሆናቸውን ገምግሟል።

    የክልላችን ሕዝቦች መንግስታዊ አገልግሎት የማግኘት ዕድሉን በሚመለከቱ የተለያዩ የአደረጃጀት ችግሮች በየደረጃው እየፈታ መምጣቱን ማዕከላዊ ኮሚቴው ገምግሟል። የክልል እንሁን ጥያቄዎችን ለመፍታት ሳይንሳዊ ጥናት በምሁራን ቡድን ያስደረገው ድርጅታችን በጥናቱ ግኝት ላይም ሰፊ ውይይት በማካሄድ መግባባት ፈጥሯል። ድርጅታችን የክልሉን ሕዝቦች ጥያቄ በበቂ መረጃና ዕውቀት ላይ ተመስርቶ እና ሕዝቡን ባሳተፈ መንገድ ለመመለስ ላለፉት ሰባት ወራት ባስጠናው ጥናት መሰረት ምላሽ ለመስጠት የተወያየ ሲሆን የሁሉንም ሕዝቦች ተጠቃሚነት ያረጋገጠ ውሳኔም አስተላልፏል።

    ጥናቱ ደረጃውን የጠበቀ አሳታፊ እና ትክክለኛ ውሳኔ ላይ ለመድረስ በሚያግዝ አግባብ መመራቱንም አረጋግጧል። በጥናቱ ደኢህዴን የክልሉን ሕዝብ መምራት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ የተገኙ ትሩፋቶች፣ ተግዳሮቶች፣ መንስዔዎችና የመፍትሄ አማራጮች የያዘ ስለመሆኑ በጥልቀት በመፈተሸ ለቀጣይ የድርጅት የመሪነት ሚና እና የሕዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ መሆኑን በጥንካሬ ወስዷል።

    በመሆኑም በወቅታዊ ሀገራዊ እና ክልላዊ የፖለቲካ እና የፀጥታ ሁኔታ እንዲሁም በክልሉ የሚነሱ ተጨማሪ ክልል ሆኖ የመደራጀት ጥያቄዎች ላይ ጊዜ ወስዶ በጥልቀት፤ ኃላፊነት በተሞላበትና በሰከነ ሁኔታ የመከረው የደኢህዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ የሚከተሉትን ባለ 6 ነጥብ የአቋም መግለጫ አውጥቷል።

