Search Results for 'አብይ-አህመድ'

Home Forums Search Search Results for 'አብይ-አህመድ'

Viewing 9 results - 1 through 9 (of 9 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    በፊትም፣ አሁንም እስትንፋሷ በመሪዋ ላይ ብቻ የሆነባት ሀገር
    (ጋዜጠኛ መላኩ ብርሀኑ)

    እንደአለመታደል ሆኖ የዚህች ሀገር ሰላምና ደህንነት ተጠቃሎ በመሪዎቿ በሰላም ውሎ በሰላም የማደር መዳፍ ውስጥ የገባው ዛሬ አይደለም።

    እንኳን በሰላም ጊዜ ሀገርን መምራት ቀርቶ በጦርነት የማሸነፍና ወጥሮ የመዋጋት ነገር እንኳን የንጉሡን በህይወት መኖር የሚታከክ ነገር ነበር – እዚህ ሀገር። እልፍ ሆኖ ተሰልፎ ድል በእጁ መግባቱን እንኳን እያወቀ ንጉሡ ከተመታ ጦሩ በቀላሉ ይፈታል። ሕዝቡ ንጉሡ ከሌሉ ሀገር የለም እየተባለ ሲሰበክ ነው የኖረው።

    እናቶች ንጉሥ ከሌለ የሚመጣውን መአትና እልቂት በመፍራት ለንጉሡ ረጅም ዕድሜ ከመመኘት በላይ “ከንጉሡ በፊት እኔን አስቀድመኝ” ብለው ይጸልዩም ነበር። ምኒልክ ሲሞቱ የሞታቸው ዜና ለሕዝብ ሳይነገር ስንት ዓመት ፈጀ? መልሱ ይኸው ነው። አጼ ኃይለሥላሴ አንድ ነገር ቢሆኑ ሀገር ያበቃላታል ብለው የሚያምኑ ኢትዮጵያውያን ደርግ በቮልስዋገን ከቤተ መንግሥት ይዟቸው ሲወጣ ሲያዩ ነው ወደሩሃቸው የተመለሱት።

    መንግሥቱ ኃይለማርያም በተራው በኢህአፓ የመግደል ሙከራ ሲደረግበት “ሞተ” ተብሎ አብዮቱ የእልቂት እንዳይሆን (ላይቀርለት ነገር) አደባባይ ወጥቶ ነው እግሩን እጥፍ ዘርጋ እያደረገ ነው “አለሁ” ያለው። መለስ ዜናዊ ሞተ ሲባልም በርካቶች በዚሁ “ሀገር ያበቃላታል” ፍርሃት ውስጥ ነበሩ። እነበረከት አደባባይ ወጥተው “ታጋይ ያልፋል ሀገር ይቀጥላል” ዓይነት ነገር ተናግረው ስጋት ቀንሰዋል።

    የዛሬው መሪ አብይ አህመድ ጉዳይ ግን ከነገሥታቱ በኋላ ካሉት መሪዎች ሁሉ በብዙ ይለያል። ጊዜው ጥቂት ቢሆንም ቅሉ ሃሳቡንና አመራሩን ተቋማዊ ማድረግና ግለሰባዊ ተጽዕኖውን በጥቂቱም ቢሆን ለመቀነስ አልቻለም። ስለዚህ አብይ ተወደደም ተጠላ አሁን ባለው አስተዳደር ውስጥ ብቸኛና መተኪያ የሌለው መሪ ነው።

    አብይ አህመድ እና ጓዶቹ ሲሠሩለት እና ሲያስተዳድራቸው የኖረውን ኢህአዴግ የተባለ ተቋም ከውጭ በነበረ ተቃውሞ ታግዘው ከውስጥ በመፈርከስ ቀንብሩን ከላያቸው ገርስሰው የጣሉ የግለሰቦች ስብስብ እንጂ የተደራጀ ተቋም አልነበሩም። የለውጡ መሪዎች ናቸው የተባሉ ሰዎች በመሃል እየተንጠባጠቡ አብይ ብቻ ሲቀር፣ ቀርቶም ብዙዎች ያደነቁትን ለውጥ እያመጣ ሲቀጥል ብቻውን ገንኖ ወጣ።

    አብይ ከመጣበት ማኅበራዊ መሠረቱ አካባቢ የገጠመው ተግዳሮት አሁን ድረስ በብርቱ ቢገርመኝም በሰሜን አካባቢ ካሉ ሰዎች ዘንድ የተጠላ ሰው መሆኑ ግን አይደንቀኝም። በካልቾ ብሎ ከወንበራቸው ላይ ያባረራቸው ሰዎችና “ገዢነት ካለኛ ለማን!?” ያሉ ጀሌዎቻቸው ሊወዱት አይጠበቅም። ይህም ከዚያ ሰፈር በአብይ ጥላቻ ሳቢያ ሀገር እንድትበተን የሚሠሩና የሚመኙ ድኩማን እንዲፈለፈሉ ምክንያት ሆኗል። መተከል ላይ እየሆነ ባለው “መሪና አቀነባባሪ” ብለው እሱ ላይ ጥርስ የነከሱበት፣ “ወለጋ ላይ ቢገኝ እኔን አያርገኝ” ያሉ የበረከቱበት፣ በመጋቢት መጥቶ በሰኔ ሞቱ የተደገሰለት ሰው ነው አብይ።

    ሰውየው የሀገሪቱን ፖለቲካ ብቻውን እየዘወረ፣ በዚህም በዚያም ሁሉን ነገር ብቻውን እየሠራ፣ አውቆም ይሁን ሳይታወቀው ያለምንም ቀሪ ብቻውን የቆመ፣ የማይካፈል ቁጥር ሆኖ ወጣ። ዛሬ በሰሜን ለተፈጠረውም፣ በደቡብ ላለውም፣ በመሃል ለሆነውም፣ በምዕራብ ለተከሰተውም ችግር ሁሉ ተጠያቂው አብይ ነው የሚል አቋም ባላቸው በርካታ አካላት ሲሰደብ ውሎ የሚያድረው ሰውዬ ወዲህ ጦር እያዘዘ፣ ወዲህ ሀገርና ከተማ እየለወጠ ብቻውን ሲሠራ አጠገቡ የሚተካው ቀርቶ የሚመስለው እንኳን አለማየታችን ፈሪ አድርጎናል።

