Search Results for 'ወሎ ዩኒቨርሲቲ'

Home Forums Search Search Results for 'ወሎ ዩኒቨርሲቲ'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 22 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ለብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የክብር ዶክትሬት ሽልማታቸውን አስረከበ

    ባሕር ዳር – የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ባሳለፍነው ነሐሴ 21 ቀን፥ 2014 ዓ.ም የተማሪዎችን ምርቃ ሥነ-ሥርዓት ላይ ለሀገራችን ኢትዮጵያ በማኅበረሰብ አገልግሎት ጉልህ አስተዋፅዖ ላበረከቱት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን (የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ) የሰሜን ወሎ እና በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የኦሮሚያ ልዩ ዞን ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ለሆኑት ለብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የክብር ዶክትሬት ሽልማት ለተወካያቸው መስጠቱ ይታወሳል። ሆኖም ግን ብፁዕ አባታችን በአሁኑ ሰዓት የሐዋርያዊ ተልዕኮአቸውን ጨርሰው በመመለሳቸው መስከረም14 ቀን፥ 2015 ዓ.ም በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጥበብ ሕንፃ ተገኝተው የክብር ዶክትሬት ሽልማታቸውን ተቀብለዋል።

    የሽልማት አሰጣጥ ሥነ-ሥርዓቱ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ፣ የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባል እና የዕለቱ የክብር እንግዳ በሆኑት በብፁዕ አቡነ አብርሃም ፀሎትና ቡራኬ ተጀምሯል።

    የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት ዶክተር ፍሬው ተገኘ በሽልማት አሰጣጥ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንዳሉት በጭንቅ እና በመከራ ወቅት ሀይማኖትና ዘር ሳይለዩ የከበረ ሥራን ሠርተው የከበሩትን ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ በማክበራችን እኛም ብዙ አትርፈናል ሲሉ ተናግረዋል። በወቅቱ አቅም ያላቸው በርካታ ነዋሪዎች ከአካባቢያቸው በሚሸሹበት ወቅት በጦርነት፣ በችግር እና መከራ ውስጥ ወደ ሚገኘው ሕዝባቸው ጋር በመሄድ የመከራው ቀንበር እንዳይሰማቸው ከሕዝቡ ጋር በመሆን የመጣውን ክፉ ቀን እንዲያልፍ በማድረጋቸው ታሪክ የማይረሳው ሥራን ሠርተዋል ሲሉ ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል።

    የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፥ እንዲሁም ዕለቱ የክብር እንግዳ የሆኑት ብፁዕ አቡነ አብርሃም በበኩላቸው የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሀይማኖት፣ ዘር እና ቀለም ሳይለይ በሥራቸው ብቻ መዝኖ ለብፁዕ አቡነ ኤርሚያስ የክብር ዶክትሬት በመስጠቱ በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ስም ምስጋና አቅርበዋል። ብፁዕ አቡነ ኤርሚያስ በዚያ ሽብር እና ጭንቅ በነገሰበት ወቅት ክርስቲያን፣ ሙስሊም፣ አማኝ እና ኢ-አማኝ ሳይሉ ሁሉንም የሰው ዘር በእኩል ዓይን በማየት የመከራውን ቀን ከሕዝባቸው ጋር ያሳለፉትን ድንቅ አባት የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክትሬት ዕውቅና ሽልማት በመስጠቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መደሰቷን ተናግረዋል።

    አቡነ ኤርምያስ በበኩላቸው የተሰጠኝ የክብር ዶክትሬት ለእኔ ሳይሆን በሁለቱም ወገን በጦርነቱ ወቅት ቆስለው በየጫካው የወደቁ ወገኖችን ቁስል በማጠብ እና ከልጆቻቸው ጉሮሮ ቀንሰው ለቁስለኞች በማብላት ትልቅ ፍቅር ላሳዩን እናቶች እና በጸሎት ሲጠብቁኝ ለነበሩት ለብጹዕ አቡነ ቄርሎስ፣ ከጎኔ ሆነው በምክር ለረዱኝ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ለሀዋርያዊ ተልዕኮ ዘወትር ለሚፋጠኑት ካህናት፣ ዲያቆናት፣ ከሙስሊሙ ማኅበረሰብ ጋር ድልድይ ሆነው ላገናኙኝ የመስጊድ ኮሚቴ አባላት፣ ሰብዓዊ ግዴታቸውን ለተወጡ አባቶቻችን እና እናቶቻችን ነው ሲሉ ተናግረዋል።

    በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የሰሜን ወሎ የባህር ዳር ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፣ የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት የአድባራት እና ገዳማት አስተዳዳሪዎች እንዲሁም የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ም/ፕሬዚዳንቶች መምህራን እና ሠራተኞች በተገኙበት በደማቅ ሁኔታ ተካሂዷል።

    ምንጭ፦ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ

    አቡነ ኤርምያስ

    Semonegna
    Keymaster

    ሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ በተለያየ የትምህርት ዘርፎች ያስተማራቸውን 659 ተማሪዎችን አስመረቀ

    ሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች በቅድመ- እና ድኅረ- ምረቃ መርሀግብሮች ያሰለጠናቸውን 659 ተማሪዎችን ጳጉሜን 3 ቀን 2012 ዓ.ም አስመረቀ። ዩኒቨርሲቲው ለ12ኛ ዙር ለምረቃ ካበቃቸው ተማሪዎች መካከል 515 ወንዶች ሲሆኑ 144 ደግሞ ሴቶች ናቸው።

    ዩኒቨርሲቲው በእጽዋት ሳይንስ፣ በእንስሳት ሳይንስ፣ በተፈጥሮ ሀብት አጠባበቅ፣ በኢኮኖሚክስ፣ በሥራ አመራር (Management)፣ እንዲሁም በጂኦግራፊና አካባቢ-ነክ ጥናቶች (Environmental Studies) በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ አስተምሮ አስመርቋል።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ የሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አህመድ ሙስጠፋ እንደገለጹት፥ ዩኒቨርሲቲው ከተቋቋመበት ከ1999 ዓ.ም ጀምሮ የመማር ማስተማር፣ የምርምር እና የማኅበረሰብ አገልግሎት ሥራዎችን ተግባራዊ ሲያደርግ ቆይቷል። እንደ ዶ/ር አህመድ ገለጻ፥ ዩኒቨርሲቲው ከዚህ ቀደም ከ15 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በማስመረቅ ለውጤት አብቅቷል።

    እንደ ተጠባባቂ ፕሬዝደንቱ ገለጻ፥ ሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ በተያዘው ዓመት በ46 የመጀመሪያ ዲግሪና በ23 የሁለተኛኛ ዲግሪ ፕሮግራሞች ከ17ሺ በላይ ተማሪዎችን በማስተማር ላይ መሆኑን ገልጸዋል።

    በጥናትና ምርምር ሥራዎች በሀገር አቀፍ ደረጃ በተለያዩ ጭብጦች 18 የምርምር ንድፈ ሀሳቦች የቀረቡ ሲሆን፥ ከእነዚህ ውስጥ 15ቱ ወደ ሥራ እንዲገቡ ተደርጓል ብለዋል – ዶ/ር አህመድ። የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከልም ከ3 ሺህ ሊትር በላይ የንጽህና መጠበቂያ ፈሳሽ (ሳኒታይዘር) በማምረት አገልግሎት ላይ እንዲውል ተደርጓልሲሉ አስረድተዋል።

    የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ እና የዩኒቨርሲቲው ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ፍቅሬ አማን በክብር እንግድነት ተገኝተው ባስተላለት መልዕክት፥ እንዳሉት የዘንድሮው የምረቃ በዓል ለዓለማችን፣ ብሎም ለሀገራችን ህዝቦች የኮርና ቫይረስ ወረርሽኝ ፈታኝ በሆነበት በዚህ ወቅት ተመራቂዎች የጥናትና ምርምር ሥራዎችን በማጠናቀቅ ለውጤት በመብቃታቸው የተሰማቸውን ልባዊ ደስታ ገልጸዋል።

    ሀገራችን በመደመር ፍልስፍና ከነበረችበት ችግር ወጥታ ወደ ብልጽግና ጎዳና እየተጓዘች ባለችበት በዚህ የይቅርታና የምኅረት ወር በሆነችው በጳጉሜ ወር ተማሪዎች ለምረቃ በመብቃታቸው እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።

    ሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ የቀድሞውን ሚዛን ተፈሪ ግብርና ኮሌጅ መሠረት አድርጎ በደቡብ ክልል ሚዛን ተፈሪ እና ቴፒ ከተሞች በ1999 ዓ.ም የተቋቋመ ዩኒቨርሲቲ ነው።

    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    ሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive

    ድሬዳዋ፣ መዳ ወላቡ እና ሰመራ ዩኒቨርሲቲዎች ከ460 በላይ ተማሪዎችን አስመረቁ

    ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የሙያ መስኮች በድኅረ ምረቃና በቅድመ መደበኛ መርሃ ግብር ያሰለጠናቸውን 118 ተማሪዎች አስመረቀ። ከተመራቂዎች መካከል 56ቱ የድኅረ ምረቃ ተማሪዎች ሲሆኑ፥ 23 ተማሪዎች ደግሞ በጤና ሳይንስ ኮሌጅ የሰለጠኑ የሕክምና ዶክተሮች እንዲሁም በቴክኖሎጂ ኢኒስቲቲዩት 39 ተማሪዎች በኪነ ህንፃ በመጀመሪያ ዲግሪ ያሰለጠናቸው ናቸው።

    የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፈጡም ሙስጠፋ ተመራቂዎች ሃገራችን በኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝ ውስጥ ሆና የተመረቁ ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ በተለይም የሕክምና ተመራቂዎች የቫይረሱን ስርጭት ለመከላከል በተጀመረው ጥረት ውስጥ የድርሻቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።

    ሌሎችም በተመረቁበት ሙያ የሀገሪቱን እድገት በማረጋገጥ ረገድ የበኩላቸውን አስተዋፅኦ እንዲያበረክቱ ጥሪ አቅርበዋል።

    የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኡባህ አደም በበኩላቸው፥ ዩኒቨርሲቲው በምርምርና ማኅበረሰብ አገልግሎት በመሰማራት በ2012 በጀት ዓመት 38 የምርምር ሥራዎች ፀድቀው ወደ ሥራ መግባታቸውንና ሃያ ሰባቱ መጠናቀቃቸውን ተናግረዋል።

    ከዩኒቨርሲቲው ጋር በተያያዘ፥ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሙሉ ነጋ እና ሌሎች የሥራ ኃላፊዎች የድሬደዋ ዩኒቨርሲቲን የሥራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል።

    በጉብኝቱ የዩኒቨርሲቲው ሪፈራል ሆስፒታል ያለበትን የግንባታ ደረጃና የኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ በዩኒቨርስቲው እየተሠሩ ያሉ ሥራዎችንና የSTEM ማዕከሉን ጎብኝተዋል።

    ከተማሪዎች ምረቃ ዜና ሳንወጣ፥ መዳ ወላቡ እና ሰመራ ዩኒቨርሲቲዎች በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች ያሰለጠናቸውን 345 ተማሪዎች ነሐሴ 16 ቀን 2012 አስመርቀዋል።

    የመዳ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር አህመድ ከሊል በምረቃው ሥነ-ሥርዓት እንደተናገሩት፥ ተቋሙ በየዓመቱ በርካታ ተማሪዎችን አሰልጥኖ ቢያስመርቅም ዘንድሮ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ከፍተኛ ጫና አሳድሯል። ሆኖም እንደ “ኦንላይን” ያሉ የተለያዩ አማራጭ በመጠቀም ምሩቃን ተማሪዎች የሚጠበቅባቸውን እንዲያሟሉ ማድረጉንም ገልጸዋል።

    መዳ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ በዕለቱ በሁለተኛ ዲግሪ መርሃ ግብር ያስመረቃቸው 208 ተማሪዎች አምስተኛው ዙር ሲሆኑ፥ በተፈጥሮ ሳይንስ፣ ቋንቋና ሥነ ጽሁፍ፣ ሕክምናና ጤና ሳይንስ፣ ማኅበራዊ ሳይንስ፣ የተፈጥሮ ቀመር፣ ቢዝነስና ምህንድስና የተማሩ ናቸው።

    ዶክተር አህመድ እንደገለጹት፥ ዩኒቨርሲቲው የአካባቢውን ማኅበረሰብ ከኮሮና ቫይረስ ለመጠበቅ ግንዛቤ ከማስጨበጡ በተጓዳኝ ለችግር የተጋለጡ ወገኖችን የመደገፍና ተመርምረው ራሳቸውን እንዲያውቁ ድጋፍ እያደረገ ይገኛል። ተመራቂዎች በትምህርት ቆይታቸው የቀሰሙትን ዕውቀት ወደ ተግባር ቀይረው ሀገራቸውንና ሕዝባቸውን እንዲያገለግሉና ኮሮናን በመከላከሉም የድርሻቸውን እንዲወጡ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

    ከተመራቂዎች መካከል መሐመድ አህመድ በሰጠው አስተያየት፥ ኮሮና ቫይረስ በትምህርቱ ዘርፍ ጫና ቢያሳድርም በቴክኖሎጂ ታግዘው ለምርቃት በመብቃቱ መደሰቱን ገልጾ፥ በሰለጠነበት ሙያ ሕብረተሰቡን ለማገልገል ዝግጁ መሆኑን ተናግሯል። ሌላው የእለቱ ተመራቂ ጣህር መሐመድ በበኩሉ በሙያው ሕዝቡን በማገልገል የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ገልጿል።

    በ1999 ዓ.ም 742 ተማሪዎች ተቀብሎ ሥራ የጀመረው መዳ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ አሁን ላይ ከ24ሺህ የሚበልጡ ተማሪዎች እንዳሉት ተመልክቷል።

    በተመሳሳይ ሰመራ ዩኒቨርሲቲ በመደበኛ፣ ርቀትና ተከታታይ የትምህርት መረሃ ግብር ያሰለጠናቸው 137 ተማሪዎች አስመርቋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር አደም ቦሪ በምረቃው ሥነ-ሥርዓት እንደገለጹት፥ ያስመረቋቸው ተማሪዎች ኮሮና ቫይረስ ጫና ቢፈጥርባቸውም አማራጭ የመገናኛ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ናቸው።

    ከተመራቂዎቹ መካከል 107 ተማሪዎች በሁለተኛ ዲግሪ በተለያዩ የትምህርት መስኮች የሰለጠኑ ሲሆኑ፥ ቀሪዎቹ በመጀመሪያ ዲግሪ መደበኛ፣ ርቀትና ተከታታይ ትምህርት የተከታተሉ መሆኑ ተመልክቷል።

    ተመራቂዎች ወደ ሥራ ሲገቡ በሰለጠኑበት ሙያ ሀገራቸውንና ሕዝባቸውን በቅንነትና ፍትሃዊነት ማገልገል እንዳለባቸው ፕሬዚዳንቱ ዶ/ር አደም ቦሪ አሳስበዋል።

    ከተመራቂዎች መካከል በሁለተኛ ዲግሪ አካውንቲንግና ፋይናንስ የትምህርት መስክ አራት ነጥብ በማምጣት የተመረቀው መሃመድ አሊ በሰጠው አስተያየት፥ ከ17 ዓመታት በኋላ ወደ ትምህርት ተመልሶ የቤተሰብ ኃላፊነትና የሥራ ጫና ተቋቁሞ ለዚህ ውጤት በመብቃቱ መደሰቱን ገልጿል። በቀጣይም እራሱን የበለጠ በማብቃት በተሰማራበት ሙያ በቅንነትና በትጋት ሀገሩን ለማገልገል እንደሚሠራ ተናግሯል።

    ድሬዳዋ፣ መዳ ወላቡ እና ሰመራ ዩኒቨርሲቲዎች ከ460 በላይ ተማሪዎችን አስመረቁ

    Anonymous
    Inactive

    በኢትዮጵያ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ የታሪክ ዳራ፥ በእኩልነት ላይ የተመሠረተች ሀገር ለመፍጠር የተደረጉ ሙከራዎች፣
    ያጋጠሙን የታሪክ ፈተናዎችና ያመለጡን ዕድሎች በብሔራዊ መግባባት መነፅር ሲታይ

    መረራ ጉዲና (ፕሮፌሰር)
    ለብሔራዊ መግባባት ውይይት የቀረበ ጥናት
    ነሐሴ 2012

    አብዛኛዎቹ የሀገራችን የታሪክ ምሁራን የኢትዮጵያ ታሪክ ከክርስቶስ ልደት በፊት፣ በአስረኛው ምዕተ ዓመት የንግስት ሳባ እና የንጉሥ ሰለሞን ግንኙነት በሚባለው ጊዜ ይጀምራል ይላሉ። ይህ ለአንዳንዶቹ የሚታመን ታሪክ ተደርጎ የሚወሰደው፤ ለሌሎች ደግሞ ተረት እንደነበረ የሚነገረው ክስተት የማስመሰያ ትርክቱ የእስራኤል አምላክ የቀባቸው ገዥዎች ተብሎ በሺዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት ንጉሦቹ ቅቡልነትን አግኝተውበታል። በትርክቱም ሀገሪቷን እስከ 1966 ሕዝባዊ አብዮት ድረስ ያለ ብዙ ጭንቀት ገዝተውበታል።

    የዛሬይቱ ሰፊዋ ኢትዮጵያ እንደ ሕብረ ብሔራዊ የነገሥታት መንግሥት (multi-ethnic empire state) የተፈጠረችው በ2ኛው የ19ኛው ክፍለ ዘመን ግማሽ፤ የዘመነ መሳፍንት ከሚባለው ዘመን በኋላ ስለሆነና ዛሬም በጣም ሰፊ ቀውስ ውስጥ የከተተን ታሪካዊ ዳራም ከዚሁ ጊዜ ጀምሮ ስለሆነ፥ ጽሑፌም ከዘመናዊ ኢትዮጵያ መፈጠር ጋር በተፈጠሩ ችግሮች ላይ ያተኩራል።

    የዘመነ መሳፍንትን ክስተት በመለወጥ የተጀመረው የዛሬዋን ሰሜናዊ ኢትዮጵያን አንድ የማድረግ ሕልም በግማሽ ምዕተ ዓመት ውስጥ ከሦስት እጥፍ በላይ የሰፋች ኢትዮጵያን መፍጠር ችሎዋል። ይህ የታሪክ ክስተት የሦስት ምኞቶች ዉጤት ነበር። እነዚህም፡-

    1ኛ/ ተበታትና የነበረችውን የዛሬዋን ሰሜናዊ ኢትዮጵያ ሕዝቦችን ለማሰባሰብ የታለመ ምኞት፣
    2ኛ/ የኦሮሞና የሶማሌ ሕዝቦችን ጨምሮ ሰፊውን የደቡብ ክፍል የማስገበር ምኞት፣
    3ኛ/ አፍሪካን ለመቀራመት የመጡትን የአውሮፓ ሀገሮች ጋር የመፎካከር ምኞት ነበሩ።

    እነዚህን ሦስት ምኞቶች ለማሳካት የመጀመሪያ የሆነውን ሙከራ የጀመሩት እንደምታውቁት አፄ ቴዎድሮስ ነበሩ። ቴዎድሮስ ሕልሞቹን ለማሳካት ጠንካራና ሰፊ ሠራዊት ማደራጀት ነበረባቸው፤ ለዚህም ሰፊ መሬት የያዙትን ቄሶች መሬት መቀማትና ዘመናዊ መሣሪያን ከክርስቲያን አውሮፓ ለማግኘት ጥረት ማድረግ ነበር። የአዉሮፓ መሪዎችን ማሳመን ሲያቅታቸው ደግሞ ሙያው የሌላቸውን አውሮፓዊያንን ሳይቀር በቤተ መንግሥታቸው ሰብስበው ከባድ የጦር መሣሪያ ውለዱ እስከማለት ደርሰዋል። ይህም ምኞታቸዉ ይሳካ ዘንድ በነበራቸዉ የጦር መሣሪያ የአካባቢ ገዥዎችንም ለማንበርከክ ተንቀሳቅሰዋል።