    1. ወቅታዊ ሀገራዊ የፖለቲካና የፀጥታ ሁኔታን በተመለከተ በእስካሁኑ ሂደት የታዩ አዎንታዊ ውጤቶችን የሚፈታተኑ ጉዳዮች መኖራቸውን የገመገመው ማዕከላዊ ኮሚቴ በድርጅታችን ኢህአዴግ መሪነትና በሕዝቦች ተሳትፎ የተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴ እንዳይቀለበስ ሁሉም አካላት በጋራ የኃላፊነት መንፈስ እንደሚገባቸው አስምሮበታል። በሀገር ደረጃ የተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴ ተስፋ የፈነጠቁ ጅምር ውጤቶች የታዩበት ሲሆን በጥንቃቄ ካልተያዘ የሀገርን ህልውና የሚፈታተኑና ሕዝባችንን ስጋት ውስጥ ሊያስገቡ የሚችሉ ነባራዊና ህሊናዊ ሁኔታዎች እየተስተዋሉ መሆናቸውን ተገንዝቧል። በቅርቡ የአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች እና የሀገሪቱ የጦር መኮንኖች እስከ ህይወት ማጥፋት ድረስ የደረሰውን ጥቃት ድርጅታችን በፅኑ ያወግዛል፣ በፅኑም ይታገላል።
    2. በእህት ድርጅቶች መካከል ከድርጅታዊ ዲስፕሊን ውጪ የሚወጡ መግለጫዎች ይህንንም ተከትሎ እየተደረሱ ያሉ ድምዳሜዎች ከኢህአዴግ መርህ ውጪ መሆናቸውን በመገምገም የትኛውም ዓይነት የሃሳብ ልዩነቶችን እንደወትሮው ሁሉ በድርጅቱ ባህል መሠረት ማስተናገድ እንደሚገባ ታይቷል። በሌላ መልኩ ደኢህዴን በውስጡ ያሉ ችግሮችን ታግሎ የሚያርምና የሚያጋጥሙ ችግሮችና ፈተናዎችን ከሕዝቡ ጋር በመሆን የመፍታት ባህልና ልምድ ያለው ድርጅት ነው። ከዚህ ውጪ እኔ አውቅልሃለሁ በሚመስል መንገድ ከሩቅ የሚሰነዘሩ ሂደቱን ያልተከተለ አመራር የማይቀበል መሆኑን ማዕከላዊ ኮሚቴው ያስገነዝባል።
    3. ክልላዊ ወቅታዊ ፖለቲካና ፀጥታ ሁኔታ ልዩ ትኩረት የሚሻ መሆኑን ማዕከላዊ ኮሚቴው በዝርዝር ገምግሟል። ሀገራዊ ፖለቲካ እና ፀጥታ ድባብ ተከትሎ በክልሉ ውስጥ የሚታዩ አዝማማያዎች የህግ የበላይነት አደጋ ውስጥ የመግባት የኢ-መደበኛ አደረጃጀቶች እንቅስቃሴዎች ስርአት መያዝ ያለባቸው መሆኑን ተሰምሮበታል። በዚህ ሂደት ለታዩ ጉድለቶች ሀገራዊ ሁኔታ የራሱ አሉታዊ አስተዋዕፆ ያለው ቢሆንም ዋናው ችግር የድርጅታችን ውስጣዊ ሁኔታ መሆኑን ማዕከላዊ ኮሚቴው በጥልቀት ተወያይቷል። ከድርጅቱ ከፍተኛ አመራሮች ጀምሮ በየደረጃው ያለው አመራር ድርሻ ሰፊ መሆኑም ታይቷል። ስለሆነም እንደ ሀገር እና እንደ ክልል ከገባንበት ያለመረጋጋት ለመውጣት የድርጅቱ ውስጣዊ ጥንካሬ ወሳኝ መሆኑን የድርጅቱ አመራሮች በከፍተኛ የሃላፊነት መንፈስ እና ሕዝባዊ ውግንና መንቀሳቀስ የሚጠይቀን ወቅት ላይ መሆናችንን መተማመን ላይ ተደርሷል። በመብት ጥያቄ ሽፋን የሚደረጉ የትኛውንም ኢ-መደበኛ እንቅስቃሴዎችን ስርዓት ለማስያዝ እንዲሁም የሕዝቦችን ሰላምና ፀጥታ ማረጋገጥ እና የህግ የበላይነትን ማስከበር ለድርድር የማይቀርብ መሆኑን ማዕከላዊ ኮሚቴው ድምዳሜ ላይ ደርሷል።
    4. በክልል የመደራጀት ጥያቄን በተመለከተ የሕዝቦች ህገ-መንግስታዊ መብት መሆኑን ድርጅታችን ይገነዘባል። በክልል የመደራጀት ጥያቄ ሲነሳ የነበረው ከአንድ አካባቢ ብቻ ባይሆንም ጥያቄውን በጥናት ላይ ተመስርቶ ምላሽ ማግኘት እንዳለበት ድርጅቱ በአስረኛ ድርጅታዊ ጉባኤ በወሰደው አቋም መሰረት በዝርዝር ሕዝቡን ያሳተፈ ጥናት ሲያደርግ ቆይቷል። በጥናቱ የቀረቡ አማራጮችን በጥልቀት በመመርመር፣ የሕዝቡን የጋራ ዘላቂ ጥቅም የሚያረጋግጠውን አማራጭ በመውሰድ የክልል አደረጃጀት ጥያቄዎች በሚመለሱበት አግባብ ላይ አቋም ተወስዷል። በክልላችን መላው ሕዝብ ምክክርና ውይይት የሚያደርግበት ሆኖ በአንድ በኩል በጥናቱም የተገኘውን የክልሉ ሕዝቦች አብሮ የመቀጠል ፍላጎትን ባከበረ በሌላ ጎኑ ደግሞ ጉባኤውን ውሳኔ ተግባራዊ ባደረገ መንገድ እና ኃላፊነት በተሞላበት ሁኔታ የመምራት ኃላፊነት ለመወጣት ማዕከላዊ ኮሚቴው ተስማምቷል።
    5. የደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በህብረ-ብሔራዊነት ላይ እየተገነባ ያለው የፌዴራል ሥርዓት ትሩፋቶችን ያስመዘገበ ሲሆን በሂደቱ የታዩ ተግዳሮቶች በማረም ሀገራችን በደረሰችበት የዕድገት ደረጃ በማሻሻል ለፌዴራል ሥርዓቱ ይበልጥ መጎልበትና ቀጣይነት የምንታገል መሆኑን አቋም ተወስዷል። ከሁሉ በላይ ህበረ-ብሔራዊ ኢትዮጵያዊ አንድነታችንን ለማጎልበት ማዕከላዊ ኮሚቴው አጽንኦት ሰጥቷል።
    6. በእያንዳንዱ አከባቢ ያለውን የልማት ሁኔታ በተመለከተ በድርጅታችን መሪነት በክልላችን የተመዘገቡ የልማት ውጤቶች እንደተጠበቁ ሆነው በተለያየ መልኩ የሚገለጽ ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የመልካም አስተዳደር እና የአመራር ሥርዓታችን ላይ የሚታዩ ችግሮች መፈታት እንዳለባቸው ተወስዷል። ከዚህም በመነሳት በክልሉ ሁሉም አከባቢዎች የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችሉ አዳዲስ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ በክልሉ ያሉ ሕዝቦች በጋራ መልማት እንዳለብን በመግባባት ሕዝቡን ባሳተፈ ሁኔታ የክልሉን ህገ-መንግስት ከማሻሻል ጀምሮ ሌሎች ዝርዝር የህግ ማዕቀፎች እንዲዘጋጁ አቋም ተወስዷል።

