Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 316 through 330 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ለሀገር እና ለሕዝብ አርአያነት ያለው ታላቅ ተግባር ያከናወኑ ኢትዮጵያውያንን በየዓመቱ ዕውቅና የሚሰጠው የበጎ ሰው ሽልማት በ2012 ዓ.ም. ለሚያካሄደው ስምንተኛው መርሐ-ግብሩ የእጩዎችን ጥቆማ ከየካቲት 1 ቀን 2012 ዓ.ም. አንስቶ ከሕዝብ መቀበል እንደሚጀምር መርሐ-ግብሩን የሚያዘጋጀው የበጎ ሰው ሽልማት ድርጅት አስታውቋል።

    ለስምንተኛው የበጎ ሰው ሽልማት መርሐ-ግብር ከየካቲት 1 እስከ የካቲት 30 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ በአስር ዘርፎች እጩዎችን እንደሚቀበል ድርጅቱ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ያሳወቀ ሲሆን ዘርፎቹም፥ መምህርነት፣ ሳይንስ (ሕክምና፣ ቴክኖሎጂ፣ ፊዚክስ፣ ምህንድስና፣ ኬሚስትሪ፣ አርክቴክቸር፣ ወዘተ)፣ ኪነ ጥበብ/ሥነ-ጥበብ (በወግ ድርሰት)፣ በጎ አድራጎት (እርዳታና ሰብዓዊ አገልግሎት)፣ ቢዘነስና ሥራ ፈጠራ፣ መንግሥታዊ የሥራ ተቋማት ኃላፊነት፣ ቅርስና ባህል፣ ማኅበራዊ ጥናት፣ ሚዲያና ጋዜጠኝነት፣ እና ለኢትዮጵያ እድገት አስተዋጽዖ ያበረከቱ ዳያስፖራዎች ናቸው።

    ካለፈው ዓመት ሰባተኛው የበጎ ሰው ሽልማት አንስቶ በሽልማት ዘርፎች ውስጥ የተካተተው ለአገራችን እድገት አርአያነት ያለው አስተዋጽኦ ያበረከቱ ዳያስፖራዎች እውቅና የሚያገኙበትን ዘርፍ ጨምሮ እስካሁን ሥራ ላይ ባዋልናቸው ዘርፎች በሙሉ ጥቆማ ማድረግ ይቻላል።

    በተለይ የማኅበራዊ ጥናት ዘርፍ ባለፉት ሁለት ዓመታት በቂ እጩዎች ባለመጠቆማቸው ሽልማቱ ስላልተካሄደ፣ በዚህ የሙያ ዘርፍ ያሉ ደርዝ ያለው ሥራ የሠሩ ኢትዮጵያውያንን ለማክበርና አርአያነታቸውን ለማጉላት ሕዝቡ በተለይም ለሙያው ቅርብ የሆኑ ሁሉ ጥቆማቸውን እንዲያቀርቡ ድርጅቱ ጠቁሟል። እንዲሁም በኪነ-ጥበብና ሥነ-ጥበባት ዘርፍ በዘንድሮው መርሐ-ግብር ከሥነ-ጽሑፍ መስኮች አንዱ በሆነው የወግ ድርሰት ላይ ትኩረት ይደረጋል። የወግ ድርሰት ኢ-ልቦለዳዊ በሆነ የሥነ ጽሑፍ ዘርፍ የሚመደብ፣ ጥበባዊ በሆነ የአጻጻፍ ብቃት የሚቀርብ ሲሆን፥ በርካታ አንጋፋና ወጣት ደራሲያን የድርሰት በረከታቸውን አቅርበውበታል። ስለዚህ የዘርፉን ጥበባዊነት ለማጉላትና ደረሲያኑንም ለማበረታታት የዘንድሮው የበጎ ሰው ሽልማት የኪነ-ጥበባት ዘርፍ የሙያ መስክ ተደርጎ ተመርጧል።

    ባለፉት ሰባት የሽልማት ወቅቶች፤ አገራችን የምትኮራባቸውና የላቀ አርአያነት ያለው ተግባር ያከናወኑ ሰዎችን እውቅና የተሰጣቸው ከሕዝብ በቀረቡ ጥቆማዎች መሰረት ነው። የበጎ ሰው ሽልማትን ለዚህ ያበቃውም በሽልማቱ ሂደት በውጭ ሀገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ የሕዝብ ተሳትፎ በመኖሩና ይህም ከዓመት ዓመት እያደገ በመሄዱ ስለሆነ ይህ ተሳትፎ አሁንም ተጠናክሮ እንዲቀጥል ድርጅቱ ጠይቋል። ጠቋሚዎች እጩዎችን በሚጠቁሙበት ጊዜ እጩው ግለሰብ ለአገርና ለሕዝብ ያከናወኑትን ተግባር በዝርዝር እንዲገልጹልንና የሚገኙበትንም አድራሻ መጠቆም እንደሚያስፈልግ ተገልጿል።

    ስለዚህ ይህን የበጎ ሰው ሽልማት ዓላማን ከግምት ውስጥ በማስገባት ከላይ በተገለጹት መስኮች ለጥቆማ በተመደበው የአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ኢትዮጵያውያን ለዚህ ሽልማት ብቁ ናቸው የሚላቸውን እጩዎች እንዲጠቁሙ ጥሪ ተደርጎላቸዋል። ጥቆማ የምንቀበለው በስልክ፣ በቫይበር (Viber)፣ በቴሌግራም (Telegram)፣ በኋትስአፕ (WhatsApp)፣ በኢ-ሜይል (email) እና በፖስታ ነው። አድራሻዎቹም፦

    ስልክ፦ 0977-23-23-23 (ቫይበር፣ ቴሌግራምና ኋትስአፕን ጨምሮ)
    ኢሜይል፦ begosewprize@gmail.com
    ፖስታ፦ 150035፣ አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ ናቸው።

    የበጎ ሰው ሽልማት ዓላማ ለሀገራችን ለኢትዮጵያ መልካም የሚሠሩ፣ ሀገራዊ ተልዕኳቸውን በብቃትና በልዩ ልዕልና የሚወጡ፣ የሕዝቡን ኑሮ ለማሻሻል ለውጥ አምጪ ተግባር የፈጸሙ፤ በብዙ ሰዎች የማይደፈረውን ተግባር በተነሣሽነት የከወኑ፣ ለድጋፍ ፈላጊ የማኅበረሰብ ክፍሎች ትኩረት በመስጠት ሀገራዊ ኃላፊነት ወስደው የሠሩ፣ የሀገሪቱ ታሪክ፣ ቅርስ፣ ባሕል፣ እንዲጠበቅ፣ የሀገሪቱ ሥልጣኔ ከፍ እንዲል የሠሩ ኢትዮጵያውያንን በማበረታታት፣ ዕውቅና በመስጠትና በመሸለም ሌሎችን በጎ ሠሪዎች ለሀገራችን ማፍራት ነው።

    ከሕዝብ የሚቀርበው ጥቆማ ከተጠናቀቀ በኋላ አስፈላጊው ማጣራት ተደርጎ፣ ለመጨረሻው ውድድር ተመርጠው ስማቸው ለዳኞች የሚላከውን እጩዎች ማንነት፣ ሕዝብ እንዲያውቀው ለማድረግ፤ አውቆም ለሀገርና ለሕዝብ ባበረከቱት አስተዋጽዖ እንዲያከብራቸው ዝርዝራቸውን በመገናኛ ብዙኃን አማካይነት ይፋ ይደረጋል።

    የመጨረሻውን የየዘርፎቹን የበጎ ሰው ሽልማት ተሸላሚ ምርጫ የሚያደርጉት ለእያንዳንዱ የሽልማት ዘርፍ በዳኝነት የተመረጡ ባለሙያዎች ናቸው። ዳኞቹ በእውቀታቸውና በሙያቸው አንቱ የተባሉ፣ የረጅም ጊዜ ልምድ ያላቸውና በታማኝነት ምርጫውን ያከናውናሉ ተብለው የታመነባቸው ናቸው። ለእያንዳንዱ ዘርፍም አምስት ዳኞች ተመርጠው ምርጫውን ያከናውናሉ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የበጎ ሰው ሽልማት

    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢ.ህ.አ.ዴ.ግ) ሕጋዊ ሰውነት ማጣትን በተመለከተ ውሳኔ ሰጠ። ይህንንም ተከትሎ አዲሱ ብልጽግና ፓርቲ እና ራሱን ያገለለው ህወሓት ንብረት እንዲከፋፈሉ ቦርዱ ወስኗል።

    አዲስ አበባ (የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ) – የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) በሊቀመንበሩ በኩል ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በላከው ደብዳቤ ግንባሩ መፍረሱን ለቦርዱ ያሳወቀ ሲሆን፥ በሌላ በኩል ደግሞ ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) በሊቀመንበሩ በኩል በተጻፈ ደብዳቤ ግንባሩ በመፍረሱ የንብረት ክፍፍልን አስመልክቶ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ (ቦርዱ) ውሳኔ እንዲሰጥበት ጥያቄ አቅርበዋል።

    የግንባርን (የጥምረት ፓርቲን) መፍረስ የመወሰን ስልጣን የቦርዱ በመሆኑ፥ ግንባሩም ሆነ ህወሓት ግንባሩ መፍረሱን መጥቀሳቸው የማይገባ ቢሆንም ቦርዱ ሁለቱ ሊቃነመናብርት ያቀረቧቸውን የጽሁፍ ጥያቄዎች መሠረት በማድረግ “ግንባሩ መፍረስ አለበት ወይ? ከፈረሰስ ውጤቱ ምን ይሆናል?” በሚል ቦርዱ መርምሮ ውሳኔ ሰጥቷል።

    በመሆኑም ቦርዱ የግንባሩ አባል ሦስት ፓርቲዎች ከግንባሩ ወጥተው አዲስ ውህድ ፓርቲ መመሥረታቸውን የብልጽግና ፓርቲን አመሠራረት ከሚያሳየው መዝገብ ተረድቷል። በመሆኑም ግንባሩ በተግባር መፍረሱን ቦርዱ በሙሉ ድምጽ ወስኗል። የግንባሩ መፍረስ ተከትሎ ቦርዱ የኢህአዴግን ንብረት አስመልክቶ ውሳኔ መስጠት እንደሚያስፈልግም ተረድቷል።

    በመሆኑም የኢህአዴግ አባል ድርጅት የነበሩት ሦስቱ ፓርቲዎች (ማለትምየአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ /አዴፓ/፣ የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ /ኦዴፓ/ እና ደቡብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ /ደኢህዴን/) “ብልጽግና ፓርቲ” የሚባል አዲስ ፓርቲ መመሥረታቸው፣ በሌላ በኩል ደግሞ ህወሃት ህልውናውን ጠብቆ የቆየ ፓርቲ በመሆኑ በሕጉ መሠረት በብልጽግና እና በህወሃት መካከል የኢህአዴግን ንብረት ክፍፍል ማድረግ እንደሚገባ ቦርዱ ተገንዝቧል። በመሆኑም ቦርዱ የኢህአዴግን ንብረት አስመልክቶ የሚከተሉትን ውሳኔዎች ወስኗል።

    1. ብልጽግና እና ህወሃት የኢህአዴግ ንብረት እና ሂሳብ የሚያጣራ አጣሪ በጋራ እንዲሰይሙ፣
    2. በኢህአዴግ ስም (የተመዘገበ) ያለ ማናቸውም እዳ ተጣርቶ እንዲከፈል፣
    3. ከእዳ ክፍያ ቀሪ የሆነ ሃብት ሦስት ሩብ ያህሉ (¾ ተኛው) ለብልጽግና ፓርቲ (የሦስቱ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ውህደት በመሆኑ) ሩብ ያህሉ (¼ተኛ) ደግሞ ለህወሃት ድርሻ መሆኑ ታውቆ በዚያ መሠረት ክፍፍል እንዲያጠናቅቁ፣
    4. ከላይ የተጠቀሱትን ተግባራት በሕጉ መሠረት በ6 ወር ውስጥ ለቦርዱ እንዲያሳውቁ ተወስኗል። (ውሳኔው በጽሁፍ የሚደርሳቸው ይሆናል)

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ
    ጥር 26 ቀን 2012 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