    ቄሶችን ለመግፋት ያደረጉት ሙከራ እግዚአብሔርን የካዱ ንጉሥ ተብሎ ተሰባከባቸዉ። የአውሮፓውያንን ዘመናዊ መሣሪያ ለማግኘት ገደብ ያለፈ ጉጉታቸው ከእንግሊዘኞች ጋር ያለጊዜ አላተማቸው። የየአከባቢውን ገዥዎች በጉልበት ለማንበርከክ እጅና አንገት በመቁረጥ የገፉበት ሙከራ ከእንግሊዞች ጋር ለመዋጋት የቁርጥ ቀን ሲመጣ፥ የትግራይ፣ የወሎ፤ የጎጃም፣ የሸዋ፣ የጎንደር ገዥዎች ሁሉም በሚባልበት ደረጃ ካዷቸው። በአጭሩ የየአከባቢዉ ገዥዎች በእንግሊዞች እጅ መሞታቸውን ሲሰሙ ከማዘን ይልቅ ተገላገልን ያሉ ይመስላል። ለዚህም ይመስለኛል ዕውቁ የታሪክ ምሁር ፕሮፌሴር ባህሩ ዘውዴ የቴዎድሮስን ሚና በተሻለ የታሪክ ሚዛን ላይ ለማስቀመጥ ሲሞክር፥ “የተወናበዱ የለዉጥ ነቢይ” (“confused prophet of change”) ያላቸዉ።

    በዚህ የቴዎድሮስ የታሪክ ሚና ላይ ብዙ ሰው ልብ የማያደርገውን የታሪክ ማስታወሻ አስቀምጬ ልለፍ። ይኼውም ቴዎድሮስ በጊዜው ለነበሩ የአውሮፓ ኃያላን መንግሥታት በፃፉት ደብዳቤ ውስጥ፥ “አባቶቼ በሠሩት ኃጢአት ምክንያት እግዚአብሔር “ጋሎችን” በሀገሬ ላይ ለቆ፣ እነሱ ጌቶች ሆነው፣ እኛ የእስራኤል ልጆች የነሱ አሽከሮች ሆነን እንኖር ነበር። አሁን እግዚአብሔር ከትቢያ አንስቶኝ የኢትዮጵያ ንጉሥ አድርጎኛል። እናንተ ከረዳችሁኝ በጋራ እየሩሳሌምንም ነፃ ልናወጣ እንችላለን” ማለታቸዉ ነዉ (ትርጉም የኔ ነው)። እዚህ ላይ ሁለት ነገሮችን ልበል፦

    1) “ጋሎቹ” የሚባሉት በዘመነ መሳፍንት የጎንደርን ቤተ መንግሥት በበላይነት ሲቆጣጠሩ የነበሩ የየጁ ኦሮሞዎች መሆናቸውና እየሩሳሌም በጊዜው በእስላሞች እጅ የነበረች መሆንዋን ነው።
    2) ከዚህ አንጻር ማስታወስ የሚያስፈልገው ትልቁ ጉዳይ አፄ ቴዎድሮስ የብሔረሰብ (የዘር) ፖለቲካን በግልፅ የተናገሩ የመጀመሪያዉ የኢትዮጵያ መሪ መሆናቸው ነው።

    ከቴዎድሮስ ሞት በኋላ ለሦስት ዓመታት በተክለጊዮርጊስ እና ካሣ (አማቾች የነበሩ ይመስለኛል) ከተካሄደው የሥልጣን ትግል በኋላ በአሸናፊነት የወጡት አፄ ዮሐንስ (ካሣ ምርጫ) ነበሩ። አፄ ዮሐንስ ከሀገር ውስጥ ከወሎ፣ ከጎጃም፣ ከጎንደር፣ ከሸዋ ገዢዎች ጋር እየተጋጩ፥ ከውጭ ደግሞ ከጣሊያኖች፣ ከግብፆችና ከሱዳን መሐዲስቶች (ደርቡሾች ) ጋር ሲዋጉ በመጨረሻ በመሐዲስቶች እጅ ወድቋዋል።

    በአጭሩ ዮሐንስ ለትግራይ ሊሂቃን የኢትዮጵያ ማዕከል ነበርን፤ የአክሱም ሀቀኛ ወራሾች እኛ ነን የሚለውን የፖለቲካ ስሜት መፍጠር ቢችሉም፥ በኢትዮጵያ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ታሪክ ውስጥ የተለየ ሚና መጫወት አልቻሉም።

    በማያሻማ ቋንቋ፥ የዛሬዋ ኢትዮጵያ በዋናነት የተፈጠረችውና የዛሬው የታሪክ ጣጣችንም በዋናነት የተፈጠረው በአፄ ምኒልክ ነው። ምኒልክ ንጉሠ ነገሥት ዮሐንስን የሱዳን መሐዲስቶች እስኪገድሉላቸው ድረስ ከአውሮፓ መንግሥታት፥ በተለይም ከጣሊያን በገፍ ባገኙት የጦር መሣሪያ እነራስ ጎበና የመሳሰሉ የኦሮሞ የጦር መሪዎችን በመጠቀም በጊዜው ጠንካራ የሚባል ግዙፍ ሠራዊት መገንበት ችለዋል። ይህንን ግዙፍ ሠራዊትን ከዮሐንስ ጋር በመዋጋት ከማድከም ይልቅ፥ በአንድ በኩል ዮሐንስን እየገበሩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ያኔ የነበረችውን ኢትዮጵያ ሦስት እጅ እጥፍ የሆነ ሰፊ ግዛት መፍጠር ችሎዋል። በዚህም መጀመሪያ ሳይጠቀለሉ የቀሩትን የሸዋ ኦሮሞዎችን ጠቅልለው ያዙ። ከዚያ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር (እ.አ.አ) በ1876 ጉራጌን ብዙ ሕይወት ከጠየቀ ጦርነት በኋላ አስገበሩ። ብዙ ዝርዝር ውስጥ ሳይገባ የምኒልክን የመስፋፋት ጦርነቶች እንደሚከተለው ማጠቃለል ይቻላል። ይኸውም በምኒልክና ጀኔራሎቹ ብዙ የግዛት መስፋፋት ጦርነቶችን ቢወጉም ሦስቱ ወሳኝ ጦርነቶች ነበሩ።

    አንደኛው በምዕራብ በኩል በእማባቦ (ዛሬ ሆሮ ጉዱሩ በሚባለው ላይ በጎበና መሪነት እ.አ.አ በ1882 የተዋጉት ጦርነት ነበር። ይህ ጦርነት ኦሮሞን ጨምሮ የምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦችን ዕድልና የጎጃም መሪዎች ከሸዋ ጋር የነበራቸውን ፉክክር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የወሰነና የሸዋንም የበላይነት ያረጋገጠ ነበር።

    ሌላው የምኒልክ ጦርነት በአርሲ ላይ እ.አ.አ በ1886 የተደመደመዉ ነው። አርሲዎች ከሌሎች የኦሮሞ አካባቢዎች በተለየ መንገድ ለአምስት ዓመታት በጀግንነት ተዋግተዋል። በመጨረሻም በራሳቸው በምኒልክ በተመራ ጦር የአውሮፓ መሣሪያ በፈጠረው ልዩነት ሊሸንፉ ችለዋል። ተመሳሳይ የመከላከል ጦርነት እንዳይገጥማቸው ይመስላል ምኒልክ ዛሬ አለ፣ የለም የሚባለውን የአኖሌ ዓይነት የጭካኔ በትር በአርሲዎች ላይ አሳርፈዋል። እዚህ ላይ ዛሬ እየተነጋገርንበት ላለው የብሔራዊ መግባባት መሳካት፥ የለም ከሚለው አጉል ክርክር ወጥተን የትናንትናውን የታሪክ ቁስላችንን በሚያክም መልኩ እንድናስተካክል መምከርን እወዳለሁ።

    ሦስተኛው የምኒልክ ትልቁ ጦርነት አሁንም በእሳቸው የተመራውና እ.አ.አ በ1887 የተካሄደው የጨለንቆ ጦርነት ነበር። የዚህ ጦርነት ውጤት በጊዜው የሀብታሟ የሐረር ከተማ መንግሥት (the Harari city-state) ጨምሮ ምስራቅ ኢትዮጵያ ያለ ደረሰኝ ምኒልክ እጅ የገባበት ሁኔታን ፈጥሯል። ከዚህም በኋላ ከፋን፣ ወላይታን፣ ወዘተ ለመያዝ ብዙ ደም የፈሰሰባቸው ጦርነቶች ነበሩ። እንደሚባለው በእንግሊዝ ተስፋፊዎችና በምኒልክ ኢትዮጵያ መካከል የመምረጥ ዕድል የገጠማቸው የቦረና ኦሮሞዎች፥ ‘ማንን ትመርጣላችሁ?’ ሲባሉ፥ የፊታወራሪ ሀብተጊዮርጊስ ፊትን አይተው፥ የእኛኑ ፊት የሚመስለው ይሻላል ብለው በሪፈረንደም (referendum) እየሰፋ በመጣው የኢትዮጵያ መንግሥታዊ ግዛት ውስጥ የተቀላቀሉበት ሁኔታም እንዳለ ይነገራል።

    እ.አ.አ በ1889 አፄ ዮሐንስ በመሐዲስቶች ሲገደሉ፥ ኦሮሞን ጨምሮ አብዛኛው ደቡብን የተቆጣጠሩት ምኒልክ ለሰሜኑ ወንድም መሪዎች ፈረንጆች እንደሚሉት “ካሮትና ዱላን ማስመረጥ” (carrot-and-stick approach) ብቻ በቂ ነበር። የሰሜኑ መሪዎች ምርጫም በማያሻማ መንገድ ካሮት ነበር። ስለካሮቱም በግልፅ ቋንቋ ለማስቀመጥ፥ የኦሮሞ አከባቢዎችን ጨምሮ በደቡብ የተገኘውን እጅግ በጣም ሰፊ ግዛት ዉስጥ በታናሽ ወንድምነት ሹማቶችን መቀራመት ነበር።

    በብሔራዊ መግባባታችን ውይይት አንፃር በምኒልክ በተፈጠረው ሰፊ አፄያዊ ግዛት ጋር የተፈጠሩ ችግሮችን ወደ ማንሳቱ ልለፍ። አንደኛው ችግር ከላይ እንዳነሳሁት፥ በጉልበት የግዛት ፈጠራ ላይ አኖሌን የመሳሰሉ የታሪክ ጠባሳዎች መፈጠራቸው። ሁለተኛውና ዋናው ነገር ግን ከማቅናቱ ጋር የተፈጠረው የፖለቲካል ኤኮኖሚው ነው። ይህም በነፍጥ ላይ የተመሠረተዉ የፖለቲካ ኤኮኖሚ ዛሬም እያወዛገበን ያለው የነፍጠኛ ሥርዓት በሚባለው ላይ የተመሠረተዉ ነዉ። ለማቅናት የተሰማራው የፊውዳሉ ሥርዓት ሠራዊት የገባር ሕዝቦችን ነፃነት ቀምተዋል፤ መሬታቸዉን ዘርፈዋል፤ ሕዝቦችን በገዛ መሬታቸው ላይ ጭሰኛና አሽከር አድርገዋል፤ ቋንቋቸውን አፍነው በ’ስማ በለው’ ገዝቷቸዋል። በአጭሩ፥ እጅግ በጣም ዘግናኝና ጨካኝ የሆነ የፖለቲካ ሥርዓት ጭነውባቸዋል። አንዳንዱ ነፍጠኛ በሃያ ሺዎች የሚቆጠር ጋሻ መሬትም ነበረው። ወረ-ገኑ የመሳሰሉ የቤተ መንግሥት መሬቶች እጅግ በጣም ብዙ ነበሩ። እዚህ ላይ ማስታወስ የሚያስፈልገው የሰሜንና የደቡብ ኢትዮጵያ የመሬት ይዞታም በፍጹም የተለያዩ መሆናቸው ነው። አነሰም በዛ የሰሜኑ ገበሬ የዘር ግንዱን ቆጥሮ መሬት ያገኛል። መሬት አያያዙም የወል ነበር። ሌላው ቢቀር የሚገዛውም በራሱ ቋንቋ ነበር። በደቡቡ ያለው ግን የመሬት ሥርዓቱ የግል ሆኖ፥ ጭሰኝነት እጅግ የተንሠራፋበት ነበር። ሲሶ ለነጋሽ፣ ሲሶ ለቀዳሽ፣ ሲሶ ለአራሽ የሚባለው የኢትዮጵያ ነገሥታት የመሬት ፖሊሲ እጅግ በጣም ዘግናኝ በሆነ ሁኔታ ሥራ ላይ የዋለው በደቡቡ የሀገራችን ክፍል ላይ ነው።

    በ1960ዎቹ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ዘመን “መሬት ላራሹ” እና “የብሔረሰቦች እኩልነት” የተባሉ ሕዝባዊ መፈክሮች የተወለዱት ከዚሁ ጨቋኝ ሥርዓት ነበር። ዛሬ የታሪክ ክለሳ ውስጥ ብንገባም፥ በእውነቱ ከሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብራክ የወጡ ወጣቶች፥ እንዲያውም በወቅቱ ‘አማራ’ ከሚባለው ክፍል የሚበዙ ይመስለኛል፤ መፈክሮቹን በጋራ አስተጋብተዋል።

    ለማንኛውም ከብሔራዊ መግባባታችን አንፃር አንድ ነገር ግልፅ ላድርግ። ‘ነፍጠኛ’ የሚባለው ሥርዓት ገዝፎ የነበረ ሥርዓት መሆኑና፥ ይህም ሥርዓት ከደቡቡ አርሶ አደር የተሻለ ኑሮ የማይኖሩትን፥ ቢፈልጉ እንኳን የደቡቡን ገበሬ ለመዝረፍ አቅሙም ሆነ ዕድሉን ያልነበራቸውን የአማራ አርሶ አደርን አይጨምርም፤ መጨመሩም ጩቡ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ዛሬ አንዳንድ የአማራ ሊሂቃን “እኔም ነፍጠኛ ነኝ” የሚለውን መፈክር ሲያሰሙ፥ ጥቅሙ ኦሮሞን ጨምሮ የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦችን ከአማራ ሕዝብ ጋር ከማጋጨት የዘለለ የፖለቲካ ትርፍ የሚኖረው አይመስለኝም። ስለሆነም የምንችለውን ያክል ሁላችንም ከሁለቱም ጩቡዎች እንጠንቀቅ ዘንድ አደራ እላለሁ።

    ወደ ሌሎች ነጥቦች ከማለፌ በፊት በዋናናት በምኒልክ የተፈጠረችዉ ኢትዮጵያን ለማስተካከል ያቃታቸዉና መሪዎች ማለፍ ያልቻሉት የታሪክ ፈተና ምንድን ነው? የሚለውን ጥያቄ በንጽጽር እንደ ታሪክ ቁጭት ማንሳትን እወዳለሁ። አፄ ቴዎድሮስ የሞቱት እ.አ.አ በ1868 ነበር። ጃፓንን ከታላላቅ የዓለም መንግሥታት ተርታ ያሰለፏት መጅ (Meiji) የሚባሉ የንጉሣውያን ቤተሰብ ወደ ሥልጣን የተመለሱት (The Meiji Restoration) በዚሁ ዓመተ ምኅረት ነበር። የጃፓን ንጉሣዊ ቤተሰቦች በሰላሳ ዓመታት ውስጥ በኢኮኖሚ የበለፀገች ታላቋ ጃፓንን ፈጠሩ። የጃፓኖች የሀገር ፍቅር ግንባታቻውም ባዶ አልነበረም። ትዝ እስከሚለኝ ድረስ አንድ የጃፓን ወታደር ንጉሤ የጃፓንን በሁለተኛው የዓለም ጦርነት መሸነፍ አልነገሩኝም ብሎ ከሃምሳ ዓመታት በኋላ በፊሊፕንስ ይሁን፤ በኢንዲኔዢያ ጫካ ውስጥ ተገኝቷል። ለሀገር ፍቅር ሲባል እራስን በራስ ማጥፋት በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በትናንሽ አይሮፕላኖችን የአሜሪካን መርከቦች ውሰጥ እየጠለቁ አጥፍቶ መጥፋትን የጀመሩት የጃፓን ካሚከዞች (Kamikaze) የሚበሉ ነበሩ። የኢትዮጵያ መሪዎች ግን በተመሳሳይ ጊዜ (እ.አ.አ 1868-1900) ድረስ ሀገሪቷን ከዓለም ጭራነት አላላቀቋትም። በነገራችን ላይ ጃፓንና ኢትዮጵያ በ1868 ላይ ተመሳሳይ የዕድገት ደረጃ ላይ ነበሩ።

    ሌላው ንጽጽሬና የታሪክ ቁጭታችን መሆን ያለበት፥ ታላቋ ጀርመንን የፈጠሩት ቢስማርክ (Otto von Bismarck) እና ምኒልክ የአንድ ዘመን ሰዎች ነበሩ። ምንም ይሁን ምን እነ ቢስማርክ ዓለምን ሁለት ጊዜ ጦርነት ውስጥ መክተት የቻለች ኃያሏን ጀርመን ሲፈጥሩ፥ የኢትዮጵያ ገዥዎች ግን ኋላቀር ኢትዮጵያን ትተውልን ሄደዋል። በነገራችን ላይ ሀገር ትፈርሳለች ተብሎ ስለተሰጋ፥ የምኒልክ ሞት ለሕዝብ ይፋ የሆነው ከዓመታት በኋላ ነበር ይበላል።

    በአጠቃላይ ከብሔራዊ መግባባት ፈጠራችን አንፃር መረሳት የሌለበት ቁመነገር፥ በምኒልክና ጣይቱ የተመራው የአድዋው የጋራ ድል እንኳ ያልፈቱት የሚጋጩ ሦስት አመለካከቶች ዛሬም ከእኛ ጋር መኖራቸዉ ነዉ።

    አንደኛው፥ የሀገራችን ሀገረ-መንግሥት ግንባታ አንድ የነበሩና የተበታተኑ ሕዝቦችን አንድ ላይ መልሶ ያመጣ ነዉ የሚላዉ አመላካከት (reunification)፤
    ሁለተኛው፥ በአንድ ላይ ያልነበሩ ሕዝቦችን ወደ አንድ ማምጣት ነዉ የሚለዉ አመላካከት (unification and/or expansion)፤
    ሦስተኛው፥ ነፃ ሕዝቦችን ጨፍልቆ በኃይል ማቅናት ነዉ የሚላዉ አመላካከት (colonial thesis) ናቸው። የበለጠ ግልፅ ለማድረግ፥ የኢትዮጵያ አንድነት አጥባቂዎች ነን የሚሉ በዋናነት የምኒልክን ኃጢአቶች አይቀበሉም። እንደሚሉት እምዬ ምኒልክ በዓለም ከተደረጉት የሀገር ግንባታዎች ምን የተለየ ነገር ሠራ የሚለውን ሐሳብ ያራምዳሉ። ከዚያም አልፈዉ ምኒልክ የሠራዉ ሥራ ተለያይተዉ የነበሩትን የኢትዮጵያ ግዛቶችን መመለሰ ነበር ይላሉ። በአንፃሩ የኢትዮጵያ አንድነትን የማያጠብቁ ብሔረተኞች ደግሞ የአቶ ሌንጮ ለታን አባባል ለመጠቀም (አሁን አቋማቸዉ ያ መሆኑን አላዉቅም)፥ ሲያንስ “ኢትዮጵያዊ ለመሆን እንደራደራለን ሲበዛ ደግሞ ነፃ መንግሥታትን እስከ መፍጠር ድረስ እንሄደለን” የሚሉ ናቸው። በጥቅሉ እነዚህ አመለካከቶች በፖለቲካችን ለሚጋጩ ሕልሞቻችን መሠረት የሆኑና ካልተገደቡ የሥልጣን ሕልሞች ጋር ተደምሮ የብሔራዊ መግባባት ጥረታችንን የሚያወሳስቡ አመለካከቶች መሆናቸውን በውል መገንዘብ ያስፈልጋል።

