Search Results for 'የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር'

Home Forums Search Search Results for 'የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 58 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    በዲላ ዩኒቨርሲቲ የሕክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የሪፈራልና ማስተማሪያ ሆስፒታል የእድሳት ግንባታ ሥራ በይፋ ተጀመረ

    ሰሞነኛ (ዲላ ዩኒቨርሲቲ) – በዲላ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የሪፈራልና ማስተማሪያ ሆስፒታል የእድሳት ግንባታ ሥራ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ተካሄደ። የእድሳት ሥራው መጀመሩን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር ችሮታው አየለ ይፋ አድርገዋል።

    ዶ/ር ችሮታው ባደረጉት ንግግር፥ ሆስፒታሉ ያሉበትን መሠረታዊ ችግሮች በትኩረት መፍታት ከተቋሙ ዋና ዋና ተግባራት አንዱ መሆኑን ገልፀዋል።

    በተለያዩ ሀገራዊና ተቋማዊ ምክንያቶች ግንባታው ቶሎ ያልተጠናቀቀውን አዲሱን የሕክምና እና ማስተማሪያ ሆስፒታል ለማጠናቀቅ ከሚደረገው ጥረት በተጓዳኝ ነባሩን ሆስፒታል በልዩ ሁኔታ እድሳት አድርጎ ለታካሚሆችና ለአካሚዎች ጭምር በሚመጥን ሁኔታ አገልግሎት እንዲሰጥ ለማድረግ ይሠራል ብለዋል ፕሬዝዳንቱ።

    ነባሩ ሆስፒታል አሁን ባለበት ደረጃ የጌዴኦ ዞንን እና አጎራባች አካባቢዎችን ማኅበረሰቦች የሕክምና ፍላጎት ለማስተናገድ ችግሮች እንዳሉ የሚታወቅ መሆኑን የጠቀሱት ዶ/ር ችሮታው፥ ስለሆነም በሆስፒታሉ ሥራ አመራር ቦርድ ታምኖበት አጠቃላይ የእድሳት ሥራው መንግሥት በሚፈቅደው የፋይናንስ ሂደት አልቆ ዛሬ [ሐምሌ 5 ቀን፥ 2014 ዓ.ም] በይፋ እንዲጀመር ተደርጓል ብለዋል።

    ዶ/ር ችሮታው አክለውም፥ እንደ ሀገር ከፍተኛ የሆነ የግንባታ ዘርፉ መቀዛቀዝ ውስጥ ቢሆንም ሆስፒታሉ ካለበት ደረጃ እንዲሁም ከሕብረተሰቡ የሕክምና አገልግሎት አንገብጋቢ ጥያቄ አንፃር አዲሱ እንሰኪጠናቀቅ ነባሩን ሆስፒታል በልዩ ሁኔታና በጥራት አድሶ ጥቅም ላይ ማዋል በትኩረት የሚሠራ ነው ብለዋል። ለዚህም ሥራውን በተቀላጠፈ እና ደረጃውን በጠበቀ ሁኔታ አድሶ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የሚመለከተው ሁሉ በርብርብ እንደሚሠራ ተገልጿል።

    የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪና የዩኒቨርሲቲው ሥራ አመራር ቦርድ አባል አቶ አብዮት ደምሴ በበኩላቸው፥ ሆስፒታሉ ለጌዴኦ ዞን ብቻ ሳይሆን ለአጎራባች ክልሎች ጭምር አገልግሎት ሰጪ በመሆኑ “መከፈል ያለበት መስዋዕትነት ሁሉ ተከፍሎ በአጭር ጊዜ ውስጥ እድሳቱ እንዲጠናቀቅ ቦርዱም ሆነ የዞን አመራሩ ጥብቅ ክትትልና ድጋፍ ያደርጋል” ብለዋል። የሥራ ተቋራጭ ድርጅቱ የተጣለበት ኃላፊነት ከፍተኛ መሆኑን ገልፀው፥ የዩኒቨርሲቲው አመራር፣ የዞኑና አካባቢው አመራር እንዲሁም ሕብረተሰቡ በጋራ ተባብረው ውጤታማ የሆነ እድሳት እንዲከናወን ይሠራሉ ብለዋል።

    የዲላ ከተማ ከንቲባና የሆስፒታሉ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ተስፋፅዮን ዳካ በበኩላቸው፥ ሆስፒታሉ ብዙ ማኅበረሰብ የሚገለገልበት ሆኖ ሳለ ከጊዜ ወደ ጊዜ አገልግሎት አሰጣጡ እየተዳከመ ከአቅም በታች የሆነ አገልግሎት እየሰጠ መጥቷል፤ ስለሆነም ከዚህ ችግር እንዲወጣ እና ሕብረተሰቡ ማገኘት ያለበትን አገልግሎት የመስጠት አቅሙን በተሻለ ለመመለስ በርብርብ ይሠራል ብለዋል።

    የእድሳት ሥራውን ለማከናወን ውል የወሰደው ደሳለኝ አሥራደ ህንጻ ሥራ ተቋራጭ የተባለ ድርጅት ሲሆን ተወካዩ አቶ ፍጹም እምሩ ሆስፒታሉ ከአምስት ሚሊዮን ህዝብ በላይ የሚታከምበት ብቸኛ የዞኑ ሆስፒታል እንደመሆኑ የእድሳት ግንባታውን በአጭር ጊዜ ውስጥ አጠናቆ ለማስረከብ በትኩረት እንደሚሰሩ ገልፀዋል።

    ተወካዩ አክለውም የተሻለ ብቃት ያላቸውን ባለሙያዎች በመመደብ በተሻለ ጥራትና በተፋጠነ ጊዜ ግንባታውን አጠናቀው በማስረከብ ሕብረተሰቡ እና ዩኒቨርሲቲው የጣሉብንን አደራ እንወጣለን ነው ያሉት።

    የዲላ ዩኒቨርሲቲ ግንባታ ፕሮጀክት ፅሕፈት ቤት ኃላፊ ኢንጂነር በፍቃዱ መኩሪያ በዕለቱ የእድሳት ግንባታውን አስመልክቶ ባቀረቡት ገለፃ የሆስፒታሉን አጠቃላይ ገፅታ በከፍተኛ ጥንቃቄ ጥናት ተደርጎ ዲዛይን ተሠርቷል ብለዋል።

    ይሄው የእድሳት ዲዛይን ለጤና ሚኒስቴር ቀርቦ ከተገመገመ በኋላ የሚጠበቀውን ደረጃ ማሟላቱ በመረጋገጡ የእድሳት ግንባታው መፈቀዱን ገልፀው፣ በጥናቱ የተለየቱን ችግሮች የሚፈታ እድሳት እንደሚሠራ እና የተወሰኑ ተጨማሪ አዳዲስ ግንባታዎችም እንደተካተቱ አስረድተዋል።

    በእድሳት ግንባታ ሥራ ማስጀመሪያ መርሃግብሩ የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የሆስፒታሉ የሥራ አመራር ቦርድ ኃላፊዎች፣ የዩኒቨርሲቲውና የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሆስፒታሉ ማኅበረሰብ አካላት የተገኙ ሲሆን ግንባታው መጀመሩን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር ችሮታው አየለ ይፋ አድርገዋል።

    ምንጭ፦ ዲላ ዩኒቨርሲቲ

    የዲላ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ሆስፒታል እድሳት ተጀመረ

    Anonymous
    Inactive

    ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ ፕሮግራሞች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች በድምቀት አስመረቀ፤ ለቴዲ አፍሮ የክብር ዶክትሬት ሰጠ

    ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ ፕሮግራሞች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ሐምሌ 24 ቀን፥ 2013 ዓ.ም በድምቀት አስመረቀ። በዚህ ደማቅ የምረቃ ሥነ ሥርዓት የኢፌዴሪ የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚንስትርና የበዓሉ ልዩ የክብር እንግዳ የተከበሩ ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ፣ አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)፣ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር አሥራት አጸደወይን፣ የጎንደር ከተማ አስተዳደር ከንቲባና የዩኒቨርሲቲው ሥራ አመራር ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ ሞላ መልካሙ፣ የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ብርሀኑ ፈይሳ፣ የቀድሞ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንትና የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አማካሪ ፕ/ር መንገሻ አድማሱ፣ የተለያዩ የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ አባላት፣ የሀይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የተመራቂ ወላጆችና ቤተሰቦች እንዲሁም የዕለቱ ተመራቂዎች ተገኝተዋል።

    በዓመቱ በዩኒቨርሲቲው በተካሄደው በዚህ በሁለተኛው ዙር የተማሪዎች የምረቃ ሥነ ሥርዓት በመደበኛ፣ በተከታታይና በክረምት መርሀግብሮች ወንድ 4153፣ ሴት 2421 በአጠቃላይ 6574 ተማሪዎችን በመጀመሪያ፣ በሁለተኛ፣ በሦስተኛና በስፔሻሊቲ የትምህርት ደረጃዎች አስመርቋል፤ እንዲሁም ለአንጋፋው የሙዚቃ ሰው አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) የክብር ዶክትሬት ማዕረግ ሰጥቷል።

    የነገ የሀገራችን ተስፋ የሆኑ የዕለቱ ተመራቂዎች በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ፈታኝ ሁኔታዎችን ሁሉ በጽናትና በታላቅ ጀግንነት ተቋቁመው ለዚህች ልዩ ቀን በመድረሳቸው የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክታቸውን የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር አሥራት አጸደወይን አስተላልፈዋል። ተመራቂዎቻችን ወረርሽኙ የፈጠረውን አዲስ ሁኔታ በመቋቋም ለዚህ መብቃታቸውም ልጆቻችን በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥም ቢሆን ተፈትነው ማለፍ እንደሚችሉ ከወዲሁ ያረጋገጠ ታሪካዊ አጋጣሚ ነው ሲሉም አክለዋል።

    ፕሬዚዳንቱ እንደገለጹትም በጎርፍ መጥለቅለቅ ለተጎዱ ዩኒቨርሲቲው የቻለው ድጋፍ አድርጓል፤ የወረታ ግብርና ኮሌጅን የሳተላይት ማዕከል አድርጎ ከፍቷል፤ 6ኛው አጠቃላይ ሀገራዊ ምርጫ በሰላም እንዲካሄድ ብዙ ሠርቷል፤ እንቦጭን ለማስወገድ በርካታ ጥረት አድርጓል፤ ከተለያዩ የውጭ ሀገራት ተማሪዎችን ተቀብሎ በማስተማርና ሀገራዊ ትስስርን የመፍጠር ሥራ ተሠርቷል፤ በማይካድራና ሌሎች አካባቢዎች በተደረጉ ዘር-ተኮር ጥቃቶች ላይ በዩኒቨርሲቲው ምሁራን ጥናቶች እየተካሄዱ ነው፤ የኮቪድ ወረርሽኝን ለመከላከል አስፈላጊው ጥንቃቄ እየተደረገ ይገኛል፤ እንዲሁም በገበታ ለሀገር መርሀ ግብር ከገንዘብ ድጋፍ በተጨማሪ በዲዛይን ሥራ እና የጎርጎራ ከተማን መሪ ዕቅድ በማዘጋጀት ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ ነው። በአጠቃላይ 54 የሚሆኑ የማኅበረሰብ አገልግሎት ፕሮጀክቶች መተግበራቸውን የገለፁት ዶ/ር አሥራት አፀደወይን፥ በዚህ አመርቂ ተግባሩም ዩኒቨርሲቲው የተለያዩ እውቅናና ሽልማቶች ከተለያዩ አካላት እንደተበረከቱለት በመክፈቻ ንግግራቸው አንስተዋል። “ከአባይ ወንዝ የምንቀዳው ፍቅር እንጅ ጥላቻ እንዳልሆነ ለተመራቂ ልጆቻችን በጓዳም በአደባባይም ነግረን አሳድገናቸዋል” በማለትም አለመግባባቶች በሰላም ይፈቱ ዘንድ በአባይ ተፋሰስ ለሚገኙ ሀገራት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