    Semonegna
    Keymaster

    ዓለምን እጅግ ያሰጋው የኖቬል ኮሮና ቫይረስ የተጠቂዎች ቁጥር እጅግ አሻቅቧል፤ ቻይና ውስጥ በአንድ ቀን ብቻ 57 በበሽታው የተጠቁ ሰዎች ሞተዋል። የተለያዩ ሀገራት ዜጎቻቸውን ከዉሃን ከተማ ማስወጣት ጀምረዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የዓለም ጤና ድርጅት የኖቭል ኖቬል ኮሮና ቫይረስ በሽታ ከታሕሳስ 21, 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በቻይና ዉሃን (Wuhan) ግዛት የተከሰተ መሆኑን ካሳወቀ ጀምሮ ይህ ዜና እስከተጠናከረበት ሰዓት ደረስ (በኢትዮጵያ ቀንና ሰዓት አቆጣጠር እስከ ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም. ከምሽቱ ሦስት ሰዓት ድረስ) በአጠቃላይ 17,488 ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን፥ ከእነዚህ ውስጥ 2,298 (13%) ታማሚዎች በሽታው ክፉኛ የጸናባቸው (in critical conditions) ናቸው። እስካሁን ድረስ በሽታው የተገኘባቸው የሀገራc ቁጥር ቻይናን ጨምሮ 24 የደረሰ ሲሆን፣ በበሽታው የሞቱት ሰዎች ቁጥር 362 ደርሷል (361 የሞቱደርሷል ቻይና ውስጥ ሲሆን፣ አንዱ ብቻ ፊሊፒንስ ውስጥ ነው)። ሰኞ ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም. ብቻ 57 በበሽታው የተጠቁ ሰዎች ቻይና ውስጥ ሞተዋል።

    በሀገረ ቻይና እንዲሁ ቫይረሱ ለመጀመሪያ ጊዜ በተስፋፋባቸው ግዛቶች ምንም ዓይነት የመግባትና የመውጣት አንቅስቃሴ እንዳይደረግ ቢታገድም የስርጭቱ መጠን ከሚታሰበው ባላይ አሳሳቢ አየሆነ እንደመጣ ለማወቅ ተችሏል።

    ይህ መላ ዓለምን እጅግ በሚያሰጋ ሁኔታ እየተስፋፋ እየተሰጨና፣ ብሎም ቻይና ውስጥ በበሽታው የሚሞቱት ሰዎች ቁጥር እያሻቀበ ያለው ኖቬል ኮሮና ቫይረስ ወደ ቻይና የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን (በተለይም የ አየር በረራዎችን) መቆጣጠር ጀምሯል። ከችግሩ አሳሳቢነት አንፃር ብዙ ጎረቤት ሀገራት ከቻይና ጋር የሚያዋስናቸውን ድንበር ለመዝጋት የተገደዱ ሲሆን፤ ሌሎች ሃገራትም ወደቻይና የሚደረጉ ማንኛውም በረራዎችን ለማቆም እንደተገደዱ ነው። ለምሳሌ የጀርመኑ ግዙፍ አየርመንገድ ሉፍታንዛ ወደ ቻይና የሚያደርጋቸውን በረራዎች (ቢያንስ እስከ የካቲት 1 ቀን 2012 ዓ.ም.) ሙሉ ለሙሉ አቁሟል። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች (UAE) ወደ ዋና ከተማ ቤጂንግ ከሚደረጉ በረራዎች በስተቀር ሌሎች ወደ ቻይና የሚደረጉ ሁሉንም በረራዎች እንደምትሰርዝ አስታውቃለች። ካናዳ በበኩሏ ዜግቿን ኖቬል ኮሮና ቫይረስ ለመጀመሪያ ጊዜ ከተነሳባት ሁቤይ (Hubei) ግዛት ከምትገኘው ዉሃን (Wuhan) ከተማ ማስወጣት ጀምራለ፤ ሌሎች ሀገራትም ተመሳሳይ እርምጃ ለመውሰድ እንቅስቃሴ ጀምረዋል።

    ቫይረሱ በሀገራቸው በሚኖሩ ዜጎች ላይ መታያቱን ያረጋገጡት የጂ-7 (G-7) ሀገራትም (ካናዳ፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ጣልያን፣ ጃፓን፣ እንግሊዝ እና አሜሪካ) በችግሩ ላይ በትብብር በመሥራት ምላሽ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን የጀርመን የጤና ሚኒስቴር ጄንስ ፋህን በትላንትናው ጥር 24 ቀን 2012 ዓ.ም. ተናግረዋል።

    ወደ ሀገራችን ስንመለስ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ከኢፌዴሪ ጤና ሚኒስቴር እና ሌሎች አጋር ድርጅቶች ጋር በመሆን ለኖቬል ኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ዝግጅት በማድረግ ላይ መሆኑን ሰኞ ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል። እንደመግለጫው እየተወሰዱ ካሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ውስጥ ብሔራዊ ታስክ ፎርስ እና በኢንስቲትዩቱ ለኮሮና ቫይረስ ድንገተኛ አደጋዎች ምላሽ የሚሰጠው ማዕከል ሥራ ጀምረዋል። ከኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት፣ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ፣ ከኦሮሚያ ክልል ጤና ቢሮ፣ ከቦሌ አየር መንገድ፣ ከግልና ከመንግስት ጤና ተቋማት ለተውጣጡ ተሳታፊዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ተሰጥቷል። በተመሳሳይ ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም. ለ200 የሚሆኑ የሆስፒታል አመራሮች እና ባለሞያዎች በጤና ሚኒስተር አማካኝነት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጥቷል። በቦሌ ኢንተርናሽናል ኤርፖርት እና 27 የተለያዩ የድምበር መግቢያ እና መውጫ ኬላዎች ላይ የሚደረገው የማጣራት ምርመራ በተጠናከረ ሁኔታ እየቀጠለ ይገኛል። የማጣራት ምርመራው ከፍተኛ የሙቀት መጠን ያላቸውን ተጓዦች የሚለይ ሲሆን ይሄም የቫይረሱ የበሽታ ምልክት የሚያሳዩትን ለመለየት ይረዳል።

    በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ አራት ሰዎች (አንድ ቻይናዊ እና ሦስት ኢትዮጵያውያን) በኖቬል ኮሮና ቫይረስ በሽታ ተጠርጥረው፥ አንድ በአክሱም እና ሦስት በቦሌ ጨፌ በለይቶ ማቆያ ክትትል እየተደረገላቸው ሲሆን፥ ናሙናቸው ተወስዶ ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመላክ ዝግጅት ተጠናቋል።

    የኖቬል ኮሮና ቫይረስ አስካሁን ድረስ ምንም አይነት ፈዋሽ መድኃኒት ወይም ክትባት ያልተገኘለት ሲሆን በዋናነት የመተንፈሻ አካላትን በማጥቃት ሰዎችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለሞት የሚዳርግ በሽታ ነው። የኖቬል ኮሮና ቫይረስ እንደአውሮፓውያኑ በ2003 በቻይና ከተከሰተው “ሳርስ” በሽታ ጋር የመተንፈሻ አካልን በማጥቃት በኩል ተመሳሳይ ቢመስልም፤ የስርጭት መጠኑ እና የሚያደርሰው ጉዳት ግን እጅግ ከፍተኛ መሆኑ የሚለየው ጉዳይ ነው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ኖቬል ኮሮና ቫይረስ

    Anonymous
    Inactive

    በኢትዮጵያ መንግሥት እየተፈጸመ ያለዉ የሰብዓዊ መብት ረገጣ በነፃ እና ገለልተኛ አካል ምርመራ ሊደረግበት ይገባል
    የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) መግለጫ

    ከምዕራብ ኦሮሚያ (የወለጋ ዞኖች) ቴሌፎንና ኢንተርኔትን የመሳሰሉት የመገናኛ አገልግሎቶች በመንግሥት ከተቋረጡ አንድ ወር አለፈ። ከዚህም የተነሳ የዕለት ተዕለት ክስተቶችን በጊዜዉ ከነበቂ መረጃ ጋር ማግኘት አዳጋች ቢሆንም እንኳ የመንግሥት ወታደሮችና ታጣቂዎች በሰላማዊ (ትጥቅ-አልባ) ዜጎች ላይ እያካሄዱ ባሉት ግድያ የሰዎች ሕይወት እንደቅጠል እየረገፈ መሆኑ መተለያየ መንገድ እየተሰማ ነዉ። በተለይም በሁለት ዞኖች (ምዕራብ ወለጋ እና ቄሌም ወለጋ) ዉስጥ የኢትዮጵያ መንግሥት ወታደሮች በሕዝቡ ላይ እየፈጸሙ ያሉትን ግድያና ጭፍጨፋ በቃላት መግለጽ እንኳን ይከብዳል። የሰብዓዊ መብት ጥሰትና የጦር ወንጀል የሚሉት ቃላቶችም በትክክልና በበቂ ሁኔታ ልገልጹት አይችሉም። በደቡብ ኦሮሚያ (በጉጂ ዞኖች) ያለዉ ሁኔታም እምብዛም ከዚህ የተለየ አይደለም። በዚህ መልኩ ከአንድ ዓመት በላይ በወታደራዊ አስተዳደር (ኮማንድ ፖስት) ሥር በሕዝቡ ላይ እየደረሰ ያለዉን እሮሮና ስቃይ በተለያዩ ጊዜያት ገልጸን መፍትሄ እንድፈለግለት ብንወተዉትም እስካሁን የሕዝባችን ኡኡታና ችግሩ ተገቢዉን ተሰሚነት ሊያገኝ አልቻለም።

    ባሁኑ ጊዜ በተጠቀሱት ቦታዎች በተለይና በተለያዩ የኦሮሚያ አከባቢዎች ባጠቃላይ በሰላማዊ (ትጥቅ-አልባ) ዜጎች ላይ የሚፈጸም ግድያና ጭፍጨፋ፣ የጅምላ እስር፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ከትምህርት ገበታቸዉ መባረር፣ ባጠቃላይ በሕዝባችን ላይ እየደረሰ ያለዉ የሰብዓዊ መብት ረገጣና የጦር ወንጀል (war crime) ከመቼዉም ጊዜ ባላይ ዘግናኝና ከባድ ሆኗል። በነፃና ገለልተኛ አካል የሚደረግ ምርመራ፣ እንዲሁም አስቸኳይ መፍትሄ የሚፈልግ አንገብጋቢ ጉዳይ ነዉ ብለንም እናምናለን።

    ሆን ተብሎ በዶ/ር አብይ አህመድ በሚመራዉ የኢትዮጵያ መንግሥት በሰላማዊ ሕዝባችን ላይ እየተፈጸመ ያለዉን ይህንን እሮሮና ሰቆቃን እጅግ አጥብቀን እናወግዛለን። ይህ እሮሮና መከራ ባስቸኳይ እንድቆምም አበክረን እንጠይቃለን። ይህ ችግር ባስቸኳይ ካልተገታ በስተቀር ከዚህም ወደባሰ ሁኔታ አድጎ ከማንም ቁጥጥር ዉጪ ልሆን እንደሚችል ስጋታችን እየጨመረ መሆኑንም አሁንም በድጋሚ አስረግጠን ልንገልጽ እንወዳለን። ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ የሕይወት መጥፋትና የንብረት ዉድመትን ጨምሮ እስካሁን ለደረሱትና በቃጣይም ልደርሱ ለሚችሉት ጉዳቶች ሁሉ ተጠያቂዉ የኢትዮጵያ መንግሥት (የዶ/ር አብይ አህመድ አስተዳደር) መሆኑንም ግልጽ እናደርጋለን።

    በመጨረሻም መፍትሄ ይሁን ዘንድ የሚከተሉት እርምጃዎች እንድወሰዱ ኦነግ በአጽንኦት ይጠይቃል፦

    1. በግድያና ጭፍጨፋ፣ በእስራት እና በማንኛዉም መልኩ በሰላማዊ ዜጎች ላይ በመንግሥት እየተካሄደ ያለዉ ይህ እሮሮና ማሰቃየት ባስቸኳይ እንዲቆምና ይህንን እያካሄዱ ያሉት የመንግሥት ኃይሎች (ወታደሮች) ወደ ካምፕ እንዲመለሱ፤
    2. ያሉት ችግሮች በዉይይትና በሰላም መፍትሄ የሚያገኙበትን ሁኔታ መንግሥት እንዲያመቻች፤
    3. ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ የተለያየ ጉዳት የደረሰባቸዉ እና ቀዬአቸዉን ለቆ ለመሸሽ የተገደዱ ሰዎች ወደ ቀዬአቸዉ ተመልሶ ስላማይ ኑሮዋቸዉን እንዲኖሩ፣ ከደረሰባቸዉ ጉዳት የሚያገግሙበት እገዛም እንዲደረግላቸዉ። ያለምንም ጥፋትና ህጋዊ ዉሳኔ በተለያዩ ቦታዎች የታሠሩት እንዲፈቱ እና በኢፍትሃዊ መንገድና በተለያዩ ሴራዎች ከትምህርት ገበታቸዉ የተለዩ ተማሪዎች ወደ ትምህርታቸዉ የሚመለሱበት ሁኔታ ባስቸኳይ ተመቻችቶላቸዉ እንዲመለሱ እንዲደረግ፤
    4. በሰላማዊ ሰዎች ላይ እየተፈጸመ ያለዉን ግፍና ሰቆቃ፣ በዚህም እየደረሰ ያለዉን ጉዳት በተመለከተ በነፃና ገለልተኛ አካል አስፈላጊዉ ምርመራ (international investigation) እንዲደረግበት።

    ድል ለሰፊዉ ሕዝብ!
    የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)
    ጥር 23 ቀን 2012 ዓ.ም.

    የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)

    Anonymous
    Inactive

    በየትኛውም ወገን የሚፈፀም፣ ሥርዓት አልበኝነት በቃ ለማለት ጊዜው አሁን ነው!
    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    የኢትዮጵያውያን የፍትህ የእኩልነትና የዴሞክራሲ ጥያቄ በርካታ አስርት ዓመታትን ያስቆጠረ ብቻ ሳይሆን የአያሌ ዜጎችን ሁለንተናዊ መስዋዕትነት የወሰደ ረጅም ጉዞ ነው። በተለይ ባለፉት አምስት ዓመታት የሁሉንም ተሳትፎ ያማከለና አገዛዙ ከሚቋቋመው በላይ የሆነ ንቅናቄ የታየበት ትግል ተደርጓል። ውጤቱም የዛሬዋን ሁኔታ ወልዷል።

    ከበርካታ የዓለም ሀገራት ተሞክሮ እንዳየነው ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን ማዋለድ ከባድ ምጥ ያለበት የጭንቅ ጊዜ ማሳለፍ የግድ መሆኑን ነው። በኢትዮጵያችንም እያየን ያለነው ይህንኑ ነው። በእንደዚህ ዓይነት አስጨናቂ ወቅት ይህን ሂደት እንደአንድ ከባድ ታሪካዊ ኃላፊነት ወስደው የሚሠሩ የመኖራቸውን ያህል ግርግር ፈጥረውና የራሳቸውን ፍላጎት በኃይል ለመጫን የሚፍጨረጨሩ ቡድኖችና ግለሰቦች መኖራቸውን በየእለቱ በየቦታው የምናየው አሳዛኝ ክስተት ሆኗል።

    ፓርቲያችን ከተመሠረተ ጀምሮ ለሀገር ሠላምና ለሕዘብ መረጋጋት የራሱን ያልተቆጠበ አሥተዋፅዖ እያበረከተ ይገኛል። በእኛ ዕምነት የተያዘው የሽግግር ሂደት ለአንድ ወገን የማይተውና የሁሉንም ተሳትፎ የሚጠይቅ እንደሆነ እናምናለን። ያም ሆኖ በዚህ ፈታኝ ወቅት የመንግሥት ሚና ትልቅና ከፍተኛ እንደሚሆን እንገነዘባለን።

    ፓርቲያችን በሀገር አቀፍ ደረጃ የተከሠቱ ፈታኝ ሁኔታዎችንና የመንግሥትን ምላሽ በመገምገም በሚከተሉት ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ያለውን አቋም ይገልፃል።

    1. የየትኛውም በኢትዮጵያ ሀገረ-መንግሥት ግዛት ውስጥ የሚንቀሳቀስ ቡድንም ሆነ ግለሰብ ተግባር የሀገራችን ሕጎ እና ሀገራችን ያፀደቀቻቸውንና የተቀበለቻቸውን ድንጋጌዎች ባከበረ መልኩ ብቻ እንዲሆን ማድረግ የሚገባን ዛሬ ነው። ዜጎች በሕግ ጥበቃ እንደሚደረግላቸው ካልተረጋገጠላቸው እና ከሕግ በታች መሆናቸውን ካልተረዱ ማንም እየተነሳ የፈለገውን አድርጎ “አልጠየቅም” የሚል ማንአለብኝነት ከሠፈነ መቼም ማቆሚያ ወደማይኖረው የሁከት ዓለም ጅው ብሎ እንዳይገባ ያሠጋል።
    2. የሁሉም የፖለቲካ አስተሳሰቦችን በነፃነት እና በሠለጠነ መንገድ መግለፅ፣ በሥልጣን ላይ ያለውንም ሆነ ሌሎች ፓርቲዎችን መተቸት፣ ማጋለጥ አልፎም በምርጫ ከሥልጣን ማውረድ የተለመደና ተገቢም ሊሆን ይችላል። ሀገርን የሚያዋርድ ተግባር መፈፀም ግን ለማንም ያልተፈቀደ የሀገር ከህደት ወንጀል መሆኑ በግልፅ ሊታወቅ ይገባል። በሕዝብ፣ በሃይማኖቶች፣ በብሔረሰቦች፣ በሰንደቅ ዓለማና በመሳሰሉት የአገር መገለጫዎች ላይ የሚፈፀም ማንኛውም የነውር ተግባር አስተማሪ የሆነ ቅጣት የሚያስከትል መሆን አለበት።
    3. ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የሚሠጠው ትኩረት ከዚህ በፊት ከነበረው የተለየና ከወቅቱ የፖለቲካ ትኩሳት የሚጠብቃቸው መሆን እደሚገባው እናምናለን። በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች ባሉ ዩኒቨርስቲ ግቢዎች የተከሠቱ ችግሮች የሕዝባችንን ልብ ሰብረው ያለፉ ክስተቶች ናቸው። ከሁሉም በላይ በደንቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ይማሩ የነበሩ ተማሪዎች ላይ የተደረገው እገታ ውሉ የጠፋና የመንግሥትን የተማሪዎችን ህይወት የመጠበቅ ኃላፊነት አለመወጣት ያጋለጠ ነው። ከዚህ ቀደም መንግሥት ስለለተማሪዎቹ እገታ ወቅቱን የጠበቀ እና ትክክለኛ መረጃ ለተማሪዎቹ ቤተሰቦች እና ለሕዝብ እንዲሰጥ ኢዜማ መጠየቁ ይታወሳል። ሆኖም መንግሥት ትክክለኛ እና ወቅታዊ መረጃ የመስጠት ከፍተኛ ክፍተት ታይቶበታል። ከዚህ አንጻር መንግሥት ተማሪዎቹን ከእገታ የማስለቀቁን ኃላፊነት በአግባቡ እንዲወጣ እና የሕዝብን ልብ እንዲያሳርፍ አበክረን እንጠይቃለን።
    4. በየትኛውም አካባቢ የሚፈጸም ግፍ ለየትኛውም አካባቢ ለሚገኝ ሰላም ጠንቅ ነው” እንዲሉ፥ ለተማሪዎቻችን የመቆም ጉዳይ የአንድ ወገን ወይም የአንድ ክልል ጉዳይ ሊሆን አይገባውም። የሁላችንንም ተናብቦ መሥራት ግድ ይላል። ከዚህ አንጻር የታገቱ ልጆቻችንን በሰላም ለማስለቀቅ ሕግ እና ሥርዓትን በተከተለ መልኩ በሀገራችን በሁሉም አካባቢዎች በሕዝባችን የሚደረጉ ሀቀኛ ጥረቶችን እንደግፋለን።
    5. ሀገርን እና ሕዝብን የማወክ አንድ አካል የሆነው የሞጣ መስጂዶችን የማቃጠል ድርጊት በአጥፊዎቹ ላይ አስተማሪ ርምጃ ተወስዶ ለሕዝብ ይፋ እንዲደረግ፤ መስጂዶቹን አድሶና ምዕመናኑን ክሶ ወደቀድሞው ሰላማዊ አገልግሎት ለመመለስ የሚደረጉትን የአብሮነት እንቅስቃሴዎችን እንደግፋለን።
    6. በቅርቡ የጥምቀት በዓል አከባበር ወቅት በተወሰኑት አካባቢዎች በተለይም በአቦምሳ የከተራ በዓል ሳይከበር የቀረበትን ሁኔታ ታዝበናል። የጥምቀት በዓል ሃይማኖታዊ ይዘቱን ጠብቆ እንዳይከበር እንቅፋት የሆኑ አካላትም ለሕግ እንዲቀርቡና ተገቢ ቅጣት እንዲያገኙ እንጠይቃለን።
    7. ኢዜማ የምርጫ ወረዳዎችን አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች እንደዚሁም ሕዝባዊ ውይይቶች በሚያካሄድበት ጊዜ ጥቂት ሥርዓት አልበኞች የሚፈጥሩት ግርግር ሕዝብን የሚወክል እንዳልሆነ ብንረዳም በአጠቃላይ የፖለቲካ ድባቡ ላይ የሚፈጠረው የስሜት መሻከር ያሳስበናል። በተለይም ወደምርጫ ለመግባት ዝግጅት እያደረግን ነው በሚባልበት በዚህ ወቅት ሕዝቡ ሕገመንግሥታዊ የሆነውን የመሰብሰብ መብቱን መጠቀም የማይችልበት ሁኔታ ይታያል። ባሳለፍነው ሳምንት በተከሠቱ በተለይ የጎንደር እና የሸዋሮቢት ድርጊቶችን ተከታትሎ አጥፊዎችን እንዲቀጣ አቤቱታችንን ለመንግሥት አቅርበናል። ኢዜማ ላይ የሚከሠቱ ችግሮች ሁለት ገጽ አላቸው አንደኛው ከመንግስት መዋቅር የሚመጣ ሲሆን ሁለተኛው ከዚያ ውጭ የሆኑ ሥርዓት አልበኞች የሚፈጥሩት ነው። “ባለጌና ጨዋ በተጣሉ ጊዜ ለጊዜውም ቢሆን ባለጌ ያሸነፈ ይመስላል” የሚል የቆየ የሀገራችን ብሂል አለ። ይህም ጨዋው በሕግ ስለሚያምንና የሕግ አስከባሪ ባለጌውን ይቀጣል፤ ብሎ በማመን ነው። በእኛ መዋቅርም የሚታየው ይሄው ሕግን የማክበር ጉዳይ ነው፤ ይህም ቢሆን ልክ አለው፤ ከገደብ ያለፈ ነውር ሲፈፀም አመራሩም፣ አባሉም፣ ደጋፊውም ራሱን፣ ፓርቲውንና ሀገሩን የመጠበቅ ተፈጥሯዊ መብት አለው። ኢዜማ ሀገርንና ሕዝብን ለድርድር አያቀርብም። ይህንንም ደግመን ደጋግመን ተናግረናል! መንግሥት በራሱ ውስጥም ሆነ ከራሱ ውጭ ያሉትን ሥርዓት አልበኞች በሕግ ሊቀጣ ይገባል። ይህ ካልሆነ ግን ሕዝቡ ራሱን ወደመከላከልና ሰላሙን ወደ ማስጠበቅ ሊገፋ ይችላል። ይህም በየትኛውም መመዘኛ ስህተት ሊሆን አይችልም።

    በመጨረሻም የዴሞክራሲ ግንባታ ሂደቱን መጠበቅ ለሁላችንም የሚጠቅም ሀገር እና ሕዝብን የሚታደግ ብቸኛው መንገድ መሆኑን አውቀን እንድንጓዝበት መልዕክታችንን እያስተላለፍን ሥርዓት አልበኝነትን በጋራ በቃ የምንልበት ጊዜው ዛሬ መሆኑን በአፅንኦት እንገልፃለን።

    ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!
    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
    ጥር 22 ቀን 2012 ዓ.ም
    አዲስ አበባ

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – ሸገር ዳቦና የዳቦ ዱቄት ፋብሪካ ግንባታ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ ወደ ሥራ ሲገባ ከዳቦ ማምረት እስከ ማከፋፈል ድረስ ባለው ሰንሰለት ለ20 ሺ ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤት ገለጸ። ከ400 በላይ ያገለገሉ የአንበሳ የከተማ አውቶብሶች ለዳቦ ማከፋፈያነት እንደሚውሉም ተገልጿል።

    የጽሕፈት ቤቱ የፕሬስ ሴክሬታሪ ኃላፊ ወ/ት ፌቨን ተሾመ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለጹት፥ በሚድሮክ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ግሩፕ አባል በሆነው ሆራይዘን ፕላንቴሽን ኩባንያ አማካኝነት እየተገነባ ያለው ሸገር ዳቦና የዳቦ ዱቄት ፋብሪካ በቅርቡ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ ወደ ሥራ ሲገባ፥ በመዲናዋ የሚስተዋለውን የዳቦና የዱቄት አቅርቦት ችግር መቅረፍ ከማስቻሉ በላይ ከዳቦ ማምረት እስከ ማከፋፈል ድረስ ባለው ሰንሰለት ለ20 ሺ ዜጎች የሥራ ዕድል ይፈጥራል።

    እንደ ኃላፊዋ ማብራሪያ፥ በመዲናዋ የሚስተዋለውን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋትና ማኅበረሰቡ ዳቦ፣ ዘይት፣ ስኳርና ዱቄት የመሳሰሉ ለዕለት ፍጆታ የሚውሉ ምርቶችን ለመግዛት በረጃጅም ሰልፎች ጊዜውን ከማባከኑም በላይ ብዙ ወጪ ያወጣል፡፡ የከተማ አስተዳደሩም ቢያንስ በዳቦ እና ዱቄት ላይ የሚስተዋለውን የዋጋ ንረትና ረጃጅም ሰልፎችን ለመቅረፍ የተለያዩ ባለሀብቶችን ወደ ኢንቨስትመንቱ እንዲገቡ የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገ ይገኛል። በዚህ ድጋፍም ሆራይዘን ፕላንቴሽን ኩባንያ አማካይነት ወደ ግንባታ ገባው የሸገር ዳቦና የዳቦ ዱቄት ፋብሪካ ግንባታ በቅርቡ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ ወደ ሥራ እንደሚገባ ጠቁመዋል።

