Search Results for 'የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን'

Home Forums Search Search Results for 'የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን'

Viewing 12 results - 1 through 12 (of 12 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ለብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የክብር ዶክትሬት ሽልማታቸውን አስረከበ

    ባሕር ዳር – የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ባሳለፍነው ነሐሴ 21 ቀን፥ 2014 ዓ.ም የተማሪዎችን ምርቃ ሥነ-ሥርዓት ላይ ለሀገራችን ኢትዮጵያ በማኅበረሰብ አገልግሎት ጉልህ አስተዋፅዖ ላበረከቱት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን (የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ) የሰሜን ወሎ እና በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የኦሮሚያ ልዩ ዞን ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ለሆኑት ለብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የክብር ዶክትሬት ሽልማት ለተወካያቸው መስጠቱ ይታወሳል። ሆኖም ግን ብፁዕ አባታችን በአሁኑ ሰዓት የሐዋርያዊ ተልዕኮአቸውን ጨርሰው በመመለሳቸው መስከረም14 ቀን፥ 2015 ዓ.ም በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጥበብ ሕንፃ ተገኝተው የክብር ዶክትሬት ሽልማታቸውን ተቀብለዋል።

    የሽልማት አሰጣጥ ሥነ-ሥርዓቱ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ፣ የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል እና የዕለቱ የክብር እንግዳ በሆኑት በብፁዕ አቡነ አብርሃም ፀሎትና ቡራኬ ተጀምሯል።

    የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት ዶክተር ፍሬው ተገኘ በሽልማት አሰጣጥ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንዳሉት በጭንቅ እና በመከራ ወቅት ሀይማኖትና ዘር ሳይለዩ የከበረ ሥራን ሠርተው የከበሩትን ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ በማክበራችን እኛም ብዙ አትርፈናል ሲሉ ተናግረዋል። በወቅቱ አቅም ያላቸው በርካታ ነዋሪዎች ከአካባቢያቸው በሚሸሹበት ወቅት በጦርነት፣ በችግር እና መከራ ውስጥ ወደ ሚገኘው ሕዝባቸው ጋር በመሄድ የመከራው ቀንበር እንዳይሰማቸው ከሕዝቡ ጋር በመሆን የመጣውን ክፉ ቀን እንዲያልፍ በማድረጋቸው ታሪክ የማይረሳው ሥራን ሠርተዋል ሲሉ ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል።

    የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፥ እንዲሁም ዕለቱ የክብር እንግዳ የሆኑት ብፁዕ አቡነ አብርሃም በበኩላቸው የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሀይማኖት፣ ዘር እና ቀለም ሳይለይ በሥራቸው ብቻ መዝኖ ለብፁዕ አቡነ ኤርሚያስ የክብር ዶክትሬት በመስጠቱ በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ስም ምስጋና አቅርበዋል። ብፁዕ አቡነ ኤርሚያስ በዚያ ሽብር እና ጭንቅ በነገሰበት ወቅት ክርስቲያን፣ ሙስሊም፣ አማኝ እና ኢ-አማኝ ሳይሉ ሁሉንም የሰው ዘር በእኩል ዓይን በማየት የመከራውን ቀን ከሕዝባቸው ጋር ያሳለፉትን ድንቅ አባት የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዕውቅና ሽልማት በመስጠቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መደሰቷን ተናግረዋል።

    አቡነ ኤርምያስ በበኩላቸው የተሰጠኝ የክብር ዶክትሬት ለእኔ ሳይሆን በሁለቱም ወገን በጦርነቱ ወቅት ቆስለው በየጫካው የወደቁ ወገኖችን ቁስል በማጠብ እና ከልጆቻቸው ጉሮሮ ቀንሰው ለቁስለኞች በማብላት ትልቅ ፍቅር ላሳዩን እናቶች እና በጸሎት ሲጠብቁኝ ለነበሩት ለብጹዕ አቡነ ቄርሎስ፣ ከጎኔ ሆነው በምክር ለረዱኝ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ለሀዋርያዊ ተልዕኮ ዘወትር ለሚፋጠኑት ካህናት፣ ዲያቆናት፣ ከሙስሊሙ ማኅበረሰብ ጋር ድልድይ ሆነው ላገናኙኝ የመስጊድ ኮሚቴ አባላት፣ ሰብዓዊ ግዴታቸውን ለተወጡ አባቶቻችን እና እናቶቻችን ነው ሲሉ ተናግረዋል።

    በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የሰሜን ወሎ የባህር ዳር ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፣ የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት የአድባራት እና ገዳማት አስተዳዳሪዎች እንዲሁም የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ም/ፕሬዚዳንቶች መምህራን እና ሠራተኞች በተገኙበት በደማቅ ሁኔታ ተካሂዷል።

    ምንጭ፦ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ

    አቡነ ኤርምያስ

    Anonymous
    Inactive

    በብሔራዊ መግባባት ዙሪያ ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ) ጥናታዊ ጽሁፍ አቀረበ

    አዲስ አበባ (ነእፓ) – በኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አስተባባሪነት በሀገራችን ብሔራዊ መግባባት በመፍጠር ሰላምና መረጋጋት እንዲሁም ዴሞክራሲያዊ ሽግግር እውን ለማድረግ በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል የመጀመሪያ ዙር ውይይት ነሐሴ 16 ቀን 2012 ዓ.ም መካሄዱ ይታወሳል። የዚሁ መድረክ ሁለተኛ ዙር ውይይት ነሐሴ 30 2012 ዓ.ም በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ECA) ተካሂዷል።

    በውይይቱ ላይ በከፍተኛ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች አራት የተለያዩ ጽሁፎች የቀረቡ ሲሆን፥ የነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ) ሊቀመንበር ዶ/ር አብዱልቃድ አደም “ብሔራዊ መግባባት በኢትዮጵያ፡ ዘላቂ ሰላም፣ ሀገራዊ አንድነት እና ዴሞክራሲያዊ ሽግግር” በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሁፍ አቅርበዋል።

    ዶ/ር አብዱልቃድር የብሔራዊ መግባባት ምንነት፣ አጠቃላይ ማዕቀፍ፣ አደረጃጀት፣ ዓለም አቀፍ ተሞክሮ እና ሌሎች ከብሔራዊ መግባባት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን ብሔራዊ መግባባትን አስመልክቶ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ግልጽ እና ተቀራራቢ አቋም እንዲኖራቸው ለማድረግ እንዲሁም ብሔራዊ መግባባትን አስመልክቱ የተሳሳቱ ግንዛቤዎችን ለማስተካካል ጥናታዊ ጽሁፉ ከፍተኛ ፋይዳ እንደነበረው በውይይቱ የተሳተፉ የፖለተካ ፓርቲዎች ገልጸዋል።

    የቀረበው ወረቀት (ጥናታዊ ጽሑፍ) በሀገራችን በቅርቡ ይጀመራል ተብሎ በሚጠበቀው ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ሂደት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንደሚኖረው ይታመናል።

    ነእፓ ቀደም ሲል በሀገራችን በብሔራዊ መግባባት ዙሪያ የመነሻ ጽሁፍ  በማዘጋጀት ሀሳቡን ለመንግስት፣ ለፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ለሲቪክ ማኅበራትና በኢትዮጵያ ለሚገኙ የውጪ ሀገር የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ ማሰራጨቱ ይታወሳል።

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ በሀገራችን ሰላም፣ መረጋጋትና አንድነት እንዲሰፍን፣ ቀጣዩ ምርጫ ነጻ ፍትሀዊ እና ቅቡል እንዲሆን ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ሂደት በአፋጣኝ መካሄድ እንዳለበት በጽኑ ያምናል። ይህንኑ እውን ለማድረግ ፓርቲው የጀመረውን ጥረት ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን አጠናክሮ ይቀጥላል።

    በመድረኩ የቀረበውን ጽሁፍ እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን ማግኘት ይቻላል።

    ምንጭ፦ ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ)

    ተመሳሳይ ዜናዎች

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ

    Anonymous
    Inactive

    በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ አሜን።
    የሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ እና ግድያውን ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል በአንዳንድ ዞኖች
    ተቀነባብረው በተፈጸሙ ጥቃቶች የተጎዱ ኦርቶዶክሳውያንን መርዳትንና መልሶ ማቋቋምን አስመልክቶ
    ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ መግለጫ

    አማን አማን እብለክሙ ከመ ትበክዩ ወትላህዉ አንትሙ፤ ወዓለምሰ ይትፌሣሕ፤ ወአንትሙሰ ተኃዝኑ፤ ወኃዘንክሙ ፍሥሐ ይከውነክሙ = እውነት እውነት እላችኋለኹ፤ እናንተ ታለቅሳላችኹ፤ ሙሾም ታወጣላችኹ፤ ዓለም ግን ደስ ይለዋል፤ እናንተም ታዝናላችኹ፤ ነገር ግን ኃዘናችኹ ወደ ደስታ ይለወጣል።” (ዮሐ.16፥20) ሃጫሉ ሁንዴሳ ስመ ጥምቀቱ ኃይለ ገብርኤል፣ ሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. ምሽት በአዲስ አበባ መገደሉ ይታወሳል። ቤተ ክርስቲያን፥ በዚያ ድንገተኛ የልጇ ግድያ ከባድ ኃዘን ተሰምቷታል። ኾኖም፣ በግድያው የተሰማትን ኃዘን ለመወጣት ጊዜ ሳይሰጣት፣ ኃዘንተኛነቷ ተረስቶ እና እንደ ጠላት ተቆጥራ፣ በኦሮሚያ ክልል በአንዳንድ አካባቢዎች በክርስቲያን ልጆቿ ላይ ዘግናኝ ፍጅት እና መከራ ተፈጸመባቸው።

    በኦርቶዶክሳዊነታቸው ብቻ በአሠቃቂ መልኩ በገጀራ ተቀሉ፤ በቆንጨራ ተቆራረጡ፤ በጦር ተወግተው በጩቤ ተዘከዘኩ፤ በሜንጫ ተተለተሉ፤ በዱላ ተቀጥቅጠው እና በደንጊያ ተወግረው ተገደሉ፤ አስከሬናቸው በጎዳና እየተጎተተ ሲንገላታ ዋለ፤ ለቀናት በየቦታው ወድቆ የቆየው የሰውነት ክፍላቸው ለከርሠ አራዊት ሲሳይ ኾነ፤ ሴቶች፥ በልጆቻቸው፣ በአባቶቻቸው እና በባሎቻቸው ፊት ተደፈሩ፤ ለዘመናት የደከሙበት ቤት ንብረታቸው፣ በጥናት እና በጥቆማ እየተለየ ከተዘረፈ በኋላ ቀሪው ጋዝ እየተርከፈከፈበት በእሳት እየጋየ ወደመ፤ ብዙዎች ከሞቀ ቀዬአቸው ተፈናቅለው የክረምቱን ጨለማ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን በሚገኙ መቃብር ቤቶች እና አዳራሾች፣ በልዩ ልዩ መንግሥታዊ ተቋማት እንዲሁም፣ በግሰለቦች ቤቶች ተጠልለው ለማሳለፍ ተገደዱ፤ ለአስከፊ ማኅበራዊ እና ሥነ ልቡናዊ ቀውሶች ተዳረጉ።

    ቤተ ክርስቲያናችን፣ ይህንኑ የተቀነባበረ ጥቃት እንደሰማች፣ ሰኔ 24 ቀን 2012 ዓ.ም. በቋሚ ሲኖዶስ የሐዘን መግለጫ አውጥታለች፤ በአገር ውስጥ እና በውጭ በሐዘንና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ስታመለክት ከርማለች፤ የሚመለከታቸው የመንግሥት አካላትም፥ “አጥፊዎችን አንታገሥም፤ ተገቢውን ፍትሕ እንሰጣለን፤ የተጎዱትን እንክሳለን፤” ብለው ቃል የገቡትን ይፈጽሙ እንደ ኾነ በማለት በትዕግሥት ጠብቃ ነበር። ኾኖም፣ ዜጎችን ከጥቃት አስቀድሞ የመከላከል እና የመጠበቅ፣ ፍትሕን የማስፈንና ተጎጂዎችን በአግባቡ የመካስ ሓላፊነታቸውን በወቅቱ እና በብቃት ሲወጡ አላየችም።

    በጉዳዩ ላይ የተወያየው ቋሚ ሲኖዶስም፣ በየሥፍራው በአካል ተገኝቶ የደረሰውን ጉዳት የሚያጠና ዐቢይ ኮሚቴ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት እንዲቋቋም መመሪያ ሰጥቷል። በዚኽም መሠረት ዐቢይ ኮሚቴው፣ ተጎጂዎችን፥ በጊዜያዊነት ለመርዳት እና በዘላቂነት ለማቋቋም የሚያስችሉ ልዩ ልዩ ንኡሳን ኮሚቴዎችን አደራጅቶ ወደ ሥራ ገብቷል።

