ነፃ አስተያየት (ስለኢትዮጵያ በኢትዮጵያውያን)

Home Forums Semonegna Stories ነፃ አስተያየት (ስለኢትዮጵያ በኢትዮጵያውያን)

Viewing 15 posts - 16 through 30 (of 36 total)
  • Author
    Posts
  • #16344
    Anonymous
    Inactive

    የሰላም ሚኒስትር ወ/ሮ ሙፈሪሃት ካሚል ሃሳብ ሊደገፍ የሚገባው ነው
    የሺዋስ አሠፋ

    ወ/ሮ ሙፈሪሃት የፌደራል መንግሥቱን (ብልፅግና) እና የትግራይ ክልል አስተዳደርን (ህወሓት) መካረር በተመለከተ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የገለፁትን አይቼ በግሌ ጥሩ ጅምር ነው – ይበርቱ ብያለሁ። ስድብ፣ ፉከራ እና ይዋጣልን ሀገርን እና ሕዝብን ምስቅልቅል ውስጥ ከመክተት ውጭ ምንም ፋይዳ የለውም። “እልህ ምላጭ ያስውጣል” እንዲሉ ለራሳችሁም ቢሆን ውስጣችሁን የሚቆራርጥ ከሚሆን በስተቀር አይጠቅምም። የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ አቋራጭ መንገድ የለውም፣ ውይይት/ድርድር ብቻ! በጉልበት/በጠመንጃ የሚሆን ቢሆን ኢትዮጵያን የሚቀድም ባልነበረም ነበር። ልብ በሉ ለውይይት አሻፈረኝ የሚሉ ወገኖች በስተመጨረሻ ቢፈልጉ አያገኙትም፤ ምክንያቱም አይበለው እንጂ ጦርነትም ቢሆን መቋጫው ውይይት/ድርድር ነው።

    በ2009 ዓ.ም ራሳቸው ወ/ሮ ሙፈሪሃት የነበሩበትን የፓርቲዎች ውይይት/ድርድር (ስያሜው ራሱ አወዛጋቢ ነበር) ባስታውሳቸው ጠቃሚ የሚሆን ይመስለኛል። ሙከራው የተቀጨው ከጅምሩ ነበር። የቀድሞ ገዢ ፓርቲን ጨምሮ 22 ሀገር አቀፍ ፓርቲዎች ለሚያደርጉት ውይይት/ድርድር የመሀል ዳኛ (mediators) ያስፈልጋሉ/አያስፈልጉም በሚለው የጦፈ ክርክር ተደርጎ ኢህአዴግ እና ሌላ አሁን ስሙን የማላስታውሰው አንድ ፓርቲ አያስፈልግም ሲሉ 20 ፓርቲዎች ያስፈልጋል ብለን በከፍተኛ ቁጥር አሸነፍን፣ mediators ሊሆኑ የሚችሉትን ወገኖች የሥራ ልምድና የትምህርት ደረጃ መግለጫ (ማለትም፥ CV) እና ዝርዝር ማዘጋጀት ጀመርን።

    በዚህ የተናደዱት የሂደቱ ፊትአውራሪ የነበሩት የተከበሩ አቶ አስመላሽ ወልደሥላሴ [የህወሓት ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል] ለሳምንት እንደገና እንየው ብለው በተኑት። በሳምንቱ ራሳቸው አጀንዳውን አንስተው mediators ያስፈልጋሉ/አያስፈልጉም እጅ አውጡ ሲሉ ጠየቁ። ከመድረክና ሰማያዊ ፓርቲ ውጭ ሁሉም አያስፈልጉም አሉ። በሳምንት ልዩነት 20 ለ 2 ውጤቱ ሲገለበጥ ወ/ሮ ሙፈሪሃት እጃቸውን በአፋቸው ጭነው ይታዘቡ ነበር።  እኔም በጣም ተበሳጭቼ “የተከበሩ አቶ አስመላሽ! ሳምንቱን ሙሉ ሲደልሉና ሲያስፈራሩ ሰንብተው ውጤቱን በጉልበት አስቀየሩት! ይሄ ጉልበት ግን አይቀጥልም፤ ነገ በሌላ ጉልበት ይሰበራል!” ብዬ ትቻቸው ወጣሁ። ሂደቱም ተጨናግፎ ቀረ (በወቅቱ ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 ሬድዮ ዘግቦታል)። ከ3 ዓመታት በኋላ እነአቶ አስመላሽን ወክለው አቶ አዲስዓለም ባሌማ ሁሉን አካታች ውይይት/ድርድር እናድርግ ብለው ሲጠይቁም፣ ያልተገባ ምላሽ ሲሰጣቸውም በተራዬ በትዝብት ተመለከትኩ።

    ዛሬ የመንግሥት አካል ከሆነው የሰላም ሚኒስትር መፍትሄው ውይይት/ድርድር ነው የሚል ተነሳሽነት ሲመጣ አያስፈልግም ብሎ መታበይም ሆነ ተለመንኩ ብሎ ማጣጣል አይገባም። ሚኒስትሯ እንዳሉት፥ ከስሜት ወጥቶ፣ ሰከን ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል። በእኔ እምነት ይሄ ትልቅ እርምጃ ነው፤ ቀጣዩን ታሪክ ለመሥራት መሽቀዳደም ለኢትዮጵያ ውለታ ነውና ማን ይሆን ፈጥኖ ወደ መቀሌ ከተማ ወይም ወደ ወለጋ ጫካዎች ነጭ ባንዲራ ይዞ የሚዘምተው? (የኬንያው Building Bridges Initiative (BBI) ጥሩ መማሪያ ይሆነናል) ወይም ወደአዱ ገነት የሚመጣው? የወጣቶቻችንን ህይወት ከመቀጠፍ፣ የእናቶቻችንን እንባ ከመፍሰስ የሚታደገው? ከፌደሬሽን ምክር ቤት? ከሰላም ሚኒስትር? ከሀይማኖት አባቶች? ከእርቀ-ሰላም ኮሚሽን? ከሀገር ሽማግሌዎች? ከግብረ ሰናይ ድርጅቶች? ከአባ ገዳዎች? ከጋሞ አባቶች? እናቶች? ከወጣቶች? ከህፃናት?… ማን ይሆን በሞራል ልዕልና እና በመንፈስ ከፍታ ቆሞ ከኢትዮጵያ ሰማይ ሥር የሚጥመለመለውን የጥላቻ አውሎ ነፋስ ገስፆ የሚያስቆመው? እስኪ “እኔ አለሁ” በሉ! (እኔ እንዳልሞክር ፓርቲ ውስጥ መሆን ይሄን ነፃነት አይሰጥም) ግን ኢትዮጵያ የሰው ድሃ አይደለችምና ፍጠኑ። ሰላም!

    የሺዋስ አሠፋ

    አቶ የሺዋስ አሠፋ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)  ሊቀ መንበር ሲሆኑ፤ ከዚያ በፊት ደግሞ የቀድሞው ሰማያዊ ፓርቲ ሊቀ መንበር ነበሩ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    አቶ የሺዋስ አሠፋ

    #16351
    Anonymous
    Inactive

    በአዳራሽ ስብሰባ ለማድረግ ፈቃድ ከልክሎ በአደባባይ ቢልቦርድ እንዲሰቀል እንዴት ፈቀዳችሁ?
    አቶ ግርማ ሰይፉ ማሩ

    “መስከረም 30 መአት ይወርዳል” ከሚሉት ጋር የማልስማም መሆኔን አስረድቻለሁ። መስከረም 30 በአዲስ አበባ ጎዳና ወጥተው የተመለከትኩት፥ በየአደባባዩ የተሰቀለው የማስታወቂያ ሰሌዳ (billboard) ግን አንድ ነገር አስታዋሰኝ። የኢትዮጵያ ሠራተኞች ፓርቲ አደራጅ ኮሚቴ (ኢሠፓአኮ) ማብቂያው ደርሶ፣ የኢትዮጵያ ሠራተኞች ፓርቲ (ኢሠፓ) ሊመሠረት ዋዜማው ላይ በከተማቸን የምናየው መፈክር ሁሉ፥ “ከጓድ መንግሥቱ ኃይለማርያም አመራር ጋር ወደፊት!”፣ “ብልሁ፣ አስተዋዩ መሪ መንግሥቱ ኃይለማርያም…” ወዘተ… የሚሉ ነበሩ። አልቀረልንም… ከዝሆን እና አንበሳ ምረጡ ተባለና ዝሆን ተመረጠ፤ አለቀ ደቀቀ። ይህ በሁለት የአንድ ፓርቲ አባላት መካከል በሚደረግ ምርጫ ዝሆን ቢመረጥ፣ አንበሳ ወይም ሚዳቋ ብዙ ትርጉም የለውም። ኢሠፓ ያለውን መንግሥቱን መርጧል።

    ዛሬም ብልፅግናዎች ዐቢያቸውን “ብልሁ መሪ” የማለት መብታቸውን አከበራለሁ። ያላቸውን የመምረጥ መብት አላቸው። በአጠቃላይ ለሀገሩ እና ለከተማው ነዋሪ ይህን በግድ መጫን ግን መብታቸው አይደለም። በመጀመሪያ ደረጃ የምርጫ ቅስቀሳ ሳይጀመር ምርጫ ቅስቀሳ ማድረግ፣ ሌላውን በቢሮ ለሚደረግ ውይይት ፍቃድ ሰጪና ነሺ የሆነ መንግሥት፥ በትራፊክ መንገድ አዘግቶ “ዐቢይ ለዘላለም ይኑር!” መፈክር ተገቢና ትክክል አይደለም። ይህ መንገድ የመንግሥቱ ኃይለማርያም መንገድ ነው። ብልፅግና ኢሠፓአኮን/ኢሠፓን መሆን ካማረው ሕጉን ይለውጥና ምርጫ ቦርድን ዘግቶ መጫወት ይችላል። የሚከተለውን ለመቀበል መዘጋጀት ብቻ ነው የሚጠበቅበት።

    አስገራሚው ዛሬም በየቀበሌና ወረዳው በዚህ ደረጃ ወርደው የሚያዋርዱ ካድሬዎች መኖራቸው ነው። “ታላቁ መሪ መንግሥቱ ኃይለማርያም!”፣ “ታላቁ መሪ ዐቢይ አህመድ!” ብሎ ለመፃፍ ልብ የሚያገኙ ካድሬዎች እንዴት ነው ማፍራት የተቻለው? መክሸፍ ማለት ይህ ነው፤ ከታሪክ መማር ያለመቻል። የሀገርን መሪ በሕዝብ ድምፅ ቢቻል በቀጥታ ድምፅ ይሰጥ የምንለው አብዛኛው ይሁንታ የሰጠው እንዲመራን እንጂ፥ ካድሬ እንዳይመርጥልን ሰለምንፈልግ ነው። ዶ/ር ዐቢይ አህመድ የአዲስ አበባ ተመራጭ አይደሉም፤ በቀጣይ አዲስ አበባም የሚወዳደሩ ከሆነ በወረዳቸው ይህን ማድረግ ይቻላል። ግን ገና ለገና መስከረም 30 መንግሥት የለም ካሉት ጋር ብሽሽቅ ለመግባት የዚህን ያህል መውረድ አያስፈልግም። የዚህ ዓይነት ድርጊቶች ሳይቃጠል በቅጠል ካልተባለ፥ ምርጫ ሲጀመር በየወረዳው ኃላፊነት ላይ ያሉት የብልፅግና ሰዎች መላወሻ ሊከለክሉን ግድ አይሰጣቸውም። ይህ መስመር ግን በወረዳ የብልፅግና ካድሬዎችንም ቢሆን አይጠቅምም፤ አያኗኑርም ብሎ መመከር ደግ ነው።

    የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት፣ ምርጫ ቦርድ፣ ወዘተ… በዚህ ዓይነት ጉዳይ ላይ የማረሚያ እርምጃ መውሰድ ያስፈልጋል። የአዲስ አበባ መስተዳደር ለዚህ ጉዳይ ፈቃድ የሰጠ መሆኑን ጋዜጠኞች እባካችሁ አጣሩልን። ሥራችሁን ብትሠሩ ጥሩ ነው። ‘በአዳራሽ ስብሰባ ከልክሎ በአደባባይ እንዴት ፈቀዳችሁ?’ በሉልን፤ የዚህ ዓይነት ድርጊት “ብልግና” ነው በሏቸው።

    ግርማ ሰይፉ ማሩ

    አቶ ግርማ ሰይፉ ማሩ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) አመራር አባል (የብሔራዊ ሥራ አስፈፃሚ አባል) ሲሆኑ፤ ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት (ፓርላማ) በቸኛው ተቃዋሚ አባል በመሆን አገልግለዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    አቶ ግርማ ሰይፉ ማሩ

    #16418
    Anonymous
    Inactive

    ይድረስ ለትግራይና ለአማራ ምሁራን
    “ሀገርን ለማዳን እስከጠቀመ ድረስ ተቃራኒን ግማሽ መንገድ ድረስ ሄዶ ማግኘት ጥበበኝነት እንጂ ተሸናፊነት አይደለም”
    አወል እንድሪስ (ዶ/ር)

    ውድ የትግራይና የአማራ ምሁራን፥ እንደምን አላችሁ? ይህ ዛሬ የምፅፍላችሁ ሀሳብ ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማችሁት እንዳልሆነ እረዳለሁ። በየግላችሁም የሀገራችንን ሁኔታ እያሰላሰላችሁ ምን ማድረግ እንደሚሻል እየተጨነቃችሁበት እንደሆነ እገምታለሁ። ሀገራችን በአጭር ተመልካች ፖለቲከኞችና እሳቱ ላይ ቤንዚን መጨመርን የመማርና የመመራመር ጥግ አድርገው የሚያዩ ኃላፊነት የማይሰማቸው የተማሩ ዜጎቻችን በሚያራግቡት የጥላቻና የመለያየት ሀሳብ ተገፍታ፣ ተገፍታ ገደሉ አፋፍ ላይ ትገኛለች። ይህን ሁኔታ ባወጣ ያውጣው ብሎ መተው ዛሬ እኛ፣ ነገ ደግሞ ልጆቻችን የሚያዝኑበትን ሁኔታ መጋበዝ ነው።

    ያለንበት ጊዜ በሁለቱም ወገን የተለሳለሰ አቋም መያዝን መሸነፍ አድርጎ የሚያሳይ በመሆኑና የማንቀበለውንም ሀሳብ ለመስማት መዘጋ ጀትን እንደ ክህደት የሚያስቆጥር በመሆኑ አብዛኞቻችን ዝምታን መርጠን ተቀምጠናል። ዝምታ ግን አሁን ባለንበት ሁኔታ በፍፁም፣ በፍፁም ተመራጭ አይደለም። ምስኪን ገበሬ ከልጆቹ አፍ እየነጠቀ በከፈለው ግብር ተምረን፣ የሚለኮሰውም እሳት ይበልጥ የሚያቃጥለው እሱን ሆኖ እያለ፥ ዝም ማለት እንደሆነ እንጂ ይሻላል የሚባልን ሀሳብ መናገር በፍፁም፣ በፍፁም ክህደት ሊሆን አይችልም። እንዲያውም ክህደት የሚሆነው ምስኪኑን ገበሬና ልጆቹን በሚለኮሰው እሳት ውስጥ መማገድ ነው። ይህ እንዳይሆን ሁላችንም የግል ኩራታችንንና እብሪታችንን ወይም የምን ይሉኛል ፍርሀታችንን ወዲያ ጥለን የመፍትሄው አካል መሆን አለብን። ይህን በማድረግም በግል ለራሳችን ህሊና፣ በወል ደግሞ ሀገራችንን ከጥፋት በማዳናችን ለዜጎቻችን እረፍትና ሰላም እናስገኛለን።

    በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ ውስጥ በሁኔታዎች አስገዳጅነት የመጣው ለውጥ ከፈጠራቸው አሳሳቢ ጉዳዮች ዋነኛው በፌዴራሉ መንግሥትና በትግራይ ክልላዊ መንግሥት መካከል የተፈጠረው መፋጠጥ ነው። ይህ ለምን እንደሆነ ሁለቱም ወገኖች የየራሳቸውን ምክንያት ይደረድራሉ፤ ግን ፖለቲካችን የቁጭት፣ የብሽሽቅና የአብሪት ሆኖ ቁጭ ስላለ ማንኛቸውም ወገን ሌላውን ሊሰማ ፈቃደኛ የሆነ አይመስልም። ታዲያ በዚህ መካከል ሁሉም የሚሆነውን ለማየት እጁን አጣጥፎና አፉን ዘግቶ ከተቀመጠ መፍትሄ ሊሆን የሚችል ነገር ለማግኘት አስቸጋሪ ነው። ይህ ሁኔታ እንዲቀየር ለማድረግ ይጠቅም እንደሆነ የግሌን አስተያየት ከዚህ በታች በአጭሩ አቀርባለሁ። ቀድሜ መናገር ያለብኝ ነገር የማቀርበው ሀሳብ መፍትሄ አይደለም፤ ወደ መፍትሄው ለመድረስ ግን አንደኛው መንገድ ነው ብዬ አምናለሁ። እንደኔ ሀሳብ መፍትሄው በአንድ ሰው ወይም በአንድ ቡድን እጅ ውስጥ አይደለም፤ መፍትሄው የሁሉም ወገኖች ግልፅና ቅን ውይይት ብቻ ነው።

    አቤቱታዬን ከፖለቲከኞቹ ይልቅ ለምሁራኑ ማድረግ የመረጥኩት ምናልባት ለግልፅነትና ለምክንያታዊነት እናንተ ትቀርቡ ይሆናል በሚል እምነት ነው። ፖለቲካ ማለት ውሸት ማለት መሆኑ በሚነገርባት ሀገር ፖለቲከኞቹም የትርጉሙን ትክክለኛነት እያረጋገጡልን በመምጣታቸው እነሱን ማመን አስቸጋሪ እየሆነብን መጥቷል። በሀገራችን ያለፉት አርባ እና ሀምሳ ዓመታት የፖለቲካ ታሪካችን ምሁራን ተብዬዎች የየራሳቸውን እንጂ የተለየ ሀሳብ ያለውን ወገን ለመስማት አለመፈለግ ትልቁ በሽታቸው ሆኖ ስለኖረ ፖለቲከኞችን ባናምን አይፈረድብንም። ለማንኛውም የመሰለኝን ላካፍላችሁና የሚሆነውን እንይ።

    ለትግራይ ምሁራን

    1. ውጥረቱ ከዚህ በላይ ከቀጠለ ምን እንደሚፈጠር መገመት ባይቻልም “ትግራይን ለመክበብና ለማንበርከክ ዘመቻ ተከፍቶብናል” የሚለውን ትርክት ከበቂ በላይ ወስደው የህልውና አደጋ ተደቅኖብናል በሚል ሀሳብ መውጫ የለኝም የሚል ሰው የሚያደርገውን አጉል ነገር እንዳያደርጉ ባላችሁ ሁሉ የግንኙነት መስመር ተጠቅማችሁ የፖለቲካ መሪዎቻችሁን ሀሳብ ለማረጋጋት መሞከር አለባችሁ። አሁን ባለንበት ሁኔታ ሊበጠስ ትንሽ የቀረው መካረር መሀል የምትለኮስ ትንሽ ፍንጣሪ እሳት ልናቆመው ወደማንችል የሰደድ እሳት የመቀየሯ ዕድል ከፍተኛ ስለሆነ በምንም ዓይነት ሁኔታ ግጭት የሚቀሰቅስ ርምጃ መውሰድ ይቅርታ የማያሰጠው ስህተት መሥራት ይሆናል። ተቃዋሚ ሆኖ የራስን ሀሳብ እያራመዱ በክርክሩና በውይይቱ መቀጠል እንደሚቻልና እንደሚገባ ሁሉም ማወቅ ይኖርባቸዋል።
    2. ከህወሓት መሪዎችና አክቲቪስቶች የሚሰማው የትግራይ ዋና ጠላት ብአዴንና አብን ናቸው የሚለውን አስተሳሰብ እንዳለ በመቀበል ለግጭት የሚጋብዝ አቋም ከመያዝ በመቆጠብ እንኳን የብዙ ሺህ ዘመናት የቅርብ ግንኙነት ያላቸው የአማራና የትግራይ ሕዝቦች ቀርቶ ምንም በማይተዋወቁ ወገኖች መካከል የሚነሳ ልዩነት ከጦርነትም በኋላ እንኳ የሚፈታው በጠረጴዛ ዙሪያ በሚደረግ ድርድር መሆኑን ተገንዝባችሁ ከከፍተኛ ጥፋት በፊት ለውይይትና ድርድር ራስን ማዘጋጄት እንደሚገባ ለትግራይ ፖለቲካ መሪዎች በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ማስረዳት ይኖርባችኋል። ምንም እንኳ ከትግራይ መንግሥት መሪዎች በተደጋጋሚ ለውይይት ዝግጁ ነን የሚል ነገር ቢሰማም ለውይይቱ ቅድመ ሁኔታ የማስቀመጥ አካሄድ መከተል ዝግጁነቱ ከልብ ለመሆኑ ጥርጣሬን ይፈጥራል። ፌደራል መንግሥቱን አጣብቂኝ ውስጥ የመክተት አካሄድ ቅንነት የጎደለው አካሄድ ነው። ስለዚህ በአሁኑ የሀገራችን ሁኔታ ከፍተኛ ስጋት ሆኖ የሚገኘው በፌዴራል መንግሥትና በትግራይ ክልላዊ መንግሥት መካከል ያለው ልዩነትና ፍጥጫ ስለሆነ ለሱ መፍትሄ እስካመጣ ድረስ ውይይቱና ድርድሩ በሁለቱ መካከል መካሄዱ ይጠቅም እንደሆነ እንጂ ጉዳት የሚኖረው አይመስለኝም።
    3. ምንም እንኳ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በፖለቲከኞች ግፊት በተፈጠሩ ልዩነቶች ምክንያት መራራቅ የተፈጠረ ቢሆንም በአማራና በትግራይ ምሁራን መካከል መሠረታዊና የማይታረቅ ልዩነት አለ ለማለት ስለማይቻል ተቀራርቦ ለመነጋገር የሚቻልበትን መንገድ ሁሉ ቅድሚያውን በመውሰድ ማመቻቸት አስፈላጊና ጠቃሚ ነው። ሀገር ማለት ቀላል ነገር እንዳልሆነ፥ አንዴ መናድ ከጀመረ ማንም ኃይል ሊያቆመው የማይችል መሆኑን ተገንዝበን አለብን የምንላቸውን ልዩነቶች በውይይትና በመተሳሰብ መንገድ እንጂ በሌላ በምንም መንገድ እንደማንፈታቸው መቀበል አለብን። ተያይዘን ከመውደቅ ተያይዘን መቆም ይመረጣል።