    የኢፌዴሪ የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚንስትርና የበዓሉ ልዩ የክብር እንግዳ የተከበሩ ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ፣ እንደአድዋ በአንድ ያቆመን የአባይን ግድብን የውሃ ሙሌት በድል ባከናወንበት ወቅት በመካሄዱ የዛሬውን ምረቃ ልዩ ያደርገዋል ብለዋል። የራሳችንን የተፈጥሮ ሀብት በአግባቡ ባለመጠቀማችንና ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ማፍለቅና መጠቀም ባለመቻላችን በድህነት እንኖራለን፤ ለዚህ ደግሞ በእውቀት የተደራጀ ኃይል ያስፈልጋል ያሉት ዶ/ር ኢንጅነር ስለሺ በቀለ፥ ስለሆነም ለትምህርት ትልቅ ትኩረት መስጠት አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል። ተመራቂዎች በትምህርት ህይወታቸው ያገኙትን እውቀት በራስ በመተማመን ስሜት ከሁሉም ጋር በመከባበርና በመሥራት ታላቅ የሆነችውን ሀገር ታላቅነቷን ማስጠበቅ እንደሚችሉ ያላቸውን የጸና እምነት በመግለጽ ለተመራቂዎች መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

    የዕለቱ የክብር እንግዳ አያይዘውም የግድቡ ሥራ ሀገር አቀፍና አለማአቀፍ ትኩረትና ድጋፍ እንዲያገኝና በስኬት እንዲጠናቀቅ ላደረገው ጉልህ ሚና ለጎንደር ዩኒቨርሲቲ እውቅና ሰጥተዋል። ሁሉም ሰው በተሰማራበት ሥራ መልካም ውጤት በማስመዝገብ ራስንም፣ ሀገርንም የሚያስከብር መሆኑን ከድምጻዊ ቴዎድሮስ ካሳሁን ሁሉ ሊማር ይገባል በማለት ለአርቲስት ቴዎድሮስ፣ ለተመራቂዎችና ቤተሰቦቻቸው እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።

    ምንጭ፦ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ

    ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለቴዲ አፍሮ የክብር ዶክትሬት ሰጠ

    Anonymous
    Inactive

    በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ የተላለፈ መልዕክት

    የከፍተኛ ትምህርትና ስልጠና ተቋማት የገጽ ለገጽ ትምህርት መስጠት መጀመራቸውን ተከትሎ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ ለተቋማት፣ ለሠራተኞች፣ ለመምህራንና ለተማሪዎች ያስተላለፉት መልዕክት የሚከተለው ነው።

    በኮቪድ-19 ዓለምአቀፍ ወረርሽኝ ምክንያት የተቋረጠውን የከፍተኛ ትምህርትና ስልጠና የገጽ ለገጽ ትምህርት (in-class teaching) ለማስቀጠል እንዲቻል በየተቋማቱ በርካታ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ሲሠሩ መቆየታቸው ይታወሳል።

    ለዚህም እንዲያግዝ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርትና ስልጠና ተቋማት በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅት የገጽ ለገጽ ትምህርትን ለማስቀጠል ሊከተሏቸው የሚገቡ ፕሮቶኮሎችን በማዘጋጀት ተቋማት በመመሪያው መሠረት እንዲዘጋጁ ሆኗል።

    ይሄንንም ዝግጅት የክትትል ግብረኃይል በማዘጋጀትና በማሰማራት በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች በአካል ተገኝተው ግምገማ አካሂደዋል። በግምገማው ውጤት መሠረትም ተቋማቱ ያላቸው ዝግጅት ተማሪዎችን ለመቀበል የሚያስችል መሆኑ በመረጋገጡ ተመራቂ ተማሪዎች ወደ ትምህርትና ስልጠናቸው እንዲመለሱ ጥሪ ተደርጓል።

    በመሆኑም ውድ ተማሪዎች ከወራት ቆይታ በኋላ ወደ ትምህርት ገበታችሁ እንደመመለሳችሁና ትምህርትና ስልጠናው የሚቀጥለው በኮቪድ-19 ወረርሽኝን በመከላከል እንደመሆኑ፥ በተቋማቱ የሚኖራችሁ ቆይታ ኃላፊነት የተሞላበት፣ ጊዜን በአግባቡ መጠቀም ላይ ያተኮረና በከፍተኛ ጥንቃቄ የተሞላ እንዲሆን አሳስባለሁ።

    ወደየዩኒቨርሲቲዎቻችሁ ስትመለሱም በአመራሩ የሚሰጣችሁን የጥንቃቄ መመሪያ ሁሉ ተግባራዊ ልታደርጉ ግድ ይላል። ወረርሽኙን ራሳችንን ብቻ በመከላከል ልንወጣው የምንችል ባለመሆኑ ለትምህርታችሁ ትኩረት ከመስጠት ጎን ለጎን ማስክ (የፊት መሸፈኛ ጭንብል) በመጠቀም፣ ንፅህናን በመጠበቅና በመመሪያው ላይ የተቀመጡ ሌሎች ሕግጋትንም ተግባራዊ በማድረግ የራሳችሁንና የጓደኞቻችሁን ሕይወት እንድትጠብቁም አሳስባለሁ።

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አመራሩም ተማሪዎች ወደዩኒቨርሲቲ ሲመለሱ መመሪያውን ተግባራዊ የሚያደርጉበት ግንዛቤ በመፍጠርና ከዚህ ቀደም ሲገለፅ እንደነበረው የጥንቃቄ መልዕክቶችን ሁሉ ተግባራዊ እንዲያደርጉ በማመቻቸት እንዲሁም መመሪያው እንዲተገበር በማድረግ ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ አሳስባለሁ።

    መምህራን ከተማሪዎቹ ጋር ሰፊ ጊዜ የምታሳልፉ እንደመሆኑ ከመደበኛ ትምህርቱ ጎን ለጎን ተማሪዎች እንዳይዘናጉ የማድረግና የጥንቃቄ መመሪያውን እንዲያከብሩ የማስገንዘብ ኃላፊነት አለባችሁ።

    የአስተዳደር ሠራተኞችም ተማሪዎች በግቢ ውስጥ የሚኖራቸው መስተጋብር ጥንቃቄ አልባ እንዳይሆን፤ የእናንተም አበርክቶ ከፍተኛ ነውና እናንተ ጠንቃቃ ሆናችሁ ተማሪዎችንም እንድታነቁ ይሁን።

    በያዝነው ዓመት የሚኖረንን የትምህርትና ስልጠና ጊዜ በአግባቡ ለመጠቀምና ትምህርትና ስልጠናው በታቀደው ጊዜ እንዲከናወን ለማስቻል ከፍተኛ ሥነ-ልቦናዊና መንፈሳዊ ዝግጅት በማድረግ በቁርጠኝነት መንቀሳቀስና እንደ ጤናችን ሁሉ ሰላማችንንም ማስጠበቅ ኃላፊነታችንና ግዴታችንም ጭምር ነው።

    ለዚህም የትምህርትና ስልጠና ማኅበረሰቡ ሚና ከፍተኛ በመሆኑ ጤናችሁንና ሰላማችሁን በመጠበቅ፣ ውድ ጊዜያችሁን ለእውቀት ሸመታ፣ ማኅበረሰባችሁን በሚጠቅሙ እና ሀገራዊ ፋይዳ ባላቸው ጉዳዮች ላይ ብቻ በማተኮር እንዲሆን ከአደራ ጭምር አሳስባለሁ።

    ዓመቱ የተለያዩ የለውጥ ሥራዎችን የምንከውንበት ውጤታማና ሰላማዊ የመማር-ማስተማር ጊዜ የምናሳልፍበት እንዲሆን ከምንጊዜውም በላይ በጋራና በትጋት እንሠራለን!

    ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ
    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር
    ጥቅምት 14 ቀን 2013 ዓ.ም

    ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ የተላለፈ መልዕክት

    Semonegna
    Keymaster

    በኢትዮጵያ ስምንት ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል ተብለው ተለዩ

    ጎንደር (ኢዜአ) – በኢትዮጵያ ስምንት የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል (Center of Excellence) በመባል መለየታቸውን የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የጎንደር ዩኒቨርሲቲ በተመረጡ ትምህርት ቤቶች በትምህርት ጥራት ዙሪያ ያካሄደውን የምርምር ግኝቶች ላይ መስከረም 29 ቀን 2013 ዓም ከባለድርሻዎች ጋር ተወያይቷል።

    የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከፍተኛ አማካሪ ዶ/ር ወርቁ ነጋሽ በወቅቱ እንደገለጹት፥ በሀገሪቱ የሚገኙ 46 ዩኒቨርሲቲዎች በምርምር፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ እንዲሁም በአጠቃላይ ትምህርት በሚል በሦስት ደረጃዎች ተለይተዋል።

    ባለፉት ዓመታት በርካታ ችግር ፈቺ የምርምር ውጤቶችን ሲያበረክቱ የቆዩና ወደፊትም አስተዋጽዖ ይኖራቸዋል የተባሉ ስምንት ዩኒቨርሲቲዎች በምርምር ዘርፍ የልህቀት ማዕከል እንዲሆኑ መለየታቸውን ተናግረዋል።

    ጎንደርአዲስ አበባባህር ዳርመቀሌጅማሀዋሳአርባ ምንጭ እና ሐረማያ ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል እንዲሆኑ ተለይተዋል” ብለዋል ዶ/ር ወርቁ።

    ለአንድ ሀገር ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ችግር ፈቺ ምርምር ቁልፍ ሚና እንዳለው የገለጹት ዶ/ር ወርቁ፥ “ያደጉ ሀገሮች የእድገት ምስጢርም ከዚህ የመነጨ ነው” ብለዋል። የምርምር (Research) ዩኒቨርሲቲዎቹ በዓለምአቀፍ ደረጃ ከሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር አቻ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ አቅማቸውን ለመገንባት በትኩረት እንደሚሠራ አመላክተዋል።

    ሌሎች 15 የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ በሳይንስና ቴክኖሎጂ (Science and Technology) ዘርፍ ትምህርትና ስልጠና እንዲሰጡ መለየታቸውን ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ በቂ እውቀትና ክህሎት ያዳበረ ዜጋ ማፍራት እንዲችሉ ተከታታይ ድጋፍ እንደሚደረግላቸው አመላክተዋል።

    ቀሪዎቹ 23 ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ አጠቃላይ ትምህርትና ስልጠና እንዲሰጡ የተለዩ መሆኑን ዶ/ር ወርቁ አስታውቀዋል።

    የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር መርሻ ጫኔ ዩኒቨርሲቲው በርካታ ችግር ፈቺ ጥናትና ምርምር በማካሄድ ለማህበረሰቡ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረጉን ተናግረዋል።

    ላለፉት ሶስት አመታት ጎንደር ከተማን ጨምሮ በሰሜን፣ በማእከላዊና በምዕራብ ጎንደር ዞኖች በተመረጡ 1,343 የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ላይ በትምህርት ጥራት ዙሪያ ጥናትና ምርምር መካሄዱን ገልጸዋል። በምርምር ውጤቶቹ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይትና ምክክር እየተካሄደ መሆኑን አስታውቀዋል።

    “በዩኒቨርሲቲው የሥነ-ትምህርት ኮሌጅ መምህራን የተዘጋጀው የምርምር ውጤት ለፖሊሲ አውጪዎች ጠቃሚ ግብዓት ሆኖ የሚያገለግል ነው” ያሉት ደግሞ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አሥራት አጸደወይን ናቸው።

    ባለፈው ዓመት ዩኒቨርሲቲው ከ200 በላይ የምርምር ሥራዎችን ማካሄዱን ዶ/ር አሥራት አስታውሰዋል፤ ዘንድሮም በተለያዩ ዘርፎች ምርምር ለማካሄድ የሚያስችል ቅድመ ዝግጅት እያካሄደ እንደሚገኝ ፕሬዝዳንቱ ማሳወቃቸውን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዘግቧል።

    ለአንድ ቀን በተካሄደው ውይይት የዩኒቨርሲቲው መምህራንና የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም ከጎንደር ከተማ አስተዳደር የተውጣጡ መምህራንና የትምህርት አመራሮች ተሳትፈዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    የምርምር ልህቀት ማዕከል

    Semonegna
    Keymaster

    ትምህርት እንደሚጀመር ከሁለቱ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች የተሰጡ ማብራሪያዎች

