Search Results for 'ጉራጌ ዞን'

Home Forums Search Search Results for 'ጉራጌ ዞን'

Viewing 12 results - 1 through 12 (of 12 total)
  • Author
    Search Results
  • #54494
    Semonegna
    Keymaster

    “ጀፎረ”/”ጀፎሮ” ― የጉራጌዎች ውብ ስፍራ

    ጀፎረ (በአንዳንድ አካባቢዎች “ጀፎሮ” ተብሎ ይጠራል) ውብ፣ ጽዱና ማራኪ በአባቶች ባህላዊ ዕውቀትና ጥበብ የተከሸነ፣ ሰፊ አረንጓዴ ጎዳና፣ በግራና በቀኙ በልምላሜያቸው ተውበው በሚታዩ እፀዋቶች የታጠረ፣ ማራኪ በሆኑ በባህላዊ እደ ጥበብ በተሽቆጠቆጡ ቤቶች የታጀበ፣ በየመሀሉ ላይ እንደ ሊባኖስ ዝግባ የገዘፉ ዛፎች ያሉት፣ ወደ መንደሩ ለሚገባ ሁሉ ለአእምሮ እፎይታን፣ ለነፍስ ደግሞ እርካታን የሚያጎናጽፍ የጉራጌዎች ልዩ ስፍራ ነው።

    ጀፎረ በጉራጌ ማኅበረሰብ ዘንድ ልዩ ታሪክ እንዳለው ይነገርለታል። ጀፎረ አገልግሎቱ ሁለገብ ነው። ለመንደሮች ውበት መላበስ ጉልህ አስተዋጽኦ ያበረክታል።

    ጀፎረ ማለት የመንደር ወይም የጎጥ ነዋሪዎች የጋራ መጠቀሚያ፣ መተላለፊያ፣ መግቢያ እና መውጫ፣ ሰፊ መሰብሰቢያ፣ ጠዋት ከብቶች ከመሰማራታቸው በፊት ማታ ደግሞ ወደ ቤታቸው ከመግባታቸው በፊት ለማቆሚያነት የሚያገለግል የጋራ ስፍራ ማለት ነው።

    ጀፎረ የጎኑ ስፋት 100-150 ሜትር፣ ርዝመቱ በመሃል የሚያልፍ ገደል፣ ደን፣ ወንዝ እስከሌለ ድረስ ሳይቋርጥ ይቀጥላል። ከጥንት ጊዜ ጀምሮ የሚለካው በዘፈቀደ ሳይሆን በባህሉ በተመረጡ አባቶች ወይም “የዥር ዳነ” የመሬት ልኬት ዳኞች አማካኝነት መሆኑን የዘርፉ አጥኚዎች ይናገራሉ።

    የጉራጌ ማኅበረሰብ ለጀፎረ ትልቅ ትኩረት ከመስጠቱ የተነሳ ጀፎረ ላይ የተተከለ የዛፍ ቅርንጫፍ፣ አፈር ወይም ሌሎችንም ነገሮች ይዞ ወደ ግል ቤት ማስገባት ክልክል ነው።

    ጀፎረ በርካታ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳዎች አሉት። የተወሰኑትን ለመጥቀስ ያክል፦ ሰው ሲሞት የለቅሶ ሥነ ሥርዓት ይከወንበታል፤ ሰርግ ሲኖር የሙሽሪትና የሙሽራው አጃቢዎችና ዘመዶች በባህላዊ ዘፈን በማጀብ ይሞጋገሱበታል፤ ባህላዊ የእርቅ ሥነ ሥርዓት ይከናወንበታል፤ ሕፃናት ይጫወቱበታል፤ በቅሎና ፈረስ ይገራበታል፤ ወጣቶች የገና ጨዋታ ይጫወቱበታል፤ ወንዶችና ሴቶች የደቦ ሥራ ለመሥራት ቁጭ ብለው ይመካከሩበታል፤ በመስቀል በዓል አዛውንት ወይም የቀዬው ሽማግሌዎች፣ ጎልማሶች እና ወጣቶች በደመራው ሥነ ሥርዓት ላይ ተሰብስበው ይመራረቁበታል፤ አባቶች በርጩማቸውን ይዘው በመውጣት ንፁህ አየር ይቀበሉበታል።

    ይህ “የመንደር አደባባይ” ለከብቶች መዋያነትም ያገለግላል። በተለይ በክረምት ወራት ከሰኔ እስከ መስከረም የግርጌ ሳር ከከብቶች መብልነት አልፎ ለቤት ክዳን መክደኛነት እስኪደርስ ድረስ እንደማስተንፈሻ ግልጋሎት መስጠት ሌላኛው የጀፎረ ተጨማሪ ጠቀሜታው ነው።

    በጉራጌ ብሔረሰብ እያንዳንዱ የመንደሩ ነዋሪ ጀፎሮን የመጠበቅና የመንከባከብ ኃላፊነት አለበት። የመንደሩ ማኅበረሰብ በዘመቻ መልክ በመውጣት በባለቤትነት ስሜት ጀፎሮን ያፀዳል።

    የጀፎረ መኖር ለእንሰት ተክል እድገት፣ ለቡናና ለሌሎች የጓሮ አትክልት ጉልህ አስተዋጽኦ አለው። በተለይም ከብቶች ጀፎረ ላይ ስለሚሰማሩ እነዚህ የጓሮ አትክልቶች በከብቶች እንዳይበሉና እንዳይረገጡ ጉልህ አገልግሎት ይሰጣል።።

    በመሆኑም ጀፎረ/ጀፎሮ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎች እንዳሉት በመረዳት በተለይ ወጣቱ አባቶች ጠብቀው ያቆዩልንን ሀብታችንን በመንከባከብ የሚጠበቅብንን ኃላፊነት በመወጣት እንዲህ ዓይነቱን ውብ ባህላችንን እንጠብቅ በማለት መልዕክታችንን በማስተላለፍ በጉራጌ ዞን የቸሃ ወረዳ ጀፎርን በዚህ መልኩ የክልሉ ኮሚዩኒኬሽን ቃኝቶታል።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን የመንግሥት ግንኙነት ጉዳዮች መምሪያ

    ጀፎረ

    Semonegna
    Keymaster

    በጉራጌ ዞን የመስቀል በዓል በተለያዩ ዝግጅቶች መከበር ተጀመረ
    (የመስቀል በዓል በጉራጌ ማኅበረሰብ)

    በሀገራችን በድምቀት ከሚከበሩ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ክብረ በዓላት መካከል የመስቀል በዓል አንዱ ነው። የመስቀል በዓል በጉራጌ ማኅበረሰብ ዘንድ ልዩ ቦታ የሚሰጠው እንደመሆኑ፥ በየዓመቱ በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ይከበራል። የዘንድሮውን የዋዜማ ዝግጅት በዞኑ ቸሃ ወረዳ የጠናቃ ቀበሌ ለኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በማያጋልጥ መልኩ የፌዴራል እና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በሀገር ሽማግሌዎች ምርቃት ከመስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ በድምቀት መከበር ተጀምሯል።

    በመክፈቻ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሐመድ ጀማል ታዳሚዎችን እንኳን አደረሳችሁ በማለት “የመስቀል በዓል የኛነታችን መገለጫ ነው፤ የመስቀል በዓል ትውፊታዊም መንፈሳዊም ነው። በመስቀል በዓል የእርስ በእርስ የመተሳሰብ፣ የአብሮነት፣ የፍቅር፣ የሰላም እንዲሆን የመልካም ምኞት ማብሰሪያ አበባ የሚሰጣጡበት ጊዜ ነው። እንዲሁም በሥራም ሆነ በሌላ አጋጣሚ ተራርቆ የቆየ ሰው የሚገናኝበት፣ ዘመድ ከዘመዱ የሚጠያየቅበት፣ የሚረዳዳበት እንዲሁም አዲስ ጎጆ የሚቀለስበት ጊዜ መሆኑ ማኅበረሰባችን ልዩ ቦታ ይሰጠዋል። አያይዘውም በበዓሉ ባህላዊ እሴቶቻችንን በደንብ አልምተን እንደ አንድ የቱሪዝም ገቢ ምንጭ በማድረግ ለሀገራዊ ብልጽግናችን መሠረት የምንጥልበት ነው ብለዋል።

    የመስቀል በዓል ከሀይማኖታዊ ክዋኔ ባሻገር ባህላዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያለው ሲሆን በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት የሚከበር ቢሆንም መስቀል በጉራጌ በተለየ የአከባበር ሁኔታ ይከበራል ብለዋል – አቶ መሐመድ።

    እንደ አቶ መሐመድ ገለፃ እንደ መስቀል ያሉ ቱባ ባህሎቻችን ታሪካቸው ሳይሸራረፍ ለትውልድ በማስተላለፍ ዘረኝነት፣ ጥላቻና ቂም በቀል በማስወገድ የሀገራችን ብልፅግና ለማረጋገጥ  ሁሉም ዜጋ የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ብለዋል።