    ዐቢይ ኮሚቴው ባወጣው መርሐ ግብር፣ የሥራው መጀመሪያ ያደረገው፣ ጥቃቱ የተፈጸመባቸውን አካባቢዎች በዝርዝር በመለየት፣ ተጎጅዎችን የማጽናናት እና መረጃ የማሰባሰብ ጉዞ ማካሔድ ነበር። ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን፣ የአገር ሽማግሌዎችን፣ መንፈሳውያን ማኅበራትንና በርካታ የብዙኃን መገናኛዎችን ጨምሮ 260 ያኽል ልኡካን የተሳተፉበት ይኸው ጉዞ፣ ከፍተኛ ጉዳት ከደረሰባቸው አካባቢዎች ውስጥ በስድስት አህጉረ ስብከት የሚገኙ 25 ወረዳዎችን የሸፈነ ነበር።

    የዐቢይ ኮሚቴው ልኡካን፣ ተጎጂዎችንና በማነጋገር እና ጉዳት የደረሰባቸውን አካባቢዎች በመጎብኘት ባቀረቡት ሪፖርት መሠረት፣ የልጃችን የኃይለ ገብርኤልን ግድያ ተከትሎ፣ በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች፣ የመንግሥትን መዋቅር ተገን ያደረጉ የእምነት እና የብሔር ጽንፈኞች አስቀድመው ከተደራጁ ኀይሎች ጋራ በመቀናጀት የፈጸሙት ስልታዊ እና አረመኔያዊ ጥቃት ዋና ዒላማ፣ ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን እንደነበሩ ተረጋግጧል።

    ከሰኔ 22 ቀን ምሽት ጀምሮ እስከ ሰኔ 24 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ ባሉት ሦስት ተከታታይ ቀናት በተፈጸመው በዚያ ጥቃት፥ ከ67 በላይ ምእመናን በግፍ እና በአሠቃቂ ኹኔታ ተገድለዋል፤ 38 ምእመናን ቋሚ(ከባድ)፣ 29 ምእመናን ደግሞ ቀላል የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፤ ከሰባት ሺሕ በላይ ምእመናን ከመኖሪያቸው ከመፈናቀላቸው ባሻገር፣ በተለያየ ደረጃ ለሚገለጽ ሥነ ልቡናዊ እና ሥነ አእምሯዊ ቀውስ ተዳርገዋል፤ ከአምስት ቢልዮን ብር በላይ የሚገመት ንብረታቸውንም በዘረፋ እና በቃጠሎ ማጣታቸውን፣ ከዐቢይ ኮሚቴው የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርት ለመረዳት ተችሏል።

    የጥቃቱን አስከፊነት በዚኽ መልኩ የተረዳው ዐቢይ ኮሚቴው፣ ተጎጅዎችን በአፋጣኝ ባሉበት ለመርዳት እና በዘላቂነት ለማቋቋም ይቻል ዘንድ፣ አደረጃጀቱን በዐዲስ መልክ በማጠናከር ተልእኮውን በአጭር ጊዜ ለማከናወን የሚያስችለውን ስልት ቀይሶ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። የጉዳቱን መጠን በነፍስ ወከፍ ደረጃ የመለየት ሥራ እየሠራ ሲኾን፣ በዚኽም መነሻነት፣ ርዳታው በቀጥታ ለተጎጂዎች እና ቤተሰቦቻቸው እንዲደርስ ይደረጋል፤ በዘላቂነት ለማቋቋምም ኹኔታዎችን ያመቻቻል።

    ዐቢይ ኮሚቴው፣ በጉዳት ጥናት መረጃው መሠረት፣ ጊዜያዊ ርዳታን ከማድረስ እና ከመልሶ ማቋቋም ባሻገር፣ መንግሥት በአስቸኳይ ሊፈጽማቸው የሚገቡ ተግባራት አሉ ብሎ ያምናል፤ እነዚኽም፤

    1. ተጎጅዎች በሃይማኖታቸው በደረሰባቸው ስልታዊ እና ዘግናኝ ጥቃት የተነሣ፣ በከፍተኛ የደኅንነት ስጋት ላይ እንደሚገኙ በቀረበው ሪፖርት እና ማስረጃ አረጋግጠናል። በወቅቱ ያሉበት ኹኔታ፣ ለኮሮና ቫይረስ እና ለሌሎችም ተላላፊ በሽታዎች የሚያጋልጣቸው እንደኾነ ለመታዘብ ተችሏል። በመኾኑም፣ የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት እና የፌዴራል መንግሥት፣ የኦርቶዶክሳውያን ኢትዮጵያውያንን በሕይወት የመኖር እና ሀብት የማፍራት ሰብዓዊ እና ዜግነታዊ መብቶችን በማስከበር፣ የደኅንነት እና የኑሮ ዋስትና በአፋጣኝ እንዲያረጋግጥላቸው ቤተ ክርስቲያናችን አጥብቃ ታሳስባለች።
    2. መንግሥት፥ ጥቃቱን ያቀዱትን፣ የፈጸሙትንና ያስተባበሩትን ኀይሎች እንዲሁም፣ የተጣለባቸውን ሓላፊነት ወደ ጎን በማለት ጥቃቱን በዝምታ የተመለከቱትን በመዋቅሩ ውስጥ ያሉትን ሹማምንት እና የጸጥታ አካላት የኾኑ አጥፊዎችን፣ በቁጥጥር ሥር በማዋል እና በሕግ ተጠያቂ በማድረግ ፍትሕ ርትዕ እስከ መጨረሻው እንዲያሰፍን ታሳስባለች። በዚኽ ረገድ፣ መንግሥት፣ ከጥቃቱም በኋላ ቢኾን፣ ሕግን ለማስከበር እያደረገ ያለውን ጥረት፣ ቤተ ክርስቲያን በቅርበት የምትከታተለውና የምታደንቀውም ነው፤ ለውጤታማነቱም፣ ማናቸውንም የበኩሏን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መኾኗን ትገልጻለች።
    3. በአሳዛኝ ኹኔታ በደል እና ግፍ የተፈጸመባቸው ኾነው እያለ፣ በጥቃቱ ምንም ሱታፌ የሌላቸው ንጹሐን ዜጎች፣ በኦርቶዶክሳዊነታቸው ብቻ ታስረው እየተንገላቱ በመኾኑ፣ ጉዳያቸው በጥንቃቄ ታይቶ ከእስር እንዲፈቱ ታሳስባለች።
    4. አንዳንድ የመንግሥት ባለሥልጣናት እና የፖሊቲካ ፓርቲዎች፥ የግፉዓን ሰማዕታቱን መጠቃት፣ አላግባብ ለቡድናዊ እና ፖሊቲካዊ ትርፍ በመጠቀም በሐዘናችን ከመሣለቅ እንዲቆጠቡ፤ መንግሥትም፣ ተገቢውን ክትትል በማድረግ እንዲያስታግሥ ቤተ ክርስቲያን አበክራ ታሳስባለች።
    5. ከወርኀ ሰኔው ጥቃት በፊትም ኾነ በኋላ፣ በኦሮሚያ እና በሌሎችም ክልሎች አንዳንድ አካባቢዎች፣ በቤተ ክርስቲያንና በምእመናን ላይ በተደጋጋሚ እየደረሱ የሚገኙ ስልታዊ የኾኑ ግልጽ ተጽዕኖዎች እና ጥቃቶች፣ በዐይነት እና በመጠን እየጨመሩ መጥተዋል። አብዛኞቹ የክልል መንግሥታት፣ ለውይይት ባሳዩት በጎ ፈቃድ፣ ጥቃቱንና ተጽዕኖውን በተወሰነ ደረጃ ለመግታት ቢቻልም፣ በተለይ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የወቅቱ አስተዳደር ግን፣ የቀረበለትን በጋራ ችግሮችን የመፍታት ጥያቄ ችላ በማለት እና ባለመቀበል ቤተ ክርስቲያናችንን በተደጋጋሚ አሳዝኗታል። በክልሉ የተወሰኑ አህጉረ ስብከት፣ ቅዱስ ሲኖዶስ ያገደው ሕገ ወጥ ቡድን፣ ለቤተ ክርስቲያን በሕግ የተሰጧትን መብቶች ከመጋፋት ጀምሮ የአስተዳደር መዋቅሯን እስከ ማፍረስ የተዳፈረው፣ ክልላዊ መንግሥቱ ለቤተ ክርስቲያን ጥያቄዎች አፋጣኝ ምላሽ ባለመስጠት በሚያሳየው ቸልተኝነት እንደ ኾነ ለመረዳት አያዳግትም። በመኾኑም፣ የትላንቱን ችግር ለማከም፣ ይልቁንም ነገ በከፋ መልኩ ሊመጣ ያለውን ለማስቀረት እንዲቻል፣ በጋራ ከመሥራት ውጪ መፍትሔ የለም፤ ብለን እናምናለን። ስለዚህ ክልላዊ መንግሥቱ፣ ጥያቄያችንን ተቀብሎ በጋራ ለመሥራት ዝግጁ እንዲኾን ቤተ ክርስቲያናችን አጥብቃ ታሳስባለች።
    6. በ2012 ዓ.ም. መባቻ፣ በአንድ ቀን 97 ዜጎች እና ምእመናን ካለቁበት የወርኀ ጥቅምቱ ጥቃት እንዲሁም የወርኀ ጥር የበዓለ ጥምቀት አከባበር ወቅት ከተፈጸሙ ግድያዎች እና ዘረፋዎች ጀምሮ፣ በልዩ ልዩ የአገራችን አካባቢዎች፣ በቤተ ክርስቲያንና በምእመናን ላይ እየደረሱ ያሉ ግፎችንና በደሎችን መንግሥት አጣርቶ ለፍርድ እንዲያቀርብ፣ ውጤቱንም በይፋ ለሕዝብ እንዲገልጽ ቤተ ክርስቲያናችን አጥብቃ ትጠይቃለች።
    7. ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን፣ ለአገር ሰላም እና ለሕዝብ አንድነት ባበረከተችው አስተዋፅኦ፣ በገነባችው የተቀደሰ ባህል እና ባወረሰችው ዘርፈ ብዙ እሴት፣ በኢትዮጵያውያን ኹሉ ልትከበር እና ልትወደድ የሚገባት ናት። ከሞላው ጸጋዋ እና በረከቷ ያልተቋደሰ ኢትዮጵያዊ ይኖራል ተብሎ የማይገመት በመኾኑ፣ የኹሉ እናት እና ባለውለታ ናት ብለን እናምናለን።

    ኾኖም፣ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ፣ በቤተ ክርስቲያናችን ላይ እየደረሱ ያሉ ተደጋጋሚ ጥቃቶች፣ አብዝቶ እንደሚነገረው፣ “በሽግግር ወቅት የሚያጋጥሙ” ተብለው ብቻ የሚታለፉ ሳይኾኑ፣ የተሳሳቱ ርእዮተ ዓለማዊ ትርክቶችንና ጂኦ-ፖለቲካዊ ዳራዎችን መነሻ በማድረግ በተቀነባበረ እና በተደራጀ ስልት የሚፈጸሙ ኦርቶዶክሳውያንን የ‘ማጽዳት’ እንቅስቃሴዎች እንደኾኑ ከጊዜ ወደ ጊዜ ግልጽ እየኾነ መምጣቱን ቤተ ክርስቲያናችን ትገነዘባለች፤ በአጭር ጊዜ ሳይታረም በዚኹ ከቀጠለም፣ የከፋ ፍጻሜ ሊያስከትል እንደሚችል ከወዲሁ ታስገነዝባለች።

    ስለዚህም፣ የፌዴራል እና የክልል መንግሥታት፥ በእኒህ ስሑት አስተሳሰቦች እና ሐሳዊ ትርክቶች ማሕቀፍ፣ ኾነ ተብሎ የሚፈጸም ኦርቶዶክሳውያንን የማሣቀቅ እና የማዳከም ሃይማኖት ተኮር ጥቃትን አስቀድሞ በመከላከል፣ ፍትሕን በማስፈን፣ ተጎጂዎችን በአግባቡ በመካስ እና በማቋቋም፣ ሕገ መንግሥታዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ በአጽንዖት ታሳስባለች።

    የተወደዳችኹ ተጎጂ ምእመናንና ምእመናት የመንፈስ ልጆቻችን፤

    የግፍ ጥቃቱ የደረሰባችኹና በአሁኑ ወቅት በዐጸደ ቤተ ክርስቲያን አዳራሾች እና በግለሰቦች መኖሪያ ቤቶች ተጠልላችኹ እንደምትገኙ ይታወቃል። ይህ፣ ስለ ቀናች ሃይማኖታችኹ የተቀበላችኹት መከራ፣ በቤተ ክርስቲያናችን የሰማዕታት መዝገብ በወርቅ ቀለም ተጽፎ የሚኖር ነው። በግፈኞች ፊት ለማዕተበ ክርስትናችኹ ታምናችኹ ባሳያችኹት ጽናት እና በከፈላችኹት መሥዋዕት፣ የአገራችኹን ህልውና እና አንድነት ታድጋችኋል፤ የቤተ ክርስቲያናችኹን ልዕልና አስመሰክራችኋል። ይኸውም፣ ለትውልድ አብነት ኾኖ በምሳሌነት ሲነገር የሚኖር በመኾኑ፣ እናት ቤተ ክርስቲያናችኹ ኮርታባችኋለች። ለወደፊትም፣ መላው ኢትዮጵያውያንና ኦርቶዶክሳውያን፣ በሚያስፈልጋችኹ ኹሉ ከጎናችኹ ይቆማሉ፤ ብቻችኹን እንዳልኾናችኹም ቤተ ክርስቲያን ታረጋግጥላችኋለች። ዛሬ ባገኛችኹ መከራ ግፍ አድራሾች ቢደሰቱም፣ በጊዜው ጊዜ ፍትሕን በሕግ ተጎናጽፋችኹ እንባችኹ እንደሚታበስ እና ኃዘናችኹ ወደ ደስታ እንደሚለወጥ ቤተ ክርስቲያናችን ታምናለች።