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ትምህርት ሚኒስቴር በሦስት ሳምንት ጊዜ ውስጥ ትምህርት እንደሚጀመር ሲያሳውቅ፤ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ደግሞ ዩኒቨርሲቲዎች እና የቴክኒክና ሙያ ተቋማት የተቋረጠውን ትምህርት የሚያስቀጥሉበት አቅጣጫን አስቀምጧል።

    ከሁለቱም የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች መቼ እና እንዴት ትምህርት እንደሚጀመር የተሰጡት መረጃዎች የሚከተሉት ናቸው።

    ትምህርት ሚኒስቴር

    የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመከላከል የተቀመጡ ቅድመ ሁኔታዎችን በሦስት ሳምንታት ውስጥ ያሟሉ ትምህርት ቤቶች ትምህርት እንዲጀምሩ ተወስኗል።

    የዓለም የጤና ድርጅትና የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ጤና ሚኒስቴር ወረርሽኙን ለመከላከል ባስቀመጡት ቅድመ ሁኔታ መሠረት ትምህርት ቤቶች ከመከፈታቸው በፊት በመድኃኒት ማጽዳት፣ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭንብልና የእጅ ማጽጃ ማሟላት እንዲሁም አካላዊ ርቀትን ማስተግበር ይጠበቅባቸዋል፡፡

    ለሌላ አገልግሎት (ለምሳሌ፥ ለለይቶ ማቆያነት) ውለው የነበሩ ትምህርት ቤቶችም አስፈላጊውን የማስተካከያ ሥራ ሊሠራላቸው እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡

    እንደየ ትምህርት ቤቶቹ ነባራዊ ሁኔታ ትምህርት በፈረቃ እና አንድ ቀን በመዝለል ተራ ሊያስተምሩም ይችላሉ፡፡

    ትምህርት ሚኒስቴር ባስቀመጠው መስፈርት መሠረት በአንድ ክፍል ውስጥ ከ20 እስከ 25 ተማሪ ማስተማር የሚችሉ መሆንም ይጠበቅባቸዋል ተብሏል፡፡

    የተቀመጠው መስፈርት እንዳለ ሆኖ፡-

    • በገጠር ወረዳና ቀበሌ ከተሞች የሚገኙ ትምህርት ቤቶች በመጀመሪያው ዙር ጥቅምት 9 ቀን 2013 ዓ.ም፤
    • በሁሉም የዞንና የክልል ከተሞች የሚገኙ ትምህርት ቤቶች በ2ኛ ዙር ጥቅምት 16 ቀን 2013 ዓ.ም፤
    • በአዲስ አበባና አዲስ አበባ ዙሪያ ኦሮሚያ ልዩ ዞን የሚገኙ ትምህርት ቤቶች ደግሞ በሦስተኛ ዙር ጥቅምት 30 ቀን 2013 ዓ.ም

    ትምህርት እንዲጀምሩ የውሳኔ ምክረ ሀሳብ መቅረቡ ይታዋሳል፡፡

    በዚህ መሠረት የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመከላከል በሦስት ሳምንታት ውስጥ አስፈላጊውን ቅድመ ሁኔታ ያሟሉ ትምህርት ቤቶች በተቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ትምህርት መጀመር ይችላሉ ተብሏል፡፡

    የሳይንስ እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    መስከረም 14 ቀን 2013 ዓ.ም የኮቪድ-19 ወረርሽኝን እየተከላከልን የዩኒቨርሲቲዎችን እና የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠናን ከተቋረጠበት ለማስቀጠል በመሪዎች ደረጃ በተካሄደው ስብሰባ አቅጣጫ ተቀምጧል።

    በዚህም መሠረት፥ በዓለም የጤና ድርጅት መስፈርትና በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ጤና ሚኒስቴር የየኮቪድ-19 መከላከያ መመሪያ መነሻ፣ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር የትምህርትና ሥልጠና ዘርፍ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅት የማስተማርና የማሰልጠን ተግባራት ዝርዝር መመሪያ እንዲያዘጋጅና ተገቢውን ውይይት ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር በማድረግና ግንዛቤ በማሳደግ፣ የተቋማትን ዝግጁነት በማረጋገጥ፣ አግባብነት ያለውን የትምህርትና ሥልጠና መርሀግብር በማዘጋጀት ተማሪና ሰልጣኝ መቀበል የሚችሉ መሆኑን፤ ለዚህም ተቋማት ቀሪ የመስከረም ወር ቀናትንና የጥቅምት ወር የመጀመሪያ ሳምንትን የዝግጅት ምዕራፍ ሥራዎችን ለማከናወን እንዲጠቀሙ ስምምነት ላይ ተደርሷል።

    ስለሆነም፥ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ እስከ ጥቅምት ወር የመጀመሪያ ሳምንት መጨረሻ የተቋማትን የዝግጅት ምዕራፍ አፈፃፀም በአካል እየተገኘ ገምግሞ በቂ የኮቪድ-19 መከላከያ ዝግጅት ላደረጉት የመንግሥትና የግል ዪኒቨርሲቲዎች እንዲሁም የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ተቋማት ተማሪና ሰልጣኝ እንዲቀበሉ የሚፈቅድ ይሆናል። በቂ ዝግጅት ያላደረጉ ተቋማት፣ ዝግጅታቸውን እስከሚያጠናቅቁ ድረስ ክትትል ይደረጋል። ያለ በቂ ዝግጅትና ያለሚኒስቴሩ የመስክ ምልከታና ፈቃድ ተማሪዎችን ወይም ሰልጣኞችን ተቀብሎ መገኘት አግባብነት አይኖረውም።

    ስለሆነም፥ የ2012 ዓ.ም ተመራቂ ተማሪዎችና የስልጠና አጠናቃቂዎች እንዲሁም በሌሎች የትምህርትና ሥልጠና እርከን የሚገኙ የሕብረተሰብ ክፍሎች በቀጣይ በሚዲያ በሚታወጀው የተማሪና ሰልጣኝ ቅበላ መርሀግብር መሠረት በየተቋሞቻቸው ጥሪ የሚደርግላቸው መሆኑን፤ እስከዚያው ድረስ አስፈላጊውን ዝግጅት እያደረጉ እንዲቆዩ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ ገልጸዋል። አያይዘውም ትምህርት/ስልጠና በሚጀመርበት ጊዜ የተጣበበ የትምህርትና ስልጠና ጊዜ የሚኖር በመሆኑ፥ ተማሪዎች/ሰልጣኞች ቀጣይ ጊዜያቸውን ለንባብና ለተያያዥ ዝግጅቶች እንዲጠቀሙበት አሳስበዋል።

    ወቅቱ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በመሆኑ፥ ሁሉን አቀፍ ጥንቃቄ እየተደረገ የትምህርትና ስልጠና ተግባራትን በጋራ ሆነን እንወጣዋለን በማለት ዶ/ር ሳሙኤል መግለጫቸውን ቋጭተዋል።

    ትምህርት እንደሚጀመር

    Semonegna
    Keymaster

    በጉራጌ ዞን የመስቀል በዓል በተለያዩ ዝግጅቶች መከበር ተጀመረ
    (የመስቀል በዓል በጉራጌ ማኅበረሰብ)

    በሀገራችን በድምቀት ከሚከበሩ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ክብረ በዓላት መካከል የመስቀል በዓል አንዱ ነው። የመስቀል በዓል በጉራጌ ማኅበረሰብ ዘንድ ልዩ ቦታ የሚሰጠው እንደመሆኑ፥ በየዓመቱ በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ይከበራል። የዘንድሮውን የዋዜማ ዝግጅት በዞኑ ቸሃ ወረዳ የጠናቃ ቀበሌ ለኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በማያጋልጥ መልኩ የፌዴራል እና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በሀገር ሽማግሌዎች ምርቃት ከመስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ በድምቀት መከበር ተጀምሯል።

    በመክፈቻ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሐመድ ጀማል ታዳሚዎችን እንኳን አደረሳችሁ በማለት “የመስቀል በዓል የኛነታችን መገለጫ ነው፤ የመስቀል በዓል ትውፊታዊም መንፈሳዊም ነው። በመስቀል በዓል የእርስ በእርስ የመተሳሰብ፣ የአብሮነት፣ የፍቅር፣ የሰላም እንዲሆን የመልካም ምኞት ማብሰሪያ አበባ የሚሰጣጡበት ጊዜ ነው። እንዲሁም በሥራም ሆነ በሌላ አጋጣሚ ተራርቆ የቆየ ሰው የሚገናኝበት፣ ዘመድ ከዘመዱ የሚጠያየቅበት፣ የሚረዳዳበት እንዲሁም አዲስ ጎጆ የሚቀለስበት ጊዜ መሆኑ ማኅበረሰባችን ልዩ ቦታ ይሰጠዋል። አያይዘውም በበዓሉ ባህላዊ እሴቶቻችንን በደንብ አልምተን እንደ አንድ የቱሪዝም ገቢ ምንጭ በማድረግ ለሀገራዊ ብልጽግናችን መሠረት የምንጥልበት ነው ብለዋል።

    የመስቀል በዓል ከሀይማኖታዊ ክዋኔ ባሻገር ባህላዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያለው ሲሆን በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት የሚከበር ቢሆንም መስቀል በጉራጌ በተለየ የአከባበር ሁኔታ ይከበራል ብለዋል – አቶ መሐመድ።

    እንደ አቶ መሐመድ ገለፃ እንደ መስቀል ያሉ ቱባ ባህሎቻችን ታሪካቸው ሳይሸራረፍ ለትውልድ በማስተላለፍ ዘረኝነት፣ ጥላቻና ቂም በቀል በማስወገድ የሀገራችን ብልፅግና ለማረጋገጥ  ሁሉም ዜጋ የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ብለዋል።

    መርሀ-ግብሩን በጋራ ያዘጋጁት የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ፤ የጉራጌ ዞን አስተዳደር እና የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር በመተባበር ሲሆን፥ የዚህ ክብረ በዓል አከዋወን በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና ባህል ድርጅት /UNESCO/ ከማይዳሰሱ የሰው ልጅ ወካይ ባህላዊ እሴቶች (“intangible heritages of Ethiopia”) ተርታ መመዝገቡን በማስመልከት ሲሆን፥ በአከባበሩ ሥርዓት ውስጥ ያሉት ትውፊቶች በትውልድ ቅብብሎሹ ውስጥ ተጠብቀው ያለ ምንም ተፅዕኖ ክዋኔዎቹ እየቀጠሉ እንዲሄዱ የማስተማር ዓላማ ያለው እንደሆነ ተነግሯል።

    በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የባህል እሴቶች ልማት ዳይሬክተር ወ/ሮ እስከዳር ግሩም በበኩላቸው፥ ሀገራችን ኢትዮጵያ የበርካታ ባህላዊና ታሪካዊ ሀብት ባለቤት ብትሆንም በተገቢው ማልማትና ማስተዋወቅ ባለመቻላችን ከዘርፉ የምናገኘው ገቢ እንዳላደገ ገልጸዋል።

    አንድነታችን አጠናክረን ሀብቶቻችን ማልማት፣ መጠበቅና መንከባከብ አለብን። ይህ ደግሞ የቱሪዝም ዘርፍ እንዲነቃቃ ያደርገዋል። በተጨማሪም ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር ይቻላል ብለዋል።

    የቸሀ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ፈለቀ የመስቀል በዓል በጉራጌ ሁሉም በድምቀት ከማክበር ባለፈ የጉራጌ እሴት የሚገለፅበት በመሆኑ የረጅም ጊዜ ቅድመ ዝግጅት እንደሚደረግበት በማስታወስ፤ በዓሉንም በድምቀት ለማክበር ሁሉም የቤተሰብ አባል የድርሻውን ኃላፊነት እየተወጣ እንደሚከበር ገልጸዋል።