    ውድ የድርጅታችን አመራሮች፥ አባላትና ደጋፊዎች፣ ድርጅታችን ደኢህዴን ዛሬ ለደረሰበት ደረጃ ያበረከታችሁት ድርጅታዊ አስተዋጽኦ ከገባንበት ፈተና ለመውጣት ያስቻለ ሆኗል። የድርጅት ቀጣይነት ለማረጋገጥ ከመቼውም ጊዜ በላይ ቁርጠኛ አቋም የተወሰደበት ወቅት ላይ ደርሰናል። ስለሆነም የተጀመረው ድርጅታዊ ሪፎርም በማጠናከር እንደወትሮ ሁሉ ግንባር ቀደምትነት ሚናችሁን አጠናክራችሁ እንድትቀጥሉ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ የክልላችን ሕዝቦች፥ በተለያዬ መልኩ የሚገለጽ የልማት፣ የመልካም አስተዳደር እና የአደረጃጀት ጥያቄዎች ውስጥም ሆናችሁ ምላሽ እንዲሰጣችሁ ላሳያችሁት ትዕግስት ድርጅቱ ምስጋና ያቀርባል። ይህ ትዕግስታችሁ በመሪ ድርጅቱ እና በመንግስት ላይ እምነት በመጣል የሚታዩ ችግሮች በጋራ ቆመን እንድንፈታ የበኩላችሁን አስተዋጽኦ እንዳበረከታችሁ ያሳየን ነው። ችግሮችን በውይይትና በምክክር የመፍታት አማራጭ ብቻ በመከተል ዛሬ ለደረስንበት ደረጃ ያበረከታችሁት አስተዋጽኦ ታሪክ የሚረሳው አይደለም። ዛሬም ድርጅታችን በጽኑ መስመር ላይ በጽናት በመቆም የሚያጋጥሙትን ፈተናዎች በድል ለመወጣት ያለውን ዝግጁነት ያረጋግጣል። ስለሆነም በድርጅቱ ላይ ያላችሁን እምነት በማጎልበት ለውጡን ከዳር ለማድረስ የሚጠበቅባችሁን ሕዝባዊ አስተዋጽኦ እንድታበረክቱ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ የክልላችን አርሶ እና አርብቶ አደሮች፥ የክልላችን ሕዝብ አብዘኛውን ቁጥር በመያዛችሁ ብቻ ሳይሆን ባለፉት ዓመታት ለተመዘገበው የኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለሕዝቦች ፍትሃዊ ተጠቃሚነት እና ለድርጅታችን ቀጣይነት ዋልታና ማገር መሆናችሁን ነጋሪ አያሻውም። ያገኛችሁትን ትሩፋቶች ጠብቃችሁ በቀጣይ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር መዋቅራዊ ችግሮች እንዳሉ ተገንዝበናል። በመሆኑም ከድህነት ለመላቀቅና ለተሻለ ህይወት የምታደርጉትን ጥረት ከጎናችሁ በመቆም አለኝታነታችንን ለማረጋገጥ ዛሬም የፀና እምነት እንዳለን እናረጋግጣለን።