    በአገር ውስጥ እና በውጭ የምትገኙ የተወደዳችኹ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

    አሠቃቂው ጥቃት ከደረሰበት ሰዓት ጀምሮ፣ በኢትዮጵያዊ ነባር አስተምህሮ እና የአብሮነት ባህል እርስ በርስ በመረዳዳት፣ ዓለም አቀፉ የኮሮና ቫይረስ ወረርሺኝ ያሳደረው ከባድ የኑሮ ጫና ሳይበግራችኹ እና ርቀት ሳይገድባችኹ የጥቃቱን ሰለባዎች ለመታደግ እና መልሶ ለማቋቋም ያደረጋችኹትንና በማድረግ ላይ ያላችኹትን ልዩ ልዩ አስተዋፅኦ፣ ቤተ ክርስቲያናችን በከፍተኛ አንክሮ ትመለከታዋለች፤ የጎሣ እና የእምነት ልዩነት ሳይገድባችኹ እስከ ሞት ደርሳችኹ ላደረጋችኹት ሰብዓዊ እና ኢትዮጵያዊ ርዳታ እና ድጋፍ፣ ልዑል እግዚአብሔር ዋጋችኹን ይከፍላችኹ ዘንድ ዘወትር ትጸልያለች።

    በሌላ በኩል፣ በክርስቲያናዊ የትብብር መንፈስ፣ በኦርቶዶክሳውያን ላይ የደረሰው ጉዳት ተሰምቷችኹ፣ ጥቃቱን በማውገዝ አጋርነታችኹን በመግለጫ እና በልዩ ልዩ ድጋፎች ላሳያችኹ የዓለም ኦርቶዶክሳውያን አብያተ ክርስቲያናት፥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የከበረ ምስጋናዋን ታቀርብላችኋለች።

    አሁንም፣ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ተጠናክሮ የተቋቋመው ዐቢይ ኮሚቴ በሚሰጠው አቅጣጫ መሠረት፣ ተጎጅዎችን ለመርዳት እና በዘላቂነት ለማቋቋም እያደረገ ያለውን እንቅስቃሴ፥ በገንዘብ፣ በቁሳቁስ እና በሞያ እንድትድገፉ፤ እንዳስፈላጊነቱም በቀጣይነት ለሚያስተላልፈው ጥሪ ንቁ ምላሽ ለመስጠት እንድትዘጋጁ አባታዊ መልእክታችንን እናስተላልፋለን። በዚኹ አጋጣሚ፣ በአገር ውስጥ እና በውጭ የምትኖሩ ምእመናን፥ ድጋፍ እና አስተዋፅኦ ማድረግ ያለባችኹ፣ በቋሚ ሲኖዶስ የተቋቋመው የርዳታ አሰባሳቢ አካል በከፈታቸው የባንክ ሒሳብ ቁጥሮች ብቻ መኾኑን እናስታውቃለን።

    ቸሩ እግዚአብሔር፥ ለአገራችንና ለዓለም ሰላምን፣ ለሕዝባችን አንድነትን፣ በግፍ ለተገደሉት ልጆቻችን ዕረፍተ ነፍስንና ለቤተ ክርስቲያናችን መጽናናትን እንዲሰጥልን እንለምናለን።

    ወስብሐት ለእግዚአብሔር
    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት

    ~~~

    ዐቢይ ኮሚቴው የከፈታቸው የባንክ ሒሳብ ቁጥሮች፡–

    በኦርቶዶክሳዊነታቸው ምክንያት በግፍ ለተፈናቀሉ ክርስቲያኖች መርጃ እና ማቋቋሚያ
    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አጭር ቁጥር፦ 8080
    ሕብረት ባንክ የሒሳብ ቁጥር፦ 1601811299653018
    ወጋገን ባንክ የሒሳብ ቁጥር፦ 0837771210101
    ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ የሒሳብ ቁጥር፦ 3359601000003
    ዓባይ ባንክ የሒሳብ ቁጥር፦ 146211349291701

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት

    ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተሰጠ መግለጫ

    Anonymous
    Inactive

    ኦርቶዶክሳዊ እንደ ወንጀለኛ የሚቆጠርበት ክልል
    (ጴጥሮሳውያን የቤተ ክርስቲያን ክብርና መብት አስጠባቂ ኅብረት)

    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኢትዮጵያ ታሪክ፣ ሀገራችን ኢትዮጵያም በኦርቶዶክስ ታሪክ ውስጥ ያላቸው ውሕደት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ እንደማለት ነው። የኢትዮጵያ ታሪክ እና ቅርስ ሙሉ ለሙሉ ማለት በሚቻልበት ሁኔታ የቤተ ክርስቲያኗ በመሆኑ ቤተ ክርስቲያኗ ሀገር መሆኗን እኛ ብቻ ሳንሆን ምዕራባውያን ጸሐፊዎችም የመሰከሩት እውነታ ነው። ኢትዮጵያ እና ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በፍጹም አንድነት ሲገለጡ ኖረዋል።

    ካለፉት 40 ዓመታት በኋላ ግን ለዘመናት የኖረው እውነት ተገፍቶና ተሽሮ ቤተ ክርስቲያኗን የማይወክል የሐሰት ትርክት ሲነገር ኖሯል። ከ1983 ዓ.ም. በኋላ ደግሞ ቤተ ክርስቲያኗን በጠላትነት በመፈረጅ “ቀና እንዳትል አከርካሪዋን ሰብረነዋል” ብለው በአደባባይ እስከ መናገር ደረሱ። አብያተ ክርስቲያናትን ለመቃጠል፣ ክርስቲያኖችን ለሞት፣ ለስደት፣ ለመፈናቀል እንዲሁም ለንብረት ውድመት ተዳረጉ። በሁለተኛው እና በሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ክርስቲያኖች ያለፉበትን ሰማዕትነት እና ትላንት በሌላው ዓለም ስንሰማውና በቴሌቪዥን መስኮት ብቻ ስናየው የነበረው አሰቃቂ ግድያ ኦርቶዶክስ በመሆናቸው ብቻ በሀገራችን ተፈጽሞ የሞትን ጽዋ ተጎነጩ ።

    በክርስቶስ ደም የተመሠረተችው ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሐዋርያት ስበከት ወደ ዓለም ሁሉ መድረሷ እና በሰማዕታት ደም መጽናቷ ይታወቃል። ሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. ማታ የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳን መገደል ምክንያት በማድረግ አስቀድመው አቅደውት የነበረውን ኦርቶዶክሳውያንን የማጥፋት እኩይ ድርጊት በአሰቃቂ ሁኔታ ፈጽመውታል፤ ቤት ንብረታቸውን አቃጥለዋል። ቅዱስ ሲኖዶስ የተረፉትን ክርስቲያኖች ለማጽናናት እና የደረሰውን ጉዳት ለማየት በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የተመራ የሀገር ሽመግሌዎች እና የማኅበራት የተካተቱበት በሦስት አቅጣጫ ጉዞ አድርጓል። ልዑኩ በሦስት ተከፍሎ ጉዞ ካደረገባቸው መካከል ይህ ዘገባ በምዕራብ አርሲ እና በምሥራቅ ሸዋ የተደረገውን የሚያስገነዝብ ነው። የማጽናናት እና የተበተኑን ለመሰብሰብ ታልሞ በተካሔደው ሐዋርያዊ ጉዞ ጴጥሮሳውያን የቤተ ክርስቲያን ክብርና መብት አስጠባቂ ኅብረት የደረሰውን ጉዳት እንደሚከተለው እናቀርባለን። ከሐምሌ 24-26 በተደረገው ሐዋርያዊ ጉዞ የተመለከትናቸው ዝዋይን፣ አዳሚ ቱሉን፣ አርሲ ነገሌን ፣ ኩየራን፣ ፍልቻን፣ ሻሸመኔን፣ አዳባን ፣ ሄረሮን፣ አሳሳን፣ ሽሬን፣ ቆሬን እና ኮፈሌን ነው።

    ዝዋይ
    በዝዋይ ከተማ የአንድ ቤተሰብ አባል የሆኑ አምስት ኦርቶዶክሳውያን በአሰቃቂ ሁኔታ ተቆራርጠው በመገደል ሰማዕትነትን ተቀብለዋል። ገዳዮቹ ጭካኔያቸውን የሰማዕታቱን አስከሬን በመሬታችን አይቀበርም በማለት አንገላተዋል። የኦርቶዶክሳውያን የንግድ ቦታቸው እና የመኖሪያ ቤታቸው ሙሉ በሙሉ በእሳት ጋይቷል። በሁሉም ከተሞች እና ወረዳዎች የክርስቲያኖች የንግድ ቦታቸው እና የመኖሪያ ቤቶቻቸው ሙሉ ለሙሉ የወደሙ ሲሆን፥ ጥቃቱ የተፈጸመባቸው ክርስቲያኖቹ “ላዩ ሣር ውስጡ ባህር” በሚባልለት ክረምት በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያኑ ተጠልለው በብርድ ይሰቃያሉ።

    ፍልቻ
    በፍልቻ ቅድስተ ማርያም ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ካህን በዱላ ተደብድበው፣ ቤታቸው ሙሉ ለሙሉ መቃጠሉን ለማየት ችለናል። በዚሁ ደብር አገልጋይ የሆኑትን ካህን እና ከዘጠና ዓመት በላይ የሆናቸውን የዕድሜ ባለጸጋ ገፍትረው ጥለው ‘እስከ ዛሬ አንተ አጥምቀሃል፤ ዛሬ እኛ እናጥምቅህ’ በማለት በባልዲ ውሃን እየደፉ እንዳሰቃዩዋቸው ነግረውናል።

    ሻሸመኔ
    በሻሸመኔ የሚገኘው የቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ አባላት ሆቴሎቻቸው እና ትምህርት ቤታቸው በእሳት ጋይቷል። ወ/ሮ ሜሮን የተባለች የ፱ ወር ነፍሰ-ጡር ልብሷን በመቅደድ እና ቢላን ሆዷ ላይ በማድረግ ክርስቲያን እንደማይወለድ ስላስፈራሯት የተፈጸመባት ድርጊት ጭንቀት እና ቅዠት ዳረጓት ሕይወቷ ዐልፏል።

    በጠቅላላው በሻሸመኔ የተፈጸመውን ውድመት መልሶ ለማልማት ከፍተኛ ገንዘብን እና ብዙ ጊዜ ይወስዳል። ጥፋት ፈጻሚዎች አሁን ድረስ የማስፈራራት እና ክርስቲያኖችን የማሳቀቅ ተግባር እየፈጸሙ መሆኑን ተጎጂዎች ተናግረዋል። የሻሸመኔ ውድመትና ጥቃት በመንግሥት መዋቅር ውስጥ በተሰገሰጉ ባለሥልጣናት እና በፓሊስ ቸልተኝነት የተፈጠረ በመሆኑ ዘወትር በታሪክ ሲታወስ ይኖራል።

    አዳባ
    የክርስቲያኖች ቤት ተቃጥሏል፤ አንድ ወጣት ክርስቲያንም በአሰቃቂ ሁኔታ ተገድሏል። ወጣቱ ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ታርዶ የተሰዋ ሲሆን፥ ቤተሰብም ‘አስከሬኑን አታነሱም’ ተብለው እስከ ረፋዱ አምስት ሰዓት ዝናብ እና ፀሐይ ተፈራርቆበታል። በተጨማሪም የወጣቱን ደም ውሾች ሲልሱት ቤተሰብ በመመልከቱ ለአእምሮ መረበሽ ተዳርገዋል። በመጨረሻም ለአራት በመሆን የሰማዕቱን አስከሬን አንሥተው ለመቅበር ችለዋል። ንብረቶቻቸው እና ቤቶቻቸው የተቃጠለባቸው ክርስቲያኖች በቤተ ክርስቲያን ተጠልለዋል። የተጎዱትን ምእመናንን የሚመግቡት አስተባባሪዎች ታስረው እንደ ነበር ለማወቅ ተችሏል።

    አሳሳ
    በአሳሳ እና ሄረሮም የክርስቲያኖች ቤት እና ንብረት ሙሉ ለሙሉ የወደመ ሲሆን፥ በአሳሳ አራት ሰዎች፣ በሄረሮ አንድ ሰው በአሰቃቂ ሁኔታ ተጨፍጭፈውና ታርደው ተገድለዋል። በሽሬ፣ በቆሬ እና በኮፈሌ የሚገኙ ክርስቲያኖችም የተጎዱ ሲሆን፥ ለዘመናት ያፈሩት ቤት ንብረት ሙሉ ለሙሉ ወድሟል። ኦርቶዶክሳውያን በሙሉ በየአብያተ ክርስቲያኑ በመቃብር ቤትና በደጀ ሰላም ለመጠለል ተግድደዋል። ለዓመታት የቀጠለው ኦርቶዶክሳውያንን የማሳደድ እና የማጥፋት ድርጊት እልባት ባለማግኘቱ፥ የመንግሥት የጸጥታ አካላት የክርስቲያኖችን ደኅነነት ማስጠበቅ ባለመቻላቸው ዛሬም ድረስ ጭንቀት ፈጥሮባቸዋል። ዛሬም የማስፈራርያና የውጡልን ዛቻው እነደቀጠለ መሆኑን ተናግረዋል።

    መንግሥት መቆጣጠር እና የኦርቶዶክሳውያንን ደኅንነት ማስጠበቅ ለምን ተሳነው?