    [ሰሞኑን] አብይ [ሞተ/ታመመ] ምናምን ሲባል ድንጋጤው የበረታው ከርሱ ሞትም በላይ ነገ ሊሆን የሚችለውን እያሰበ ሁሉም ሰላምና ደህንነቱ ስላስጨነቀው ነው፤ ይህ አለመታደል ነው።

    በግሌ ኢትዮጵያን በከረጢት ውስጥ እንዳለ የተፈጨ ዱቄት፣ አብይን ደግሞ ከረጢቱን የዝቅዝቆሽ አዝሎ ጫፉን በእጁ ጨምድዶ እንደያዘው ተሸካሚ ዓይነት ነው የምመስላቸው። የከረጢቱ ጫፍ ከተለቀቀ ዱቄቱ ከአፈር ይደባለቃል። ይሄ ነው የሚያስፈራኝ።

    አብይን በብዙ የማደንቀው መሪ ቢሆንም በዚህ “the one and only” አካሄዱ ግን ቅሬታ አለኝ። ስለዚህ የእርሱን ደህንነት አጥብቄ የምመኘው በግል ለርሱ ባለኝ ጥሩ ስሜት እና ከፍ ያለ አድናቆት ብቻ ሳይሆን በዋናነት ለዚህች ሀገር ሰላምና መረጋጋት፣ ሲቀጥል ለሕዝቡ በሰላም ወጥቶ በሰላም መግባት፣ ጠበብ ሲል ለቤተሰቤ ደህንንት፣ በጣም ሲጠብ ለራሴ ደህና ወጥቶ ደህና መግባት ብዬ ነው።

    ሰሜኑ አቅሙ ከነሞራሉ ቢደቅቅም ቂሙ ግን ከምንጊዜውም በላይ ጠንኖ ሀገር ብትፈርስ ደስ እንደሚለው በአደባባይ በሚናገርበት፣ ምዕራቡ በፈሪ ዱላ ጫካ ለጫካ እየተሯሯጠ የተሸከመውን መሣሪያ አፍ እያስከፈተ ንጹኃንን በሚረፈርፍበት፣ ከውጭ ግብጽና ሱዳን ቤንዚን በጀሪካን ይዘው እሳታችን ላይ ለመድፋት አጋጣሚ በሚቋምጡበት፣ ብቻ በየትኛውም መስመር ለዚህች ሀገር መልካም የሚመኝ በታጣበት በዚህ ጊዜ አብይ አንድ ነገር ቢሆን ስርዓት ሲናድና ነገር እንዳልነበር ሲሆን ሰዓት የሚፈጅበት አይመስለኝም። ሌሊት እንኳን ቢሆን በርህን ለመስበር እስኪነጋና ከእንቅልፍህ እስክትነቃ እንኳን የሚጠብቅህ የለም!

    በበኩሌ በመሪ ደህንንት ላይ የተንጠለጠለች ሀገር ይዘን ዛሬ ድረስ መኖራችንን ስታዘብ ያለመታደል እለዋለሁ።

    ሰውየውን መደገፍና መቃወም ሌላ ነገር ሆኖ የማንክደው ሃቅ ግን አሁንም ሰላማችን በዚህ ሰው ደህና መሆንና አለመሆን የተወሰነ ሆኖ መዝለቁ ነው። ስለዚህ የተወራበት እንኳን ሀሰት ሆነ! አሹ! ብያለሁ። እንደሰው ሳስብ ደግሞ አብይን ሞት ቀርቶ ጭረት እንዲነካው አልመኝም። [እርሱም ቢሆን] እንደማናችንም የሰላም እንቅልፍ ተኝቶ ማደር አይጠላም። ሀገር ብሎ መሰለኝ የጋለ ምጣድ ላይ የተቀመጠው።

    በግሌ ግን መንግሥት ይሁን አስተዳደር ተቋማዊ ሆነው “ሰዎች ያልፋሉ፣ ሀገር ግን ትቀጥላለች” የምንልበትን ዘመን እናፍቃለሁ።

    ጋዜጠኛ መላኩ ብርሀኑ

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    እስትንፋሷ በመሪዋ ላይ ብቻ የሆነባት ሀገር

    Anonymous
    Inactive

    ተመራቂዎች ለኢትዮጵያ አንድነትና ብልጽግና እንዲሰሩ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሳሰቡ
    —–

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ተመራቂዎች ከፊታቸው ውጣ ውረድ ያለበት ሕይወት ስለሚጠብቃቸው በትጋት ለመወጣት ጥረታቸው ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ተናገሩ።

    አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በቅድመ ምረቃ እና በድህረ ምረቃ በቀን፣ በማታ፣ በርቀት እና በክረምት መርሃ ግብር ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የቆዩ 9,637 ተማሪዎችን ሐምሌ 6 ቀን 2011 ዓ.ም. የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር)፣ ከፍተኛ የመንግስት ባስልጣናት፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ጣሰው ወልደሃና፣ የዩኒቨርሲቲው አመራሮችና ሙሁራን በተገኙበት በከፍተኛ ድምቀት በሚሊኒየም አዳራሽ አስመርቋል።

    ከተመረቁት 9,637 ተማሪዎች ውስጥ በቅድመ ምረቃ 5,876፣ በድህረ ምረቃ 3,761 ሲሆኑ ከእነዚህም ውስጥ 2,763 ሴቶች ናቸው።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ምንም እንኳን በቀጣይ የሚጠብቃቸውና መውደቅና መመረቅ ያሉባቸው ሰፊ ትምህርት ቤቶች ቢኖሩም የዛሬውን መመረቅ ልዩ የሚያደርገው የዛሬ ተመራቂዎች ለቀጣይ ሕይወታቸው ስንቅ ይዘው በብዛትና በአንድነት የሚመረቁበት ዕለት መሆኑ ነው። በቀጣይ የሚጠብቃቸውም የትዳር ዩኒቨርሲቲ፣ የሥራና የሕይወት ዩኒቨርሲቲ ከባድ ፈተና በታላቅ ስብዕና ለማለፍ እንዲሁም በሕይወት የሚገጥማቸውን ችግሮች በጽናት ለመወጣት ጥረትና ትጋት ያስፈልጋቸዋል ብለዋል።