    መርሀ-ግብሩን በጋራ ያዘጋጁት የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ፤ የጉራጌ ዞን አስተዳደር እና የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር በመተባበር ሲሆን፥ የዚህ ክብረ በዓል አከዋወን በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና ባህል ድርጅት /UNESCO/ ከማይዳሰሱ የሰው ልጅ ወካይ ባህላዊ እሴቶች (“intangible heritages of Ethiopia”) ተርታ መመዝገቡን በማስመልከት ሲሆን፥ በአከባበሩ ሥርዓት ውስጥ ያሉት ትውፊቶች በትውልድ ቅብብሎሹ ውስጥ ተጠብቀው ያለ ምንም ተፅዕኖ ክዋኔዎቹ እየቀጠሉ እንዲሄዱ የማስተማር ዓላማ ያለው እንደሆነ ተነግሯል።

    በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የባህል እሴቶች ልማት ዳይሬክተር ወ/ሮ እስከዳር ግሩም በበኩላቸው፥ ሀገራችን ኢትዮጵያ የበርካታ ባህላዊና ታሪካዊ ሀብት ባለቤት ብትሆንም በተገቢው ማልማትና ማስተዋወቅ ባለመቻላችን ከዘርፉ የምናገኘው ገቢ እንዳላደገ ገልጸዋል።

    አንድነታችን አጠናክረን ሀብቶቻችን ማልማት፣ መጠበቅና መንከባከብ አለብን። ይህ ደግሞ የቱሪዝም ዘርፍ እንዲነቃቃ ያደርገዋል። በተጨማሪም ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር ይቻላል ብለዋል።

    የቸሀ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ፈለቀ የመስቀል በዓል በጉራጌ ሁሉም በድምቀት ከማክበር ባለፈ የጉራጌ እሴት የሚገለፅበት በመሆኑ የረጅም ጊዜ ቅድመ ዝግጅት እንደሚደረግበት በማስታወስ፤ በዓሉንም በድምቀት ለማክበር ሁሉም የቤተሰብ አባል የድርሻውን ኃላፊነት እየተወጣ እንደሚከበር ገልጸዋል።

    ለበዓሉ ማብሰሪያ የጉራጌ ዞን የባህል ቡድንም ያሰናዳቸውን ሙዚቃዊ ክዋኔዎች እንደነ “ጊቻዌ፣ ጊቻዌ”፣ “አዳብና” የመሳሰሉት ተውኔታዊ ክዋኔዎች በሴቶችና ወንዶች የታየበት፣ የሥራ ባህልን፣ ሠርቶ ማደግን የሚያወድሱ፣ የሚያስተምሩ ማሳያዎች፣ ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅኑ በአንድነት በአብሮነት ባህላዊ እሴቶች የሚጎለብቱበት ተውኔታዊ ትዕይንቶች የተንፀባረቁበት ነበር።

    የመስቀል በዓል በጉራጌ ማኅበረሰብ

    Anonymous
    Inactive

    ወልቂጤ ከተማ ውስጥ ከ50 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተገነባው ባሮክ ሆቴል ተመርቆ ሥራ ጀመረ
    የዞኑ ኢንቨስትመንት ለማሳደግ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን የጉራጌ ዞን አስተዳዳር አስታውቋል።

    ወልቂጤ (ሰሞነኛ) – በወልቂጤ ከተማ ከ50 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተደረገበት ባሮክ ሆቴል ተመርቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን የጉራጌ ዞን መንግሥት ኮሚኒኬሽን መምሪያ ዘግቧል። ባሮክ ሆቴል ባዘጋጀው የምረቃ ሥነ ሥርዓት ላይ የተለያዩ ተጋባዥ እንግዶች ተገኘተዋል።

    በሆቴሉ ምረቃዉ ላይ የተገኙት የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሀመድ ጀማል ለአንድ ከተማ እድገትና ለዉጥ በኢንቨስትመንት ዘርፍ የሚሰማሩ ባለሀብቶች ሚና የጎላ መሆኑን በማስገንዘብ እንደተናገሩት፥ የዞኑ ኢንቨስትመንት ለማሳደግ ከመቼዉም ጊዜ በተሻለ ሁኔታ አጽንኦት ተሰጥቶ እየተሠራ ነዉ።

    በተለይም ከዚህ ቀደም ይስተዋሉ የነበሩ የኢንቨስትመንት ልማት ሥራዎችን ለማሳደግ እንደ ክፍተት የሚስተዋሉትን የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ በተደረገዉ እንቅስቃሴ አሁን ላይ ባለሀብቶች በዞኑ ኢንቨስት እያደረጉ ይገኛል።

    ይህንንም አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚያስችሉ ሂደቶችም መኖራቸዉንም አቶ መሀመድ ጠቁመዉ፥ በቀጣይ በዘላቂነት የዞኑ ኢንቨስትመንት ለማሳደግ ከባለሀብቶች ጋር እየተሠራ ያለዉን ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም በመግለጽ፤ ባለሀብቶች በዞኑ ባሉ የልማት አማራጮች እንዲሰማሩ አስፈላጊዉን ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።

    የወልቂጤ ከተማ ከንቲባ አቶ እንዳለ ገብረመስቀል፥ በበኩላቸዉ ከዚህ ቀደም በከተማዉ ኢንቨስት ለማድረግ ይስተዋሉ የነበሩ ችግሮችን ለመቅረፍ ባለሀብቶች በማበረታታት ኢንቨስት እንዲያደርጉ እየተሠራ ነዉ ብለዋል።

    ከተማዉን ለማልማት የሚመጡ ባለሀብቶች አስፈላጊዉን ድጋፍ በማድረግ ከዞኑ መንግሥት ጋር በመሆን እየተሠራ መሆኑም በመጠቆም፤ በአሁኑ ሰዓት በሆቴል ዘርፍ የተሰማራዉን ባርክ ሆቴል አገልግሎት መስጠት በመጀመሩ ለሌሎች ባለሀብቶች የሚያበረታታ መሆኑም አቶ እንዳለ ጠቅሰዋል።

    ሌሎች በተለያዩ ዘርፎች ኢንቨስትመንት ለሚሰማሩ ባለሀብቶች የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር በተገቢው መንገድ ተቀብሎ እንደሚያስተናግዳቸው በመግለጽ፥ “ኑ! ተደጋግፈን አብረን እንልማ” የሚል ጥሪ አሰተላልፈዋል።

    የባሮክ ሆቴል ባለቤት አቶ አሰፋ በቀለ በበኩላቸው ሆቴሉ ተጠናቆ አገልግሎት መሰጠት በመጀመሩ ደሰተኛ መሆናቸዉም አስረድተዋል። ሆቴሉ ሙሉ ለሙሉ ሲጠናቀቅ 50 ሚሊየን ብር እንደሚፈጅም ተናግረዉ በሆቴሉም ከ50 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጠርም አስረድተዋል ።

    ባሮክ ሆቴል 39 አልጋዎችና አንድ የስብሰባ አዳራሽ ያካተተ መሆኑን የገለጹት የሆቴሉ ባለቤት አቶ አሰፋ፥ በአካባቢያቸዉ በማልማታቸዉ ደስተኛ መሆናቸዉ እንዲሁም ለተደረገላቸዉ ድጋፍ የከተማ አስተዳደሩና የዞኑ መንግሥት አመስግነዋል።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን መንግሥት ኮሚኒኬሽን መምሪያ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ባሮክ ሆቴል Baroc Hotel Wolkite

    Anonymous
    Inactive

    በ2013 ዓ.ም የጉራጊኛ የፊደል ገበታ በተመረጡ ትምህርት ቤቶች ለሚያስተምሩ መምህራን በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ስልጠና ተሰጠ

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ከጉራጌ ዞን አስተዳደር በጋራ በመሆን የጉራጊኛ የፊደል ገበታ የቅድመ መደበኛ ተማሪዎች ለማስተማር በዞኑ ከተለያዩ ወረዳዎች ለተዉጣጡ መምህራን ስልጠና የሰጠ ሲሆን፤ በቀጣይ የጉራጊኛ ቋንቋ የትምህርት፣ የሚዲያና የሥራ ቋንቋ ለማድረግ የፊደል ገበታዉ ለቅድመ መደበኛ ተማሪዎች መስጠት አጋዥ መሆኑ ተገልጿል።