    በተለይ በኦሮሚያ ክልል የሚፈጸሙ ጥቃቶች ማቆም እና ኦርቶዶክሳውያንን መታደግ ያልተቻለበት ምክንያት ጥቃቱ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ባሉ ኃላፊዎች ይመራ እና ከለላ ይደረግለት ስለነበር ነው። የሚፈጸምን ወንጀል ማቆም የተሳነው የጸጥታ አካል ‘ትዕዛዝ አልተሰጠኝም’ በማለት ኦርቶዶክሳውያን ሲጨፈጨፉ እና ሀብት ንብረታቸው ሲወድም ይመለከት ነበር።

    መፍትሔ

    መንግሥት ኃላፊነቱን በመወጣት ሕግ ማስከበር ይኖርበታል። የሰዎችን የመኖር ተፈጥሯዊም ሕገ መንግሥታዊ መብት ማስጠበቅ አለበት። ወንበዴዎችን ተከታትሎ በመያዝ የጀመረውን ሥርዓት የማስጠበቅና ሕግ የማስከበር ተግባሩን አጠናክሮ መቀጠል፣ የኦርቶዶክሳውያንን ስጋት ማቃለል ኖርበታል፤ ለተፈናቀሉ እና ሀብት ንብረት ለወደመባቸው ወገኖች ተገቢው ካሳ በመስጠት መልሶ ማቋቋም ይኖርበታል፤ በፍጥነት በመሥራት የእኩይ ተግባር ተቃዋሚነቱን ማሳየት ይገባዋል። ይህ ካልተደረገ ኦርቶዶክሳዊ መሆኑ እንደ ወንጀለኛ እየተቆጠረ ሲሳደድ ይኖራል።

    ኦርቶዶክሳዊ ኅብረት እንዲጠናከር እና እራስን የመጠበቅ የመከላከል ሥራ ተግባር እንዲፈጽም ማንቃት ያስፈልጋል። በየአካባቢው የሚኖረው ክርስቲያን ቅንጅት የመፍጠር እና የመሳተፍ ግዴታ ይኖርበታል።

    በመጨረሻም፡-

    የተፈጸመው ኦርቶዶክሳውያንን የማጥፋት ተግባር መሆኑን ለማረጋገጥ ችለናል። ተመሳሳይ ጥቃት እንዳይፈጸምብን መንቃት ይኖርብናል። የተጠናከረ ጥበቃ በማድረግ ወገኖቻችንን መታደግ ግድ ይለናል። ወደ ፊት ለሚፈጸመው ጥቃት መንግሥት ኃለፊነቱን እንዲወስድ ማድረግ ይገባል።

    ይቆየን…

    መጋቤ ሥርዓት ዮሴፍ ዓባይ
    ጴጥሮሳውያን የቤተ ክርስቲያን ክብርና መብት አስጠባቂ ኅብረት የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ

    ጴጥሮሳውያን የቤተክርስቲያን መብትና ክብር አስጠባቂ ኅብረት

     

    Anonymous
    Inactive

    የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን እህተ ማርያም በሌሎች ወንጀሎችም በመጠርጠሯ ምርመራውን እያጠናከረ መሆኑን ገለጸ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ራሷን ንግሥተ ነገሥት (እህተ ማርያም) እያለች በምትጠራው ትዕግሥት ፍትህአወቅ ላይ የአስቸኳይ አዋጁን ከመጣስ በተጨማሪ በሌሎች ወንጀሎችም በመጠርጠሯ ምርመራውን እያጠናከረ መሆኑን ገለጸ።

    በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የልዩ ልዩ ወንጀል ዲቪዥን ምርመራ ኃላፊ ኢንስፔክተር በድሉ ግርማ ትዕግሥት ፍትህአወቅ (እህተ ማርያም) ላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን እምነቴንና ቀኖናዬን አቃላለች መገልገያ አልባሳቴን ያለ አግባብ ጥቅም ላይ አውላለች በሚል ያቀረበችው ክስም በምርመራው እየታየ እንደሆነ ገልጸዋል።

    ግለሰቧ ሃይማኖትም ሆነ ማኅበር ለመመሥረት ከኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዲሪ) የሰላም ሚኒስቴር ተገቢውን ፈቃድ ሳታገኝ ርትዕት ተዋሕዶ የሚል ሃይማኖት መሥርታ ተከታዮቿን አላግባብ እየሰበሰበች የነበረበት ሂደትም እየተመረመረ ነው ተብሏል።

    ተጠርጣሪዋ የትዳር አጋሯ በትራፊክ አደጋ እንደሞተ ብትገልጽም የሟች ቤተሰቦች ይህ ስለመሆኑ ምንም ማስረጃ ባለመኖሩ ተጨማሪ ምርመራ ይደረግልን ማለታቸውም ምርመራው የሚያተኩርበት ሌላ ጭብጥ መሆኑንም ኢንስፔክተሩ ገልጸዋል።

    በተጠርጣሪዋ ቤት የተገኘው አስከሬንም ለምርመራ ወደ ሆስፒታል መላኩንም ኢንስፔክተር በድሉ ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    —–
    ሌሎች ዜናዎች፦

    እህተ ማርያም

    Semonegna
    Keymaster

    ‘አገር የሆነች ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅ የመንግሥት ግዴታ መሆኑን’ በማሳሰብ ማኅበረ ቅዱሳን ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) ደብዳቤ ጻፈ። የደብዳቤው ሙሉ መልዕክት እንደሚከተለው ይነበባል።

    ለክቡር ዶክተር ዐቢይ አህመድ
    የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዲሪ) ጠቅላይ ሚኒስትር
    አዲስ አበባ
    ጉዳዩ፡- በተለያዩ አካባቢዎች በቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሱ ያሉ ጥቃቶች እንዲቆሙ ስለመጠየቅ

    ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ሆይ፡- አስቀድመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኢትዮጵያ የሀገር ግንባታ የነበራትን ታላቅ ሚና ተገንዝበው ለቤተ ክርስቲያናችን አንድነትና ሰላም ያረጉትን አስተዋጽኦ ሳናመሰግን አናልፍም።

    ይሁንና በአሁኑ ወቅት ይህን ደብዳቤ ለእርስዎ ለመጻፍ ያነሳሳን ዐቢይ ጉዳይ በሀገራችን በየጊዜው ድንገት በሚፈጠሩ ሁከቶችና ብጥብጦች ሁሉ ምክንያት ተፈልጎ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም ካህናቶቿና ተከታዮቿ ምእመናን የአደጋ ሰለባ እንዲሆኑ እየተደረገ መምጣቱ በከፍተኛ ደረጃ አሳሳቢና አፋጣኝ መፍትሔ በመንግሥት ሊሰጠው የሚገባው ሆኖ አግኝተነዋል።

    በየትኛውም ዓለም የሚኖሩ የእምነት ተቋማት ለሀገር ግንባታና ዕድገትም ያላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑ ግልጽ ነው። እንደዚሁ ሁሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኢትዮጵያ የሀገረ መንግሥት ግንባታ የማይተካ ሚና እንደ ነበራት ግልጽ ነው። በሥነ ጥበብ፣ በኪነ ሕንፃ፣ በሥነ ሥዕል፣ በሥነ ጽሑፍ፣ በሕግ ቀረጻና ሀገራዊ ክብርና እሴትን በማስጠበቅ ከፍተኛ ሚና የተጫወተች መንፈሳዊ ተቋም ናት። በረከታቸው ይደርብንና በሕይወት የተለዩን ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በተለያዩ ጽሑፎቻቸውና አባባሎቻቸው እንዳስቀመጡት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥነ ጽሑፍ ከነፊደሉ፣ ነጻነት ከነክብሩ፣ ዘመን ከነቀመሩ፣ ሀገር ከነድንበሩ፣ አንድነት ከነጥብዓቱ ያስረከበች የኢትዮጵያ ባለውለታ ናት። ቀደም ሲል በክቡርነትዎም አንደበት እንደተነገረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሀገር ባለውለታ ከማለት ይልቅ ራሷን ሀገር አድርጎ መግለጽ የውለታዋን ታላቅነት በተሻለ ሁኔታ ያሳያል። ይህን የምታደርገው ደግሞ የሀገሪቱን ከፍተኛ ቁጥር የያዘ ሕዝብ የምትመራ እንደመሆኗ እንደ ሀገር ስለምታስብና ለሀገር ልማትና እድገት ትኩረት ሰጥታ ስለምትሠራ መሆኑን ለመረዳት አያስቸግርም ።

    ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር፡-

    ቤተ ክርስቲያን ለሀገር ያበረከተችው አስተዋጽኦና ውለታ ይህ ሆኖ ሳለ ወርቅ ላበደረ ጠጠር እንዲሉ እየተፈጸመባት ያለው ግፍ ከበጎነቷ በተቃራኒ ከመሆኑም በላይ ከጊዜ ወደ ጊዜ በይዘቱ እየባሰና እየጨመረ በዐይነቱም ለመናገር እስከሚሰቀጥጥ ድረስ ዘግናኝ እየሆነ መጥቷል። ይህ ግፍ የተጀመረው ዛሬ ባይሆንም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ እያጋጠሙ ያሉ ተደጋጋሚና ቀን ቆጥረው የሚፈጸሙ ጥቃቶች በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተበረታቱባት ይገኛሉ። በተለይም ጽንፍ የረገጠው የዘውግ ፖለቲካ ርእዮተ ዓለምና ኢትዮጵያን በጠላትነት የፈረጁ “የውጭ አካላትን” ሽፋን ያደረገ እንቅስቃሴ ግብ ቤተ ክርስቲያንን የማጥፋትና ለሀገር አንድነትና ነጻነት ያላትን ሚና መቀነስ እንደሆነ ግልፅ እየሆነ መጥቷል። ከሀገራዊ የለውጥ እንቅስቃሴ ጋር ተያይዘው የመጡ የብዙ አካላት ፍላጎቶችም እንዲህ ዐይነት ቀውሶች እንዲፈጠሩ አስተዋጽኦ እንዳላቸውም እንረዳለን። በሀገር ውስጥም የወደፊቷ ኢትዮጵያ ምን መምሰል አለባት በሚለው ሃሳብ ላይ ዋልታ ረገጥ የሆነ አመለካከት በሚያራምዱ አካላት መካከል ያለው ውጥረትም ቀላል እንዳልሆነ እንገምታለን።

    ይህም ሁሉ ሆኖ መንግሥት ችግሩን ለመፍታትና ምላሽ ለመስጠት ያሳየውን በጎና ቅን ሙከራዎችን ግን ሳንጠቅስ አናልፍም። ነገር ግን አሁንም ቤተ ክርስቲያን የጥፋት መልእክተኞች የጥቃት ዒላማ ሆና ትገኛለች። በዚህ ረገድ የሕግ የበላይነት ኖሮ ፍትሕ ማግኘት አለመቻል ከመንግሥትም በቂ ከለላ ሳታገኝ መቅረቷ በኦርቶዶክሳውያን አእምሮ ብሶትና እሮሮ ያስነሳ በመንግሥትም ላይ ትልቅ ጥርጣሬን የሚያጭር እየሆነ መጥቷል። ለዚህም በምሳሌነት ቀደም ያለውን እንኳ ትተን የቅርቡን ብናይ በሲዳማ የክልልነት ጥያቄ በተነሳው ውዝግብና ከአክቲቪስት ጃዋር መሐመድ ጥበቃ መነሣት ውዝግብ ጋር ተያይዞ በተቀሰቀሰው ረብሻ በቤተ ክርስቲያን፤ በአገልጋዮችና በምእመናን የተፈጸመውን ጥቃትና የደረሰውን ዕልቂት ማስታወስ ይበቃል። በአጠቃላይ ሐምሌ 28 ቀን 2010 ዓ.ም ጀምሮ በጅግጅጋና አካባቢው ከተፈጸመው ጥቃት እስከ አሁን ቤተ ክርስቲያን ብዙ መከራን አስተናግዳለች። እርስዎ ከመጡ ጀምሮ በተረጋገጠ መረጃ መሠረት በትንሹ 25 አብያተ ክርስቲያን ተቃጥለዋል። ጅግጅጋ፣ ጅማ፣ ሲዳማ፣ ከሚሴ፣ ምሥራቅና ምዕራብ ሐረርጌ፣ ምሥራቅና ደቡብ ምዕራብ ሸዋ፣ ባሌና አርሲ በተፈጸሙ ጥቃቶች በመቶዎች የሚቆጠሩ ካህናትና ምእመናን በአሰቃቂ ሁኔታ በድንጋይ ተቀጥቅጠው፣ በእሳት ተቃጥለውና በገጀራ ተቆራርጠው ሕይወታቸውን አጥተዋል። በመቶዎች የሚቆጠሩ ከፍተኛ የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል። ሕፃናትንና አሮጊቶችን ጨምሮ ብዙ ሴቶች ተደፍረዋል። የብዙ ክርስቲያኖች ቤቶች ተቃጥለዋል። በሺዎች የሚቆጠሩ ከቀያቸውና ከሀብት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል። በተለያዩ የሥነ ልቡና ጫናዎች ውስጥ ወድቀው በፍርሃትና በሥጋት የሚኖሩት ቁጥራቸው ቀላል አይደለም።