    ”የሕይወት ፈተናን ተጋፍጣችሁ ሌላውን ሕይወት በብቃት ለመወጣት ማንበብና እራስን ማብቃት ወሳኝ ነውም” ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ።

    በተለይ በዩንቨርሲቲ ሕይወት ያገኙትንና ያዳበሩትን አብሮ የመኖር ባህል ለትውልድ በማስተላለፍ የተሻለች ኢትዮጰያን ለመመስረት ጥረት ማድረግ እንደሚጠበቅባቸውም አሳስበዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።

    በተለይም ለሰው ልጅ ለመማር ወይም ለመላቅ ብዙ ገፊ ምክንያቶች እንዳሉት ያወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ከእነዚህ ሁሉ ምክንያቶች ሕይወትን በትርጉም ለመምራት የሚያስችሉና ማፍቀር፣ መስጠት እንዲሁም ማገልገል ትልቁ መርህ አድርጋችሁ አገራችሁን አገልግሉ ብለዋል።

    በመስጠትና በማገልገል መርህም በዘንድሮው ክረምት ብቻ በአዲስ አበባ ከ400 በላይ ትምህርት ቤቶች፣ ከ10 በላይ ሆስፒታሎች እና ከ1000 በላይ የአቅመ ደካሞች መኖሪያ ቤቶች የማደስ ሥራ እየተሠራ መሆኑን ያወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በአዲስ አበባ የመንግስት ትምህርት ቤቶች ለሚማሩት ከ600 ሺህ በላይ ተማሪዎች የደብተርና ዩኒፎርም ስጦታ መዘጋጀቱንም አውስቷል።

    አገሪቷ በችግኝ ተከላ ዘመቻ ላይ መሆኗን ያወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ “ስንኖር ኢትዮጵያዊ ለመሆን የምንችለው አረንጓዴ ኢትዮጵያን መፍጠር ከቻልን ነው፤ ስንሞት ኢትዮጵያም መሆን የምንችለው ቢያንስ በለምለምና በጥላ ስር ዘላለማዊ እረፍት ማድረግ ስንችል ነው” በማለት ተማሪዎቹ ጠንክረው እንዲሠሩ አሳስበዋል።

    ሳይማር ያስተማረውን ህብረተሰብ በማገልገል፣ አርሶ አደሩን ከሞፈርና ከቀንበር የማላቀቅ፣ የጽናትንና የማገልገል ልምድ ዛሬ መጀመር ማድረግ እንዳለባቸውም ጠቁመዋል። ዜጎች ሳይቸገሩ በሁሉም ቦታ ተንቀሳቅሰው እንዲኖሩና ለኢትዮጵያ ጽናትና ብልጽግና እንዲሠሩም ጠይቀዋል። ትምህርት መነሻ እንጂ መድረሻ አይደለም የሚሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ እውቀታቸውን ለማሻሻል ጥረት ማድረግ እንዳለባቸውም አመልክተዋል። ተመራቂዎች አባቶች ያቆዩዋትን ኢትዮጵያ ጉዳይ ለክርክርና ለድርድር እንዳያቀርቡም አክለው አሳስበዋል።

    በዘንድሮው የምረቃ በዓል ላይ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሁለት የክብር ዶክትሬቶችን፥ ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገብረማርያም እና ለኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ካውንስል ኃላፊ እና የዑለማ ኃላፊ ሀጂ ሙፍቲ ሼክ ዑመር እድሪስ ሰጥቷል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)/ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    Semonegna
    Keymaster

    ቀዳማዊ እመቤት ዝናሽ ታያቸው ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድና ከሌሎች የሥራ ኃላፊዎች ጋር በመሆን የመቄዶንያ የአረጋውያንና አእምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከልን ከጎበኙ በኋላ የ15 ዘመናዊ ባለሞተር ዊልቸሮችን ድጋፍ አድርገዋል።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታየቸው ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአእምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል የአካል ጉዳተኞች መንቀሳቀሻ ወንበር (ዊልቸር/wheelchair) ድጋፍ አደረጉ።

    ቀዳማዊ እመቤቷ የ2011 ዓ.ም አዲስ ዓመትን ምክንያት በማድረግ በማዕከሉ ለሚገኙ አረጋውያንና የአእምሮ ህሙማን የምሳ ግብዣ ባደረጉበት ወቅት ባለቤታቸው ጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ማዕከሉን እንደሚጎበኙ ቃል መግባታቸው ይታወሳል።

    በመሆኑም ቀዳማዊ እመቤት ዝናሽ ታያቸው ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድና ከሌሎች የሥራ ኃላፊዎች ጋር በመሆን ማዕከሉን ከጎበኙ በኋላ የ15 ዘመናዊ ባለሞተር ዊልቸሮችን ድጋፍ አድርገዋል። ድጋፉ የሚውለውም በማዕከሉ በከፋ የእንቅስቃሴ እክል ውስጥ ለሚገኙ አረጋውያንና የአእምሮ ህሙማን መሆኑ ተገልጿል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በችግር ውስጥ ያሉ ኢትዮጵያውያን በራሳቸው ወገን ሲደገፉ ማየት ጥልቅ ሞራልና ተስፋ እንደሚሰጥ ገልጸዋል። እውነተኛው አክሊል የሚገኘውም እንደዚህ ዓይነቱን ተግባር በመፈጸም ነው ሲሉም አሳስበዋል።

    “መናገር የማይችሉ እራሳቸውን መቆጣጠር የማይችሉ ሰዎችን የሚያየን ያየናል ብለው በንጹህ ልቦና ማገልገል መታደል ነው። እውነተኛው አክሊል የሚገኘው ከእንደዚህ አይነት ስፍራ ነው።እውነተኛውን የሚሹ ሰዎች ዝቅ ብለው መደገፍ የሚገባቸውን ሲደግፉ ሲያግዙ ማየት በኢትዮጵያ እንደዚህም አይነት ስራ የሚሰሩ ግለሰቦችን ማየት ጥልቅ ሞራል ተስፋ የሚሰጥ ነው።” በማለት ተናግረዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።