    በእነምኒልክ የተፈጠረችዉን ኢትዮጵያን ለማስተካከል የተደረጉ ሙከራዎችና ያመለጡን ዕድሎች፡-

    1) የልጅ ኢያሱ ሙከራ

    ልጅ ኢያሱ የምኒልክ ልጅ ልጅ ሲሆን፥ በእኩልነት ላይ የተመሠረተች ኢትዮጵያን ለመፍጠር ልዩ ዕድል የነበረውና ያንንም ልዩ ዕድል አውቆ ለመጠቀም ሲሞክር በወጣትነት ዕድሜው ላይ የተቀጨ መሪ ነበር። በብሔር ግንዱ ኦሮሞና አማራ የነበረ፣ በሃይማኖት ጀርባዉ ክርስቲያንና ሙስሊም የነበረ ሰዉ ነዉ። ከወሎም በመወለዱ፣ ትግራይንና ሸዋን ለማገናኘት የተሻለ ድልድይ ለመሆን ይችል ነበር። የሚገርመው ግን፥ የልጅ ኢያሱ ወንጀሎች የሚመነጩት እነዚህኑ አዎንታዊ እሴቶችን ለሀገረ-መንግሥት ግንባታ ለመጠቀም መሞከሩ ነበር። ለምሳሌ አንዳንድ የታሪክ ማስታወሻዎች እንደሚያስረዱት፥ አርሲዎች እንደልጃቸው ይመለከቱት ነበር ይባላል። ከሱማሌዎችና ከአፋሮች ጋር ጥብቅ ግንኙነት እንደነበረው በቂ የሆነ የታሪክ ማስረጃ አለ። ከጎጃሙ ራስ ኃይሉና ከወለጋው ደጃዝማች ጆቴ ቱሉ ጋር የጋብቻ ዝምድና እንደነበረው ይታወቃል። ቤተ ክርስቲያንን ለማሠራት የሚጥረውን ያክል (ለምሳሌ የቀጨኔውን መድሃኔዓለምን እሱ ነው ያሠራው ይባላል) መስግዶችን ያሠራ ነበር። ከሥልጣን ላወረዱት የሸዋ ሊሂቃን ግን፤ አንዱና ትልቁ የልጅ ኢያሱ ወንጀል መስጊዶችን ማሠራቱ ነበር። የመጨረሻው ትልቁ ወንጀል ደግሞ ኢትዮጵያን ለመቀራመት ያንዣበቡ የቅኝ ገዥ ኃይሎች ከሰሜንና ምስራቅ ጣሊያን፣ በምዕራብ፣ በደቡብና በምስራቅ እንግሊዝ፣ በምስራቅ ፈረንሳይ የሦስትዮሽ ስምምነት (tripartite treaty) የሚባለውን እ.አ.አ በ1903 ፈርሞ የምኒልክን ሞት ይጠብቁ ከነበሩት መራቅና በአንደኛው የዓለም ጦርነት በአከባቢያችን ግዛት ካልነበራቸው ከነጀርመንና ቱርክ ጋር ለመደጋገፍ መሞከሩ ነበር።

    በጥቅሉ ከሁሉም በላይ ወንጀሎቹ ሰፊዋን ኢትዮጵያን የፈጠርን እኛ ነን የሚሉትን የሸዋ ልሂቃንን መጋፋቱ ነበር። በግልፅ ቋንቋ ለማስቀመጥ፥ የኢያሱ ወንጀሎች የሸዋ ልጅ አለመሆኑ (የኢያሱ አባት ወሎ ነው)፣ ሐቀኛ የክርስቲያን ልጅ አለመሆኑ (አባቱ የግድ ክርስቲያን ከመሆናቸው በፊት መሐመድ ዓሊ ነበሩና) እንዲሁም የአውሮፓ የቅኝ ገዥ ኃይሎችን ማስቀየሙ ናቸው።

    እ.አ.አ በ1916 በመስቀል ቀን ኢያሱን ለማውረድ ሁሉም መሣሪያዎቻቸውን ይዘው ተሰለፉ። ቄሶቹ ኢያሱ ሐቀኛ የክርስቲያን ልጅ አይደለም በማለት በማውገዝ፣ የሸዋ ሊሂቃን ሠራዊታቸውን በመሳለፍ፣ የአውሮፓዊያኑ መንግሥታት ምክርና ጥበባቸውን ይዘው ተሰለፉ። የአውሮፓዊያኑ ጥበብ የሚገርም ነበር፤ ኢያሱ በኢትዮጵያ ባንዲራ ላይ የእስልምና ምልክት የሆነውን ግማሽ ጨረቃ ለጥፎ ለቱርኮች ዲፕሎማት ሲሰጥ የሚያሳይ ፎቶ ሾፕ የሆነ ሥዕል (ፎቶ ሾፕም፣ የባንድራ ፖለቲካም በልጅ ኢያሱ ዘመንም ነበር) መፈንቅለ መንግሥት እንድያከሄዱ የሸዋ ሊሂቃንን መርዳት ነበር። እዚህ ላይ ለታሪክ ትዝብት አንድ ነገር ልብ በሉልኝ። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያን ፖለቲካ ሳስተምር፥ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ችግሮቻችንን በሚመለከት ፈተናም ፈትኜበታለሁ፤ የሸዋው ጦር መሪ የነበሩት ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴ የመፈንቅለ መንግሥቱም መሪ ነበሩ፤ ልጅ ኢያሱን ሲያወርዱ ባስተላለፉት መልዕክት ውስጥ የሚከተለው ይገኝበታል።

    “He claims that he eats flesh of cattle slain by Muslims in order to extend frontiers and to win hearts. But these Somali and Muslims have already been brought to heel [and do not need such diplomacy]”

    በጥሬው ሲተረጎም፥ ግዛትን ለማስፋፋትና ልቦችን ለመሳብ ብዬ በሙስሊም የታረደውን የከብት ሥጋ እባላለሁ ይላል። ነገር ግን እነዚህን ሱማሌዎችና ሙስሊሞችን ቀድሞውኑ ስላንበረከክን እንዲህ ዓይነቱ ዲፕሎማሲ አያስፈልጋቸውም።

    ይህንን የሀብተጊዮርጊስን ንግግር በሚመለከት ሰፊውን ትንተና ለናንተ ትቼ፥ በዚህ ዓይነት የተዛባ አመለካከት ላይ የተገነባችውን ኢትዮጵያን አስተካክሎ በሰፊ መሠረት ላይ የተገነባችውን ኢትዮጵያን ለመፍጠር የተደረገው የመጀመሪያ ሙከራ፥ ልጅ ኢያሱን ለሥልጣን ተብሎ በተጠነሰሰው ሤራ መውረዱን እንዳትረሱት አደራ ማለት እፈልጋለሁ። ያመለጠንን ዕድል ትርጉም ግን ለታሪክ መተውን አመርጣለሁ።

    2) ኢያሱን በወሳኝነት የተኩት ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ

    የሀገራችንን ሀገረ-መንግሥት ግንባታን በተሻለ መሠረት ላይ ለመገንባት ረጅም ጊዜ (ለ60 ዓመታት ገደማ አገሪቷን መርተዋል) በልጅነታቸው የተሻለ የፈረንጅ ዕውቀት የቀመሱና ከማንም የበለጠ ተደጋጋሚ ዕድል ያገኙ ነበሩ። ነገር ግን በእኔ ግምት ታሪክ የሰጣቸዉን ዕድል አልተጠቃሙበትም። ንጉሥ ኃይለ ሥላሴን የተለያዩ ሰዎች በተለያዩ የታሪክ ሚዛን ላይ ቢያስቀጣቸውምና እኔም ቢሆን በዘመናዊ ትምህርትና በመሳሰሉት ላይ የነበራቸውን አሻራ ቀላል ነው ብዬ ባላስብም፥ ንጉሡ ሕይወት ዘመናቸውን በሙሉ የግል ዝናንና ሥልጣንን ማዕከል ማድረጋቸው ኢትዮጵያዉያንን የ20ኛው ክፍለ ዘመን ሕዝቦች ማድረግ አልተቻላቸውም። ስለዘር ግንዳቸው ሀሜቱ እንዳለ ሆኖ፥ ከኢያሱ በተሻለ ደረጃ ኦሮሞም፣ ጉራጌም አማራም ነበሩ። ይህንን ስረ ግንድ አልተጠቀሙም። በተለይ ኦሮሞ ከሚባል ሕዝብ ሲሸሹ እንደኖሩ ብዙ ማስረጃዎች አሉ። ለማንኛዉም፤ አንድንድ ወሳኝ ነገሮችን እንመልከት።

    አምቦ 2ኛ ደረጃ ተማሪ በነበርኩበት ጊዜ የሰማሁት ይመስለኛል፤ አንድ ጋዜጠኛ ካነበቡት መጽሐፍት ዉስጥ የትኛውን እንደሚያደንቁ ሲጠይቃቸው፥ ቀልባቸውን በጣም የሳበውና ብዙ ጊዜ ደጋግመው ያነበቡት በኒኮሎ ማኪያቬሊ (Niccolò Machiavelli) የተፃፈውን “The Prince” የተባለውን እንደነበረ ትዝ ይለኛል። ንጉሡ አብዘኛዉን የሕይወት ዘመናቸዉን የተመሩት በማኪያቬሊ ምክር ነበር ብዬ እጠረጥራለሁ። በማክያቬሊ ትምህርት በመመራትም የሥልጣን ተቀናቃኞቻቸውን አንድ በአንድ አስወግደው ከአስራ አራት ዓመታት በኋላ እ.አ.አ በ1930 ጥቁር ማክያቬሊ ፈላጭ ቆራጭ ንጉሥ ሆነው ወጡ።

    እንደ ሀብተጊዮርጊስ ዓይነቱን እግዚአብሔር በጊዜ ሲገላገልላቸው፣ እንደ ጎንደሩ ራስ ጉግሳና ባለቤታቸው ንግስት ዘዉድቱን ያስወገዱበት የፖለቲካ ጥበብ፣ በጊዜው በርግጥም አስደናቂ ነበር። ይህ የንጉሡ ጥበብ፤ አርባ ዓመታትን ቆጥራ የአድዋን ሽንፈት ለመበቀል የመጣቸውን ጣሊያንን ለመከላከል አልረዳም። መንግሥታቸዉንም፤ ሀገሪቷንም ለክፉ ቀን አላዘጋጁም።

    አድዋ ላይ ታሪካዊ ድል ያስገኙ ጀግኖችም የሉም። አንድ ለታሪክ የተረፉት ደጀዝማች ባልቻ ሣፎም በንጉሡ ዉሰኔ እስር ቤት ነበሩ። እዚህም ላይ አንድ የታሪክ ትዝብት አስቀምጬ ማለፍ እፈልጋለሁ። ኃይለ ሥላሴ ለሥልጣናቸዉ ብሎ የገፏቸው ብዙ የአከባቢ መሪዎች፥ ከትግራዩ ደጃዝማች ኃይለሥላሴ ጉግሳ ጀምሮ የጎንደር፣ የጎጃም፣ የሸዋ፣ የጅማ፣ የወለጋ ገዥዎች የጣሊያን ባንዳ ሆኑ። ከሚታወቁት ውስጥ ለታሪክ ‘ተፈሪ ሌላ፣ ሀገር ሌላ’ ብለው ሲዋጉ የሞቱት ደጃዝማች ባልቻ ብቻ ነበሩ። በንጉሡ ስህተት ሀገሪቷ ውድ ዋጋ ከፍላለች። ለዚህ ነው ጠቅላይ ሚኒስቴሩን ጨምሮ የብልጽግና ፓርቲ ባለሥልጣናት ጠዋትና ማታ ባንዳ፣ ባንዳ ሲሉ፥ ግብፅ ሱዳንን ይዛ የምር ከመጣች ሰው ያላሰበውን አሳስበው ለኪሳራ እንዳይዳርጉን የሚፈራው።

    ያም ሆነ ይህ፥ ኃይለ ሥላሴ ለጦርነት ያላዘጋጇትን ሀገር በክፉ ቀን ጥለው ሸሹ። ሐረርጌ ላይም የጂቡቲን ባቡር ሲሳፈሩ ከጦር ሜዳ መሸሻቸውን ለመሸፈን፥ ‘የት ይሄደሉ?’ ብሎ ለጠያቀቸዉ የፈንሳይ ጋዜጠኛ፡ “Je ne suis pas né soldat” (“ወታደር አይደለሁም”) ብለው ያለፉት። ለሳቸዉም ፍትሃዊ ለመሆን፥ የአውሮፓ ዲፕሎማቶች ቢክዷቸውም በዓለም መንግሥታት ማኅበር ላይ የሚያስመካ ሥራ ሠርተዋል። ሆኖም ከጦር ሜዳ የመሸሻቸው ጉዳይ እስከ መንግሥታቸው ፍፃሜ ድረስ እንደ ጥቁር ነጥብ ስትከታላቸዉ ኖራለች። የአርበኞችም ሆነ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ዋናው የተቃውሞ መፈክርም ይህች የሽሸት ጉዳይ ነበረች። ከጣሊያን ወረራ በኋላም ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ በሁለት መሠረታዊ ነገሮች ምክንያት፥ ጋዜጣቸውን “አዲስ ዘመን” ብለው እንደሰየሙ፥ በእርግጥም አዲስ ዘመን፤ ለአዲስቷ ኢትዮጵያ ይፈጠራሉ ብሎ የጠበቁ ብዙ መሆናቸውን ብሎ መገመት አስቸጋሪ አይመስለኝም።

    ለአምስት ዓመታት በእንግሊዝ ሀገር በስደት ሲኖሩ ስለራሳቸው ስህተትም ሆነ የሰለጠነው ዓለም ንጉሦች እንዴት ሕዝቦቻቸውን እንደሚመሩና በዚያም ምክንያት በሕዝቦቻቸው ዘንድ ተከብረው እንዴት እንደሚኖሩ ተምረዋል ብሎ መጠበቅ ይቻል ነበር። ከሁሉም በላይ በጣሊያን ወረራ ምክንያት እሳቸውንም ሆነ ሀገራቸውን ከገጠመው ውርደትና ኪሳራ ይማራሉ ተብሎ ይጠበቅም ነበር። ከሁሉም አልተማሩም። በባሰ ሁኔታና ፍጥነት ወደ ድሮአቸው ተመለሱ። ለዓቢይነት፥ አስተዳደራቸውን የተቃወሙ የራያ ገበሬዎችን (ቀዳማይ ወያኔ የሚባለዉ ነዉ) ከየመን በመጡ የእንግሊዝ አይሮፕላኖች አስደበደቡ። የሪፐብሊካን አስተሳሰብ ነበራቸው የሚባሉትን አርበኛ ደጃዝማች ታከለን (ደጃዝማች ታከለ ወልደሀዋርያት) አሰሩ። እኚህ ሰው ከተደጋጋሚ እስር በኋላ በመጨረሻም ሊይዟቸው ከተላኩ የንጉሡ ወታደሮች ጋር ሲዋጉ ሞቱ። ሌላው ስመጥር አርበኛ የነበሩ በላይ ዘለቀንም ያለርህራሄ ሰቀሉ።

    የአምባሳደር ብርሃኑ ድንቄ ግልፅ ደብዳቤ እንኳን (አምባሳደር ብርሃኑ፤ በአሜሪካ አምባሳደር የነበሩና ንጉሡ የገፉበት መንገድ ዉሎ አድሮ ንጉሡንም ሆነ ሀገሪቷን ለዉርደት እንደሚያበቃ የመጀመሪያ የማስጠንቃቂያ ደወል በአደባባይ የሰጡ ባለስልጣን ነበሩ) አሠራራቸውን አላስለወጧቸውም።

    በፖለቲካ ሥርዓታቸው ላይ በተከታታይ ቦንቦች ፈነዱ። የመጀመሪያዉ ትልቁ ቦንብ በራሳቸው ቤተ መንግሥት ውስጥ የፈነዳው የነመንግሥቱ ንዋይ ያውም የእሳቸውን ክብርና ሞገስ ለመጠበቅ ከፈጠሩት የክብር ዘበኛ ጦር ነበር። ንጉሡ ከክስተቱ ከመማር ይልቅ ጀኔራል መንግሥቱ ንዋይን በሞት ቀጡ፤ የታናሽ ወንድማቸውን ሬሳ እኔን ያየህ ተቀጣ በሚመስል መንገድ በስቅላት ቀጡ። የበሉበትን [ወጭት] ሰባሪዎች ናቸው ብለውም በአዝማሪ አዘለፏቸው።

    ማን እንደመከራቸው ባይታወቅም ትልቁን የመንግሥታቸውን የዲፕሎማሲ ውጤትን ያበላሸውና ለትልቅ ኪሳራ ያበቃንን የኤርትራን ፌዴሬሽንን አፈረሱ። ውጤቱም ሁላችንም እንደምናውቀው የኤርትራ ነፃ አውጪ ግንባር መፈጠር ሆነ። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ኦሮሞዎች የሜጫና ቱለማ ልማት ማኅበር በመፍጠራቸው ጠገቡ ተብሎ መሪዎቹ እነ መቶ አለቃ ማሞ መዘምር ተሰቀሉ፤ ኃይለማርያም ገመዳ እስር ቤት ውስጥ በተፈፀመበት ድብዳባ ሞተ። ጀኔራል ታደሰ ብሩ ሞት ተፈርዶባቸው በአማላጅ ወደ ሐረርጌ በግዞት ተላኩ። እኔ እስከ ማውቀው ድረስ ሁሉም በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ጥያቄ አልነበራቸውም። ውጤቱ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)ን መፍጠር ሆነ። በነገራችን ላይ በእነ ኤሌሞ ቅልጡ በኦነግ ስም የመጀመሪያዋ ጥይት የተተኮሰችው ጀኔራል ታደሰ ብሩ የታሰሩበት ሥፍራ ሐራርጌ ዉስጥ ነበር። በዚሁ ጊዜ ሰፋፊ ማኅበራዊ ፍትህን የሚጠይቁ ተከታታይ ጥያቄዎችም መቅረብ ጀመሩ። እ.አ.አ በ1965 የንጉሡ ፊውዳላዊ ሥርዓት የተመሠረተበት ላይ በመሬት ላራሹ ሰልፍ ድንገተኛ የፖለቲካ ቦንብ ፈነዳ። ከአራት ዓመት በኋላ ደግሞ እስከዛሬ ኢትዮጵያን እያመሰ ያለው በእነ ዋለልኝ መኮንን የብሔረሰቦች ጥያቄ ታወጀ። ይህችኛውን ንጉሡና ሥርዓቱ በቀላሉ የተመለከቷት አይመስልም። ንጉሡ የቀ.ኃ.ሥ ዩኒቨርሲቲ፥ የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ማኅበር ፕሬዝደንት የነበረውን ጥላሁን ግዛዉን በማሰገደል “ልጆቼ” ከሚሏቸው ተማሪዎች ጋር ደም መቃባት ዉስጥ ገቡ። በዚህም የታሪክ ጎማው ወደፊት እንዳይሽከረከር ጣሩ።

    አሳዛኙ ጉዳይ መካሪዎቻቸውም ሆኑ እሳቸው አስተዳደራቸው ለሃያኛዉ ክፍለ ዘመን የማይመጥን መሆኑን፣ በጣም እወዳታለሁ የሚሏትም ኢትዮጵያ በታሪክ ፍራሽ ላይ ተኝታ የምትሸሞነሞን ሀገር መሆኗን አልተረዱም። የኤርትራ ግንባሮች ጥይትም ከረጅም ዘመን እንቅልፋቸው አላነቋቸውም። የባሌና የጎጃም ሕዝብ አመፅም አልቀሰቀሳቸውም። ለዓመታት የቆየው የተማሪዎች ንቅናቄ ጩኸትም አላነቃቸውም። ከኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ በቀጥታ የወጡ የመኢሶንና የኢህአፓ የሶሻሊስት አብዮት ደወልም አላነቃቸውም። በመጨረሻም በመቶ ሺዎች የሚቆጠረው የወሎ ሕዝብ እልቂት እንኳን ከእንቅልፋቸዉ አላበነናቸውም።