    ለአማራ ምሁራን

    1. ላለፉት ሦስት አስርት ዓመታት አማራው የእኩልነት ፀር እንደሆነ በመወሰዱና ከክልሉ ውጭ ያለው ተራና ለፍቶ አዳሪ የአማራ ተወላጅ የጥቃት ሰለባ በመሆኑ አማራው ድሮ ያልነበረውን የአማራነት ስሜት ይዞ ራሱን ለመከላከል በአማራነት በመደራጀቱ የትግራይም ሆነ ሌሎች የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች አማራው “ያጣውን የበላይነት ለማስመለስ የሚታገል” ሆኖ እንዲታይ አድርጎታል። በዚህ የተነሳ የአማራውን መደራጀት የስጋት ምንጭ አድርጎ ማየት የተለመደ ሆኗል። ይህ ስሜት ለውይይትና ድርድር እንቅፋት እንዳይሆን አማራው ሌላውን የመጫን ምንም ዓይነት ፍላጎት እንደሌለው ደጋግሞ ማስረዳትና በተግባርም ከሌሎች ወንድም የኢትዮጵያ ሕዝቦች ጎን በመቆም ማረጋገጥ ይገባል። አሁን እየታየ ያለው ሁሉም ደረሰብኝ የሚለውን ችግርና አደጋ በተናጠል ለመቋቋም የሚደረግ አካሄድ አንዱ የሌላው ችግርና ጉዳት የሱም መሆኑን በሚያሳይ አካሄድና ተግባር መቀየር አለበት። ለዚህም አማራው ምንም እንኳ በሱ ላይ የደረሰውና እየደረሰ ያለው ችግር ከፍተኛና ጊዜ የማይሰጥ ቢሆንም የሌሎች ወንድምና እህቶቹ ኢትዮጵያውያን ችግርና ጉዳት የሱም መሆኑን፥ ለመፍትሄውም የራሱን አስተዋፅዖ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን በተቻለው ሁሉ ማሳየት አለበት።
    2. በዚህ ረገድ ከትግራይ ወንድም ሕዝብና ከልጆቹ ምሁራን ጋር ተቀራርቦ ለመነጋገርና ልዩነቶችን ለማጥበብ ያለውን ዝግጁነት ቅድሚያ በመውሰድ በተግባር ማሳየት ተገቢ ነው። ይህ የሚደረገው በተሸናፊነትና በአጎብዳጅነት ስሜት እንዳልሆነ አስረግጦ በመናገር የጋራ የሆነ ሀገር የማዳን ጥረቱን በሆደ ሰፊነትና በከፍተኛ የኃላፊነት መንፈስ ማራመድ ያስፈልጋል። ይህን ለማድረግም አሉ የተባሉ የግንኙነት መስመሮችን ሁሉ በመጠቀም ከትግራይ ምሁራን ጋር ለመወያየት ዝግጁነትን መግለፅ ይጠቅማል። ሀገርን ለማዳን እስከጠቀመ ድረስ ተቃራኒን ግማሽ መንገድ ድረስ ሄዶ ማግኘት ጥበበኝነት እንጂ ተሸናፊነት ሊሆን አይችልም።
    3. ፅንፈኛ የሆነ አቋም በማንም ይያዝ በማን አውዳሚ መሆኑን ማወቅና ፅንፈኛ ወደሆነ አቋም የሚደረግን ግፊት መቋቋም እጅግ አስፈላጊ ነው። በዚህ ረገድ ልክ እንደ አንዳንድ የትግራይና የኦሮሞ አክቲቪስቶች አንዳንድ የአማራ አክቲቪስቶችም የሚያራምዱትን ፅንፈኛ አቋም መታገል ተገቢ ነው። የሁሉም ጥሩ ነገር ምንጭ አማራ፥ የዚች ሀገርም መሥራችና ጠባቂ አማራ ነው የሚል አቋም ሌሎች ኢትዮጵያውያንን የሚያስከፋና የሚያርቅ፣ በመጨረሻም ሀገራችንን የሚጎዳ መሆኑን ማመን ያስፈልጋል። ሀገራችን የምትድነው በሁላችንም ጥረት እንደሆነ፥ ለዚህም ሁሉም እኩል ድርሻ እንዳለው መቀበል ይገባል። ይህ ሲሆን ጠንካራና ሁሉንም በእኩል ዓይን የምታይ ሀገር ይኖረናል። ለዚህ ውጤት የትግራይና የአማራ ምሁራን ትልቅ ድርሻ አላችሁ። ይህንን ኃላፊነታችሁን ለመወጣት አንዱ አንዱን ሳይጠብቅ ቅድሚያውን ወስዶ በመነጋገር መፍትሄ መፈለግ ይጠበቅባችኋል። ሀገራችን ከአንድ ወይም ሌላ የፖለቲካ ድርጅት፣ ከአንድ ወይም ሌላ የፖለቲካ ሰው፣ ከአንድ ወቅት የፖለቲካ እብደት በላይ ነች። ይህ ሁሉ ሲያልፍ “ሊያልፍ ውሀ አደረገኝ ድሀ” ከማለት ያውጣን!!

    አወል እንድሪስ (ዶ/ር)

    ዶ/ር አወል እንድሪስ የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት (UNESCO) አቅም ግንባታ ዓለምአቀፍ ተቋም የአፍሪካ መርሀግብር ተጠሪ (Program Officer, UNESCO International Institute for Capacity Building, Africa) ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ይድረስ ለትግራይና ለአማራ ምሁራን

    #16580
    Anonymous
    Inactive

    የወቅቱ አብይ ጥያቄ – የህወሓትን ሀገር አፍራሽ፣ ሕዝብ አጫራሽ ሴራ በጋራ ቆመን፣ በአንድነት በመንቀሳቀስ ማምከን ነው
    አቶ ነአምን ዘለቀ

    ሰላም ወገኖቼ፥

    የወቅቱ አብይ ጥያቄ ኢትዮጵያ ሀገራችንንና ኢትዮጵያዊነት ከህወሓት ሀገር አፍራሽ፣ ሕዝብ አጫራሽ ሴራ በጋራ ቆመን፣ ከዳር እሰክዳር በአንድነት በመንቀሳቀስ ማምከን ነው። መሆን ወይንም አለመሆን ነው ለእያንዳዱ ዜጋ የቀረበው ጥያቄ!

    የክፋት፣ የነውር፣ የመሰሪነት ጥግ የሆኑት፣ ይህ ነው የማይባል ዘረፋ፣ ዘረኝነትና ግፍ በሚሊዮኖች ዜጎች ላይ የፈጸሙ፣ በእውነቱ ቃላትም የማይገልጻቸው የህወሓት መሪዎች ኢትዮጵያን በበላይነት ካልገዛን ትፈርሳለች የሚል ለዘመናት የቆየ ቅዠት እውን ለማድረግ እየተቅበዘበዙ መሆናቸውን የሰሞኑ ዋና መነጋገሪያ መሆኑ ይታወቃል። ከነበራዊ እውነታ ጋር የተጣሉ፣ የሞራልም የእእምሮም በሽተኞች በመሆናቸው የ27 ዓመት የክፋት፣ የዘረፋ፣ የከረፋ ዘረኝነታቸው ውስጥ ፍዳውን ሲያይ የነበሩ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ዜጎች የሚረዳው መሆኑ ግልጽ ነው።

    ከለውጡ በኋላ ወደ ስልጣን የመጣው አመራር የነዚህን ጉዶች ባህርይና ለዘመናት የተተበተበ በሽታ በሚገባ ተገንዝቦ፣ ስትራቴጂም ነድፎ ህወሓትን የማዳከም ልዩ ልዩ እርምጃዎችን መወሰድ ይገባው ነበር። ያ ግን አልተደረገም። በተለይም ወንጀለኛውን ጌታቸው አሰፋ ሕግ ፊት እንዲቀርብ የፌደራል መንግሥቱ ሲጠይቅ አናስረክብም ባሉ ጊዜ፥ በሀገሪቱ ልዩ ልዩ ክፍሎችም ግጭት ለመፍጠር በርካታ የሳቦታጅ ሥራዎች ማደራጀታቸው፣ መቆስቆሳቸው በሚገባ የሚታወቁ ሆነው ሳለ፥ ፈዴራል መንግሥቱ ከጦርነት በመለስ ሁሉንም የመንግሥት ማድረግ አቅም መጠቀምና ህወሓትን አይቀጡ ቅጣት መቅጣት ነበረበት። በቅርብ ሳምንት በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል በአማራ ማኅበረሰብ አባላት ላይ የተደረገውን አሰቃቂ ጭፍጨፋ በገንዘብና በመሣሪያ ያገዙ፣ በክልሉ ሰፊ መሬት ያላቸው የህወሓት አባል የሆኑ ባለሃብቶች መሆናቸው የክልሉ መንግሥት ባለስልጣን ለኢሳት ጋዜጠኛ መሳይ መኮንን የተናገረውን ልብ እንበል።

    በመንግሥት አካባቢ ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ተንሠራፍቶ የነበረ ‘የት ይደርሳሉ?’ መሰል የተዛባና አደጋውን የመረዳት የማይመጥን አመለካከት ሳቢያም፣ ህወሓትን የልብ ልብ ሰጥቶ ኢትዮጵያን ወደ ጦርነት ለመክተት፣ በዚህም የትግራይንም ሆነ የሌላውን ኢትዮጵያዊ በጦርነት እሳት ለመማገድ ዛሬ ላይ የደረሰበት የለየለት እብደት እንዲደርስ ዕድል ባልተሰጠው ነበር፤ አጥፍቶ ከመጥፋትም አይመለሱም። ያ በሀገርና በሕዝብ ላይ የነበራቸውንም ዓይን ያወጣ የጥቂት ዘረኞች የበላይነት፣ ፈልጭ ቆራጭነት እንዳይመለስ አጥተውታልና አዲሱን እውነታ ፈጽሞ ተቀበለው በእኩልነት፣ በአቻነት ሊኖሩ በዘረኝነት፣ በትምክህትና በትእቢት የታጨቀው አእምሮአቸው አይፈቅድላቸውም።

    ለሁለት ዓመት ተኩል የተዘጋጁበት፣ ከጅምሩም ህወሓትና አጋሮቹ እንደ ጊዜ ቦንብ እንዲፈነዳ ቀብሩውት የነበሩት ሰፋፊ የማንነት ስንጥቆች፣ የብሔር ቅራኔዎችን ተጠቅመው ሀገሪቱን በቀውስ ውስጥ ለመክተት፣ ብሎም ለመበታተን ላሰፈሰፉ በየክልሉ ያደፈጡ ጽንፈኞችም ምቹ ሁኔታዎችንም ፈጥሯል። የህወሓት መሪዎች ለበርካታ ዓመታት የነደፉትን መሰሪ ‘ፕላን B’ የሆነውን አባይ ትግራይ-ትግራይ ትግሪኝ፣ ወዘተ… ለመመሥረት የሚችል መስሏቸው እየተንፈራገጡ ይገኛሉ። ለሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ግልጽ መሆን ያለበት የጦርነት እሳት ኢንዲቀጣጠል፣ ብሎም በመላው ኢትዮጵያ እንዲዛመት ያላቸውን ሁሉ በማድረግ ላይ የሚገኙት መሰሪዎቹ ጸረ-ኢትዮጵያ የህወሓት መሪዎች በጠላትነት የፈረጁት ጠ/ሚ ዐቢይ አህመድን ብቻ እንዳልሆነ ግልጽ መሆን ይገባዋል፤ ወይንም ፈደራል መንግሥቱ፣ የብልጽግና ፓርቲ አይደሉም።

    ይልቅስ ዓይን ቀቅሎ የበላው የሀሰትና የነውር ቋት የሆነው የስዩም መስፍንና ሌሎቹ የህወሓት መሪዎች መሠረታዊ ግብ ኢትዮጵያን የማፈራረስ ነው። በፍርስራሹም ላይ በዘረኝነት የታጨቀው የትግራይ ትግርኝ ሀገር መንግሥት የመመሥረት ቀቢጸ-ተስፋ እውን የማድረግ ግብ ነው። ይህ ነው አብይ ግባቸው። ለምን ቢባል የህወሓት መሪዎች ኢኮኖሚውን፣ መከላከያውን፣ ደህንነቱን፣ የውጭ ጉዳዩንና ባጠቃላይም በኢትዮጵያ ሀገረ መንግሥት ላይ በበላይነት የማያሸከረክሩባት፣ ፈላጭ ቆራጭና ሁሉን አድራጊ ፈጣሪ፣ ሌላው የእነርሱ አጎብዳጅ፣ ፈርቶና ተጎናብሶ የማይኖርባት የ27 ዓመቷ ኢትዮጵያ ማስቀጠል የማይችሉበት ነባራዊ ሁኔታን እንዴት ተቀብለው ሊኖሩ ይችላሉ?

    ልብ እንበል፤ ቆም ብለን በቅጡ እናስብ፤ ያቺ ኢትዮጵያ ዛሬ ላይ የለችም። ይህን እጅግ መራር እውነታ ሊቀበሉ ሊውጡት ደግሞ ፈጽሞ አልቻሉም። የእነ ስዩም መስፍን “ዓይናችሁን ጨፍኑና እናሞኛችሁ” የለየለት ውሸቶች፣ ማስመሰሎች፣ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም ቆመው፣ ሠርተው እንደነበር፣ ለሕዝብ ጥቅም የታገሉና ሲሠሩ እንደነበሩ ለቀባሪው ማርዳት ሙከራዎች ሁሉ ከዚህ ሃቅ የሚመነጭም ጭምር ነው። ይህን ሃቅ አስምረን ግልጽና ፍንትው አድርገን ማየት ቀዳሚው ተግባር ነው። ህወሓት ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ እውነተኛ ፍትህ፣ እኩልነት፣ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሞች የቆመበትና የሠራበት ሁኔታና ጊዜስ መቼ ነበሩ? ብለን ብንጠይቅ፣ እነ ስዩም መስፍን ነጋ ጠባ ሊያጭበረብሩን ከሚሞክሩት ውጭ ማንም አፉን ሞልቶ ሊመሰክር የሚችል ኢትዮጵያዊ የሚገኝ አይመስለኝም። ሀገሪቱን እንደ ቅኝ ተገዢ ሲመዘብሩ፣ በከረፋ ዘረኝነታቸውም ትግርኛ ተናጋሪ ያልሆነውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ እንደ የበታችና 3ኛ ዜጋ ሲያንገላቱ፣ ሲገፉ፣ በንቀት ሲመለከቱ፣ ሲዘርፉና ሲገድሉ የነበረው መራራ ታሪክ ሁሉም ያለፈበት የቅርብ ጊዜ አስነዋሪውና አሳፋሪው ትሪካቸውና የእኛም የኢትዮጵያውያን ቁስል ነውና።

    ለምን? ምክንያቱም ከጅምሩም የተነሱበት መሠረት በመሆኑ ለአያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ግልጽ መሆን ይገባዋል፤ መወናበድ ማክተም አለበት። ለአወናባጆችና ውዥንብር ነዥዎችም ሰለባ መሆን የለብንም፤ ብዙዎች ከዳር ቆሞው ጉዳዩ የዐቢይ አህመድ እና የህወሓት ጠብ አድርጎ መመልክት በሀገርና በሕዝብ ላይ ትልቅና ከባድ አደጋ፣ እንደ ሀገርና ሕዝብ ለውድቀትም ሊዳርግ የሚችል፣ ይህ ነው ተብሎ ሊገመት የማችል ዋጋ የሚያስከፍል ስህተት ይሆናል። አለፍ ሲልም ቅጥረኞችና ከራሳቸው ጥቅም በላይ ለጋራ ሀገር፥ ለኢትዮጵያ ሰፊ ሕዝብ ማሰብ የማይችሉ፣ ዐቢይን ሰለጠሉ ኢትዮጵያም ሆነች ሀገረ መንግሥቱ ቢፈርስ፣ በፍርስራሹ ላይ ስልጣን የሚያገኙ የሚመስላቸው እኩዮች “ፓለቲካ ሊያስተምሩን” እንደሚዳዱት የህወሓትና የፌደራል መንግሥቱ/የብልጽግና ጠብና ግጭት ተደርጎ መወሰድ የለበትም። የህወሓት መሪዎች እንቅስቃሴ በሀገራችን ኢትዮጵያና በሕዝብ ሰላም፣ ደህነትና መረጋጋት ላይ የመጣ የህልወና አደጋ ተደርጎ መወሰድ ያለበት ነው።

    የዛሬው አብይ ጥያቄ ኢትዮጵያ ሀገራችንንና ኢትዮጵያዊነት ከህወሓት ሀገር አፍራሽ፣ ሕዝብ አጫራሽ ሴራ ማምከን ነው። መሆን ወይንም አለመሆን ነው ለእያንዳዱ ዜጋ የቀረበው ጥያቄ።

    ነአምን ዘለቀ

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የወቅቱ አብይ ጥያቄ የህወሓትን ሀገር አፍራሽ ሴራ በአንድነት በመንቀሳቀስ ማምከን ነው

    #16603
    Anonymous
    Inactive

    ገዳዮችና አስገዳዮች ሆይ! በጭራሽ አይሳካላችሁም!!!
    (መቅደስ ፀጋዬ)

    ገዳዮችና አስገዳዮች ሆይ! በጭራሽ አይሳካላችሁም!!!

    የሞታችሁ፣ የቆሰላችሁና በገዛ ሀገራችሁ የተፈናቀላችሁ ወገኖቼ!!!

    ህመማችሁ ህመሜ፣ ሞታችሁ ሞቴ ነው!!! አቤት ስንቱን የጭካኔ ዓይነት ዓየን!!! አማራ በመሆናችሁ ብቻ ይህንን ግፍ የተቀበላችሁ ወገኖቼ፥ ነፍሳችሁን እግዚአብሔር አምላክ በገነት ያኑረው!!! በየዋሁ ሕዝብ ላይ የተፈፀመውን ይህን በደል እግዚአብሔር ያያል። ከሰው በላይ የእርሱን ፍርድና ከለላነት እንጠብቃለን!!! እስትንፋሴ እስክታልፍ በሀገሬ ተስፋ አልቆርጥም!!!

    ገዳዮችና አስገዳዮች ሆይ! በጭራሽ አይሳካላችሁም!!!

    ሕዝባችን ተባብሮና ተከባብሮ ብቻ ሳይሆን ተዛምዶና ተዋሕዶ ለዘመናት የኖረ ሕዝብ በመሆኑ ምን ያክል የላቀ ሰላማዊ ሕዝብ እንደሆነ ያስመሰከረ ሕዝብ ነው። የናንተ ምኞት ግን አሁን እየታየ ያለው ማንነትን መሠረት ያደረገ ግድያና ማፈናቀል በሕዝቦች መካከል የተፈጠረ መስሎ እንዲታየን ማድረግና እርስ በርሳችን መተላለቅ እንድንጀምር መሆኑን እናውቃለን። በጭራሽ አይሳካላችሁም!!! እንእደናንተ ምኞትና ጥረት ቢሆን ኖሮ ሀገራችን የአንዲት ጀንበር እድሜ ባልኖራት ነበር፤ ግን አልተሳካላችሁም!! አይሳካላችሁምም!!

    የምወዳችሁ ወገኖቼ፥

    ይህ ወቅት በውስጣችን ብዙ ልዩነቶች ያሉበትና የውጭ ጠላቶቻችን ደግሞ ያለንበትን ሁኔታ እንደጥሩ አጋጣሚ ለመጠቀም እየተሯሯጡ ያለበት ጊዜ እንደሆነ ሁላችንም እንደምንገነዘበው እምነት አለኝ። ታዲያ ጠላቶቻችን የሚያተርፉት እርስ በርሳችን መበላላት የጀመርን ቀን ሲሆን፥ የሚከስሩት ደግሞ በትዕግስትና በፍጹም ሰላማዊነት ይህንን አስቸጋሪ ጊዜ ማለፍ ስንችል ብቻ ነው። ዓላማቸው እርስ በርሳችን እንድንጫረስ ነው ካልን፥ ድላችን ደግሞ አንድነታችንንና ሰላማችንን ጠብቀን መቆየታችን ላይ ነው የሚሆነው። ስለዚህ እያንዳንዳችን ሀገራችንን የምንወድ ዜጎች ሁሉ የአካባቢያችንን ሰላም በንቃት ከመጠበቅ ባሻገር፥ ተቃውሞዎቻችንንና ቁጣችን እንኳ ሳይቀር የሀገራችንን ሰላምና አንድነት በማያናጋ መልኩ ማድረግ እንዳለብን መረዳት ያስፈልገናል። ሰላም ላይ የሚደረሰው በሰላም መንገድ ብቻ ስለሆነ።

    ከመንግሥት በኩል ደግሞ እጅግ ፈጣንና የሚታይ እርምጃ ሲወሰድ ማየት እንፈልጋለን።

    ከሁሉም በላይ እግዚአብሔር ሀገራችንንና ሕዝቦቿን ይጠብቅልን!!