    በስልጠናዉ ተገኝተዉ ንግግር ያደረጉት የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ፋሪስ ደሊል የሱፍ እንዳሉት፥ የሀገራችን ሕገ-መንግሥት የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች በቋንቋቸዉ የመናገር፣ የመፅሀፍ፣ ቋንቋቸዉን የማሳደግ መብት እንዳላቸዉ አስፍሯል። የቤተ-ጉራጌ ህጻናትም በአፍ መፍቻ ቋንቋቸዉ እንዲማሩ ለማድረግ ይሁንታ ያገኘዉን የጉራጊኛ የፊደል ገበታ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ ለማድረግ እየተሄደበት ያለዉን መንገድ አበረታች ተግባር እንደሆነም አስታዉቀዋል። የጉራጊኛ የፊደል ገበታ የትምህርቱን መስክ መሣሪያ በማድረግና ወደ መሬት ለማውረድ የሰልጣኝ መምህራን ሚና የጎላ እንደሆነም አስረድተዋል።

    ለህጻናት በአፍ መፍቻ ቋንቋ ትምህርት መስጠት አስፈላጊዉን የቤተሰብ ድጋፍ በቀላሉ ለማግኘት የሚያስችላቸዉን ዕድል ለማስፋትና ሳይንሱን ይበልጥ ለመረዳት፥ እንዲሁም አዳዲስ ነገሮችን ለመፍጠር የሚያስችላቸዉ ተመራጭ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴ እንደሆነም አስታዉቀዋል።

    በስልጠናዉ ተገኝተዉ ንግግር ያደረጉት የጉራጌ ዞን ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ መሠረት አመርጋ እንዳሉት፥ የጉራጊኛ ቋንቋ የትምህርት፣ የሚዲያ እና የሥራ ቋንቋ እንዲሆን ለማድረግ የምሁራን ሚና የጎላ ነዉ። ቋንቋ የአንድ ማኅበረሰብ የማንነት መገለጫ እንደመሆኑ መጠን ዜጎች የራሳቸዉ ቋንቋ እንዲማሩ ሕገ-መንግሥቱ ላይ ተደንግጓል ብለዋል።

    ህጻናት በአፍ መፍቻ ቋንቋቸዉ መማር እንዲችሉ ለማድረግና የጉራጊኛ ቋንቋ በማልማት የትምህርትና የሚዲያ ቋንቋ ለማድረግ የተሄደበት ርቀት ከቁጭት ባሻገር ወደ ተግባር አለመገባቱም አስታዉሰዉ፥ የተለያዩ ምሁራን መጽሐፍ በማዘጋጀት በጥናትና ምርምር ሁሉም የበኩሉን ቢያበረክትም ዉጤታማ እንዳልሆነም አንስተዋል።

    ቋንቋዉን ለማልማት የኮምፒዩተር ቀመር (ሶፍትዌር) በመቅረጽ፣ ጥናትና ምርምር በማድረግ እና የተለያዩ ዕቅዶችን በማቀድ የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲና ምሁራን እያደረጉት ያለዉን ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም አስረድተዋል።

    በስልጠናዉ የተሳተፉ አንዳንድ መምህራን በሰጡት አስተያየት፥ የጉራጊኛ ቋንቋ የትምህርትና የሚዲያ ቋንቋ እንዲሆን የበኩላቸዉን ሚና እንደሚወጡም አስረድተዋል።

    በስልጠናዉ ያገኙት እዉቀት በመጠቀም የጉራጊኛ የፊደል ገበታዉ የቅድመ መደበኛ ተማሪዎች ከማስተማር በተጨማሪ በሁሉም የትምህርት ደረጃ እንደ አንድ የትምህርት ዓይነት ቢሰጥ መልካም ነዉ ብለዋል።

    በመጨረሻም ከሁሉም ወረዳዎች ከሚገኙ ሁለት ሞዴል ትምህርት ቤቶች አራት አራት መምህራን ስልጠና ተሰጥቷል ሲል የዘገበዉ የጉራጌ ዞን መንግሥት ኮሚኒኬሽን መምሪያ ነዉ።

    የጉራጊኛ የፊደል ገበታ

    Anonymous
    Inactive

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ መርሀግብሮች ያስተማራቸውን ከ900 በላይ ተማሪዎችን አስመረቀ

    ወልቂጤ (ሰሞነኛ) – የሦስተኛ ትውልድ ዩኒቨርሲቲ የሆነው ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ መርሀግብሮች ያስተማራቸውን 929 ተማሪዎች ነሐሴ 30 ቀን 2012 ዓ.ም ለሰባተኛ ጊዜ ባካሄደው የምረቃ ሥነ ሥርዓት አስመርቋል።

    በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ በክብር እንግድነት ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሙሉ ነጋ እንዳሉት፥ እውቀትና ብቃት ያለው የሰለጠነ የሰው ኃይል ለአንድ ሀገር እድገትና ቀጣይነት የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ ነው። በዚህ ረገድ ጥራትና አግባብነት ያለው ትምህርት በተለይ ደግሞ ከፍተኛ ትምህርት ማስፋፋት ወሳኝ ነው ብለዋል።

    ዶ/ር ሙሉ አክለውም፥ መንግሥት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሀገራችንን ሕዝብ ህይወት ቀላልና ዘመናዊ በማድረግ ወደተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር ቁልፍ ሚና እንዳላቸው በማመን በየዓመቱ ከፍተኛውን የሀገሪቱን በጀት ለትምህርት መድቦ እየሠራ ይገኛል ብለዋል።

    ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የለውጥ ሃሳቦችን በማፍለቅና በመተግበር መልካም አርአያ የሚሆኑ ዜጎችን ማፍሪያ፣ የዲሞክራሲያዊ አስተሳሰቦችና ቴክኖሎጂዎች መፍለቂያ፣ የባህላዊ እሴቶቻችን መጎልበቻ፣ የሕዝቦች የመተሳሰብ፣ የመቻቻልና የአብሮነት ባህል የሚቀመርባቸው ማዕከላት እንዲሆኑ ማድረግ አማራጭ የሌለው መፍትሄ ነው ብለዋል – ዶ/ር ሙሉ።

    ሚኒስትር ዴኤታው ሰላም በምንም ነገር የማይተካ መሆኑን ገልጸው፥ ተመራቂዎች የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት እንዲደግፉና በህይወት ጎዳናቸው ከጽዩፍ አስተሳሰብና እና ድርጊት ተጠብቀው በተሰማሩበት መስክ የችግሮች መፍትሄ በመሆን ሀገራቸውን እንዲያገለግሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ዶ/ር ሙሉ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸው፤ ተመራቂዎች ሀገራችሁንና ሕዝባችሁን በሚጠቅሙ ሥራዎች ላይ በመሰማራት ታታሪ፣ የሀገራችሁን ሁለንተናዊ እድገት እና ብልጽግና የምታረጋግጡ ሰላም ወዳድ እንድትሆኑ አደራ እላለሁ ብለዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ፋሪስ ደሊል በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው በአዋጅ የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት በምርምር፣ በማኅበረሰብ-አቀፍ አገልግሎት (community-based service) እና መማር-ማስተማር መስክ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም ኮቪድ-19 ከመጣ በኋላ የዩኒቨርሲቲው ሠራተኞች የአንድ ወር ደመወዛቸውን በማዋጣት አቅመ ደካሞችን መርዳታቸውን ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው ከ3,000 ሊትር በላይ ሳኒታይዘር፣ 4,000 የፊት ጭንብል (face-mask)፣ 1800 ብሊች (bleach) የማምረት ሥራዎችን ሠርቶ በጉራጌ ዞን ለሚገኙና በሥራ ጸባያቸው ለቫይረሱ ተጋላጭ ለሆኑ ተቋማት ማበርከቱን ጠቁመዋል። ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የለይቶ ማቆያ ማዕከል (quarantine center) ሆኖ በማገልገል ላይም ይገኛል ብለዋል።

    በምርምር ረገድም ድርቅን በመቋቋም የሚታወቀውን ቆጮን ጨምሮ በተለያየ መልኩ ለምግብነት የሚውለውን እና የአከባቢው ማኅበረሰብ የኑሮ አለኝታ የሆነውን የእንሰት ተክል እንዳይጠፋ፣ እንዲሁም ዝርያው እንዲጠበቅና እንዲሻሻል የእንሰት ማዕከል በማደራጀት ዝርያዎችን የማሰባሰብ ሥራዎችን እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

    ዶ/ር ፋሪስ ባስተላለፉት መልዕክት ተመራቂ ተማሪዎች ሥራ ወዳድና ታታሪ፣ በሕግ የበላይነት ላይ የማትደራደሩ፣ የጥላቻን ዘር የማትዘሩ በጥላቻ ሳይሆን የተዘራውን ክፉ አረም በፍቅርና አብሮነት የምትነቅሉ በሥነ-ምግባር የታነጻችሁ ሀገር ተረካቢ ብቻ ሳትሆኑ አሻጋሪ ናችሁ ብለዋል።

    በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የዛሬው ምረቃ ሥነ ሥርዓት የተሳተፉት በክረምትና በማታ መርሀግብሮች በአምስት ኮሌጆች ስር በሚገኙ 15 ትምህርት ክፍሎች ከዓለምአቀፉ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ (ኮቪድ-19) በፊት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ወንድ 597፣ ሴት 143፤ በድምሩ 840 የቅድመ ምረቃ ተማሪዎች እና በቢዝነስና ኢኮኖሚክስ እንዲሁም በግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ኮሌጆች ስር በሚገኙ አራት ትምህርት ክፍሎች ከወረርሽኙ በኋላም በቴክኖሎጂ አማራጮች ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ በመደበኛና በማታው የድኅረ ምረቃ መርሀግብሮች ወንድ 81፣ ሴት 8፤ በድምሩ 89 ምሩቃን ናቸው።

    በ2004 ዓ.ም በ13 የትምህርት መስኮች 595 መደበኛ ተማሪዎችን ተቀብሎ ማስተማር የጀመረው ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በአሁኑ ጊዜ በስምንት ኮሌጆችና አንድ ትምህርት ቤት በቅድመ ምረቃ 50 መርሀግብሮች እንዲሁም ሁለተኛ ዲግሪ እና 12 ፕሮግራሞች በጠቅላላው ከ14 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በመደበኛ፣ በማታና በክረምት መርሃ ግብሮች እያስተማረ ይገኛል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    ጉራጌ በክልል የመደራጀት ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄ የክልሉ መንግሥት በሰላማዊና በሰለጠነ መንገድ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጠው የብሔሩ ተወላጆች ጠየቁ።

    ኧዣ ወረዳ ፥ጉራጌ ዞን (ሰሞነኛ) – የደቡብ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ርስቱ ይርዳው ከጉራጌ ማኅበረሰብ ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ በጉራጌ ዞን ኧዣ ወረዳ በደሳለኝ ሎጅ ውይይት አካሄዱ። የውይይቱ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት ጉራጌ በክልል የመደራጀት ሕገ መንግሥታዊ መብቱ በሰላማዊና በሰለጠነ መልኩ የክልሉ መንግሥት አፋጣኝ ምላሽ ሊሰጠው እንደሚገባ ጥሪ አቀረቡ።

    በጠንካራ የሥራ ባህሉና ከየትኛውም ብሔር ብሔረሰቦች ጋር ተግባብቶ፣ ተቻችሎና ተከባብሮ የመኖር የቆየ ልማድ ያለው የጉራጌ ብሔር ባለፋት 27 ዓመታት በማኅበራዊ፣ በፓለቲካዊና በኢኮኖሚው ከፍተኛ በደልና ጭቆና ሲደርስበት እንደነበር ያስታወሱት አስተያየት ሰጪዎቹ፥ አሁን በመጣው የሀገሪቱ ለውጥ ፍትሃዊ የኢኮኖሚና የፓለቲካ ተጠቃሚነቱ ሊረጋገጥለት እንደሚገባ ተናግረዋል።

    አክለውም ብዙ ጊዜ በክልል የመደራጀት ጥያቄ ሲነሳ ጉራጌ ክልል አያስፈልገውም የሚል አስተያየት የሚሰጥ መሆኑን የገለጹት ተሳታፊዎቹ፥ ክልል የማያስፈልግ ከሆነ አሁን ያለው የዞን አስተዳደር ለምን ያስፈልጋል፣ ጉራጌ በክልል ቢደራጅ ስጋቱ ምንድን ነው የሚል ጥያቄዎች ተነስተው በመድረክ አወያዮቹ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል።

    የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሀመድ ጀማል እንደገለጹት፥ ዞኑ የብዙ ብሔር ብሔረሰቦች መኖሪያ ስትሆን መንግሥት እንኳ ባይኖር ሕዝቡ ራስ በራሱ መምራት የሚችልበት ቱባ ባህል፣ እሴትና እምነት እንዲሁም ባህላዊ የዳኝነት ሥርዓት ያለው ነው ብለዋል።

    የዞኑ ሰላም ለማስጠበቅ የሀይማኖት አባቶችና ሽማግሌዎች እየሠሩት ያለው ሥራ የሚበረታታ መሆኑን የገለጹት አቶ መሀመድ፥ በቀጣይም የሕዝቦች አንድነት ለማጠናከር በትኩረት ይሠራል ብለዋል። ጉራጌ በክልል የመደራጀት ጥያቄ የሚጠይቀው ለቅንጦት ሳይሆን ሕገ መንግሥታዊ መብቱ ስለሆነ መንግሥት አፈጣኝ ምላሽ እንዲሰጥ አቶ መሀመድ ጠይቀዋል።

    በክብር እግድነት የዞኑ ማኅበረሰብ ለማወያየት የመጡት የደቡብ ክልል የብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ እንደተናገሩት፥ የጉራጌ ብሔር ለሥራ እንጂ ለግጭትና ለንትርክ ጊዜ የሌለው ከየትኛውም ብሔር ብሔረሰብ ጋር ተከባብሮና ተዋዶ በፍቅር የሚኖር ነው ብለዋል። ጉራጌ በክልል እንዲደራጅ ለተጠየቀው ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት አሁን አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ መልስ መስጠት እንደማይችሉና በቀጣይ በመመካከር ለህብረተሰቡ ምላሽ እንደሚሰጠው አቶ ሞገስ ተናግረዋል።

    የደቡብ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ርስቱ ይርዳው ከውይይቱ ተሳታፊዎች ለተነሳላቸው ጥያቄዎች መልስ ሲሰጡ እንደተናገሩት፥ በመስቃን ቤተ ጉራጌና በማረቆ መካከል የተፈጠረው ግጭት ለመፍታት ከሀይማኖት አባቶች፣ ከሀገር ሽማግሌዎች እና ከሌሎችም የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር በመሆን ጥረት እየተደረገ መሆኑንና በአጭር ጊዜ መፍትሄ ያገኛል ብለዋል።

    ክቡር ርዕሰ መስተዳድሩ የሕዝቡ በክልል የመደራጀት ጥያቄ ሲመልሱ እንደተናገሩት፥ ጉራጌ በክልል የመደራጀት መብት እንዳለው ጠቁመው ጥያቄው የሀገሪቱ የለውጥ ጉዞ በማያደናቅፍ መልኩ መሆን አለበት በማለት አቋማቸውን ተናግረዋል።

    በመድረኩ የደቡብ ክልል የካቢኔ አባላት፣ ከአዲስ አበባ የመጡ አመራሮችና ተወላጆች፣ ባለሀብቶች፣ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር አመራሮች ፣ የሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳታፊ ነበሩ ሲል የዘገበው የጉራጌ ዞን አስተዳደር ሕዝብ ግንኙነት ጽህፈት ቤት ነው።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን አስተዳደር ሕዝብ ግንኙነት ጽህፈት ቤት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ጉራጌ በክልል የመደራጀት

    Semonegna
    Keymaster

    አቶ ርስቱ ይርዳው በሹመት ንግግራቸው “ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ያጋጠሙ ውስብስብ ችግሮች መፍትሔ በሚሹበት ሰዓት ቢሆንም፤ የሕዝቦችን ኃላፊነት በመቀበሌ ኩራት ይሰማኛል” ብለዋል።

    ሀዋሳ (ሰሞነኛ) – የደቡብ ክልል ምክር ቤት ዘጠነኛ መደበኛ ጉበኤው የክልሉን ምክትል ርዕሰ መስተዳድር በመሾምና ከ40 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት በማጽደቅ ተጠናቀቀ።

    የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን) ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የክልሉን ወቅታዊ ሁኔታ ከገመገመ በኋላ የርዕሰ መስተዳድር ለውጥ እንዲደረግ በወሰነው መሠረት አቶ ርስቱ ይርዳው የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሆነው እንዲመሩ ሾሟቸዋል።

    በተጨማሪም ደኢህዴን ለ2012 በጀት ዓመት 40 ቢልዮን 56 ሚሊዮን 938 ሺህ 826 ብር አጽድቋል። በጀቱ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የ3 ቢሊዮን ብር ብልጫ አለው።

    የበጀቱ ምንጭ ከፌዴራል መንግሥት ድጎማ፣ ከውጭ እርዳታና ከክልሉ ገቢ እንደሚሰበሰብ የክልሉ ፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ታምራት ዲላ ገልጸዋል።

    አቶ ርስቱ ይርዳው በሹመት ንግግራቸው ጥፋተኞችን ለሕግ ማቅረብና ሠላምን ማስፈን ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሠራ ገልጸዋል። በመልዕክታቸው “ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ያጋጠሙ ውስብስብ ችግሮች መፍትሔ በሚሹበት ሰዓት ቢሆንም፤ የሕዝቦችን ኃላፊነት በመቀበሌ ኩራት ይሰማኛል” ብለዋል።

    ከደኢህዴን የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች የጣሉባቸውን እምነት፣ ሁሉንም በእኩል ዓይን በማገልገል ለመወጣት ቅን ፍላጎት እንዳላቸው አቶ ርስቱ ይርዳው ገልፀዋል።