    በነገራችን ላይ፥ ብልጡ ደርግ በጠዋቱ ሊያወርዳቸው፣ ማታ ያሳየው የወሎ ሕዝብ እልቂት፥ በአንድ በኩል የንጉሡ ውሻ በጮማ ሥጋ ሲጫወት፣ በሌላ በኩል ደግሞ በረሃብ በተረፈረፈ ሕዝብ ውስጥ ሕፃን ልጅ የሞተች እናቷን ጡት ስታጠባ የሚያሳየዉን የጆናታን ዲምበልቢ (Jonathan Dimbleby, “The Unknown Famine”) ፊልም ነበር። ያንን ፊልም ደርግ በቅድሚያ ንጉሡና የኢትዮጵያ ሕዝብን እንዲያዩ ስለጋበዘ ቴሌቪዥን ያልነበረን የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በስድስት ኪሎና አራት ኪሎ አካባቢዎች ያሉትን ቡና ቤቶችን አጣብበን ስንመለከት ነበር። የንጉሡ ደጋፊዎች እንኳ ጃኖሆይ እንዲህ ጨካኝ ነበሩ እንዴ? የሚሉትን ይዘን ወደ ዶርማችን እንደገባን ትዝ ይለኛል። ምናልባት ከእንቅልፋቸው የነቁት በማግስቱ የደርግ አባላቱ በኩምቢ ቮልስዋገን ከቤተ መንግሥታቸው ወደ አራተኛ ክፍለ ጦር ሲወስዷቸው በሠሩባቸው ድራማ ይመስለኛል። ብልጣብልጦቹ ደርጎች የተጠቀሙት ቮልስ መጀመሪያ መስኮቷ ዝግ ነበር ይባላል።

    ንጉሡ ከውጭ ብዙ ሰው ሲጮህ ተመልክተው፥ “እናንተ ልጆች የሚወደን ሕዝባችን ንጉሤን የት እየወሰዳችሁ ነው እያለ ነዉ” ሲሉ፥ ብልጦቹ ደርጎችም መስኮቱን ከፍተው የሕዝቡን ድምፅ ሲያሰሟቸው ጩኼቱ “ተፈሪ ሌባ፤ ተፈሪ ሌባ” የሚለውን ሰምተው፥ “አይ ኢትዮጵያ ይኼን ያክል በድዬሻለሁ እንዴ?” አሉ ይባላል። በዚህ ሽኝታቸው ድሮ ቤተ ክርስቲያን ሲሄዱ ዳቦ የሚጥሉላት ለማኝ ዳቦዋን ስትጠብቅ፥ ‘ንጉሡ ወረዱ፤ ንጉሡ ወረዱ’ ሲባል ሰምታ፥ ‘ለዚህ ያበቃኸኝ አንተ ነህ!’ ብላ በቮልሷ አቅጣጫ የወረወረችው ዳቦ ብቻ ነበር ይባላል። የንጉሡ ሬሳም ከ17 ዓመታት በኋላ ከመንግሥቱ ኃይለማርያም ሽንት ቤት ሥር ተቆፍሮ እንደተገኘ ይታወቃል። እዚህ ላይ ልብ አድርገን ማለፍ ያለብን የፖለቲካ ቁም ነገር ለ60 ዓመታት ገደማ (የአምስት ዓመቱ የጣሊያን ወረራ እንዳለ ሆኖ) በፈላጭ ቆራጭነት ኢትዮጵያን ሲገዙ የሀገረ መንግሥታቸው ግንባታ ፕሮጀክት በአጉል ምክርም ይሁን በራሳቸው ገታራ አቋም ከሽፎ ሽኝታቸው በለማኟ ዳቦ፣ ቀብራቸው ደግሞ በአሳደጓቸው ወታደሮች ሽንት ቤት ሥር መሆኑ ነው።

    3) አብዮቱ እና የደርግ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ሙከራ

    አዲስቷን ኢትዮጵያን ለመፍጠር ሕዝባዊ አብዮቱ ልዩ ዕድል ፈጥሮ ነበር። አብዮቱ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ማኅበረሰቦች የመጡ የአዲሱ ትዉልድ ምሁራን ድጋፍና ተሳትፎ ነበረው። እንደ አብዮቱ መሪ ወደፊት የመጣውን መንግሥቱ ኃይለማርያምም ‘ቪቫ መንግሥቱ፣ ቪቫ መንግሥቱ!’ ብለን ተቀብለን ነበር።

    የኢትዮጵያ አብዮትን አብዮት ያደረገው የጭሰኝነት ሥርዓትን ያስወገደውና የደርግ እርምጃ (ውለታው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ቢሆንም) እስከዛሬ በኢትዮጵያ የሕዝቦች የትግል ታሪክ ውስጥ ልዩ ሥፍራ አለው ብዬ ባምንም፥ ነገሮችን በቶሎ የሚያዩ ወጣቶች “ተፈሪ ማረኝ፤ የደርጉ ነገር አላማረኝ ” ማለት የጀመሩት ብዙዉም ሳይቆዩ ነበር። በአጭሩ ለማስቀመጥ፥ የደርግ የሥልጣን ፍቅር፣ የመኢሶንና የኢህአፓ አሳዛኝ ክፍፍል፣ የኤርትራ ግንባሮችና የህወሓት የተናጠል የፖለቲካ ፕሮጀክቶች በአብዮቱ መፈንዳት የተፈጠረውን ልዩ ታሪካዊ ዕድል አምክኖታል።

    ደርግ መሃይምነትና የሥልጣን ፍቅር ስለተደባለቀበት፥ የሶሻሊስት አብዮቱን እንደሰው ማሰርና መግደል ወሰደው። በዚህ ሶቭዬት ህብረት ድረስ ሄዶ የሌኒን ሐውልት አይተው የመጡት ባለሥልጣኖቹ ስለሶሻሊዝም የተማርነው ከበሰበሰ ከቡርዧ ቤተ መፃሕፍት ሳይሆን ከምንጩ ከሌኒን ሀገር ነው እያሉ ተዘባበቱ። ካደሬዎቻቸው ድንቅ የሶሻሊስት ዕውቀታቸውን ከፍተኛነት ለማሰየት በሚመስል መንገድ የስታሊን ቀይ በትር ሥራ ላይ ይዋል አሉ። ደርግ የሱማሌ ወረራን፣ የኤርትራ ግንባሮችና የህወሓት እንቅስቃሴዎች በኢትዮጵያ አንድነት እንዲነግድ ልዩ ሁኔታ ስለፈጠሩለት “አብዮታዊት እናት ሀገር፥ ወይም ሞት!” አለ።

    ከኤርትራ ግንባሮች እስከ ኢህአፓ እና መኢሶን (ኢጭአት/ ኦነግን ጨምሮ ሌሎች ድርጅቶች እዚህ መሃል ናቸው) የኢትዮጵያ ሕዝቦች የአንድነትና የአብዮት ጠላቶች ሆነው ልዩ ልዩ ስሞች ተለጣፈበቸው። በአጭሩ የኢህአፓና መኢሶን መከፋፈልም ደርግን ብቻኛ የሀገር አንድነትና የአብዮት ተወካይ አደረገው። ሌሎች ዝርዝሮችን ትቼ ለኢትዮጵያ አንድነትና አብዮት ግንባታ ወሳኝ የሆኑ እርምጃዎችን ላንሳ።

    የደርግ የመጀመሪያው ሊቀ መንበር አማን አንዶም የሚባሉ ኤርትራዊ ጀኔራል ነበሩ። የደርግ ሊቀ መንበር ተብሎ ከደርግ ውጭ የተመረጠትም ለኢትዮጵያ አንድነት ብሎ እስከ ሞቃዲሾ ድረስ ሄዶ ካልተዋጋሁ ብሎ ንጉሡን ያስቸገሩ መኮንን ስለነበሩ ነዉ። በወታደሮቹ ዘንድም ተወዳጅ ስለነበረ በራሳቸው በደርግ አባሎቹ ጥያቄ መጀመሪያ መከላከያ ሚኒስቴር፣ ከዚያም ከደርግ ውጭ የደርግ ሊቀ መንበር የሆነው የተመረጡትና በአደባባይ እስከሚታወቀውም በኢትዮጵያ አንደነት ላይም (መቼም በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ልዩ ፍቅር አለን የሚሉ ብዙ ቢኖሩም፥ ፍቅራቸውን የሚለካልን መሣሪያ በሜዲካል ሳይንስ እስካሁን አልተፈጠረልንም) ምንም ዓይነት ጥያቄ ያልነበራቸውና የኤርትራን ችግር በሰላም ለመፍታት አሥመራ ድረስ ሄዶ ሕዝቡን ያወያዩ ነበሩ። ለኢትዮጵያ ልዩ ፍቅር አለኝ የሚሉ እነሻለቃ መንግሥቱ ኃይለማርያም ግን ጠረጠሯቸዉ፤ በታንክ እቤታቸው ውስጥ ገደሉት። በእኔ ግምት ውጤቱ የኤርትራና የኢትዮጵያን አንድነት መግደል ነበር። በዚህም ኤርትራ የደም ምድር ሆነች። ዛሬ እንዲህ ልንሆን የፈሰሰው የሰው ደም ዋጋም ሆነ ለጠፋው ሀብትና ንብረት ሂሳብ ለፈረደበት ታሪክ መተው ይመረጣል።

    የብሔራዊ አንድነት መንግሥትን ልታመጡብኝ ብሎ መንግሥቱ ኃይለማርያም ሁለተኛውን የደርግ ሊቀ መንበር የነበሩትን ጀኔራል ተፈሪ በንቲን ከደጋፊዎቻቸው የደርግ አባላት ጋር ረሸናቸው።

    ኮሎኔል አጥናፉ አባተንም ቅይጥ ኢኮኖሚ ልታመጣብን ነው ብሎ መንግሥቱ ኃይለማርያም በፀረ-አብዮታዊነት ረሸነዉ። በነገራችን ላይ የመጨረሻ ጭንቅ ሲመጣ መንግሥቱ ኃይለማርያም የአጥናፉን ቅይጥ ኢኮኖሚ ላይ ለመንጠላጠል ሞክሮ ነበር።

    በዛሬው የኦሮሞ ፖለቲካ ውስጥ ልዩ ሥፍራ ያላቸው ጀኔራል ታደሰ ብሩ ለሁለተኛ ጊዜ ሞት ተፈርዶባቸው ተረሸኑ። እኔ መከታተል እስከቻልኩ ድረስ ታደሰ ብሩ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ፍጹም ጥያቄ ያልነበራቸው፤ ለኢትዮጵያ ብሎ ከሰላሌ ጫካ እሰካ ሞቃዲሾ ድረስ ተወስደው የታሰሩ እንግሊዞች ኢትዮጵያን ነፃ እናወጣለን ብለው ሲመጡ ከነሱ ጋር እየተዋጉ የመጡ አርበኛ ነበሩ። ከተራ ወታደርነት እስከ ጀኔራል ማዕረግ ድረስ ሀገራቸውን ያገለገሉም ነበሩ። እግር ጥሏቸው አብዮቱ ውስጥ የገቡት መንግሥቱ ኃይለማርያም ያላርህራሄ ገደሏቸዉ። በነገራችን ላይ ከጀኔራል ታደሰ ብሩ ጋር በፀረ አንድነት ክስ የተገደለ፣ ብዙ ሰው የማያስታውሰው መለስ ተክሌ የሚባል በቀ.ኃ.ሥ ዩኒቨርሲቲ ከተማሪ መሪዎች አንዱ የሆነ የትግራይ ተወላጅ ነበር (በጊዜዉ ከነበረዉ አቋም ተነስቼ፥ ይህ ሰው ቢቆይ ኖሮ የትኛው ድርጅት ውስጥ ሊገባ እንደሚችል ዶክተር አረጋዊን ደግሜ መጠየቄን አስታውሳለሁ)። ይህ ሰዉ ሌላ ተከታይ ቢያጣ ለሩብ ምዕተ ዓመት አከባቢ የምኒልክ ቤተ መንግሥትን ተቆጣጥሮ በፈላጭ ቆራጭነት ሀገሪቷን የገዛው ለገሠ ዜናዊ ስሙን አንስቶ ትግራይ በረሃ ገብቷል። ይህም ደርግ በኢትዮጵያ አንድነት ስም ያመጣብን የታሪክ ዕዳ ነው።

    በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ምንም ዓይነት ጥያቄ እንዳልነበራቸው በተሻለ የማውቃቸውን የመኢሶን መሪዎችን ላንሳ። ለሥልጣን ተብሎ በደርግና ብዙ የፖለቲካ ተቀናቃኞቹ ዘንድ እንደ ኦሮሞ ድርጅት፥ በኦሮሞ ደግሞ እንደነፍጠኛ ድርጅት የሚታየው መኢሶን በዘመኑ በየትኛውም ሚዛን የተሻለ ትምህርት የነበራቸው መሪዎች ነበሩት፤ በስብጥራቸውም ኤርትራዊ የዘር ግንድ አላቸው ከሚባሉት ኅሩይ ተድላ እና አበራ የማነአብ እስከ ሲዳማው እሼቱ አራርሶ የነበሩበት ነው። ሽኩሪ የሚባል አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አብረን የነበርነው ልጅ በስተቀር ሰፊ ተሳትፎ እንደልነበራቸዉ የማዉቀዉ የሱማሌ ምሁራንን ብቻ ነበር።

    የመጀመሪያዉ የመኢሶን ሊቀ መንበር የሰሜን ሸዋ አማራ ከሚባለው የተወለዱ፥ ዶ/ር ወርቁ ፈረደ፣ ሁለተኛው ኃይሌ ፊዳ፣ ሦስተኛው የወሎ አማራ ከሚባለው የመጡ ዶ/ር ከበደ መንገሻ ነበሩ። ሕብረ ብሔር ነን፤ ለሀገረ- መንግሥት ግንባታው የተሻለ ግንዛቤም እዉቀትም አለን ለሚሉ የመኢሶን ምሁራንም ደርጎች ርህራሄ አላደረጉም። በተለይ የመጀመሪያው የኦሮሞ የምሁር ትዉልድ የሚባሉት ኃይሌ ፊዳን ጨምሮ አብዱላህ ዩሱፍ፣ ዶ/ር ከድር መሀመድ፣ ዶ/ር ተረፈ ወልደፃዲቅ፣ ዶ/ር መኮንን ጆቴ የመሳሰሉት ሕበረ ብሔር በሚባለው መኢሶን ውስጥ አልቀዋል። በእኔ እምነት ብዙዎች ሊቀየሙኝ ቢችሉም፥ እንደስማቸው በኢትዮጵያ ምድር ሕብረ ብሔር የነበሩ ድርጅቶች መኢሶንና ኢህአፓ ብቻ ነበሩ። አላስፈላጊ ክርክር ዉስጥ ሳልገባ፥ እኔ እስከ ማምነው ድረስ ኢሠፓ የወታደሮች ፓርቲ ነበር። የኢህአዴግን ምንነት ለብልጽግና አበላት እተዋለሁ። የብልጽግናን ምንነት ደግሞ የታሪክ ፈተናዉን ሲያልፍ ብንነጋገርበት የተሻለ ይመስለኛል።

    ደርግ ሕበረ ብሔር ድርጅቶችን በቀላሉ አንድ በአንድ ቀርጥፎ በላቸው። ኢህአፓን ቁርስ አደረገ፤ መኢሶንን ምሳ አደረገ:: ብሔር ሆኖ ለመውጣት ገና ዳዴ የሚሉትን ወዝሊግንና ማሌሪድን እራት አደረጋቸው። ከደርግ ዱላ የተረፉት በደርግ አስተዋጽኦ ጭምር በተሸለ ሁኔታ ኃይል ሆነዉ የወጡት የብሔር ንቅናቄዎች ናቸው። ኢጭአት (የኢትዮጵያ ጭቁኖች አብዮታዊ ትግል) ወደ ኦነግ ተጠቃልሎ ገብቶ ዛሬ የምናውቀው ኦነግን ፈጠረ። የሱማሌ ድርጅቶች ኦብነግ ዓይነትን ፈጠሩ። የሲዳማ አርነት ንቅናቄ ቢያንስ ዋናው ክንፍ ዛሬ ሲአን (የሲዳማ አርነት ንቅናቄ) የሚለው ሆነ። አፋሮችም የአፋር ግራ ክንፍ አርዱፍ እያሉ በሕይወት ያሉ ድርጅቶች አሏቸው። በጣም የተሳካላቸው የብሔር ንቅናቄዎች በኢትዮጵያና ኤርትራ ላይ ደርግን ለሁለት ቀብረው መንግሥታት ሆኑ።

    የደረግ ዘመንን ስናጠቃልል መረሳት የሌለባቸው ሦስት ዋና ዋና ጉዳዮች፥ ለሥልጣን ብሎ ደረግ ባካሄዳቸው ጦርነቶች፡-

    የሀገረ-መንግሥት ግንባታውን የበለጠ አወሳስቦ መሄዱን፣
    ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በፃፉት መጽሐፍ በትክክል እንዳስቀመጡት፥ ደርግ ትቶት የሄደው በደም እምባ የታጠበች ሀገር መሆንዋን፣
    በሀገር አንድነት ስም ባካሄደው ትርጉም-የለሽ ጦርነት የባከነው የሀገር ሀብት ብቻ ሳይሆን በዓለም ትልቋ ወደብ-አልባ ሀገር ኢትዮጵያን ትቶ መሄዱን ነዉ።

    ደርግ ለ17 ዓመታት የተጫወተዉ የአጥፍቶ መጥፋት ፖለቲካን እንደ ኑዛዜም፣ እንደ ቁጭትም የደርግ ከፍተኛ ባለሥልጣን የነበሩት ኮሎኔል ፍስሃ ደስታ (ኮ/ል መንግሥቱ ኃይለማርምም ሆነ ሻምበል ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ እድፋቸውን ከታጠቡበት በጣም ይሻላል) በፃፉት መጽሐፍ ልዝጋ።

    የኢህአፓ ወጣቶችን የትግል ስሜት፣ የመኢሶን መሪዎች ዕውቀትና የእኛን የወታደሮቹን የሀገር ወዳድነት ብንጠቀምበት ኖሮ ሀገራችን እንዲህ አትሆንም ማለታቸውን እስር ቤት ሆኜ ማንበቤ ትዝ ይለኛል። ምክራቸው ለጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይም የሚሆን ይመስለኛል። በነገራችን ላይ በታሪክ አጋጣሚ ወደ አስር ወሮች ገደማ በኢህአዴግ እስር ቤት የተኛሁበት አልጋ ኮ/ል ፍስሃ ደስታ ይተኙበት እንደነበረ ሰምቻለሁ።

    4) የኢህአዴግ ዘመን የሀገረ-መንግሥት ግንባታ

    ለአራተኛ ጊዜ የሀገራችን ፖለቲካን ማሰልጠንና የተሻለ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ዕድል ያመለጠን የኢህአዴጉ ዘመን ነው (ይህ የመለስ እና የኃይለማርያም ዘመንን ይጨምራል)። የኢህአዴግ ዘመን ሌላው ቢቀር የብሔረሰቦች ጥያቄን ለሁሉም ሕዝቦች ተቀባይነት ባለው መንገድ ይመልሳል ብሎ (እኔን ጨምሮ) የጠበቁ ብዙ ናቸው። ይህም ለሀገረ-መንግሥት ግንባታ የተሻለ ዕድል ይፈጠራል ተብሎም ተገምቶ ነበር።

    ገና የሽግግር መንግሥቱ ሲመሠረት፥ የኢህአዴግ ባለሥልጣናት እንደግል ሠርጋቸው የፈለጉትን ጠርተው፣ ያልፈለጉትን በመተው የሠሩት የፖለቲካ ቲያትር ጫካ ሆነው ስደግፋቸው ከነበሩት የኢህአዴግ መሪዎች ተለየሁ። እኔም ብቻ ሳልሆን ብዙ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ጓደኞቼ በዚህ ጊዜ የተለዩዋቸዉ ይመስለኛል። ኢህአዴግ መጀመሪያ በጦርኛነት፤ ቀጥሎ ደግሞ በዘመኑ ቋንቋ የሽብርተኝነት ታርጋ እየለጠፈ ለ27 ዓመታት ሕዝብና ሀገርን አመሰ። ዝርዝር ነገሮች ውስጥ ሳልገባ፥ በኦሮሚያ እና በሱማሌ ክልሎች፤ በሲዳማ፣ በሀዲያ፤ በወላይታ፣ በጋምቤላ፣ በአፋር፣ ቁጥራቸውን የኢህአዴግ ባለሥልጣናት እንኳ የማያውቁት ሕይወት ጠፋ። የአፍሪካ መዲና የምትባለው አዲስ አበባ/ፊንፊኔም ሆነች የኢህአፓን ጠበል በቀመሱ ብአዴኖች የሚመራው የአማራ ክልልም ውሎ አድሮ ከኢህአዴግ ዱላ አልተረፉም።

    በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ርዕዮተ ዓለም (ነገርየው መሬት ላይ ሲፈተሽ፥ የአብዮታዊነትም የዴሞክራሲያዊነትም ባህርይ አልነበረውም) የተተበተበው የሞግዚት አስተዳደር እውነተኛ የፌዴራል ሥርዓት ሊሆን አልቻለም። የሕዝቦችን እራስን በራስ ማስተዳደር ጋር ምንም ግንኙነት ያልነበረው፥ ጆርጅ ኦርዌል የእንስሳት እርሻ (George Orwell, “Animal Farm”) በሚለዉ መጽሐፉ ላይ፥ ሁሉም እንስሶች እኩል ናቸው፤ አንዳንድ እንስሶች የበለጠ እኩል ናቸው “All animals are equal, but some are more equal than others” ከሚለው ያለፈ የፖለቲካ ፋይዳ አልነበረውም። ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ተብዬዎቹም ከ97ቱ በስተቀር ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መፍጠር ይቅርና ቅርጫ እንኳ ሊ ሆኑ አልቻሉም። ዉጤቱም ዴሞክራሲያዊ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ዕድል መጨናገፉ ብቻም ሳይሆን ለ27 ዓመታት ውድ የሕይወት ዋጋ ጭምር ሲያስከፍለን ኖሯል። በዚህም ምክንያት የታሪክ ጣጣችንን አስተካክለን በእኩልነት ላይ የተመሠረተ ዴሞክራሲያዊ ፌዴራሊዝም የመፍጠር ተስፋችን ሕልም ሆኖ ቀርቷል።

    5) በማምለጥ ላይ ያለ አዲስ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ሙከራ

    አሁን እየገጠመን ያለውን የታሪክ ፈተናን ለማለፍ፥ ጨክነን በቁርጠኝኘት ብሔራዊ መግባባት ውስጥ መግባት ወይም ኢትዮጵያን እንደ ሀገረ-መንግሥት የምታበቃበት የሚጨምር ቀውስ ውስጥ መግባት ይመስለኛል። እዚህ ላይ የሌሎች ሀገሮችን ፖለቲካ በድኅረ ቅኝ ግዛት ዘመን ብቻ እንኳን በመቀኛት ብጀምር፥ ችግሮቻቸውን ለመፍታት በቁርጠኝነት የሠሩት ተሳክቶላቸዋል። ያንን ያልቻሉት ወይ ፈርሰዋል ወይም አሁንም በቀውስ ውስጥ እየዳከሩ ነዉ። ቅኝታችንን በላቲን አሜሪካ ብንጀምር፥ ቀዉስ ገጥሟቸዉ አነ አርጀንቲና፣ ቺሌ፣ ፔሩ፣ ኒካራጓ፣ ኮሎምቢያ የመሰሰሉ ሀገሮች በተለያየ ደረጃ ፖለቲካቸውን ያስተካከሉ ሀገሮች ናቸው። ከ60 ዓመታት በላይ ለልዕለ ኃያሏ አሜሪካ ሳትበገር በአሜሪካ አፍንጫ ሥር የኖረችው አስደናቂዋ ሶሻሊስት ኩባና በአሜሪካ ጣልቃ ገብነት ምክንያት አሁን በሁለት ፕሬዝዳንቶች የምትገዛዋ ሶሻሊስት ቬኔዙዌላም በዚሁ ክፍለ ዓለም ይገኛሉ። በአውሮፓ ፖርቹጋል፣ ስፓኝ፣ ግሪክ፣ ፖለቲካቸዉን ማስተካከል ችለዋል። ዩጎዚላቪያ ውድ ዋጋ ብትከፍልም ከመፍረስ አልደነችም። ሶቭዬት ህበረትና (ግማሽ አውሮፓ ነች) ቼኮዝላቫኪያ በሰላማዊ መንገድ ፈርሰዋል። በኤዥያ፥ ኔፓል የፓለቲካ ችግርዋን በብሔራዊ መግባባት ስትፈታ፥ፓኪስታን፣ ቬየትናም፣ ካምቦዲያና ላኦስ ደግሞ ችግሮቻቸውን በጦርነት ፈተዋል። አፍጋኒስታን፣ ኢራቅ፣ ሶሪያና የመን አሁንም እየቀወሱ ነው። ወደ አፍሪካችን ስንመጣ፥ ደቡብ አፍሪካና ጋና ከመሳሰሉት በስተቀር አብዘኛዎቹ በይስሙላ ምርጫ ላይ የተመሠረቱ አምባገነን መንግሥታት ሲሆኑ፥ የአፍሪካ ሕብረትም የዲክታተሮች ማኅበር (trade union of dictators) ከመሆን አላለፈም (በኢህአዴግ ጊዜ የተከሰስኩበት አንዱ ወንጀሌ የአፍሪካ መሪዎችን ተሰደብክ የሚል ነበር)። ሱማሊያና ሊቢያ ፈረንጆች የወደቁ መንግሥታት (failed states) የሚሏቸው ሲሆኑ፤ ሩዋንዳ ጊዜውን ጠብቆ የሚፈነዳ ሌላ ቦንብ የምትጠብቅ ይመስለኛል።

    በዚህ የአፍሪካ ፖለቲካ ምስቅልቅል ጉዞ ውስጥ አንዱ የሚገርመኝ ላለፉት 60 ዓመታት ፖለቲካቸውን ማስተካከል አቅቷቸው በቀውስ ሲናጡ የኖሩ ሁለት ሀገሮች፥ በተፈጥሮ ፀጋ እጅግ ሀብታሟ የኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፑቢሊክና የሦስት ሺህ ዓመታት ዕድሜ አለኝ የምትለዋ ድሃዋ ኢትዮጵያ መሆናቸው ነው።  ከንጉሡ ዘመን ጀምሮ ይህንኑ የሀገራችንን የፖለቲካ እንቆቅልሾችን የተከታተለ፣ ያጠና፣ ያስተማረና ብዙ ጽሑፎችን የፃፈበት ጆን ማርካከስ (John Markakis) የሚባል ፈረንጅ፥ የታሪክና ፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፌሴር “Ethiopia: The Last Two Frontiers” (የኢትዮጵያ፥ የመጨረሻዎቹ ሁለት ድንበሮች) ብሎ ፅፏል። ምሳ ጋብዞኝ መፅሐፉን ለዶ/ር ዓቢይ ስጥልኝ ብሎኝ፥ ዶ/ር ዓቢይ ያንብበው አያንብበው ባላውቅም፥ እሳቸውን ማግኘት ለሚችል ለኦፒድኦ ባለሥልጣን ልኬላቸው እንደነበርም አሰታዉሰለሁ። መፅሐፉ በአጭሩ የኢትዮጵያ መሪዎች የሀገረ-መንግሥት ግንባታ የንጉሦቹ ሞዴል (the Imperial model) ፣ የደርግ የሶሻሊስት ሞዴልና የኢህአዴጉ ፌዴራሊስት ሞዴል በሙሉ ከሽፈዋል ይላል። የከሸፉበትም ዋናዉ ምክንያት የባለጊዜ ገዥዎችን ሥልጣን ለማሳካት የተገፋበት መንገድ የኢትዮጵያ ሕዝቦችን እኩልነት ያላጎናፀፈና የልማት ጥማታቸውንም ያላረካ በመሆኑ ነው ይላል።

    ይህ የፈረንጅ ምሁር እንዳለው፥ ፖለቲካችንን ማሰልጠን ባለመቻላችን ሚሊየኖች ሕይወታቸውን አጥተዋል፤ ሚሊዮኖች ከቀዬያቸው ተፈናቅለዋል፤ ሚሊዮኖችም ተሰደዋል። እኔም ከላይ ባነሳሁት ከዚሁ ምሑር ዕይታ ተነስቼ ሀገራችን ስለገባችበት የፖለቲካ ቅርቃርና በብሔራዊ መግባባት አንፃር ከቅርቃሩ ለማውጣት በሌኒን ቋንቋ ምን መደረግ አለበት (What is to be done?) የሚለውን መሠረታዊ ጥያቄ የሀገራችን ፖለቲካ እስከገባኝ ድረስ ልመልስ።

    1. መሠረታዊ ችግራችን በታሪክ አጋጣሚ ሥልጣን ላይ የወጡ መሪዎቻችን ሀገርን የመምራት ሕልማቸው፤ ሥልጣንን ጨምድዶ ከመቆየት ሕልማቸው ጋር ሁሌ ስለሚጋጭባቸው ነው። ለሕዝብ አለን ከሚሉት ፍቅር የሥልጣን ፍቅራቸው ስለሚበልጥባቸው ነው። ለዚህ ነው ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ የሚወደንና (ሕዝቡ ምን ያከል እንደሚወደቸዉ እንዴት እነዳወቁ ባናዉቅም) የምንወደው ሕዝባችን ሲሉ ኖረው ለ60 ዓመታት ገደማ የገዟትን ኢትዮጵያ ለ20ኛዉ ክፍለ ዘመን ሳያበቁ ከዓለም ሀገሮች ጭራ ደረጃ ትተዋት የሄዱት። የሕዝብ ፍቅራቸውንም ደረጃ በረሃብ በመቶ ሺህዎች ያለቀው የወሎ ሕዝብ ይመሰክራል። ይህን የመሳሰሉ የመሪዎቻችን ባዶ የሕዝብና የሀገር ፍቅር፥ የንጉሡ ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ፣ የመንግሥቱ ኃይለማርያም አብዮታዊት እናት ሀገር ወይም ሞት የመለስ ዜናዊ በቀን ሦስት ጊዜ የሚመገቡ ዜጎችን እፈጠራለሁ ወ.ዘ.ተ መሸፈን አይችልም። ለዚህ አሁን ያሉ መሪዎቻችንም ሆኑ ተስፈኛ መሪዎች ይህንን የታሪክ እውነታ በውል እንዲገነዘቡት እፈልጋለሁ።
    2. የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችና የተቀሩት ልሂቃን በተለያየ ደረጃ የሚጋጩ ሕልሞቻቸውን ይዘው መጓዛቸው ነው። ከመኢሶንና ኢህአፓ ዘመን እስከዛሬ ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶቻችንና መሪዎቻቸው ይህንን እውነታ በውል መገንዘብ ይኖርባቸዋል። የሕልሟን ጉዳይ በፈንጆቹ አባባል ከዜሮ ድምር ፖለቲካ (zero-sum game politics) የመውጣቱን ጉዳይና የፖለቲካ ፍላጎቶቻቸዉን በገደብ የማድረጉን ነገር በጥብቅ እንዲያስቡበት እመክራለሁ። ዋና ጉዳያችን ሥልጣን ሆኖ ከፊንፊኔ እስከ መቀሌ ባንዳ፣ ባንዳ እየተባባሉ መካሰሱ ሕዝባችንን ከማደናገር በላይ ብዙ የፖለቲካ ትርፍ የለውም። ዛሬ በአሜሪካና በአውሮፓ በሚደረጉ ሰልፎች ላይ በአንድ እጅ እስክንድር ነጋ ይፈታ፣ በሌላ እጅ ጃዋር ሽብርተኛ ነው የሚሉት መፈክር ዓይነቶቹ ለሀገረ-መንግሥት ግንባታችንም ሆነ ለብሔራዊ መግባባት ሥራችን ብዙ የሚጠቅሙ አይመስሉኝም። በእኔ በኩል እንዲህ ዓይነቱ ጉዳይ ስላስቸገረኝ ነበር በ2008 በፃፍኩት መፅሐፍ ላይ ለቡዳ ፖለቲካችን መላ እንፈልግ ብቻ ሳይሆን የሚጋጩ ሕልሞች ሊታረቁ ወይስ ኢትዮጵያን ሊያፈርሱ በሚል ግልፅ ጥያቄ የደመደምኩኝ። ለእኔ መፍትኼው ለአዲስቷ ኢትዮጵያ ፈጠራ የሚሆን አዲስ ማኅበራዊ ውል (new social contract) ከመፈራረም ውጭ የተሻለ የማጂክ ፎርሙላ ያለን አይመስለኝም። ይህንን እውነታ የምኒልክ ቤተ መንግሥት ያሉ የብልጽግና ወንድሞቻችንም ሆኑ ከአዲስ አበባ/ፍንፍኔም እስከ አውሮፓና አሜሪካ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ግፋ በለው የሚሉ ሁሉ እንዲረዱልኝ አደራ እላለሁ። በቅርብ ጊዜ በተፈጠረው ቀውስ በሁሉም በኩል ላለቁትም የተሻለ የሐዘን መግለጫ የሚሆነውና ዕንባቸውን የሚያብሰው የችግሮቻችን ምንጭ አዉቀን ዘለቂ መፍትኼ ስንፈልግ ይመስለኛል።
    1. ከላይ ካነሳኋቸው ሁለት ነጥቦች ጋር ተያይዞ ሺህ ጊዜ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ እየተባለ በሕዝብ ላይ የሚሠራዉ የፖለቲካ ትያትር መቆም አለበት።
      የንጉሡ ዘመን የምርጫ ትያትሮች፣ የደርግ ዘመን የምርጫ ትያትሮች፣ የኢህአዴግ ዘመን የምርጫ ትያትሮች በግልፅ ቋንቋ ለማስቀመጥ፥ ሲያንሱ በዴሞክራሲ ስም የተቀለዱ  ቀልዶች፣ ሲበዙ ደግሞ በኢትዮጵያ ሕዝቦች ላይ የተሠሩና ታሪክ ይቅር የማይላቸው ወንጀሎች ነበሩ። በሰለጠነው ዓለም የሕዝብን ድምፅ ከመስረቅ በላይ ወንጀል የለም። እዚህ ላይ ሁለት ነገሮችን አስታውሼ ልለፈው። በ“ኢህአዴግ-1” ዘመን አቶ በረከት፥ “ኢህአዴግ ከስድስት ሚሊዮን በላይ አባላት አሉትና በዝረራ ያሸንፋል” ብሎ ሲያስቸግረኝ፤ አቶ በረከት፥ “ኢህአዴግ ሁለት ምርኩዞች አሉት፤ አንደኛው ምርጫ ቦርድ ነው። ሁለተኛው ጠመንጃችሁ ነው። ሁለቱን ምርኩዞቻችሁን አስቀምጣችሁ ተቃዋሚዎችን ካሸነፋችሁ፥ እኔ በግሌ እናንተ የምትሉትን 20 ና 30 ዓመታት ብቻ ሳይሆን ለሃምሳ ዓመታት እንድትገዙን እፈርምልሀለሁ” እንዳልኩት አሰታዉሰለሁ። በ“ኢህአዴግ-2” ጊዜ ደግሞ ዶ/ር ዓቢይ በጠሩት ድንገተኛ ስብሰባ ላይ ገለልተኛ የሆነው ጠቋሚ ኮሚቴ ስምንት ሰዎች አጣርቶ ስላቀረበ አራት ሰዎች መመረጥ ስላለባቸው በተጠቆሙት ሰዎች ላይ አስተያየት ስጡ አሉን። ሌሎች ስብሰባው ላይ የተገኙ የየድርጅት መሪዎች ያሉትን ብለዋል፤ እኔ ጨዋታው ስላላማረኝ፥ “አብዛኛዎቹን ዕጩዎች ብዙዎቻችን አናዉቃቸውምና ከየት እንደመጡ እንኳ ለማወቅ የ24 ሰዓት ጊዜ ስጡኝ” ብዬ አጥብቄ ጠየኩኝ። ዶ/ር አቢይ ‘አይቻልም’ አሉ። ነገ የምናገረው እንዳይጠፋኝና ለታሪክም ቢሆን ተአቅቦ (reservation) መዝግቡልኝ ማለቴ ትዝ ይለኛል። ምስክሮችም አሉኝ። የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መጥቶ የምርጫ ቦርድ ኃላፊዎች የምርጫ ጊዜውን ሰሌዳ ለማስተላለፍ በጠሩት የምክክር ስብሰባ ላይ እንደተናገርኩኝ፥ መለኮታዊ ጣልቃ ገብነት (divine intervention) ነው እንዳልኩኝ ምርጫው ባይተላለፍ ኖሮ የአዲሱ ምርጫ ቦርድ አካሄድ ሌላ ከበድ ቀውስ ሊያስከትል ይችል እንደነበረ ዛሬ ላይ ሆኜ በእርግጠኝነት መናገር እችላለሁ። ይህንኑ ደግም ብዙ ጊዜ በታጋይነቷ ለምናውቃት ክብርት ብርቱካንም ጭምር መናገሬን አስታውሳለሁ።

    ስለሆነም የሚመጣውን ምርጫ አዲስቷን ዴሞክራትክ ኢትዮጵያ እንድትወለድበት ካላደረግን፥ የንጉሥ የማክያቬሊ ምክር፣ የመንግሥቱ ኃይለማርያም፣ የጆሴፍ ስታሊን ቀይ በትር፣ የመለስ ዜናዊ፣ የሊቀ መንበር ማኦ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ውሰት፣ ኢትዮጵያን ለመለወጥ የታሪክ ፈተናውን ለማለፍ እንዳላስቻላቸዉ፥ የዶ/ር ዓቢይም የመደመር የፖለቲካ ቀመር አዛውንቱ የፈረንጅ ምሁር የሚለውን የኢትዮጵያ ፖለቲካ የመጨረሻ ሁለት ድንበሮችን የሚያሻግረን አይመስለኝም። እሱን ካልተሻገርን ደግሞ ሁሌም እንደምለው ለሁላችንም የምትሆን ዴሞክራትክ ኢትዮጵያ የምትፈጠር አይመሰልኝም።

    ከማጠቃለሌ በፊት የብሔረታዊ መግባባቱ የፖለቲካ ጥረታችን ይሳካ ዘንድ መፍትሄ የሚሹ ቁልፍ ጉዳዮች ላስቀምጥ፦

    1. ያለ ሀገራዊ ስምምነት በዋናነት በአንድ ቡድን ሕልምና ፍላጎት (በተለይ የአንድ ቡድን ፍኖተ-ካርታ /road map/) የመመረቱ ጉዳይ ለዉጡን አጣብቂኝ ዉስጥ ማስገበቱን የማወቅ ጉዳይ፤
    2. ለውጡን ለማምጣት በዋናነት የላቀ አስተዋጽኦ ያላቸው ኃይሎች (ለምሳሌ እንደ ኦሮሞ ቄሮ ዓይነቶቹ) ወደ ዳር የመገፋታቸው ጉደይ፤
    3. ለውጡን እየመራ ያለው ከራሱ ከኢህአዴግ የወጣ ቡድን ቢሆንም፥ በለውጡ ምንነት፣ ፍጥነት፣ ስፋትና ጥልቀት ላይ የተለያዩ የኢህአዴግ ክንፎች ስምምነት ማጣታቸውና በዚህም ምክንያት እያመጣ ያለው አደገኛ ሁኔታ፤
    4. በሚጋጩ ሕልሞቻችን ምክንያት ላለፉት 50 ዓመታት መፍትሄ ያላገኘንለት የመከፋፈል ፖለቲካችን (political polarization) ጉዳይ፤
    5. ዴሞክራሲያዊ ለውጡ ለአብዛኛዉ የኢትዮጵያ ሕዝቦችና የፓለቲካ ኃይሎች ተቀባይነት ያለዉ፣ ሰላማዊና የተሳካ እንዲሆን የጋራ ፍኖተ-ካርታ (roadmap) የመቀየስ አስፈላጊነት ጉዳይና፤ የተቀየሰዉን በጋራ ሥራ ላይ የማዋል ጉደይ፤
    6. ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ማለት በእርግጥም በሕዝቦች ይሁንታ ላይ የተመሠረተ የፓለቲካ ጨዋታ መሆኑን የመረዳት ጉዳይ፤
    7. ሀገራችን እዉነተኛ ዲሞክራሲያዊ የፈድራል ሥርዓት ያስልጋታል ስንል፥ ከሕልሞቻችን በሻገር በሕዝቦቻችን ፍላጎት ላይ የተመሠረተ የፖሊቲካ ሥርዓት መሆኑን የማረጋገጥ ጉዳይ፤
    8. ብሔራዊ መግባባቱ በተሻለ መንገድ የሚሳካው፥ በደቡብ አፍሪካ እና ኮሎምቢያ በመሰሰሉት ሀገሮች እንዳየነው የፖለቲካ እስረኞችንና የጫካ አማፅያንን መጨመርን የማስፈለጉ ጉዳይ፤
    9. የተሳካ ብሔራዊ እርቅን ለመምጣት ከሥልጣን በሻገር የምር የፖለቲካ ቁረጠኝነት (political will) የማስፈለጉ ጉዳይ፤
    10. ስለኢትዮጵያ አንድነት ያለን ግንዘቤ ከፊታዉራሪ ሀብተጊዮርጊስ እይታ የሰፋና ለሀገሪቷ ያለን ፍቅርም ገደብ የማድረጉ ጉደይ ናቸዉ።