    ለበዓሉ ማብሰሪያ የጉራጌ ዞን የባህል ቡድንም ያሰናዳቸውን ሙዚቃዊ ክዋኔዎች እንደነ “ጊቻዌ፣ ጊቻዌ”፣ “አዳብና” የመሳሰሉት ተውኔታዊ ክዋኔዎች በሴቶችና ወንዶች የታየበት፣ የሥራ ባህልን፣ ሠርቶ ማደግን የሚያወድሱ፣ የሚያስተምሩ ማሳያዎች፣ ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅኑ በአንድነት በአብሮነት ባህላዊ እሴቶች የሚጎለብቱበት ተውኔታዊ ትዕይንቶች የተንፀባረቁበት ነበር።

    የመስቀል በዓል በጉራጌ ማኅበረሰብ

    Anonymous
    Inactive

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን መቀበል ከመጀመራቸው በፊት የተቋማቱ ዝግጁነት እንደሚረጋገጥ ተገለጸ

    አዲስ አበባ (የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር) – የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን መልሶ ለመክፈት የሚያስችሉ ሁኔታዎች ላይ መስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም በጅማ ዩኒቨርሲቲ መሰብሰቢያ አዳራሽ ውይይት ተካሂዷል።

    በውይይቱ መጀመሪያ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሙሉ ነጋ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በመከላከል የትምህርትና ስልጠና ተቋማት መልሶ የመክፈት ሂደትና ዝግጅት በሚል ርዕስ ምክረ-ሃሳብ አቅርበዋል።

    በ2012 ዓ.ም የተቋረጠዉን ትምህርት በልዩ ዕቅድ ለማጠናቀቅ በሚሠሩ ሥራዎችና ትምህርት ሲጀመር ሊደረጉ ስለሚገባቸው ጥንቃቄዎች እንዲሁም ቀደም ተብለው በከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ የሚደረጉ ጥንቃቄዎች ምን መምሰል እንዳለባቸው በምክረ-ሃሳባቸው ቀርቦ ውይይት ተካሂዶባቸዋል።

    በጉባኤው የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ በበኩላቸው ‘መቼ እንክፈት?’ ለሚለው ትክክለኛ መልስ እያንዳንዱ ዩኒቨርሲቲ በዓለም የጤና ድርጅት መለኪያ መስፈርት መሠረት ደረጃውን ጠብቆ በተዘጋጀ ዝርዝር በጥልቀት የዝግጅት መጠኑ ተፈትሾ ዝግጁ ሲሆን ብቻ ነው ብለዋል። በዚያ መሠረት የተቋማት ዝግጅት ይፈተሻል፤ በዳሰሳውም መሠረት መቀበል እንደሚችሉ ፍቃድ ይሰጣል ሲሉ አብራርተዋል።

    ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ እንደገለፁት፥ ቅድሚያ ለተመራቂዎች [ቅድሚያ] በመስጠት፣ ተማሪዎችን በመከፋፈል በትንሽ ቁጥር ይጀመራል። ይህም ከሚታዩ ነገሮች እየተማርን የተማሪ ቁጥር ለመጨመር ዕድል ይሰጠናል ብለዋል። ዝርዝር አፈጻጸሙ በምን እንደሚመራ ከጤና ሚኒስቴር ጋር በመሆን ፕሮቶኮል ይዘጋጃልም ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲዎች የለይቶ ማቆያ ማዕከላት እንደመሆናቸው የክልል መንግሥታት ሥራ ይጠበቅባቸዋል። አማራጭ የለይቶ ማቆያ (quarantine) ቦታዎችን ማዘጋጀትም ግድ ስለሚላቸው እዚያ ላይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ይሠራል ብለዋል። ተማሪዎችን በማጓጓዝ ሂደት ችግር እንዳያጋጥም ከትራንስፖርት ሚኒስቴር እና ጤና ሚኒስቴር ጋር በትብብር እንሠራበታለን ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎችን መልሶ ለመቀበል የሚያስችል እቅድ ካሁኑ አዘጋጅተው ከአስተዳደር ሠራተኞችና መምህራን ጋር በመወያየት የጋራ ሊያደርጉ እንደሚገባም አሳስበዋል። የበፊቱን አሠራር ይዘን መቀጠል አንችልም፤ ዝግጅታችንን፣ ተጋላጭነታችንን አውቀን ተማሪ እንቀበላለን። አንድ ብሎክ ወይም አንድ ካምፓስ ኮቪድ-19 ቢያጋጥም ምን እናደርጋለን ከሚለው ጀምሮ በዝርዝር መሥራት እና እያንዳንዱ እቅድ ያለተማሪዎች እገዛ ተፈፃሚ ስለማይሆን ወደእነሱ ለማስረፅ መሥራት የግድ ይለናል ብለዋል።

    ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ እንዳሉት፥ ጊዜው የተማሪዎች ሕብረት ኃላፊነት የሚፈተንበት ነው። የተማሪዎች ሕብረት አባላት የመፍትሄ ሃሳብ ሆናችሁ ለተፈፃሚነቱ ከዩኒቨርሲቲያችሁ ጋር በትብብር እንድትሠሩ ከእናንተ ይጠበቃል። ሰላማችሁን ማስጠበቅና ለደህንነታችሁ ዘብ መቆም ለትምህርታችሁ ቀጣይነት ዋስትና ነው ሲሉ አብራርተዋል። ዩኒቨርሲቲዎች መከፈታቸው ላይ ብቻ ሳይሆን ተመልሰው እንዳይዘጉም ጭምር የተማሪዎች ድርሻ ከፍተኛ እንደሆነም ጠቁመዋል።

    የጥንቃቄ ቁሳቁሶችን አስመልክቶም የትኞቹ በዩኒቨርሲቲዎች ይቅረቡ የትኞቹ በተማሪዎች ይሟሉ የሚለውን ከተጨባጭ ሁኔታ አንፃር ለይቶ መወሰን አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል።

    በውይይቱ ማጠቃለያ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ ውይይቱ ተቋማት የት ላይ እንደሆኑ ለይተን ድጋፍ ለማድረግ የሚያስችል ግንዛቤ ለመያዝ ታስቦ የተካሄደ ነው ብለዋል። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መሪዎች በአሁኑ ጊዜ ቁርጠኝነት የሚፈልግ የለውጥ ሥራ እየሠራን እንደሆነ መገንዘብ እና በዚያው መጠን መፍጠን ያስፈልጋቸዋል ብለዋል። ተማሪዎችን ወደ ትምህርት የመመለስ ሂደት ባለድርሻ አካላትን በተገቢው መንገድ የማቀናጀት ኃላፊነት ተወስዶ መሠራት ያለበት ጉዳይ ነውም ብለዋል።

    ተማሪዎችን ከመመለስና የኮቪድ-19 ለይቶ ማቆያ ቦታዎችን ከማዘጋጀት አንፃር የፌደራልም ሆነ የክልል መንግሥታት እያንዳንዱ የራሱን ኃላፊነት ወስዶ እንዲሠራ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሥራት ያስፈልጋል ሲሉ ገልፀዋል። እንደከፍተኛ ትምህርት ዓለም-አቀፋዊና ሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ ትኩረት እናደርጋለን። ምርምር ላይ የተገኘውን እውቀት ተጠቅመን ለሀገር የሚውል አድርገን መጠቀምም ይገባናል ብለዋል።

    ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ ሥራውን በማስፈፀም ሂደት ኃላፊዎች የግንኙነት (communication) ክፍተት እንዳይኖር በመነጋገር ሊሠሩ እንደሚገባ ጠቁመው አመራር የሁሉ ነገር ቁልፍ እንደመሆኑ በጋራ መሥራት ያስፈልጋል ብለዋል።

    ነገ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በጉዳዩ ላይ እንደሚወያይና ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ይጠበቃል የተባለ ሲሆን፤ ከዚያም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ተቋማቱን ለመክፈት ያበቃሉ ተብለው የተቀመጡ ዝርዝሮችን በመያዝ በዩቨርሲቲዎች በመገኘት ብቁ መሆን አለመሆናቸው ታይቶ አስፈላጊውን መስፈርት ካሟሉ ብቻ እንዲከፍቱ ይደረጋል ብለዋል – ዶ/ር ሳሙኤል።

    ተማሪዎችን መልሶ ለመቀበል በሚደረግ ቅድመ ዝግጅት ወደኋላ የቀራችሁ ዩኒቨርሲቲዎች ካላችሁ ፈጥናችሁ ዝግጅታችሁን አጠናቅቁ ብለው መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን፤ ጉዳዩንም እንደፕሮጀክት ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንዳለባቸው አስበዋል።

    ከተሳታፊዎች የተለያዩ ስጋት ናቸው ተብለው የተነሱ ጉዳዮች ተነስተው ውይይት የተደረገባቸው ሲሆን በሂደት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሆኖ ለመፍታት እንደሚሠራ ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን መቀበል

    Anonymous
    Inactive

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ መርሀግብሮች ያስተማራቸውን ከ900 በላይ ተማሪዎችን አስመረቀ

    ወልቂጤ (ሰሞነኛ) – የሦስተኛ ትውልድ ዩኒቨርሲቲ የሆነው ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ መርሀግብሮች ያስተማራቸውን 929 ተማሪዎች ነሐሴ 30 ቀን 2012 ዓ.ም ለሰባተኛ ጊዜ ባካሄደው የምረቃ ሥነ ሥርዓት አስመርቋል።

    በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ በክብር እንግድነት ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሙሉ ነጋ እንዳሉት፥ እውቀትና ብቃት ያለው የሰለጠነ የሰው ኃይል ለአንድ ሀገር እድገትና ቀጣይነት የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ ነው። በዚህ ረገድ ጥራትና አግባብነት ያለው ትምህርት በተለይ ደግሞ ከፍተኛ ትምህርት ማስፋፋት ወሳኝ ነው ብለዋል።

    ዶ/ር ሙሉ አክለውም፥ መንግሥት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሀገራችንን ሕዝብ ህይወት ቀላልና ዘመናዊ በማድረግ ወደተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር ቁልፍ ሚና እንዳላቸው በማመን በየዓመቱ ከፍተኛውን የሀገሪቱን በጀት ለትምህርት መድቦ እየሠራ ይገኛል ብለዋል።

    ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የለውጥ ሃሳቦችን በማፍለቅና በመተግበር መልካም አርአያ የሚሆኑ ዜጎችን ማፍሪያ፣ የዲሞክራሲያዊ አስተሳሰቦችና ቴክኖሎጂዎች መፍለቂያ፣ የባህላዊ እሴቶቻችን መጎልበቻ፣ የሕዝቦች የመተሳሰብ፣ የመቻቻልና የአብሮነት ባህል የሚቀመርባቸው ማዕከላት እንዲሆኑ ማድረግ አማራጭ የሌለው መፍትሄ ነው ብለዋል – ዶ/ር ሙሉ።

    ሚኒስትር ዴኤታው ሰላም በምንም ነገር የማይተካ መሆኑን ገልጸው፥ ተመራቂዎች የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት እንዲደግፉና በህይወት ጎዳናቸው ከጽዩፍ አስተሳሰብና እና ድርጊት ተጠብቀው በተሰማሩበት መስክ የችግሮች መፍትሄ በመሆን ሀገራቸውን እንዲያገለግሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ዶ/ር ሙሉ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸው፤ ተመራቂዎች ሀገራችሁንና ሕዝባችሁን በሚጠቅሙ ሥራዎች ላይ በመሰማራት ታታሪ፣ የሀገራችሁን ሁለንተናዊ እድገት እና ብልጽግና የምታረጋግጡ ሰላም ወዳድ እንድትሆኑ አደራ እላለሁ ብለዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ፋሪስ ደሊል በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው በአዋጅ የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት በምርምር፣ በማኅበረሰብ-አቀፍ አገልግሎት (community-based service) እና መማር-ማስተማር መስክ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም ኮቪድ-19 ከመጣ በኋላ የዩኒቨርሲቲው ሠራተኞች የአንድ ወር ደመወዛቸውን በማዋጣት አቅመ ደካሞችን መርዳታቸውን ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው ከ3,000 ሊትር በላይ ሳኒታይዘር፣ 4,000 የፊት ጭንብል (face-mask)፣ 1800 ብሊች (bleach) የማምረት ሥራዎችን ሠርቶ በጉራጌ ዞን ለሚገኙና በሥራ ጸባያቸው ለቫይረሱ ተጋላጭ ለሆኑ ተቋማት ማበርከቱን ጠቁመዋል። ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የለይቶ ማቆያ ማዕከል (quarantine center) ሆኖ በማገልገል ላይም ይገኛል ብለዋል።