    የተከበራችሁ የክልላችን ወጣቶች፥ በክልሉ በሁሉም አከባቢዎች የወጣቶች የተሳትፎና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ጥያቄ አንገብጋቢና የተለየ ምላሽ መስጠት የሚጠይቅ መሆኑን በጥልቀት ያየው ማዕከላዊ ኮሚቴው በቀጣይ የክልሉ የልማት ኮሪደሮችን ለይቶ የጋራ ሀብቶችን በማልማት፣ ወጣቱን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚሰራ መሆኑን አቅጣጫ አስቀምጧል። በመሆኑም በክልላችን ያለውን የጋራ ፀጋ መሰረት ያደረጉ አዳዲስ የልማት ቀጠናዎችን በመፍጠር የወጣቱን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ቆርጠን መነሳታችንን እንገልጻለን። ስለሆነም የክልላችን ወጣቶች ከድርጅታችን ጎን በመሰለፍ የማይተካ አዎንታዊ ሚናችሁን እንድትወጡ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ የክልላችን ሴቶች፥ እስካሁን ለተገኙ ትሩፋቶች ሚናችሁ የላቀ ሲሆን ባጋጠመን ተግዳሮቶች ቀዳሚ ተጎጂ መሆናችሁ ግልጽ ነው። በመሆኑም የሴቶችን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማስፋት በእስካሁኑ ጉዟችን የነበሩ ጉድለቶችንም ለማረም ከምንም ጊዜ በላይ ዝግጁነታችንን እናረጋግጣለን። የክልላችን ሴቶች ከህብረተሰቡ ውስጥ ከቤተሰብ ጀምሮ ያላችሁን ግዙፍ ሚናችሁን ይዛችሁ ከድርጅታችን ጎን ሆናችሁ ትግላችሁን እንድታጠናክሩ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ የክልላችን ምሁራን፥ ድርጅታችን ባስመዘገበው ስኬቶች ለነበራችሁ አዎንታዊ አስተዋፅኦ ክብር አለን። አሁንም ከሰፊው የዕውቀት ማዕድ ካገኛችሁት ልምድና የህብረተሰብ ችግሮች ላይ መፍትሄ ለመስጠት ያላችሁ የመተንተን አቅማችሁን ሳትነፍጉ ለሀገራችሁና ለሕዝባችሁ ለወገናችሁ ለማበርከት ከጎናችን እንድትሰለፉ ጥሪ ያቀርባል።