    በክልሉ የተነሱ የክልልነትና የአደረጃጀት ጥያቄዎች ለክልሉና ለደህኢዴን ከባድ ፈተና ስለመሆናቸው ያነሱት አቶ ርስቱ፥ የተፈጠሩትም ሁከቶች ከባድ ጉዳት ያደረሱና የአብሮነት ሕልውናን የተፈታተኑ ነበሩ ብለዋል።

    በክልሉ የሕግ የበላይነትን የማረጋገጥ፣ ሰላም የማስፈንና ጥፋተኞችን ለሕግ ማቅረብ ላይ ትኩረት የሚያደርጉ መሆናቸውንም አቶ ርስቱ ገልፀዋል።

    አቶ ርስቱ በሹመት ንግግራቸው “የብሔር ፅንፈኝነትን፣ የሀይማኖት አክራሪነትን እና ሕገ ወጥነት ለመከላከል ጠንካራ ሥራ ይሠራል” ብለዋል።
    የአመራር ማስተካካያዎችም በጥብቅ ትኩረት እንደሚከናወንም ነው አቶ ርስቱ በንግግራቸው ያስገነዘቡት።

    የኑሮ ውድነትንና ሥራ አጥነትን ለማሻሻል ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እንደሚሠራ የተናገሩት አቶ ርስቱ፥ ከባለሀብቶች ጋር ተቀራርቦ ለመሥራት ያላቸውን ፍላጎት በመግለፅ፣ የእንደጋገፍ ጥሪ ለባለ ሀብቶቹ አቅርበዋል።

    አቶ ርስቱ ይርዳው ከ1985 እስከ 2001 ዓ.ም. በክልሉ ጉራጌ ዞን ከወረዳ አመራርነት እስከ ዞን አስተዳዳሪነት ያገለገሉ ሲሆን፤ ከ2002 ዓ.ም. ጀምሮ የደኢህዴን ሥራ አስፈፃሚ እና በፌደራል ደረጃ የኢፌዴሪ ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር በመሆን ሲያገለግሉ ቆይተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ርስቱ ይርዳው Ristu Yirdaw


    Semonegna
    Keymaster

    በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ በተካሄደው የሰላም ንቅናቄ ላይ ከተለያዩ ቦታዎች የመጡ እና በተለያዩ ሙያዎች ላይ የተሰማሩ የአገራችን ታዋቂ ሰዎች ስለ ሰላም እና በሰላም እጦት ምክንያት የሚከሰቱ አስከፊ ጉዳቶች ለታዳሚው አቅርበዋል።

    ወልቂጤ (ሰሞነኛ)– “ጥበብ ለሰላም” በሚል መሪ ቃል በጉራጌ ዞን ከሚገኙ 17 ወረዳዎችና ከ4 ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ የሀይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የአገራችን ታዋቂ የኪነ ጥበብ ሰዎች፣ አመራሮች፣ የሲቪል ሰርቪስ (civil service) ሠራተኞች እና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች በተገኙበት በወልቂጤ ከተማ ትልቅ ስብሰባ/ውይይት በድምቀት ተካሂዷል።

    በዚህም ዞን አቀፍ የሰላም ንቅናቄ የአገራችን ታዋቂ ሰዎች (በጥቂቱ ለመጥቀስ ያህል ደራሲና መምህር ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፣ ደራሲ እንዳላጌታ ከበደ፣ ደራሲ ህይወት ተፈራ፣ የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ዳይሬክተር ጀነራልና የሙዚቃ ሀያሲው አቶ ሠርፀ ፍሬስብሐት እና ደራሲ ተስፋዬ ጎይቴ ስለ ሰላም እና በሰላም እጦት ምክንያት የሚከሰቱ አስከፊ ጉዳቶች ለታዳሚው አቅርበዋል። የሁሉም የመቋጫ ሀሳብ የአገራችን ህዝቦች አጥር ሳይገድባቸው በብሔር፣ በዘር፣ በጎሳ፣ በሀይማኖትና በመሳሰሉ ከፋፋይ ጉዳዮችን ትተው በአንድነትና በሰብዓዊነት ስሜት ተዋደውና ተቻችለው እንደቀድሞው አብረው ሊኖሩ እንደሚገባ ነው።

    በዚህ ታላቅ የሰላም ንቅናቄ የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሀመድ ጀማልና የባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ወ/ሮ መሠረት አመርጋ ሰላም ለሁሉም ጉዳዮች መሠረት መሆኑ እና ሰላም በሌለበት ምንም ሊኖር እንዳማይችል ገልፀው የዞኑ ህዝብ በሙሉ ለሰላም ዘብ መቆም እንዳለባቸው አሳስበዋል።

    “ጥበብ ለሰላም” በሚል በተካሄድው በዚህ መርሀግብር ታዋቂ የአገራችን ደራሲያን፣ የጉራጌ ዞን የባህል ኪነት ቡድን፣ ከወልቂጤና ከቡታጅራ ከተማ አስተዳደሮች የኪነ ጥበብ ክበባት የተውጣጡ አማተር ኪያንያን ድንቅ የሙዚቃ፣ ድራማና የሥነ ግጥም ሥራዎቻቸውን አቅርበዋል። እንዲሁም በሱዑዱ አብደላ የተሳሉ ድንቅ የሥነ ስዕል ሥራዎቹን አቅርቧል። የ11ኛ ክፍል ተማሪ ይዘዲን የፈጠራ ሥራዎች በመድረኩ ከቀረቡ ሥራዎች ይገኝበታል።

    በመጨረሻም ለፕሮግራሙ መሳካት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ላበረከቱ አካላት የዞኑ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ያዘጋጃቸው ባህላዊ ስጦታዎች፣ የማበረታቻ ሽልማትና የምስጋና የምስክር ወረቀት አበርክቷል።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን አስተዳደር የሕዝብ ግንኙነት ቢሮ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ጥበብ ለሰላም መድረክ በጉራጌ ዞን


    Semonegna
    Keymaster

    በቤተ ጉራጌ ዘንድ በወጌሻ ሕክምና ሙያቸው ስማቸው እጅግ ከፍ ብሎ የሚጠራው አቶ ፈንቅር ሳረነ ሲሆኑ፥ ይህም ሙያ ከእርሳቸው አልፎና ከልጅ ልጆቻቸው ተዋርሶ፣ አሁን የልጅ ልጆቻቸው በቤተ ጉራጌ ብቻ ሳይሆን በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች እያገለገሉ ይገኛሉ። አቶ መኮንን አመርጋ ደግሞ የአቶ ፈንቅር ሳረነ አራተኛ የልጅ ልጅ ናቸው።

    ኑሬ ረጋሳ (የጉራጌ ዞን ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ)

    ወልቂጤ (ሰሞነኛ) – ከባህላዊ የሕክምና ዘዴዎች ውስጥ የወጌሻ ሕክምና አንዱ ነው። የሰዉ ልጆች በተለያዩ ምክንያቶች በአካላቸዉ ላይ የተለያዩ አደጋዎች ይገጥማቸዋል። በአንድ ወቅት በወጌሻ ፈንቅር ሳረነ በሰውነታቸው ላይ እባጭ ወጥቶባቸው ሁለተኛ ወገን ባለማግኘታቸው በቻሉት አቅም ራሳቸውን አክመው እባጩን በማዳናቸው ምክንያት አድርገው የጀመሩት የባህላዊ ወጌሻ ሙያ ከልጅ ልጅ እየተላለፈ አሁንም ድረስ የፈንቅር ሳረነ የልጅ ልጆቻቸው ከቤተ ጉራጌ ክልል አልፈው በሌሎችም ቦታዎች ህብረተሰቡን እያገለገሉ ይገኛሉ።

    አቶ ፈንቅር ሳረነ የተወለዱት በ1814 ዓ.ም. በጉራጌ ዞን ኧዣ ወረዳ የወግወረ በቢባል አካባቢ ነበር። የአካባቢው ማህበረሰብ አንደግባ የሚል የክብር ስም ሰጥቷቸዋል። በባህላዊ ሕክምና ህዝቡን የማገልገል እሳቤ ይዘው ወደ ወጌሻነት ሙያ የገቡት ፈንቅር ሳረነ ለዘመናት ህዝቡን አገልግለዋል። የወጌሻነ ሕክምና አገልግሎታቸው እና ከተለያዩ እፅዋት በባህላዊ መንገድ በመቀመም የሚያዘጋጇቸው መድኃኒቶች እስከ በጊዜው እስከ ቤተ መንግስት ድረስ አድርሷቸዋል። ፈንቅር ሳረነ የ8 ወንድ ልጆችና የአንድ ሴት ልጅ ወላጅ አባት ሲሆኑ ለአብነት ያህል ካቤ ፈንቅር ሳረነ፣ ጫሚሳ ፈንቅር፣ ድድራ ፈንቅር፣ ገብረማሪያም ፈንቅር፣ እንዱሁም ሌሎችም ይጠቀሳሉ። ወጌሻ መኮንን አመርጋ የአራተኛ የልጅ ልጅ (ማለትም ፈንቅር፣ መኮንን አመርጋ ጫሚሳ ፈንቅር) ሲሆኑ፥ እሳቸውም በሚሰጡት የወጌሻነት ሕክምና አገልግሎት አንቱታን አትርፈዋል።