    በመደምደሚያዬም፥ እዚህ ያደረሰንን የሀገራችንን ፖለቲካ ጉዞ ታሪክ ወደኋላ እያየሁ፥ የወደፊቱን የሀገራችንን ዕጣ ፈንታንም እያማተርኩ ለጠቅላይ ሚኒስትሩም፣ ለሁላችንም የታሪክ የግርጌ ማስታወሻ ልተዉ።

    በቅርብ ቀን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‘ኢትዮጵያ አትፈርስም፤ ኢትዮጵያን የሚያፈርሷት እኛን ቀድሞ ሲያፈርሱ ነው፤ ኢትዮጵያን ለማፍረስ አይፈቀድላቸውም’ ሲሉ አዳምጫለሁ። ሀገርን ለመፍረስ የሚፈልጉ ኃይሎች መጀመሪያኑ ፈቃድ ይጠይቃሉ፤ አይጠይቁም የሚለዉን ክርክር ውስጥ ሳልገባ፥ በጨዋ ቋንቋ ንግግራቸውን አልወደድኩላቸውም። ንግግራቸውንም ተከትሎ የኢሳት ቴሌቪዥን የፖለቲካ ተንታኞች የሚታወቁ የአዛውንት ምሁርን በመጥቀስ (ይህኑን ምሁር መንግሥቱ ሀይለማርያምም ያዉቃል ብለን ስለተሠሩ የንጉሡ ባለስልጣኖች ምክር ጠይቀነዉ፥ ጠመንጃዉ በእናንተ እጅ ነዉ፤ የምን ምክር ትጠይቁናላችሁ ብሎኛል ማለቱን አንብቤአለሁ) ዶ/ር ዓቢይ ጥሩ ይዘዋል፤ ሕጉንም ሰይፉንም እየተጠቀሙ ነው ያሉት የበለጠ ሥጋት ፈጥሮብኛል። እዚህ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ሁላችንም ደጋግመን ማሰብ ያለብን ጨዋታው ከተበላሸ አብዛኛው ዓለምን በሰዓታት ውስጥ ወደ አመድነት የሚለወጥ ወይም ሕይወት-አልባ ሊያደርግ የሚችል የኒዩክሊየርር መሣርያ የታጠቀ፣ ነፍሷን ይማርና የሶቭዬት ህብረት ሠራዊት ዓይኑ እያየ ሀገራቸው መበቷን ነው። የሀገራችንን ፖለቲካ በጋራ አስተካክለን ሁላችንንም በእኩልነት የምታስተናግድ ዴሞክራቲክ ኢትዮጵያን ለመፍጠር እግዚአብሔር ይርዳን እላለሁ።

    ዋቢ መፃሕፍት:

    1. Bahiru Zewde (1991) A History of Modern Ethiopia, 1885 -1991.
    2. Gebru Tareke (1996) Ethiopia: Power and Protest, Peasant Revolts in the Twentieth Century.
    3. John Markakis, (2011) Ethiopia: The Last Two Frontiers.
    4. Merera Gudina, (2002) Ethiopia: Competing Ethnic Nationalisms and the Quest for Democracy, 1960-2000.
    5. Teshale Tibebu, (1995), The Making of Modern Ethiopia, 1896-1974.

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forumsላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    በኢትዮጵያ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ የታሪክ ዳራ… መረራ ጉዲና (ፕሮፌሰር)

    Anonymous
    Inactive

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ በሁለተኛ ዲግሪ ያሰለጠናቸውን 419 ተማሪዎችን አስመረቀ

    ደሴ (ኢዜአ/ወ.ዩ.) – ወሎ ዩኒቨርሲቲ (ወ.ዩ.) በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች በሁለተኛ ዲግሪ (Masters program) ያሰለጠናቸውን 350 ወንድ 69 ሴት በድምሩ 419 ተማሪዎችን ነሐሴ 2 ቀን 2012 ዓ.ም. ተማሪዎቹ ባሉበት ቦታ በኦንላይን (online) አስመረቀ።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን በምረቃው ሥነ ሥርዓት ወቅት እንደተናገሩት ተቋሙ በየዓመቱ በርካታ ተማሪዎችን አሰልጥኖ ቢያስመርቁም ዘንድሮ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ (ኮቪድ-19) ከፍተኛ ጫና አሳድሯል። በወቅታዊ የወረርሽኝ ምክንያት የመማር ማስተማሩ ሥራ ቢቋረጥም አጋዥ ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅሞ ተማሪዎችን በማስተማር የጀመሩትን ትምህርት እንዲያጠናቅቁ መደረጉን አስታውቀዋል።

    ተማሪዎች በመደበኛ፣ በማታ እና ሳምንታዊ መረሃ ግብር ትምህርታቸውን የተከታተሉ መሆናቸውን አመልክተው ትምህርታቸውን አጠናቀው ከተመረቁት መካከል 69 ሴቶች እንደሚገኙበት ዶ/ር አባተ ገልጸዋል።

    ዶ/ር አባተ የዘንድሮ ተመራቂ ተማሪዎች ዓለም በኮረና ቫይረስ ወረርሽኝ በተናወጠበት እና የታላቁ ሕዳሴ ግድብ የውሃ ሙሌት በተከሄደበት ዓመት መመረቃቸው ታሪካዊና ልዩ ያደርጋቸዋል ብለዋል። አያይዘውም፥ ፕሬዝዳንቱ ዩኒቨርሲቲው ዕቅዱን በአዲስ መልክ በማዋቀር ሀገር-በቀል እውቀቶችን ከምርምር ጋር በማቀናጀት ለውጥ በሚያስመዘግብ መልኩ ለመሥራት የተዘጋጀ በመሆኑ፥ ተመራቂዎች በቆይታቸው ያገኙትን እውቀት በሚሰማሩበት የሙያ ዘርፍ ተግባራዊ ከማድረግ ጀምረው አዳዲስ ምርምሮችን ከዩኒቨርሲቲው ጋር የመሥራት ዕድል ሊኖር እንደሚችል ጠቁመዋል።

    ተመራቂዎች በትምህርት ቆታቸው ያገኙትን እውቀት ወደ ተግባር ቀይረው ሀገራቸውን እና ሕዝባቸውን እንዲያገለግሉና የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን በመከላከሉም የድርሻቸውን እንዲወጡ ዶ/ር አባተ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ ነሐሴ 2 ቀን ያስመረቃቸው ተማሪዎች 12ኛ ዙር ሲሆኑ፥ በሕግ፣ ተፈጥሮ ሳይንስ፣ ሕክምና እና ጤና ሳይንስ፣ ማኅበራዊ ሳይንስ፣ የተፈጥሮ ቀመር፣ ቢዝነስ እና ምህንድስና የሰለጠኑ ናቸው።

    የደሴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ አበበ ገብረ መስቀል በበኩላቸው፥ ምሩቃን በቆይታቸው በቀሰሙት እውቀት በታማኝነት እኩል ሕብረተሰቡን ሊያገለግሉ ይገባል ብለዋል። የኢትዮጵያ የአንድነትና የሰላም እሴት ተጠብቆ ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፍም በእውቀት ላይ የተመሠረተ እገዛ በማድረግ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባም አቶ አበበ አመልክተዋል።

    ከተመራቂዎች መካከል መላኩ በላይ በሰጠው አስተያየት ምንም እንኳ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ (ኮቪድ-19) በትምህርቱ ዘርፍ ጫና ቢያሳድርም፥ በቴክኖሎጂ ታግዘው በዕለቱ ለመመረቅ በመብቃቱ መደሰቱን ገልጿል። በተማረበት ሕክምና እና ጤና ሳይንስም ሕብረተሰቡን በታማኝነት ለማገልገል መዘጋጀቱን ጠቁሞ፥ “በተለይ ኮሮና ቫይረስን ለመከላከል የድርሻዬን እወጣለሁ” በማለት አክሏል።

    ሌላዋ የፕሮጀክት አመራር (project management) ተመራቂ ገነት ኪሮስ በበኩሏ፥ በሙያዋ ሕዝቡን በማገልገል የበኩሏን አስተዋጽኦ እንደምታደርግ ተናግራለች። ወቅቱ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ዓለምን የሚያስጨንቅበት ቢሆንም በተለያዩ ቴክኖሎጂዎች ታግዛ ለዚህ በመብቃቷ መደሰቷን ገልጻለች።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)/ ወሎ ዩኒቨርሲቲ (ወ.ዩ.)

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ በሁለተኛ ዲግሪ ተማሪዎችን አስመረቀ

    Semonegna
    Keymaster

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ ባደረገው ድጋፍ የተቋቋመው የባቲ ለይቶ ማቆያ ማዕከል ተመረቀ

    (ወሎ ዩኒቨርሲቲ) – ከአፋር ክልልና ከጅቡቲ የሚመጡ መንገደኞችን ለይቶ በማቆየት የኮረና ቫይረስ ወረርሽኝ ስርጭትን ለመከላከል በባቲ ወረዳ የተቋቋመው የለይቶ ማቆያ ማዕከል (quarantine center) ተመርቋል።

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ ባደረገው ድጋፍ የተቋቋመው የባቲ ለይቶ ማቆያ ማዕከል ከሰኔ 8 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል። ማዕከሉን የወሎ ዩኒቨርሲቲ፣ የኦሮሚያ ብሔረሰብ ዞን አስተዳደር፣ የባቲ ወረዳና ከተማ አመራሮች፣ በጎ ፍቃደኞችና የሀገር ሽማግሌዎች በጋራ ተመርቋል።

    የቅኝት አምባ፣ የወሎየነት ተምሳሌትና የንግድ የመተላለፊያ አውድ ባቲ በታሪክ አጋጣሚ ከጅቡቲ አፋርን አቋርጠው በሚመጡ መንገደኞች የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መተላለፊያ ኮሪደር ልትሆን ትችላለች የሚል ስጋት ተጭኖባታል። ከጅቡቲና አፋር ክልል እያቋረጡ የሚመጡ መንገደኞች ምርመራና ክትትል ሳይደርግላቸው ከመሀል ሀገር እንዳይገቡ ለማድረግ የለይቶ ማቆያ ማዕከል በባቲ ወረዳ ማቋቋም ተገቢ መሆኑን በጥናት ለይተናል ያሉት የወሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን ባቲ ወረዳን ማዳን ወሎን፣ ሰሜን ሸዋን በአጠቃላይ ከቫይረስ ስርጭት ሀገርን መታደግ ነው ብለዋል።

    አያይዘውም ፕሬዚዳንቱ የኦሮሚያ ብሄረሰብ ዞንና የባቲ ወረዳ አስተዳደር ዩኒቨርሲቲው የሰጣቸውን የለይቶ ማቆያ ቁሳቁስ በቀናት ውስጥ ሁሉን ነገር አዘጋጅተው ለአገልግሎት ዝግጁ ማድረጋቸው የአመራሩ፣ የኮሚቴውና የማኅበረሰቡ የቅንጅት ውጤት ነው ሲሉ ተናግረዋል።

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ በደሴና ኮምቦልቻ ካቋቋመው የለይቶ ማቆያ ማዕከል እኩል ግብአቶችንና ቁሳቁሶችን በማሟላት ሦስተኛው ማዕከል እንዲሆን የቻልነውን ሁሉ ለማድረግ እንሞክራለን ያለት የዩኒቨርሲቲው የአስተዳደርና ተማሪዎች አገልግሎት ምክትል ፕሬዚዳንት አማረ ምትኩ (ዶ/ር) ባቲ ወረዳ ከጅቡቲና አፋር የሚመጡ የከባድ መኪና ሹፌሮችና መንገደኞች መተላለፊያ ማዕከል እንደመሆኗ መጠን ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሥራት እንዳለበት ተናግረዋል።

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ የወሎ ሕዝብ አምባሳደርነቱን በተግባር እያስመሰከረ ነው ያሉት የኦሮሚያ ብሔረሰብ ዞን አስተዳዳሪ አቶ አህመድ ሀሰን ዩኒቨርሲቲው የዞናችንን አቅም መሠረት ያደረጉ የልማት ሥራዎችን ከመሥራትና ከማስተዋወቅ ጀምሮ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል ለከሚሴና ባቲ ወረዳዎች የለይቶ ማቆያ ማዕከሎች ያደረገው ድጋፍ በታሪክ የትውልድ ቅብብሎሽ የሚዘከር ይሆናል ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

    ዩኒቨርሲቲው የባቲ ወረዳ ለይቶ ማቆያ ማዕከልን ለማቋቋም ከ5 መቶ ሺ ብር በላይ የሚያወጡ የቁሳቁስ ድጋፍ ማድረጉን ወሎ ዩኒቨርሲቲ ከዚህ በፊት ዘግቦ ነበር።

    ምንጭ፦ ወሎ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ ባደረገው ድጋፍ የተቋቋመው የባቲ ለይቶ ማቆያ ማዕከል

    Anonymous
    Inactive

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ በከሚሴ ከተማ ቅርንጫፍ (ካምፓስ) ለመክፈት ቦታ ተረከበ

    ከሚሴ (ወሎ ዩኒቨርሲቲ) – ወሎ ዩኒቨርሲቲ ተደራሽነቱን በማስፋፋት የግቢ (የካምፓስ) ብዛቱን ሦስት ለማድረስ ከከሚሴ ከተማ አስተዳደር 100 ሄክታር መሬት ተርክቧል። በዚህም የቦታ ርክክብ የዩኒቨርሲቲውን ፕሬዝዳንት ጨምሮ ምክትል ፕሬዚዳንቶች፣ የኮሌጅ ዲኖችና ዳይሬክተሮች ተገኝተዋል።

    የዩኒቨርሲቲው አመራሮች የከሚሴ ከተማ አስተዳደር በስጦታ ያበረከተውን ቦታ ከጎበኙ በኋላ ከከተማ አስተዳደሩ አመራሮች ጋር ተወያይተዋል። በዚህም ውይይት የወሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን በከሚሴ በቀጣይ የሚከፈተው ኮሌጅ የከሚሴንና የአካባቢውን ማኅበረሰብ ጥቅም፣ ፍላጎትና ሃብት መሰረት ያደረገ እንዲሆን በጥናት ላይ ተሞርኩዞ ውሳኔ እንደሚሰጥበት ተናግረዋል። ፕሬዚዳንቱም የከሚሴ ከተማ አስተዳደር ላደረገው የቦታ ስጦታ ላቅ ያለ ምስጋና ካቀረቡ በኋላ፥ ምክትል ፕሬዚዳንቶች በየዘርፋቸው ቦታውን ተረክቦ የከሚሴንና የአካባቢውን ማኅበረሰብ ጥያቄዎች ለመመለስ በሎም የተሰማቸውን አስተያየት እንዲሰጡ አድርገዋል። ወሎ ዩኒቨርሲቲ በርካታ በሆኑ የቅድመና ድኅረ ምረቃ ፕሮግራም ስልጠናዎችን እየሰጠ እንደሆነ የገለጹት የአካዳሚክ ጉዳዮች ም/ ፕሬዝዳንት ተወካይ ዶ/ር ብረሃን አስማሜ የአካባቢውን ማኅበረሰብ የትምህርት ፍላጎት መሠረት ያደረጉ ኮሌጆችን፥ ትምህርት ክፍሎችንና መርሀ-ግብሮችን (ፕሮግራሞችን) ለመክፈት እንደሚሠሩ ቃል ገብተዋል።

    በምሥራቅ አማራ ጨፋ ሸለቆ ያለው ከፍተኛ የሃብት ክምችት ከአካባቢው ማኅበረሰብ ተርፎ ለገበያ እንዲውል የምርምር ማዕከል በቦታው በመክፈት ሕዝባችንን ከድህነት የሚያወጡ የምርምር ሥራዎችን በማካሄድ ዕድሉን ለመጠቀም እንደሚሠሩ የተናገሩት የዩኒቨርሲቲው የምርምርና ማኅበራዊ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ፋሪስ ኃይሉ ናቸው። የቦታው ሕጋዊ ሰነዶች በሙሉ በዩኒቨርሲቲው ስም ሆነው እንደተጠናቀቁ ተገቢውን የግንባታና ተቋሙን የማደራጀት ተግባራት እንደሚጀምሩ የገለጹት የዩኒቨርሲቲ የአስተዳደርና ተማሪዎች አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር አማረ ምትኩ፥ ዩኒቨርሲቲው ተደራሽነቱን በማስፋት የማኅበረሰቡን ጥያቄዎች ለመመለስ የአቅሙን ሁሉ ይሠራል ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

    በከሚሴና አካባቢ ያለውን ሥራ አጥነት ለመቅረፍ ከክህሎት ስልጠና ጀምሮ በአዋጭ የሥራ መስኮች ወጣቱ እንዲሰማራ በማድረግ ኃላፊነታቸውን ለመወጣት የቢዝነስ ልማትና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ምክትል ፕሬዝዳንቷ ዶ/ር አጸደ ተፈራ ሲገልጹ፥ የኮምቦልቻ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ዶ/ር መላኩ ታመነ በበኩላቸው የአካባቢውን ማኅበረሰብ ፍላጎት በማየት በኮምፒዩተር ሳይንስ መርሀ-ግብሮችን መክፈት እንደሚችሉ ተናግረዋል።

    የኮሌጅ ዲኖችና ዳይሬክተሮች በጉብኝቱ ያዩትን፣ የተሰማቸውንና በቀጣይ በቦታው ቢሠራ ያሏቸውን አስተያየቶች ሰጥተዋል። ዩኒቨርሲቲው ከዚህ በፊት ከከተማ አስተዳደሩ ለወጣቶች የሥነ-ተዋልዶ፣ የመዝናኛ፣ የቤተ መጻሕፍትና ተዛማጅ የማኅበረሰብ አገልግሎቶችን የሚሰጥበት ማዕከል ተቀብሎ ወደ ሥራ መግባቱ የሚታወቅ ነው።

    ምንጭ፦ ወሎ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ ከሚሴ ካምፓስ

    Anonymous
    Inactive

    ኮምቦልቻ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት በአርክቴክቸር ዘርፍ ለአምስት ዓመት ተኩል ያስተማራቸውን ተማሪዎች አስመረቀ

    ኮምቦልቻ (ወሎ ዩኒቨርሲቲ) – በወሎ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሚገኘው ኮምቦልቻ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት (Kombolcha Institute of Technology) የአርክቴክቸር ትምህርት ክፍል ለአምስት ዓመት ተኩል ሲያስተምራቸው ከነበሩት ተማሪዎች ውስጥ መጋቢት 3 ቀን 2012 ዓም በዋለው ሴኔት ውጤታቸውን መርምሮ ሃያ ስድስት ተማሪዎችን በደማቅ ዝግጅት አስመርቋል።

    በኮምቦልቻ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ዶ/ር መላኩ ታመነ ለእንግዶች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ባስተላለፉበት ወቅት፥ ኢትዮጵያ በኪነ ህንፃ ዘርፍ የቆየ ጥበብ ባለቤት መሆኗን አስታውሰው፤ ተማሪዎች በቆዩባቸው ዓመታት ከአካዳሚያዊ እውቀት ባለፈ ሰላማዊ የመማር ማስተማር እንዲሰፍን ላበረከቱት አስተዋጽዖ ምስጋና ችረዋል።