    ውድ የሀገራችን ባለሀብቶችና የንግዱ ማኅበረሰብ፥ በክልላችን ብሎም በሀገራችን ለተመዘገበው ልማት የጀርባ አጥንት በመሆን ለምታበረክቱት ሁለንተናዊ አስተዋጽኦ ምስጋናችንን እናቀርባለን። በክልላችን ያለውን የመልማት ጸጋ በጋራ ለማልማትና ሕዝባችን ተጠቃሚ ለማድረግ ከምንግዜውም በላይ ተዘጋጅተናል። ስለሆነም በግልና በጋራ ሆናችሁ አብረን ለመስራት ጥሪ ያቀርባል።

    ውድ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፥ የክልላችን ሕዝቦች መለያና መታወቂያ የሆነውና እየተገነባ የመጣውን ደቡባዊ ስነ ልቦና ለክልላችን ሕዝቦችም ሆነ ለሀገር ግንባታ ያለው ፋዳ ትርጉም ያለው ነው። ይሁንን እምቅ አቅም ይበልጥ በማውጣት ረገድ ኪነ ጥበብ ያለው ሃይል ላቅ ያለ በመሆኑ የሕዝቦችን ትስስርና አንድነት በቀጣይነት ለመገንባት እንድታውሉ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ እሀት ደርጅቶችና አጋሮች፥ ደኢህዴን/ኢህአዴግ የክልሉን ሕዝቦች ሰላም ልማት ዴሞክራሲ ብሎም ለሀገራዊ አንድነትና ክብር የበኩሉን አዎንታዊ ሚና ሲጫወት የቆየ ድርጅት ነው። በሀገር ግንባታ ሂደት የበኩሉን ሚና እየተወጣ እንደመጣ ሁሉ ዛሬም ለሀገራችንና ለሕዝቦቿ እንዲሁም ለዜጎቿ ክብር መብት ነፃነት ብልጽግና ዴሞክራሲያዊ አንድነት ተግቶ ይታገላል።በዚህ ሂደት ከጎናችን እንደቆማችሁ ሁሉ ዛሬም የተለመደው አዎንታዊ ሚናችሁ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ ተፎካካሪ ፓርቲዎች፥ በተለያየ ሙያ ውስጥ ያላችሁ በሙሉ ደኢህዴን የስካሁን ስኬቶቹን ጠብቆ ማቆየት ሳይሆን ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች በመወጣት ለሀገራችን መፃኢ ተስፋ አዎንታዊ ሚና ለመጫወት ቆርጦ ተነስቷል። ይህ ሂደት የሁላችሁም አዎንታዊ ድጋፍና እይታ ይፈልጋል። ስለሆነም በድርጅታችን የሚቀመጡ አቅጣጫዎችና ውሳኔዎች መመዘን ያለባቸው ከሕዝቡ ሰላምና የህግ የበላይነት ዘላቂ ጥቅም አንጻር መሆናቸው ይታወቃል። ስለሆነም ገንቢ ሚናችሁ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ ያቀርባል።

    የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን)

    የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ - ደኢህዴን


    Semonegna
    Keymaster

    የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) ማዕከላዊ ኮሚቴ በቀጣይ የሕግ የበላይነትን የማስከበር ጉዳይ ሕዝብን ማዕከል ባደረገ እና ባሳተፈ መንገድ አጠናክሮ ለመቀጠል በቁርጠኝነት መወሰኑንም አቶ አብርሀም አለኸኝ ተናግረዋል።

    ባህር ዳር (አዴፓ) – የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) ለአማራ ሕዝብ ህልውና እና ለሀገር እንድነት አስፈላጊውን መስዋትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆኑን ገለፀ።

    ፓርቲው ሲያካሂድ የቆየውን የማዕከላዊ ኮሚቴ ውይይት ማጠናቀቁን አስመልክቶ የማዕከላዊ ኮሚቴ ጽሕፈት ቤቱ የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ አብርሀም አለኸኝ ለሚዲያ አካላት ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጠዋል።