    ፋብሪካው ወደ ሥራ ሲገባ በሰዓት 80 ሺህ ዳቦ የሚያመርት ሲሆን፣ ምርቱም ዝቅተኛውን የማኅበረሰብ ክፍል ባገናዘበ ዋጋ የሚያከፋፍል ይሆናል። ይህም በከተማው የሚስተዋለውን የዳቦ አቅርቦት ማነስና የዋጋ ንረት ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ከመቅረፉ በላይ፥ ከዳቦ ማምረት እስከ ማከፋፈል ድረስ ባለው ሰንሰለት ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል።

    ለረጅም ጊዜ ከሥራ ውጭ የነበሩ 420 ያገለገሉ አንበሳ የከተማ አውቶብሶችም ለሸገር ዳቦ ማከፋፈያነት ለማዋል የተለያዩ የማስዋብና የማስጌጥ ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን የሚናገሩት ወ/ት ፌቨን፥ በአደጉ አገሮች ተንቀሳቃሽ ሱቆች የተለመዱ መሆኑን ጠቁመዋል። በአውቶቡሶቹ ላይ ወጣቶች ተደራጅተው ዳቦ በማከፋፈል የሥራ ዕድል የሚፈጠርላቸው ሲሆን፥ በ116 ወረዳዎች የዳቦ ማከፋፋያ ማዕከል ሆነው ስለሚያገለግሉ ማኅበረሰቡ በአቅራቢያው ዳቦን በተመጣጣኝ ዋጋ ለመሸመት እንደሚያስችሉ አስገንዝበዋል።

    የሆራይዘን ፕላንቴሽን ኩባንያ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ጀማል አህመድ በበኩላቸው፥ የፋብሪካው የግንባታ ሥራ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቅቆ ማሽኖች ከጣሊያን አገር ተገዝተው ወደ አገር ውስጥ እየገቡ ሲሆን የተወሰኑት ወደ ፕሮጀክቱ ሄደዋል፤ ቀሪዎቹ ደግሞ ሞጆ ደረቅ ወደብና ጅቡቲ ወደብ መድረሳቸውን ተናግረዋል።

    የመዲናዋን ማኅበረሰብ የዳቦ ጥያቄ ለመመለስ ሼህ ሙሀመድ ሁሴን አሊ አል አሙዲ የፕሮጀክቱን ሙሉ ወጪ በመሸፈን እንዲገነባ ማድረጋቸውን ዳይሬክተሩ ጠቁመው፥ በሚቀጥለው ወር የማሽን ተከላ ሥራው ተጠናቆ ወደ ምርት ይገባል።

    በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ በ40 ሺ ካሬ ሜትር ወይም አራት ሄክታር ላይ ያረፈው ሸገር ዳቦና ዱቄት ፋብሪካ እስከ አሁን ለግንባታው ከ900 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉን የሚናገሩት ዳይሬክተሩ፤ በፕሮጀክቱ ሥራ 450 ሰዎች የሥራ ዕድል እንደተፈጠርላቸው ጠቁመዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ሸገር ዳቦና የዳቦ ዱቄት ፋብሪካ

    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለቦች የስታዲየም መገንቢያ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተረከቡ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለቦች የስታዲየም መገንቢያ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ አስረከበ።

    በኢትዮጵያ እግር ኳስ ውስጥ በርካታ ደጋፊዎችን በመያዝና የአዲስ አበባ ከተማ ተወካዮች በመሆን በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ላይ እየሳተፉ ለሚገኙት ለኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለቦች የይዞታ ማረጋገጫ ካርታውን ያስረከቡት የከተማዋ ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማ በንቲ ናቸው። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለሁለቱ ክለቦች ከወራት በፊት የስታድየም እና ሁለገብ የስፖርት ማዕከል መገንቢያ የሚሆኑ የመሬት ይዞታዎችን እንደሚሰጣቸው ቃል ገብቶላቸው ነበር።

    የሁለቱ ክለቦች የቦርድ የሥራ አመራሮች፣ የደጋፊ ማኅበር ተወካዮች፣ የክለቦቹ ደጋፊዎች እና የከተማ  የአስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት በከንቲባው ጽሕፈት ቤት በተካሄደ ሥነ ሥርዓት ላይ ምክትል ከንቲባው ባደረጉት አጠር ያለ ንግግር ሁለቱን ክለቦች መደገፍ እና የከተማዋን አብዛኛውን ወጣቶች ፍላጎት መደገፍ ተገቢ እንደሆነ አስገንዝበዋል። ኢንጂነር ታከለ ኡማ በንቲ እንደገለጹት፥ ሁለቱ ክለቦች የከተማዋ አምባሳደር ከመሆናቸውም ባለፈ በስፖርታዊ ጨዋነት እና በከተማዋ ሁለንተናዊ ሰላምን በማረጋገጥ፣ ወንድማማችነትን በመስበክ የበኩላቸው ሚና እየተወጡ ይገኛሉ ብለዋል። ከዚህ ጋር ተያይዞም ሁለቱ ክለቦች በከተማዋ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች እንዲጎለብት እና ወጣቱ ጊዜውን አልባሌ ስፍራ በመዋል ወይም አልባሌ ሥራ በመሥራት እንዳያሳልፍና እንዲቆጠብ ለሚያርጉት አዎንታዊ ተግባር የከተማ አስተዳደሩ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ኢንጂነር ታከለ ተናግረዋል።

    ‘የከተማው አስተዳደር ከሁለቱ ክለቦች ጋር መሥራት ግዴታው ነው፤ የስታድየም ማስፋፊያ የመሬት ይዞታውን ከመስጠት ባሻገርም ክለቦቹ ለሚያከናውኗቸው ግንባታዎች በመዋዕለ አቅም ለመደገፍም አስተዳደሩ ዝግጁ ነው። ለክለቦቹ ከመሬት ይዞታው በተጨማሪም በአዲስ አበባ ከተማ ስር ከሚገኙ የወጣት ማዕከላት መካከል ሁለት የወጣት ማዕከላትን ለሁለቱ ክለቦች በመስጠት ኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖርት ክለቦች እንዲያስተዳድሯቸው በስጦታ ለመስጠት ዕቅድ አለው” ብለዋል ኢንጂነር ታከለ።

    የኢትዮጵያ ቡና እና የቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ አመራሮችም በበኩላቸው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በተለይ ኢንጂነር ታከለ ኡማ በንቲ ለስታዲየም መገንቢያ የቦታ ይዞታ መረጋገጫ ከመስጠት ጀምሮ ሌሎች አስፈላጊ ድጋፎችን በማድረጉ በደጋፊዎቻቸው እና በእግር ኳስ ክለቦቹ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለቦች


    Semonegna
    Keymaster

    ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ብሔራዊ ምክር ቤት የተሰጠ መግለጫ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ብሔራዊ ምክር ቤት ጥር 16 እና 17 ቀናት 2012 ዓ.ም. 5ኛ መደበኛ ጉባዔውን በማካሄድ የንቅናቄያችንን አጠቃላይ ፓለቲካዊ እንቅስቃሴ፣ የምርጫ ዝግጅት፣ የታሠሩ የአብን አመራሮችና አባለትን፣ የታገቱ አማራ ተማሪዎችን እና በሌሎችም ጉዳዮች ላይ ውይይት በማድረግ ውሳኔ እና አቅጣጫ በማስቀመጥ አጠናቋል።

    በአገራችን ኢትዮጵያ አማራ-ጠል የተሳሳተ ትርክት በፈርጣጭ ብሔርተኞች መቀንቀን ከጀመረ ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ ያሳለፈ ቢሆንም፥ ለሦስት አስርት ዓመታት መዋቅርና ሕግ ሆኖ አማራን እንደ ሕዝብ ለመጨቆን ሥራ ላይ ውሏል። የአማራ ሕዝብ የተገንጣይ ብሔርተኞች የተሳሳተ ትርክት እንዲቆም ብሎም ኢትዮጵያዊያን በሰላምና በአንድነት ተከባብረው እንዲኖሩ ሲታገል ቆይቶ በ2010 ዓ.ም. ለውጥ እንዲመጣ ቢያድርግም ለውጡን እንመራለን እና እናሻግራለን የሚሉት “ተረኛ ነን” ባዮች የቆየውን ትርክት ለማስቀጠል በሚያደርጉት ልፊያ ሕዝባችን በተደጋጋሚ ዋጋ እየከፈለ ይገኛል።

    የአማራ ሕዝብ በሰላምና በመተሳሰብ እሴቱ ከሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝቦች ጋር ተዋዶና ተከባብሮ የኖረ ወደፊትም የሚኖር ሕዝብ መሆኑ በሁሉም ዘንድ የሚታወቅ ሀቅ ሆኖ ሳለ የኢትዮጵያዊያንን የቆየ እሴት የማይወክሉ ብሎም እንቆምለታለን ብለው የሚምሉለትን ሕዝብ ዓላማና ፍላጎት የማያውቁ ተገንጣይ የፖለቲካ ቡድኖች በሚያቀነቅኑት የአማራ-ጠል ትርክትና እንቅስቃሴ የተነሳ የአማራ ሕዝብ ለከፍተኛ ጭቆና ተዳርጎ ቆይቷል። የአማራ ሕዝብ ትግል የኅልውናና ፀረ-ጭቆና መሆኑ የታወቀ ሲሆን፥ ባለፉት ዓመታትም ጭቆናን ሲታገል የነበረው አንደኛው ጨቋኝ በሌላኛው ጨቋኝ እንዲቀየር አልነበረም፤ አይደለምም። ሆኖም ግን “የአማራን ሕዝብ ማኅበራዊ እረፍት መንሳት” የሚለው ትህነጋዊ ትርክት በተረኛ መንግሥት ነን ባይ ቡድኖችና ተቀፅላዎች በመተካቱ ባለፉት ሁለት ዓመታት የአማራ ሕዝብ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰ ነው። በመሆኑም የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ብሔራዊ ምክር ቤት በ5ኛ መደበኛ ጉባዔው በሚከተሉት ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔና አቅጣጫ አስቀምጧል።

    የታገቱ አማራ ተማሪዎችን በተመለከተ፡-

    በደንቢዶሎ ዩንቨርሲቲ ይማሩ የነበሩ አማራ ተማሪዎች ታግተው ከጠፉ ሁለት ወራት አልፈውታል። ይህ የአሸባሪነት ተግባር በአስቸኳይ መፍትሄ እንዲሰጠውና የታገቱ ልጆች እንዲለቀቁ አብን መጠየቁ ይታወሳል። የአማራ ሕዝብ እና ሁሉም ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ይህን ነውረኛ የአሸባሪነት ተግባር አውግዞ መንግሥት ኃላፊነቱን እንዲወጣ በትዕግስት ሲጠይቅ ቆይቷል። የአብን ብሔራዊ ምክር ቤት በዚህ የአሸባሪነት ተግባር የታገቱ አማራ ተማሪዎች በአስቸኳይ እንዲለቀቁ አሸባሪዎችም ተገቢውን ቅጣት እንዲያገኙ መንግሥት ኃላፊነቱን እንዲወጣ እያሳሰበ፤ ለታገቱ አማራ ተማሪዎች ድምፅ ለማሰማት በተለያዩ ከተሞች በአማራ ወጣቶች የተጠራውን ሰልፍ አብን የሚደግፍ መሆኑን ያረጋግጣል።

    ሰላማዊ ሰልፉም ከየትኛውም ጥቃትና ጥፋት ነፃ በሆነ መንገድ በሰላም እንዲጠናቀቅ መንግሥት አስፈላጊውን ጥበቃና ከለላ የማድረግ ኃላፊነቱን በሚገባ እንዲወጣ እናሳስባለን። ከዚህ ጋር በተያያዘ የአማራ “ክልል” መንግሥትና ማዕከላዊ መንግሥቱ ላሳዩት የበዛ ቸልተኝነት ተጠያቂነታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ ድርጊቱን ላልተገባ የፖለቲካ ቁማር ከማዋል ተቆጥበው ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ በጥብቅ እናሳስባለን። መላው የአማራ ሕዝብ ቀጣይ በልጆቹ ዙሪያ መንግሥት የሚሰጠውን ምላሽ እየተከታተለ ለቀጣይ ትግሎችም ራሱን እንዲያዘጋጅ አብን ጥሪውን ያቀርባል።

    የፖለቲካና የኅሊና እስረኛ የሆኑ የአብን አመራርና አባላትን በተመለከተ፡-

    የአማራ “ክልል” ከፍተኛ አመራሮች እና የፌዴራል የጦር መኮንኖች ግድያ ተከትሎ “የክልሉ”ም ሆነ ማዕከላዊ መንግሥት ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው ከመሆኑም በላይ ካላንዳች የፖለቲካ ትርፍ ስሌት ኃቁን በወቅቱ ለሕዝብ ማቅረብ ሲገባቸው፤ በሕዝብ ላይ የደረሰውን አሳዛኝ በደል እንደ ጥሩ አጋጣሚ በመጠቀም ይባስ ብሎ ንጹሃን የንቅናቄያችን አመራሮችና አባሎቻችንን በታሪክ አጋጣሚ መንግሥት የመሆን ዕድል የገጠመው ቡድን ለአማራ ሕዝብ ካለው የተሳሳተ የጥላቻ አመለካከት በመነሳት በግፍ አግቷቸው እንደሚገኝ ይታወቃል። ገዢው መንግሥት የንቅናቄያችንን አመራሮችና አባላት በቂ ባልሆነ ማስረጃ በፖለቲካ አስተሳሰባቸው ብቻ ላለፉት ሰባት ወራት በእስር ላይ አቆይቷቸዋል።