    ወጌሻ መኮንን አመርጋ እንደሚሉት በባህላዊ ሕክምና ሙያ፣ ልምድና ዕውቀት የቀሰሙት የልጅ ልጅ በሆኑት በወጌሻ ወልዴ ጫሚሳ እንደሆነና ወጌሻ ወልዴ ጫሚሳ ከቤተ ጉራጌ ክልል አልፈው እስከ ስልጢ ድረስ እየዞሩ ያገለግሉ እንደነበረም ተናግረዋል። ድርድራ ፈንቅር ከጅማ እስከ ከፋ ድረስ የባህላዊ ሕክምና ሲሰጥ እንደነበረ እንዲሁም የካቤ ፈንቅር ልጆች (ለምሳሌ ዜናዬ ካቤ፣ መዝገበ ካቤ) አዲስ አበባ ላይ አገልግሎት እንደሰጡ፤ በወሊሶና አካባቢው ደግሞ ተክሌ ሙራረ በአግባቡ የወጌሻነት አገልግሎት ለህብረተሰቡ ይሰጡ እንደነበረም አስረድተዋል። የልጅ ልጅ የሆኑትን ወይዘሮ ዙሪያሽ ደግሞ አጠቃላይ ቤተ ጉራጌ በአካለለ መልኩ ቸሃ ላይ መቀመጫ አድርገው ይሠሩ እንደነበረም ጠቅሰዋል።

    የEBS ቴለቭዥን አርአያ ሰብ መርሀግብር በፈንቅር ሳረነ የሕይወት ታሪክ ላይ የሠራውን ጥንቅር እዚህ ጋር ይመልከቱ

    የወጌሻነት ሙያ ከአጎታቸው የተማሩት መኮንን አመርጋ ወልቂጤ ከተማ ላይ በመምጣት ለህብረተሰቡ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ። ወልቂጤና አካባቢዋ የሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማገልገል ተጠቃሽ የሆነው ወጌሻ መኮንን አመርጋ ለበርካታ ዓመታት ቤታቸው ውስጥ በተለያዩ ምክንያቶች የተጎዱ የህብረተሰብ ማለትም በስፖርታዊ ውድድሮች ተሰብሮና እግሩ ወልቆ ለሚመጣ፣ የተሸከርካሪ አደጋ ለደረሰበት፣ ውልቃትና መሰል አደጋ ለደረሰበት ሰው አገልግሎት በመስጠት ይታወቃሉ።

    ወጌሻ መኮንን አመርጋ የወልቂጤ ከነማ እግር ኳስ ክለብ ብሔራዊ ሊግ እያለ ለሁለት ዓመት ከመንፈቅ ያህል በወጌሻነት በማገልገል ለስፖርተኞች ጥሩ ወንድማዊ ፍቅርን በመለገስ በጫወታ ወቅት የሚደርስባቸው ጉዳት በማከም ስፖርተኞች ውጤታማ እንዲሆኑና አሁን ለደረሱበት ከፍተኛ ሊግ በሙያቸው የበኩላቸውን ሚና ተወጥተዋል። ከዚህም በተጨማሪ ለበርካታ ዓመታት የወረዳውና የዞን ውድድሮችን እንዲሁም በየዓመቱ በሚደረጉ የትምህርት ቤቶች ውድድሮች ላይ ሳይሰለቹ በቅንነት በማገልገል ስማቸው ከምስጋና ጋር ይነሳል።

    ለሙያው እና ለተገልጋዩ ህብረተሰብ ባላቸው ክብር የተነሳ በጣም ጉዳት ደርሶበት ውይም ደርሶባት መኖሪያ ቤቱ መምጣት የማይችሉት ጉዳተኞች እስከ መኖሪያ ቤታቸው ድረስ በመሄድ ሙያዊ እገዛ በማድረግ ይታወቃሉ – ወጌሻ መኮንን። አንድ ባለ ጉዳይ አገልግሎቱን ለማግኘት ከመጣ ገንዘብ እንኳን ባይኖረውም መጎዳትና አካለ ስንኩል መሆን የለበትም በማለት አገልግሎቱን በነጻ በመስጠት በጎነታቸው የሚታወቁት መኮንን ዓመርጋ፥ የወጌሻነት ሙያ ወደ ልጆቻቸው ለማስረጽ ሙያውን ሙሉ ለሙሉ እንዲያውቁት ለማድረግ የዕውቀትና የሙያ ሽግግር የማድረግ ዓላማ ይዘውም ይሠራሉ።

    በዚህም የበኩር ልጃቸው የአባቱን የወጌሻነት የጥበብ ትምህርት የእረፍት ጊዜውን በመጠቀም አባቱን በማገዝና ለህብረተሰቡ የሚሰጡትን አገልግሎት በመቅሰም ወይም ትምህርት በመውሰድ፣ ወጌሻ መኮንን ራቅ ወዳለ ቦታ ከሄዱ አገልግሎት ፈልገው ለሚመጡ ደንበኞች አገልግሎት እየሰጠ እንደሆነና ሙያውን ሙሉ ለሙሉ አውቆ በእረፍት ጊዜው እየሠራበት እንደሆነም ወጌሻ መኮንን ገልጸዋል።

    መንግስት የባህላዊ ሕክምናው ዘርፍ ለማዘመን ነጻ የትምህርትና ስልጠና እድል በማመቻቸት የሕክምናውን ሳይንስ እንዲያውቁት በማድረግ ረገድ ውስንነት መኖሩን አስታውቀው፥ የጤናውን ትምህርት ባይወስዱም ህብረተሰቡን እያገለገሉበት ያለውን የወጌሻ ሙያ ዕውቀታቸውን የበለጠ ለማዳበር ቴክኖሎጂ በመጠቀም እና ሀኪም ጓደኞቻቸውን በማማከር ትምህርት እየተማሩ እንደሆነና በሥራ ላይ የሚገጥማቸውን ውስንነት እየቀረፉ እንደሆነም አስረድተዋል። በሳምንት በርካታ ሕመምተኞች በቀላልና ከባድ አደጋ ቤት ድረስ መጥተው አገልግሎት እንደሚያገኙ የተናገሩት መኮንን ዓመርጋ በከተማው ለበርካታ ዓመታት አገልግሎት የሚሰጡት በመኖሪያ ቤታቸው ሲሆን መንግስት በከተማው ሴንተር ቦታዎች ላይ ቋሚ መሥሪያ ቦታ ቢያመቻችላቸው የበለጠ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋና ውጤታማ አገልግሎት መስጠት ያስችላቸዋል።

    የወጌሻ ሙያ ከጀመሩ ብዙ ዓመታትን ያስቆጠሩት መኮንን በሥራ ላይ ብዙ ገጠመኞች እንደገጠማችው አስታውሰው ለአብነት ያህል በአንድ ወቅት በእግር ኳስ ሜዳ ላይ አንድ አጥቂ ጎል ለማግባት ሲል እርስ በእርስ ተጋጭተዉ ላንቃው ሙሉ ለሙሉ ተዘግቶ ምላሱን ማንቀሳቀስ አቅቶት ሊሞት ሲል አንደምንም ርብርብ አድርገን አፉን በመክፈት በባንድራ እንጨት አፉን በመክፈት ወደ ሕክምና ማእከል በመውሰድ እንዳዳኑትም ተናግረዋል።

    አቶ ኢሳያስ ናስር ቀደም ሲል የወልቂጤ ከነማ ሥራ አስኪያጅ የነበሩ ሲሆ ወጌሻ መኮንን ዓመርጋ ከሕክምናው ሙያው በተጨማሪ ክለቡን ውጤታማ እንዲሆን ከፍተኛ መስዋትነት የከፈሉ ምርጥ ባለሙያ ናቸው ብለው ይመስክሩላቸዋል። አክለውም፥ ስፖርተኞች የከፋ አደጋ እንኳን ቢደርስባቸው ጊዜያቸውንና ዕውቀታቸውን በመጠቀም የተቻላቸውን ጥረት በማድረግ ጉዳት የደረሰባቸው ሲታደጉ ነው የሚታዩት። ከስፖርተኞች ጋር ጥሩ ፍቅር በማሳየት ከብሔራዊ ሊግ ጀምሮ ክለቡ አሁን ለደረሰበት ሁኔታ የአንበሳውን ሥራ ሰርተዋል፤ አሁንም ድረስ በበጎ ፍቃደኝነት በሙያው አገልግሎት በመስጠት ናቸው በማለት የወጌሻ መኮንን አመርጋ ታታሪነት ይመሰክራሉ። አቶ ኢሳያስ በመቀጠልም የሙያና የዕውቀት ሽግግር እንዲኖር ለማድረግ መንግስት እነዚህ የወጌሻ ባለሙያተኞች በተገቢው ምቹ የሥራ ቦታ ቢያመቻችላቸው የተሻለ ሥራ እንዲሠሩ ያስችላቸዋል ብለዋል።