    አቶ አብርሀም በመግለጫቸው፥ ማዕከላዊ ኮሚቴው የለውጥ ሂደቱ ከተጀመረ እስከ አሁን ምን ጥንካሬዎች ምን ጉድለቶች ነበሩ? የሚለውን በዝርዝር መገምገሙን ገልፀው፤ የለውጥ ሂደቱ ጥንካሬዎችም ፈተናዎችን አንድ በአንድ ለመለየት ጥረት ማድረጉን ገልፀዋል።

    እንደ አቶ አብርሀም ገለፃ በተለይም የዲሞክራሲ ምህዳሩን ለማስፋት በተመለከተ ከሞላ ጎደል በተሻለ ሁኔታ መመራቱን የማዕከላዊ ኮሚቴው በግምገማው ማረጋገጡን ገልፀዋል።

    በለውጥ ሂደቱ ውስጥ ደግሞ ትልቁ ፈተና እና መሰረታዊ ችግር ሁኖ የተነሳው የሰላም እጦትና የሕግ የበላይነት መከበር ላይ የነበሩ ጉድለቶች እንደነበሩ ማዕከላዊ ኮሚቴው በስፋት መገምገሙን ገልፀዋል::

    አቶ አብርሀም አክለውም የሕግ የበላይነት እየተንገራገጨ ሔዶ ሔዶ በመጨረሻም መሪዎቻችንን መብላቱ በታሪክ የማይረሳ ጠባሳ ሁኖ አልፏል ብለዋል።

    ኢትዮጵያ ሀገራችንን ከእልቂት ለማዳን ቆም ብለን በሰከነ ሁኔታ ማሰብና መራመድ እጅግ አስፈላጊና ወሳኝ ጊዜ ላይ እንገኛለን

    በክልሉ ባጋጠመው የሰላም እጦት ምክንያትም ክልሉን ለማልማት በተሟላ መነሳሳት ወደ ሥራ የገቡ ባለሀብቶችንም ለስጋት መዳረጉን ጨምረው ገልፀዋል።

    ከዚህ አኳያ የአዴፓ ማዕከላዊ ኮሚቴ በቀጣይ የሕግ የበላይነትን የማስከበር ጉዳይ ሕዝብን ማዕከል ባደረገ እና ባሳተፈ መንገድ አጠናክሮ ለመቀጠል በቁርጠኝነት መወሰኑንም አቶ አብርሀም አውስተዋል።

    ሰኔ 15 በአመራሮች ላይ የተፈፀመው አሰቃቂ እና በጭካኔ የተሞላ ግድያ ለአማራ ሕዝብ ታሪክ የማይመጥን ነው ያሉት አቶ አብርሀም የተፈጠረውን ችግር ለመቀልበስ የፀጥታ ኣካላት መስዋትነትና የህዝባችን ድጋፍ ወሳኝ እንደነበር በመግለፅ ፓርቲው ለፀጥታ አካላት እና ለህዝቡ ያለውን እድናቆትና አክብሮትም ገልፃል ብለዋል።

    በዚህ ሳቢያም የተፈጠረውን የአመራር ክፍተት ለመሙላት ማዕከላዊ ኮሚቴው በአጀንዳነት ይዞ አመራሩን መምረጡንም አብራርተዋል።

    በቀጣይም ፓርቲው የአማራ ሕዝብ መሰረታዊ ጥያቄዎች ለመፍታት ከፍተኛ ርብርብ እንደሚያደርግ የገለፁት አቶ አብርሀም ፓርቲው ለአማራ ሕዝብ ህልውና እና ለሀገር አንድነት ሲል መስዋትነት ለመክፈል መዘጋጀቱንም ገልፀዋል።

    በተለይም የክልላችን ልማት ለማፋጠን የሥራ እድል ፈጠራ እና ወቅታዊውን የገበያ ንረት ለማረጋጋት ሰፊ ርብርብ እንደሚያደርግ አቅጣጫ ማስቀመጡንም ጨምረው ገልፀዋል።

    ምንጭ፦ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ


Viewing 15 results - 406 through 420 (of 730 total)