    ቀደም ሲልም የቤተክርስቲያን መቃጠልና ጥቃት ይቁም ብለው የተሰባሰቡና ለክቡርነትዎ ቀርበው ሃሳባቸውን ገልጸው እርስዎም በሰጡት ምላሽ ከክልሎች ጋር በመወያየት ችግሮችን ለመፍታት ብዙ ጥረቶች ተደርገዋል። ብዙ ክልሎችም አዎንታዊ ምላሽ ሰጥተዋል። የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ግን ጉዳዩ ላይ ትኩረት አልሰጠም፤ ፍላጎትም አላሳየም። አሁን እንደሚታዩት አብዛኞቹ ችግሮች የተፈጸሙትና በመፈጸምም ላይ የሚገኙት በዚሁ ክልል ውስጥ ነው። ይህን የምንጠቅሰው ስለማያውቁት ሳይሆን እንዲህ ዐይነቶች ጥቃቶች እየተፈጸሙ በአጥፊዎች ላይ አስተማሪ ርምጃ ሳይወሰድ ሲቀርና የዜጎች የደኅንነት ዋስትና አለመረጋገጥ ምን ማለት እንደሆነ ምንስ ያህል ከባድ እንደሆነ በኋላ የሚያስከትለውም አደጋ ከባድ እንደሆነ ለማሳሰብ ጭምር ነው።

    በያዝነው ወርኃ ኅዳር ደግሞ የጥቃት ዒላማ ተረኛ የሆኑት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ናቸው። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ብዙ ፍላጎቶች የሚስተናገዱባቸው፣ የሀሳብ ፍጭቶች የሚካሔዱባቸውና፣ ማኅበራዊ መስተጋብሮች የሚፈጸሙባቸው የልሕቀት ማእከላት ናቸው። በአግባቡ ከተያዙ ሀገርን ከድህነት የሚያወጡና ለሀገር ፈውስ የሚሆኑ ሊቃውንት የሚወጡባቸው፣ በአግባቡ ካልተያዙና ለጥፋ መልእክተኞች መሣሪያ ከሆኑ ግን ሀገርን የሚያጠፉ ትምህርትን በአግባቡ ያልተጠቀሙበት የጥፋት ዐርበኞች የሆኑ ትውልዶች የሚፈሩባቸው እንደሚሆኑ የታመነ ነው። ይህን እውነት ከግንዛቤ አስገብተን ስንመለከተው ለሀገር የሚበጅ፣ በሥነ ምግባር የታነጸ፣ ለሕዝብ የሚቆረቆር የተማረ ዜጋ ማፍራት የሚቻለው ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የተረጋጋ የመማር ማስተማር ከባቢያዊ ሁኔታ መፍጠር ከቻሉ ብቻ ነው። በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ላይ አጥልቶ የሚታየው የጥቃት ድባብ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እንዲማሩ ልጆቻቸውን የላኩ ወላጆችንም ሆነ ተማሪዎችን በተረጋጋ መንፈስ እንዲኖሩ የሚፈቅድ አይደለም። በአንዳንድ ቦታ አልፎ አልፎ እየተከሰቱ ያሉ አደጋዎችና ሁከቶች ወላጆችን ለከፍተኛ ሥጋትና ጭንቀት እየዳረጋቸው ነው። በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እየተፈጸመ ያለው ጥቃትም ሃይማኖትን ማእከል ያደረገ መሆኑ ደግሞ ጉዳዩን የበለጠ አሳሳቢ ያደርገዋል። ስለሆነም መንግሥት በአጥፊዎች ላይ ርምጃ አለመውሰድን እንደ “ትዕግሥት” በመቁጠር ቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃት በዝምታ መመልከቱ ብዙ ዋጋ የሚያስከፍል ነውና የዜጎችን የመኖር መብትና የደኅንነት ዋስትና ማረጋገጥን መንግሥት በአግባቡ እንዲተገብረው እንጠይቃለን። ሰሞኑን እንደተመለከትነው ጥቃቶችና ግጭቶችን በእንጭጩ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሳይወጡ መቆጣጠር እየተቻለ ከትኩረት ማነስ ምክንያት ይህንን ማድረግ ባለመቻሉ በምሥራቅና ምዕራብ ሐራርጌ ምእመናንና አብያተ ክርስቲያናት በሁለት ቀናት ብቻ የደረሰውን ጥፋት ዘርዝረን የማንጨርሰው ሆኖብናል።

    በመሆኑም በተለይም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች እየተፈጸሙ ያሉ ጥቃቶች በሚዲያ እንደተገለጸው ከመንግሥት አቅም በላይ ካልሆኑ በአጭር ጊዜ ችግሮቹ እልባት እንዲያገኙ መደረግ አለበት፣ ካልተቻለ ደግሞ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለተወሰነ ጊዜ ተዘግተው የማረጋጋት ሥራዎችን ሠርቶ እንደገና ማስጀመር እንደ አማራጭ መፍትሔ መታየት ይገባዋል ብለን እናምናለን። ከዚህም በተጨማሪ ጥቃቶችን እየፈጸሙና እያስፈጸሙ ባሉ አጥፊዎች ላይ አስተማሪ ርምጃ በግልጽና ሁሉንም ዜጋ በሚያሳምን መልኩ መውሰድ ለዜጎች ደኅንነት ማረጋገጥ ለነገ የማይባል ጉዳይ መሆኑን መግለጽ እንወዳለን። ችግሩ አልፎ አልፎ ከኦርቶዶክሳውያን ውጭ የሚገኙትንም የሚያካትት ቢሆንም አሁን ግልፅ ሆኖ ግን የሚታየው ኦርቶዶክሳውያኑ ላይ እጅግ ያነጣጠረ የሰፋና የከፋም ነው። አስቸኳይ መፍትሔ ካልተገኘለትም ‘’ኦርቶዶክሳውያኑ በሁሉም አካባቢ የጥቃት ዒላማ ተደርገን እየተቆጠርን ያለነው እኛን ነን’’ በማለት የራሳቸውን ደኅንነት የማስጠበቅ ግዴታ ውስጥ ሊገቡ ይችላሉ። ይህ ደግሞ ከፍተኛ መተላለቅንም ሊያስከትል ይችላል። አንዳንድ የመንግሥት ሚዲያዎች አደጋዎችን በትክክል እንደመዘገብ እውነትን ማስተባበልና የተሳሳተ መረጃ ማስተላለፋቸው ደግሞ አሳዛኝ ከመሆኑም በላይ ሆነ ተብሎ የሚወሰድ ርምጃና በአብዛኛውም ምእመንም ዘንድ መንግሥታዊ ሽፋን ያለው ተደርጎ እንዲወሰድ አድርጎታል። በአጠቃላይ የችግሮቹ ሂደት ከመንግሥት ቁጥጥር ውጪ የሆኑ ጉዳዮች ከመፈጠራቸው በፊት መንግሥት አስፈላጊውን ሁሉ እንዲያደርግ በተለይም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ላይ እየተፈጸሙ ያሉ ጥቃቶች በአስቸኳይ መፍትሔ እንዲሰጣቸው እየጠየቅን በጉዳዩ ዙሪያ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማትም ሆኑ ሃይማታዊ ተቋማት ሊሳተፉባቸው በሚገባቸው ኃላፊነቶች ሁሉ የድርሻችን ለመወጣት ዝግጁ መሆናችንን በዚሁ አጋጣሚ ለመግለጽ እንወዳለን።

    እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ!!!
    ማኅበረ ቅዱሳን (EOTCMK)

    ማኅበረ ቅዱሳን

    Semonegna
    Keymaster

    ሀገር የማዳን ጥሪ
    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ሕዝብ ግንኙነት

    ባለፉት ሁለት ቀናት ውስጥ በሥርዓት አልበኞች በተወሰደ የጥፋት እርምጃ የማይተካ የዜጎቻችንን ሕይወት አጥተናል፣ የብዙዎች አካል ጎድሏል፣ ዜጎች ለፍተው ያፈሩት ንብረት ወድሟል እዲሁም በተዘጉ መንገዶች ምክንያት ዜጎች ተንገላተዋል፤ የሀገሪቷ የኢኮኖሚ እቅስቃሴም ተስተጓጉሏል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በዜጎች ሕይወት ላይ በደረሰው ጥፋት የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን ይገልጻል። ሕይወታቸውን ላጡ ዜጎች ቤተሰቦች እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ መጽናናትን ይመኛል። የተፈጸመውን ሕገ ወጥ እና አሳፋሪ ተግባር አጥብቆ ያወግዛል!

    የፖለቲካ ፍላጎትን በኃይል ለመጫን የሚደረጉ የሥርዓት አልበኞች ሙከራዎች ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሱ መጥቷል። የመንግሥት እነዚህን ሙከራዎች አስቀድሞ የመተንበይ፣ ሲከሰቱም አፋጣኝ እና ተገቢውን ምላሽ የመስጠት አቅሙ ከጊዜ ወደጊዜ መሻሻል እየታየበት አይደለም። በዚህም ምክንያት የዜጎች ሕይወት በተደጋጋሚ አደጋ ላይ ወድቋል፤ አሁንም እየወደቀ ይገኛል። በቁጥር ቀላል የማይባሉ ዜጎች በሀገራቸው ደኅንነታቸው ተጠብቆ በነጻነት የመንቀሳቀስ፣ የመሥራት እና የመኖር መብታቸውን መጠቀም የማይችሉበት ብቻ ሳይሆን በማያቋርጥ ስጋት እና ጭንቀት ውስጥ ሕይወታቸውን እንዲመሩ የተገደዱበት ደረጃ ላይ ደርሰናል። ከዚህም አልፎ በዕምነት ተቋማት እና ማንነት ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች ደግሞ በማኅበረሰቡ ውስጥ ያለመተማመን ክፍተት እንዲፈጠር ምክንያት እየሆነ ነው። ይህ ጉዳይ በአስቸኳይ የማይታረም ከሆነ የሽግግር ሂደቱ ተጨናግፎ ወደማንወጣው ቀውስ ውስጥ ሊከተን ይችላል።

    መንግሥት የችግሩን ጥልቀት እና ሕግ የማስከበር ድክመቱን በሚገባ ፈትሾ በአስቸኳይ ክፍተቶቹን እንዲያስተካክል እና የዜጎችን ሰላም እና ደኅንነት የማስጠበቅ እና ጥፋተኞችን ሕግ ፊት የማቅረብ ኃላፊነቱን በአግባቡ እንዲወጣ ከመቼውም ጊዜ በላይ አጥብቀን እናሳስባለን።

    መላው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን ከመቼውም ጊዜ በላይ የጋራ ሀገራችንን ከጥፋት አፋፍ ለማዳን የምንችለውን ሁሉ ማድረግ የሚገባን ወቅት ላይ መሆናችንን ተገንዝበን ልዩነቶቻችንን አቻችለን በአንድነት እንድንቆም እና ሀገራችን ከተደቀነባት ከባድ አደጋ እንድንታደግ ከአደራ ጭምር ጥሪ እናስተላልፋለን።

    የኢዜማ ሕዝብ ግንኙነት

    ምንጭ፦ ኢዜማ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    —–
    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    ሀገር የማዳን ጥሪ

    Semonegna
    Keymaster

    ባንዲራ ይዛችሁ ወጥታችኋል በማለት ክርስቲያኖችን የሚያዋክቡ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ተጠየቀ
    ሕዝብን ከሕዝብ ለማጋጨት የሚሞክሩ ጽንፈኞች ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ፣ በቤተ ክርስቲያን እና በምእመናን ላይ እየተፈጸመ ያለው ግፍ እንዲቆም የሚያግዝ እና ጥፋት ከመፈጸሙ በፊት ሙያዊ ትንተና የሚያቀርብ ኮሚቴ እንዲቋቋም ጉባኤው ጠይቋል።

    —–

    አዲስ አበባ (ማኅበረ ቅዱሳን) – የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ዓርማ አድርጋ ስትጠቀምበት የኖረችውን እና አሁንም የምትጠቀምበትን ባንዲራ ለበዓል ይዛችሁ ወጥታችኋል፤ በቤተ ክርስቲያን ጣሪያ እና ጉልላት ላይ ቀብታችኋል በማለት ምእመናንን የሚያዋክቡ፣ ወጣት ክርስቲያኖችን የሚያስሩ አካላት ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ተጠየቀ።

    በተጨማሪም የቤተ ክርስቲያንን ተቀማጭ ገንዘብ ከንግድ ባንክ አውጥታችሁ እኛ በምንፈልገው ባንክ አስቀምጡ በማለት የሚያስገድዱ በአንዳንድ አህጉረ ስብከት የሚገኙ አካላት ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ያስጠነቀቀው 38ኛው የመንበረ ፓትርያርክ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ቅዳሜ ጥቅምት 8 ቀን 2012 ዓ.ም. በተጠናቀቀበት ዕለት ነው።

    ቤተ ክርስቲያንን ለማጥቃት ርዕዮተ ዓለም ቀርጸው፣ የሐሰት ታሪክ ፈጥረው በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን የሚነዙ አቀጣጣዮችን (‘አክቲቪስት’/ ‘activist’ ነን ባዮች) እና ፖለቲከኞችን እኩይ ድርጊት መቃወም እንደሚገባ ጉባኤው በመግለጫ አሳውቋል።