    በምርምር ረገድም ድርቅን በመቋቋም የሚታወቀውን ቆጮን ጨምሮ በተለያየ መልኩ ለምግብነት የሚውለውን እና የአከባቢው ማኅበረሰብ የኑሮ አለኝታ የሆነውን የእንሰት ተክል እንዳይጠፋ፣ እንዲሁም ዝርያው እንዲጠበቅና እንዲሻሻል የእንሰት ማዕከል በማደራጀት ዝርያዎችን የማሰባሰብ ሥራዎችን እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

    ዶ/ር ፋሪስ ባስተላለፉት መልዕክት ተመራቂ ተማሪዎች ሥራ ወዳድና ታታሪ፣ በሕግ የበላይነት ላይ የማትደራደሩ፣ የጥላቻን ዘር የማትዘሩ በጥላቻ ሳይሆን የተዘራውን ክፉ አረም በፍቅርና አብሮነት የምትነቅሉ በሥነ-ምግባር የታነጻችሁ ሀገር ተረካቢ ብቻ ሳትሆኑ አሻጋሪ ናችሁ ብለዋል።

    በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የዛሬው ምረቃ ሥነ ሥርዓት የተሳተፉት በክረምትና በማታ መርሀግብሮች በአምስት ኮሌጆች ስር በሚገኙ 15 ትምህርት ክፍሎች ከዓለምአቀፉ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ (ኮቪድ-19) በፊት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ወንድ 597፣ ሴት 143፤ በድምሩ 840 የቅድመ ምረቃ ተማሪዎች እና በቢዝነስና ኢኮኖሚክስ እንዲሁም በግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ኮሌጆች ስር በሚገኙ አራት ትምህርት ክፍሎች ከወረርሽኙ በኋላም በቴክኖሎጂ አማራጮች ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ በመደበኛና በማታው የድኅረ ምረቃ መርሀግብሮች ወንድ 81፣ ሴት 8፤ በድምሩ 89 ምሩቃን ናቸው።

    በ2004 ዓ.ም በ13 የትምህርት መስኮች 595 መደበኛ ተማሪዎችን ተቀብሎ ማስተማር የጀመረው ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በአሁኑ ጊዜ በስምንት ኮሌጆችና አንድ ትምህርት ቤት በቅድመ ምረቃ 50 መርሀግብሮች እንዲሁም ሁለተኛ ዲግሪ እና 12 ፕሮግራሞች በጠቅላላው ከ14 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በመደበኛ፣ በማታና በክረምት መርሃ ግብሮች እያስተማረ ይገኛል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    በሁለቱ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲዎች ያሉ የልህቀት ማዕከላት የሚሹትን ትኩረት ለይቶ ለመደገፍ ያለመ ጉብኝት ተካሄደ

    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ ዳይሬክተር ጄኔራሎች፣ ከፍተኛ አማካሪዎች እና ሌሎች ባለሙያዎችን የያዘ ቡድን በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ እና በአዳማ ሳይንስና ቴክሎጂ ዩኒቨርሲቲዎች የሥራ ጉብኝት አድርጓል።

    በጉብኝቱ በሁለቱም ዩኒቨርሲቲዎች በአካል በመገኘት ዩኒቨርሲቲዎቹ የልህቀት ማዕከላት ሆነው ከተፈጠሩ ጊዜ አንስቶ ‘የመንግሥትን ተልዕኮ ተሸክመው የት ደርሰዋል? ምን ውጤት አስመዝግበዋል? ያጋጠማቸው ማነቆ ካለስ ምንድን ነው?’ የሚሉትን ጉዳዮች ለመለየትና መፍትሄ ለማስቀመጥ እንደተካሄደ ተገልጿል።

    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ፕ/ር አፈወርቅ ካሱ የጉብኝቱ ዓላማ በሀገራችን 16 የተለያዩ የልህቀት ማዕከላትን የያዙት አዲስ አበባ እና አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲዎች ከተቋቋሙለት ዓላማ አንፃር የሚገባቸውን ያህል እየሠሩ ነው ወይ የሚለውን ለማየት፣ ያጋጠሟቸውን ችግሮች ለመለየትና በዚያው መጠን ድጋፍ ለማድረግ መሆኑን ገልፀዋል።

    ሁለቱን ዩኒቨርሲቲዎች ሐምሌ 2006 ዓ.ም መንግሥት የሳይንስና ቴክኖሎጂ ተቋም እንዲሆኑ አድርጎና ተጠሪነታቸውን በወቅቱ ለሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አድርጎ ሲያዋቅራቸው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ስርጸት ዩኒቨርሲቲዎች ተብለው በልዩ ሁኔታ የተመሠረቱ ሲሆን፤ ከመማር-ማስተማር ሥራ ጎን ለጎን በጥናትና ምርምር ልህቀት ማዕከልነት (centers of excellence) በኢንዱስትሪ-ዩኒቨርሲቲ ትስስር (industry-university linkages) እና በኢንኩቤሽን ማዕከልነት (incubation centers) እንዲያገለግሉ ታስበው ነው ብለዋል።

    በልህቀት ማዕከላቱ ተማሪዎች ተምረው ሲወጡ ኢንዱስትሪውን በቀጥታ መቀላቀል የሚችሉበት አቅም እንዲያፈሩ ታልሞ መሠራት እንዳለበት ጠቁመው፥ ይህ እውን እንዲሆን ከመቼውም ጊዜ በተለየ ሁኔታ በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ሥራዎች ጋር አገናዝበን በቋሚነት በዕቅድ እንድናግዛቸው እንሠራለን ብለዋል ፕ/ር አፈወርቅ። የልህቀት ማዕከላት በሀብት መደገፍ እንዳለባቸው ገልጸው፥ ነገር ግን ከመንግሥት ቋት ብቻ ሊሆን ስለማይቻል ሀብቶች ማፈላለግ ላይ በጋራ መሥራት ይጠበቃል ብለዋል።

    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ በበኩላቸው፥ የተደራጀ ተቋማዊ አሠራር በመፍጠርና ተቋማዊ አቅምን በመገንባት ተቋማቱን ወደ ትክክለኛ የልህቀት ማዕከልነት መለወጥ ይቻላል ብለዋል። በአከባቢያቸው ከሚገኙ ኢንዱስትሪዎች ጋር ትስስር በመፍጠር መሥራት እንደሚያስፈልግም ጠቁመዋል። የሀገራችን የቴክኖሎጂ፣ ምህንድስና፣ ሳይንስና ምርምር ተቀባይ ብቻ ሆኖ መቀጠል የለበትም ያሉት ዶ/ር ሳሙኤል፥ መሪ እንዲሆኑ ሀብት አፈላልጎ ዩኒቨርሲቲ-ኢንዱስትሪ ትስስር ፈጥሮ መሥራት ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። ቴክኖሎጂ ላይ ትኩረት ሰጥተው እንዲሠሩ በሁሉም የልዕቀት ማዕከላት የሰው ኃይል ችግር መፍታት እንደሚገባ ጠቁመው፤ ለዚህም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥልና ለሀገር ብልጽግና ካላቸውም ፈይዳ አንጻር በየደረጃው ካሉ ባለድርሻ አካላት ጋር በመነጋገር አስፈላጊው ድጋፍና ክትትል እንዲሚደረግላቸውም ገልፀዋል።

    ቡድኑ በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በነበረው ጉብኝት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ደረጀ እንግዳ በዩኒቨርሲቲው ያለውን ነባራዊ ሁኔታ የገለፁ ሲሆን፤ ዓለምአቀፍ እውቅና ለማግኘት የሚያግዙ የአሠራር ሂደቶችን ተከትለው ለመሥራት እየጣሩ መሆኑን ገልፀው፥ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ቢያግዘን ያሏቸውን ተግዳሮቶች አቅርበው ውይይቶች ተካሂደው የመፍትሄ ኃሳቦችም ተጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው ግቢ ውስጥ ያሉ የልህቀት ማዕከላት፣ ቤተ-ሙከራዎች እና የግንባታ ሥራዎችም ተጎብኝተዋል።

    በተመሳሳይ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ጉብኝት ሲካሄድ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ለሚ ጉታ ዩኒቨርሲቲው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ተብሎ ከተሰየመበት ከ2006 ዓ.ም ጀምሮ የተሰሩ ሥራዎችን እና ያጋጠሙ ችግሮችን፥ እንዲሁም የተፈጠሩ ትስስሮችን (partnerships) እና አጠቃላይ በዩኒቨርሲቲው ያለውን የሰው ሀብትና ተማሪዎች መረጃ አቅርበው ውይይት ተካሂዷል። በዩኒቨርሲቲው ልዩ ነው ያሉትን የደብል ሜጀር እና ፋስት ትራክ የትምህርት አሰጣጥ ሁኔታንም ጨምረው አብራርተዋል። ፕሬዚዳንቱ እንዳሉት፥ በአሁኑ ጊዜ በዩኒቨርሲቲው 161 የሦስተኛ ዲግሪ (doctoral) ተማሪዎች አሉ።

    በሁለቱ ጉብኝቶች ከተነሱት ዋና ዋና ድጋፍ የሚሹ ጉዳዮች ውስጥ የግዥ ሥርዓት ችግሮች፣ የተሽከርካሪዎች እጥረት፣ ብቁ መምህራን ከገበያ ላይ በቀላሉ ያለማግኘት፣ በፋይናንስ ምክንያት የግንባታ ሥራዎች መዘግየት ይገኙበታል።

    በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በነበረው ቆይታ ማጠቃለያ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሙሉ ነጋ እንዳሉት፥ የልህቀት ማዕከላት ሲባል አንድ ተቋም በአገሪቱ መሪ የሆነ የቴክኖሎጂ ማዕከል መሆን ማለት ነው። ይሄንን ደግሞ ከኢንዱስትሪ ጋር ትስስር በመፍጠር፣ ከቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና (TVET) ማዕከላት ጋር በመቀናጀት ኢንዱስትሪውን የሚመጥን፣ የኢንዱስትሪውን ፍላጎት ያሟላ ሰልጣኝ ለገበያ የሚያቀርብ፣ ተግባራዊ ምርምሮች የሚካሄዱበት መሆን ሲቻል ነው ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲዎቹ ከሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ድጋፍ እንፈልጋለን ብለው ያቀረቧቸውን በመውሰድ እንሠራበታለን ሲሉም ዶ/ር ሙሉ አክለዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ ዘመናዊ የሳይንሳዊ አስተሳሰቦች እና የቴክኖሎጂ ውጤቶች ተገናኝተው ለሀገር ብልጽግና የሚውሉባቸው እንደመሆናቸው አስፈላጊው ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።

    በሁለቱም ዩኒቨርሲቲዎች ያሉ የልህቀት ማዕከላት በቡድኑ የተጎበኙ ሲሆን፤ በጉብኝቱም ዩኒቨርሲቲዎቹ የተለያዩ የሀገር ሀብት የሆኑና ምናልባትም በኢትዮጵያ ውስጥ በሌሎች ተቋማት የሌሉና በተለይ ለምርምር ትልቅ ፋይዳ ያላቸው እንደ ኤሌክትሮማይክሮስኮፕ ያሉ መሣሪያዎች መኖራቸው ተመልክቷል። ይሄንንም ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር ትስስር በመፍጠር በጋራ ለመጠቀም የሚቻልባቸው ሁኔታዎች ማመቻቸት ያስፈልጋል ተብሏል። በቀጣይም ተቋማቱ የተፈጠሩበትን ዓላማ ማሳካት እንዲችሉ እና ውጤታማ ሥራዎችን ለመሥራት እንዲቻላቸው የሚያግዙ የታቀዱ ድጋፍና ክትትሎች ከሌላው ጊዜ በተለየ ይካሄዳሉ ተብሏል።

    አዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሚገኙ የልህቀት ማዕከላት፦

    1. Sustainable Energy
    2. Mineral Exploration, Extraction and Processing
    3. Nano Technology
    4. Bioprocessing and Biotechnology
    5. Construction Quality and Technology
    6. High Performance Computing and Big Data Analysis
    7. Artificial Intelligence and Robotics
    8. Nuclear Reactor and Technology

    አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሚገኙ የልህቀት ማዕከላት፦

    1. Space Technology Institute
    2. Institute Of Pharmaceutical Science
    3. Institute Of Water Resource and Irrigation Engineering
    4. Electrical System and Electronics
    5. Advanced Manufacturing Engineering
    6. Advanced Material Engineering
    7. Urban Housing and Development
    8. Transportation and Vehicle

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ እና መቀሌ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን አስመረቁ

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የመደበኛ እና የተከታታይ ትምህርት መርሀ ግብር የድኅረ-ምረቃ ተማሪዎቹን ነሐሴ 23 ቀን 2012 ዓ.ም አስመርቋል። የክብር እንግዳና አስመራቂ በመሆን በቪዲዮ ኮንፍረንስ መልዕክታቸዉን ለተመራቂዎች ያስተላለፉት የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤ ክፍሌ፥ ተመራቂዎች ሀገራቸዉን ከድህነትና ኋላ-ቀርነት ለማላቀቅ በያዙት ሙያ ጠንክረዉ በመሥራት የበኩላቸዉን እንዲወጡ ጥሪያቸዉን በማስተላለፍ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክታቸዉን ለተመራቂዎችና ለቤተሰቦቻቸዉ አስተላልፈዋል ።

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ (ኮቪድ-19) ጋር ተያይዞ ከሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር በተቀመጠዉ አቅጣጫ መሠረት፥  በበይነ-መረብ (online) አማካኝነት በማስተማር የድኅረ-ምረቃ ትምህርታቸዉን ሲከታተሉ ከነበሩ ከ45 ተማሪዎች ዉስጥ 38 ተመራቂዎች በኤሌክትሪካል ፓወር ኢንጂነሪንግ (electric power engineering)፣ በሕብረተሰብ ጤና ሳይንስ (public health)፣ በቢዝነስ አድሚንስትሬሽን (business administration)፣ በአካዉንቲንግ እና ፋይናንስ( accounting and finance) በዩኒቨርሲቲዉ ሴኔት ሌጅስሌሽን መሠረት የድኅረ ምረቃ  መስፈርቱን ስላሟሉ መመረቃቸዉን የዩኒቨርሲቲዉ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሀብታሙ አበበ በይፋ በማስታወቅ፤ ተመራቂዎች በተማሩበት መስክ የሰዎች ልጆችን ክብር ጠብቀዉ ሀገራቸዉን በቅንነት እንዲያገለግሉ ጥሪያቸዉን አስተላልፈዋል ።

    ፕሬዝዳንቱ አክለዉም ተመራቂዎች ወደ ብልጽግና ሀገሪቱን ለሚያሸጋግሩት ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ እና ለልዩ ልዩ የገበታ ለሀገር ፕሮጀክቶች የበኩላቸዉን አስተዋፅኦ እንዲያበረክቱ ጥሪ በማስተላለፍ በራሳቸዉ እና በዩኒቨርሲቲዉ ማሕበረሰብ ስም የእንኳን ደስ ያላችሁ መልዕክታቸዉን ለተመራቂዎች እና ለቤተሰቦቻቸዉ አስተላልፈዋል ።

    የደቡብ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ አቅናዉ ካዉዛ፣፥ የሀድያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ፣ እና የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የሥራ አመራር ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ አቶ አሸናፊ ጴጥሮስ እንዲሁም የዩኒቨርሲቲዉ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት እና የዩኒቨርሲቲዉ የማኔጅመንትና የሴኔት አባላት የምረቃዉን ሥነ-ሥርዓት መታደማቸዉም ተመልክቷል።

    በዕለቱ ከተመረቁት ተማሪዎች መካከል ተሾመ ሊሬ በሰጠው አስተያየት፥ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ተጽዕኖ ተቋቁሞ ለምረቃ በመብቃቱ መደሰቱን ገልጿል። በሀገሪቱ መከፋፈልን የሚፈጥሩ ጉዳዮችን በመተው፥ በአንድነት ለእድገት መሰለፍ እንደሚባ አመልክቶ በሰለጠነበት ሙያ ሀገሩን ለማገልገል እንደሚጥርም ተናግሯል።

    በሀገሪቱ የተጀመረውን የለውጥ ጉዞ ለማሳካት በቅንጅት መሥራት ያስፈልጋል ያለው ደግሞ በቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን (business administration) ሙያ የተመረቀው መስቀሉ ዳራ ነው። በሰለጠነበት ሙያ ራሱን፣ ብሎም ቤተሰቡንና ሀገሩን በመገልገል የዜግነት ግዴታውን ለመወጣት ዝግጁ መሆኑንም ገልጿል።

    ከተማሪዎች ምርቃት ዜና ሳንወጣ፥ መቀሌ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የሙያ መስኮች እና የዲግሪ መርሀ-ግብሮች ያስተማራቸውን ተማሪዎች በዚሁ ዕለት (ነሐሴ 23 ቀን 2012 ዓ.ም) በበይነ-መረብ (virtual) አስመርቋል። በዕለቱ በመጀመሪያ ዲግሪ (bachelor)፣ በሁለተኛ ዲግሪ (master) እና በሦስተኛ ዲግሪ (doctorate) እና ስፔሻሊቲ ዲግሪ (specialty degree) ትምህርታቸውን ተከታትለው ያሰመረቃቸው ተማሪዎች ቁጠር በአጠቃላይ 4,290 እንደሆነ ከዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ፕ/ር ክንደያ ገብረሕይወት ያገኘንው መረጃ ያመለክታል። በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ሊቀመንበር ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ናቸው።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive

    ለመጪው የትምህርት ዘመን ትምህርት ቤቶች ከነሐሴ 20 ጀምሮ ምዝገባ እንደሚጀምሩ ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)፦ የ2013 ዓ.ም. የትምህርት ዘመን ምዝገባ ከነሐሴ 20 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ እንደሚጀመር ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ ትምህርት ቤቶች የቀጣይ ዓመት የትምህርት ምዝገባን ከነሐሴ 20 ጀምረው ማካሄድ ይችላሉ ብሏል።

    የትምህርት ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ወ/ሮ ሀረጓ ማሞ፥ ትምህርት ቤቶች ምዝገባውን ሲያካሂዱ ኮሮና ቫይረስን (ኮቪድ 19) ለመከላከል በዓለም የጤና ድርጅት እና በኢፌዲሪ ጤና ሚኒስቴር የተቀመጡ ቅድመ ዝግጅቶችንና መከላከያ መንገዶችን በሚገባ በመተግበር መሆን እንዳለበት አሳስቧል።

    ትምህርት የሚጀመርበት ቀን በቀጣይ እንደሚወሰንና ይፋ እንደሚደረግም የገለፁት ዳይሬክተሯ፥ የቀጣዩ ዓመት የትምህርት ሂደት ስኬታማ እንዲሆንም ተማሪዎች፣ መምህራን፣ ወላጆችና መላው የትምህርት ማኅበረሰብ ይህን አስቸጋሪ ወቅት ለማለፍ የሚተላለፉትን ገዢና አስፈላጊ መልዕክቶች ብቻ በመከታተልና ቫይረሱ ሊተላለፍ የሚችልባቸውን መንገዶች ከውዲሁ በማስወገድ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግም አሳስበዋል።

    አካላዊ ርቀትን ጠብቆ ለማስተማር፣ የንፅህና መጠበቂያዎችን ከማዘጋጀትና መሰል የኮሮና ቫይረስን  የመከላከያ መንገዶችን ተግባራዊ ለማድረግ በሚያስችል መልኩ ቀድመው ዝግጅት የሚደረግባቸው ተግባራትም እንደሆኑ አክለው ገልጸዋል።

    በምን ዓይነት መልኩ ትምህርት መጀመር እንዳለበት የተለያዩ አማራጮችን ለማመላከት ሰፊ ውይይት እየተደረገባቸው ሲሆን፥ ውሳኔዎች ላይ ሲደረሱ በቀጣይ ይፋ ይደረጋሉ።

    የ8ኛና የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ጊዜን በተመለከተ ትምህርት ሚኒስቴር በቅርብ የሚያሳውቅ ሲሆን ተማሪዎች ራሳቸውን እያዘጋጁ እንዲቆዩ ሚኒስቴሩ አሳስቧል።

    በመጪው የትምህርት ዘመን ተማሪዎች ለኮሮና ተጋላጭ እንዳይሆኑ ትምህርት ሚኒስቴር ምን ዓይነት ዝግጅት እያደረገ ነው?

    በ2013 የትምህርት ዘመን ተማሪዎች ለኮሮና ተጋላጭ እንዳይሆኑ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ትምህርት ሚኒስቴር ነሐሴ 19 ቀን 2012 ዓ.ም. አስታወቋል።

    የትምህርት ሚኒስትሩ ዶ/ር ኢ/ር ጌታሁን መኩሪያ እንደገለጹት፥ የቀጣዩ ዓመት ትምህርት ምዝገባ ከነገ ነሐሴ 20 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ በመንግሥት እና በግል ትምህርት ቤቶች እንደሚጀመር እና ትምህርት ቤቶች የኮሮና ቫይረስ መከላከያ ቅደመ ዝግጅቶችንና  ተግባራትን በተገቢው መንገድ በመተግበር ምዝገባ እንዲያከናውኑ አሳስበዋል።

    የበሽታው ሁኔታ እየተስፈፋ ቢሆንም የትምህርት ዝግጅት እና እንቅስቃሴ መጀመር አስፈላጊ ሆኑ መገኘቱን ነው ሚኒስትሩ የተናገሩት።

    ወደ መማር ማስተማር ተግባር በሚገባበት ወቅት ለተማሪዎች ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር እንደሚሠራ ገልጸው፥ የፊት መሸፈኛ ጭንብል (face mask)፣ የእጅ ማፅጃ (sanitizer) እና መሰል አቅርቦቶችን ከባላድርሻ አካላት ጋር በመሆን ለማቅረብ በዝግጅት ላይ መሆናቸውን ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    በግልም ሆነ በመንግሥት ትምህርት ቤቶች የኮሮና ቫይረስ ስርጭት እንዳይከሰት ተማሪዎች የፊት መሸፈኛ ጭንብል በማድረግ፣ አካላዊ ርቀትን በመጠበቅ እና እጅን በተደጋጋሚ በመታጠብ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚኖርባቸው ሚኒስትሩ አሳስበዋል።

    ከቅድመ መደበኛ ጀምሮ እስከ 12ኛ ክፍል ላሉት ተማሪዎች በ2012 የትምህርት ዘመን በ2ኛ ሴሚስተር ያለፋቸውን ትምህርቶች ማካካሻ ለመስጠት መታሰቡንም ዶ/ር ኢ/ር ጌታሁን ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮሮፖሬሽን (EBC) ጋር በነበራቸው ቆይታ ገልጸዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    በመጪው የትምህርት ዘመን ተማሪዎች

    Anonymous
    Inactive

    የማዕድንና ነዳጅ ሚኒስቴር እስካሁን ድረስ አስር የማዕድን ምርመራ እና ሁለት የማዕድን ምርት ፈቃዶችን ሰጥቷል

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የማዕድንና ነዳጅ ሚኒስቴር በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች የማዕድናት ፍለጋ እና ልማት ለማካሄድ ፈቃድ ለጠየቁና የፈቃድ መውሰጃ መስፈርቶችን አሟልተው ለቀረቡ ለ12 የማዕድን ኩባንያዎች ፈቃድ ተሰጥቷል። ሁለቱ የምርት ፈቃዶች ሲሆኑ አስሩ የምርመራ ፈቃዶች ናቸው።

    የምርት ፈቃድ የተሰጣቸው የባዛልት እና የዕምነበረድ ማዕድን ምርት ሲሆኑ ሌሎች አስር ኩባንያዎች ደግሞ በደለል ወርቅ፣ ወርቅ እና መሰል ማዕድናት፣ ብረት፣ ማንጋኔዝ፣ ክሮማይት፣ ብር እና ጀምስቶን ማዕድናት ምርመራዎች ናቸው።