    አንዳንድ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ የህብረተሰብ ክፍሎች በሰጡት አስተያየት ወጌሻ መኮንን ዓመርጋ ቅንና ለሙያው ክብር ሰጥተው የሚሠሩ ባለሙያ እንደሆኑ፣ ሰውን ለማዳን እንጂ ገንዘብ ማትረፍን ዓላማ አድርገው የማይሠሩና አቅም ለሌላቸው በነጻ ሕክምና እንዲያገኙ በማድረግ ከህመማቸው እንዲድኑ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት የሚያደርጉ ባለሙያ መሆናቸውን ይመሰክሩላቸዋል። የዚህ ጹሁፍ አዘጋጅም ወጌሻ መኮንን ዓመርጋ በሙያው ያላቸውን የካበት ልምድ እና ህብተረሰቡን ለማገልገል ያላቸውን ከፍተኛ ፈላጎት ከግምት ውስጥ በማስገባት ለሙያው ያላቸውን መልካም ፍቃድ የበለጠ አጠናክሮ እንዲሰራበትና በተለያዩ ምክንያቶች የአካል ጉዳት የሚደርስባቸው የህብረተሰብ ክፍሎችን እንዲታደግ እያልኩኝ ወጌሻ መኮንን ዓመርጋ መንግስት በዘርፉ ውጤታማ ሥራ እንዲሰራ የመስሪያ ቦታ እንዲያመቻችለት እና ተተኪ ባለሙያተኞች መፍጠር ይኖርበታል።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    መኮንን ዓመርጋ


    Anonymous
    Inactive

    ግብርን በመክፈል አገራዊ ለውጡን ማገዝ ይገባል — የደቡብ ክልል ገቢዎች ባለስልጣን
    —–

    የንግዱ ማህበረሰብ የሚጠበቅበትን ግብር በወቅቱ በመክፈል የተጀመረውን አገራዊ ለውጥ እንዲያግዝ የደቡብ ክልል ገቢዎች ባለስልጣን ጠየቀ።

    ክልል አቀፍ የታክስ ንቅናቄ በወልቂጤ ከተማ ተጀምሯል ።

    ባለስልጣኑ ዋና ዲያሬክተር አቶ ንጉሴ አስረስ በወቅቱ እንደገለጹት በግብር አሰባሰቡ ሂደት ላይ ያጋጠሙ ችግሮችን በመፍታት የክልሉ ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ መሰብሰብ ትኩረት ተሰጥቷል።

    “የክልሉ ህብረተሰብ በተለይም ግብር ከፋዩ የታክስ ስወራና ማጭበርበርን በመከላከል የገቢ አሰባሰቡ ስኬታማ እንዲሆን ኃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል” ብለዋል ።

    ”የህዝቡ የልማት ጥያቄ ሊመለስ የሚችለው የንግዱ ማህበረሰብ ገቢውን በማሳወቅ የሚጠበቅበትን ግብር መክፈል ሲችል ነው” ያሉት ኃላፊው ግብር ከፋዩ ኃላፊነቱን በመወጣት ለውጡን እንዲያግዝ ጠይቀዋል ።

    “ተጠቃሚውም ደረሰኝ በመጠየቅ የድርሻውን ሊወጣ ይገባል” ብለዋል።

    በገቢዎች ሚኒስቴር የሀዋሳ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍቃዱ ወልደመሰቀል በበኩላቸው “የታክስ ጉዳይ የግብር ሰብሳቢው ተቋም ብቻ ሳይሆን፤ የሁሉም ዜጎች በመሆኑ ህዝቡ ከሚመለከተው አካል ጋር በጋራ ሊሰራ ይገባል” ብለዋል ።

    “ስራ አጥ ወጣቶችን የስራ እድል ባለቤት ማድረግና የመሰረተ ልማት ተቋማትን ማስፋፋት የሚቻለው ተገቢውን ገቢ መሰብሰብበ ሲቻል ነው” ያሉት ደግሞ የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ኮሚሽን የሐዋሳ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ ታደሰ መርዕድ ናቸው ።

    ተገቢውን ግብር ለመሰብሰብ እንዳይቻል የሚያደርጉ በርካታ ጉዳዮች እንዳሉ የጠቆሙት አቶ ታደሰ ህገወጥ ንግድ፣ የኮንትሮባንድ ታክስ ማጭበርበር ዋነኛ ምክንያቶች መሆናቸውን ተናግረዋል።

    በገቢና በወጪ ንግዱ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እያስከተለ ያለውን የኮንትሮባንድ ንግድ ለመከላከል ህዝቡ ከመንግስት ጎን ሊቆም እንደሚገባ አሳስበዋል።

    የጉራጌ ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪና የዞኑ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን መምሪያ ኃላፊ አቶ ታጁ ናስር በበኩላቸው በዞኑ ባለፉት ስድስት ወራት ለመሰብሰብ ከታቀደው 918 ሚሊዮን ብር ውስጥ 362 ሚሊዮን ብር ብቻ መሰብሰቡን ተናግረዋል ።

    ግብይትን ያለደረሰኝ ማካሄድ፣ የንግድ ፈቃድን በቤተሰብ ከፋፍሎ ማውጣት፣ የታክስ ስወራና ማጭበርበር ዕቅዱን እንዳይሳካ ያደረጉ ምክንያቶች መሆናቸውን ጠቁመዋል ።

    የወልቂጤ ከተማ የሰላም በር ትምህርት ቤት የታክስ ክበብ አባል ተማሪ አያልነሽ አይተንፍሱ “ግብር ያለ ማጭበርበርና በስርዓት መክፈል አገርን ከድህነት እንድታድግ ያስችላል” ብላለች ።

    ግብርን አለመክፈል አገራዊ እድገትን እንደሚጎዳም ገልጻለች ።

    ግዴታዬን እወጣለሁ መብቴን እጠይቃለሁ!” በሚል መሪ ቃል የተጀመረው ክልል አቀፉ የታክስ ንቅናቄ እስከ የካቲት 30 ቀን 2011 ድረስ ይቆያል።

    የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የጃፓን መንግስት በኢትዮጵያ ለትምህርትና ጤና አገልግሎት የሚውል ከ452 ሺህ ዶላር በላይ ድጋፍ አደረገ። የጃፓን መንግስት አዲስ አበባ በሚገኘው ኤምባሲው በኩል ያደረገው የገንዘብ ድጋፍ በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የሚገኙ አራት ፕሮጀክቶችን ለመገንባትና ለማስፋፋት ያስችላል።

    በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ዲያሱኬ ማሱናጋ (Daisuke Matsunaga) የፕሮጀክት ግንባታና ማስፋፊያ ከሚደረግላቸው ትምህርት ቤቶች ኃላፊዎች ጋር የድጋፍ ስምምነት ተፈራርመዋል።

    ፕሮጀክቶቹ በደቡብ ክልል ጉራጌ ዞን የጉንችሬ እና እነሞር ወረዳ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታና በኦሮሚያ ክልል በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን የሀሮ ሾጤ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ማስፋፊያ ናቸው።

    በተጨማሪም ለሻሻመኔ ከተማ የአረጋዊያንና አካል ጉዳተኞች የምግባረ ሰናይ መጠለያ ግንባታና ለጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የዩሮሎጂ እና ድንገተኛ ክፍል የህክምና መሣሪያዎች ግዥ የሚውል ነው።

    እነዚህ አራት የትምህርት እና የጤና ፕሮጀክቶች ከአራት ሺህ በላይ ህዝብ ተጠቃሚ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል ሲል የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዘግቧል።

    አምባሳደር ዲያሱኬ ማሱናጋ እንዳሉት አገራቸው ለኢትዮጵያ ልማት ተሳትፎ የምታደርገውን ድጋፍ አጠናክራ ትቀጥላለች። ጃፓን በኢትዮጵያ እ.አ.አ ከ1989 ጀምሮ በተለያዩ ክልሎች ከ400 በላይ ፕሮጀክቶችን በመሥራት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ እያደረገች ነው።

    በትምህርት፣ በቴክኒክና ሙያ ስልጠና፣ በንጹህ ውሃ አቅርቦት፣ በኢኮኖሚ ልማትና ሌሎችም መስኮች ድጋፍ ስታደርግም ቆይታለች።

    በስምምነቱ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ ስፖርት ኮሚሽነር እርስቱ ይርዳው የተደረገው ድጋፍ የዝቅተኛውን የህብረተሰብ ክፍል የትምህርት ፍላጎት ለማሟላት እንደሚያስችል ገልጸዋል።