    የኢትዮጵያ ሕዝብ ደግና ሩህሩህ በመሆኑ ማዕከሉን በቀጣይነት እንደሚደግፍ እምነት እንዳላቸው የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ፥ እርሳቸውም በተቻላቸው አቅም በማዕከሉ ያሉ አረጋውያንንና የአእምሮ ህሙማንን ለመጎብኘት ቃል ገብተዋል።

    “እኔ ልነግራችሁ የምፈልገው ነገር የኢትዮጵያ ሕዝብ ደግ ህዝብ ነው። የማየት እድል ካገኘ ይህን የተቀደሰ ዓላማና ተግባር በመደገፍ ከጎናችሁ ሆኖ አልባሌ ቦታ የሚባክን ጉልበትና ሃብት ሰብስቦ እናንተን በማገዝ ከጎናችሁ በመሆን ቤተሰብ መሆኑን እንደሚያረጋግጥ ሙሉ እምነት አለኝ ፤እኔም አቅሜ በፈቀደ መጠን እናንተን በመጎብኘት ከጎናችሁ እንደምሆን ላረጋግጥላችሁ እፈልጋለሁ።” ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ

    የማዕከሉ መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ ብንያም በለጠ በበኩላቸው ኢትዮጵያውያን በተለይም ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች የጠቅላይ ሚንስትሩን አርአያ በመከተል በማዕከሉ የሚገኙ ወገኖቻቸውን እንድጎበኙ ጥሪ አቅርቧል።

    ለመልካም ሥራ ጊዜ መስጠት እንደሚያስፈልግ በመጠቆም አቶ ብንያም፥ “የዶክተር አብይን አርአያ ተከትለን ዛሬ መጥተው በመጎብኘታቸው ማንም ሰው ከፈለገ ጊዜ እንዳለውና ለእግዚአብሔር ሥራ ጊዜ ሊያንሰው እንደማይገባ ስለአስተማሩን፤ ከእርሳቸው የበለጠ ጊዜ የሌለው ሰው የለም፤ ኢትዮጵያን የሚያህል አገር እየመሩ ጊዜ የለኝም ቢሉ ተቀባይነት አለው። እና ሁላችሁም የመንግስት ሠራተኞችም ብትሆኑ፣ ሚንስትሮችም ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎችም የእርሳቸውን አርአያ በመከተል ሰዎችን በመርዳት ከእግዚአብሔር ዋጋ እንድናገኝና በዚህ ውሸት በሞላበት ዓለም ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለመግለጽ እወዳለሁ።” ብሏል።

    ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታየቸው ያደረጉት ድጋፍም ለማዕከሉ ትልቅ ፋይዳ እንዳለውም አቶ ብንያም አክሎ ተናግሯል።

    የመቄዶንያ የአረጋውያንና አእምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል አርባ አረጋውያንና አእምሮ ህሙማን በመያዝ የተቋቋመ የበጎ አድራጎት ድርጅት ሲሆን፤ ማዕከሉ በአሁኑ ወቅት ወደ ሁለት ሺህ ለሚጠጉ ወገኖች ድጋፍ እያደረገ ይገኛል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታየቸው

    Semonegna
    Keymaster

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊን የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አድርገው መረጡ። ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያ ሴቶች ማኅበር መሥራች ናቸው።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ጥቅምት 22 ቀን 2011 ዓ.ም በሚያካሂደው መደበኛ ስብሰባ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ሹመትን ያጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊን የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አድርገው መርጠዋቸዋል።

    የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ 5ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን፣ 4ኛ መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ይካሄዳል። በስብሰባው በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 81 ንዑስ አንቀጽ 1 መሰረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚያቀርቡትን የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት እጩ ፕሬዚዳንትና ምክትል ፕሬዚዳንት ሹመት መርምሮ እንደሚያጸድቅ ይጠበቃል። ስለዚህ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምርጫ ያቀረቧቸው ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ሆነው ይሾማሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    በአሁኑ ወቅት ፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንትና ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው እያገለገሉ ያሉት አቶ ዳኜ መላኩ እና አቶ ጸጋዬ አስማማው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተሾሙት ሰኔ 16 ቀን 2008 ዓ.ም ነበር።

    ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ ማን ናቸው?

    ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ  በ1985 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ሕገ መንግስት ኮሚሽን የሕግ አማካሪ ሆነው አገልግለዋል። በ1987 ዓ.ም. የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያ ሴቶች ማኅበርን (Ethiopian Women Lawyers Association/ EWLA) ከሌሎች የሕግ ባለሙያ ሴቶች ጋር በመሆን አቋቁመው በ1988 ዓ.ም. ማኅበሩ በይፋ ሥራ ጀመረ። በዚያም ጊዜ ወ/ሮ መዓዛ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚ ሆነው እስከ 1997 ዓ.ም. ድረስ ሠርተዋል።

    ወ/ሮ መዓዛ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የምጣኔ ሀብት ኮሚሽን ለአፍሪካ (United Nations Economic Commission for Africa) የተባለው ዓለም-አቅፍ ድርጅትን በ2003 ዓ.ም. በመቀላቀል፥ በዚሁ ድርጅት ውስጥ ከሰኔ ወር 2004 ዓ.ም. ጀምሮ የሴቶች መብት አማካሪ ሆነው ሠርተዋል።

    ከሕግ ባለሙያነታቸው በተጨማሪ በ2003 ዓም ኢትዮጵያ ውስጥ በ13 ጠንካራ ኢትዮጵያውያን ሴቶች ተደራጅነት የተቋቋመው እናት ባንክ (አ/ማ) ሲመሠረት ከመሥራችቹ ውስጥ ጉልህ ሚና የተጫወቱ አባል ነበሩ። ባንኩ ውስጥም ከአራት ዓመታት በላይ የዳይሬክተሮች ቦርድ አባል ሆነው አገልግለዋል።

    ኢትዮጵያ ውስጥ ለሴቶች እኩልነትና ለሴቶች መብት በመታገል ላደረጉት አንጸባራቂ ውጤት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ በህዳር ወር 1996 ዓ.ም ‘የሀንገር ፕሮጀክት ሽልማት’ (Hunger Project Award) የአፍሪካ ተሸላሚ ሆነዋል። ከዚያም ቀጥሎ (ከሁለት ዓመት በኋላ) የኖቤል የሰላም ሽልማት ዕጩ ሆነው ሊቀርቡ ችለዋል።