    መቅደስ ፀጋዬ

    መቅደስ ፀጋዬ ኢትዮጵያ ውስጥ ዝናን ካተረፉ የፊልም ባለሙያዎች አንዷ ስትሆን፥ የተለያዩ ፊልሞችን ፕሮዲዩስ ከማድረግና በተለያዩ ፊልሞች ላይ ከመተወን በተጨማሪ (ትስስር፣ የ አዳም ገመና፣ ዘራፍ፣ የከረመ…) ራሷ የመሠረተችውና በዋና ሥራ አስኪያጅነት የምትመራው መቅዲ ፕሮዳክ ሽን በተመልካች ዘንድ ተወዳጅ የነበሩትን ሞጋቾች እና ግማሽ ጨረቃ የተሰኙ ተከታታይ የቴሌቭዥን ድራማዎችን፥ እንዲህም መቅዲ ሾው የተሰኘ የቴሌቭዥን ሳምንታዊ መርሀግብር አቅርቧል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    መቅደስ ፀጋዬ

    #16627
    Anonymous
    Inactive

    በህወሓትና በውጭ ኃይሎች የተቃጣውን የእብሪት ጦርነት በጋር ከመመከት ውጭ ሌላ አማራጭ የለም
    ነአምን ዘለቀ

    በሀገራችን አንድነትና በኢትዮጵያ ሕዝብ ደህንነት ላይ በህወሓትና በውጭ ኃይሎች የተቃጣውን የእብሪት ጦርነት በጋር ከመመከት ውጭ ሌላ አማራጭ የለም።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ከባድ የህልውና አደጋ፣ ከባድ ፈተና ውስጥ እየገባች ነው። በእብሪት፣ በበታችነት፣ በዘረኝነት በሽታ የተለከፈው፣ በኢትዮጵያ ላይ የነበረውን ሁለንተናዊ የበላይነት ያጣው የመሰሪው የህወሓት መሪዎች ትግራይ ወስጥ በሚገኘው የሰሜን እዝ የመከላከያ ካምፕ ላይ የኃይል እርምጃ በውሰድ ሀገሪቱን ወደ ጦርነት ለመውሰድ የመጀመሪያ እርምጃቸውን እንደወሰዱ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት የተላለፈው መልዕክት ያሳያል።

    1ኛ) የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዳር እስከ ዳር በጋራ ከመቆም ሌላ አማራጭ የለም። በልዩ ልዩ የህገሪቱ ችግሮች ከመንግሥት ጋር የሚገኙ ልዩነቶች ሁሉ ወደ ጎን ማድረግ አማራጭ የለውም።

    2ኛ) በሀገራችን አንድነትና በሕዝብ አብሮነት ላይ የተቃጣውን የህወሓት እብሪት በጋር ከመመከት ውጭ ሌላ አማራጭ የለም።

    3ኛ) የህወሓቶች ዒላማ የፌደራሉ መንግሥት ብቻ አይደለም፤ ይህ ጥቃት የተቃጣው በኢትዮጵያ ህልውና፣ በሕዝባችን ሰላም፣ ደህነትና አብሮነት ላይ ነው።

    4ኛ) የህወሓቶች ጥቃት በመከላከያ ሠራዊትበብልጽግና ፓርቲና እና በመንግሥት ላይ ብቻ አይደለም፤ የህወሓቶች እብሪትና ጠብ አጫሪነት እነሱ ያልገዟት ኢትዮጵያ እንድትፈርስ፣ ብሎም እነሱ የሚያስታጥቁትና የሚደግፉዋቸው ኃይሎች በቤኒሻንጉል፣ በወለጋ እንደተደረጉት እጅግ ዘግናኝና አረመኔያዊ ግድያዎች በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች እንዲደደገሙ በማድረግ ኢትዮጵያን ማፍረስ ነው። ይህን በጋራ ህልውናችውን ላይ የተቃጣ ከባድ አደጋ ኢትዮጵያውያን ሁሉ በጋራ ሆነን መመከት አለብን።

    5ኛ) ሕወሓት፣ ኦነግ ሸኔ፣ ግብጽ፣ እና በዲያስፓራም በሀገር ውስጥ የሚገኙ ቅጥረኖቻቸው ኢትዮጵያን ለማተራመስ ከቻሉ ማዕከላዊ መንግሥቱን ዳግም ለመቆጣጠር፥ ካልቻሉም ደግሞ ህወሓት አባይ ትግራይን ይመሠርታል፤ ግብጽም የአባይን ግድብ ህልውና እና አገልግሎት ለማምከን ትችላለች፤ ኦነግ ሸኔም የኦሮሚያ ሪፑብሊክ ይመሠርታል። አነዚህን ዋና ዒላማቸው አድርገው በጋራ እየተንቀሳቀሱ መሆኑ ግልጽ ነው። ከዚያ ስለሚከተለው ምድራዊ ሲኦል ህወሓትና የኦነግ ሽኔ የሞራልና የስብዕና ድኩማኖች ፈጽሞ ሊረዱ የሚችሉት አይደለም።

    ኢትዮጵያውያን ሁሉ፥ በዲያስፓራ የምንገኝ ሀገር ወዳዶች ሁሉ፥ በሀገር ውስጥም ወጣቱ፥ ጀግናው የቀድሞ ሠራዊት አባላት ሁሉ ከዳር አስከ ዳር በጋራ ሆነን፣ በጋራ ቆመን ከማዕከላዊ መንግሥትና ከመከላከያ ሠራዊቱ ጀርባ በመሰለፍ፣ አሰፈላጊውን ድጋፍና መስዋዕትነት መክፈል አለብን። የሀገራችንን ህልውና፣ የሕዝብን ሰላምና ደህነት፥ የጥፋት፣ የዘረኝነት፣ የእብሪት ክምችት ከሆነው ከህወሓትና ግብረ-አበሮቹ ለመታደግ በጋራ መቆም፣ በጋራ መሰለፍ የወቅቱ [ዋና ተግባራችን መሆን አለበት።]

    ይህን የማያደርግ የታሪክ ተወቃሽ ብቻ ሳይሆን የራሱንም፣ የቤተሰቡንም ዕጣ ፈንታ ለህወሓቶች ዳግማዊ የክረፋው ዘረኝነት፣ ጭካኔና ባርነት መዳረግ ይሆናል፤ ከዚያም ሲያልፍ ሀገር-አልባ መሆንም ይከተላል።

    ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድም ሆነ ከብልጽግና ጋር ያለ ማናቸውም ልዩነት ወደ ጎን አድርገን የመጣብንን የህልወና አደጋ በጋራ መመከት የወቅቱ አብይ ተግባር ነው!!

    ነአምን ዘለቀ (ከአሜሪካ)

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    በህወሓት የተቃጣው የእብሪት ጦርነት

    #16763
    Anonymous
    Inactive

    ሰላም ነሺው የክህደት ቡድን ላይ የሚወሰደው ሦስተኛውና የመጨረሻው ምዕራፍ
    (ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ)

    የተከበራችሁ የሀገራችን ሕዝቦች፥

    በትግራይ ክልል የጀመርነው ሕግን የማስከበር ርምጃ ሁለተኛ ምዕራፍ ተጠናቅቋል። አሁን በመጨረሻውና በሦስተኛው ወሳኝ ምዕራፍ ላይ እንገኛለን።

    እየወሰድን ያለነው ሕግን የማስከበር እርምጃ ሦስት ምዕራፎች እንዳሉት ቀደም ብለን የገልጸን ሲሆን፤ የመጀመሪያው ምዕራፍ፥ በገዛ ወገኑ የተጠቃውን የመከላከያ ሠራዊታችንን አሰባስበንና አጠናክረን፣ ተቋርጦ የነበረውን የእዝ ሰንሠለቱን ወደ ቦታው መልሰን ግዳጁን እንዲወጣ ማስቻል ነበር። በዚህም መሠረት ሠራዊቱ በከፍተኛ እልህ፣ ቁጭትና ወኔ ከገጠመው አደጋ በፍጥነት አገግሞ፣ የሕዝቡን ከፍተኛ ድጋፍ በልቡ ይዞ የሀገር ክህደት የፈጸመውን የህወሓት ቡድን ለሕግ ለማቅረብ በተለያዩ አቅጣጫዎች ተንቀሳቅሷል።

    የእርምጃው ሁለተኛ ምዕራፍ ዋና ዓላማ፥ የህወሓትን ጁንታ ከየአካባቢው እያስለቀቀ፣ አቅሙንም ከጥቅም ውጭ እያደረገ፣ ሕዝቡን ከዚህ የክህደት ቡድን ይዞታ ነጻ በማድረግ፣ የመሸገበትን የመቀሌ ከተማ መክበብ ነበር። ከመቀሌ ውጭ ያለውን ህወሓት የያዘውን ቦታ ነጻ በማውጣት፤ የተዘረፉ ትጥቆችንና ካምፖችን መልሶ በመያዝ፤ የክህደት ቡድኑ የዘረፋቸውን ስትራቴጂያዊ የሆኑ መሣሪያዎችን ለውድመት ሳያውላቸው በፊት ከጥቅም ውጭ ማድረግ፤ በግዳጅ የያዛቸውን የሠራዊታችን አባላት ማትረፍ፤ የተሠውትን መቅበር እና አደጋ የሚደርስባቸውን ዜጎች መታደግ የሁለተኛው ምዕራፍ እርምጃ ዝርዝር ዓላማዎች ነበሩ።

    በዚህ መሠረት በዳንሻ፣ ሑመራ፣ ሽሬ፣ ሽራሮ፣ አክሱም፣ አድዋ፣ አዲግራት፣ አላማጣ፣ ጨርጨር፣ መሖኒ፣ ኮረምና በሌሎችም ቦታዎች በተወሰደ እርምጃ ሠራዊታችን ሕዝብ እየታደገና ድል እያደረገ ተጉዟል። ሕዝብ ለመታደግ በነበረው ዓላማ በተቻለ መጠን ሕግ የማስከበር እርምጃው በከተሞች አካባቢ ጥፋት እንዳያስከትሉ እና ሰላማዊ ዜጎች ዒላማ እንዳይሆኑ፤ ታሪካዊ ቅርሶች፣ የሀይማኖት ቦታዎች፣ የሕዝብ መገልገያዎች፣ መሠረተ ልማቶች፣ የተፈጥሮ ሀብቶችና የመሳሰሉት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት እንዳይደርስባቸው ከፍተኛ ጥንቃቄ ተደርጓል። ምንም እንኳን የክህደት ቡድኑ የጥፋቱ ደረጃ ሰፊ እንዲሆን ቢፈልግም፥ በሕግ ማስከበር እርምጃችን ወቅት፥ የአየር ኃይል አውሮፕላኖቻችን ለሕዝቡ በነበራቸው ከፍተኛ ጥንቃቄ፣ ወደ ዒላማዎቻቸው የቀረበ አንድም ሰው እንኳን ከገጠማቸው የታጠቁትን ትጥቅ ይዘው እስከ መመለስ ደርሰዋል።

    በዚህም፥ ምንም ዓይነት ኃላፊነት የማይሰማው ቡድኑ በሀይማኖት ተቋማትና በቅርሶች አካባቢ ተኩስ እንዲኖር የነበረውን ፍላጎት፣ በሠራዊቱ ተልዕኮን በጥበብ የማከናወን ችሎታ አማካኝነት የቡድኑ ፍላጎት ሊመክን ችሏል። ነጻ በወጡ አካባቢዎች በሀገር ሽማግሌዎች አማካኝነት ሕዝቡን መልሶ እንዲደራጅ፣ በመከላከያ ሠራዊቱ አማካኝነት የተጎዱ ወገኖቻችን እንዲደገፉ፣ ሕዝቡ የተፈጸመውን ነገር በትክክል እንዲረዳና ራሱን የሂደቱ አካል ለማድረግ ተችሏል። የተበላሹና የተበጣጠሱ ማኅበራዊ ተቋማትን፣ የመገናኛና የትራንስፖርት መሠረተ ልማቶችን በመጠገን፣ ሕዝቡ የሰላም አየር መተንፈስ ጀምሯል።

    ሁለተኛው የርምጃው ምዕራፍ ሕዝቡን የታደገ፣ የጁንታውን አከርካሬ ሰብሮ አቅሙን ወደ መቀሌ ማጥበብ ተችሏል።

    አሁን የቀረው ጉልበት መቀሌ ላይ ያደራጀው ምሽግ እና አልፎ አልፎ የሚያሰማው ከንቱ ፉከራ ነው። በዚህ ሕግን የማስከበር እርምጃ ወቅት ሕዝባችን ከመከላከያ ሠራዊቱ ጎን መሆኑን በግልጽ አሳይቷል። ህወሓት ስለ መከላከያ ሠራዊቱ የነዛው ፕሮፓጋንዳም ስሕተት መሆኑን የትግራይ ሕዝብ በዓይኑ ለማየት ችሏል። የሠራዊቱን ደግነትና ከጥፋት ለመታደግ የከፈለውን መስዕዋትነት ሕዝቡ ራሱ መመስከር ጀምሯል። በየአካባቢው ከዕለት ጉርሱ እየቀነሰ ለሠራዊቱ በማብላት፣ የክህደት ቡድኑ የሚሄድባቸውን መንገዶች በመጠቆም፤ የተደበቁ መሣሪያዎችንና ልዩ ልዩ ቁሳቁሶችን በማጋለጥ ከሠራዊቱ ጎን ሆኖ የሚያስደንቅ ተጋድሎ ፈጽሟል። በዚህም የትግራይ ሕዝብ ቀድሞም በህወሓት የጥፋት መንገድ ምን ያህል እንደተንገሸገሸ በግልጽ አሳይቷል።

    ሠራዊቱ ሽሬ በገባበት ጊዜ ሕዝቡ በነቂስ ወጥቶ በሆታ ከመቀበሉም በላይ፣ ጁንታው ያስታጠቀውን ከ200 በላይ መሣሪያ ሰብስቦ ለመከላከያ አስረክቧል። ሠራዊታችን አክሱም በደረሰም ጊዜ ሕዝቡ ራሱ በክህደት ቡድኑ ቁጥጥር ሥር የዋሉ የሠራዊት አባላትን ነጻ አድርጎ፣ የቆሰሉትን አክሞና ተከባክቦ፣ በክብር ለመከላከያ ሠራዊቱ አስረክቧል። የአክሱም ሕዝብ የመከላከያ ሠራዊቱ ከእርሱ ጋር እንዲሆን ከመጠየቁም በላይ አብሮ ተሰልፎ የሕግ ማስከበሩ ዳር እንዲደርስ ቁርጠኝነቱን አሳይቷል። በተመሳሳይ ሠራዊታችን አዲግራት ሲገባ፣ ሕዝቡ ራሱ የተደበቁትን የልዩ ኃይልና የሚሊሻ አባላት እየያዘ ለመከላከያ አስረክቧል።

    በተቃራኒው የቆመው የክህደት ቡድን ስንትና ስንት የሀገር ሀብትና ጉልበት የፈሰሰባቸውን መሠረተ ልማቶችን እያፈረሰ፣ ትምህርት ቤቶችንና የጤና ተቋማትን ከጥቅም ውጭ እያደረገ፣ መንገዶችና ድልድዮችን እየደረማመሰ ሸሽቷል። የታሪካዊቷ አክሱም የአውሮፕላን ማረፊያ ላይ ጭምር ውድመት በማድረስ የቀጣይ ዓመታት የቱሪዝም እንቅስቃሴያችን ላይ ከፍተኛ ጠባሳ ጥሎ አልፏል። የክልሉ ነዋሪ የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ የሚያደርግባቸውን መንገዶች በዶዘር ማፈራረሱ ሳይበቃው፥ የመቀሌ ከተማን ልክ እንደ ጦርነት አውድማ ለማድረግ በመዛት ቅንጣት ታህል ኃላፊነት የማይሰማው መሆኑን በግልጽ አሳይቷል

    ውድ ኢትዮጵያውያን፥

    አሁን ሕግ የማስከበር ርምጃው ወደ ሦስተኛውና ወሳኙ ምዕራፍ ተሸጋግሯል። ሦስተኛው ምዕራፍ በመቀሌ የሚካሄደውና የክህደት ቡድኑን ለሕግ ለማቅረብ የሚደረግ የመጨረሻው እርምጃ ነው። የዚያኑ ያህል ከፍተኛ ጥበብ፣ ጥንቃቄና ትዕግስት የሚፈልግ እንደሆነ ግልጽ ነው።

    ይህ የክህደት ቡድን ለምንም ነገር ደንታ እንደሌለው፥ ለሕዝቡ፣ ለታሪኩ፣ ለባህሉ፣ ለቅርሱና ለእምነቱ ቅንጣት ርኅራሄ እንደሌለው በግልጽ አሳይቷል። ሁሉም ነገር ጠፍቶ እርሱ ብቻ ቢተርፍና ከሕግ ቢያመልጥ ደስተኛ ነው። በዚህም የተነሣ በመቀሌ ከተማ ውስጥ የሀይማኖት ተቋማትን፣ ሆቴሎችን፣ የመንግሥት ተቋማትን፣ የሕዝብ መኖሪያ መንደሮችን፣ ትምህርት ቤቶችን፣ ቅርሳ ቅሶችንና መካነ መቃብሮችን ሳይቀር እንደ ምሽግ ተጠቅሞባቸዋል። መጥፋቱ ላይቀር ብዙዎችን ይዞ ለመጥፋት ተዘጋጅቷል። ልክ በአንዳንድ ሀገራት እንደሚታዩት የሽብር ቡድኖች፣ ለሕዝብና ለሀገር ምንም ደንታ የሌላቸው አሸባሪዎች እንደሚያደርጉት ሁሉ፣ ይሄ የጥፋት ቡድን መቀሌን እንደ ሕዝብ መኖሪያነት ሳይሆን እንደ ጦር አውድማነት ቆጥሯታል።

    በዚህ ቡድን ምክንያት እንዲሞቱ የተገደዱት ነዋሪዎች ዜጎቻችን እንደመሆናቸው መጠን እና የሚወድመውንም ከተማ ነገ መልሶ ለመገንባት ዞሮ ዞሮ የእኛው ኃላፊነት እንደመሆኑ መጠን በመቀሌ የሚኖረን የሕግ ማስከበር እርምጃችን፥ ጉዳትን እጅግ በቀነሰ መልኩ መከናወን እንዳለበት እናምናለን። ስለዚህም፥ የመቀሌ ከተማን ከከፋ ጉዳት ታድገን ዘመቻውን በድል የምናከናውንበትን መንገድ እንደምንከተል ለመግለጽ እወዳለሁ። መንግሥት ይሄንን የሚያደርገው በዚህ የክህደት ቡድን የተነሣ ሕዝብና ሀገር እንዳይጎዳ ከመፈለግ ነው።

    በመሆኑም፥

    አንደኛ፡- የመቀሌ ከተማ ነዋሪዎች፥ በጀመርነው ሕግን የማስከበር እርምጃ ቁልፍ ተዋናዮች እንድትሆኑ፣ ከሠራዊታችን ጎን በመቆም ይሄንን የክህደት ቡድን አባላት ለፍርድ በማቅረብ ወሳኝ ሚናችሁን እንድትወጡ ጥሪ እናቀርባለን። ለጥቂት ስግብግብ ጁንታዎች ሲባል አንድም ሰው መሞት፣ አንዲትም ንብረት መውደም የለበትም።

    ለዚህም የእናንተ ትብብር አይተኬ ሚና የሚጫወትና ብዙ ጉዳቶችን እንደሚያቀል እሙን ነው።

    ሁለተኛ፡- የክህደት ቡድኑን ዓላማ በማስፈጸም ላይ ያላችሁ የትግራይ ልዩ ኃይልና ሚሊሻ አባላት፥ አሁንም ቢሆን እጃችሁን በሰላም ለመስጠት ጊዜው አልረፈደም። ሕግ የማስከበር እርምጃው የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ መሆናችንን ተረድታችሁ የማያዳግመውን ዕድል እንድትጠቀሙበት፤ ከአሁኗ ሰዓት ጀምሮ ባለው በ72 ሰዓታት ውስጥ እጃችሁን በሰላም ለመንግሥት እንድትሰጡ የመጨረሻ ጥሪያችንን እናቀርብላችኋለን።

    ሦስተኛ፡- የጁንታው አባላት፥ የጥፋት ጉዟችሁ ጀንበሯ እየጠለቀች መሆኑን አምናችሁ፣ ከማትወጡበት ቅርቃር ውስጥ መግባታችሁን ተገንዝባችሁ በቀጣይ 72 ሰዓታት ውስጥ እጃችሁን በሰላም እንድትሰጡ እንጠይቃችኋለን፤ የመጨረሻዋን ዕድል ተጠቀሙበት። ተጨማሪ የሕዝብ እልቂት ከመፍጠርና ከተማ ከማውደም ተቆጥባችሁ ከታሪክ ውግዘት እንድትድኑ ጥሪ እናቀርባለን።

    በመጨረሻም መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲረዳው የምንፈልገው ነገር ቢኖር፥ ሦስተኛውን ምዕራፍ የሕግ ማስከበር እርምጃ ከማከናወን ጎን ለጎን በጥፋት ቡድኑ ምክንያት ቀያቸውን ጥለው ወደ ተለያዩ አካባቢዎች የሸሹ ወገኖቻችንን ለመመለስ፤ የተፈናቀሉትን መልሶ ለማቋቋም፤ መሠረተ ልማቶችን ለመጠገን፤ ነጻ የወጡ አካባቢዎች ላይ የሚኖሩ ዜጎች ወደ መደበኛ የሕይወት እንቅስቃሴያቸው እንዲመለሱ ለማድረግ በሁሉም ረገድ ዝግጅት አድርገናል። ወደ ትግበራ ስንገባ ከእጃችን እንዳያጥር እና ዓይናችንን ወደ ሌሎች እንዳናማትር ሁሉም ኢትዮጵያዊ የበኩሉን ድጋፍ ለማድረግ እንዲነሳ ጥሪ እናቀርባለን። እኛ ኢትዮጵያውያን የቆየና የዳበረ እርስ በእርስ የመረዳዳት ባህል ስላለን፣ የማንንም የውጭ እጅ ሳንጠብቅ ወገኖቻችንን እኛው ልናቋቁማቸው ይገባል። ለዚህም በመንግሥትና በተለያዩ የማኅበረሰብ አንቀሳቃሾች አማካኝነት የተጀመረውን እንቅስቃሴ እንድትቀላቀሉ ስል ጥሪ አቀርባለሁ።

    ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራ፣ ተከብራና በልጽጋ ለዘላለም ትኑር!
    ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
    ኅዳር 13 ቀን 2013 ዓ.ም

    ሰላም ነሺው የክህደት ቡድን ላይ የሚወሰደው ሦስተኛውና የመጨረሻው ምዕራፍ (ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ)

    #17271
    Anonymous
    Inactive

    ቀጣዩን ሀገር-አቀፍ ምርጫ ባሰብን ጊዜ…
    (የብሔር ፖለቲካ እና መጪው የኢትዮጵያ ምርጫ)
    ጌታሁን ሄራሞ (ኢ/ር)

    በሀገራችን በምርጫ ዲሞክራሲ ሂደት ብሔርን መሠረት ያደረጉ ፓርቲዎችን ተከትሎ ከሚከሰቱ ተቃርኖዎች (paradoxes) ውስጥ አንዱም፥ ተወዳዳሪዎቹ መነሻ ላይ ብሔራቸውን ብቻ ወክለው ካሸነፉ በኋላ በድኅረ-ምርጫው 82 ብሔሮች የሚኖሩባትን ሀገርን ለመምራት መብቃታቸው ነው። ጅምር ላይ የአንድ ብሔር ውክልና ብቻ ያለው ተወዳዳሪ በምን አመክንዮ ነው 82 ወይም ከዚያም በላይ ብሔሮች የሚኖሩባትን ሀገር መምራት የሚችለው?