    ድጋፉ በተለይም ትምህርት ቤት ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች መሆኑ የትምህርት ሽፋንን በማስፋት የመንግስትን ጥረት እንደሚያግዝም ተናግረዋል፡፡

    ከዚህ ጋር በተያያዘ የጃፓን ኤምባሲ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሚገኘውን የራስ መኰንን አዳራሽ ለማደስ የ85 ሺሕ 679 ዶላር (2,403,500 ብር) ዕርዳታ መለገሱን ሪፖርተር ጋዜጣ በእሁድ ታህሳስ 7 ቀን 2011 ዓ.ም. እትሙ ዘግቧል።

    አምባሳደር ዲያሱኬ ማሱናጋ እና የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ዳይሬክተር አህመድ ሐሰን (ዶ/ር) የእርዳታ ስምምነቱን የተፈራረሙ ሲሆን፣ ገንዘቡም የራስ መኰንን አዳራሽ ባህላዊና ታሪካዊ ዳራው ሳይጠፋ ለማደስ፣ የተበላሹ ክፍሎችን ለመጠገን፣ ውስጣዊ ክፍሉን ለማደስ እና አዳዲስ ቁሳቁስ ለማስገባት መሆኑ ታውቋል።

    የጃፓን መንግስት ትምህርታዊ ድጋፍ ከማድረጉም በተጨማሪ የራስ መኰንን አዳራሽን ለማደስ መነሳቱ፣ የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም ኢትኖሎጂካል ሙዚየም በርካታ ጎብኚዎች እንዲስብ ያስችላል ተብሏል።

    በሙዚየሙ ከአሥር ሺሕ በላይ የኢትዮጵያ ባህላዊና ሃይማኖታዊ እሴቶች የሚገለጹባቸው አልባሳትና ቁሳቁሶች አሉ፤ ይህም በአፍሪካ አንዱ ታዋቂ ሙዚየም እንዲሆን አስችሏል።

    በቀድሞው የገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት ሕንፃ ውስጥ የሚገኘው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም፣ ከ50 ዓመታት በላይ ዕድሜው በስሩ ያቀፋቸው ቤተ-መጻሕፍት፣ የኢትኖግራፊክ ሙዚየም የምርምርና የጥናት ማዕከልን ነው። በውስጡም መጻሕፍት፣ ታሪካዊ ሰነዶችና መዛግብት፣ የዳግማዊ ምኒልክና የእቴጌ ጣይቱን ጨምሮ የድምፅና የምስል ቅጂዎች፣ ከመጀመሪያ ዲግሪ እስከ ሦስተኛ ዲግሪ ማሟያ የጥናት ድርሳኖች፣ ጆርናሎች፣ ረጅም ዕድሜን ያስቆጠሩ የብራና መጻሕፍትንም ይዟል።

    እንዲሁም እስከ 20 ሺሕ የሚደርሱ የኅትመት ክምችቶች ከቅድመ ምረቃ እስከ ድኅረ ምረቃ ተማሪዎች፣ ለተመራማሪዎች ጥናትና ምርምር አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።

    የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በ2010 ዓ.ም. መስከረም ወር ከጃፓኑ ኪዮቶ ዩኒቨርሲቲ ጋር ትምህርታዊ ልውውጥና የጥናት ትብብር ለማድረግ የመግባቢያ ሰነድ መፈረሙ ይታወሳል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ እና ሪፖርተር ጋዜጣ

    የጃፓን መንግስት

    Semonegna
    Keymaster

    በሐረር የሚኖሩ የጉራጌ ህብረተሰብ አባላት በመስቃን እና ማረቆ በተፈጠረው ግጭት ለተጎዱ ወገኖች የሚውል ስልሳ ኩንታል ሩዝ እና አስር ኩንታል የፉርኖ ዱቄት ድጋፍ ማድረጋቸዉና ይህም በገንዘብ ሲተመን ከ1 መቶ 41 ሺህ ብር በላይ ነው።

    ሀረር (ሰሞነኛ) – በሐረር የሚኖሩ የጉራጌ ብሔረሰብ ተወላጆች በመስቃን እና በማረቆ ብሔረሰብ አባላት መካከል በተፈጠረዉ ግጭት ለተጎዱ እና ለተፈናቀሉ ወገኖች ከአንድ መቶ ሺህ (100,000) ብር በላይ ድጋፍ ማበርከታቸው ተገለጸ።

    በግጭቱ በርካታ ቁጥር ያላቸዉ የህብረተሰብ ክፍሎች ከቤት ንብረታቸዉ ተፈናቅለዉ በአንድ ማዕከል እየተረዱ እንደሆነም ተዘግቧል።

    በሐረር ከተማ የጉራጌ ማህበረሰብ የድጋፍ አሰባሰብ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ዱላ ሟኖጂ በርክክቡ ወቅት በሰጡት አስተያየት ለዘመናት ተዛምደውና ተከባብረው በሚኖሩ በመስቃንና ማረቆ ህብረተሰብ መካከል በተፈጠረዉ ግጭት ለጠፋው የሰዉ ሕይወትና ለወደመው ንብረት እጅግ ማዘናቸዉም ገልፀው፥ ተፈናቅለዉ የሚገኙ ወገኖችም መላዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሚችለው መንገድ (በገንዘብ፣ በቁሳቁስ፣ ወዘተ) ተገቢዉን ድጋፍ ሊያደርግላቸዉ ይገባል ብለዋል።

    አሁን የተፈጠረው የለዉጥ ሂደት ባልጣማቸውና የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ተከባበረው እንዲኖሩ የማይፈልጉ ጥቂት ግለሰቦች ቡድኖች በጠነሰሱት ተንኮል ምንም የማያዉቁ ጨቅላ ሕፃናት፣ እናቶች፣ እንዲሁም አቅመ ደካሞች መሰቃየታቸውና ቀዬአቸውን ጥለው መፈናቀላቸው በጣም ልብ የሚነካ ነዉ ብለዋል።

    መንግስት እንደሀገር የጀመረውን አብሮ የመኖር (‘የመደመር’) አሰተማሪ እርምጃ አጠናክሮ በማስቀጠል ሕይወት እንዲጠፋ፣ ንብረት እንዲወድምና ዜጎች ከቀዬአቸው አንዲፈናቀሉ ያደረጉ አካላትና ድርጊቱን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የፈጸሙ ግለሰቦች ወይም ቡድኖች በአስቸኳይ ለፍርድ መቅረብ አለባቸው ብለዋል።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ከወራት በፊት የጀመረችውን የጀመረችውን የለወጥ ጎዞን ለማደናቀፍ ሕዝቡ የሚያነሣቸ የወሠንና የመልካም አሰተዳደር ጥያቄዎችን በተሳሳተ ወይም አጥፊ በሆነ መንገድ በማሳየት ሕዝቡን ወደ እልቂትና የማያባራ ግጭት እንደገባ የሚየደርጉ አካላትን ከየተኛውም ወገን ሕዝቡ ከመንግሥት ጋር በመተባበር አጋልጦ መስጠት አንዳለበት አሳስበዋል።

    በተለያዩ ከተሞች የሚኖሩ የቤተ ጉራጌዎች እምቅ አቅም ከዞኑ አልፈው ከጂግጂጋ፣ በቡራዪና በተለያዩ አካባቢ ጉዳት ለደረሰባቸው ኢትዮጵያውያን ድጋፍ ማድረጋቸው አሰታዉሰዉ አሁንም በዞኑ በተለያዩ ምክንያት ለችግር የተጋለጡ እንዲሁም ከመኖርያ መንደራቸው ወገኖችን ለማቋቋም የሚደረገው ደጋፍ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አቶ ዱላ ሟኖጂ አሳስበዋል።

    በሐረር የሚኖሩ ቤተ ጉራጌዎች በመስቃንና ማረቆ በተፈጠረው ግጭት ለተጎዱ ወገኖች የሚውል ስልሳ ኩንታል ሩዝ እና አስር ኩንታል የፉርኖ ዱቄት ድጋፍ ማድረጋቸዉና ይህም በገንዘብ ሲተመን ከ1 መቶ 41 ሺህ ብር በላይ እንደሆነም አስረድተዋል።

    በመጨረሻም ለወገን ደራሽ ወገን ነዉና በቀጣይ እነዚህ ወገኖች በቋሚነት እስኪቋቋሙ ድረስ ደጋፋቸዉን አጠናከረዉ እንደሚቀጥሉ የኮሚቴዉ ሰብሳቢ አቶ ዱላ ተናግረዋል።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን ግንኙነት ጽህፈት ቤት | ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የጉራጌ ህብረተሰብ

Viewing 12 results - 1 through 12 (of 12 total)