    ሕዝብን ከሕዝብ ለማጋጨት የሚሞክሩ ጽንፈኞች ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ፣ በቤተ ክርስቲያን እና በምእመናን ላይ እየተፈጸመ ያለው ግፍ እንዲቆም የሚያግዝ እና ጥፋት ከመፈጸሙ በፊት ሙያዊ ትንተና የሚያቀርብ ኮሚቴ እንዲቋቋም ጉባኤው ጠይቋል።

    የሕግ ባለሙያዎች የተካተቱበት ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን የሚደርስ ኮሚቴ በቅዱስ ሲኖዶስ እንዲቋቋም ጉባኤው አሳስቦ አገራዊ ለውጡ ተስፋ የሰጠ ቢሆንም በቤተ ክርስቲያን እና በምእመናን ላይ እየደረሰ ያለው እኩይ ተግባር ቤተ ክርስቲያንን እያሳዘናት እና እያሳሰባት መሆኑንም አስገንዝቧል።

    በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚፈጸመውን ጥፋት በሰላማዊ መንገድ በሽምግልና እና በውይይት ለመፍታት ጥረት ማድረግ የሚገባ መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የሚመራ ዓለም አቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ መደረግ እንደሚኖርበትም አሳስቧል።

    የጥምቀት እና የመስቀል በዓላት ማክበሪያ ቦታዎችን ሙሉ በሙሉ ነጥቀው፣ አንዳንድ ጊዜም ቆርሰው ለሌሎች የሚሰጡ አካላትን እኩይ ድርጊት አጥብቆ የተቃወመው መግለጫው በአገር ውስጥም በውጭም የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ለመፈታተን የሚሞክሩ ግለሰቦችን እና ቡድኖችን እኩይ ድርጊት ቅዱስ ሲኖዶስ በጥበብ እና በትዕግሥት ማሳለፉ የሚያስደንቅ መሆኑን ገልጧል።

    ምንጭ፦ ማኅበረ ቅዱሳን / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ባንዲራ ይዛችሁ ወጥታችኋል

    Semonegna
    Keymaster

    ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በወቅታዊ የቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳዮች ላይ የተሰጠ የአቋም መግለጫ

    የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጥንታዊት፣ ታሪካዊትና ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን እንደመሆኗ መጠን አገራችን ኢትዮጵያ አሁን ከደረሰችበት የሥልጣኔና የእድገት ደረጃ ከመድረሷ በፊት ብራና ዳምጣ፣ ቀለም በጥብጣና ፊደል ቀርጻ ትምህርትና ሥልጣኔን ያስጀመረች፣ የመጀመሪያው ዩኒቨርሲቲና የትምህርት ሚኒስቴር፣ የፍትሕ ሥርዓቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ መዋቅራዊ አደረጃጀት ገና ሳይኖረው ፍርድ እንዳይጓደልና ደሃ እንዳይበደል በማሰብ የፍትሐ-ነገሥት መምህራኖቿን በዳኝነት መድባ የፍትሕ ሥርዓትን የመሠረተች፣ ዜጎችን በሥነ-ምግባርና በግብረ-ገብነት ትምህርት ኮትኩታ በማሳደግ ሀገር ወዳድ ትውልድ በማፍራት መሠረት የጣለች፣ በውጭ ወራሪ ኃይል የሀገር ሉዓላዊነት በተደፈረ ወቅት የእምነቱ ተከታይ ምእመናኖቿና አገልጋይ ካህናቶቿ እንዲሁም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የእምነታችን መገለጫ የሆነውን የቃልኪዳኑን ታቦት ይዘው በየጦር ግንባሩ በመሰለፍና በመሰዋት እንኳንስ ሕዝቦቿ ምድሪቱም ለወራሪ ጠላት እንዳትገዛ በማውገዝ የሀገር ሉዓላዊነት ያስከበረችና ኢትዮጵያ ሀገራችን ከሌሎች አፍሪካ አገራት በብቸኝነት ቅኝ ገዥዎች ያልደፈሯት አገር ተብላ በታሪክ ድርሳናት እንድትመዘገብ ግንባር ቀደም ሚና የተጫወተች የሀገር ባለውለታ እናት ቤተ ክርስቲያን መሆኗን እንኳንስ እኛ ልጆቿ ይቅርና የታሪክ ምሁራን ዘወትር በየአደባባዩ የሚመሰክሩት በብዕር ሳይሆን ለነጻነት በተከፈለ በአበው አባቶቻችን ደም የተጻፈ አኲሪ ታሪካችን ነው።

    እናት ቤተ ክርስቲያን ከላይ በአጭሩ የተጠቀሱትን ዘመናት የማይሽሩት ታሪካዊ ውለታዎችን ለሀገር ያበረከተች ቤተ ክርስቲያን ብትሆንም አንዳንድ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና የጥፋት ኃይሎች በተለያዩ ጊዜያት በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የሚፈጽሙት ከፍተኛ የሆነ አስተዳደራዊ በደልና የተቀናጀ ጥቃት እያደረሰብን ያለውን መከራና ችግር ቤተ ክርስቲያናችን ባላት ሀገራዊ ኃላፊነት ችግሩን በትዕግስት አሳለፈችው እንጂ እየተፈጸመባት ካለው ግፍና በደል አንጻር ይከሰት የነበረው ችግርና ሀገራዊ ቀውስ በቀለሉ የሚታለፍ ባልሆነም ነበር።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ እየደረሰብን ያለውን በደልና መከራ ከዛሬ ነገ ይሻላል በማለት ታግሰን ብንችለውም እያደር እየባሰና የችግሩም አድማስ እየሰፋ ሊሄድ ችሏል። ምንም እንኳን በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ እየደረሰ ያለው በደል ዘመናትን ያስቆጠረ ቢሆንም ቅሉበተለይ በአሁኑ ወቅት መልኩን እየቀያየረ እና ለዘመናት የቆየ አንድነቷን በማፈራረስ ከቤተ ክርስቲያኒቱም አልፎ ሀገራዊ ቀውስና አለመረጋጋት የሚያስከትል የጥፋት አጀንዳን ባነገቡ ግለሰቦች በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም የጀመሩት እንቅስቃሴ ወደከፋ ደረጃ ከመድረሱ በፊት የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ እና የመጨረሻ ውሳኔ ሰጭ አካል የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ በጉዳዩ ላይ አስቸኳይ ስብሰባ በማድረግ በስፋት ከተወያየ የሚከተለውንየአቋም መግለጫ አውጥቷል፡-