    ናይጄሪያ ውስጥ የብሔር ፓርቲዎች እንደ አሸን በፈሉበት ወቅት ከላይ የጠቀስኩት ግራ አጋቢ ውክልና አወዛጋቢ በመሆኑ በሂደት ሁለት ቅድመ ሁኔታዎች በፖሊሲ አውጪዎቹ ተቀመጡ። የመጀመሪያው “የትኛውም የብሔር ፓርቲ ሀገራዊ ስሜትን (national sense) የሚያንፀባርቁ አንቀፆችን በፕሮግራሙ ውስጥ በግልፅ ማስቀመጥ አለበት” የሚል ነበር። እናም ፕሮግራሙ ውስጥ የራሱን ጎጥ ጥቅምና ጥያቄ ብቻ የጠቀጠቀ የብሔር ፓርቲ ሀገርን መምራት አይችልም፤ በምርጫ ቦርዱም የመመዝገብ ዕድሉ የለውም። ሁለተኛው ቅድመ ሁኔታ ደግሞ… አንዳንድ የብሔር ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች የመጨረሻ ህልማቸው ትልቋን ናይጄሪያን መምራት ከሆነ በምርጫ ወቅት ከራሳቸው ክልል በዘለለ ሌሎች ብሔሮች በሚኖሩበት ክልሎችም ጭምር እንዲወዳደሩ የሚያስገድድ ነበር። በነገራችን ላይ ናይጄሪያ ብሔርን ከፖለቲካ ለማፋታት የተጠቀመችበት ዘዴ “positive banning” ተብሎ ይጠራል። ሂድ አትበለው ግን እንዲሄድ ግን አድርገው ዓይነት… (ብሔርን ከፖለቲካ ማፋታት ማለት የብሔር ብሔረሰቦች መብት ባህልና ታረክን አለማክበር ማለት እንዳልሆነ እዚህ ጋር ይሰመርልኝ፤ ብዙ ሀገሮች ጎጥ፣ ጎሳና ብሔር ወደ ፖለቲካ ሰፈር ድርሽ ሳይሉ የዜጎቻቸውን ባህልንና ራስን በራስ የማስተዳደር መብትን በአማራጭ የፌዴራል ዲዛይን ተግብረዋል።)

    በምርጫ ወቅት ብሔሩን ወክሎ የማታ ማታ ለሀገር መሪነት የሚበቃ መሪ፦

    1. በሥልጣን ወንበሩ ላይ እንደተቀመጠ ሀገራዊ ስሜትን አንፃባርቆ ሁሉንም ብሔሮች በእኩልነት መምራት ሲጀምር ቀደም ሲል ውክልናውን በሰጠው በገዛ ብሔሩ ዘንድ እንደ ከሀዲ ይቆጠራል።
    2. ሌሎች ብሔሮችን በእኩልነት ከመምራት ይልቅ በመንግሥታዊ ተቋማት ምሥረታና በሌሎች ሲቪክ መሥሪያ ቤቶች መዋቅር ውስጥ የብሔሩን ተወላጆች ብቻ እየመረጠ የሚሾም ከሆነ ደግሞ በሌሎች ብሔሮች ዘንድ “ተረኝነት”ን እንደሚተገብር፣ ወገንተኛና ኢ-ዲሞክራሲያዊ መሪ ሆኖ ይከሰሳል።

    ይህ የብሔር ፓርቲ የሚያስከትለው አዙሪት የፖለቲካ ሳይንትስቶችንም የሚያወዛግብ ነው፤ በካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ የአንፃራዊ ፖለቲካ (comparative politics) ሳይንትስት የሆነው ፕሮፈሰር አረንድ ሊፓርት (Arend Lijphart) በብሔር ፖለቲካ የምትመራ ሀገር ካለች በመሪነቱ ሂደት ልዩ ልዩ ሀሳቦችን የሚያንፀባርቁ ልሂቃን በ“grand coalition” አጋዥነት ተሳባስበው በአመራሩ መሳተፍ አለባቸው ያለው ከላይ ያነሳሁትን ተቃርኖ ለመቀነስ በማቀድ ነው፤ እንዲሁም የብሔር ፖለቲካን የሚያራምዱ ሀገራት በየትኛውም መስፈርት መተርጎም ያለባቸው ተመጣጣኝ ውክልናን መሠረት ያደረገ የምርጫን ሥርዓት ነው ያለውም ከዚሁ ተነስቶ ነው። በተመጣጣኝ የውክልና ምርጫ መርህ ቢያንስ ሌሎች ተፎካከሪ ፓርቲዎች ወደ ፓርላማ በመግባት ሚዛኑን ሊያስጠብቁ ይችላሉ።

    ከፕሮፈሰር ሊፓርት በተጨማሪ የሕግና የፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፈሰሩ ዶናልድ ሆሮውዝም (Donald Horowitz) (በብሔር ግጭቶች ጥናት ጥርሱን የነቀለ ሳይንትስት ነው) የብሔር ፓርቲ መዘዝ የሚያመጣውን የአመራር ሳንካ ለመቀነስ “centripetal” ዲሞክራሲን መተግበርን በቅድመ ሁኔታነት ያስቀምጣል። ከላይ ናይጄሪያዎች ጥቅም ላይ እንዳዋሉት ያስቀመጥኩት ጽንሰ-ሀሰብ ባለቤትነቱ የፕሮፈሰር ሆሮውዝ ነው… የአንድ ብሔር ተወካይ የሆነው የምርጫ ተወዳዳሪ ሕልሙ ሁሉም ብሔሮች የሚኖሩባትን ሀገር መምራት ከሆነ መወዳደር ያለበት ከራሱ ቀዬ ባለፈ በሌሎችም ክልሎችም ነው… የሚለው መርህ የሆሮውዝ ነው።

    ከላይ ያነሳሁትን የብሔር ፓርቲን መዘዝ እኛ ኢትዮጵያዊያን ለፖለቲካ ሳይንሱ ባይተዋር ብንሆን እንኳ መሬት ላይ ወርዶ ያየነው እውነት ነው። ህወሓት በቀዬዋ ለምርጫ ተወዳድራ አመሻሽ ላይ ለሀገር መሪነት ስትበቃ የሀገሪቷን ተቋማት ያስወረረችው በራሷ ሰዎች ነበር፤ ሌላው ቀርቶ ክልሎችም ይመሩ የነበሩት በሞግዚትነት በራሷ ተወካዮች ነበር። ለዚህም ነበር በሀገሪቱ የፖለቲካ መዋቅር ውስጥ የ“አንድ ብሔር በላይነት” ስለመስተዋሉ ብዙዎች እሪታቸውን ሲያስደምጡን የነበረው!! የአሁኑ ጠቅላይ ሚኒስትር የሆኑት ዶ/ር አብይም በብሔር ፖለቲካ ባቡር ተሳፍረው ወደ ሥልጣን ከመጡበት ማግስት ጀምሮ ብዙዎች ስለ “ተረኝነት” ስጋት ተሰምቷቸው ድምፃቸውን ማሰማታቸው የአንድ ብሔር ውክልና ከፈጠረው ድባብ የተነሳ ነው። በብሔር ፖለቲካ ቦይ ፈስሶ ለሥልጣን መብቃት ፈተናው ለተሿሚውም ቢሆን ብዙ ነው።

    በነገራችን ላይ አሁን የታሪክ አጋጣሚ ሆኖ ሀገራችን እየተመራች ያለችው የብሔር ፖለቲካ ውልዶች በሆኑ የፖለቲካ ሰዎች ነው። ምናልባትም በቀጣዩ ምርጫ አሸናፊዎቹ በቦሌም ይሁን በባሌ እነሱ ሊሆኑ ይችላሉ። ሀገራችን ብሔርን ብቻ መንደርደሪያ ካደረገው የፖለቲካ ሥርዓት በተለየ ሌላ ዓይነት የፌዴራል የአስተዳደር መዋቅር እስከሚያጋጥማት ድረስ ገዥው የብልፅግና ፓርቲ ከሀገራችን የፖለቲካ አውድ በሚስማማ መልኩ የነአረንድ ሊፓርትንና የዶናልድ ሆሮውዝን ጽንሰ-ሀሰቦችን ቢያጤን መልካም ነው። የብሔር ፖለቲካ ያመጣብን መዘዝ ሀገር በቀል በሆኑ እሳቤዎች ብቻ እልባት የሚያገኝ አይደለም። ሐኪሞች በሀገር ውስጥ ለማከም የሚያዳግታቸውን በሽታ ከአቅማችን በላይ ነው በማለት እልባት ያገኝ ዘንድ ወደ ውጭ ሀገር “refer” ያደርጉ የለ? እዚህ ጋር ያስቀመጥኳቸው ምስሎች የሚያመለክቱት የኔዜርላንድና የአሜሪካ ጥምር ዜግነት ያለው ፕሮፈሰር ሊፓርት /Lijphart/ ከአራት ዓመታት በፊት ለካናዳ የምርጫ ኮሚቴ ስለ ተመጣጣኝ ምርጫና ስለ ዲሞክራሲ መርሆች ከራሱ ንድፈ ሐሳቦች ጋር በማገናኘት የቪዲዮ ኮንፍረንስ ላይ ሀሳቡን ሲሰጥ ነው። ካናዳዎቹ ለመፍትሔዎቻቸው “ሀገር-በቀል” መፍትሔ ብቻ ያስፈልጋል በሚል ግትር አቋም ሳይወሰኑ ጠቃሚ እስከሆነላቸው ድረስ በዘርፉ ጥናት ካደረጉ ምሁራን ለመማር ያላቸው ተነሳሽነት የቱን ያህል እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል። እንዲያው ለነገሩ እንጂ እኛስ ብንሆን የብሔር ፖለቲካውን የቀዳነው ከቀድሞዋ ሶቪዬት መሪዎች ከአምባገነኑና ጨፍጫፊው ጆሴፍ ስታሊን (Joseph Stalin)ና ሌኒን (Vladimir Lenin) አይደል? የጨፍጫፊውን የስታሊንን እሳቤ ለመቅዳት ያላፈርን የሌሎች የውጭ ሀገራት ምሁራንን ሳይንሳዊ ምክርን ከመስማት ለምን እንታቀባለን? ከሁሉም በላይ እኛ በስታሊናዊ የብሔር ፖለቲካ አንቀፆች ተጣብቀን ቀርተን በተቃራኒው የእሳቤው ምንጭ የነበሩ እነራሺያ የስታሊንን እሳቤ በሀገር በታኝነት ፈርጀው አሽንቀጥረው ከጣሉ ዓመታት እንዳለፉ ገና መረጃው አልደረሰንም ማለት ነው? የብሔር ፖለቲካ የታሪክ ምዕራፉ እስከሚዘጋ የብልፅግና ፓርቲ ቢያንስ የእነ ሊፓርትና የእነ ዶናልድ ሆሮውዝን ምክሮችን በድኅረ ምርጫውም ቢሆን ከሀገራዊ አውድ ጋር አመሳክሮ ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኝነቱን ማሳየት ይጠበቅበታል… ከ“grand coalition” እስከ ተመጣጣኝ የውክልና ምርጫ ተግባራዊ እስከማድረግ ጭምር!

    ጌታሁን ሄራሞ (ኢ/ር)

    የብሔር ፖለቲካ እና መጪው የኢትዮጵያ ምርጫ

    #17354
    Anonymous
    Inactive

    አስር ሞት፤ አቦይ ስብሐት እና በነፍስ የተያዙ የህወሓት አመራሮች
    /
    የአቶ ስብሐት ነጋ በሕይወት መያዝ ከተገደሉት አመራሮች የበለጠ ያለው አንድምታ/

    (ያሬድ ኃይለማርያም*)

    ልክ እንደ አቦይ ስብሐት [ስብሐት ነጋ]* የቀሩትም የህወሓት አመራሮች በህይወት ተገኝተው በሕግ ጥላ ስር እንዲሆኑ እመኛለሁ። በህይወት እንዲገኙ መመኘቴ መቼም ሳይገባችሁ አይቀርም። እነሴኮ ቱሬ ጌታቸው አንድ ሞት ነው የሞቱት። እኔ ለህወሓት አመራሮች አንድ ሞት ስለሚያንሳቸው አስር ሞት ነው የምመኘው። አስር ሞት ደግሞ አንቱ በተባልክበት ቴሌቪዥን ጣቢያ ‘ጁንታው ስብሐት ነጋ ተያዘ’ ከሚለው ይጀምራል። ብዙዎችን በግፍ ወዳሰቃየህበት ቃሊቲ መውረድ ሌላው ሞት ነው። በወንጀል ሊያውም በዓለም አቀፍ ወንጀል ጭምር በሚያስከስስ ወንጀል መከሰስ ደግሞ የሞት ሞት ነው። በየቀኑ ያንን ቢጫ የእስረኞች ቱታ አጥልቀው ይንቁት በነበረው ችሎት ፊት መቅረብ ዘጠነኛው ሞት። በየቀኑ ሱፍና ከረባት አጥልቀህ በምትንጎማለልበት ከተማ እና አስሬ ስምህ በበጎ በሚጠራበት ቴሌቪዥን ላይ ዳኞች ፊት ቀርበህ የፍርድ ቤት ውሎህ እና የወንጀል ታሪክህ ሲዘከዘክ እና መጨረጫም ሲፈረድብህ አስር ሞት ማለት ነው።

    ላለፉት ሰላሳ አመታት በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያንን የገደሉና ያስገደሉ፣ በየእስር ቤቱ  አጉረው ፍጹም ጸያፍ በሆነ መንገድ ያሰቃዩና የደበደቡ፣ ብዙ ሺዎችን ከአገር ያሰደዱ፣ ሚሊዮኖች ከቤት ንብረታቸው እንዲፈናቀሉ ያደረጉ፣ ኢትዮጵያንን በጎጥ ከፋፍለው ሕዝቡን ወደ እርስ በርስ ግጭት የዶሉ፣ የብዙ ሺህ ወጣቶችን ህልም እና ተስፋ ያጨለሙ፣ የሀገር ሀብት የዘረፉ እና ያዘረፉ፣ እጅግ የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን የፈጸሙና ያስፈጸሙ እነዚህ የህወሓት አመራሮች ለፍርድ ቀርበው በጥፋታቸው ልክ ሲቀጡ ማየት የዘወትር ምኞቴ ነበር።

    እነዚህ ሰዎች ሁሉም በጦርነቱ ተደምሰው ቢሆን ኖሩ በብዙ መልኩ ጥሩ እንድምታ አይኖረውም ነበር። ሌላውን ልተወውና የሁሉም መሞት አንዱ መጥፎ እንድምታ እነዚህን ሰዎች ታሪካቸውን በደንብ ካለማወቅ፣ የፈጸሙትን የወንጀል ልክ በቅጡ ካለመረዳት በተወላጅነትም ይሁን በሌላ መልኩ ሲደግፏቸው የኖሩ እና አሁንም የሚደግፏቸው ሰዎች ከምን ዓይነት ሰዎች ጀርባ ወይም ጎን እንዲቆሙ እንዳያውቁ እና ሰዎቹንም እንደ ጀግና ሳይሆን በወንጀል የተዘፈቁ ኃጥአን መሆናቸውንም ይረዳሉ።

    ነጻና ፍትሓዊ በሆነው የፍርድ ሂደት ህወሓት እና አመራሮቿ ከውልደታቸው እስከ ክሽፈታቸው የፈጸሙት ወንጀል በግልጽ ችሎት ፊት ይነገራል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። የሠሯቸው ወንጀሎች ከነማስረጃዎቹ በአግባቡ ተሰንደው ለታሪክም ጭምር ይቆያሉ። ፍትህም ቀና ትላለች። ተበዳዮችም ቢያንስ በሞራል ይካሳሉ። የዛሬዎቹም ሹሞች ከህወሓት ውድቀት ትምህርት ይወስዳሉ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።

    ለዛሬዎቹ ሹሞች ከዚህ የሚማሩበት ልቦና ይስጣቸው!

    * ማስታወሻ፦
    በሀገራችን ላለፉት 27 ዓመታት የማተራመስ ስትራቴጂ የነደፈ፣ ያስተባበረ እና ያደራጀ በመጨረሻም ጦርነት እንዲቀሰቀስ በማድረግ በሀገራችን ሠራዊት ላይ እጅግ ዘግናኝ ጦርነት በመክፈት ሠራዊቱን ያስጨፈጨፈው የህወሓት ቁንጮ እና ከመሥራቾቹ አንዱ የሆነው  ስብሐት ነጋ (በሥራ ባልደረቦቹ አቦይ ስብሐት በመባል ይታወቃል) መዋሉን ታህሳስ 30 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    አቶ ያሬድ ኃይለማርያም መቀመጫውን ጄኔቭ ከተማ፥ ስዊዘርላንድ ያደረገ ስብስብ ለሰብዓዊ መብቶች በኢትዮጵያ (Association for Human Rights in Ethiopia) የተባለ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የአቶ ስብሐት ነጋ መያዝ

    #17412
    Anonymous
    Inactive

    የህወሓቶች እብሪት ― የህወሓቶች ውድቀት ― እንደሀገር፣ እንደዜጋ የሚያስተምረን ትምህርት
    (አቶ ነአምን ዘለቀ)

    ጆርጅ ሳንታያና (George Santayana) የተባለው ፈላስፋ “ታሪክን የማያስተውሱ ታሪክን በመድገም ይረገማሉ” (‘Those who cannot remember the past are condemned to repeat it.’) እንዳለው፥ አምባገነኖች ከሂትለት እሰከ ሳዳም ሁሴን – ካለፈው መማር ሳይችሉ ያንኑ ሲደጋግሙ ኖሩ። የህወሓቶች እብሪት፣ ትእቢት፣ ለኢትዮጵያ ሕዝብ የነበራቸው ንቀት የዚሁ እብሪተኞች ካለፈው ለመማር አለመቻልና የፍትህን ማዕከላዊነት ጥሎ ልከኝነት ረግጦ የመራመድ ቅጥያ ውጤት ነው።

    ለ27 ዓመታት ፍጹም ሊባል በሚችል የበላይነት የመንግሥት፣ የኢኮኖሚ፣ የወታደራዊና የደህንነት ቦታዎች ላይ የአንበሳ ድርሻውን ይዞ የነበረው ህወሓት፥ ከ2018ቱ (እንደ አውሮፓውያን አቆጣጥር) ለውጥ በኋላ በእኩልነት ለመኖር የተሰጠውን ዕድል መቀበል እንዳልቻለ ግልጽ የነበረው የዛሬ ሁለት ወር ተኩል ገደማ በትግራይ በሚገኘው የሰሜን እዝ ሠራዊት አባላት ላይ ያደረሰው መብረቃዊ ጥቃትና ጭካኔያዊ እርምጃ ያን ተከተሎ በተደረገው ሕግን የማስከበር ወታደራዊ ዘመቻ የተጀመረ ሳይሆን ከሁለት ዓመት ተኩል ጀምሮ አንደ ነበር ግልጽ ነው ።

    ያ የነበረውን ሁለንተናዊ የበላይነት ሲያጣ የሞት ሞት ሆነበትና እንዴት ያድርገው!? መላ ቅጡ ጠፋው። ከጅምሩም የያዙትን ስልጣን ለፍትህ፣ በልከኝነት፣ ለሕዝብና ለሀገር ጥቅም ለማስከበር ሳይሆን በሀገርና በሕዝብ ኪሳራ የራሳቸውን፥ አለፍ ሲልም የአንድ ብሔር ሊሂቃን የበላይነት ለማረጋገጥ የተቀሙበት የዘረፋ፣ የዘረኝነትና የመንግሥታዊ ሽብር መሣሪያቸው ነበር። ህወሓቶች ስለራሳቸው ልዩ መሆን፣ ከሌላው ኢትዮጵያዊ የተለየ ጀግንነት፣ ብቃትና ክህሎት ራሳቸው በፈጠሩት የሀሰት ትርክት በእብሪትና በትእቢት የተወጠረው አእምሮአቸው አዲሱን የኢትዮጵያ የለውጥ መንገድ እንዲሁም ከለውጡ ጋር ተከትሎ የመጣውን ነባራዊ እውነታ ሊቀበሉ አልቻሉም።

    እነ ስዩም መስፍን ኢትዮጵያን “ሶርያና የመን እናደርጋታለን” ብለው በአደባባይ አወጁ። እነ ጌታቸው ረዳ “ትግራይ ሀገር መንግሥት መሆን እንዳለባትና እና በቀጣይም ከኢትዮጵያ ጋር ሶማሌላንድ ከሞቃድሾ ጋር እንዳላት ግንኙነት ነው የምንፈልገው” በማለት በድፍረት ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነገሩ። “ተራራን ያንቀጠቀጥን”፣ “የደርግን ሠራዊት የደመሰስን”፣ “ከወርቅ ሕዝብ የተገኘን”፣ “ኢትዮጵያን እንደ አዲስ የሠራን”፣ “የብሔር ብሔረሰቦችን መብት ያረጋገጥን”፣… ብለው ለአስርት ዓመታት የሰበኩት ህወሓቶች የሀሰት ትርክቶቻቸውንም አብጠው አብጠው በአምሮአቸው ውስጥም ተገንብተው፣ ጠጥረውና ደድረው እውነታን ለማየት የማያስችል ግርዶሽ ሆነው ቆዩ። በርካታ የትግራይን ወጣቶችንም በዚሁ ትርክት እወናበዱ። መሬት ላይ ካለው ከነባራዊው እውነታ ጋር ፍጹም በተቃራኑ ቆሙ። እውነታውን ተቀብለው ለመሄድም በትዕቢት፣ በእብሪት፣ በዘረኝነት የተተበተበው ልቦናቸውና ህሊናቸው ፈጽሞ አልፈቅድላቸው አለ።

    በመሆኑም ህወሓቶች ማድባትና መዘጋጀት ጀመሩ። ለሁለት ዓመታት ሲደራጁ፣ ሲዘጋጁ ቆይተው ማዕከላዊ መንግሥቱን ዳግም ለመቆጣጠር፥ ይህ ካልሆነም ኢትዮጵያን አተራምሰውና በታትነው “የትግራይን ሀገር መንግሥት” ለመመሥረት “በመብረቃዊ ጥቃት” በሰሜን እዝ ላይ ክህደትና ጭካኔ የተሞላበት ግፍ ፈጸሙ። በስልጣን ዘመናቸውም ግፍና መከራ ለሕዝብ ሲሰፍሩ ኖሩ። በሰፈሩት ቁና መስፈር አይቀርምና የሚሊዮኖች እምባ፣ የብዙ ሺዎች ደም፣ ዋይታና ሰቆቃ፣ በህወሓቶች ግፍ የተሰደዱ የአስር ሺዎች ኢትዮጵያውያውን መከራ ፈጽሞ ይሆናል ብለው ባልጠበቁትና ባልተዘጋጁበት የበስተርጅና እድሜያቸው፣ በመጦሪያ ዘመናቸው እጅግ የመረረ ዋጋ ጠየቃቸው። በመጨረሻም መራሩን ውድቀትና ውርደት አከናነባቸው። የኢትዮጵያ ሕዝብም ‘አክ እንትፍ!’ እንዳላቸው ሊከሰትላቸው ፈጽሞ ሳይችል ቀርቶ በስተርጅና እድሜያቸው ለውድቀትና ለውርደት፣ ገሚሶቹ ደግሞ በመደምሰስ ፍጻሜያቸው ባጁ።

    የኢትዮጵያ አምላክም በእነዚህ ግፈኞች ላይ መብረቃዊ ጥቃት ያደረሰ ይመስለኛል። ስልጣንና ሀብት ደደብና ደነዝ አድርጎ ለውርደት ከዳረጋቸው ከህወሓቶችና ካለፉ አምባገነኖች ታሪክ ለመማር ያልቻሉ፥ አሁንም በያዙት ስልጣን መከታ በማድረግ በሕዝብ ጫንቃ ለመናጠጥ የሚሞክሩ፣ ፍትህን፣ ሰላምን፣ ለሀገር የሚበጀውን፣ የዜጎችን ህይወት የሚለውጥ ተግባር ላይ ከማተኮርና ከመትጋት ይልቅ ሕዝብን ከሕዝብ የሚከፋፍሉ፣ የብሔር ካርድ ለስልጣን ማጠናከሪያ የሚመዙ፣ የሕዝብ ሰላም የሚያውኩና ሀገሪቱ እንዳትረጋጋ የሚደነፉ፣ በየመድረኩም የሚፎክሩ አፍራሽ በየብሔሩ ስም የተደራጁ ኃይሎችና ቡድኖች በገዢው ፓሪቲ የሚገኙ እንዳንድ መሪ ካድሬዎች ከዚህ ታሪክ ይማሩ ይሆን?