    በ2006 ዓ.ም. ዘረሰናይ ታደሰ ተደርሶ የተዘጋጀው (ዳይሬክት የተደረገው) “ድፍረት” የተሰኘውና በዓለም አቀፍ ደረጃ መልካም ተቀብይነትን ያገኘው ፊቸር ፊልም (feature film) ሂሩት አሰፋ የተባለች አንዲት የ14 ዓመት ልጃገረድ ኢፍትሀዊ በሆነ ባህል የሞት ፍርድ ተፈርዶባት ከዚያም የሕግ ባለሙያ (ጠበቃ) የሆነችውን ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊን አግኝታ የሚሆነውን የሚተርክ እንደሆነ ይታወሳል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    መዓዛ አሸናፊ

    Semonegna
    Keymaster

    የፈረንሳይ መንግስት በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ጥያቄ መሰረት፥ ለላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያን እድሳት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል፤ የኢትዮጵያ መከላከያን ለማዘመን ተስማምቷል፤ ለአየር መንገድ ከ100 ሚሊዮን ዩሮ በላይ ድጋፍ ያደርጋል።

    ፓሪስ፥ ፈረንሳይ – የፈርንሳይ መንግስት ለላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያን ድጋፍ እንዲያደርግ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) የቀረበለትን ጥያቄ በፕሬዝዳንቱ ኢማኑኤል ማክሮን (Emmanuel Macron) በኩል ተቀብሎ ተስማምቷል።

    በፈረንሳይ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት በማድረግ ላይ የሚገኙት የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ፥ ትናንት ምሽት ነው በፓሪስ ኢልዚ ቤተ መንግስት (Élysée Palace) ከፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ኢትዮጵያ በባህል፣ በእምነትና በቋንቋ ከፈረንሳይ ጋር የነበራትን ወዳጅነት እንድታጠናክር የፈረንሳይ የመጀመሪያ ሥራ በላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያን የደረሰውን ችግር መቅረፍ ሊሆን እንደሚገባ ለፕሬዝዳንት ማክሮን ጥያቄ አቅርበው አዎንታዊ ምላሽ መገኘቱን ሁለቱ መሪዎች በጋራ በስጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ አስታውቀዋል።

    መሪዎቹ በሰላም፣ በዴሞክራሲና በልማት ዙሪያ ዝርዝር ውይይት ማድረጋቸውን የጠቀሱት ዶ/ር አብይ፥ ፈረንሳይ የሀገር መከላከያን ለማዘመን የሰው ኃይል ለማሰልጠን መስማማቷንም  አስታውቀዋል።

    መሪዎቹ በኢኮኖሚው መስክ ባደረጉት ውይይትም ፈረንሳይ የኢትዮጵያ አየር መንገድን ለማዘመን ከ100 ሚሊዮን ዩሮ በላይ በማውጣት የአዲስ አበባ ኤርፖርትን ለመሥራት፣ እንዲሁም የፈረንሳይ ኢንቨስተሮች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ኢንቨስት እንዲያደርጉ ከስምምነት መድረሳቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት።

    ኢትዮጵያ የጀመረችውን የኢኮኖሚ ማሻሻያ ከማገዝ አንጻርም ከፈረንሳይ የልማት ኤጀንሲ (ኤ.ኤፍ.ዲ)፣ ከአለም ባንክ እና ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይ.ኤም.ኤፍ) ከምታገኘው የበጀት ድጋፍ በተጨማሪ የፈረንሳይ መንግስት የቀጥታ ድጋፍ ለማድረግ ያለውን ዝግጁነት ፕሬዝዳንት ማክሮን መግለፃቸውን ዶ/ር አብይ አስታውቀዋል።

    የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት እ.ኤ.አ በመጋቢት ወር 2019 ኢትዮጵያን እንደሚጎበኙ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል።

    በአፍሪካ ቀንድ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የመጣውን ሰላም በማስቀጠል በኤርትራና በጅቡቲ መካከል ሰላም እንዲጠናከር ለማድረግ በጋራ ለመስራት መስማማታቸውንም አስታውቀዋል በማለት ኤፍ.ቢ.ሲ ዘግቧል።

    ፕሬዚዳንት ማክሮን ኢትዮጵያን የሚጎበኙት ከጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ በቀረበላቸው ግብዣ መሰረት መሆኑም ታውቋል። ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከውይይቱ በኋላ ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ጋር በሰጡት የጋራ መግለጫ፥ የፊታችን መጋቢት ወር 2011 ዓ.ም ላይ ኢትዮጵያን እንደሚጎበኙ አስታውቀዋል።

    የፈረንሳይ የልማት ኤጀንሲ (ኤ.ኤፍ.ዲ) እ.ኤ.አ በመስከረም ወር 2017 ዓም የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅትን ለማሻሻልና በአዲስ ቦታ ለማደራጀት ከ70 ሚሊዮን ዩሮ በላይ ድጋፍ ማድረጉን፣ እ.ኤ.አ በሰኔ ወር 2018 ደግሞ ለከተማ ልማት እና የጂኦተርማል ኤሌክትሪክ ኃይል ፕሮጀችት 18 ሚሊዮን ዩሮ ለመደገፍ ከኢፌዴሪ የፋይናንስና ገንዘብ ሚኒስቴር ጋር ስምምነቶችን መፈራረሙን መዘገባችን ይታወሳል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    የፈረንሳይ መንግስት


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አባባ – የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም በይፋ ገንዘብ መሰብሰብ መጀመሩን የጠቅላይ ሚኒስትር ልዩ ጽህፈት ቤት አስታወቀ።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ከሁለት ወር በፊት ለኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማህበረሰብ የትረስት ፈንዱ እንዲቋቋም ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበው እንደነበረ ይታወሳል።

    በይፋ የተቋቋመው ትረስት ፈንድ ጥቅምት 12 ቀን ገንዘብ መሰብሰብ መጀመሩን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ አማካሪ ምክር ቤት ተቋቁሞ በይፋ ሥራ እንዲጀምር ላደረጉት ትጋትና ጥረት አባላቱን በኢትዮጵያ ሕዝብ ስም አመስግነዋል።