    1. አንዳንድ የመንግሥት ባለሥልጣናት እና ሥራ ኃላፊዎች ሥልጣናቸውን መከታ በማድረግ እና ለጥፋት ለተደራጁ ቡድኖች ፖለቲካዊ ሽፋን በመስጠት በልዩ ልዩ ክልሎች የተፈጸሙት የአብያተ ክርስቲያናት መቃጠል፣ የአገልጋይ ካህናት እና ምእመናን መገደል፣ ዘመን የማይተካቸው የሀገር መገለጫ የሆኑትን ጥንታውያን እና ታሪካውያን ቅርሶችን በማቃጠል ሀገሪቱ እና ሕዝቦቿን ታሪክ እና ቅርስ አልባ በማድረግ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ እየተፈጸሙ ያሉትን በደሎች እና ግፎች ቅዱስ ሲኖዶስ በጽኑ ያወግዛል።
    2. ቤተ ክርስቲያኒቱ ባህል፣ ቀለም፣ ቋንቋ እና ብሔር ሳትለይ በአንድነት እና በአቃፊነት ለሀገር ውለታ ያበረከተች መሆኗ ተዘንግቶ በእምነት ሽፋን የቤተ ክርስቲያኒቱ አማኞች የሆኑ ምእመናን ካደጉበትና ሀብት እና ንብረት ካፈሩበት ቀያቸው እንዲፈናቀሉ መደረጉ፣ በእምነታቸው ብቻ ተገደው በመደፈር እና ልዩ ልዩ የሥነ ልቦና ጥቃት እንዲደርስባቸው በማድረግ እንዲሁም በድብደባ እና በዛቻ ሃይማኖታቸውን እንዲቀይሩ እየተደረገ ያለውን ሕገ ወጥ አድራጎትን ቅዱስ ሲኖዶስ በጽኑ ያወግዛል።
    3. ለባለውለታዋ እናት ቤተ ክርስቲያን በማይመጥን እና ኢፍትሐዊ በሆነ መንገድ ሕጋዊ ይዞታዋን እና የአምልኮት ቦታዎቿን በመንጠቅ መንግሥታዊ ሥልጣናቸውን እንደ ሽፋን በመጠቀም በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ በደል እና ግፍ የሚፈጽሙ አንዳንድ የመንግሥት ባለሥልጣናት እና ሥራ ኃላፊዎችን ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ አድራጎታቸው እንዲታቀቡ በጥብቅ ያሳስባል።
    4. እየደረሰ ያለውን ግፍ እና መከራ በሀገራዊ የሀላፊነት ስሜት ታግሶ እና ችሎ ሞቱ፣ እሥራቱ፣ ዛቻው፣ ስደቱ እና እንግልቱ ሳይበግረው ሀገር በአንድነት እና በፍቅር እንዲሁም በመተሳሰብ እንድትቀጥል ታሪክ የማይረሳው መስዋዕትነት እየከፈሉ ያሉትን አገልጋይ ካህናት እና መላውን ምእመናንን እንዲሁም ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት በአጠቃላይ መላው የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ላሳያችሁት ትዕግስት የተመላበት ሀገራዊ ሀላፊነት ቅዱስ ሲኖዶስ በእጅጉ እያመሰገነ እንደአሁን ቀደሙ ሁሉ ትዕግስት የተመለበትን ሀገራዊ ኃላፊነታችሁ እንደተጠበቀ ሆኖ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ እየደረሰ ያለውን እና ወደፊትም ሊደርስ የታቀደውን ግፍ እና ጥፋት በአንድነት እና በኅብረት ከእኛ ከመንፈስ ቅዱስ አባቶቻችሁ ጋር በመሰለፍ በጽናት ቤተ ክርስቲያናችሁን እንድትጠብቁ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ጥሪውን ያስተላልፋል።
    5. በቤተ ክርስቲያናች እምነት እና ቀኖና መሠረት በእምነታቸው ምክንያት በሰይፍ የታረዱ፣ በጥይት የተገደሉት፣ በእሳት የተቃጠሉ፣ ሕይወታቸውን ስለ ቤተ ክርስቲያናቸው የሰጡ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ በሰማእትነት ክብር እና ማዕረግ ዘወትር እንዲታሰቡ ቅዱስ ሲኖዶስ የወሰነ ሲሆን በሰማእትነት ሕይወታቸውንየሰጡ አገልጋዮች እና ምእመናን ቤተሰቦች ማኅበራዊ እና መንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዳይናጋ በተቻለ አቅም ድጋፍ እና እንክብካቤ በማድረግ ሁላችንም ከጎናቸው በመሆን የድርሻችንን እንወጣ ዘንድ ለመላው ኢትዮጵያውያን እና የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ቅዱስ ሲኖዶስ ጽኑ መንፈሳዊ ጥሪውን ያስተላልፋል።
    6. እናት ቤተ ክርስቲያችን በእንግዳ ተቀባይነቷ እና በአቃፊነቷ ዛሬ ለቁጥር አዳጋች የሆኑት ቤተ እምነቶች ሕገ መንግሥታዊ መብታቸው ተከብሮ ሰላማዊ፣ የማምለክ መብታቸው እንዲረጋገጥ የበኩሏን ድርሻ የተወጣች መሆኗን ሁሉም ቤተ እምነቶች በየአደባባዩ የሚመሰክሩት እውነታ እንደመሆኑ መጠን በእናት ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያናችን ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍ እና መከራ ሁሉም ቤተ እምነቶች በአንድነት እና በተባበረ ድምጽ በጽናት እንዲያወግዙ እና ለእምነት ተከታዮቻቸውም የቤተ ክርስያናችን ጥፋት እና በደል እንዲወገድ የበኩለቸውን ሚና እንዲወጡ መንፈሳዊ ጥሪያቸውን እንዲያስተላልፉልን በቅድስተ ቤተ ክርስቲያናችን ስም የከበረ ጥሪያችንን እናስተላልፋለልን።
    7. የፍትሕ አካላት ለምሥረታችሁ እና ለእድገታችሁ ውለታ የከፈለችውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የቀደመ ውለታዋን ከግምት ውስጥ በማስገባት ሕግ ተጥሶ እና ፍትሕ ተጓድሎ በቤተ ክርስቲያነቱ ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍ እና በደል በጽናት ከማውገዝ በተጨማሪ አጥፊዎችን ለፍትሕ በማቅረብ እና ተመጣጣኝ እና ለሌሎችም አስተማሪ የሆነ ውሳኔ በመስጠት እና በማሰጠት የራስዋየሆነ ተቋማዊ ሕልውና እና መዋቅር ያላት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ሕጋዊ መብት እና ልእልና መከበር የበኩላችሁን ድርሻ ትወጡ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥብቅ ጥሪ ያስተላልፋል።
    8. በሀገሪቱ ሕገ መንግሥት የተከበረውን እና የተረጋገጠውን የእምነት ተቋማት ነፃነት እና ሉዓላዊ ክብር በሚጋፋ ሁኔታ እየተፈጸሙ ያሉት የመብት ጥሰቶች እና የጥፋት በደሎችን የማረም እና ከመፈጸማቸውም በፊት የመከላከል ኃላፊነት ያለባችሁ በየደረጃው የምትገኙ የመንግሥት አካላት በሕገ መንግሥቱ የተጣለባችሁን ሕግን የማስከበር አደራና ኃላፊነት፣ በሀገሪቱ ውስጥ ያሉ ሀገራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት መብት የማስጠበቅ ሀገራዊ ኃላፊነት በመወጣት የቤተ ክርስያኒቱን ልዕልና እና ክብር እንድታስጠብቁ በቅድስት ቤተ ክርስያናችን ስም ቅዱስ ሲኖዶስ አደራውን ጥሎባችኋል በማለት በጽኑ ያሳስባል፤
    9. አንድነትን፣ መተሳሰብን፣ መከባበርን፣ ሰላም እና ፍቅርን በመስበክ እና በተግባር በመፈጸም ለሀገር እና ለመላው ዓለም አርኣያ የሆነችውን እናት ቤተ ክርስቲያን ያለ ስሟ ስም፣ ያለግብረዋ ግብር በመስጠት በተለይም የተከበረውን እና የቤተ ክርስቲያኒቱን ባለውለታ የሆነውን የኦሮሞን ሕዝብ ቤተ ክርስቲያናችን እንዳገለልችው እና አቅዳ እንደበደለቸው ለማስመሰል እና ለማስቆጠር አቅደው ቤተ ክርስያኒቱን እና ሀገርን ለመከፋፈል ድብቅ አጀንዳ ይዘው በተነሡ ግለሰቦች እና ቡድኖች አለአግባብ እየተሠራጨ ያለው አፍራሽ እና ከፋፋይ ድርጊት የቤተ ክርስቲያኒቱ አቋም እና ድምጽ ካለመሆኑ በተጨማሪ ትክክለኛው የቤተ ክርስቲያኒቱ ታሪክ እንደሚያስረዳን ሕገ ወጦቹ ግለሰቦቹ እና ቡድኖች የተከበረው የኦሮሞ ሕዝብ የሚያገለግለው እና የሚባርከው መንፈሳዊ አባት እንደሌለው ቢገልጹም እንኳንስ ለቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት ለሀገር አንድነት፣ ሉዓላዊነት እና ነፃነት ከተከበረው የኦሮሞ ሕዝብ አብራክ የተገኙት እና ነፍሳቸውን ሳይሳሱ በሰማዕትነት ዋጋ የከፈሉትን የሰማዕቱ ቅዱስ አቡነ ጴጥሮስን ታሪክ የማይረሳውን ውለታ የዘነጋ እና ቤተ ክርስቲያኒቱ በተለያዩ ጊዜያት በመዓርገ ጵጵስና ሹማ በክልሉ ባሉ አህጉረ ስብከት ለሐዋርያ አገልግሎት አሠማርታ መላውን የክልሉን ሕዝበ ክርስቲያን በማገልገል ከቤተ ክርስቲያኒቱ አልፎ ለክልሉ ሰላም እና አንድነት ዋጋ በመክፈል ላይ የሚገኙትን ከኦሮሞ ሕዝብ የተገኙትን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ሐዋርያዊ አገልግሎት እና በእነሱ የሚመሩ ከአጥቢያ እስከ ሀገረ ስብከት ያሉ በርካታ ጽ/ቤቶች ከዐሥራ አምስት የሚበልጡ በሊቃነ ጳጳሳት የሚመሩ የቤተ ክህነት ጽሕፈት ቤቶች እና መዋቅሮችን ፈጽሞ የካደ አድርጎት በመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ በጽኑ እያወገዘ በዚህ አድርጎት ውስጥ እየተሳተፉ ያሉትን ግለሰቦችን እና ቡድኖችን ከዚህ አድርጎታቸው እንዲቆጠቡ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥብቅ ያሳስባል።
    10. የተከበራችሁ እና የተወደዳችሁ የኦሮሞ ሕዝብ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን እናት ቤተ ክርስቲያናችሁ እንደ ትናንቱ ሁሉ ባህልን፣ ቀለምን፣ ቋንቋ እና ብሔርን መሠረት ሳታደርግ በተቻላት አቅም መንፈሳዊ እና ሐዋርያዊ አገልግሎቷን ተደራሽ ለማድረግ የጸሎት፣ የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ እና ሃይማኖታዊ የትምህርት መጻሕፍትን በኦሮምኛ ቋንቋ በመተርጎም እና በማዘጋጀት፣ ከአምስት በላይ የካህናት ማሠልጠኛ ተቋማትን፣ አንድ ከፍተኛ መንፈሳዊ ኮሌጅን በጀት መድባ በማቋቋም መላውን የኦሮሞ ብሔር ሕዝበ ክርስቲያን ስታገለገል የቆየችውን እና ያላቸውን ወደ ፊትም ዘመኑን በዋጀ መልኩ አጠናክራ የምታገለግለውን እናት ቤተ ክርስያናችሁ መሆኗን አውቃችሁ አንድነታችሁን እና ፍቅረ ቤተ ክርስቲያናችሁን ለመከፋፈል የተነሡትን የጥፋት ኃይሎች በጽናት በመቃወምና አንድነት እና ፍቅራችሁን አጠናክራችሁ ቤተ ክርስያናችሁን እና ሃይማኖታችሁን ከጥፋት ኃይሎች ትጠብቁ እና ትንከባከቡ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ያሳስባል።
    11. አዲስ የኦሮምያ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የሚል መዋቅር በራሳቸው ሥልጣን መሥርተው በመገናኛ ብዙኃን መግለጫ የሰጡት ግለሰቦች ቅዱስ ሲኖዶስ በአካል ቀርበው እንዲያስረዱ በሰጣቸው እድል ቀርበው የተወያዩ ሲሆን በውይይቱም ወቅት ጥያቄውን አስመልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ከአሁን ቀደም በኮሚቴ ተጠንቶ እንዲቀርብ ውሳኔ ሰጥቶበት እያለ ለጉዳዩ ትኩረት እንዳልሰጠው በማስመሰል ከቅዱስ ሲኖዶስ እውቅናና ፈቃድ ውጭ አዲስ መዋቅር ፈጥረው መግለጫ መስጠታቸው አግባብ አለመሆኑን አምነው ይቅርታ ለመጠየቅ ከሌሎች የኮሚቴ አባላት ጋር ተወያይተን እንመለስ ብለው ባቀረቡት ጥያቄ መሠረት ለጳጉሜን 2 ቀን 2011 ዓ.ም. ከጠዋቱ 2፡30 የተቀጠሩ ቢሆንም በዕለቱ የኮሚቴው ዋና ተጠሪ ሊቀ አዕላፍ ቀሲስ በላይ መኰንን ያልተገኙ ሲሆን 2 የኮሚቴው አባላት ብቻ ከተሰጣቸው ሰዓት አሳልፈው ከመምጣታቸውን በላይ 2ቱ ግለሰቦች በጽሑፍ ባቀረቡት ምላሽ በሕገወጥ አቋማቸው የፀኑ መሆናቸውን የገለጹ በመሆኑ የግለሰቦቹ እንቅስቃሴም ሆነ የኦሮሞ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ተብሎ የተጠቀሰው አደረጃጀት ሕጋዊ እውቅና የሌለው መሆኑን ሁላችሁም የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን አውቃችሁ የግለሰቦቹን ሕገወጥ እንቅስቃሴ በመቃወምና በቀደመው አንድነታችሁ ጸንታችሁ ቤተ ክርስቲያናችሁንና ሃይማኖታችሁን ትጠብቁ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ያስተላልፋል።
    12. ከዚህ በላይ በተገለጸው መሠረት ምንም ዓይነት ሕጋዊ ውክልናም ሆነ ከሕገ የመነጨ ሥልጣን ሳይኖራቸውና የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከሕግ የመነጨ መብት በመጋፋት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሎጎ /አርማ/፣ ማህተምና መጠሪያ ስያሜ መጠቀማቸው ሕገወጥ አድራጎት በመሆኑ የሚመለከታችሁ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ግለሰቦቹ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሎጎ /አርማ/ እና ማህተም እንዲሁም መጠሪያ ስያሜ መጠቀም የማይችሉ መሆኑ ታውቆ አስፈላጊውን አስተዳደራዊ እርምት በመስጠት የቤተ ክርስቲያኒቱን መብትና ጥቅም ታስከብሩ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት እያሳሰበ፤ የጽ/ቤታችን የሕግ አገልግሎት መምሪያም በሕገወጦች ግለሰቦች ላይ ክስ በመመስረት የቤተ ክርስቲያኒቱን መብትና ጥቅም ያስከብር ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥብቅ አዟል።

    ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ በላይ በዝርዝር በተገለጹት የአቋም መግለጫዎችና በሌሎችም ዓበይት ጉዳዮች ላይ በመወያየትና ተገቢውን ውሳኔ በመስጠት ስብሰባውን በጸሎት አጠናቋል።

    እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ
    ጳጉሜን 2 ቀን 2011 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ
    ኢትዮጵያ

    (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ)

    ቅዱስ ሲኖዶስ


    Semonegna
    Keymaster

    በለውጡ ሂደት እያጋጠሙ ያሉ ፈተናዎች ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ ጋር በተደረገው ውይይት ላይ የተነሱ ሲሆን፥ በአንዳንድ አካላት እየተፈጸሙ ያሉ ጥፋቶችን በማንሳት ቅዱስ ሲኖዶስ ለጠቅላይ ሚኒስትር አቅርበዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጋር ጳጉሜን 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ጠዋት በቢሯቸው ተወያይተዋል። የቤተ ክርስቲያኒቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ባቀረበው ጥያቄ መሠረት በተደረገው ውይይት ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከለውጡ ወዲህ መንግሥት ቤተ ክርስቲያንን በተመለከተ ያለውን አቋምና ያከናወናቸውን ተግባራት አውስተዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ እና ሌሎችም ሊቃነ ጳጳሳት ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ሥልጣን ከመጡ ወዲህ ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን የተከናወኑ በጎ ተግባራትን በመዘርዘር ምስጋና አቅርበዋል።

    በለውጡ ሂደት እያጋጠሙ ያሉ ፈተናዎች በውይይቱ የተነሡ ሲሆን፥ በአንዳንድ አካላት እየተፈጸሙ ያሉ ጥፋቶችን በማንሳት ጳጳሳቱ ለጠቅላይ ሚኒስትር አቅርበዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩም የእርሳቸውም ሆነ የመንግሥታቸው ፍላጎት የተጠናከረች፣ ለሀገር ግንባታ የሚቻላትን ሁሉ የምታደርግና አንድነቷ የተጠበቀ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ማየት መሆኑን ገልጠዋል። የኢትዮጵያ የእምነት ተቋማት መጠናከርና አንድ መሆን ጥቅሙ ለእምነት ተቋማቱ ብቻ ሳይሆን ለሀገር ጭምር መሆኑንም ተናግረዋል።

    የቀረቡት ችግሮች በለውጥ ውስጥ ካጋጠሙት ተግዳሮቶች መካከል መሆናቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ያነሱ ሲሆን ዓይነታቸው ቢለያይም የተለያዩ የእምነት ተቋማት በለውጡ ሂደት ፈተና አጋጥመዋቸዋል፣ በመሆኑም ዕንቅፋት የሚፈጥሩትን አካላት መታገል ያለብን በጋራ ነው ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ። የቀረቡትን ችግሮች በዝርዝር በማጥናትና በየደረጃው ካሉ አመራሮች ጋር በመነጋገር በጋራ እንደሚፈቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምላሽ ሰጥተዋል። በሀገር ላይ የሚደርሱ ጥፋቶች በሁሉም ላይ የሚደርሱ በመሆናቸው መንግሥትና የእምነት ተቋማት በጋራ በመሥራት መፍታት እንዳለባቸው ገልጠዋል።

    በመጨረሻም የተፈጠሩትን ችግሮች የጋራ በማድረግ የቤተ ክርስቲያኒቱን አንድነትና ክብር በጠበቀ መልኩ በጋራ ለመፍታት ከስምምነት ላይ ተደርሷል።

    ምንጭ፦ የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስት ቢሮ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    —–
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ቅዱስ ሲኖዶስ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)–በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት ኅዳር 27 ቀን 2011 ዓ.ም. የዩኒቨርሲቲው የበላይ ኃላፊ ዶ/ር ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት፣ የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ እንዲሁም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ከባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ ከጀርመን፣ ከፈረንሳይና ከጣልያን የባህል ማዕከላትና ሌሎችም ጥሪ የተደረገላቸው ልዩ ልዩ እንግዶች በተገኙበት በይፋ ተመርቆ ተከፍቷል።

    በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት ረዳት ዳይሬክተር መ/ር ተመስገን ዮሐንስ ሙሉ ፕሮግራሙን የመሩት ሲሆን የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ካፈራቸው ምሁራን አንዱ ናቸው።