    ከስልጣን ጋር በሚመጣ እብጠትና ማን አለብኝነት ብዙ ርቀት የማያስኬድ መሆኑን ማጤን ትልቅ አስተውሎ ነው። ከፋፋይና ሕዝብን በጭንቀት ውስጥ እንዲኖር ከሚያደርጉ የማኅበራዊ ሚዲያዎችና በየሚዲያው ከሚሰነዘሩ መርዛማና ከፋፋይ አሰተያየቶች ለመሰንዘር ከመሽቀዳደም በጎ በጎውን፣ ለሀገር የሚበጀውን፣ ለሕዝብ ተስፋ የሚሆንውን፣ ለሥራ-አጡ ሥራ የሚፈጥረው፣ ኢትዮጵያን የሚያለማውን፣ ሕዝብ ከሕዝብ የሚያቀራርቡ ተግባራት ላይ ማተኮርና መትጋት በኃላፊነት ላይ ለሚገኙ እነዚህ የገዥው ፓርቲ መሪ ካድሬዎች ቅድሚያ ሊሰጡት ይገባል።

    የሕዝብን ጥቅም ማስቀደም፣ የሕግ የበላይነትና ፍትህን ያማከለ ብሎም ለእያንዳዱ ዜጋ በየትኛውም ክልልና ቦታ ለሚኖር ኢትዮጵያዊ/ት የደህንነት ዋስትናው የሚጠበቅበት፣ ሠርቶ ለፍቶ በሰላም መኖሩ የሚረጋገጥበት፣ የዜጎችን ህይወት የሚቀይሩ እንቅስቃሴዎች ላይ በማተኮር ሕዝብን የሚጠቅም ሥራ ሠርቶ ጊዜው ሲደርስ ስልጣን ማስተላለፍ መሆን ይገባዋል። ስልጣንን ለማቆየት የብሔር ካርድ በየዕለቱ መምዘና ህወሓቶች እንዳደረጉት የሕዝብም አብሮነት የሚሸረሽሩ፣ ብሔር ለብሔር የሚያጋጩ ተግባራት ላይ መጠመድ ዋና ሥራ ሆኖ መቀጠል የለበትም። ከሶማሌ ክልል ፕሬዝዳንት ከሙስጠፋ ኦማርና ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ እና ከሌሎችም ሊማሩ ይገባል።

    ሕዝብ በአግባቡና በቅጡ ማገልገል ቅድሚያ መስጠቱ በህወሓቶች ውድቀትና ውርደት ዋዜማ ትልቁ ትምህርት ይህ እንደሆነ መቀበል ብልህነት ነው ። ለሀገርና ለሕዝብም ብቸኛው መንገድ የሕዝብን ሰላም፣ ደህንነት፣ ፍትህ፣ መብቶችና ጥቅሞች እንዲሁም አስከፊውን ድህነት ለማስወገድ አካታችና ዘላቂ ልማትን ማስቀደም መሆን አለባቸው። የህወሓቶች ውድቀት ዋዜማ እንደ ሀገር ምን እንማራለን ለሚለው አንዱ አስተምሮና አስተውሎ ይህ ይመስለኛል።

    አቶ ነአምን ዘለቀ

    የህወሓቶች እብሪት ― የህወሓቶች ውድቀት

    #17762
    Anonymous
    Inactive

    በፊትም፣ አሁንም እስትንፋሷ በመሪዋ ላይ ብቻ የሆነባት ሀገር
    (ጋዜጠኛ መላኩ ብርሀኑ)

    እንደአለመታደል ሆኖ የዚህች ሀገር ሰላምና ደህንነት ተጠቃሎ በመሪዎቿ በሰላም ውሎ በሰላም የማደር መዳፍ ውስጥ የገባው ዛሬ አይደለም።

    እንኳን በሰላም ጊዜ ሀገርን መምራት ቀርቶ በጦርነት የማሸነፍና ወጥሮ የመዋጋት ነገር እንኳን የንጉሡን በህይወት መኖር የሚታከክ ነገር ነበር – እዚህ ሀገር። እልፍ ሆኖ ተሰልፎ ድል በእጁ መግባቱን እንኳን እያወቀ ንጉሡ ከተመታ ጦሩ በቀላሉ ይፈታል። ሕዝቡ ንጉሡ ከሌሉ ሀገር የለም እየተባለ ሲሰበክ ነው የኖረው።

    እናቶች ንጉሥ ከሌለ የሚመጣውን መአትና እልቂት በመፍራት ለንጉሡ ረጅም ዕድሜ ከመመኘት በላይ “ከንጉሡ በፊት እኔን አስቀድመኝ” ብለው ይጸልዩም ነበር። ምኒልክ ሲሞቱ የሞታቸው ዜና ለሕዝብ ሳይነገር ስንት ዓመት ፈጀ? መልሱ ይኸው ነው። አጼ ኃይለሥላሴ አንድ ነገር ቢሆኑ ሀገር ያበቃላታል ብለው የሚያምኑ ኢትዮጵያውያን ደርግ በቮልስዋገን ከቤተ መንግሥት ይዟቸው ሲወጣ ሲያዩ ነው ወደሩሃቸው የተመለሱት።

    መንግሥቱ ኃይለማርያም በተራው በኢህአፓ የመግደል ሙከራ ሲደረግበት “ሞተ” ተብሎ አብዮቱ የእልቂት እንዳይሆን (ላይቀርለት ነገር) አደባባይ ወጥቶ ነው እግሩን እጥፍ ዘርጋ እያደረገ ነው “አለሁ” ያለው። መለስ ዜናዊ ሞተ ሲባልም በርካቶች በዚሁ “ሀገር ያበቃላታል” ፍርሃት ውስጥ ነበሩ። እነበረከት አደባባይ ወጥተው “ታጋይ ያልፋል ሀገር ይቀጥላል” ዓይነት ነገር ተናግረው ስጋት ቀንሰዋል።

    የዛሬው መሪ አብይ አህመድ ጉዳይ ግን ከነገሥታቱ በኋላ ካሉት መሪዎች ሁሉ በብዙ ይለያል። ጊዜው ጥቂት ቢሆንም ቅሉ ሃሳቡንና አመራሩን ተቋማዊ ማድረግና ግለሰባዊ ተጽዕኖውን በጥቂቱም ቢሆን ለመቀነስ አልቻለም። ስለዚህ አብይ ተወደደም ተጠላ አሁን ባለው አስተዳደር ውስጥ ብቸኛና መተኪያ የሌለው መሪ ነው።

    አብይ አህመድ እና ጓዶቹ ሲሠሩለት እና ሲያስተዳድራቸው የኖረውን ኢህአዴግ የተባለ ተቋም ከውጭ በነበረ ተቃውሞ ታግዘው ከውስጥ በመፈርከስ ቀንብሩን ከላያቸው ገርስሰው የጣሉ የግለሰቦች ስብስብ እንጂ የተደራጀ ተቋም አልነበሩም። የለውጡ መሪዎች ናቸው የተባሉ ሰዎች በመሃል እየተንጠባጠቡ አብይ ብቻ ሲቀር፣ ቀርቶም ብዙዎች ያደነቁትን ለውጥ እያመጣ ሲቀጥል ብቻውን ገንኖ ወጣ።

    አብይ ከመጣበት ማኅበራዊ መሠረቱ አካባቢ የገጠመው ተግዳሮት አሁን ድረስ በብርቱ ቢገርመኝም በሰሜን አካባቢ ካሉ ሰዎች ዘንድ የተጠላ ሰው መሆኑ ግን አይደንቀኝም። በካልቾ ብሎ ከወንበራቸው ላይ ያባረራቸው ሰዎችና “ገዢነት ካለኛ ለማን!?” ያሉ ጀሌዎቻቸው ሊወዱት አይጠበቅም። ይህም ከዚያ ሰፈር በአብይ ጥላቻ ሳቢያ ሀገር እንድትበተን የሚሠሩና የሚመኙ ድኩማን እንዲፈለፈሉ ምክንያት ሆኗል። መተከል ላይ እየሆነ ባለው “መሪና አቀነባባሪ” ብለው እሱ ላይ ጥርስ የነከሱበት፣ “ወለጋ ላይ ቢገኝ እኔን አያርገኝ” ያሉ የበረከቱበት፣ በመጋቢት መጥቶ በሰኔ ሞቱ የተደገሰለት ሰው ነው አብይ።

    ሰውየው የሀገሪቱን ፖለቲካ ብቻውን እየዘወረ፣ በዚህም በዚያም ሁሉን ነገር ብቻውን እየሠራ፣ አውቆም ይሁን ሳይታወቀው ያለምንም ቀሪ ብቻውን የቆመ፣ የማይካፈል ቁጥር ሆኖ ወጣ። ዛሬ በሰሜን ለተፈጠረውም፣ በደቡብ ላለውም፣ በመሃል ለሆነውም፣ በምዕራብ ለተከሰተውም ችግር ሁሉ ተጠያቂው አብይ ነው የሚል አቋም ባላቸው በርካታ አካላት ሲሰደብ ውሎ የሚያድረው ሰውዬ ወዲህ ጦር እያዘዘ፣ ወዲህ ሀገርና ከተማ እየለወጠ ብቻውን ሲሠራ አጠገቡ የሚተካው ቀርቶ የሚመስለው እንኳን አለማየታችን ፈሪ አድርጎናል።

    [ሰሞኑን] አብይ [ሞተ/ታመመ] ምናምን ሲባል ድንጋጤው የበረታው ከርሱ ሞትም በላይ ነገ ሊሆን የሚችለውን እያሰበ ሁሉም ሰላምና ደህንነቱ ስላስጨነቀው ነው፤ ይህ አለመታደል ነው።

    በግሌ ኢትዮጵያን በከረጢት ውስጥ እንዳለ የተፈጨ ዱቄት፣ አብይን ደግሞ ከረጢቱን የዝቅዝቆሽ አዝሎ ጫፉን በእጁ ጨምድዶ እንደያዘው ተሸካሚ ዓይነት ነው የምመስላቸው። የከረጢቱ ጫፍ ከተለቀቀ ዱቄቱ ከአፈር ይደባለቃል። ይሄ ነው የሚያስፈራኝ።

    አብይን በብዙ የማደንቀው መሪ ቢሆንም በዚህ “the one and only” አካሄዱ ግን ቅሬታ አለኝ። ስለዚህ የእርሱን ደህንነት አጥብቄ የምመኘው በግል ለርሱ ባለኝ ጥሩ ስሜት እና ከፍ ያለ አድናቆት ብቻ ሳይሆን በዋናነት ለዚህች ሀገር ሰላምና መረጋጋት፣ ሲቀጥል ለሕዝቡ በሰላም ወጥቶ በሰላም መግባት፣ ጠበብ ሲል ለቤተሰቤ ደህንንት፣ በጣም ሲጠብ ለራሴ ደህና ወጥቶ ደህና መግባት ብዬ ነው።

    ሰሜኑ አቅሙ ከነሞራሉ ቢደቅቅም ቂሙ ግን ከምንጊዜውም በላይ ጠንኖ ሀገር ብትፈርስ ደስ እንደሚለው በአደባባይ በሚናገርበት፣ ምዕራቡ በፈሪ ዱላ ጫካ ለጫካ እየተሯሯጠ የተሸከመውን መሣሪያ አፍ እያስከፈተ ንጹኃንን በሚረፈርፍበት፣ ከውጭ ግብጽና ሱዳን ቤንዚን በጀሪካን ይዘው እሳታችን ላይ ለመድፋት አጋጣሚ በሚቋምጡበት፣ ብቻ በየትኛውም መስመር ለዚህች ሀገር መልካም የሚመኝ በታጣበት በዚህ ጊዜ አብይ አንድ ነገር ቢሆን ስርዓት ሲናድና ነገር እንዳልነበር ሲሆን ሰዓት የሚፈጅበት አይመስለኝም። ሌሊት እንኳን ቢሆን በርህን ለመስበር እስኪነጋና ከእንቅልፍህ እስክትነቃ እንኳን የሚጠብቅህ የለም!

    በበኩሌ በመሪ ደህንንት ላይ የተንጠለጠለች ሀገር ይዘን ዛሬ ድረስ መኖራችንን ስታዘብ ያለመታደል እለዋለሁ።

    ሰውየውን መደገፍና መቃወም ሌላ ነገር ሆኖ የማንክደው ሃቅ ግን አሁንም ሰላማችን በዚህ ሰው ደህና መሆንና አለመሆን የተወሰነ ሆኖ መዝለቁ ነው። ስለዚህ የተወራበት እንኳን ሀሰት ሆነ! አሹ! ብያለሁ። እንደሰው ሳስብ ደግሞ አብይን ሞት ቀርቶ ጭረት እንዲነካው አልመኝም። [እርሱም ቢሆን] እንደማናችንም የሰላም እንቅልፍ ተኝቶ ማደር አይጠላም። ሀገር ብሎ መሰለኝ የጋለ ምጣድ ላይ የተቀመጠው።

    በግሌ ግን መንግሥት ይሁን አስተዳደር ተቋማዊ ሆነው “ሰዎች ያልፋሉ፣ ሀገር ግን ትቀጥላለች” የምንልበትን ዘመን እናፍቃለሁ።

    ጋዜጠኛ መላኩ ብርሀኑ

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    እስትንፋሷ በመሪዋ ላይ ብቻ የሆነባት ሀገር

    #17907
    Anonymous
    Inactive

    የብልፅግናው ታዬ ደንደዓ … ስለማያወቀው ታሪክ የሚጽፈው ነገርስ ምን ይሉታል?
    (ጋዜጠኛ ፋሲል የኔዓለም)

    ለታላቋ ኢትዮጵያ ተብሎ ዝም ቢባል አሁንስ በዛ። ታዬ ደንደዓ፣ የብልፅግናው ባለስልጣን፣ ስለማያውቀው ታሪክ እየጻፈ የአብይ አህመድን መንግሥት አጣብቂኝ ውስጥ እየከተተው ነው። አብይ አህመድ ህወሓት የቀደዳትን ኢትዮጵያን እንቅልፉን አጥቶ ለመስፋት ይሞከራል፤ ታዬ ደንደዓ እና መሰሎቹ ደግሞ በጎን ይተረትራሉ።

    አብይ አህመድን ለማመስገን የኢትዮጵያን ታሪክ ማጠልሸት አይስፈልግም። አብይ በተደጋጋሚ እንዳለው ነው፤ ኢትዮጵያ ከሱ በፊት በነበሩ መሪዎች እየተገነባች እዚህ የደረሰች አገር ናት።

    ታዬ ደንደዓ ስለ ቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተወልድ የተሳሳተ ታሪክ ጻፈ። በዚህ ስህተቱ ሳያፍር ቀጥሎ ደግሞ የዛግዌንና የዶ/ር አብይን መንግሥት አወዳድሮ ሌላ የማይሆን ታሪክ ጫረ። “ሞኝ ባያፍር፣ የሞኝ ዘመድ ያፍር” ነው ነገሩ።

    ታዬ ከዛገዌ መጨረሻ እስከ አፄ ኃይለሥላሴ ዘመን የነበረውን የነገሥታቱን ዘመን ምንም ሥራ እንዳልሠራ አድርጎ ረገመው። በአጭሩ የደርግን ፕሮፓጋንዳ ደገመው። ዓላማው እነሱ የአማራ መንግሥት የሚሉት የሰሎሞናዊው መንግሥት ምንም እንዳልሠራ በማሳየት አማራን መወረፍ ነው።

    አላዋቂነት የወለደው ድፍረትና ስልጣን የወለደው ትዕቢት ታዬን እያቅበዘበዘው ነው።

    ከዛገዌ በኋላ ሸዋ ላይ የተመሠረተው ታላቅ ስልጣኔ በማን እንደፈረሰ ታዬ የሚያውቅ አይመስልም። አክሱም፣ ዛግዌና የሰሎሞናዊው ስርወ-መንግሥት ስልጣኔዎች የማይነጣጠሉ፣ ተያያዥነትና ተደጋጋፊነት ያላቸው የኢትዮጵያ ታሪኮች መሆናቸውን ለማወቅ የልብ ብርሃን ያስፈልጋል።

    ደግሞ የታሪክ ሒሳብ ማወራረድ ውስጥ ከተገባ በማን እንደሚከፋ ታዬና ቢጤዎቹ ያወቁትም ያሰቡበትም አይመስልም። ደርግ እንዳስወራውና ታዬ እንደደገመው ሳይሆን፥ የኢትዮጵያ ነገሥታት ለእደ ጥበብ ሰዎች አክብሮት ነበራቸው። በሄዱበት ሁሉ ይዘዋቸው ከሚዞሩ ሰዎች መካከል የእደ ጥበብ ባለሙያዎች ይገኙበት ነበር። የኢትዮጵያ ነገሥትታና የሙስሊም ነጋዴዎች ቁርኝት በታሪክ ተመዝግቦ የሚገኝ ነው። ይህ ሲባል እንከን አልነበረም ማለት አይደለም፤ እንኳንስ ትናንት ዛሬም ብዙ እንከኖች አሉ።

    የመካከለኛው ዘመን ነገሥታት የሠሩትን ሥራ ለማወቅ እኮ የዛሬዋን አዲስ አበባ ቆፈር ቆፈር ማድረግ ነው። አንቶን ዲ አባዲ የተባለው ፈረንሳዊው አሳሽ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የቆመበት ቦታ ላይ የነበረውን በመካከለኛው ዘመን የተሠራውን የቤተ ክርስቲያን ፍርስራሽ ዓይቶ አግራሞቱን እንዲህ ሲል ገልጾ እንደነበር Abba Emile Foucher እንዲህ ሲል ጽፏል፦

    Who could have been the architect of such a building? … People who constructed such a building with well-cut stone, linked with mere clay, must have been of another type of civilizations.

    የረርን፣ በራራን፣ ፈጠጋርን፣ ጋሞን፣ ጉራጌን በአጠቃላይ የሸዋን የጥንት ታሪክ ያጠና ሰው፣ የኢትዮጵያ ነገሥታት የኢትዮጵያን ሕዝብ አንድነት ለማጥናት እየዘመቱ፣ በጎን ደግሞ ታላቅ ስልጣኔ ገንብተው እንደነበር ይረዳል። ያው እነዚህ ስልጣኔዎች እንዴት እና በእነማን እንደፈረሱ ዝርዝር ውስጥ አልገባም። ታሪካችን ስለሆነ ከመቀበልና ወደፊት ከመጓዝ ውጭ በታሪክ ‘እኘኘ…’ ስንል አንገኝም። እንደ ታዬ ደንደዓ ዓይነት አምቦጫራቂዎች ከበዙ ግን እውነቱን ከመናገር ወደ ኋላ አንልም።

    ታዬ የዛግዌ መንግሥትን ከአብይ አህመድ መንግሥት ጋር ሲያነጻጻር በተዘዋዋሪ መንገድ የአብይን መንግሥት የኦሮሞ መንግሥት አድርገን እንድንቀበለው እየነገረን ነው። አብይን የሚደግፈው አብዛኛው ሰው የአብይን መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት እንጅ የኦሮሞ መንግሥት አድርጎ አያየውም። ከተሳሳትኩ እታረማለሁ። እንዲህ ከሆነማ አንዳንዶች “ተረኝነት አለ!” የሚሉት ትክክል ነው ማለት ነው።

    አብይ አህመድ የራሱን መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት እንጂ የኦሮሞ መንግሥት ብሎ ሲጠራው ወይም ተራው የኦሮሞ ነው በሚል አስተሳሰብ ስልጣን እንደያዘ ሲናገር ሰምቼ አላውቅም። አብይን የደገፉት ሰዎች ሁሉ አብይን በኢትዮጵያዊነት እንጂ በኦሮሞነት የሚስሉትም አይመስለኝም። አብይ ከኦሮሞ ነገድ ቢወጣም፥ ስልጣን የያዘው በኢትዮጵያዊነቱ እንጂ የስልጣን ተራው የኦሮሞ ስለሆነ አይደለም። ስልጣን በብሔር ተራ ተከፋፍሎ ከሆነማ ኦሮሞ በየትኛው የዕጣ ድልድል ነው ከሶማሌ፣ ከአፋር፣ ከጋምቤላ፣ ከአማራ ወይም ከጉራጌ ቀድሞ ስልጣን የያዘው? እስኪ ዕጣው መቼ እንደወጣና እንዴት እንደወጣ ንገሩን?