    በአሁኑ ወቅት በትረስት ፈንዱ ገንዘብ የማሰባሰብ ሥራ የመጀመሪያ ደረጃ ላይ እንዳለና ከዚህም በኋላ ብዙ ሥራ መሥራት እንደሚገባ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት።

    ———————————————-

    ———————————————-

    የትረስት ፈንድ አማካሪ ምክር ቤቱ የፈንዱን አቅምና ውጤታማነት ለማሻሻል በትጋት መሥራት እንዳለበትም ዶክተር አብይ ተናግረዋል።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማህበረሰብ የሚሰጡትን የተወሰነ ገንዝብ በአንድ ወይም በሁለት ጊዜ ጠቅልለው በመክፈል በጣም ወሳኝ ለሚባሉ ፕሮጀክቶች የሚያስፈልገውን ድጋፍ እንዲያፋጥኑም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠይቀዋል።

    በቀን ከአንድ ዶላር በላይ መስጠት ለሚችሉ ዜጎች ድጋፋቸውን በፍጥነት እንዲያድርጉና ዓለም አቀፉ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማኅበረሰብ ከትረስት ፈንድ ምክር ቤቱ ጋር ትብብራቸውን እንዲያደርጉ ዶክተር አብይ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

    የኢትዮጵያ የዳያስፖራ ትረስት ፈንድ የዳይሬክተሮች ቦርድ የተመረጡ ሲሆን ስም ዝርዝራቸው በቅርቡ ይፋ እንደሚደረግም መጠቆማቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የላከው መግለጫ ያስረዳል።

    ፈንዱ የዳያስፖራውን ተሳትፎ ለማቀናጀትና የልገሳውን ገንዘብ ለማሰባሰብ የሚያስችል እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን የባንክ ሒሳብ ቁጥሩም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 1000255726725 (አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ) ነው። ከዚህ የባንክ የሒሳብ ቁጥር በተጨማሪ ተቋሙ በኢንተርኔትም ገንዘብ እንደሚያሰባስብና ኦፊሴላዊ ድረ ገጹም “https://www.ethiopiatrustfund.org” እንደሆነ ክስር በተመለከተው ጋዜጣዊ መግለጫ አሳውቋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በተለያዩ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የተሻለች ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን እንዲወጡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው ባደረጉት ንግግር ጥሪ ማቅረባቸው ይታወቃል።

    በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በቀን ቢያንስ 1 የአሜሪካ ዶላር በመለገስ ለተለያዩ የልማት ሥራዎች ድጋፍ እንዲያደርጉ መጠየቃቸው የሚታወስ ነው።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ ተቋም ምክር ሰጪ ካውንስል መግለጫ (ጥቅምት 10 ቀን 2011 ዓ.ም)

    የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ዳያስፖራ ፈንድ ተቋም ሰኞ ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም (October 22, 2018) ለሕዝብ መዋጮ መሰብሰቢያ ይከፈታል።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ፈንድ ተቋም ምክር ሰጪ ካውንስል (ኢዲቲኤፍ) ሰኞ ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም (October 22, 2018) ለሕዝብ መዋጮ መሰብሰቢያ ያዘጋጀዉን ዝግጅት ለሕዝብ ይፋ አድርጎ ሥራዉን በኦፊሴላዊ ድረ-ገጽ https://www.ethiopiatrustfund.org እንደሚጀምር በደስታ ያስታዉቃል።

    ባለፉት ሳምንታት ካውንስሉ የዲያስፖራ ፈንዱን ሕጋዊና መንግስታዊ ደንቦችን በተከተለ መንገድ ፈንዱን ለመመስረት በትጋት ሠርቷል።

    የፈንዱ ካውንስል ምክር ቤት በዓለም ያሉ ዲያስፖራ ኢትዮጵያውያን ክቡር ጠ/ሚ ዶ/ር አብይ አህመድ በቀን 1 ዶላር ለህዝብ አርዳታ አዋጡ ያሉትን ጥሪ ተመልከቶ መዋጮ ለመስጠትና ፈንዱን በስራ ላይ ለማዋል ከፍ ያለ ጉጉት አንዳላቸው ይገነዘባል።

    ይህን ፍላጎት ለሟሟላትና ፈንዱን በሥነ ስርዓት ሥራ ማስጀመር ምክር ቤቱ ለትርፍ ያልተቋቋመ የበጎ አድራጎት ድርጅት ማቋቋም የባንክ ሂሳብ ቁጥር መክፈት ከኢንተርኔት ክፍያ ስርዓቶች እና ሌሎች የፋይናንስ መድረኮችን ጋር መደራደር አና የተለያዩ ደንቦችን ሟላትና አስተዳደራዊ እና የአፈፃፀም ሂደቶችን ለመቆጣጠር እና ግልጽነትን ለማረጋገጥ ምክር ቤቱ እነዚህን ሥራዎች በፍጥነት መወጣት ችሏል።

    ካውንስሉ ዓለምአቀፍ ዲያስፖራዎች ማኅበረሰቦች ለፈንዱ ላሳዩት መታገስና የማያወላዉል ድጋፍ ከፍተኛ ምስጋናዉን ያቀርባል።

    ካውንስሉ የኢትዮጵያ ዲያስፖራን የኢትዮጵያ ወዳጆች እና ሌሎች ነፃነት ዲሞክራሲ ሰብአዊ መብቶችን እና መልካም አስተዳደርን በኢትዮጵያ ማበልፀግ የሚፈልጉን ሁሉ በቀን 1 ዶላር መዋጮቻቸዉን በአንድ ጊዜ በጠቅላላው 365 የአሜሪካን ዶላር እንዲከፍሉ ባክብሮት ይጠይቃል። ይህንም በማድረግ አስፈላጊ ፕሮጀክቶችን ባፋጣኝ ለማስጀመር ይቻላል።

    ስለ ፈንዱ ለመማር እና መዋጮ ለማድረግ ወድዚህ ድህረ ገፅ ይሂዱ (ይጫኑ) https://www.ethiopiatrustfund.org/