    በመርሐ ግብሩ መሠረት የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት በይፋ መጀመሩን ያበሰሩት የዩኒቨርሲቲው የበላይ ኃላፊ ዶ/ር ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ሲሆኑ በመግቢያ ንግግራቸው ላይ ኮሌጁ በመማር ማስተማሩ ሂደት ዛሬ ላይ ለመድረስ የነበሩትን ብዙ ውጣ ውረዶችን አልፎ ለዩኒቨርሲቲ ደረጃ መድረሱ እግዚአብሔርን ካመሰገኑ በኋላ ዩኒቨርሲቲው አሁን የደረሰበትን ደረጃ እንዲደርስ ሌት ተቀን የሠሩት የቤተ ክርስቲያኒቱ የሥራ ኃላፊዎች ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስን፣ ብፁዓን ሊቃነጳጳሳት፣ የቦርድ የሥራ አመራር አባላትና የዩኒቨርሲቲውን ማኅበረሰብ ከፍ ያለ ምስጋና አቅርበዋል።

    ከብፁዕነታቸው በመቀጠል ንግግር ያደረጉት በዩኒቨርሲቲው የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት ዳይሬክተር ተባባሪ ፕሮፌሰር ኃይሉ ሀብቱ ናቸው።ተባባሪ ፕሮፌሰ ርኃይሉ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ከሚገኙ አምስት ኮሌጆችና ት/ቤቶች ውስጥ አንዱ መሆኑን ገልፀው፥ ትምህርት ቤቱ ከጥቅምት 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በማስተርስ ኦፍ አርትስ (M.A.) ዲግሪ ደረጃ የድኅረ ምረቃ ትምህርት መስጠት መጀመሩን ተናግረዋል። ፕሮግራሙን ለማጠናቀቅ የሚወስደው ጊዜ ሁለት ዓመት መሆኑንና የአንደኛው ዓመት መርሐ ግብር ለተማሪዎች፦ (1) በኢትዮጵያ ታሪክ፣ (2) በኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ፣ (3) በብሔረሰቦች ወግና ሥርዓት ሰፊጥናትና ጥልቅ ግንዛቤ የሚሰጥ ሲሆን በሁለተኛው መርሃ ግብርም፦ (1) በትውፊታዊ ሥነ መድኃኒት/ ሥነ ፈውስ፣ (2) በትውፊታዊ ሥርዓተ ሕግ፣ (3) በኢትዮጵያ ጥናት አውራ ርዕሰ ጉዳዮች የሚያተኩሩ እንደሆኑ አብራርተዋል። የማስተማሪያ መደበኛ ቋንቋ እንግሊዝኛ ቢሆንም አገርኛ ቋንቋዎች ግዕዝን ጨምሮ እንደ አማራጭ ማስተማሪያ ሆነው ሊያገለግሉ እንደሚችሉ ተናግረዋል።

    የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ባህልና ነፃነት ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ነው። ለአብነት ያህል በ17ኛው እና 20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበሩ እንደነ ወለተ ጴጥሮስ፣ አቡነ ጴጥሮስና አቡነ ማካኤልን የመሳሰሉ አባቶችና እናቶች ለኢትዮጵያ ሉአላዊነት ሰማዕት ሆነዋል ብለዋል።

    ከዚህ በመቀጠል የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የሥራ አመራር ቦርድ አባል የሆኑት ዶ/ር የራስወርቅ አድማሴ ንግግር አድርገዋል። ከተለያዩ የመንግሥትና መንግሥታዊያ ልሆኑ የትምህርት ተቅዋማትና ድርጅቶች የመጡትን እንግዶች እንኳን ደህና መጣችሁ በማለት ከልብ አመስግነዋል። በቀጣይም ዩኒቨርሲቲው በትምህርት ጥራት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ ተናግረዋል።

    በመቀጠልም በፕሮግራሙ መክፈቻ መርሐ ግብር ላይ የተገኙ እንግዶች ለዩኒቨርሲቲው ግብዓት ሊሆኑ የሚችሉ ሀሳቦችና አስተያየቶች የሰጡ ሲሆን ከቅድስት በዓታ ለማርያም ቤተክርስቲያን የመጡ መምህር በዓሉን የሚገልጽ ቅኔ አቅርበዋል።

    በመጨረሻም በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት በብራና መጻሕፍት ዝግጅት ክፍል የሚዘጋጁትን የተለያዩ የብራና መጻሕፍት፣ ቀለምና የብራና መሣሪያዎችን በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙ እንግዶች ጐብኝተዋል።

    የቀድሞ ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በ1935 ዓ.ም. ለመጀመርያ ጊዜ ካህናትንና የቤተክርስቲያን ሊቃውንትን ዘመናዊውንና የአብነት ትምህርታቸውን አስተባብረው እንዲይዙ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድጋፍ እንደተጀመረ የታሪክ ድርሳናት ያስረዳሉ። ኮሌጁ በዚህ ደረጃ ለመጀመርያ ጊዜ የመጀመርያ ደረጃ ትምህርት ቤት ሆኖ ያገለገለ ሲሆን፥ በመቀጠልም በከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ማዕረግ በማስተማር ወደ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የሚገቡ ዕጩዎችን ሲያበቃ ቆይቷል። የኮሌጅን ደረጃ በ1960 ዓ.ም. ካገኘ በኋላ ከሦስት ዓመት በኋላ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የቲኦሎጂ ፋኩልቲ አካል ሆኖ እስከ 1966 ዓ.ም. ድረስ ዘልቋል። የመንግሥት ለውጥን ተከትሎ ፋኩልቲው ሲዘጋ በወቅቱ በትምህርት ገበታ ላይ የነበሩት በሚፈልጉት የትምህርት መስክ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተዛውረው ትምህርታቸውን እንዲያጠናቅቁ መደረጉ ይታወሳል። መንፈሳዊ ኮሌጁ ተወርሶ አራት ኪሎ ከጎኑ የሚገኘው የሳይንስ ፋኩልቲ ለራሱ የትምህርት መርሐ ግብር እንዲጠቀምበት ተደረገ። በ1987 ዓ.ም. ጀምሮ ኮሌጁ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተመልሶ በነበረው ዕውቅናና ደረጃ የመማር ማስተማሩን ሒደት ሲያከናውን ቆይቷል። ኮሌጁ ከመማር ማስተማሩ ጎን ለጎን ከፍተኛ የሆኑ የልማት ሥራዎችን ሲሠራ ቆይቷል።

    መንፈሳዊ ኮሌጁ እስከ አሁን ድረስ ከ3,500 በላይ ተማሪዎችን አሰልጥኖ ያስመረቀ ሲሆን ከዚሁ በበለጠ መልኩ እንዲጠናከርና የቤተክርስቲያኒቱ የጥናትና የምርምር ተቅዋም እንዲሆን መሉ ዝግጁቱን አጠናቅቆ በመጨረሱ በአሁኑ ሰዓት በቲዮሎጂ (ስነ መለኮት) የትምህርት ዘርፍ በዶክትሬት፣ በማስተርስ ዲግሪ፤ በመደበኛ የመጀመሪያ ዲግሪ፤ በማታው ተከታታይ እና በርቀት ትምህርት መርሃ ግብር የመጀመሪያ ዲግሪ፤ ዲፕሎማ፤ በግእዝቋንቋ (extension) ዲግሪና ዲፕሎማ ተማሪዎችን ተቀብሎ በማስተማር ላይ ይገኛል።

    ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ከብዙ ድካምና ጥረት በኋላ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት መልካም ፈቃድ ወደ ከፍተኛ ዩኒቨርሲቲ ደረጃ እንዲያድግ ተደርጓል። በዚሁም መሠረት ከኅዳር 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ተብሎ እንዲጠራ መወሰኑ ይታወሳል።

    ምንጭ፦ ዩኒቨርሲቲው / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ


    Semonegna
    Keymaster

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ የሚጀምረው የግዕዝ ቋንቋ ትምህርት በቋንቋው የተጻፉ ሥራዎችን ወደ ሌሎች አገርኛ ቋንቋዎች በመተርጎም ጥቅም ላይ ለማዋል እንደሚያስችል በዩኒቨርሲቲው የማኅበራዊና ሥነ ሰብእ ኮሌጅ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ጽሁፍ ትምህርት ክፍል ተጠሪ ተናግረዋል።

    ደሴ (ኢዜአ) – የወሎ ዩኒቨርሲቲ ከያዝነው የትምህርት ዘመን ጀምሮ የግዕዝ ቋንቋን በመጀመሪያ ዲግሪ ለማስተማር ዝግጅቱን ማጠናቀቁን አስታወቀ።

    ዩኒቨርሲቲው ትምህርቱን ለመጀመር በቀረጸው ሥርዓተ ትምህርት (curriculum) ዙሪያ ከምሁራንና ባለድርሻ አካላት ጋር መስከረም 29 ቀን 2011 ዓ.ም ተወያይቷል።

    በዩኒቨርሲቲው የማኅበራዊና ሥነ ሰብእ ኮሌጅ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ጽሁፍ ትምህርት ክፍል ተጠሪ ዶክተር እንድሪስ አብይ እንዳስረዱት ግዕዝ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የላቀ ሥፍራ አለው።

    ትምህርቱን ለማስጀመር አራት መምህራን የተቀጠሩ ሲሆን፣ እስከ 18 ተማሪዎችን ለመቀበል ዝግጅት ማድረጉን ገልጸዋል።

    ሥርዓተ ትምህርቱ ጋዜጠኝነትን ጨምሮ አገር በቀል ህክምናና መድኃኒት፣ የሥነ ከዋክብት ቀመርና የቀን አቆጣጠር፣ የባህልና የህግ ሥርዓቶች ተካተውበታል።

    ትምህርቱ በቋንቋው የተጻፉ ሥራዎችን ወደ ሌሎች አገርኛ ቋንቋዎች በመተርጎም ጥቅም ላይ ለማዋል እንደሚያስችል ዶክተር እንድሪስ ተናግረዋል።

    በቋንቋው በፍልስፍና፣ በህክምና፣ በሥነ ከዋክብትና በመሳሰሉት የዕውቀት ዘርፎች በርካታ ጽሁፎች ቢጻፉም፤ ህዝቡንም ሆነ አገሪቱን መጠቀም የሚገባቸውን ያህል አልተጠቀሙበትም። ዕውቀቱም ለሌሎች ሳይተላለፍ ለረጅም ዓመታት መቆየቱን ተጠሪው ገልጸዋል።

    በዩኒቨርሲቲው የታሪክና ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ትምህርት ክፍል አስተባባሪና መምህር አቶ ዘላለም ጌትነት በበኩላቸው የመጥፋት አደጋ ላይ የሚገኘውንና የዕውቀት ምንጭ የሆነውን ቋንቋ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ መስጠቱ ታሪክን ከማቆየትና እውቀትን ከማጋራት አንጻር ጠቀሜታው ጉልህ ነው ብለዋል።

    ሥርዓተ ትምህርቱ በተለይ ቋንቋው ከኢትዮጵያ ታሪክ ጋር ያለውን ቁርኝት በሚያሳይ መልኩ ቢቀረጽ የተሻለ እንደሚሆን አመልክተዋል።

    በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቲያትር ጥበባት ትምህርት ክፍል መምህርና የሥነ ጥበባት ኮሌጅ የድህረ ምረቃ ተባባሪ ዲን ረዳት ፕሮፌሰር አሰፋ ወርቁ ”ዩኒቨርሲቲው የአገር ሃብት የሆነውን የግዕዝ ቋንቋ ለማስተማር መወሰኑ የሚያስመሰግነውና ሌሎችም ዩኒቨርሲቲዎች ተመሳሳይ ኃላፊነት እንዲወስዱ መነቃቃትን የሚፈጥርላቸው ነው” ብለዋል።

    ግዕዝ ኢትዮጵያን የምናውቅበት የዕውቀት ምንጭ መሆኑን አስታውሰው፣ ይህንን መገናኛ ብዙኃን አገራዊ ፋይዳ ያለውን የዕውቀት ዘርፍ በማስተዋወቅ ድርሻቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።

    የወሎ ዩንቨርሲቲም ተማሪዎችን ካስመረቀ በኋላ የሥራ ዕድል እንዲያገኙ ከባለድርሻ አካላት ጋር መምከር እንዳለበትም አቶ አሰፋ አሳስበዋል።

    በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የደቡብ ወሎ አገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ መአምራን ብርሃነሕይወት እውነቱ ቋንቋው በዩኒቨርሲቲው መሰጠቱ በርካታ አገራዊ ታሪኮች፣ ቅርሶች፣ መንፈሳዊና ዓለማዊ ሥራዎች፣ ምርምርን የሚጋብዙ ሥራዎች ለማወቅና ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በአዲስ መንፈስ ለማስቀጠል ጠቀሜታ እንዳለው አስረድተዋል።
    የአብነት ተማሪዎች እንቅስቃሴ መዳከም ቋንቋውን እንዳዳከመው አውስተው፣ የወሎ ዩንቨርሲቲ የጀመረው ጥረት እንዲሳካ ቤተክርስቲያኗ ድርሻዋን ለመወጣት ዝግጁ መሆኗን አስታውቀዋል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ በ1999 ዓ.ም. የተመሠረተው የወሎ ዩኒቨርሲቲ ዓመታዊ የቅበላ አቅም ዘንድሮ ከ20 ሺህ በላይ ደርሷል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ

Viewing 12 results - 1 through 12 (of 12 total)