    ሁለቱ የምርት ፈቃዶች ለኢንቨስትመንት 270,186,310.00 (ሁለት መቶ ሰባ ሚሊዮን አንድ መቶ ሰማንያ ስድስት ሺ ሶስት መቶ አስር) ብር የተመዘገበ ካፒታልና ለ187 ዜጎች የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ ሲሆን፥ የምርመራ ፈቃዶች ደግሞ 131,935,555.00 ብር (አንድ መቶ ሰላሳ አንድ ሚሊዮን ዘጠኝ መቶ መቶ ሰላሳ አምስት ሽህ ዘጠኝ አምስት መቶ አምሳ አምስት) ብር የተመዘገበ ካፒታል እና በምርመራ ወቅት በድምሩ ለ293 ዜጎች የሥራ ዕድል ይፈጥራሉ። ምርመራ ሂደታቸውን በስኬት አጠናቀው ወደ ሥራ ሲገቡም ከሥራ ዕድል ፈጠራ እስከ ውጭ ምንዛሬ ግኝትና ማዳን ጉልህ አስተዋፅኦ ያበረክታሉ።

    የምርመራ ፈቃዱ የውሉ ስምምነት ፊርማው ከተፈረመበት ቀን ጀምሮ እንደ የፍቃድ ዓይነት ከ1 ዓመት እስከ 3 ዓመት የሚፀና ሆኖ፥ የፈቃድ ዘመኑም ሲጠናቀቅ በባለፈቃዱ ጥያቄ መሠረትና ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ሲያምንበት ሊታደስ የሚችል ነው።

    ስምምነቱን በፈቃድ ሰጪው መሥሪያ ቤት በኩል የፈረሙት ወ/ሮ ስመኝ ውቤ የማዕድንና ነዳጅ ሚኒስቴር ሚንስትር ዴኤታ (የማዕድን ዘርፍ) ሲሆኑ፥ በባለፈቃዶቹ በኩል የፈቃድ ወሳጅ ኩባንያዎች ዋና ሥራ አስፈጻሚዎች ናቸው። ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ኢትዮጵያ ለወጠነችው የኢንዱስትሪያዊነት መዋቅራዊ ሽግግር የኢንዱስትሪ ዘርፉ የሚፈልገውን የማዕድናት ግብዓት ለሟሟላት በሁሉም ዓይነት የዘርፉ ሃብቶቻችን ላይ በስፋት እየተሠራ ይገኛል።

    ዛሬ ፈቃድ የወሰዱ ኩባንያዎች የምርትም ሆነ የምርመራ ሥራቸውን ሲያከናውኑ በፌደራልና በክልል የማዕድን አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎችን መሠረት አድርጎ በጥንቃቄ በትጋትና ቅልጥፍና በተሞላበት ሁኔታ በማዕድን ኢንዱስትሪው ዘርፍ ተቀባይነት ባለው የአሠራር ዘዴ ለማከናወን በስምምነቱ ውስጥ የተካተተ ሲሆን፥ ተመጣጣኝ ዕውቀት፣ ችሎታና ልምድ ላላቸው ኢትዮጵያዊያን ባለሙያዎች ቅድሚያ የሥራ ዕድል ለመስጠትና ለሥራው አስፈላጊ የሆነውን ሥልጠና የመስጠት ግዴታ አለባቸው።

    የአካካቢ ጥበቃን (environmental protection) በተመለከተ የሠራተኞቹን፣ የአካባቢውን ማኅበረሰብ ጤንነትና ደህንነት በማይጎዳና ብክለት በማያስከትል መልኩ የምርት ሥራውን ለማከናወን ውል የተፈፀመ ሲሆን፥ ሥራውን ሲያቋርጥ በተፈጥሮ አካባቢ ላይ፣ በሰው ሕይወትና ንብረት እንዲሁም ዕፅዋት ላይ ጉዳት ሊያስከትሉ የሚችሉ ማናቸውም ቅሪቶችና ግንባታዎችን ያስወግዳል።

    የማዕድንና ነዳጅ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት የፕሮጀክቶችን ውልና አፈጻጸም በየጊዜው እየገመገመ በገቡት ውል መሰረት ሥራቸውን በአግባቡ የሚያከናውኑትን የመደገፍና የማበረታታት፣ በውላቸው መሠረት የማይሠሩትን ደግሞ ፍቃድ የመሰረዝና ሌሎች ሕጋዊ እርምጃዎችን እየወሰደ ይገኛል።

    ከሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ዜና ሳንወጣ፥ የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ የነበሩት ኢ/ር ታከለ ኡማ ነሐሴ 12 ቀን 2012 ዓ.ም. የማዕድንና ነዳጅ ሚኒስቴር ሚኒስትር ሆነው ተሹመዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በዕለቱ አስር ሹመቶችን በሰጡበት ጊዜ፥ የሚኒስቴሩ ሚኒስትር የነበሩት ዶ/ር ሳሙኤል ሁርካቶ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ሁነው ተሹመዋል። በዕለቱ የተሰጡት አስር ሹመቶች የሚከተሉት ናቸው።

    1. ዶ/ር ቀንዓ ያደታ – የመከላከያ ሚኒስትር
    2. ዶ/ር ጌድዮን ጢሞቴዎስ – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ
    3. ዶ/ር ሳሙኤል ሁርካቶ – የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር
    4. ኢንጂነር ታከለ ኡማ – የማዕድንና ነዳጅ ሚኒስትር
    5. አቶ ተስፋዬ ዳባ – ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ
    6. አቶ ዮሐንስ ቧያለው – የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ስትራቴጂክ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር
    7. አቶ ንጉሡ ጥላሁን – የሥራ ዕድል ፈጠራ ኮሚሽን ኮሚሽነር
    8. አቶ እንደአወቅ አብቴ – የብረታ ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ዳይሬክተር
    9. አቶ ፍቃዱ ጸጋ – ምክትል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ
    10. ፕ/ር ሂሩት ወልደማርያም – በሚኒስትር ማዕረግ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ዘርፍ አማካሪ በመሆን መሾማቸውን የጠቅላይ ሚኒስቴር ፅሕፈት ቤት አስታውቋል።

    የማዕድንና ነዳጅ ሚኒስትር

    Anonymous
    Inactive

    የቡራዩ የልዩ ተሰጥኦ እና ተውህቦ ማበልጸጊያ ኢንስቲትዩት ፕሮጀክት ግንባታ ደረጃ 84 በመቶ መድረሱ ተገለጸ

    አዲስ አበባ – በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እየተገነባ ያለውን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ የልዩ ተሰጥኦ እና ተውህቦ ማበልጸጊያ ኢንስቲትዩት /Innovation and Technology Talent Development Institute/ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ዘርፍ የፌደራልና የክልል ቢሮ አመራሮች ነሐሴ 8 ቀን 2012 ዓ.ም. ጎብኝተውታል። ከጉብኝቱ በተጨማሪም አመራሮቹ የአረንጓዴ አሻራቸውን በማዕከሉ ቅጥር ግቢም አኑረዋል።

    እንደ የኢኖቬሽን ልማትና ምርምር ዘርፍ ሚኒስቴር ዲኤታ ክቡር አቶ ሲሳይ ቶላ ፕሮጀክቱ ባለፉ ዓመታት በነበሩ ሀገራዊ ምክንያቶች መዘግየት አጋጥሞት ነበር። በአሁኑ ወቅት በተሻለ የአፈጻጸም ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ጠቁመው፥ በተጠናከረ አመራርና ድጋፍ በማጠናቀቅ በ2013 ዓ.ም. ሁለተኛ ሩብ ዓመት መጀመሪያ ወራት ሥራ ለማስጀመር እየተሠራ ነው ብለዋል።

    ማዕከሉ ሥራ ሲጀምር ለአካባቢው ማኀበረሰብ የሥራ ዕድል ከመፍጠሩ ባሻገር በሀገራችን የሚገኙ ባለተሰጥኦዎችን አሰባስቦ ተሰጥኦዋቸውን በማጎልበት ወደ ተጨባጭ ውጤት የሚቀይሩበት ስለሆነ፥ መላ ኢትዮጵያውያን እንዲደግፉትና እንዲሳተፉበት ጥሪ አቅርበዋል። ያለፉ ዓመታት በነበሩ ሀገራዊ ለውጥ ሂደቶች የተነሳ ያጋጠሙ መዘግየቶችን በቀሪ ወራት አካክሶ ሥራ ለማስጀመር የፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅም ተመድቦለታል።

    ክቡር አቶ ሲሳይ አክለውም ለዓመታት ያጋጠመ የመዘግየት ችግር ተካክሶ በሦስት ወራት ውስጥ አመርቂ የግንባታ ደረጃ ላይ ማድረስ ተችሏል። በቀጣይም በተሻለ ጥራትና ፍጥነት ተጠናቆ ሥራ እንዲጀምር ቅድመ ዝግጅቶች እየተደረጉና መሟላት የሚገባቸው ግብዓቶችን ከግንባታው ጎን ለጎን እየተሟሉ ይገኛል። ለስልጠናና ትምህርት እንዲሁም ተሰጥኦ ማፍለቅና ትግበራ የሚውሉ የቁሳቁስ እገዛና ድጋፍ ከልዩ ልዩ አካላት መገኘት ጀምሯል ያሉት ክቡር አቶ ሲሳይ፥ በቀጣይ የግሉ ዘርፍ፣ ሀገር-አቀፍና ዓለም-አቀፍ እርዳታ ለጋሽ ድርጅቶች፣ ልዩ ልዩ ተቋማት እና የመንግሥት አካላትን ትብብር እንዲያደርጉ እንጠይቃለን ብለዋል።

    የቡራዩ የልዩ ተሰጥኦ እና ተውህቦ ማበልጸጊያ ኢንስቲትዩት ሥራ ሲጀምር በየደረጃው ካሉ አመራሮች፣ መንግሥታዊ ካልሆኑ ተቋማትና ባለ ድርሻ አካላት ዘርፈ ብዙ ድጋፍ እንደሚጠበቅ አውስተው፥ ተቋሙ የታለመለትን ግብ እንዲያሳካና ዘላቂነት እንዲኖረው የአሠራር መመሪያዎችን፣ የትብብር ማዕቀፎችን፣ የሥርዓተ ትምህርት ዝግጅትን፣ የተውህቦና የክህሎት መለያ መስፈርቶችን የሚመለከቱ ጉዳዮችን ቀድሞ የማዘጋጀት ሥራ ከወዲሁ እየተሠራ ነው ብለዋል።

    በመጨረሻም ለዚህ ሀገራዊ ማዕከል መገንቢያ ቦታ በመስጠት፣ ባሳለፍናቸው ሁለት ዓመታት በነበሩ ሀገራዊ ክስተቶች ወቅት የተጀመሩ ግንባታዎችና ቁሳቁሶች ላይ ጉዳት እንዳይደርስ ጥበቃና እንክብካቤ ላደረጉ የቡራዩ ከተማ አስተዳደርና አካባቢዋ ነዋሪዎች ምስጋና አቅርበዋል። ባለተሰጥኦዎችም ወደፊት ወደተቋሙ መጥተው በሚኖራቸው ቆይታ አስፈላጊውን እገዛና እንክብካቤ ማግኘት የሚያስችላቸውን ቅድመ ዝግጅት ሁሉ ትብብራቸው እንዳይቋረጥ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

    ተቋሙን ሥራ ማስጀመር የሚያስችሉትን የግንባታ ሥራዎችን ቅድሚያ ሰጥቶ መሥራት እንዲቻል በተሰጠ አመራር እየተሠራ ነው ያሉት ደግሞ የግንባታ ሥራ ተቋራጩ ሥራ አስኪያጅ ኢ/ር መስፍን ባልቻ ናቸው። እንደ ኢ/ር መስፍን የቤተ መጻሕፍት፣ ቤተ ሙከራ፣ ወርክሾፖች፣ የመማሪያ ክፍል እና የማደሪያ ሕንጻዎችን በልዩ ትኩረት ተገንብተው ከ78% እስከ 90% የአፈጻጸም ደረጃዎች ማድረስ ተችሏል። በአሁኑ ወቅት ግንባታው ያለበት አማካይ የአፈጻጸም ደረጃ ከ84% በላይ ነው። ቀሪ የሲቪል ሥራዎችን በማጠናቀቅ የቁሳቁስ ገጠማና ሌሎች አስፈላጊ ግብዓቶችን በማቅረብ ለማጠናቀቅ እየተሠራ በመሆኑ በቀጣይ ሦስትና አራት ወራት ጊዜ ማጠናቀቅ ይቻላል ብለዋል።