    ዶ/ር መላኩ በመልዕክታቸው፥ በ2012 ዓ.ም. ከተመረቁት ሃያ ስድስት ተማሪዎች መካከል በትምህርታቸው ብልጫ ላመጡ ሁለት ተማሪዎች በትምህርት ክፍሉ እና በማኔጅመንት ውሳኔ በተቋሙ ውስጥ በመምህርነት እንዲቀጠሩ መወሰኑን አብስረዋል።
    የወሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን በበኩላቸው ተመራቂ ተማሪዎች ወደ ቀጣዩ የሕይወት ምዕራፍ ሲሸጋገሩ ያገኙትን እውቀት እና ልምድ በተግባር በማዋል ዘርፉ ላይ ትልቅ አስተዋጽዖ ሊያበረክቱ እንደሚገባ አሳስበው፤ ምሩቃኑ በአገሪቱ ነባራዊ ሁናቴ ላይ በጎ አሻራ በማስቀመጥ የዜግነት ግዴታቸውን መወጣት መቻል እንዳለባቸው ምክረ ሃሳብ ለግሰዋል።

    ዶ/ር አባተ ኢትዮጵያ ከጣራ ወደ መሠረት እነዲሁም ከአንድ ፍልፍል ደንጋይ ህንፃ በማዋቀር የቀደመ የጥበብ ተምሳሌት መሆኗን አውስተው ተመራቂ ተማሪዎች ራሳቸወን በማብቃት በአለም ገበያ ጭምር ተወዳዳሪ መሆን እንደሚገባቸው አሳስበዋል።

    የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር አህመድ የሱፍም በምረቃ ፕረግራሙ ወቅት በክብር እንግድነት ተገኝተው ለምሩቃኑ ንግግር አድርገዋል።

    በ2012 ዓ.ም. ትምህርት ዘመን ከአጠቃላይ ተመራቂዎች 3.67 በማምጣት ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገበችው ኤደን ሽመልስ እና 3.54 ያመጣው ዳዊት ማለደ ወደ ኮምቦልቻ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት መቀላቀላቸው እንዳስደሰታቸው ገልጸው፤ በቆይታቸው ባገኙት እውቀትና ልምድ ተቋሙን እና አገራቸው ለማገልገል ትልቅ መነሳሳት እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ፥ ወሎ ዩኒቨርሲቲ በሳይንስ፣ በቴክኖሎጂ፣ በምህንድስናና በሒሳብ የትምህርት መስኮች የተሻለ ፍላጎት ያላቸው ተማሪዎች እንድኖሩ የSTEM ማዕከል በማቋቋም እየሠራ ይገኛል። ይህንን የSTEM ማዕከል በቴክኖሎጅ ለማደራጀት የወሎ ዩኒቨርሲቲ ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር “የኮምፒዩተርና የኤሊክትሮኒክስ” ቤተ-ሙከራ ከፍቷል። ይህ የወሎ ዩኒቨርሲቲ የSTEMpower ማበልጸጊያ “የኮምፒተርና የኤሌክትሮኒክስ ቤተ ሙከራ” በአሜሪካን STEMpower.org ከተሰኘ ድርጅት በተገኘ ድጋፍ የተመሠረተ ነው። ማዕከሉ በዘመናዊና ደረጃቸውን በጠበቁ የቤተ-ሙከራ ማቴሪያሎች የተደራጀ እንዲሆን ድርጅቱ ሁሉንም መሣሪያዎች በቀጥታ ከውጭ እንድገቡ አድርጓል። ይህም የSTEM ማዕከል የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች፣ መምህራንና ድጋፍ አድራጊው የSTEMpower.org ድርጅት ተወካይ ባሉበት “ማዕከሉ” በይፋ ተከፍቷል።

    ምንጭ፦ ወሎ ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ኮምቦልቻ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት

    Semonegna
    Keymaster

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ እና ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን አስመረቁ

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ 34 የሕክምና ዶክተሮችን ጨምሮ ለሁለተኛ ዙር ያሰለጠናቸውን 1233 ተማሪዎቸ መጋቢት 5 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመርቋል።

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ በዋና ግቢው እና በዱራሜ ካምፓስ 6 ኮሌጆች በመጀመሪያ ዲግሪ፣ በሁለተኛ ዲግሪ እና በተከታታይ ትምህርት በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ነው ያስመረቀው።

    በምርቃቱ ሥነ-ሥርዓት ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የሳይንስና እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ፥ ኢትዮጵያ ለእርሷ እና ለዜጎቿ ክብር እና ፍቅር ያለው ባለሙያ ያስፈልጋታል ብለዋል። አክለውም ተመራቂዎች ያገኙትን እውቀት በተገቢው ሁኔታ ለማኅበረሰብ ለውጥ እንዲያውሉት አሳስበዋል።

    ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ መጠናቀቅ ድጋፋቸውን በማጠናከር የአገሪቱን ሉዓላዊነት እንዲያስረግጡም ዶ/ር ሳሙኤል ጠይቀዋል።

    የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሐብታሙ አበበ በበኩላቸው፥ ተመራቂዎች ያገኙትን እውቀት ወደ ተግባር በመቀየር ሙያዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። አሁን ላይ በሀገሪቱ በተለያየ መልኩ ከሚንፀባረቀው የአስተሳሰብ እና የአመለካከት ኋላ ቀርነት በመራቅ ለኅብረተሰብ ዕድገት እና ብልፅግና እንዲረባረቡ ጠይቀዋል።

    በሌላ በኩል ደግሞ ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ለመጀመሪያ ጊዜ በሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም ያሰለጠናቸውን 33 የሕክምና ዶክተሮችን አስመረቀ።

    ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ለመጀመሪያ ጊዜ በሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም (hybrid innovative curriculum) በሕክምና ዶክትሬት ያሰለጠናቸውን 33 ተማሪዎች በተመሳሳይ ቀን አስመርቋል።

    በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ለተማሪዎቹ የሥራ መመሪያ የሰጡት የሳይንስ እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ፥ ተመራቂዎቹ ቃለመሀላ በገቡለት የሕክምና ሥነ-ምግባር በመታገዝ ቅን አገልጋዮች እንዲሆኑ አሳስበዋል። ከዚህም ባለፈ በተግባር በተደገፈው ሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም የቀሰሙትን የሕክምና ትምህርት የሀገሪቱን ብሎም የዓለምን ሕዝብ ስጋት ላይ ከጣሉ ዘመን-ወለድ የጤና ችግሮች ኅብረተሰቡን ለመታደግ ተግባራዊ እንዲያደርጉት ጥሪ አቅርበዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አነጋግረኝ ጋሻው በበኩላቸው፥ ተመራቂዎቹ ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ በውጤት በታገዘው የቅይጥ ፈጠራ-አከል ሥርዓት (ሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም) ለመጀመሪያ ጊዜ ያሰለጠናቸው በመሆናቸው ማኅበረሰቡን ከጤና እክሎች ከመታደግ ባለፈ በምርምር ዘርፍ በመሰማራት ለሀገር ብልፅግና የድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።

    ዩኒቨርሲቲው በዕለቱ 26 የማስተርስ ዲግሪ (ሁለተኛ ዲግሪ) ተማሪዎችንም አስመርቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    በ2013 ዓ.ም የጉራጊኛ ቋንቋ ከቅድመ መደበኛ የትምህርት ደረጃ ጀምሮ እንዲሰጥ እየተሠራ ነው

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በ2013 ዓ.ም. የጉራጊኛ ቋንቋ ከቅድመ መደበኛ የትምህርት ደረጃ ጀምሮ እንዲሰጥ እየሠራ መሆኑን ገለጸ። ዩኒቨርሲቲው ከ135 በላይ ለመድኃኒት የሚሆኑ እጽዋት ላይ ምርምር እያደረገ መሆኑን ጨምሮ ገልጿል።

    ወልቂጤ (ኢዜአ) – ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የአገር በቀል እውቀት ዳይሬክተር አቶ ካሳሁን ጥሩውሃ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደተናገሩት፥ እስካሁን የጉራጊኛ ቋንቋ በትምህርት ቤት፣ በመሥሪያ ቤት እንዲሁም በሃይማኖት ተቋማት ውስጥ አልተካተተም። በቋንቋው ውስጥ የተለያየ የአነጋገር ዘዬ መኖር በትምህርት እንዳይሰጥ ካደረጉት ዋነኛው ምክንያት መሆኑን ተናግረዋል።

    በዚህም አብዛኛው የማኅበረሰብ ክፍል ጉራጊኛ ቋንቋን እየረሳ በመምጣቱ ከዞኑ ባህልና ቱሪዝም እንዲሁም ትምህርት መምሪያ ጋር በመተባበር የፊደል ገበታ መቀረጹን ገልጸዋል። የተወሰኑ ፎነቲኮች በአማርኛ ፓወር ግዕዝ ላይ ባለመኖራቸው ዩኒቨርሲቲው “የተንቢ” የተሰኘ የኮምፒተር መተየቢያ አበልጽጓል።

    በጉራጊኛ ቋንቋ 13 የአነጋገር ዘዬ የሚገኝ ሲሆን በየትኛው መጀመር እንዳለበት ዩኒቨርሲቲው ለማኅበረሰቡ አማራጭ ሃሳቦችን ለማቅረብ ተዘጋጅቷል።

    ”የኮምፒተር መተየቢያና የፊደል ገበታን በማሰልጠን እንዲሁም ሌሎች ግብአቶች እንዲሟሉ በመጠቆም  የጉራጊኛ ቋንቋ በቀጣዩ የትምህርት ዘመን ከቅድመ መደበኛ ክፍል ጀምሮ እንዲሰጥ ለማስቻል እየተሠራ ነው” ብለዋል አቶ ካሳሁን።

    በሌላ በኩል ዩኒቨርሲቲው ከ135 ዓይነት በላይ ለመድኃኒትነት የሚውሉ ተክሎች ላይ ምርምር እያደረገ መሆኑን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። ለዚህም የተፈጥሮ መድኃኒት ማምረት የሚያስችል የስልት ሰነድ (strategic document) እየተዘጋጀ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

    እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ፥ መድኃኒቱን ማምረት የሚያስችሉ ቅድመ ሁኔታዎች እየተመቻቹ ነው። በዚህም ንጥረ ነገሮችን የመሥራትና የአሠራር ዘዴ ሙከራ እየተደረገ እንደሆነ ጠቁመዋል።

    ምርምር እየተደረገባቸው ያሉ እጽዋት ለደም ብዛት፣ ጋንግሪን፣ አስም፣ አጥንት ካንሰርና ለሌሎች በሽታዎች ፈውስ ያስገኛሉ የተባሉ ናቸው።

    ቀደም ሲል ከእጽዋት የባህላዊ መድኃኒቶች ልኬት እንደማይታወቅ ያነሱት አቶ ካሳሁን፥ የፋርማሲና የኬሚስትሪ ባለሙያዎች ከአካባቢው የባህል መድኃኒት አዋቂዎች ጋር በምርምሩ እንዲሳተፉ ተደርጓል።

    በሌላ በኩል የማኅበረሰቡ ለበርካታ ዓመታት ይተዳደርበት የነበረው ባህላዊ የሕግና አስተዳደር ዘዴ እየቀነሰ በመምጣቱ መልሶ እንዲያንሰራራ ለማስቻል ዩኒቨርሲቲው ምርምር እያደረገ ነው።

    ቋንቋና ሥነ-ጹህፍ፣ አገር በቀል መድኃኒት፣ አስተዳደርና ሕግ፣ ባህልና የማይዳሰሱ ቅርሶች በዩኒቨርሲቲው ትኩረት ተሰጥቷቸው ምርምርና ጥናት እየተካሄደባቸው ነው።

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በደቡብ ክልል የሚገኝ የመንግስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ሲሆን የተመሠረተው በ2004 ዓ.ም. ነው።

    ምንጭ፦ ኢዜአ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የጉራጊኛ ቋንቋ

    Anonymous
    Inactive

    ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ 221 የህክምና ዶክተሮችና ስፔሻሊስቶችን አስመረቀ

    ሀዋሳ (ኢዜአ) – የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሳይንስና ቴክኖሎጂ ምንጮች ብቻ ሳይሆኑ በመልካም ሥነ-ምግባር የታነፀ ዜጋን ማፍሪያ ማዕከላት ጭምር መሆን እንዳለባቸው የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አሳሰቡ።

    ዩኒቨርሲቲው የካቲት 8 ቀን 2012 ዓ.ም. በአጠቃላይ 221 የጤና ባለሙያዎችን (192 የህክምና ዶክተሮችና 29 ስፔሻሊስት ዶክተሮችን) አስመርቋል። ከተመራቂዎች ውስጥ 22 በመቶ የሚሆኑት ሴቶች መሆናቸውም ተጠቁሟል።

    በምረቃ በዓሉ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር አያኖ በራሶ እንደገለፁት፥ ዩኒቨርሲቲው በአሁኑ ወቅት በመጀመሪያ ዲግሪ፣ በሁለተኛ ዲግሪ፣ በህክምና ስፔሻሊስትና በሦስተኛ ዲግሪ በርካታ የትምህርት መስኮችን (ፕሮግራሞችን) በመክፈት ከ43 ሺህ 800 በላይ ተማሪዎችን በመደበኛና በተከታታይ ትምህርት መርሀ ግብሮች እያስተማረ ይገኛል። የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅም የመምህራን ልማት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው ብለዋል።

    ሀገሪቱ ካላት ውስን ሀብት ላይ አንድ አራተኛውን በጀት ለትምህርት ማዋሏን የተናገሩት ፕሬዝዳንቱ፥ ተመራቂዎችም ያላቸውን ዕውቀት፣ ክህሎትና ጉልበት ላስተማራቸው ማኅበረሰብ በማበርከት ለሀገራቸው ዕድገት የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት ሊወጡ እንደሚገባ ጠይቀዋል።

    ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሳይንስና ቴክኖሎጂ ምንጮች ብቻ ሳይሆኑ በመልካም ሥነ-ምግባር የታነፀ ዜጋን ማፍሪያ ማዕከላትም ናቸው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፥ ተመራቂዎች ራሳቸውን ከመጥፎ ምግባር በመቆጠብና ሙያው በሚጠይቀው ሥነ-ምግባር ህሙማንን በፍቅር ማገልገል እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።

    በምረቃ በዓሉ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ አባል ፕሮፌሰር በየነ ጴጥሮስ በበኩላቸው ለተመራቂዎች የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ፕሮፌሰር በየነ እንዳሉት፥ ሀገሪቱ ባለፉት ሃያና ሰላሳ ዓመታት ውስጥ በጤናው ዘርፍ በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ እመርታ በማስመዝገብ የዓለም ጤና ድርጅትን ጨምሮ ሌሎች ተፅዕኖ ፈጣሪ የሆኑ ታላላቅ ዓለም ዓቀፍ ተቋማትና መንግሥታት ዕውቅና ማግኘቷን ተናግረዋል።

    ይሁን እንጂ አሁንም የጤና ሽፋንን ከመጨመርና ጥራትና ፍትሐዊነት ያለው አገልግሎት ከመስጠት አንጻር ብዙ ርቀት መጓዝ እንደሚጠይቅ የተናገሩት ፕሮፌሰር በየነ፥ የሚፈለገውን ለውጥ ለማምጣት ጠንክረን በጋራና በትብብር መንፈስ መሥራት አለብን ብለዋል። የዛሬ ተመራቂዎችም የነገዋ ኢትዮጵያ ተስፋዎች መሆናቸውን በመረዳት ሀገራቸውን ማገልገል እናዳለባቸው ጠቁመዋል።

    በሙያቸው ገፍተው ዕውቀትና ክህሎታቸውን በማዳበርም የተሻለ አገልግሎት እንዲሰጡና ችግር ፈቺ በሆኑ ምርምሮች ውስጥ በመሳተፍ ኢትዮጵያ ውስጥ እየተተገበረ ያለውን ፈርጀ ብዙ ለውጥ የማቀጣጠልና የማስቀጠል ኃላፊነታቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል ።

    ከተመራቂዎች መካከል ከፍተኛ ውጤት በማምጣት የሜዳልያ ተሸላሚ የሆነው ዶ/ር አቤል ጌታቸው በሰጠው አስተያየት፥ የህክምና ትምህርት ጽናትን የሚጠይቅ መሆኑን ገልፆ ሁኔታዎችን በትዕግስት በማለፍ ለዚህ መብቃቱን ተናግሯል።

    የህክምና ሙያ በራሱ ለሰዎች ክብር መስጠትና ርህራሄ መላበስን የሚያስተምር እንደሆነ የተናገረው ዶ/ር አቤል፥ ያለአድሎ ሰብዓዊነትን በመላበስ ህብረተሰቡን ለማገልገል ዝግጁ መሆኑን አስረድቷል።

    በውስጥ ደዌ ህክምና ስፔሻላይዝድ በማድረግ የተመረቀው ዶ/ር ሙባረክ ሁሴን በበኩሉ፥ የህክምና ሥነ-ምግባር ከሀሳብ ይልቅ በተግባር የሚገለፅ መሆኑንና ታካሚዎችን እንደ ቤተሰብ በማየት ያለአድሎ ለማገልገል መዘጋጀቱን ተናግሯል።

    የዩኒቨርሲቲው የህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የህክምና ዶክትሬት ተማሪዎችን ሲያስመርቅ ለ11ኛ ዙር ሲሆን ስፔሻሊስት ሀኪሞችን ደግሞ ለ4ኛ ዙር መሆኑ ተዘግቧል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ 221 የህክምና ዶክተሮችና ስፔሻሊስቶችን አስመረቀ

    Semonegna
    Keymaster

    “እኔ ለወገኔ” የወሎ ዩኒቨርሲቲ የበጎ አድራጎት ማኅበር በደሴ ከተማ ድጋፍ አደረገ

    በወሎ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የተመሰረተው “እኔ ለወገኔ” ማኅበር ድጋፍ ለሚሹ አቅመ ደካሞችና ሕፃናት የአልባሳት ድጋፍ አድርጓል። በቀጣይም አረጋውያንን በማዕከል በማሰባሰብ በቋሚነት የሚጦሩበትና የጎዳና ተዳዳሪ ወጣትና ሕፃናትን ደግሞ ወደ ትምህርት ቤት በማስገባት ለማስተማር ይሠራል።

    ደሴ (ኢዜአ) – በወሎ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች የተመሠረተው “እኔ ለወገኔ” የበጎ አድራጎት ማኅበር ከ700 ሺህ ብር በላይ ግምት ያላቸው አልባሳትና ቁሳቁሶችን አቅመ ደካሞችና ለዳና ተዳዳሪዎችን ጨምሮ ድጋፍ ለሚሹ የደሴ ከተማ ኗሪዎች ድጋፍ አደረገ። የማህበሩ አባላት በተለያዩ የመንግስት ተቋማት፣ ድርጅቶችና ግለሰቦች ያሰባሰቡትን ቁሳቁስ በከተማዋ ለሚኖሩ አቅመ ደካሞችና ሕፃናት አሰራጭተዋል።

    የማኅበሩ አባል ተማሪ አቡሽ ግርማ እንዳለው የዛሬ ሁለት ዓመት የተመሠረተው “እኔ ለወገኔ” ማኅበር ደሴ ከተማ እና በአካባቢው የሚገኙ አቅመ ደካሞችንና ችግረኛ የሕብረተሰብ ክፍሎችን በማገዝ ሥራ ተሰማርቷል። በዚህም ተማሪዎች ከባለሃብቶች፣ ፋብሪካዎችና ከተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች በማሰባሰብና ጫማ በመጥረግ ሥራ የሚያገኙትን ገንዘብ በመቆጠብ ለ300 አቅመ ደካሞችና የጎዳና ተዳዳሪዎች የካቲት 2 ቀን 2012 ዓ.ም. ድጋፍ አበርትቷል። ድጋፉ የተደረገውም የንጽህና መጠበቂያ ቁሳቁሶች፣ ብርድ ልብስ፣ አንሶላ እና ሌሎች አልባሳት የመሳሰሉት ናቸው። በቀጣይም አረጋዊያንን በማዕከል በማሰባሰብ በቋሚነት የሚጦሩበትና የጎዳና ተዳዳሪ ወጣትና ሕፃናትን ደግሞ ወደ ትምህርት ቤት በማስገባት ለማስተማር እንደሚሠሩ ተናግሯል።