    የአማራን ሕዝብ ሰላምና ደኅንነት ብሎም የአገርን ኅልውና ግምት ውስጥ በማስገባት ያለአግባብ የታሰሩ የአብን አመራሮችና አባላት በውይይት እንዲፈቱ ከ7 ወራት በላይ ኃላፊነት በተሞላበት እጅግ ከፍተኛ ትዕግስት የጠየቅን ከመሆኑም በላይ ጓዶቻችን ያልተገባ መስዋዕትነት እየከፈሉ ይገኛሉ። ይህንንም አስመልክቶ ንቅናቄያችን ለሕዝብና ለመንግሥት በተከታታይ ያሳወቀ ቢሆንም ከመንግሥት በኩል ፍትህ በመነፈጉ ምክንያት ለሕዝባችን በገባነው ቃል መሰረት ቀጣይ የሰላማዊ ትግል አማራጮችን ለመጠቀም ተገደናል። ስለሆነም መንግሥት ያለአግባብ በአፈሳ የፈፀመውን እስር ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ክሳቸው ተቋርጦ በአንድ ወር ውስጥ በአስቸኳይ እንዲፈቱ እያሳሰብን፤ በተቀመጠው ጊዜ የማይፈቱ ከሆነ በየደረጃው ያሉ የንቅናቄያችን አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ሕዝባችንን በማስተባበር እንደሚከተለው በተገለጸው የጊዜ ቅደም ተከተል መሠረት ሁሉንም የሰላማዊ ትግል አማራጮች እንተገብራለን።

      • የካቲት 22/2012 ዓ.ም፡- በተመረጡ የአገሪቱ ከተሞች ሰላማዊ ሰልፍ ይደረጋል፤
      • የካቲት 26 እና 27/2012 ዓ.ም፡- አድማ ይደረጋል፤
      • ከመጋቢት 3/2012 ዓ.ም ጀምሮ አመራሮቻችን እና አባሎቻችን እስከሚፈቱ ድረስ ለተከታታይ ቀናት ሕዝባዊ እምቢተኝነት እንዲካሄድ ምክር ቤቱ በሙሉ ድምፅ የወሰነ ሲሆን ለዚህም ከወዲሁ አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅቶች እንዲጠናቀቁ አቅጣጫ አስቀምጧል።

    ከዩኒቨርሲቲዎች ስለተፈናቀሉ ተማሪዎች፡-

    መንግሥት አገር የመምራት ኃላፊነቱን በአግባቡ ባለመወጣቱ ምክንያት በተለያዩ የአገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎች የሚማሩ ተማሪዎች በሰላም ትምህርታቸውን መከታተል ካለመቻላቸውም በላይ አካላዊ፣ ሥነ ልቦናዊና የሞት አደጋ ገጥሟቸዋል። በመሆኑም በአሁኑ ወቅት በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች የዩኒቨርሰቲ ትምህርታቸውን አቋርጠዋል። ይህ በአማራ ተማሪዎች ላይ የሚፈጸም በደል አማራ ላይ የእውቀት ሽግግር እንዳይኖር ሲደረግ የኖረው መንግሥታዊ ጭቆና መገለጫ መሆኑን አብን ይገነዘባል። ስለዚህ መንግሥት ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት ተማሪዎቹ ደኅንነታቸው በተጠበቀ ሁኔታ ትምህርታቸውን የሚቀጥሉበትን መንገድ በአስቸኳይ እንዲያመቻች አብን ያሳስባል።

    አገራዊ ምርጫን በተመለከተ፡-

    ንቅናቄያችን ያዘጋጀው የምርጫ ማኒፌስቶ ለብሔራዊ ምክር ቤቱ ቀርቦ የተገመገመ ሲሆን ምክር ቤቱም ተጨማሪ ጉዳዮች ተካተውበትና በተለያዩ አካላት ውይይት እንዲደረግበት እንዲሁም ንቅናቄያችን በቅርቡ በሚያካሂደው ጠቅላላ ጉባዔ እንዲፀድቅ አቅጣጫ አስቀምጧል።

    በመጨረሻም በአገር ውስጥም ከአገር ውጭም ያለ መላው የአማራ ሕዝብና አገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ በማንኛውም ቡድን የሚፈጸምን ኢ-ሰብአዊና የአሸባሪነት ተግባር ተባብሮ እንዲያወግዝ ብሎም ለፍትኅ፣ እኩልነትና ነጻነት እንዲሁም የሕግ የበላይነት መረጋጋጥ እንዲታገል ንቅናቄያችን ጥሪውን ያስተላልፋል።

    አማራ በልጆቹ ትግል ታሪኩን ያድሳል!
    የአማራ ብሔራዊ ነቅናቄ (አብን) ብሔራዊ ምክር ቤት፤
    ጥር 17 ቀን 2012 ዓ.ም
    አዲስ አበባ፣ ሸዋ፣ ኢትዮጵያ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ብሔራዊ ምክር ቤት


    Anonymous
    Inactive

    የተሻሻለው የወሎ ቴሪሸሪ የህክምናና የማስተማሪያ ሆስፒታል ዲዛይን ለሕዝብ ይፋ ሆነ

    ደሴ (ወሎ ዩኒቨርሲቲ) – በጥቂት ሀገር ወዳድ ግለሰቦች ሀሳቡ ተጠንስሶ ሀገራዊ የሕዝብ ፕሮጀክት የሆነው የወሎ ልዕለ ህክምና የማስተማሪያ ሆስፒታል /ሦስተኛ ትውልድ ሆስፒታል/ (Wollo Tertiary Care and Teaching Hospital) ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች በየጊዜው እየፈታ ከመጨረሻው ምዕራፍ ላይ ተዳርሷል።

    ይህንን የሕዝብ ፕሮጀክት ነሐሴ 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ያለ በጀትና ዲዛይን በባለቤትነት የተረከበው ወሎ ዩኒቨርሲቲ ወደ ሥራ ለመግባት ከሕዝብ የተሰበሰበውን በጀትና ዲዛይን ሊያስረክብ የሚችል አካል በመጥፋቱ ተቸግሮ ቆይቷል።

    ዩኒቨርሲቲው የሕዝቡ ፍላጎትና ጥያቄዎች እየተበራከቱ ሲመጡበት የዋና ሆስፒታል ዲዛይን መረከብ እስኪችል ድረስ በራሱ ወጭ በ460 ሚሊዮን ብር የተማሪዎች መኖሪያ G+4 10 ህንጻዎችን በመገንባት ላይ ይገኛል።

    የሆስፒታሉን ዲዛይን የተረከበው አማካሪ ድርጅት ሰርቶ ማቅረብ ባለመቻሉ በ2011 ዓ.ም. አጋማሽ ዩኒቨርሲቲው ውለታውን በማቋረጥ ከአዲሱ የኤምቲቲ አማካሪ አርክቴክቶችና ምህንድስና ኃ/የተ/ የግል ኩባንያ (MTT Consulting and Architects and Engineers PLC) ድርጅት ጋር ውለታ በመፈጸም ዲዛይኑን ለአዲሱ ድርጅት አስረክቧል።

    የኤምቲቲ አማካሪ ድርጅት የተረከበው ዲዛይን ከዓለም የቴክኖሎጅ እድገትና ከዘመኑ የኪነ ህንጻ ጥበብ ጋር ሊዛመዱ በማይችሉ የመዋቅር፣ የኤሌክትሮ መካኒክ፣ የፍሳሽ ማስወገጃና መሰል በርካታ ተግዳሮቶች ያሉበት በመሆኑ የዲዛይን ማሻሻያዎችን ሠርቶ ለሕዝብ ይፋ አድርጓል።

    የኤምቲቲ አማካሪ ድርጅት የሆስፒታሉን ዲዛይን ከማሻሻሉም ባሻገር የሆቴል ቱሪዝምን ለማበረታታት ባለ 5 ኮኮብ ሆቴል፣ የባሕላዊ ህክምና መስጭያ ማዕከልና ከአካባቢው ባህልና ሥነ-ምህዳር ጋር የሚዛመዱ ተያያዥ ማዕከላትን የሆስፒታሉ አካል እንድሆኑ በማካተት ይፋ አድርጓል።

    ይህንን ይፋ የሆነ የሆስፒታል ዲዛይን የተመለከቱት የደሴ ከተማ የሕዝብ ተወካዮች፣ የዘርፉ ባለሞያዎች፣ የዩኒቨርሲቲው አመራሮችና ባለሙያዎች በተሻሻለው ዲዛይን ላይ የተሰማቸውን ስሜት በመግለጽ ቢካተቱ ያሏቸውን ጥያቄዎች አቅርበዋል።

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን ዋናውን ሆስፒታል ወደ መሬት ለማውረድ ያጋጠማቸውን ተግዳሮቶች በመጥቀስ ዩኒቨርሲቲው የሕዝብን ስሜት ለመጠበቅ በራሱ የተጓዘውን ርቀት አብራርተዋል። ፕሬዚዳንቱ አያይዘውም ዩኒቨርሲቲው ከሕዝብ የተሰበሰበውን አምስት ሳንቲም እንኳን እንዳልተረከቡ በመግለጽ ፕሮጀክቱን እውን ለማድረግ አማካሪው ኤምቲቲ አማካሪ ድርጅት የሀሳቡ ጠንሳሽ ዶ/ር በላይ አበጋዝን ጨምሮ በጤና ሚኔስተርበአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲበጥቁር አንበሳና በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታሎች ያሉ የዘርፉ ምሁራንን በማሳተፍ ሆስፒታሉ እውን እንድሆን ለተሠራው ሥራ አመስግነዋል።

    የኤምቲቲ አማካሪ ድርጅት በበኩሉ በሕዝብ የተነሱትን ጥያቄዎችና አስተያየቶች በማካተት ፕሮጀክቱ ወደ መሬት በቅርብ ቀን እንዲወርድ የቻለውን ሁሉ እንደሚሠራ ቃል ገብቷል።

    ምንጭ፦ ወሎ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የወሎ ልዕለ ህክምና የማስተማሪያ ሆስፒታል


    Semonegna
    Keymaster

    ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ «ባላገሩ አይድል» በሚል ስያሜ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ይተላለፍ በነበረ የሙዚቃ ዉድድር ከዓመታት በፊት አሸናፊ ነበር። ዉድድሩ ሲጠናቀቅም ለአሸናፊዉ የሙዚቃ አልበም ማዘጋጀት የሽልማቱ አካል ስለነበር፤ በዉድድሩ ዳዊት ፅጌ ያሳየዉ ድንቅ ችሎታ በሙዚቃ አፍቃሪ ኢትዮጵያውያን ዘንድ አልበሙ በጉጉት እንዲጠበቅ አድርጎት ነበር።

    እናም እንደተጠበቀዉ በቅርቡ «የኔ ዜማ» በሚል መጠሪያ የመጀመሪያ የሙዚቃ አልበሙን (debut album) ለአድናቂዎቹ እንካችሁ ብሏል። የአልበሙን መለቀቅ ተከትሎ በኢትዮጵያ ሙዚቃ አድማጮችና አድናቂዎች ዘንድ በብዛት መነጋጋሪያ የሆነው ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ ጥር 17 ቀን 2012 ዓ.ም. ከጀርመኑ የዶይቸ ቬለ ሬድዮ አማርኛ ዝግጅት ክፍል ጋር ቃለ ምልልስ አድርጓል።

    አሥራ አራት የሙዚቃ ሥራዎች የተካተቱበት የድምፃዊ ዳዊት ፅጌ «የኔ ዜማ» አልበም ዉድድሩን ካሸነፈ ከአራት አመታት በኋላ የወጣ በመሆኑ የሙዚቃ አልበሙ ዘግይቷል የሚሉ ብዙዎች ናቸዉ። የዶይቸ ቬለ ጋዜጠኛም ለዳዊት በመጀመሪያ ያነሳችለት ይህንኑ ጥያቄ ነበር።

    በዉድድሩ የተለያዩ አንጋፋና ወጣት ድምፃዉያንን ሙዚቃ ይጫወት ስለነበር የአራት ዓመት ቆይታዉ የራሱን የሙዚቃ ቀለም ፈልጎ ለማግኘት የጣረበት እንደነበርም ድምፃዊዉ ገልጿል። ለዚህም አንጋፋዉ የሙዚቃ ሰዉ አበበ መለሰ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጎለታል።