    የእነ ታዬ ደንደዓ አመለካከት በጣም አደገኛ የሚሆነው በምርጫ ቢሸነፉ፣ እንደ ህወሓቶች ሁሉ፣ “ኦሮሞ መሪ ካልሆነ ወይም በእጅ አዙር ካልገዛ ስልጣን አንለቅም” የሚሉ መሆናቸው ነው። ስልጣንን በብሔር መንጽር ማየት ኢትዮጵያዊነትን ማዳከም ብቻ ሳይሆን፣ የብሔር አምባገነንነትም ይፈጥራል። ዋ!

    የታዬ አስተሳሰብ ያላቸው ብዙ የኦሮሞ ብሔርተኞች መንግሥት ውስጥ እንዳሉ ይታወቃል። ዶ/ር አብይ አህመድ ከእነዚህ በብሔር ከሚያስቡ ሰዎች በላይ ከፍ ብሎ የሚበር ስልጡን ሰው እንደሆነ በግሌ አስባለሁ። ስለኢትዮጵያ ታሪክ ያለው አመለካከትም ከብዙዎቹ የተለየና በእውቀት ላይ የተመሠረተ ነው። አብይ እንደነ ታዬ ደንደዓ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ አያላግጥም። በአላዋቂነት ድፍረትም ሆነ በስልጣን ግብዝነት የማያውቀውን ታሪክ ሲዘባርቅ ሰምቼው አላውቅም። አብይ ንባብ ከአላዋቂነት ድፍረት ነጻ ያወጣው ሰው ነው።

    የኦሮሞ ብልፅግና ውስጥ እንደ አብይ አህመድ ንባብ ነጻ ያወጣቸው አርቀው የሚያዩ ስንት ሰዎች አሉ? ስለአንድ አብይ ብለን የኦሮሞ ብልፅግናን ሁሉ ይቅር እንበለው ወይስ ስለኦሮሞ ብልፅግና ብለን አንድ አብይ አህመድን እንርገመው የሚለውን ጥያቄ መመለሱ ከባድ እየሆነ ነው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የብልፅግናው ታዬ ደንደዓ

    #18229
    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀ መንበር ብርቱካን ሚደቅሳ መጪውን ሀገራዊ ምርጫ አስመልክተው ያስተላለፉት መልዕክት

    መልካም ዕድል ለተወዳዳሪዎች

    የተከበራችሁ የፓርቲዎች አመራር አባላት፣ የፓርቲ ዕጩ ተወዳዳሪዎች እና በግላችሁ የምትሳተፉ ዕጩዎች፥

    ዛሬ ለ6ኛው አጠቃላይ ምርጫ በዕጩነት ስትመዘገቡ ወይም እንደ ፓርቲ ዕጩዎቻችሁን ስታስመዘግቡ ከፊታችን ያለው መንገድ ከፊል ተስፋ፣ ከፊል ስጋትን አዝሎ እንደሚጠብቃችሁ፣ እንደሚጠብቀን ለሁሉም ግልፅ ነገር ይመስለኛል። ይሁን እና ስጋትን ለመቀነስ፥ ብሎም ወደ መልካም ሁኔታ ለመቀየር የሚያስችለን አቅም እና ዕድል በየፈርጃችን ይዘን ይህን የጋራ ሙከራችንን በዝለት ሳይሆን በጥንካሬ ልንጀምረው ይገባል እላለሁ።

    በቀደሙ ምርጫዎቻችን ባልነበረ ሁኔታ የሂደቱን ዋና ተዋናዮች፥ ማለትም ተፎካካሪዎቹን ግራ ወይም ቀኝ፣ ትንሽ ወይም ትልቅ፣ ሀገራዊ ወይስ ክልላዊ ሳይል፣ በጥረታቸው ሊያግዝ እና ሳንካቸውን ሊፈታ የተዘጋጀ፣ አቅሙን የጨመረ፣ የገለልተኝነቱን መጠን እና ስፋት ከተፅእኖ ሁሉ የሚከላከል የምርጫ ቦርድ ሂደቱን እያስተዳደረ ይገኛል።

    በፍትሃዊነት በተቃኘ በጎ ሀሳብ ሳይሆን በሸፍጥ፣ ሌላውን በማክበር ሳይሆን ማንኛውንም መንገድ ተጠቅሞ በእንፃሩ የቆመውን በማጥፋት ባለመ ሀሳብ፣ የሁሉንም የዜጎችን ሀሳብን የመግለፅ ሰላማዊ ዕድል ሳይሆን ኋላቀር የሆነ ግጭታዊ መስተጋብርን ታሳቢ ያደረገ አቅጣጫን ያሰበ ተወዳዳሪ ቢኖር ይህን ከምርጫ ፖለቲካ ውጪ የሆነ ሥራውን ለአደባባይ አውጥተው ለሰው ዓይን እና ጆሮ ሊያደርሱ የሚችሉ በቁጥር ትንሽ የማይባሉ የሚዲያ አውታሮች እንደ ሀገር ያለን መሆኑም ለተሻለ ሽግግር ወደፊት ለመቀጠል የሚያስችል አንድ በጎ እውነታ ነው።

    የሲቪል ማኅበራቶቻችንንም አናቂ ይባል ከነበረ የሕግ ማእቀፍ ወጥተው ዜጎችን ስለእውነተኛ ምርጫ ሊያሳውቁ፥ እንዲሁም የምርጫ ሂደታችን ጉበኛ /watchman or watchwomen/ ሆኖ በታዛቢነት ለማገልገል በጣት በሚቆጠሩ ሳይሆን በመቶዎች በሚቆጠሩ አደረጃጀቶቻቸው ላይ መሰናዶአቸውን ለማጠናቀቅ ደፋ ቀና ይላሉ።

    የአውሮፓ እና የአሜሪካ ታዛቢዎችም ይህን ለሀገራችን ትልቅ ትርጉም ያለውን ኩነት በእንግድነት ሊታዘቡ ከመንግሥት ግብዣው ደርሷቸው ከእኛው ጋር የሂደቱ አካል ሊሆኑ ዝግጅታቸውን እያጠናቀቁ ነው።

    ብዙ ሌሎች የምርጫ ማሻሻያችን ብዙ ጎኖች መጥቀስ ይቻላል። ሆኖም በዚህ እንደ ብርቱካን ሚደቅሳ በማወጣው የመጀመሪያ የፌስቡክ መልዕክቴ በዝርዝር ላሰለቻችቸሁ አልወደድኩም።

    ለማጠቃለል፥ ዛሬ ፓርቲዎች በሀገራችን የተለያየ አካባቢ ዕጩዎችን በማስመዝገብ፣ በዕጩነት በመመዝገብ የምርጫ ዘመቻውን ምዕራፍ ስትከፍቱ ለሂደቱ የሚጠቅም በጎ እሴት ለመጨመር፣ በችግር ፈቺነት በጋራ ለመሥራት፣ የፖለቲካ ጥቃትን አሮጌ ባህል እለት እለት ለመግደል (old habits die hard ወይም ከክፉ አመል መላቀቅ በቀላሉ አይሆንም የሚለውን ያስቧል)፤ ለዘመናዊ እና ስልጡን ውድድር ራሳችንን ለማደስ፣ ከምንም በላይ የዜጎቻችንን ባለስልጣንነት በማክበር እንዲሆን እያሳሰበኩ፥ በዚህ አስፈላጊ እና ትልቅ ትርጉም ባለው ሥራ የሁላችንንም አብሮነት እና የእያንዳንዳችንን ድርሻ ሳንረሳ በበጎ መንፈስ የምርጫ ውድድሩን እንጀምር ስል ጥሪዬን አቀርባለሁ።

    በድጋሚ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያለበትን ሕጋዊ ኃላፊነት እና ግዴታ እንደሚወጣ፣ እየተወጣም እንደሚገኝ አረጋግጥላችኸዋለሁ።

    መልካም የምርጫ ዘመን!
    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀ መንበር ብርቱካን ሚደቅሳ

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀ መንበር ብርቱካን ሚደቅሳ

    #18520
    Anonymous
    Inactive

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ያለችበት የሕልውና አደጋ በአቶ ልደቱ አያሌው እይታ

    ስንብት፥ ለመሰንበት
    ልደቱ አያሌው
    የካቲት 29 ቀን 2013 ዓ.ም.

    ሀገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ የሕልውና አደጋ ውስጥ ትገኛለች። ብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ የሆነ የዕውቀት፣ የአቅምና የቅንነት ድክመት ያለበት በመሆኑ ሀገሪቱ የገጠማትን ችግር ከማቃለልና ከመፍታት ይልቅ፥ የበለጠ እያባባሰውና እያወሳሰበው ይገኛል። በዚህም ምክንያት ሀገራችን ሕልውናዋን የሚፈታተን አሳሳቢ የእርስ በርስ ግጭት ውስጥ ከመግባቷም በላይ፥ ከኤርትራና ከሱዳን መንግሥታት ግልጽ ወረራ ተፈጽሞባታል። ከታሪኳና ከማንነቷ በተቃራኒም ይህንን ግልጽ ወረራ  ለመቀልበስ የሚያስችል አቅምና ወኔ ያጣች ደካማ ሀገር ሆናለች። ይህ ክስተት ሀገሪቱ ምን ያህል በሂደት ውስጣዊ አንድነቷ እየተዳከመ እንደመጣና ወደ መበታተን አደጋ ውስጥ እየገባች ስለመሆኑ አንድ ማሳያ ነው።

    ብልጽግና ፓርቲ እያራመደ በሚገኘው የተሳሳተ የውጭ ግንኙነት ምክንያትም ሀገራችን ለከፍተኛ የዲፕሎማሲ ጫና ተጋላጭ በመሆን ብሔራዊ ጥቅሞቿንና ሉዓላዊነቷን በአግባቡ ማስከበር የማትችልበት ሁኔታ ውስጥ ገብታለች። ‘በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ’ እንዲሉም ሀገራዊ ሕልውናችንን በሚፈታተን መጠን ኢኮኖሚያችን ወደ ጥልቅ ቀውስና ኪሣራ ውስጥ እየገባ ይገኛል።

    ይህ ሁሉ እየሆነ ያለው በብዙ የሕይወት መሥዋዕትነት የተገኘውና የዛሬ ሦስት ዓመት ገደማ ተጀምሮ የነበረው የለውጥ ሂደት በአመራር ድክመትና በአምባገነናዊ ባህርይ ምክንያት እንዲከሽፍ በመደረጉ ነው። በሥልጣን ላይ የሚገኘው ብልጽግና ፓርቲ ለለውጡ መምጣት ምክንያት የሆኑትን ፖለቲካዊ ችግሮች ሕጋዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ሰላማዊ በሆነ አግባብ ከመፍታት ይልቅ አማራጭ ሀሳቦችን በማፈን፣ በፖለቲካ ተቀናቃኞቹ ላይ የስም ማጥፋት ዘመቻ በማካሄድና የፈጠራ ክስ በመመሥረት፣ በሕገ-ወጥ መንገድ ተቀናቃኞቹን በማሰርና ‘ለሕልውናዬ ስጋት ናቸው’ ብሎ የሚፈራቸውን የፖለቲካ ድርጅቶች ሕጋዊ ዕውቅና በመሠረዝ ጭምር ካለፈው የ27 ዓመቱ የኢሕአዴግ ሥርዓት የባሰ እንጂ የተሻለ አለመሆኑን በተግባር አሳይቷል። ባጭሩ፥ ሀገራችን ከእንግዲህ በብልጽግና ፓርቲ ወይም በዶ/ር ዐቢይ አሕመድ እየተመራች ከአንድ ቀውስ ወደ ሌላ የባሰ ቀውስ የመሸጋገር እንጂ ወደ በጎና የተሻለ ሥርዓታዊ ለውጥ የመሸጋገር ዕድል እንደሌላት በማያሻማ ሁኔታ ግልጽ ሆኗል።

    እኔም ሆንኩ አባል የሆንኩበት ፓርቲ፥ በአንድ በኩል የተጀመረው የለውጥ ሂደት ስኬታማ እንዲሆን ከተፈለገ ምን ዓይነት መዋቅራዊ ለውጦች በቅደም ተከተል መካሄድ እንዳለባቸው፤ በሌላ በኩል ደግሞ በአመራር ብቃት ማነስ ምክንያት የተጀመረው የለውጥ ሂደት ከከሸፈ በሀገራችን አጠቃላይ ሕልውና ላይ ሊያስከትል የሚችለው አደጋ ምን ያህል ከባድና አደገኛ እንደሚሆን የሚያሳስብ የሀሳብ ትግል ላለፉት ሦስት ዓመታት ስናካሂድ ቆይተናል።

    ነገር ግን የወቅቱ የሀገራችን ፖለቲካ በዕውቀት፣ በምክንያታዊነትና በሐቀኝነት የሚካሄድ ሳይሆን ብሔርተኝነት፣ ጽንፈኝነት፣ ሤረኝነት፣ ጥላቻና ውሸት የነገሠበት በመሆኑ ጩኸታችን የቁራ ጩኸት ሆኖ ቀርቷል። ሆኖም ቀደም ብለን ስናቀርበው የነበረው ስጋት ከተራ ሟርተኝነት ሳይሆን፥ ከተጨባጭ የፖለቲካ ግምገማ፣ ግንዛቤና ትንታኔ የመነጨ ስለነበር እንደፈራነው የለውጥ ሂደቱ ከሽፎ አሁን ሀገሪቱ ወደባሰና ውስብስብ የሕልውና አደጋ ውስጥ ገብታለች።

    የለውጥ ሂደቱን መክሸፍ ተከትሎ ሀገራችን ወደ ከፍተኛ የእርስ በርስ ጦርነት የገባችና በውጭ ኃይሎች ወረራ ሥር የወደቀች ቢሆንም፥ ግብዞቹ የብልጽግና አመራሮችና የእነርሱ የፕሮፓጋንዳ ሰለባ የሆኑ ተከታዮቻቸው ግን ዛሬም ጭምር ሀገሪቱ ወደላቀ የብልጽግና ጎዳና እየገሰገሰች እንደሆነ ሊነግሩን ሲደፍሩ እያየን ነው። ብልጽግና ፓርቲ የከሸፈን የለውጥ ሂደት ተከትሎ የሚካሄድ ሀገራዊ ምርጫ፥ የተጨማሪ ቀውስ ምንጭ ከመሆን ባለፈ ለሀገሪቱ መዋቅራዊ የፖለቲካ ችግሮች የሚያስገኘው ምንም ዓይነት አዎንታዊ ፋይዳ የሌለ መሆኑን መገንዘብ ተስኖት የሥልጣን ቅቡልነት ልባስ ለመደረብ ሲል ብቻ ትርጉም የለሽ ምርጫ ለማካሄድ እየተጣደፈ ይገኛል። ይህም ሀገሪቱ ወደባሰና ከቁጥጥር ውጭ ወደሆነ የፖለቲካ ቀውስ ልትገባ ትችላለች የሚል ተጨማሪና ምክንያታዊ ስጋት ፈጥሯል።

    በእኛ በኩል ውጤታማ ሽግግር ባልተካሄደበትና አንጻራዊ ሰላምና መረጋጋት ባልተፈጠረበት ሁኔታ በችኮላ ወደ ምርጫ ውስጥ መግባት አደገኛና ኃላፊነት የጎደለው ውሳኔ ነው የሚል የጠነከረ አቋም ያለን ቢሆንም፥ ምርጫው መካሔዱ የማይቀር ከሆነ ግን ቢያንስ በምርጫው ሂደት ሊፈጠር የሚችልን አደጋ ለመቀነስ በሚያስችል አግባብ በምርጫው ተሳታፊ ለመሆን በዝግጅት በማድረግ ላይ ነበርን።

    ነገር ግን ከሁሉም ነገር በላይ ሀሳብን አብዝቶ የሚፈራውና ከሀገሪቱ ደኅንነት በላይ ለራሱ የሥልጣን የበላይነት ሰፍሳፋ የሆነው የወቅቱ መንግሥት በመጭው ምርጫም ሆነ በቀጣዩ የትግል ሂደት ተሳትፎ እንዳይኖረን ስለፈለገና ስለወሰነ በሕገ-ወጥ መንገድ ፓርቲያችን እንዲሰረዝና ከትግሉ ሜዳ እንዲወገድ አድርጓል።

    በእኔ ላይም በባለቤትነት በሚቆጣጠራቸውና ለልዩ ተልዕኮ ባቋቋማቸው የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ቅጥረኞቹን አሰማርቶ ሰፊ የስም ማጥፋት ዘመቻ በማካሄድ፣ የዛቻና ማስፈራራት ድርጊት በመፈጸም፣ የፈጠራ ክስ በመመሥረትና በሕገ-ወጥ መንገድ በማሰር የትግል ተሳትፎዬን ለመገደብ ሞክሯል። ይህም አልበቃ ብሎት በፖለቲካ መድረኩ ላይ ብቻ ሳይሆን በሕይወትም እንዳልኖር ስለፈለገ፥ ያለምንም ሕጋዊ ድጋፍ ያለብኝን ከፍተኛ የልብ ሕመም ወደውጭ ሀገር ሄጄ እንዳልታከም እገዳ ጥሎብኛል። ይህ ሕገ-ወጥ እገዳ እንዲነሳልኝ የተለያዩ የመንግሥት ተቋማትንና ባለሥልጣናትን ለማነጋገርና ለመማጸን ያደረግኩት ጥረትም ስኬታማ ሳይሆን ቀርቷል። በዚህም ምክንያት ከፍተኛ የልብ ቀዶ ጥገና ሕክምና ለማድረግ የነበረኝ ቀጠሮ በመስተጓጎሉ በእያንዳንዱ ሰዓትና ዕለት ሕይወቴ ለዕልፈት ሊጋለጥ በሚችልበት አደጋ ውስጥ እገኛለሁ። በዚህ ድርጊቱም የወቅቱ መንግሥት አምባገነናዊ ብቻ ሳይሆን ምን ያህል ኢ-ሰብአዊ መሆኑን በተግባር አሳይቷል። በርግጥም ሥርዓቱ ከግለሰብ ግድያ ጀምሮ እስከ የሕዝብ ጅምላ ጭፍጨፋ ከሚደርስ ቀውስ የፖለቲካ ትርፍ ለመቃረም የሚጥር ኃይል በመሆኑ በእኔ ላይ ይህንን ማድረጉ እምብዛም አያስደንቅም።

    ሰሞኑን የምገኝበትን አሳሳቢ የጤና ሁኔታ በተመለከተ ከሐኪም ጋር ባደረግሁት ምክክርም ለሕመሜ አስተማማኝ ሕክምና እስካገኝ ድረስ በአካሌም ሆነ በአዕምሮዬ ላይ ምንም ዓይነት ጫናና ውጥረት የሚፈጥር ሥራ እንዳልሠራና በቂ ረፍት እንዲኖረኝ ከባድ ማስጠንቀቂያና ምክር ተሰጥቶኛል። ጤናዬ ከሚገኝበት አሳሳቢ ደረጃ (risk) አኳያ በሕይወት ለመሰንበት የምፈልግ ከሆነ፥ ለጊዜው ያለኝ ብቸኛ አማራጭ ይህንን ማድረግ እንደሆነ ተነግሮኛል።

    ሀገራችን የምትገኝበትን እጅግ አሳሳቢ ሁኔታ ግምት ውስጥ በማስገባት በእኔ በኩል አስቸኳይ የሕክምና እርዳታ አግኝቼና ጤናዬ ተስተካክሎ በትግሉ ሂደት የጎላ ተሳትፎ እንዲኖረኝ ከፍተኛ ፍላጎት የነበረኝና አሁንም ያለኝ ቢሆንም የሕክምና እርዳታ እንዳላገኝ ራሳቸውን በፈጣሪ ቦታ ሊተኩ በሚፈልጉ ገዥዎች በመከልከሌ ምክንያት ይህንን ምኞቴን ማሳካት የማልችልበት እንቅፋት ገጥሞኛል። ስለሆነም ተገቢውን የሕክምና እርዳታ አግኝቼ ጤናዬ እስኪመለስ ድረስ በሕይወት የመሰንበት ዕድሌን ለመሞከር ስል ከማንኛውም ዓይነት የትግል እንቅስቃሴ (ገንዘብ ወይም ምክር ከማዋጣት ባለፈ) ራሴን ለጊዜው ለማቀብ የተገደድኩ ስለመሆኑ በከፍተኛ ቁጭትና ሐዘን እገልጻለሁ።

    በዚህ ጉዳይ ላይ የሚሰማኝ ቁጭትና ሐዘን ልብን የሚሰብር የሆነብኝ ያለምክንያት ሳይሆን፥ ሀገራችን ከመቼውም ጊዜ በላይ የሕልውና አደጋ ውስጥ በገባችበትና ዋጋ የሚከፍልላት ዜጋ በሚያስፈልጋት በአሁኑ ወቅት ከአቅሜ በላይ በሆነ የጤና ችግር ምክንያት ራሴን ከትግሉ ሜዳ ለማግለል መገደዴ ያልጠበቅሁትና ከፍላጎቴ ውጭ የሆነ መጥፎ ገጠመኝ ስለሆነ ነው።