    ልዩ ማስታወሻ – የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ በሚል ስም አንዳንድ በግል የተደራጁ ሰዎች ገንዘብ ለመሰብሰብ ጥረት እንደሚያደርጉ የፈንዱ ምክር ቤት ይረዳል። ነገር ግን ኦፊሴላዊ የሆነው በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እ.ኤ.አ. ነሐሴ 9, 2018 በካውንስሉ የተቋቋመው ኤድቲኤ (EDTF) ብቸኛና መደበኛ በሕግ የታወቀው ነው።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ

    Semonegna
    Keymaster

    የአሜሪካ ድምፅ ለባለሞያዎቹ ሥልጠና ሲሰጥ ያገር ውስጥ ጋዜጠኞችንም ቢያካትት ፍላጎታቸው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ስልጠና ለመስጠት አዲስ አበባ ከሚገኙ የአሜሪካ ድምጽ ጋዜጠኞች ጋር በተገናኙበት ጊዜ አስታውቀዋል።

    አዲስ አበባ – የአሜሪካ ድምፅ ለባለሞያዎቹ ሥልጠና ሲሰጥ ያገር ውስጥ ጋዜጠኞችንም ቢያካትት ፍላጎታቸው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) አስታውቀዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የአሜሪካ ድምፅ የአፍሪካ ዲቪዥን ዳይሬክተር አቶ ንጉሤ መንገሻን እና የአፍሪካ ቀንድ ማኔጂንግ ኤዲተር ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸውን በቢሯቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።

    የአሜሪካ ድምፅ በኢትዮጵያና በጎረቤት ሃገሮች ለሚገኙ ዘጋቢዎቹ እስካለፈው ዓርብ የቆየ የአንድ ሣምንት ሥልጠና አዲስ አበባ ላይ ሰጥቷል።

    በኢሕአዴግ መንግሥትና በአሜሪካ ድምፅ መካከል ላለፉት 27 ዓመታት ከዘለቀ ውጣ ውረድ ያልተለየው ግንኙነት በኋላ አንድ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የጣቢያውን ኃላፊዎች ተቀብሎ ሲያነጋግር ይህ የመጀመሪያው ነው።

    ለተጨማሪ መረጃ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ። ዘጋቢ እስክንድር ፍሬው ለአሜሪካ ድምጽ የአማርኛ ዝግጅት ክፍል

    ጋዜጠኛ ንጉሤ መንገሻ
    ትውልደ ኢትዮጵያዊው ንጉሤ መንገሻ ከ2014 (እ.ኤ.አ) ጀምሮ የአሜሪካ ድምጽ የአፍሪካ ዲቪዥን ዳይሬክተር (Africa Division Director) ሆኖ እያገለገለ ይገኛል። ጋዜጠኛ ንጉሤ ወደ አሜሪካ የመጣው እ.ኤ.አ በ1981 ዓም ሲሆን በ1982 የአሜሪካ ድምጽን በሲኒየር ኤዲተርነት ተቀላቅሏል። ቀጠሎም የአሜሪካ ድምጽ የመካከለኛው አፍሪካ ሰርቪስ ቺፍ (Service Chief)፣ የአፍሪካ ዲቪዥን ፕሮግራም ማናጀር (Africa Division Program Manager)፣ አሁን ደግሞ ሆኖ የአፍሪካ ዲቪዥን ዳይሬክተር አገልግሏል/እያገለገለ ይገኛል።

    ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸው
    በ ኤሉባቡር ዞን (የቀድሞው ኤሉባቡር ክፍለሀገር) ያዮ ወረዳ ውስጥ የተወለደችው ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸው ወደ አሜሪካ የመጣችው እ.ኤ.አ በ1973 ሲሆን፥ ትምህርቷን ዋሽንግተን ዲሲ በሚገኘው ሐዋርድ ዩኒቨርሲቲ (Howard University) ተከታትላ የአሜሪካ ድምጽን የተቀላቀለችው የአማርኛ ዝግጅት ክፍሉ በተመሠረተ በሁለት ዓመቱ (እ.ኤ.አ በ1984) ነበር። በአሜሪካ ድምጽ (የአማርኛ ዝግጅት ክፍሉን ጨምሮ) በተለያዩ የጋዜጠኝነት ሙያ እርከኖች ያገለገለች ሲሆን በአሁኑ ወቅት የአፍሪካ ቀንድ ማኔጂንግ ኤዲተር (Horn of Africa Managing Director) ሆና እየሠራች ነው።

    የአሜሪካ ድምፅ

    Semonegna
    Keymaster

    አዲሱ የካቢኔ አባላት ሹመት የቀረበው የአስፈፃሚ አካላት ስልጣንና ተግባር ለመወሰን የወጣውን አዋጅ እንደገና ለማሻሻል የቀረበውን አዲስ ረቂቅ አዋጅ በምክር ቤቱ መፅደቁን ተከትሎ መሆኑን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት  አስታውቋል።

    አዲስ አበባ – የኢትዮጵያ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከ20 አዳዲስ የካቢኔ አባላት ሹመት ውስጥ 50 በመቶ ሴቶች ሆነው እንዲያገለግሉ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) የቀረበውን ሹመት ጥቅምት 6 ቀን 2011 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ አፀደቀ።

    የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሁለተኛ መደበኛ ስብሰባውን እያደረገ የሚገኝ ሲሆን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ከሚሾሙት 20 ካቢኔዎች ውስጥ 10 ሴቶች ሆነው በተሰጣቸው ኃላፊነት እንዲያገለግሉ ለምክር ቤቱ አቅርበዋል።

    አዲሱ የካቢኔ አባላት ሹመት የቀረበው የአስፈፃሚ አካላት ስልጣንና ተግባር ለመወሰን የወጣውን አዋጅ እንደገና ለማሻሻል የቀረበውን አዲስ ረቂቅ አዋጅ በምክር ቤቱ መፅደቁን ተከትሎ ነው።

    በዚህም መሠረት የሹመቱ ዋና መስፈርት ብቃት፣ የትምህርት ዝግጅትና ለውጥን የመምራት አቅም መሆኑ የተገለፀ ሲሆን ከሚሾሙት ካቢኔዎች 50 በመቶ (በቁጥር፥ ወይም ከ20ዎቹ 10 ሴት) ካቢኔዎች መሆናቸውንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልፀዋል።

    ይህም በኢትዮጵያ ምናልባትም በአፍሪካ ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑም በምክር ቤቱ ተገልጿል።