    በዳዊት ፅጌ «የኔ ዜማ» አልበም የ«ባላገሩ አይድል» አዘጋጅ የነበረውና የእውቁ የሙዚቃ ባለሙያ የአብርሃም ወልዴ አሻራ ያረፈበት ሲሆን፥ «ባላገሩ » ቁጥር አራት በዚህ አልበም ተካቷል። «አስመሪኖ»በሚለዉ ዜማዉ ደግሞ ፀሀይቱ ባራኪን የመሳሰሉ አንጋፋ የኤርትራ ድምፃዉያን ተዘክረዉበታል። (አብርሃም ወልዴ ከተለያዩ ድምጻውያን ጋር በመተባበር “ባላገሩ” በሚል ርዕስ ከዚህ በፊት አራት ሥራዎችን ሠርቷል። የመጀመሪያው ባላገሩ ፩ ድምፃዊ ደሳለኝ መልኩ፣ ሁለተኛው ባላገሩ ፪ ድምፃውያን ኤፍሬም ታምሩ እና ጎሳዬ ተስፋዬ (በኅብረት)፣ ሦስተኛው ባላገሩ ፫ ድምፃዊ መስፍን ዘበርጋ /ጉራጊኛ/ ናቸው።)

    «ባላገሩ አይድል» በሚለዉ የሙዚቃ ዉድድር በነበረዉ ቆይታ በሙዚቃ አፍቃሪዎች ልብ ዉስጥ ትልቅ ቦታ ይዞ የቆየዉ ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ፤ በቅርቡ ያወጣዉ አዲሱ አልበም በአድማጩ ዘንድ ጥሩ ምላሽ እየተቸረዉ መሆኑን በቃለ ምልልሱ ላይ ገልጿል። ከአዲሱ የሙዚቃ አልበሙ ዉስጥም «ልቤ ሰዉ ይወዳል» ለሚለዉ ሙዚቃዉ የተለየ ስሜት አለዉ።

    ከዶይቸ ቬለ ጋር ያደረገውን ቃለ ምልልስ ሙሉውን እዚህ ጋር በማስፈንጠር መስማት ይችላሉ።

    ልቤ ሰው ይወዳል (ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ)

    ልቤ ሰው ይወዳል (2x)
    ልቤ ሰው ይወዳል ወድያው ይላመዳል፣
    የቀረበኝ ሁሉ ወዳጅ ይመስለዋል፤
    ይላመዳል ሰው ያምናል ይወዳል፣
    ይሄ ልቤ ሰው ያምናል ይወዳል፤
    ይመስለዋል ወዳጅ ይመስለዋል፣
    ይሄ ልቤ ሰው ያምናል ይወዳል።

    አይቶ አለመራመድ እግሩን ቢያስነክሰው፣
    በማጣት ቢያሳሹት እንዴት ይድናል ሰው?
    በእሳት ከነደደ አመድ መች ይገዳል?
    ሰው ሁሉ እንደዚህ ነው አጥፊውን ይወዳል። (2x)

    አንዳንዴ እንዲ ነው አንዳንዴ እንዲ ነው፣
    ሰው ወዶ ሰው መጥላት ለካስ ፈተና ነው።
    ጥርስ አልሰንፍ አለ እንጂ ቀድሞ ለመሳቁ፣
    እኔን ባይ አይጠፋም ተገፍተው ስወድቁ።

    ልቤ ሰው ይወዳል ወድያው ይላመዳል፣
    የቀረበኝ ሁሉ ወዳጅ ይመስለዋል፤
    ይላመዳል ሰው ያምናል ይወዳል፣
    ይሄ ልቤ ሰው ያምናል ይወዳል፤
    ይመስለዋል ወዳጅ ይመስለዋል፣
    ይሄ ልቤ ሰው ያምናል ይወዳል።

    ቀን ይዞ ቢጠልቅም ወዳጅ እንደጀንበር፣
    ሰው ጨረቃ አያጣም ባመሸበት ሀገር፤
    ልቤ አይጉደል እንጂ በሰው ያለ ተስፋ፣
    በመጪው ይካሳል በሄደው የከፋ። (2x)፤

    አንዳንዴ እንዲ ነው፥ አንዳንዴ እንዲ ነው፣
    ሰው ወዶ ሰው መጥላት ለካስ ፈተና ነው።
    አንዳንዴ እንዲህ፥ ነው አንዳንዴ፣
    ሰው ወዶ ሰው መጥላት አይለምደውም ሆዴ።

    አረ አይጣል ነው (8x)

    አንዳንዴ እንዲ ነው፥ አንዳንዴ እንዲ ነው፣
    ሰው ወዶ ሰው መጥላት ለካስ ፈተና ነው።

    ደሃ አይጣላ ከውሃ (ድምፃዊ ዳዊት ፅጌ)

    አንዲት ሴት ነበረች የቤት ሠራተኛ፣
    ቀን ስትደክም ውላ ሌሊ’ትን የማት’ተኛ፤
    ኑሮዋ ሆነና የአርባ ቀን ዕድሏ፣
    ልጅ እያጠባች ነው የተለያት ባሏ፤
    ለአንድ ልጇ ስትል በነፃ እየሠራች፣
    ደሞዟን ሳትል ለፍታ ያሳደገች።
    እንደወጣ ቢቀር ያ’ ባሏ ያ’ ጎበዝ፣
    ስትረግም ትኖራለች ያሻገረውን ወንዝ።

    ለራሷ’ምትቀምሰው ’ምትልሰው ሳይኖራት፣
    ምን ልታጠባው ነው የምትወልደው ሲሏት፤
    ልጅ ስህተት አይደለም ከመጣ በኋላ፣
    ብላ ተስፋ ቆርጣ ሄደች ዳግም ጥላ።
    ሀገር ጥላ ጠፍታ ተሰዳ በርቁ፣
    ትኑር ትሙት እንኳን አንዳቸው ሳያውቁ፤
    ስንት ዘመን አልፎ ናፍቃ ብትመለስ፣
    ይኸው ፊት አስነሳት የታቀፈችው ነፍስ።
    ምን አለ ብትተወው የባሏን እሮሮ፣
    ያሻገረውን ወንዝ መርገም በእንጉርጉሮ።
    ወንዙን አለችው ብላ ጠጋ፣
    ለአንተም አለ በጋ!!
    እሷም አለችው ብላ ጠጋ፣
    ለአንተም አለ በጋ!!

    ከሀገር ሀገር ስትዞር ተሸክማ ጓዟን፣
    ስንት አሳር አይታለች ለማሳደግ ልጇን፤
    እረፍት እንኳን ሳታውቅ በነፃ እየሠራች፣
    ወዟን አራግፋ ነው ለፍታ ያሳደገች።

    ታድያ አንድ ቀን ጥዋት ማለዳ ተነስታ፣
    ቅጠል ጠርጋ መጥታ ሳታርፍ እንኳን ላፍታ፤
    ልጇን በአንቀልባ አዝላው ውሃ ልትቀዳ፣
    ከለመደችው ወንዝ መሸት ሲል ወርዳ፤
    ጎንበስ ባለችበት በድካም ስሜቷ፣
    አመለጣት ልጇ አይ እድሏ ሀብቷ፤
    ደራሽ ወሰደባት የት ገባ ጸሎቷ?
    የምትወደው ልጇን ሆነ የውሃ ሽታ!

    ምን ያደርግላታል ብታለቅስ ብትረግመው፣
    ከውሃ ተጣልታ የትም ለማትደርሰው?
    እሷም አለችው ብላ ጠጋ፣
    ለአንተም አለ በጋ!!
    እሷም አለችው ብላ ጠጋ፣
    ለአንተም አለ በጋ!!

    ድሃ አይጣላ ከውሃ! (5x)
    ድሃ ኣኣኣ አይጣላ ከውሃ!! (8x)

    ምንጭ፦ ዶይቸ ቬለ ሬድዮ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዳዊት ፅጌ የኔ ዜማ


    Anonymous
    Inactive

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በሀገራችን ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂን መሠረት ያደረጉ የክፍያ ሥርዓቶችን በማስተዋወቅ ቀዳሚ የሆነው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሀገሪቱ የመጀመሪያ የሆነውን የዲጂታል ማዕከል ከፈተ።

    ይህ የዲጂታል ማዕከል በቀን ከ300 ሺ ሰው በላይ በሚንቀሳቀስበትና ከፍተኛ የደንበኞች ፍሰት ባለበት መገናኛ አካባቢ፣ የባንኩ ህዳሴ ህንፃ ላይ ነው የተከፈተው።

    በዲጂታል ማዕከሉ መክፈቻ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የባንኩ ፕሬዚዳንትና ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ባጫ ጊና እንዳሉት፥ ማዕከሉ ከሃያ በላይ የገንዘብ መክፈያና መቀበያ ማሽን በአንድ ቦታ በማስቀመጥ ደንበኞች በቀላሉ የባንክ አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ታስቦ የተዘጋጀ ነው ብለዋል።

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሀገራችንን የክፍያ ሥርዓት ለማዘመን በሚደረገው ጥረት ፋና ወጊ መሆኑን ገልፀው፥ በተመሳሳይ ሁኔታ ከ16 ዓመታት በፊት የኤቲኤም ማሽንን (ATM) በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ያስተዋወቀውና አገልግሎት ላይ ያዋለው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሆኑም አቶ ባጫ አስታውሰዋል።

    በዲጂታል ማዕከል ውስጥ ከተቀመጡ በርካታ ኤቲኤሞች መካከል ሁለቱ ገንዘብ ገቢና ወጪ ማድረግ እንዲችሉ ተደርገው የተዘጋጁ መሆናቸውን ፕሬዝዳንቱ ገልፀው፣ በቀጣይ ተመሳሳይ ገንዘብ ገቢና ወጪ የሚያደርጉ ከ100 በላይ ተጨማሪ ኤቲኤሞችን በተለያዩ አካባቢዎች የሚቀመጡ መሆኑን አስታውቀዋል።

    ከዚሁ ዜና ጋር በተያያዘ፥ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሚሰጣቸው የባንክ አገልግሎቶች ጥራታቸውን ጠብቀውና የደንበኞችን ፍላጎት አሟልተው እንዲሰጡ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገለጸ። ይህ የተገለጸው ባንኩ የ6 ወራት የዕቅድ አፈጻጸሙን በዝርዝር ገምግሞ በቅርንጫፎች እየተሰጡ ያሉ አገልግሎቶችን ተዘዋውሮ ከተመለከተ በኋላ ነው።

    አቶ ባጫ ጊና የገነተ ጽጌ፣ ቸርችል፤ ፍልዉሃ እና ጥላሁን አባይ ቅርንጫፎችን ከተመለከቱ በኋላ እንደተናገሩት፥ ቅርንጫፎች እየሰጧቸው የሚገኙ የባንክ አግልግሎቶች ቀላል፣ ቀልጣፋና ለደንበኞች ምቾት መስጠት ላይ አተኩረው መሥራት ይገባቸዋል።

    የባንክ አገልግሎት ሁልጊዜም እየዘመነና ድካምን እየቀነሰ መሄዱን ያስታወሱት አቶ ባጫ ጊና፥ ባንኩም በፍጥነት እየተለዋወጠ ከሚሄደው ዓለም ጋር አብሮ የሚራመድ አገልግሎት ማቅረብ ይገባል። ለዚህም ባንኩ ለቅርንጫፎች አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ ለደንበኞቹ የሚመጥን አገልግሎት መስጠት የሚያስችለውን ጥረት እያደረገ እንደሆነ ገልጸዋል።

    ከግማሽ ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ጎን ለጎን በቅርንጫፎች እየተሰጡ የሚገኙ አገልግሎቶችን በአካል ተዘዋውሮ ምልከታ በማድረግና አስፈላጊውን የቁሳቁስና የሰው ኃይል በማሟላትና ስልጠና በመስጠት ክፍተቶችን መሸፈንና አገልግሎቶቹ በጥራት እንዲሰጡ የሚደረገው ጥረት በሁሉም የባንኩ ቅርንጫፎች ተጠናክሮ እንደሚሠራ ከጉብኝታቸው በኋላ ገልጸዋል።

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለአንድ ወር የሚቆይ “የአገልግሎት ጥራት መሻሻል እናመጣለን” በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሄደ የሚገኘው ንቅናቄ ያለበትን ሁኔታ የአመራር ቡድኑ የተመለከተ ሲሆን፥ ከደንበኞች ከተሰጡ አስተያየቶች ለመረዳት እንደተቻለው ባንኩ አገልግሎቶቹን ጥራታቸውን በጠበቀ መልኩ በመስጠት የሚታወቅ በመሆኑ አልፎ አልፎ የሚከሰቱ የጥራት መጓደሎችን በትኩረት ማስተካከል እንደሚገባው ለአመራር ቡድኑ ጠቁመዋል።

    ጥር 15 ቀን 2012 ዓ.ም. የባንኩ ከፍተኛ አመራሮች በተለያዩ ቡድኖች ተከፋፍለው በአዲስ አበባ ከተማ የተለያዩ ቅርንጫፎችን በመመልከት ክፍተት በታየባቸው ቅርንጫፎች ፈጣን ማስተካከያ እንዲያደርጉ አቅጣጫ በመስጠት ነው የዕለቱን ምልከታቸውን ያጠናቀቁት።