    የቡራዩ የልዩ ተሰጥኦ እና ተውህቦ ማበልጸጊያ ኢንስቲትዩት ግንባታ ከሦስት ዓመት በፊት በኦሮሚያ ክልል በቡራዩ ከተማ አስተዳደር በተሰጠ አምስት ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ በተያዘ የመንግሥት በጀት የተጀመረ ነው። ከመላው ኢትዮጵያ ከ8ኛ እስከ 12ኛ ክፍል እስከ 1000 ባለተሰጥኦዎችን መልምሎና ተቀብሎ ከመደበኛ ትምህርታቸው ጎን ለግን ተሰጥኦዋቸውን በማልማት፣ በማጎልበትና ወደ ተጨባጭ አምራችነት በመቀየር ለሀገራዊ ብልጽግና መሠረት መጣል የሚችል ተቋም መሆኑን መግለጻችን ይታወቃል።

    ምንጭ፦ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር

    የቡራዩ የልዩ ተሰጥኦ እና ተውህቦ ማበልጸጊያ ኢንስቲትዩት

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እና ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በአጠቃላይ ከ10,900 በላይ ተማሪዎችን አስመረቁ

    አዲስ አበባ/ ጎንደር (ሰሞነኛ) – አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎችና መርሃግብሮች ያስተማራቸውን ተማሪዎች ሐምሌ 18፣ 2012 ቀን አስመርቋል።

    ዩኒቨርሲቲው የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ፕሬዝዳንት ክብርት ሳህለወርቅ ዘውዴ በክብር እንግድነት በተገኙበት 5,642 ተማሪዎችን በቨርቹዋል አስመርቋል። ፕሬዝዳንቷ በዓለም አቀፍ ደረጃ በተከሰተው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ (COVID-19) ምክንያት ምርቃቱን በተንጣለለ አዳራሽ ማከናወን ባይቻልም ተመራቂ ተማሪዎች ትምህርታችሁን በማጠናቀቃችሁ እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።

    ተመራቂዎች ቀጣዩ የሕይወት ምዕራፍ ትልቅ ኃላፊነት ያለበት፣ ለሕዝብ እና ለሀገር ለውጥ ለማምጣት የሚተጉበት መሆኑን አመላክተው ራሳቸውን ከኮሮና ቫይረስ እንዲከላከሉና ጥንቃቄ እንዳያጓድሉ እንዲሁም ችግር ፈቺ ተግባራት ላይ እንዲሳተፉ አሳስበዋል።

    የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሐና ዩኒቨርሲቲው ካስመረቃቸው ተማሪዎች መካከል 2,270 የሚሆኑት በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት የገፅ-ለገፅ ትምህርት (in-class and face-to-face education) ከመቋረጡ በፊት ጥናታቸውን ያቀረቡ ሲሆን 3,372 ተማሪዎች ደግሞ በትምህርት ዓመቱ መጨረሻ ማቅረባቸውን ገልፀዋል።

    ተመራቂዎቹ ኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ መከሰትና ወደሀገራችን መግባት በፊት በገፅ-ለገፅ ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ የመጀመሪያ ዲግሪ ተማሪዎች፣ እና በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት የገፅ-ለገፅ ትምህርት ከተቋረጠ በኃላ በኦንላይን (online) ያስተማራቸው የሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪ ተማሪዎች ናቸው።

    የምረቃ ሥነ ሥርዓቱ በዩኒቨርሲቲው 6 ኪሎ ግቢ ራስ መኮንን አዳራሽ የተከናወነ ሲሆን፥ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በቀጥታ በማስተላለፍ ተመራቂ ተማሪዎች ከቤታቸው ሆነው በሥነ ሥርዓቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ መመቻቸቱ ተገልጿል።

    ቀደም ብሎ ከሁለት ሳምንታት በፊት (ሐምሌ 4 ቀን 2012 ዓ.ም.) ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በዩኒቨርሲቲው የሳይንስ አምባ መሰብሰቢያ አዳራሽ 5,315 ተማሪዎችን አስመርቋል። ከተመራቂዎቹ መካከል ቀደም ብለው ትምህርታቸውን አጠናቅቀው ለመመረቅ እየተጠባበቁ የነበሩ እንዲሁም ኤክስተርንሽፕ እና ፕሮጀክት ላይ የነበሩ የመጀመሪያ ዲግሪ ተማሪዎችና በኦንላይን ትምህርታቸውን የተከታተሉ የሁለተኛ እና ሦስተኛ ዲግሪ ተማሪዎች ይገኙበታል። ተመራቂዎቹ በየቤታቸው ሆነው የምረቃ ሥነ ሥርዓቱን በአማራ ቴሌቪዥን እንዲሳተፉ መደረጉን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አስራት አፀደወይን ገልፀዋል።

    የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ተመራቂ ተማሪዎችን እንኳን ደስ አላችሁ እያለ የአገራችንና ሕዝባችንን ኑሮ የሚያሻሽሉ፣ ለወገን ፍቅር የሚሰጡ፣ ከድህነት የሚያላቅቁና ወደ ብልፅግና የሚያሻግሩ ተግባራት ላይ በመሳተፍ ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ መልዕክቱን አስተላልፏል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እና ጎንደር ዩኒቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive

    ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ በዘጠኝ የትምህርት ዘርፎች የድኅረ ምረቃ መረሃ ግብር ይጀምራል
    መቀሌ ዩኒቨርሲቲ ለ900 ተማሪዎች የትምህርት መከታተያ ሬድዮ እና ተንቀሳቃሽ ስልክ ድጋፍ አደረገ

    ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ በመጪው የትምህርት ዘመን በዘጠኝ የትምህርት ዘርፎች የድኅረ ምረቃ መረሃ ግብር ለመጀመር ዝግጅት ማድረጉን አስታወቀ።

    የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ፀጋዬ ደዮ በተቋሙ በተካሄደው የሥርዓተ ትምህርት ግምገማ ላይ እንዳሉት፥ በ2013 የትምህርት ዘመን በአማርኛ፣ ኦሮምኛ፣ እንግሊዘኛ ቋንቋና ሥነ-ልሳን በተጨማሪ በሶሻል አንትሮፖሎጂ (social anthropology) ዘርፍ የድኅረ ምረቃ መረሃ ግብር ይጀምራል።

    እንዲሁም በጤና ሣይንስ ኮሌጅ የትምህርት ዘርፍ በሥነ ተዋልዶ፣ ሥነ ምግብ፣ ማኅበረሰብ ጤና፣ እናቶችና ሕፃናት ጤና የትምህርት ዘርፎች እንደሚከፈቱም አስታውቀዋል።

    ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ በሚጀምራቸው ዘጠኝ የድኅረ ምረቃ መረሃ ግብር በእያንዳንዱ የትምህርት ዘርፍ እስከ 15 የሚደርሱ ተማሪዎችን ተቀብሎ እንደሚያስተምርና ይህም ዩኒቨርሲቲው አዲስ ከመሆኑ አንፃር ትልቅ ለውጥ መሆኑን ዶ/ር ፀጋዬ ገልጸዋል።

    የትምህርቱ ዓላማ ዩኒቨርሲቲው አቅምና ዕውቀትን ከማጐልበትና ከማሻገር በተጓዳኝ በጥናትና ምርምር የተደገፉ ችግር ፈቺ ሥራዎችን ለኅብረተሰቡ ለማመቻቸት ነው ብለዋል። በተለይ በትምህርት ጥራት ላይ እየተስተዋሉ ያሉ ችግሮች እንዲወገዱ የትምህርት መርሃ ግብሩ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራም አመልክተዋል።

    የዩኒቨርሲቲው የውጭ ሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ዶ/ር የሺመቤት ቦጋለ በበኩላቸው፥ ዩኒቨርሲቲው ለሚጀምረው የድኅረ ምረቃ መረሃ ግብር በቂ የሰው ኃይልና የሥርዓተ ትምህርት ዝግጅት ማድረጉን አስታውቀዋል። መረሃ ግብሩ በትምህርት ተግባቦት ቴክኖሎጂ በቤተ ሙከራዎችና በኢንተርኔት በመታገዝ የ24 ሰዓት አገልግሎት የሚሰጥበት ቤተ መጽሕፍትን አደራጅተናል ብለዋል።

    የሚጀምረው መረሃ ግብር የተቋሙ መምህራንና ተማሪዎች አቅም ከማሳደግ ባለፈ ለሀገሪቱ ቋንቋና ባህል ትኩረት የሰጠ በመሆኑ ለተግባራዊነቱ የበኩላቸውን እንደሚወጡ የተናገሩት ደግሞ የዩኒቨርስቲው የኦሮምኛ ቋንቋ ዲፓርትመንት ኃላፊ ወ/ት ሁርሜ ደገፋ ናቸው።

    በዩኒቨርሲቲው ቅጥር ግቢ ለአንድ ቀን በተካሄደው የሥርዓተ ትምህርት ግምገማው ከ100 በላይ መምህራንና ተጋባዥ እንግዶች ተካፍለዋል።

    ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ በ2009 ዓ.ም. ከተቋቋመ ጀምሮ በ33 የትምህርት ዘርፎች ከ4 ሺህ 500 በላይ ተማሪዎችን ሲያስተምር መቆየቱም ተመልክቷል።

    ከከፍተኛ ትምህርት ዜና ሳንወጣ፥ መቀሌ ዩኒቨርሲቲ በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት ትምህርታቸውን በሬዲዮ በመከታተል ላይ ለሚገኙ 900 ተማሪዎች የሬድዮ እና ተንቀሳቃሽ የእጅ ስልክ ድጋፍ አደረገ። ድጋፉ ከ700ሺህ ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገዙ 500 ሬዲዮኖችና 400 ተንቀሳቃሽ የእጅ ስልኮች ናቸው።

    የዩኒቨርስቲው ፕሬዝዳንት ፕ/ር ክንደያ ገብረሕይወት እንደገለጹት፥ ድጋፉ በመቀበያ ችግር ምክንያት የሬድዮ ትምህርት ፕሮግራም መከታተል ላልቻሉ ተማሪዎች ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው። ድጋፉ የተደረገላቸው መቀሌን ጨምሮ በአምስት የክልሉ ወረዳዎች የሚገኙ ችግረኛ ተማሪዎች እንደሆኑ አመልክተው፥ በየቤታቸው ትምህርታቸውን በሬዲዮ ለመከታተል እንደሚያግዛቸው ተናግረዋል።

    የትግራይ ክልላዊ መንግሥት የአንደኛና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ትምህርታቸውን እንዳይቋረጥ እያደረገ ያለውን ጥረት ዩኒቨርስቲው የበኩሉን ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል – ፕ/ር ክንደያ። ተማሪዎች በሬድዮ የሚተላለፍ ትምህርት በመከታተል ጥራትን ለማረጋገጥ እንደሚረዳም ፕ/ር ክንደያ አስረድተዋል።

    የክልሉ ትምህርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ባህታ ወልደሚካኤል በበኩላቸው፥ የተደረገው ድጋፍ በኢኮኖሚ ችግር ምክንያት ትምህርታቸውን መከታተል ላልቻሉ ተማሪዎች የሚውል መሆኑን ተናግረዋል። ከዓይደር ክፍለ ከተማ ነዋሪ የሆነው የዘጠነኛ ክፍል ተማሪ አይነስውሩ አለም ተስፋዬ በሰጠው አስተያየት የተደረገው ድጋፍ ከትምህርት መርሃ ግብሩ በተጨማሪ ወቅታዊ የዓለማችን ሁኔታ ለመከታተል የሚያስችለን ነው ብሏል። በተለይም ለአካል ጉዳተኞች የተለየ ድጋፍ ማድረግ ሰብአዊና ዜግነታዊ ኃላፊነት መሆኑን ተናግሯል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 58 total)