    በዚህ በተደረገው የካቢኔ ሹመት ለውጥ ውስጥ ከዚህ በፊት “የፐብሊክ ሰርቪስ እና ሰው ሀብት ልማት ሚኒስቴር” ተብሎ ይጠራ የነበረው ሚኒስቴር ተለውጦ አሁን “ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን” (Civil Service Commission) በሚል እንደተተካ ታውቋል። ከዚህ በተጨማሪ ሶስት ኮሚሽኖችም በአዲስ መልክ ተካተዋል፤ እነዚህም (1) የሥራ ፈጠራ ኮሚሽን (Job Creation Commission)፣ የአካባቢ፣ የደንና የአየር ንብረት ለውጥ ኮሚሽን (Environment, Forestry and Climate Change Commission) እና የፕላንና እድገት ኮሚሽን (Plan and Development Commission) ናቸው።

    አዲስ በተዋቀረው ካቢኔ ውስጥ የተሰየሙት ባለስልጣናትና የተሰየሙበት ስልጣን ዝርዝር

    1. ዶ/ር ሂሩት ካሳው ― የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር
    2. ዶ/ር ሂሩት ወልደማርያም ― የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር
    3. ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል ― የሰላም ሚኒስቴር
    4. ዶ/ር ሳሙኤል ሆርቃ ― የማዕድንና ነዳጅ ሚኒስቴር
    5. ዶ/ር ኢ/ር ስለሺ በቀለ ― የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር
    6. አቶ ብርሃኑ ጸጋዬ ― ጠቅላይ ዐቃቤ ህግ
    7. አቶ አህመድ ሺዴ ― የገንዘብ ሚኒስቴር
    8. ዶ/ር አሚን አማን ሐጎስ ― የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር
    9. ወ/ሮ አዳነች አበበ ― የገቢዎች ሚኒስቴር
    10. ኢ/ር አይሻ መሀመድ ሙሳ ― የሀገር መከላከያ ሚኒስቴር
    11. አቶ ኡመር ሁሴን ― የግብርና ሚኒስቴር
    12. ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬ ― የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር
    13. ወ/ሮ የዓለምፀጋይ አስፋው — የሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር
    14. ወ/ሮ ዳግማዊት ሞገስ ― የትራንስፖርት ሚኒስቴር
    15. አቶ ጃንጥራር አባይ ― የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስቴር
    16. ዶ/ር ኢ/ር ጌታሁን መኩሪያ ― የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር
    17. ዶ/ር ጥላዬ ጌጤ ― አምባዬ የትምህርት ሚኒስቴር
    18. ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ ― የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር
    19. ወ/ሮ ፈትለወርቅ ገብረ-እግዚአብሔር ― የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር
    20. ዶ/ር ፍፁም አሰፋ ― የፕላን ልማት ኮሚሽን ኮሚሽነር

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የካቢኔ አባላት ሹመት

    Semonegna
    Keymaster

    የጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ መርክል ባደረጉላቸው ግብዣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክትር አብይ አህመድ በጥቅምት ወር ለይፋዊ ጉብኝት ወደ ጀርመን የሚያቀኑ ሲሆን፥ በአውሮፓ የሚገኙ ኢትዮጵያዊንን አግኝተው ያነጋግራሉ ተብሏል።

    አዲስ አበባ (የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክትር አብይ አህመድ በጥቅምት ወር ለይፋዊ ጉብኝት ወደ ጀርማን የሚያቀኑ ሲሆን፥ በዚሁ ጉብኝታቸውም ከጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ መርክል (Angela Merkel) እና ሌሎች የሀገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር በጀርመን ዋና ከተማ በርሊን እንደሚገናኙም ነው የተገለጸው።

    የጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ መርክል በፈረንጆቹ ነሃሴ ወር በኢትዮጵያ እየመጣ ያለውን ለውጥ በመደገፍ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ጎን መሆናቸውን በስልክ በገለጹበት ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጀርመን ይፋዊ ጉብኝት እንዲያደረጉ መጋበዛቸውም ታውቋል።

    በዚህም ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክትር አብይ አህመድ በጥቅምት ወር መጨረሻ ለይፋዊ ጉብኝት ወደ ጀርመን የሚያቀኑ ሲሆን፥ በአውሮፓ የሚገኙ ኢትዮጵያዊንን አግኝተው ያነጋግራሉ ተብሏል።

    በፈረንሳይ ፓሪስ፣ ጀርመን ፍራንክፈርት ከተሞችም በሚዘገጁ መድረኮችም ነው ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክትር አብይ ከኢትዮጵያዊያኑ ጋር እንደሚገናኙ የተገለጸው።

    ሀገራዊ ዜና፦ አብይ አህመድ (ዶ/ር) እና ደመቀ መኮንን በድጋሚ የኢህአዴግ ሊቀመንበር እና ምክትል ሊቀመንበር ሆነው ተመረጡ

    በፈረንጆቹ ጥቅምት 31 ቀን 2011 (ጥቅምት 21 ቀን 2011 ዓም) ዓም በጀርመን ሁለተኘዋ ከተማ ፍራንክፈርት ላይ መድርክ እንደሚዘጋጅ እና ጠቅላይ ሚኒትሩ በአውሮፓ የሚገኙ ኢትዮጵያዊንን አግኝተው እንደሚያነጋግሩም ታውቋል።

    ለዚሁ ፕሮግራምና የጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አቀባበልን እስመልክቶ ከ80 ማህበራት የተውጣጡ አበላት ያሉት ኮሚቴ አየሰራ መሆኑንም ነው የተገለጸው።

    በጀርመን የኢትዮጵያ ቆንሰላ ጄኔራል ምህረት አብ ሙሉጌታ እንደገለጹት አሁን ላይ በኢትዮጵያ እየታየ ያለውን ለውጥ በመደገፍ 25 ሺህ ያህል ኢትዮጵያን ፍርንክፈረት ኮመርዝባክ አረና ስታዲየም (Commerzbank-Arena) በሚዘጃጀው ፕሮግራም ላይ ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    ምንጭ፦ የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት

    ጀርመን

Viewing 9 results - 1 through 9 (of 9 total)