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እስካሁን ከ1,560 በላይ በሚሆኑ ቅርንጫፎች፣ ከ23.5 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ደንበኞችን ማፍራት የቻለ ሲሆን፣ ከ3,000 በላይ የገንዘብ መክፈያ ማሽኖች፣ ከአምስት ሚሊዮን በላይ ለኤቲኤም ካርድ ተጠቃሚ ደንበኞች አገልግሎት እየሰጠ ያለ አንጋፋና በሀገሪቱ ትልቁ ባንክ ነው።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ


    Anonymous
    Inactive
    • ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የዩኒቨርሲቲውን የመማር-ማስተማር ሥራ አውከዋል ባላቸው 21 ተማሪዎች ላይ የተለያዩ እርምጃዎችን ወሰደ።
    • ዩኒቨርሲቲው “ንፁህ ትዉልድ እንፍጠር” በሚል መሪ ቃል ደማቅ የኪነ ጥበብ ምሽት አካሂዷል።

    ባሕር ዳር (ሰሞነኛ) – ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የመማር ማስተማር ሥራውን በማወክ በተለዩና ተጨባጭ ማስረጃ በተገኘባቸው 21 ተማሪዎች ላይ እርምጃ መወሰዱን አስታወቀ። በዩኒቨርሲቲው አንዳንድ የትምህርት ክፍሎች ተቋርጦ የነበረው ትምህርት ሙሉ በሙሉ መጀመሩንም ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ዘግቧል።

    የዩኒቨርሲቲው ኢንፎርሜሽን ስትራቴጂክ ኮሙዩኒኬሽን ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዘውዱ እምሩ፥ አራት ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ ከትምህርት መታገዳቸውን እና በ21 ተማሪዎች ላይ ደግሞ ከአንድ ዓመት እገዳ ጀምሮ እርምጃ መወሰዱን ገልጸዋል። ሌሎች ከጉዳዩ ጋር ግንኙነት ያላቸውን አካላት በመለየትና በማጣራት በቀጣይ ተመሳሳይ እርምጃ እንደሚወሰድም ዩኒቨርሲቲው አስታውቋል።

    የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ከመማር-ማስተማር ሥራው ጎን ለጎን ተማሪዎችን በሥነ ምግባር በማነጽ ችግር ፈቺ ሆነው እንዲወጡ ማድረግ እንደሚገባም ዶ/ር ዘውዱ ተናግረዋል።

    ባለፉት ሳምንታት ተማሪዎች በሚያነሷቸው ጥያቄዎች ዙሪያ ተደጋጋሚ ውይይትና ምክክር ቢደረግም ምክንያታዊ ባልሆነ መንገድ በፖሊ፣ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ፣ ፔዳና ይባብ ግቢዎች ትምህርት ተቋርጦ እንደነበር ተዘግቧል።

    ከባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሳንወጣ፥ በዩኒቨርሲቲው ፔዳ ግቢ አዳራሽ “ንፁህ ትዉልድ እንፍጠር” በሚል መሪ ቃል የዩኒቨርሲቲዉ ተማሪዎች፣ አመራሮችና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት ጥር 9 ቀን 2012 ዓ.ም. ደማቅ የኪነ ጥበብ ምሽት ተካሂዷል።

    የኪነ ጥበብ ምሽቱን በንግግር የከፈቱት የዩኒቨርሲቲዉ የዉስጥ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ታደሰ አክሎግ፥ በተማሪዎች አነሳሽነት እና በባህል ማዕከሉ ተባባሪነት ፕሮግራሙ መዘጋጀቱን አመስግነዉ፤ መሰል ዝግጅቶች በሚኖሩበት ጊዜ የዩኒቨርሲቲው ድጋፍ እንደማይለያቸዉ ጠቁመዋል። አክለዉም፥ የዉጭ ሀገራት ተሞክሮዎችን በመጥቀስ መሰል የኪነ ጥበብ ፕሮግራሞች በተማሪዎች ሕይወት ላይ አዎንታዊ ተፅዕኖ ስለሚያሳድሩ መዘውተር አለባቸው ብለዋል።

    በፕሮግራሙ ላይ በክብር እንግድነት ተገኝተዉ ለታዳሚዎች አነቃቂ ንግግር ያደረጉት በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲዉ የሳይኮሎጅ መምህር አቶ ታምሩ ደለለኝ እንደተናገሩት፥ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ሁለት ዋነኛ ችግሮችን ሊያስቡባቸው ይገባል ብለዋል። አንደኛው ስብዕናና ክህሎት በማይገነቡ ጊዜያዊ እርካታ ላይ በሚያተኩሩ ክዋኔዎች ለምሳሌ ቲሸርቶችን እያሳተሙ የቀለም ቀን (Color Day)፣ የሕፃናት ቀን (Baby Day)፣ የውሃ ቀን (Water Day) ወይም ሌሎች የመሳሰሉት ላይ ማተኮር ሲሆን፤ ሌላው እና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ትልቅ ችግር እየሆነ የመጣው ደግሞ ሰክኖ ከመወያየት ይልቅ አለመግባባትና ግጭት በስፋት መከሰት ናቸው። ከአለመግባባት እና ግጭት ጋር በተያያዘም ተማሪዎች በዙሪያቸው ያሉ ሌሎች ተማሪዎችን እንደ ተማሪ እንዲመለከቷቸውና እርስ-በእርስ እንዲተሳሰቡ መክረዋል። አቶ ታምሩ በመቀጠልም ተማሪዎች ትዕግስትና ማስተዋልን አጥብቀዉ በመያዝ የዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው ለሕይወታቸው የሚያስፈልጋቸውን ተጨማሪ ስንቅ የሚያገኙበት እንዲሆን እንዲያደርጉት አሳስበዋል።

    በኪነ ጥበብ ምሽቱ “የንፁህ ትዉልድ እንፍጠር” በጎ ሀሳብ አፍላቂ ተማሪዎች የተሳተፉበት ሲሆን በቀጣይም መሰል ፕሮግራሞች በየ 3 ሳምንቱ እንደሚካሄዱ የዩኒቨርሲቲዉ የተማሪዎች ባህል ማዕከል ኃላፊ ተማሪ ተመስገን ሙሉቀን ተናግረዋል። በኪነ ጥበብ ምሽቱ በርካታ ታዳሚያን የተገኙ ሲሆን፥ በበመርሃ-ግብሩ መደሰታቸዉን ለመረዳት ተችሏል።

    በኪነ ጥበብ ምሽቱ በርካታ የግጥም ሥራዎችን ጨምሮ ‘በቃን’ በሚል ርዕስ የተዘጋጀ አዝናኝና አስተማሪ ጭዉዉት አንዲሁም ‘ከኛ ጓዳ’ የተሰኘ ተከታታይ የኮሜድ ሥራ ቀርቧል።

    ምንጮች፦ ፋና/ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive

    “በአሁኑ ጊዜ የህወሓት አመራሮችና አባላት በመሆናቸው ብቻ ከፌዴራል መንግሥትና ከአዲስ አበባ አስተዳደር የኃላፊነት ቦታዎች እንዲነሱ እየተደረገ ነው። ይህ ተግባር በፍፁም ተቀባይነት የለውም።”

    የህወሓት ማዕከላይ ኮሚቴ መግለጫ

    መቐለ (ህወሓት ማዕከላይ ኮሚቴ) – ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) ውስጥ የተፈጠረው የሃሳብና የመስመር ልዩነት እየሰፋ መጥቶ አሁን ኢህአዴግ በያዘው መስመርና ከነበረው የግንባሩ አደረጃጀት ሥርዓት እና አሠራር ውጭ ጨርሶ እንዲፈርስ በማድረግ በይዘቱ አዲስ ፓርቲ እንዲመሠረት ተደርጓል። ህወሓት ይህ ሕገ-ወጥና ፀረ-ዴሞክራሲ አካሄድ በተደጋጋሚ እንዲታረም፣ የሀገራችንን ህልውና አደጋ ውስጥ በገባበት ወቅት ቅድሚያ ተሰጥቷቸው ሊታዩ በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ እንድናተኩር በፓርቲው ውስጥም ሆነ ለመላው የሃገራችን ሕዝብ በተደጋጋሚ ስንገልፅ ቆይተናል።

    ይሁን እንጂ ይህንን ሊቀበል ወይም ሊሰማ ዝግጁ ያልሆነው አመራር ኢህአዴግን በፀረ- ዴሞክራሲያዊ መንገድ እንዲፈርስ እና ሕዝብ ያልመረጠው አዲስ ፓርቲ ስልጣን ይዞ እንዲቀጥል አድርጓል። ከዚህ በኋላ እንደ ድርጅት የነበረን ብቸኛው አማራጭ በጉዳዩ ላይ ሕዝባችን በተወካዮቹ በኩል ተወያይቶ እንዲወስን፤ ይህንን ተከትሎም በመጀመሪያው አስቸኳይ ጉባዔያችን ላይ ሂደቱንና ሁኔታዎችን በዝርዝር እንዲወስን ማድረግ ነበር። በዚሁ መሠረት ከተፈጠረው አዲስ ፓርቲ ጋር እንደማንወሃድ መወሰኑ ይታወቃል።

    በፓርቲ ደረጃ በያዝነው መስመር እንለያይ እንጂ በሕገ-መንግሥታችን የተቀመጠውን የፌደራል እና የክልል መንግሥት ግዴታና መብት አክብረን እንደምንሄድ በግልፅ አስታውቀናል። በተለይ ደግሞ የኢትዮጵያ ሕዝብ ኢህአዴግን በያዘው ዓላማና ፕሮግራም እስከ ቀጣይ ምርጫ የሰጠውን ኃላፊነት በጥብቅ ሊከበር ይገባል። የኢትዮጵያ ሕዝብ የኢህአዴግ ድርጅቶችን ነው የመረጠው። መንግሥት እንዲመሠርቱም፣ እንዲመሩም ስልጣን የተሰጣቸው እነዚህ ድርጅቶች ናቸው። ከዚህ ውጭ በማን አለብኝነት ሕዝብ ያልመረጠው ሌላ አዲስ ድርጅት ስልጣን እንዲይዝም ሆነ አገር እንዲመራም ማድረግ የሕዝቡን ስልጣን መቀማትና ሕገ-መንግሥቱን መርገጥ ነው። ሀገር እንዲመራ በጋራ ለተሰጠን ኃላፊነት በተወሰኑ ኃይሎች ፍላጎት ሕጋዊ እና ዴሞክራሲያዊ ያልሆኑ ውሳኔዎች ሊወሰኑና ሊተገበሩ አይገባም።

    በአሁኑ ጊዜ የህወሓት አመራሮችና አባላት በመሆናቸው ብቻ ከፌዴራል መንግሥትና ከአዲስ አበባ አስተዳደር የኃላፊነት ቦታዎች እንዲነሱ እየተደረገ ነው። ይህ ተግባር በፍፁም ተቀባይነት የለውም። በመሆኑም ይህ ሆነ ተብሎ እየተፈፀመ ያለው እና ከዚህ ቀደም የተፈፀመ መረን የለቀቀ ተግባር ሊታረም ይገባል። ካልሆነ ግን ይህንን ተከትሎ ለሚፈጠር ሁኔታ ኃላፊነት የሚወስደው ይህ ሕገ-ወጥ ተግባር እየፈፀመ ያለው አካል መሆኑን ግልፅ ሊሆን ይገባል።

    የህወሓት ማዕከላይ ኮሚቴ
    መቐለ

    የህወሓት ማዕከላይ ኮሚቴ


    Semonegna
    Keymaster

    ምርጫ የሚደረግበት የመጨረሻ ቀን ወደፊት ይገለጣል፤ ጊዚያዊ የምርጫ ቅስቀሳ ማድረግ አይቻልም

    አዲስ አበባ (ዶይቸ ቬለ አማርኛ) – ኢትዮጵያ ዉስጥ ምርጫ የሚደረግበት የመጨረሻ ጊዜ ወደፊት ይፋ እንደሚያደርግ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ አስታወቀ። ቦርዱ ነሐሴ 10 ቀን 2012 ዓ.ም.ን ጊያዊ የምርጫ ቀን ማድረጉን በቅርቡ አስታዉቆ ነበር። የቦርዱ ቃል አቀባይ ወ/ት ሶሊያና ሽመልስ ጥር 13 ቀን 2012 ዓ.ም. እንዳስታወቁት ግን የመጨረሻዉ የምርጫ ቀን ከፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችና “የሕብረተሰብ ክፍል” ካሏቸዉ ወገኖች ጋር ቦርዱ ከተወያየ በኋላ ይወሰናል። ቦርዱ ያስቀመጠዉ ጊዜያዊ የምርጫ ቅስቀሳ ጊዜ ሳይጀመር የምረጡኝ ቅስቀሳ በሚያደርጉት ፖለቲካ ፓርቲዎች ላይ ሕጋዊ እርምጃ ለመውሰድ በመመርመር ላይ እንደሆነም የቦርዱ ቃል አቃባይ ወ/ት ሶሊያና ሽመልስ ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የዘንድሮዉ ምርጫና ዝግጅቱ የሚደረግበት ጊዜያዊ የጊዜ ሰሌዳ በቅርቡ ይፋ አድርጓል። በጊዜ ሰሌዳዉ መሠረት ካለዉ ታህሳስ 22 ቀን ጀምሮ የምርጫ ክልል ቢሮዎችን እያደራጀ ነዉ። የቦርዱ የተረጋገጠ ውጤት ማሳወቂያ ጊዜን ነሐሴ 20 ቀን 2012 ዓ.ም. ለማድረግ ጊዚያዊ ቀጠሮ መያዙንም ነው ይፋ የተደረገው የጊዜ ሰሌዳ የሚያለክተው።