    ሌላው የ3ኛ ዓመት የሥራ አመራር (management) ተማሪ ምትኩ ደጉ በበኩሉ፥ ቁሳቁሱንና አልባሳቱን ማሰባሰብ የተቻለው የትምህርት ጊዜያቸውን በማይነካ መልኩ በመንቀሳቀስ ነው። የኢትዮጵያውያን አኩሪ እሴት ከሆኑት መካከል መረዳዳትና መደጋገፍ መሆኑን በሌሎች ተማሪዎች ዘንድ ለማስረጽ ማኅበር መሥርተው መንቀሳቀሳቸውን አስረድቷል።

    የወሎ ዩንቨርሲቲ አስተዳደርና ተማሪዎች አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር አማረ ምትኩ በበኩላቸው፥ ተማሪዎች ከትምህርታቸው ጎን ለጎን የሚያደርጉት የተለያየ በጎ ተግባር የሚደነቅ ነው። ዩኒቨርሲቲዎች በግጭት በሚታመሱበት በዚህ አስቸጋሪ ወቅት የማኅበሩ አባላት ተማሪዎች በአንድ ላይ ሕብረተሰቡን አስተባብረውና የሌሎችን ጫማ ጠርገው ደካሞችን መደጋገፋቸው አርአያነት ያለው ተግባር ነው ብለዋል። አያይዘውም ፕሬዚዳንቱ በትውልዱ እየተሸረሸረ የመጣውን መረዳዳት፣ መተዛዘን እና የተገኘውን ተካፍሎ የመጠቀም ተግዳሮቶች ምላሽ የሰጠ ሊበረታታና ሊስፋፋ የሚገባው መልካም ተግባር እንደሆነ ገልጸዋል። በቀጣይም ተማሪዎቹ ለሚያከናውኑት መልካም ምግባር ዩኒቨርሲቲው አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ቃል ገብተዋል።

    የድጋፉ ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል አቶ ጸጋዬ ቢያድግልኝ እንደ ገለጹት፥ ረዳትና ተንከባካቢ ቤተሰብ ስለሌላቸው አንድ ሱሪና ጃኬት ለብሰው ለዓመታት ኖረዋል። በወሎ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች አማካኝነት ብርድ ልብስ፣ ሱሪ፣ ሸሚዝና ጃኬት በማግኘታቸው እየቀያየሩ በመልበስ ንጽህናና ጤንነታቸውን ለመጠበቅ እንደሚያስችላቸው ተናግረዋል።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)/ ወሎ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    እኔ ለወገኔ ወሎ ዩንቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive

    የተሻሻለው የወሎ ቴሪሸሪ የህክምናና የማስተማሪያ ሆስፒታል ዲዛይን ለሕዝብ ይፋ ሆነ

    ደሴ (ወሎ ዩኒቨርሲቲ) – በጥቂት ሀገር ወዳድ ግለሰቦች ሀሳቡ ተጠንስሶ ሀገራዊ የሕዝብ ፕሮጀክት የሆነው የወሎ ልዕለ ህክምና የማስተማሪያ ሆስፒታል /ሦስተኛ ትውልድ ሆስፒታል/ (Wollo Tertiary Care and Teaching Hospital) ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች በየጊዜው እየፈታ ከመጨረሻው ምዕራፍ ላይ ተዳርሷል።

    ይህንን የሕዝብ ፕሮጀክት ነሐሴ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ያለ በጀትና ዲዛይን በባለቤትነት የተረከበው ወሎ ዩኒቨርሲቲ ወደ ሥራ ለመግባት ከሕዝብ የተሰበሰበውን በጀትና ዲዛይን ሊያስረክብ የሚችል አካል በመጥፋቱ ተቸግሮ ቆይቷል።

    ዩኒቨርሲቲው የሕዝቡ ፍላጎትና ጥያቄዎች እየተበራከቱ ሲመጡበት የዋና ሆስፒታል ዲዛይን መረከብ እስኪችል ድረስ በራሱ ወጭ በ460 ሚሊዮን ብር የተማሪዎች መኖሪያ G+4 10 ህንጻዎችን በመገንባት ላይ ይገኛል።

    የሆስፒታሉን ዲዛይን የተረከበው አማካሪ ድርጅት ሰርቶ ማቅረብ ባለመቻሉ በ2011 ዓ.ም. አጋማሽ ዩኒቨርሲቲው ውለታውን በማቋረጥ ከአዲሱ የኤምቲቲ አማካሪ አርክቴክቶችና ምህንድስና ኃ/የተ/ የግል ኩባንያ (MTT Consulting and Architects and Engineers PLC) ድርጅት ጋር ውለታ በመፈጸም ዲዛይኑን ለአዲሱ ድርጅት አስረክቧል።

    የኤምቲቲ አማካሪ ድርጅት የተረከበው ዲዛይን ከዓለም የቴክኖሎጅ እድገትና ከዘመኑ የኪነ ህንጻ ጥበብ ጋር ሊዛመዱ በማይችሉ የመዋቅር፣ የኤሌክትሮ መካኒክ፣ የፍሳሽ ማስወገጃና መሰል በርካታ ተግዳሮቶች ያሉበት በመሆኑ የዲዛይን ማሻሻያዎችን ሠርቶ ለሕዝብ ይፋ አድርጓል።

    የኤምቲቲ አማካሪ ድርጅት የሆስፒታሉን ዲዛይን ከማሻሻሉም ባሻገር የሆቴል ቱሪዝምን ለማበረታታት ባለ 5 ኮኮብ ሆቴል፣ የባሕላዊ ህክምና መስጭያ ማዕከልና ከአካባቢው ባህልና ሥነ-ምህዳር ጋር የሚዛመዱ ተያያዥ ማዕከላትን የሆስፒታሉ አካል እንድሆኑ በማካተት ይፋ አድርጓል።

    ይህንን ይፋ የሆነ የሆስፒታል ዲዛይን የተመለከቱት የደሴ ከተማ የሕዝብ ተወካዮች፣ የዘርፉ ባለሞያዎች፣ የዩኒቨርሲቲው አመራሮችና ባለሙያዎች በተሻሻለው ዲዛይን ላይ የተሰማቸውን ስሜት በመግለጽ ቢካተቱ ያሏቸውን ጥያቄዎች አቅርበዋል።

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን ዋናውን ሆስፒታል ወደ መሬት ለማውረድ ያጋጠማቸውን ተግዳሮቶች በመጥቀስ ዩኒቨርሲቲው የሕዝብን ስሜት ለመጠበቅ በራሱ የተጓዘውን ርቀት አብራርተዋል። ፕሬዚዳንቱ አያይዘውም ዩኒቨርሲቲው ከሕዝብ የተሰበሰበውን አምስት ሳንቲም እንኳን እንዳልተረከቡ በመግለጽ ፕሮጀክቱን እውን ለማድረግ አማካሪው ኤምቲቲ አማካሪ ድርጅት የሀሳቡ ጠንሳሽ ዶ/ር በላይ አበጋዝን ጨምሮ በጤና ሚኔስተርበአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲበጥቁር አንበሳና በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታሎች ያሉ የዘርፉ ምሁራንን በማሳተፍ ሆስፒታሉ እውን እንድሆን ለተሠራው ሥራ አመስግነዋል።

    የኤምቲቲ አማካሪ ድርጅት በበኩሉ በሕዝብ የተነሱትን ጥያቄዎችና አስተያየቶች በማካተት ፕሮጀክቱ ወደ መሬት በቅርብ ቀን እንዲወርድ የቻለውን ሁሉ እንደሚሠራ ቃል ገብቷል።

    ምንጭ፦ ወሎ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የወሎ ልዕለ ህክምና የማስተማሪያ ሆስፒታል


    Anonymous
    Inactive

    በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ በተፈጠረው የሰላም እጦት ጋር በተያያዘ ከ640 በላይ ተማሪዎች፣ 40 መምህራን እና ከ240 በላይ የአስተዳደር ራተኞች ላይ የተለያዩ እርምጃዎች መወሰዳቸው ተገለጸ

    አዲስ አበባ (ኢብኮ) – ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ተፈጥሮ የነበረው የጸጥታ ችግር ለማረጋጋት በ22 ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ በነበሩ ከ640 በላይ ተማሪዎች፣ 40 መምህራን እና ከ240 በላይ የአስተዳደር ሠራተኞች ላይ የተለያዩ እርምጃዎች እንደተወሰደ የሳይንስና የከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ገልጿል።

    በዩኒቨርሲቲዎች በተፈጠረ የሰላም እጦት 35 ሺህ ተማሪዎች ትምህርት ጥለው መውጣታቸውን የገለጸው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ፥ እነዚህን ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው ለመመለስ እየተሠራ መሆኑን አስታውቋል። የተማሪዎችን አደረጃጀት በኅብረ ብሔር ለማሰባጠር መታሰቡንም ሚኒስቴሩ ገልጿል።

    የሳይንስ እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ዩኒቨርሲቲዎች ሰላም ባጡባቸው ጉዳዮች ላይ ከተለያዩ አካላት ጋር ግምገማ እና ምክክር እያደረገ ይገኛል።

    በ22 ዩኒቨርሲቲዎች ተፈጥሮ የነበረውን የጸጥታ ችግር ለማጣራት የተዋቀረው ኮሚቴ ባደረገው የመስክ ምልከታ ያዘጋጀው ሪፖርት በመድረኩ ላይ ቀርቧል። በቀረበው ሪፖርትም የዩኒቨርሲቲዎች የሰላም መታወክ የፖለቲካ አመራሮች ትልቅ ሚና እየተጫወቱ እንዳለ ተገልጿል።

    በተለያዩ ክልሎች ባሉ የተለያዩ የፖለቲካ አመራሮች የሚወጡ መግለጫዎች እና ከግቢ ውጭ ተማሪዎችን ሰብስቦ ተልእኮ የመስጠት ሥራዎች ለመማር ማስተማሩ መታወክ እንደ አንድ ምክንያት ተጠቁሟል። ተልእኮ የተቀበሉ ተማሪዎች መማር የሚፈልጉ ተማሪዎች ላይ የሥነ ልቦና፣ አካላዊ፣ የሕይወት እና ንብረት ጉዳት በማድረስ ግጭት እንደሚያነሳሱም ተጠቁሟል። በሚዲያዎች፣ በሶሻል ሚዲያዎች እና በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን የተጋነኑ እና የተዛቡ መረጃዎች መሰራጨት፣ የዩኒቨርሲቲ አመራሮች ችግሮችን ውጫዊ ማድረግ ወይም ቸልተኝነትም ሌላው ለዩኒቨርሲቲዎች የሰላም እጦት የተነሣ ተግዳሮት ነው። በዩኒቨርሲቲዎች ያለው በቤተ ዘመድ የተሳሳበ የሠራተኛ አደረጃጀት እንዲሁ እንደ አንድ ችግር ተጠቅሷል።

    ችግር የፈጠሩ እና ምንም ዓይነት የሕግ እርምጃ ሳይወሰድባቸው በነፃ የሚለቀቁ እና እንዲማሩ የሚፈቀድላቸው ተማሪዎችም በዩኒቨርሲቲዎች ለሚታየው የሰላም እጦት ሌላው ምክንያት መሆናቸው ተጠቁሟል።

    በዩኒቨርሲቲ አመራሩ በኩል ውጫዊ ማስፈራሪያዎችን በመፍራት ውሳኔ ሰጭነት ላይ የሚታየውን ማፈግፈግ እንዲሻሻል እና ጠንካራ አስተዳደራዊ እርምጃ እንደሚወሰድም ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢብኮ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የሳይንስና የከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር በዩኒቨርሲቲዎች የሰላም እጦት

    Anonymous
    Inactive
    • ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ በዩኒቨርሲቲው የጸጥታ ችግር የተሳተፉ ተማሪዎች ላይ እርምጃ ወሰደ
    • ወሎ ዩኒቨርሲቲ በ335 ተማሪዎች፣ ሁለት የአስተዳደር ሠራተኞች እና አንድ መምህር ላይ እርምጃ ወሰደ
    • የጋምቤላ፣ ቦንጋ እና አርባምንጭ ዩኒቨርሲቲዎች የተማሪዎች ጥያቄዎች በተለያዩ ሀይሎች ሴራ እንዳይጠመዘዝ አስቀድመው በመሥራታቸው የመማር ማስተማር ሂደቱ በሰላማዊ ሁኔታ መቀጠሉን አስታወቁ

    የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ሴኔት ታህሳስ 27 ቀን 2012 ዓ.ም. ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በ2012 ዓ.ም. በተደጋጋሚ በተፈጠረው የጸጥታ ችግር የተለያየ ተሳትፎ በነበራቸው ተማሪዎች ላይ የሚከተሉትን ውሳኔዎች ወስኗል።

    1. ሁለት (2) ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ ከትምህርት ገበታቸው እንዲሰናበቱ፣
    2. ሰባት (7) ተማሪዎች እያንዳንዳቸው ለሦስት (3) ዓመት ከትምህርት ገበታቸው እንዲታገዱ፣
    3. ስምንት (8) ተማሪዎች እያንዳንዳቸው ለሁለት (2) ዓመት ከትምህርት ገበታቸው እንዲታገዱ፣
    4. አንድ (1) ተባሮ የነበረ (በወቅቱ የዩኒቨርሲቲው ተማሪ ያልነበረ) ነገር ግን በተፈጠረው የጸጥታ ችግር ውስጥ ተሳታፊ የነበረ ዩኒቨርሲቲው ክስ መስርቶ ግለሰቡን በሕግ ተጠያቂ እንዲያደርግ፤

    በመጨረሻም በወቅቱ ለሴኔቱ ውሳኔ ለቀረበ ተጨማሪ ስልሳ ዘጠኝ (69) ተማሪዎች ዲሲፕሊን ጉዳይ ላይ ተወያይቶ ጥፋታቸው በሂደት ተጣርቶ ወደ ፊት እርምጃ እንደሚወሰድባቸው እንዲሁም በቀጣይ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በተፈጠረው የጸጥታ ችግር በተለያየ መልኩ ተሳታፊ የነበሩ የዩኒቨርሲቲው ሠራተኞች ላይ እንደየጥፋታቸው እርምጃ እንደሚወሰድ አቅጣጫ ተቀምጧል።

    በተያያዘ ዜና የጋምቤላ፣ ቦንጋ እና አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲዎች የተማሪዎች ጥያቄዎች በተለያዩ ሀይሎች ሴራ እንዳይጠመዘዝ አስቀድመው በመሥራታቸው የመማር ማስተማር ሂደቱ በሰላማዊ ሁኔታ መቀጠሉን አስታወቁ።

    ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሃይማኖትና የብሄር ተኮር ግጭቶች ማዕከል ሆነው እና የጸጥታ ችግር ተጋርጦባቸው ጥቂት የማይባሉ ዩኒቨርሲቲዎችም በተደጋጋሚ ትምህርት ለማቆም ተገደዋል፤ በተማሪዎች ላይም ጉዳት አጋጥሟል። የግጭት መንስኤዎች የተለያዩ ሲሆን አንዳንዶቹ ከአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮች ጋር የተያያዙ ናቸው።

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ የመማር ማስተማር ሥራውን አውከዋል ያላቸውን 332 ተማሪዎች፣ ሁለት የአስተዳደር ሠራተኞች እና አንድ መምህር ላይ እርምጃ መውሰዱን አስታወቋል።

    ከፀጥታ መዋቅሩ ጋር በመሆን ባለፉት ሁለት ወራት ችግር ፈጣሪዎችን ለመለየት በተከናወነው ጠንካራ የሕግ ማስከበር ሥራ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሥራው እንዳይቀጥል ፍላጎት ባላቸው 332 ተማሪዎች፣ ሁለት የአስተዳደር ሠራተኞች እና አንድ መምህር ላይ እርምጃ መወሰዱን ዩኒቨርስቲው አስታውቋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን ለ ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደገለጹት፥ ዩኒቨርሲቲው በሰላማዊ የመማር ማስተማር ሥራ ተመራጭ እና ተምሳሌት ሆኖ ቆይቷል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በብሔር እና በሀይማኖት ሽፋን በተፈጠረ አለመረጋጋት የመማር ማስተማር ሥራው ባለፉት ወራት ውስጥ ለሦስት ጊዜ መቋረጡን አውስተዋል።

    በዚህም የሁለት ተማሪዎች ሕይወት ማለፉንና በተወሰኑት ላይ ደግሞ የአካል ጉዳት መድረሱን ጠቅሰው፣ ይህም ከአንድ የእውቀት ምንጭ ተቋም የማይጠበቅ አሳፋሪ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል።

    የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጴጥሮስ ወልደጊዮርጊስ ግን በከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ የሚታዩት የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮች ለግድያ የሚያደርሱ እንዳልሆኑ ይናገራሉ። አብዛኛዎቹ ተማሪዎች ሰላም ወዳድ መሆናቸውን የሚገልጸው ዩኒቨርሲቲው የመማር ማስተማሩን ለማወክ የሞከሩ ጥቂት ተማሪዎች እንዳልተሳካላቸው የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ገልፀዋል።

    ከ4 ሺህ በላይ ተማሪዎችን እያስተናገደ የሚገኘው ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲም ሁነኛ የጸጥታ ችግር ሳያጋጥመው የመማር ማስተማሩ ሂደት በሰላማዊ ሁኔታ ከቀጠለባቸው ዩኒቨርሲቲዎች መካከል ተጠቃሹ ነው። ዩኒቨርሲቲው ባወጣው መርሃ ግብር መሠረት የአንደኛ መንፈቅ ዓመት ትምህርትን ወደማገባደድ መቃረቡን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኡጁሉ ኦካክ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተናግረዋል።

    የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛም የመማር ማስተማር ሂደቱ በሰላማዊ ሁኔታ መቀጠሉን አንስተዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ በተለይም ተማሪዎች በተደጋጋሚ የሚያነሷቸውን የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመቅረፍ ካልተቻለም ለማሻሻል ጥረት ማድረጋቸውን አስታውቀዋል።

    ተማሪዎችን ተቀብለው ማስተናገድ ከጀመሩ በኋላ የሚነሱ ቅሬታዎችን በአጭሩ ለመፍታትም ከተማሪዎች ጋር የሰከነ እና የሰለጠነ ውይይት ማድረጋቸውን የአርባምንጭ እና ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች ገልፀዋል። ለዚህም ተማሪዎች እያንዳንዱ ጥያቄ በሂደት እንደሚፈታ ማመናቸውና አርቆ ተመልካችነታቸው ሰላማዊ ሁኔታው እንዲቀጥል ትልቁን ድርሻ እንደተወጣም ተጠቁሟል።

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገኙባቸው አካባቢዎች የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሀይማኖት መሪዎች እና ወጣቶች በሰላማዊ የመማር ማስተማሩ ሂደት ላይ የራሳቸውን ሚና እንዲወጡ መደረጉንም ዩኒቨርሲቲዎቹ የገለጹት።

    የዩኒቨርሲቲዎቹ ባለቤት የሆነው ማኅበረሰብ ተማሪዎቹን እንደ ራሱ ልጆች ተመልክቶ እንዲጠብቃቸው የተሰራው ሥራም ውጤታማ እንደነበር ነው ፕሬዚዳንቶቹ የገለጹት።

    ተማሪዎችም በሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች የታዩ አሰቃቂ ተግባራት እንዳይደገሙ በጋራ መሥራት አለባቸው፤ ከስሜታዊ ድርጊትም ሊታቀቡ ይገባልም ነው ያሉት። የብዙሃኑን ሰላም ለመጠበቅ ጥቂት በጥባጮችን አደብ ማስገዛት ይገባል ብለዋል በመልዕክታቸው።

    ምንጮች፦ ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ / የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    በዩኒቨርሲቲዎች የጸጥታ ችግር

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 22 total)