    የሆነው ሆኖ ይህንን መጥፎ አጋጣሚ እንደ አንድ ጊዜያዊ ስንብት ልቁጠረውና ስለ ዛሬዋ ኢትዮጵያ ሕዝቡ ግንዛቤ ሊወስድ ይገባዋል ብዬ በማምንባቸው በሚከተሉት ስምንት ነጥቦች ዙሪያ የሚሰማኝን በመግለጽ ለመሰናበት ልሞክር።

    1. ከእንግዲህ በብልጽግና ፓርቲ የሚባባስ እንጂ የሚፈታ ችግር የለንም

    በአሁኑ ወቅት ሀገራችን ለገጠማት የሕልውና አደጋ በአስተሳሰብና በመዋቅር ደረጃ ዋናዎቹ ተጠያቂ ምክንያቶች የጽንፈኝነት ፖለቲካ፣ ብሔርተኝነትና የፖለቲካ አመራር ድክመቶች ናቸው። ስለሆነም ለወቅቱ የለውጥ ሂደት መክሸፍ ዋናው ተጠያቂ የእነዚህ መዋቅራዊ ድክመቶች ሰለባ የሆነው የቀድሞው ኢሕአዴግ፣ የአሁኑ ብልጽግና ፓርቲ ነው።

    ብልጽግና ፓርቲ በእጁ የገባውን ወርቃማ የለውጥ ዕድል በአግባቡ መጠቀም ሳይችል የቀረበት ተጨማሪ ምክንያትም ፓርቲው ከሀገሪቱ ጥቅምና ደኅንነት በላይ ለራሱ የፖለቲካ ሥልጣን የበላይነት ቅድሚያ በመስጠት ውስጣዊ አንድነቱን በማዳከሙና ወደ የእርስ በርስ የሥልጣን ሽኩቻ ውስጥ በመግባቱ ነው። የፓርቲው ውስጣዊ ክፍፍል በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች እየተፈጠሩ ላሉ የእርስ በርስ ግጭቶችና በትግራይ ክልል ለተከሰተው ጦርነት ዋናው ምክንያት ሲሆን፥ ውስጣዊ ችግሩ አሁንም የተሻለ ትኩረት አግኝቶ ካልተፈታ በስተቀር ሀገሪቱን ለባሰ ቀውስና ጦርነት የሚዳርጋት ይሆናል። የራሱን ውስጣዊ ችግር መፍታት ያልቻለና ከራሱ የፖለቲካ ሥልጣን በላይ የሀገሪቱን ጥቅም ማስቀደም የተሳነው ደካማ ገዥ ፓርቲ የለውጥ ሂደቱን ስኬታማ ሊያደርግም ሆነ ሀገሪቱን ከጥፋት ሊታደጋት አይችልም።

    ቀደም ሲል ብልጽግና ፓርቲ ይህንን መሠረታዊ ድክመቱን አምኖ በመቀበልና በማረም ራሱንም ሆነ ሀገሪቱን ከጥፋት ሊታደጋት ይችላል የሚል ግምት (ምናልባትም የሞኝነት) የነበረን ቢሆንም ግምታችን ስህተት እንደነበር ያለፉት ሦስት ዓመታት ሂደት በተግባር አሳይቶናል። በዚህም ምክንያት ብልጽግና ፓርቲ እንደ ፈጣሪውና አሳዳጊው ህወሓት ሁሉ፥ ከመሞት መዳን ያለመቻል መዋቅራዊ ችግር ያለበት ግትርና ጀብደኛ ድርጅት እንደሆነ መገንዘብ ችለናል። ምክንያቱም ብልጽግና ፓርቲ አምባገነን የሆነው አምባገነን እንዲሆን ያስገደዱት ነባራዊ ሁኔታዎች ስላሉ ሳይሆን በራሱ ፍላጎትና ውሳኔ አምባገነን መሆንን የመረጠ ድርጅት ስለሆነ ነው።

    ከይቅርታ ጋር፥ እዚህ ላይ በከፍተኛ ድፍረትና ርግጠኛነት ልናገር የምችለው፥ የ21ኛዋን ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያን በ16ኛው ክፍለ ዘመን የማክያቬሊ የፖለቲካ ሤራ ስልት (conspiracy theory) እና የንግርት አምልኮት ለመግዛት እየሞከረ ያለው ብልጽግና ፓርቲ አሁን በያዘው አቅጣጫ መጓዝ ከቀጠለ ራሱንም ሆነ ሀገሪቱን የማፍረስ እንጂ ወደ ዘላቂ ለውጥ የማሸጋገር ሚና ከቶውንም ሊኖረው አይችልም። በአሁኑ ወቅት ትግራይ ውስጥ የገባንበትን ከባድ ጦርነት፣ በኤርትራናና በሱዳን መንግሥት የተፈጸመብንን ወረራ፣ በሕዳሴ ግድብ ምክንያት ከግብጽና ከሱዳን ጋር የገባንበትን ፍጥጫ፣ በተለያዩ የሀገሪቱ ክልሎች እየተፈጸመ የሚገኘውን የሕዝብ መፈናቀልና የጅምላ ጭፍጨፋ፣ በገዥው ፓርቲና በበርካታ ተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል የሚታየውን ፍጥጫ፣ ከዓለም አቀፉ ኅብረተሰብ እየደረሰብን ያለውን ከባድ ተጽዕኖ፣ የኮሮና ወረርሽኝ እያስከተለብን ያለውን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ቀውስ፣ ከፊታችን እየመጣ ያለውን ሁለንተናዊ ኢኮኖሚያዊ ውድቀትና ሌሎች ተመሳሳይ ፈተናዎቻችንን በጥቅሉ ደምረን ስናያቸው እንኳንስ ብልጽግና ፓርቲ ብቻውን ሆኖ ሁላችንም ተባብረን በአንድነት ብንቆም የወቅቱን የሀገሪቱን ፈተና በቀላሉ መወጣት አዳጋች ነው። ስለሆነም የውስጥ ችግራችንን ፈተን በአንድነት እስካልቆምን ድረስ በብልጽግና ፓርቲ የተናጠል ጥረት ችግራችን ፍጹም ሊፈታ እንደማይችል መገንዘብ ያስፈልጋል።

    1. ወቅቱ ኢትዮጵያውያን በአስተሳሰብና በሞራል ዝቅታ ላይ የምንገኝበት ነው

    የምንገኝበት ወቅት ኢትዮጵያውያን ከመቼውም ጊዜ በላይ ጭካኔን፣ ጅምላ ግድያን፣ የሤራ ፖለቲካን፣ የጥላቻ ንግግርን፣ ውሸትንና የግለሰብ አምልኮትን እየተለማመድን የምንገኝበት ነው። እነዚህን እኩይ ተግባራት በፊት አውራሪነት እያለማመደን የሚገኘው መንግሥት ሲሆን፥ ጋሻጃግሬዎቹ ደግሞ ሀይማኖተኛ፣ ብሔርተኛና ምሁራን ነን ባይ “ልሂቃን” መሆናቸውን እያየን ነው።

    በርግጥም ወቅቱ የ“ዝቅታችን” ወቅት ነው። ለአንድ “ህወሓት” የተባለ አምባገነናዊ የሆነና በሕዝብ ትግል ከሥልጣን ለተወገደ ኃይል ባለን ገደብ የለሽ ጥላቻ ምክንያት ዓይነልቦናችን ታውሮ የዛሬ ገዥዎቻችን በሕዝብና በሀገር ላይ እየፈጸሙት ያለን የዛሬ ግፍና በደል ፈጽሞ ማየትና መረዳት ተስኖናል። የወቅቱ ገዥዎቻችን ለራሳቸው የሥልጣን የበላይነት ሲሉ በሀሰትና በአስመሳይነት በጥብጠው የሚግቱንን ሥልታዊ ፕሮፓጋንዳ፣ በሀገር ጥቅምና በሕግ ማስከበር ሰበብ እየፈጸሙት ያለን በውጤቱ ሀገር በታኝ የሆነ የሤራና የበቀል ተግባር መገንዘብ ተስኖን እንደ ሕዝብ የአዲስ አምባገነናዊ ኃይል አዋላጅና ወላጅ ሆነናል። እወደድ ባይና ደካማ በሆነው የብልጽግና ፓርቲ አመራርና ተከታዮቹ በሆኑት የኅብረተሰብ ክፍሎች መካከል ያለው የጋራ አጀንዳ፥ በዋናነት ህወሓትን በመጥላትና በመበቀል ዙሪያ የተቃኘ ቢሆንም፥ ዋናውና የጋራ መገለጫቸው የሆነው ባሕርያቸውና ግብራቸው ግን የህወሓት አውዳሚ አመለካከትና ውርስ (legacy) አራማጅና አስቀጣይ መሆን ነው። እነዚህ ግብዝ ኃይሎች በህወሓት መንገድ መጓዝ ህወሓት በከፋፋይ አጀንዳው ያዳከማትን ሀገር ለይቶላት እንድትፈርስ ከማድረግ ያለፈ ውጤት እንደማያመጣ መገንዘብ ተስኗቸዋል። ይህም በራሱ ኢትዮጵያውያን ከሌሎችም ሆነ ከራሳችን ያለፈ ስህተትና ውድቀት የመማር አቅማችን እጅግ አናሳ መሆኑን ያሳያል።

    በአጠቃላይም ወቅቱ ኢትዮጵያውያን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በራሳችን ታሪክ፣ አንድነት፣ ሉዓላዊነት፣ ሰላም፣ የወደፊት ዕድገትና ጥቅም ላይ ራሳችን ጦርነት ያወጅንበት ወቅት ነው ማለት ይቻላል። በአጭሩ የራሱን ፍላጎትና ዘለቄታዊ ጥቅም የማያውቅ ግብዝ ሕዝብ ሆነናል። ከገባንበት ዝቅጠት ጥልቀትና ስፋት አኳያም አንዳንዶች “ኢትዮጵያውያን እርስ በርስ ተጨራርሰን ከምንጠፋ በስምምነት ተለያይተን መኖር የምንችልበት ዕድል ይኖር ይሆን?” ብለው ራሳቸውን ለመጠየቅ የተገደዱበት ወቅት ላይ ደርሰናል። ኢትዮጵያውያን እንደ “ሕዝብ” በዚህ ዓይነት የአስተሳሰብና የሞራል ዝቅታ ላይ እንደምንገኝ ተገንዝበን ስክነትና ብስለት ወደተላበሰ የፖለቲካ አቅጣጫ በፍጥነት ካልገባን በስተቀር ሀገራችንን ከገጠማት የመፈራረስ አደጋ ልንታደጋት አንችልም። እጅግ አማላይና መሠሪ በሆነው የሥርዓቱ የፕሮፓጋንዳ ስልት ሰለባ በመሆን፣ ወይም በአድር ባይነት፣ ወይም በጥቅመኝነትም ሆነ በማንኛውም ሌላ ምክንያት የወቅቱን ሥርዓት እየደገፍን የምንገኝ ዜጎች በታሪክና በትውልድ ፊት የየራሳችን የተጠያቂነት ድርሻ እንደሚኖርብን ተገንዝበን፥ ሥርዓቱን መቃወምና መታገል ቢያቅተን እንኳን ቢያንስ ዝም በማለት የሀገሪቱ ጥፋትና ውድቀት ቀጥተኛ ተጋሪ ከመሆን ልንቆጠብ ይገባል።

    1. በይስሙላ ምርጫ የሚፈታ ችግር የለንም

    ነጻና ፍትሐዊ ምርጫ ለማካሄድ የሚያስችል ውጤታማ የሽግግር ሂደት ባላካሄድንበት ሁኔታ የሚካሄደው የዘንድሮው ሀገራዊ ምርጫ ሂደትም ሆነ ውጤት የሀገሪቱን የፖለቲካ ቀውስ የበለጠ የማባባስ እንጂ የመፍታት አንደምታ አይኖረውም። ምርጫው ሳይጀመር ያለቀና ውጤቱም ሀገሪቱን ወደ ባሰ ቀውስ ማስገባት ወይም አምባገነናዊነትን ማጽናት መሆኑ አስቀድሞ የታወቀ ነው። ይህ ምርጫ ብልጽግና ፓርቲ በማንኛውም መንገድ አሸናፊ ሆኖ በሥልጣን ላይ ለመቀጠል ወስኖና ተዘጋጅቶ የገባበት ምርጫ ስለሆነ፥ የዚችን ደሃ ሀገር በጀት ከማባከን ያለፈ ፋይዳ አይኖረውም። በአጭሩ መጭው ምርጫ ነጻና ፍትሐዊ እንደማይሆን ሳይሆን እንዳልሆነ የቅድመ ምርጫው ሂደት በማያሻማ ሁኔታ አሳይቷል። የወቅቱ የፖለቲካ ችግር በዘላቂነት ሊፈታ የሚችለው በአንጻራዊነት ነጻ፣ ገለልተኛና ጠንካራ የዴሞክራሲ ተቋማትን ለመገንባት፣ ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች በነጻነትና በእኩልነት ምርጫ የሚወዳደሩበትን ሁኔታ ለማመቻቸት፣ ብሔራዊ መግባባትና ዕርቅን ለማስፈን፣ ብሎም ሕገ-መንግሥታዊ ማሻሻያ ለማድረግ በሚያስችል ሁሉን አቀፍ በሆነ የሽግግርና የሀሳብ ግብይት ሂደት (national dialogue) ነው እንጂ በተለመደው ዓይነት የታይታ የምርጫ ግርግር አይደለም።

    ወደ መዋቅራዊና ዘላቂ ለውጥ ለመግባት ከተፈለገ መፍትሔው የችኮላ ምርጫ ማካሄድ ሳይሆን በቅድሚያ ከፖለቲካ ጉዳይ ጋር በተያያዘ በመላው ሀገሪቱ የታሠሩ የፖለቲከኛ እስረኞችን መፍታት፣ ዜጎች ላይ የሚደረግ አፈናና ግድያን ማስቆም፣ የሀገሪቱ ሕግጋትና ተቋማት ሀገር ጠቀም በሆነ አግባብ እንዲሻሻሉ ማድረግና ቢያንስ ዶ/ር ዐቢይ ወደ ሥልጣን በመጡባቸው በመጀመሪያዎቹ ጥቂት ሳምንታት የታየው ዓይነት የዕርቅና የመቻቻል መንፈስ በሀገሪቱ እንዲሰፍን ማድረግ ያስፈልጋል።

    1. ልዩ ትኩረት አዲስ አበባ ከተማን ለማሸነፍ

    በተግባር እየተፈጸመ ከሚገኘው ግልጽ ድርጊት እንደምንረዳው ብልጽግና ፓርቲ ነጻና ፍትሐዊ በሆነ ምርጫ ተወዳድሮ በማሸነፍ ሳይሆን በአፈናና በኃይል በሥልጣን ላይ ለመቀጠል የወሰነ አምባገነን ኃይል ነው። ገዥው ፓርቲ የሚጠላቸውንና የሚፈራቸውን የፖለቲካ ፓርቲዎች ከፖለቲካ መድረኩ በማስወገድና የፓርቲ አመራሮችን በማሰር በወሰደው እርምጃ መጭው ምርጫ ነጻና ፍትሐዊ እንዳልሆነ ከወዲሁ በተግባር አረጋግጧል። ሆኖም ምርጫው በታሰበበት ጊዜ የሚካሄድ ከሆነ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ራሳቸውን ከሂደቱ ከማግለል ይልቅ አቅማቸውና ሁኔታው በፈቀደላቸው መጠን በምርጫው ተሳታፊ ቢሆኑ የተሻለ ይሆናል እላለሁ።

    ነገር ግን በቂ ዝግጅት አድርገውና የገዥውን ፓርቲ ሁለንተናዊ ተጽዕኖ በብቃት ተቋቁመው በሀገር ደረጃ መንግሥት ለመሆን በሚያስችል መጠን ምርጫውን ለማሸነፍ የሚኖራቸው ዕድል እጅግ ጠባብ መሆኑን በመገንዘብ ሙሉ ትኩረታቸውን አዲስ አበባ ከተማን ለማሸነፍ ማድረግ ይኖርባቸዋል። አዲስ አበባ ከተማን አሸንፎ ለመረከብም አንድነት ተኮር የሆኑ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የመተባበር ጉዳይ ምንም ዓይነት ቅድመ ሁኔታ ሊቀርብበት የማይገባና ምትክ የለሽ እርምጃ መሆኑን መገንዘብ አለባቸው። ግለሰብን በመጥላት የሀገርን ጥቅም ጥያቄ ውስጥ ማስገባት ከማንኛውም ኃላፊነት ከሚሰማው ፓርቲ የማይጠበቅ ተግባር ቢሆንም ምናልባት የእኔ ለጊዜውም ቢሆን ከምርጫውና ከትግሉ ሂደት ገለል ማለት ለተቃዋሚው ጎራ መተባበር አንድ ጥሩ አጋጣሚ ሊሆን እንደሚችል እገምታለሁ።

    የአንድነት ኃይሉ ምንም ዓይነት ድምጽ ሊባክን በማይችልበት ሁኔታ እርስ በርስ ላለመፎካከር አስቀድሞ ካልተስማማ በስተቀር፥ ብልጽግና ፓርቲና አጋሮቹ (በፓርቲም ሆነ በግል የሚወዳደሩ) አዲስ አበባን የማሸነፍ ዕድል እንደሚኖራቸው መገንዘብ ያስፈልጋል። ብልጽግና ፓርቲና አጋሮቹ አዲስ አበባን የማሸነፍ ዕድል ካገኙም የአዲስ አበባ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን የመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ ጥቅምና ሕልውና አደጋ ውስጥ እንደሚገባ መገንዘብ ያስፈልጋል። በተጨማሪም በምርጫ 97 ሲሆን እንደታየው “ምርጫው ስለተጭበረበረ ያሸነፍነውን ወንበር ወይም ምክር ቤት አንረከብም” በሚል የተሠራው ታሪካዊ ስህተት በዘንድሮውም ምርጫ እንዳይደገም ፓርቲዎች ከወዲሁ በጉዳዩ ላይ መተማመንና መወሰን ይኖርባቸዋል።

    1. መፍትሔው ሁሉን አቀፍ የሆነ የሽግግር ሂደት መፍጠር ነው

    በአሁኑ ወቅት ሀገራችን በሁለት የጎረቤት ሀገራት (በኤርትራና ሱዳን) ሉዐላዊነቷ ተደፍሮ የግዛት ወረራ ተፈጽሞባታል። ይህ ወረራ ከማንኛውም ውስጣዊ ችግሮቻችን በላይ ቅድሚያ ትኩረት ሊሰጠውና በአስቸኳይ ሊቀለበስ የሚገባው ነው። ይህንን ማድረግ ሳንችል ኢትዮጵያውያን እንደ ሀገርና ሕዝብ የነጻነት ታሪክም ሆነ ሉዐላዊ ሕልውና አለን ብለን መናገር አስቸጋሪ ይሆናል። የወቅቱ መንግሥት በሀገር ውስጥ እየተፈጸመ ያለውን ብሔር ተኮር ጭፍጨፋ ማስቆምም ሆነ የሀገሪቱን ሉዓላዊነት ማስከበር ስላለመቻሉ የሚያቀርበው ማንኛውም ምክንያትም ተቀባይነት ሊኖረው አይገባም። የወቅቱ መንግሥትም ሆነ መንግሥትን በዋናነት የሚመሩት ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ እነዚህን ሁለት ቁልፍና መሠረታዊ የአንድ መንግሥት ኃላፊነቶች በአግባቡ መወጣት ስላልቻሉ ከእንግዲህ የሚኖራቸው ብቸኛ አማራጭ ችግሩን ለመፍታት የሚያስችል ሀገራዊ የሀሳብ ግብይት ሂደት (national dialogue) መጀመርና ሁሉን ዐቀፍ የሆነ የሽግግር ሂደት ማካሄድ ነው።

    የወቅቱ መንግሥት ቀደም ሲል በኢሕአዴግ ስም፣ አሁን ደግሞ በብልጽግና ፓርቲ ስም ሕዝባዊ ይሁንታ ሳይኖረው ለ30 ዓመታት በሥልጣን ላይ ያለ ኃይል ነው። ይህ መንግሥት የሀገሪቱን መሠረታዊ ፖለቲካዊ ችግሮች መፍታት ካለመቻሉም በላይ ይበልጥ እያባባሰውና እያወሳሰበው ይገኛል። ስለሆነም የወቅቱ ብልጽግና ፓርቲ በአንድ በኩል የሀገሪቱን አንድነትና ሉዓላዊነት ማስከበር ባልቻለበት ሁኔታ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ነጻና ፍትሐዊ ምርጫ አካሒዶ የሕዝብ እውነተኛ ውክልና ለማግኘት በሐቅ ባልተዘጋጀበት ሁኔታ የሀገሪቱን የፖለቲካ ሥልጣን በቋሚ ርስትነት ይዞ ሊቀጥል አይገባውም።

    ገዥው ብልጽግና ፓርቲ ከግለሰብ በላይ የሆነ ሚና አለኝ ብሎ የሚያምንና ድክመቱ የኔ ሳይሆን የመሪዎቼ ወይም የመሪዬ ነው ብሎ የሚያስብ ከሆነም ሀገሪቱ ለይቶላት ከመፍረሷ በፊት መሪዎቹን ወይም መሪውን የመቀየር ርምጃ ሊወስድ ይገባዋል። ይህንን ማድረግ ካልቻለ ግን ለሀገሪቱ ውድቀት ፓርቲውም እንደ ድርጅት ተጠያቂ ይሆናል።

    ከዚህ ውጭ በአንድ ሀገር የዘር ጭፍጨፋን ማስቆምና የውጭ ወረራን መከላከል ያልቻለ ማንኛውም መንግሥት በሥልጣን ላይ መቀጠል የሚችልበት ሕጋዊ፣ ፖለቲካዊም ሆነ ሞራላዊ ምክንያት የለም። ከዚህ በተጻራሪ የዘር ጭፍጨፋን ማስቆምና ሀገሪቱን ከውጭ ወራሪ መከላከል ያልቻለ መንግሥት፥ “ሌላ አማራጭ የለንም” በሚል ሰበብ በሥልጣን ላይ ሊቀጥል የሚችለው ኢትዮጵያ ሕልውናዋን ከጥፋት አድኖ የሚያስቀጥላት ትውልድና ዜጋ ያልፈጠረች መካን ሀገር መሆኗን አምነን ከተቀበልን ብቻ ይሆናል።