    የምርጫ ቦርዱ ጊዜያዊ የጊዜ ሰሌዳን ሕጋዊ እና ትክክለኛ በማለት ስምምነታቸውን የገለጹ የመኖራቸውን ያህል ምርጫዉ በከባዱ የክረምት ወቅት ይደረጋል መባሉ፣ በመንገድ መሠረተ ልማት እና የወንዞች ሙላት ምርጫው ያለ ችግር ስለመከናወኑ ጥርጣሬ የገባቸው እንዳሉም ታይቷል።

    የምርጫ ቦርድ በበኩሉ የመጨረሻ በሚለው የምርጫ ማስፈጸሚያ የጊዜ ሰሌዳ ለማውጣት እየሠራ መሆኑን አስታውቋል። ቀደም ሲል ለመነሻነት ይፋ ያደረገው የጊዜ ሰሌዳ ላይ አስተያየት እያሰባሰበበት ስለመሆኑም ነው የቦርዱ ቃል አቀባይ ወ/ሪት ሶሊያና ሽመልስ ለዶይቸ ቬለ የተናገሩት።

    በኢትዮጵያ በየአምስት ዓመቱ ሀገራዊ ምርጫ መካሔድ እንዳለበት በሕገ መንግሥቱ ተደንግጓል። በዚሁ በሥራ ላይ ያለው ሕገ- መንግሥት ሥራ ላይ ከዋለ ለስድስተኛ ጊዜ ሊካሄድ በጊዜያዊነት የተያዘለት ቀነ-ቀጠሮ ውዝግብ ማስነሳቱ ከሕግ አንጻር እንዴት ይታይ ይሆን?

    በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሕግ መምህሩ ዶ/ር ጌታቸው አሰፋ እንደሚሉት የምርጫ ቦርዱ በሕግ የተሰጠውን ስልጣን ተጠቅሞ ከአሠራሩ ጋር በሚያመቸው መልኩ የጊዜ ሰሌዳ ማዘጋጀት ይችላል በማለት ይናገራሉ። ቦርዱ ሕግን የሚተላለፍ ተግባር እስካልፈጸመ ድረስ በየትኛውም የአየር ጠባይ ውስጥ ቀጠሮውን የመያዝ ስልጣን ቢኖረውም ሁሉን ሊያስማማ ወደ ሚችል የውይይት መድረክ ቢያመራ የተሻለ ውጤት ሊገኝበት እንደሚችል እምነታቸው መሆኑን ያስረዳሉ።

    ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ በጊዜያዊነት ይፋ ያደረገው የየምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ተግባራዊ መደረግ ባልጀመረበት አንዳንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ቅስቀሳ እና ሕዝባዊ ስብሰባዎችን እያደረጉ መሆናቸው ቦርዱ የፖለቲካ ፓርቲዎቹን በሕግ ማዕቀፍ ውስጥ እንዲንቀሳቀሱ ተገቢውን ቁጥጥር አላደረገም የሚል ወቀሳ እና ትችት ሲሰነዘር ይሰማል።

    የምርጫ ቦርድ ቃል አቃባይ ወ/ሪት ሶሊያና ሽመልስ እንደሚሉት የፖለቲካ ፓርቲዎች ከተሰጣቸው ሕጋዊ የመንቀሳቀሻ መንገድ ወጥተው በሚገኙት ላይ ሕጋዊ እርምጃ ለመውሰድ በቅድሚያ ተፈጸሙ የተባሉ የሕግ ጥሰቶች መመርመር አለበት ይላሉ።

    የፖለቲካ ፓርቲዎች ከተዘጋጀላቸው የሕግ ማዕቀፍ ወጥተው ሲገኙ ይህንኑ ለማስተዳደር በወጣው ሕግ ሊዳኙ እንደሚገባ የሚያሳስቡት ደግሞ ዶ/ር ጌታቸው አሰፋ ናቸው። ከሰሞኑ ጀምሮ አንዳንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሚያደርጌቸው ጊዜያቸውን ያልጠበቁ የምርጫ ቅስቀሳዎች ወይም የቅስቀሳ ይዘት ያላቸው ሕዝባዊ ስብሰባዎች ሕጋዊ መንገድን ሊከተሉ እንደሚገባም ነው የሚያሳስቡት።

    የብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የ2012 ምርጫ ቀነ-ቀጠሮን ቁርጥ ባያደርግም የአዳዲስ ተወዳዳሪ ፓርቲዎችን ግን መመዝገቡን ቀጥሏል። ቦርዱ ጥር 13 ቀን 2012 ዓ.ም. እንዳስታወቀው ለአራት ፓርቲዎች የእውቅና ምስክር ወረቀትና ጊዜያዊ የምዝገባ ፈቃድ ሰጥቷል። የእውቅና ምስክር ወረቀትና ጊዜያዊ የምዝገባ ፈቃድ የተሰጣቸው አራቱ ፓርቲዎች ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ፣ አንድ ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ አማራ ጊዮናዊ ንቅናቄ እና እናት ፓርቲ ናቸው።

    ምንጭ፦ ዶይቸ ቬለ አማርኛ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ምርጫ የሚደረግበት የመጨረሻ ጊዜ

    Anonymous
    Inactive

    የጋሞ ሽማግሌዎች (የጋሞ አባቶች) መንግሥት ኖረም አልኖረ በአካባቢያቸው ላይ፤ በተለይም በገዛ ልጆቻቸው የማንም ሌላ ኢትዮጵያውን ሕይወትም ሆነ ንብረት እንደማይወድም ተንበርክከው፤ ግን ደግሞ በመንፈስ ልዕልና ከፍ ብለው አሳይተውናል።

    ታላቅ ክብር ለጋሞ ሽማግሌዎች ይሁን!
    (ያሬድ ኃይለማርያም)

    ለእውነት የቆሙ ሽማግሌዎች እጦት፣ በካድሬ እና በመንጋ ፖለቲከኛ ክፉኛ ለተመታችው አገሬ የጋሞ ሽማግሌዎች (የጋሞ አባቶች) ፍቱን መድኃኒት ናቸው። እንደ ጋሞ ሽማግሌዎች ዓይነት ቅን አሳቢ፣ የፍቅር መምህር፣ የተግባር ሰው፣ ደፋር እና ዝቅ ብለው የከፍታን ውሃ ልክ የሚያሳዩ ሽማግሌዎች ከየማህበረሰቡ ቢገኙ ከገባንበት ቅርቃር በቀላሉ ለመውጣት ዕድል ይኖረን ነበረ። በሽማግሌ እና በካድሬ መካከል ያለውን ልዩነት መለየት ያልቻሉ ቀሳውስት፣ ሼኾች፣ አባገዳዎች፣ ፓስተሮች፣ መንፈሳዊ አባቶች ኮሽ ባለ ቁጥር አበል እየተከፈላቸው በየሆቴሉ ሲማማሉ እና በሕዝብ ስም እነሱ ሲታረቁ ቢውሉም መሬት ላይ ጠብ ያለ ነገር የለም።

    የአገራችን ችግር ቅን አሳቢ እና ለእውነት የወገነ፣ ያመነበትን በትክክል የሚናገር፣ ክፉን የሚያወግዝን እና ጥሩውን የሚያበረታታ እውነተኛ ሽማግሌ፣ ደፋር ምሁር፣ ሃቀኛ ፖለቲከኛ፣ ሚዛናዊ ጋዜጠኛ እና መሰሪ ያልሆነ የአገር መሪ ይፈልጋል። ለጋሞ ሽማግሌዎች እና ሽማግሌዎቹንም ለሚያከብሩት የጋሞ ወጣቶች ትልቅ ክብር አለኝ። ጥሩ ምሳሌም ሊሆኑ ይችላሉ።

    የአማራ ሽማግሌዎች ከወዴት አላችሁ? የትግራይ ሽማግሌዎች ከወዴት አላችሁ? የኦሮሞ ሽማግሌዎች እና አባገዳዎች ከወዴት አላችሁ? እነዚህን ክልሎች በተለየ ሁኔታ የምጠራው ሦስቱም ክልል ውስጥ ያለው እሳት አገሪቱን ወደ ከፋ ሁኔታ እየገፋት ያለ ስለመሰለኝ ነው። በማኅበረሰብ ውስጥ ግጭት ሲፈጠር፣ ዜጎች በጠራራ ፀሀይ ሲታረዱ፣ እናት ከነልጆቿ ከቅዮዋ ተፈናቅላ ዱር ስታድር፣ ሕጻናት በነፍሰ በላዎች ታፍነው ገሚሱ ሲገደሉ፣ የዩንቨርሲቲ ሴት ተማሪዎች በወሮበላ ታጣቂዎች ታፍነው ሲወሰዱ የመንግስት ክርን ቢዝል እናንተ የአገር ሽማግሌዎች የት ገባችሁ?

    የጋሞ ሽማግሌዎች (የጋሞ አባቶች) መንግሥት ኖረም አልኖረ በአካባቢያቸው ላይ፤ በተለይም በገዛ ልጆቻቸው የማንም ሌላ ኢትዮጵያውን ሕይወትም ሆነ ንብረት እንደማይወድም ተንበርክከው፤ ግን ደግሞ በመንፈስ ልዕልና ከፍ ብለው አሳይተውናል። ከዛም አልፈው ይህን ትልቅ የሽምግልና እና የፍቅር መንፈስ ይዘው ከአንድ አገሪቱ ጫፍ ወድ ሌላው ጫፍ ተጉዘዋል። መንፈሳችሁ በሌሎች ሽማግሌዎች ይደር!!

    ክብር ለጋሞ ሽማግሌዎች ይሁን!
    (ያሬድ ኃይለማርያም)

    ከጋሞ ኢትዮጵያውያን ጋር በተያያዘ የጋሞ አባቶች እና ወጣቶች ጥር 14 ቀን 2012 ዓ.ም. “የሰላም ጉዞ” በሚል መርህ ከአርባ ምንጭ በመነሳት የተለያዩ ከተሞችን በማቋረጥ መዳረሻቸውን ጎንደር ከታማ እና የጥምቀት በዓልን አድርገው መጓዛቸውንበዚህ ሳምንት ተዘግቧል።

    በጉዞው የጋሞ አባቶች የአካባቢያቸውን ሰላም እንዴት እንዳስጠበቁ ተሞክሮዎቻቸውን ለሌሎች እንዳካፈሉ እና የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሰላም ተምሳሌትነትም ለሌሎች የመንግስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በተሞክሮነት አሳይተዋል። አባቶች በጉዞው የተለያዩ ከተሞችን ያቋረጡ ሲሆን፥ በጉዟቸው መሃል ባረፉባቸው ከተሞችም ስለ ሰላም እና አንድነት ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር ምክክር አድርገዋል። እንዲሁም ተማሪዎችን ስለአቃፊነት፣ ስለ ሰላምና አንድነት እንደመከሩም የጋሞ ዞን ኮሙዩኒኬሽን መምሪያ መረጃ ሰጥቶ ነበር።

    የሰላም ዦቹ የጋሞ አባቶች እና ወጣቶች በአዲስ አበባ በብሔራዊ ቤተ መንግሥት ተገኝተው የአንድነት ፓርክን የጎበኙ ሲሆን፥ የጉዞው መዳረሻ በሆነችው ታሪካዊቷ የጎንደር ከተማም ከከተራ በዓል ጀምረው እስከ ጥር 14 ቀን 2012 ዓ.ም. ለአራት ቀናት እንደሚቆዩ ተዘግቧል።

    የአብሮነትና የሰላም ጉዞውን ኅብረ መንጎል ሚዲያና ኦሞቲክ ጀኔራል ጠቅላላ ንግድ ድርጅት በጋራ ያዘጋጁት ሲሆን፥ የጉዞውን አላማ በመደገፍ የሰላም ሚኒስቴር፣ የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ እንዲሁም የደቡብ ክልል ሰላም እና ፀጥታ ቢሮዎች ለአዘጋጆች የድጋፍ ደብዳቤ ሰጥተዋቸዋል።

    ምንጮች፦ ያሬድ ኃይለማርያም እና ፋና ብሮድካስቲንግ

    የጋሞ አባቶች

Viewing 15 results - 316 through 330 (of 730 total)