    በተጨማሪም በቅርቡ ትግራይ ክልል ውስጥ የገባንበት ጦርነት የሀገሪቱን አንድነት ከፍተኛ ጥያቄ ውስጥ የሚጥልና ከኛ ዘመንም አልፎ ምናልባትም ለልጅ ልጆቻችን የሚተርፍ ጣጣ የሚያስከትል አሳሳቢ ክስተት ነው። ስለሆነም ይህ ችግር በዘላቂነት በጦርነት ሊፈታ እንደማይችል በመገንዘብ ከሥልጣን ጥያቄ፣ ከበቀል፣ ከስሜትና ከጀብደኝነት በራቀ አተያይ ለችግሩ አስቸኳይ ሰላማዊና ፖለቲካዊ መፍትሔ መፈለግ ይኖርበታል።

    1. ሀገሪቱን ከሕልውና አደጋ መታደግ የሚችል ጠንካራ ፓርቲ መፈጠር አለበት

    ኢትዮጵያውያን ሁልጊዜም በሀገሪቱ በጎ የፖለቲካ ለውጥ እንዲመጣ የምንመኝና የምንፈልግ ቢሆንም ይህንን የሁልጊዜ ምኞታችንን ዕውን ለማድረግ የሚያስችል ጠንካራና ለመርህ ታማኝ የሆነ ፓርቲ መፍጠር እስካሁን አልቻልንም። ዛሬም እንደ ትናንቱ የሥርዓቱን ድክመቶችና ጥፋቶች ስንቆጥር የምንውል የፖለቲካ ድርጅት መሪዎች፣ ምሁራን፣ ጋዜጠኞችና አክቲቪስቶች ብንኖርም ያለጠንካራ ፓርቲ መኖር ሀገሪቱን ከጥፋት መታደግም ሆነ ዘላቂ ለውጥ ማምጣት እንደማይቻል መገንዘብ የቻልን አይመስልም። በምሬት፣ በጩኸትና በውግዘት ብቻ ሊመጣ የሚችል ዘላቂ ለውጥ እንደማይኖር ተገንዝበን ለመጭው ትርጉም የለሽ ምርጫ ከምንሰጠው ትኩረት በላይ ለሀገሪቱ ችግሮች የሚመጥን ጠንካራና ታማኝ ፓርቲ በመፍጠር ሥራ ላይ ማተኮር አለብን። በተለይም አንድነት ተኮር የሆነው የፖለቲካ ኃይል ከመቼውም ጊዜ በላይ በተዳከመበትና በተበታተነበት ሁኔታ ኢትዮጵያን ከጥፋት ለመታደግ የሚያስችል አስተማማኝ ለውጥ ማምጣት እንደማይቻል በመገንዘብ አዲሱ ትውልድ ዋና ተዋናይ የሚሆንበት ጠንካራና ታማኝ ፓርቲ መፍጠር ቀዳሚና ለነገ የማይባል አጀንዳችን መሆን ይገባዋል እላለሁ። ይህንን ማድረግ ካልቻልን “አማራጭ የለም” በሚል ሰበብ አምባገነኖችና የሀገርን ሕልውና አደጋ ላይ የሚጥሉ ፓርቲዎች ወይም መሪዎች ሁልጊዜም በሥልጣን ላይ የሚቀጥሉበትን ዕድል እንፈጥራለን።

    1. የቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረት ለሰላም

    የወቅቱ የሀገራችን ፖለቲካዊ ሁኔታ በብዙ ውጥረቶች የተሞላና በቀላሉ ተሰባሪ ነው። በዚህ ምክንያት ውጤታማ በሆነ የሽግግር ሂደት ሳይታለፍ የሚካሄደው መጪው ምርጫ ሀገራችንን ወደ ባሰ ግጭትና ትርምስ ሊያስገባ የሚችልበት ሰፊ ዕድል አለ። ይህ ስጋት በቂ መነሻ ምክንያት ያለው መሆኑን በመረዳት ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች የምርጫ ሂደቱ ወደ ግጭትና ብጥብጥ እንዳያመራ የማድረግ የጋራ ኃላፊነት አለባቸው። ይህንን በመገንዘብ ከፍተኛ ጥንቃቄ የተሞላበትና የሰከነ ሰላማዊ የምርጫ ቅስቀሳ ሊያካሒዱ ይገባል። አሁን ከምንገኝበት እጅግ ከባድና ውስብስ የፖለቲካ ሁኔታ አንጻር የሰላም እጦት የሀገሪቱን ሕልውና የሚፈታተን አደጋ ይዞብን ሊመጣ ስለሚችል፥ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምርጫውን አሸናፊ ለመሆን ከመሥራት በላይ ለሰላም መኖር የቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረት መስጠት ይኖርባቸዋል።

    በአግባቡ ካልተጠቀምንበትም በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ ያለው ማኅበራዊ ሚዲያ የብሔራዊ ደኅንነታችን ዋና የአደጋ ምንጭ ሊሆን ይችላል። ይህንን እውነታ በመገንዘብ ማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚ የሆኑ ዜጎቻችን በምርጫው ወቅት የሚኖራቸው ሚና ለሰላም ቅድሚያ በሚሰጥ የኃላፊነት ስሜት ሊካሄድ ይገባዋል። በአጠቃላይ ሀገራችን በአሁኑ ወቅት በውስጥም በውጭም ከፍተኛና አሳሳቢ ውጥረት ውስጥ የምትገኝ መሆኑን በመገንዘብ ለሰላም መኖር የቅድሚያ ቅድሚያ ትኩረት መስጠት ግዴታችን መሆኑን መገንዘብ ያስፈልገናል።

    1. ሕገ-መንግሥቱ ሳይሻሻል የፖለቲካ ችግራችን አይፈታም

    የወቅቱ የሀገራችን የፖለቲካ ችግር የሀገራዊ ብሔርተኞችንና የንዑስ ብሔር ብሔርተኞችን የተካረረ የፖለቲካ ቅራኔ በአንጻራዊነት በሚያቻችል አግባብ የወቅቱን ሕገ-መንግሥት ከማሻሻል ባነሰ ሌላ የመፍትሔ ርምጃ ሊፈታ አይችልም። ሕገ-መንግሥቱ እስካልተሻሻለ ድረስ ከማንነት ጋር በተያያዘ በአሁኑ ወቅት የተነሱትም ሆነ ወደ ፊት ባልተቋረጠ ሁኔታ ሊነሱ የሚችሉ ጥያቄዎች የሀገሪቱን ሰላምና ሕልውና እያወኩ መቀጠላቸው አይቀርም። ይህ ችግር ዘላቂ መፍትሔ እስካላገኘ ድረስም የሀገሪቱ ሰላም፣ አንድነት፣ ሕልውናና የኢኮኖሚ እጥረት በዘላቂነት መፍትሔ ሊያገኝ አይችልም።

    ከዚህ ግንዛቤ ጋር በተያያዘ በኔ በኩል ለውይይት መነሻ የሚሆን የሕገ-መንግሥት አማራጭ ረቂቅ ሰነድ በመጽሐፍ መልክ በማሳተም ላይ እገኛለሁ። የሕገ-መንግሥቱ መሻሻል ለሀገሪቱ የፖለቲካ ችግሮች መፈታት የሚኖረውን ምትክ የለሽ አዎንታዊ አስተዋዕፆ የምትገነዘቡ መገናኛ ብዙኃን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ምሁራንና ዜጎች በረቂቅ ሰነዱ ላይ ውይይት በማድረግ ትችት እንድታቀርቡበትና እንድታዳብሩት፣ ከተቻለም ሰነዱን በመጭው ምርጫም ሆነ በቀጣዩ የትግል ሂደት የጋራ የትግል አጀንዳ አድርጋችሁ እንድትጠቀሙበት በዚህ አጋጣሚ ጥሪዬን አቀርባለሁ።

    በመጨረሻም ከአቅም በላይ በሆነ የጤና ምክንያት ቢሆንም ሀገራችን ከመቼውም ጊዜ በላይ ዋጋ የሚከፍልላት ዜጋ በሚያስፈልጋት በአሁኑ ወቅት ለጊዜውም ቢሆን ከትግል ተሳትፎዬ ለመታቀብ በመገደዴ፥ የትግል አጋሮቼንና የዐላማ ደጋፊዎቼን ሁሉ ከልብ ይቅርታ እጠይቃለሁ። ይህንን የምለው ከእኔ ብዙ እንደምትጠብቁና ለእኔ ለራሴ እንደሆነብኝ ሁሉ ለእናንተም ይህ ክስተት ድንገተኛ መርዶ እንደሚሆንባችሁ ስለምገነዘብ ነው። ወደፊት የጤና ሁኔታዬ ተሻሽሎ እስከመጨረሻው በፖለቲካ ሂደቱ ለመቀጠል ለራሴ የገባሁትን ቃል ለመፈጸም ፈጣሪ ዕድል እንደሚሰጠኝ ተስፋ እያደረግኹ ሀገራችን ኢትዮጵያ መልካሙ ሁሉ እንዲገጥማት ያለኝን ልባዊ ምኞት በዚህ አጋጣሚ እገልጻለሁ።

    ልደቱ አያሌው

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ያለችበት የህልውና አደጋ በአቶ ልደቱ አያሌው እይታ

    #19108
    Anonymous
    Inactive

    ሚያዝያ 11 ቀን፥ 2013 ዓ.ም.
    አቶ ልደቱ አያሌው
    ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን
    አዲስ አበባ

    ጉዳዩ:- በድጋሚ አቤቱታ ማቅረብን ይመለከታል

    በቅድሚያ በእኔ በአመልካቹ ላይ በተደጋጋሚ እየደረሰ የሚገኘውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት መፍትሄ እንዲያገኝ መሥሪያ ቤታችሁ እያደረገ ስላለው ያልተቋረጠ ጥረት ልባዊ ምስጋናየን አቀርባለሁ። ሆኖም በእኔ ላይ እየተፈፀመ የሚገኘው የሰብዓዊ መብት ጥሰት አሁንም ያልተቋረጠና ለሕይወቴ አስጊ በሆነ ደረጃ ተጠናክሮ የቀጠለ በመሆኑ፥ ይሄንን አቤቱታ በድጋሚ ለማቅረብ ተገድጃለሁ።

    የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በሀገሪቱ የተፈጠረውን የፖለቲካ ቀውስ ሰበብ በማድረግ በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንድውል ከተደረገበት ከሐምሌ 17 ቀን፥ 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በሀገሪቱ ሕግና የሕግ የበላይነት የለም ሊያስብል በሚባል ደረጃ በርካታና ተከታታይ የሰብዓዊ መብት መብት ጥሰት በእኔ ላይ እየተፈፀመ ይገኛል። ለማስታወስ ያህል…

    1. ሕጋዊ ነዋሪነቴ ተመዝግቦ የሚገኘው በአዲስ አበባ ከተማ ሆኖ እያለ፥ እንድታሰር የተደረገው ግን ያለ አግባብ በኦሮሚያ ክልል ነው።
    2. በስልክ ተጠርቼና ለፌደራሉ ፖሊስ ኮሚሽን በእራሴ ፈቃድ እጄን ሰጥቼ በቁጥጥር ስር ከዋልኩ በኋላም በሕጉ መሠረት በ48 ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት እንድቀርብ አልተደረገም።
    3. በቁጥጥር ስር ከዋልኩ በኋላ ያለምንም ፍርድ ቤት ትዕዛዝ በስልክና በኢንተርኔት አማካይነት ያደረኳቸው የግል የመልዕክት ልውውጦች በሕገ-ወጥ መንገድ እንዲበረበሩና በሲዲ እንዲቀዱ ተደርገዋል። የግል ማስታወሻወቼና ረቂቅ የፅሁፍ ሰነዶቸ ሳይቀሩ በፖሊስ ተወስደዋል።
    4. በቁጥጥር ውስጥ ውዬ ገና ክስ እንኳ ባልተመሠረተብኝ ወቅት የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኛ ነን የሚሉ ሰዎች ወንጀለኛ እንደሆንኩ አድርገው ሰፊ የስም ማጥፋት ዘመቻ እንዲያካሂዱብኝ ተደርጓል።
    5. በምርመራ ወቅትና የምርመራ ፋይሌ ከተዘጋ በኋላም የዋስ መብት ተከልክዬና ክስ ሳይመሠረትብኝ በጊዜ ቀጠሮ ሰበብ ከሁለት ወራት በላይ ለሆነ ጊዜ በሕገ-ወጥ መንገድ በእስር ቤት እንድቆይ ተደርጓል።
    6. በፍርድ ሂደቱ ወቅት በግልፅ እንደታየው፥ በቢሾፍቱ ከተማ አመፅ አስነስተሀል፤ ሕገ-ወጥ መሣሪያ ታጥቀህ ተገኝተሀል፤ መንግሥትን በሕገ-ወጥ መንገድ አፍርሰሀል የሚሉ የፈጠራ ክሶች እንዲቀርቡብኝ ተደርጓል።
    7. “መንግሥትን በሕገ-ወጥ መንገድ አፍርሰሀል” በሚል የተከሰስኩበት ወንጀል አዲስ አበባ በሚገኝ የፌደራሉ ፍርድ ቤት መታየት ሲገባው ያለ አግባብ በአዳማ ከተማ የሚገኘው የኦሮሚያ ክልል ጥቅላይ ፍርድ ቤት በውክልና እንዲያየው ተደርጓል። ይህም መሆኑ የፍርድ ሂደቱ በማልናገረው ቋንቋ እንዲካሄድና ብዙ ውጣ ውረድ እንዲደርስብኝ አድርጓል።
    8. በፍርድ ሂደቱ ወቅት ለሁለት ጊዜ ያህል የዋስ መብት በፍርድ ቤት ቢፈቀድልኝም ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ በመጣስ ለሁለት ወራት ያህል በእስር አቆይቶኛል። ከዋስትና መብቴ ጋር በተያያዘም ፍርድ ቤት ለአምስት ጊዜ የሰጣቸው የተለያዩ ትዕዛዞች በፖሊስ እምቢተኝነት ሳይፈፀሙ ቀርተዋል።
    9. ለሕይወት አስጊ የሆነ ከፍተኛ የልብ ህመም ያለብኝ ሰው መሆኔ እየታወቀም የኮቪድ ወረረሽኝ ተጠቂ ከሆኑ ሰዎች ጋር በአንድ ጠባብ ግቢ ውስጥ ታስሬ ለረጅም ጊዜ እንድቆይ ተደርጓል።
    10. ከአምስት ወራት መታሰር በኋላ የዋስ መብቴ ተጠብቆ ከተፈታሁ ከጥቂት ቀናት በኋላም እኔንና የትግል ጓደኞቼን ከሀገሪቱ የፖለቲካ ሂደት ለማግለል ሲባል አባል የሆንኩበት የፖለቲካ ፓርቲ በሕገ-ወጥ መንገድ እንዲሰረዝና ህልውናውን እንዲያጣ ተደርጓል።
    11. ከእስር ቤት ወጥቸ አስቸኳይ የቀዶ ጥገና የሕክምና እርዳታ ለማግኘት ወደ ውጭ ሀገር ለመጓዝ ለሁለት ጊዜ ያደረኩት ሙከራም ምንም አይነት የፍርድ ቤት እገዳ ባልተጣለብኝና እንዲያውም ጉዳዩን ይመለከት የነበረው ፍርድ ቤት ወደ ውጭ ሀገር ሄጀ የመታከሜን አስፈላጊነት በማመን ረዥም ቀጠሮ ሰጥቶኝ እያለ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት መሥሪያ ቤት በሕግ ባልተሰጠው ሥልጣን ባደረገብኝ ሕገ-ወጥ ክልከላ ምክንያት ከሀገር የመውጣት ሕገ- መንግሥታዊ መብቴ ተጥሷል።
    12. ይህ የተጣለብኝ ሕገ-ወጥ እገዳ እንዲነሳልኝ ለማድረግ የተለያዩ ጉዳዩ የሚመለከታቸውን የመንግሥት ባለ ስልጣናት ቀጠሮ ይዤ ለማነጋገር በተደጋጋሚ ብሞክርም ባለስልጣናቱ ሊያናግሩኝ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ሙከራዬ ሳይሳካ ቀርቷል።
    13. መሥሪያ ቤታችሁ ባደረገው ጥረት ምክንያት የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት መሥሪያ ቤት በእኔ ላይ ምንም ዓይነት የጉዞ ክልከላ እንዳላደረገ የሚክድ ደብዳቤ ለመሥሪያ ቤታችሁ ከፃፈ በኋላም ለሦስተኛ ጊዜ ከሀገር ለመውጣት ያደረኩት ሙከራ የኢሚግሬሽን ዜግነትና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ ክልከላ ስላደረገብኝ ጉዞዬ ሳይሳካ ቀርቷል። የጉዞ ፓስፖርቴም በመሥሪያ ቤቱ ባልደረቦቼ ተወስዶብኛል።
    14. የኢሚግሬሽን መሥሪያ ቤት ለምን የጉዞ ክልከላ እንዳደረገብኝና እንደቀማኝ በማግስቱ ዋናው መሥሪያ ቤት ድረስ ሄጄ ለመጠየቅ ባደረኩት ሙከራ የፌዴራሉ ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል ባቀረበው ጥያቄ መሠረት በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውዬ ምርመራ እስከሚካሄድብኝ ድረስ የፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የአራዳ ምድብ አንደኛ ችሎት የካቲት 4 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. በዋለው ችሎት ወደ ውጭ እንዳልጓዝ እገዳ የጣለብኝ ስለመሆኑ ተነግሮኛል።

    ከእነዚህ ከዚህ በላይ ከተዘረዘሩት ተደጋጋሚ የመብት ጥሰቶች በግልፅ መረዳት እንደሚቻለውና በእኔ በኩል እንደምገነዘበውም መንግሥት በእኔ ላይ ይህን ሁሉ የመብት ጥሰት እየፈፀመ የሚገኘው የፈፀምኩት ወንጀል ስላለ ሳይሆን መብቴን በሕገ-ወጥ መንገድ በመጣስና በመገደብ ከፖለቲካ ተሳትፎ ውጭ እንድሆን ስለፈለገ ነው።

    እኔ አመልካቹ የአለፈ ታሪኬ እንደሚያሳየው ለሃያ ስምንት ዓመታት በሀገሪቱ ፖለቲካ በነበረኝ ተሳትፎ ስድስት ጊዜ በሕገ-ወጥ መንገድ በፈጠራ ክስ የታሰርኩ ቢሆንም አንድም ጊዜ በወንጀለኝነት ተፈርዶብኝ አያውቅም። የኢትዮጵያ ህዝብ በግልፅ እንደሚያውቀው በዚህ የረጅም ጊዜ የፖለቲካ ተሳትፎዬ ስታገል የኖርኩት በሀገሪቱ ዘላቂ ሰላም፣ እርቅና የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን ሲሆን፤ በአንፃሩም ሕገ-ወጥነትን፣ አመጽንና የኃይል አማራጭን በግልፅና በድፍረት በማውገዝ የምታወቅ ሰላማዊ የፖለቲካ ሰው ነኝ። ሆኖም መንግሥት ከላይ በተገለፀው ሁኔታ በፈጠረብኝ ተከታታይ ሕገ-ወጥ ጫና ምክንያት በአሁኑ ወቅት ከፖለቲካ ተሳትፎዬ ሙሉ በሙሉ ለመገለል የተገደድኩ ሲሆን ከዚያም በላይ ያለብኝን ከፍተኛ የልብ ህመም ወደ ውጭ ሀገር ሄጀ መታከም ባለመቻሌ ምክንያት በህይወት የመኖር ዕድሌ ከፍተኛ አደጋ ላይ ወድቋል። በአጠቃላይም እየደረሰብኝ ባለው ተደጋጋሚ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ምክንያት ለከፍተኛ የጤና መታወክ፣ የሞራል ውድቀት፣ የገንዘብና የጊዜ ብክነት ተዳርጊያለው።

    ይህ ሁሉ በተደጋጋሚ የተፈጸመብኝ በደል አልበቃ ብሎም እኔ አመልካቹ ፈጽሞ ባልተነገረኝና በማላውቀው ሁኔታ፣ ምንም ዓይነት ጥያቄ ባልቀረበልኝና ምርመራ ባልተካሄደበት ሁኔታ፣ ከዚያም በላይ ተፈልጌ የጠፋሁ ወንጀለኛ የሆንኩ በሚያስመስል ሁኔታ የጉዞ እገዳ የተጣለብኝ ስለመሆኑ የአራዳ ፍርድ ቤት ሰጠ የተባለው ትዕዛዝ አሁንም በእኔ ላይ የፈጠራ ክስ እንደገና በመመሥረት እንድታሰርና ሕይወቴ አደጋ ውስጥ እንዲወድቅ እየታሰበና ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ነው።

    በአንድ ሰው የደረሰ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በሁሉም ሰው ላይ እንደደረሰ ጥሰት የሚቆጠር መሆኑን ታሳቢ በማድረግና በእኔ ላይ እየተፈፀመ ያለው ተደጋጋሚ መቋጫ ያጣ የሰብዓዊ መብት ጥሰትም የፖለቲካና ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ ሕገ-መንግሥታዊ መብቴን ከመጣስም በላይ በሕይወት ለመኖር ያለኝን የማይገሰስ ሰብዓዊ መብቴን አደጋ ላይ የጣለ መሆኑን ግምት ውስጥ በማስገባት፥ መሥሪያ ቤታችሁ በጉዳዩ ልዩ ትኩረት በመስጠት ምርመራ እንዲያካሂድልኝና አስቸኳይ መፍትሔ እንዳገኝ እንዲያግዘኝ በድጋሚ በአክብሮት እጠይቃለሁ።

    ከሰላምታ ጋር!
    ልደቱ አያሌው

    ግልባጭ፦
    ለመገናኛ ብዙሀን

    አቶ ልደቱ አያሌው ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የጻፉት ደብዳቤ

Viewing 15 posts - 16 through 30 (of 36 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.