Search Results for 'መተከል'

Home Forums Search Search Results for 'መተከል'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 16 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    ሱዳን በኢትዮጵያ ላይ ያደረገችውን ወረራ አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) የተሰጠ መግለጫ

    “ከድንበሩ ቆሞ ጌታ ካልመለሰው፥
    መሬትም ይሄዳል እግር አለው እንደ ሰው።”

    የሀገራችን ዳር ድንበር በአባቶቻችንና በእናቶቻችን ደምና አጥንት ተለስኖ የተሠራ የማይነቃነቅ አምድ እንጂ፥ እንደ ሰንበሌጥ አጥር ማንም በፈለገው ጊዜ እየጣሰው የሚገባ ድንበር አይደለም። ሀገሩንና ድንበሩን የማያስከብር ሕዝብ ለባርነት እንደተዘጋጀ ይቆጠራል። ለአንድ ዜጋ ሀገርና ድንበር የክብሩ ከፍተኛ መገለጫው ነውና።

    ኢትዮጵያ ሀገራችን በትግራይ ከአሸባሪው የህወሓት ቡድን እንዲሁም በመተከል በኦሮሚያ ክልል ጽንፈኞችን ለማጽዳት ከፍተኛ ግብግብ በምታደርግበት ወቅት፣ ሱዳን ድንበራችንን ተሻግራ ጦሯን ማስፈሯንና በአካባቢው በነበሩ ኢትዮጵያውን ገበሬዎች ላይ ጥቃት መፈጸሟን የተለያዩ የዜና አውታሮች የዘገቡት ሃቅ ነው። አሁን በቅርቡ ደግሞ በምዕራብ አርማጭሆ በደለሎ የገበሬዎችን የእርሻ ምርት ማቃጠሏን በከፍተኛ ቁጭት ሰምተናል። ይህ የሱዳን ድፍረት ማንኛውንም ኢትዮጵያጵያዊ ዜጋ እጅግ የሚያስቆጣ እርምጃ በመሆኑ ሁላችንንም እንቅልፍ የሚነሳ ድፍረት ነው ይላል ኢሕአፓ።

    የድንበር ውዝግቡ ለረዥም ጊዜ እልባት ሳያገኝ የቆየ መሆኑ ቢታወቅም፥ ኢትዮጵያ አንድም ጊዜ ድንበሯን አልፋ አንድ ጋት መሬት ከሱዳን ፈልጋ አታውቅም። ሱዳን ግን አጋጣሚ እየጠበቀች በተደጋጋሚ ከመተንኮስ ቦዝና አታውቅም። በሰላማዊ ጊዜም ከብቶቿን ወደ ኢትዮጵያ መሬት አሻግራ እንዲግጡ በመድረግ፣ ለእጣን የሚሆን ሙጫ በመሰብሰብ፣ ለቤትና ለማገዶ የሚሆን እንጨት እየቆረጠች በመውሰድ የምትፈጽማቸውን ድርጊቶች ኢትዮጵያውያን ገበሬዎች በመቃወማቸው በተደጋጋሚ ስትጋጭ ኖራልች። ኢሕአፓ በአካባቢው በሚንቀሳቀስበት ጊዜም ይህን ለማስቆም ለሱዳን መንግሥት ገበሬዎቻቸው ድንበራችንን እየተሻገሩ የሚያደርጉትን የጥሬ ሀብት ስብሰባና የከብት ግጦሽ እንዲያስቆሙ በተደጋጋሚ ጠይቆ አሻፈረኝ ስላሉ፤ የአካባቢውን የምዕራብ በጌምድርን (መተማ፣ ቋራ፣ ጫቆ) ሕዝብ አስተባብሮ የሱዳንን ጦር በመውጋት ድል አድርጎ የኢትዮጵያን ድንበር አስከብሮ አንደነበረ የሚታወቅ ነው። በዚህም ምክንያት ሱዳን የነበሩ የድርጅቱ አባሎች ለእስርና እንግልት ተዳርገዋል፤ የተወሰኑትንም ለህወሓት በማስረከብ ለሰቆቃ/ግርፋትና እስር እንዲዳረጉ አድርገዋል። ገዳሪፍ የነበረውን የድርጅቱን ጽሕፈት ቤት በርብረው የድርጅቱን ንብረቶች ወስደዋል። ከህወሓት ጋር በመተባበር ኢሕአፓን ከበው ወግተዋል። ህወሓትንም አጅበው አዲስ አበባ አስገብተው ተመልሰዋል።

    ህወሓት እና የሱዳን መንግሥት ከመጀመሪያ ጀምረው የጠበቀ ወዳኝነት እንደነበራቸው ይታወቃል። በደርግ ዘመን ህወሓት ጉልበት ያገኘውና የኢትዮጵያን ጦር አሸነፍኩ ያለው ሱዳን ከፍተኛ መከታና ደጀን ሆና ስለረዳቻቸው ጭምር ነው። ለዚህ ውለታ ሱዳኖች ድንበራችን ጥሰው በደለሎ በኩል ገብተው ኢትዮጵያውያን ገበሬዎችን አፈናቆለው ለረዥም ዓመታት ሲያርሱ ኖረዋል። የአካባቢው ገበሬዎች ድርጊቱን በመቃወም ሲከላከሉ፣ የህወሓት ካድሬዎች “መንግሥትና መንግሥት ይነጋገራል እንጂ ገበሬውን አያገባውም” በማለት ኢትዮጵያውያንን ገበሬዎችን ያስሩና ያንገላቱ ነበር። እውነታው ግን ሱዳን እንደፈለገች የኢትዮጵያን መሬት እንድትጠቀም በነአባይ ፀሐዬ የተሸረበ ሤራ መሆኑ ነው። የገበያ ግርግር ለሌባ ያመቻል እንዲሉ፥ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት የህወሓትን አሸባሪ ቡድን ለማፅዳት ጦርነት እያደረገ በነበረበት ወቅት ሱዳን ድንበራችንን ተሻግራ ኢትዮጵያውያን ገበሬዎችን ከማሳቸው ያፈናቀለችው የወዳጇ የህወሓት መመታት ስለከነከናትና በአጋጣሚውም የረጅም ጊዜ ምኞቷን ለማሳካት የወሰደችው እርምጃ ነው።

    ሱዳን ድንበራችንን የጣሰችበት ሌላው ምክንያት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሥራ ለማደናቀፍ እንዲቻል ከሱዳን ጀርባ ተጫማሪ ገፊ ኃይል ሊኖር እንደሚችል መገመት አይቸግርም። ከዚህ በተጨማሪ ህወሓትና የውጭ ደጋፊዎቻቸው ትግራይ ውስጥ የሚደረገውን የሀገር አፍራሹን ቡድን የማጽዳት ዘመቻ ቀጣናዊ መልክ ለማስያዝ የሚጥሩትን እውን ለሜድረግ ሱዳን የጦስ ዶሮ ሆና መቅረቧ አጠራጣሪ አይደለም እንላለን።

    በጦርነቱ ሳቢያ በትግራይ ውስጥ የተጎዳው ሕዝባችን አስፈላጊው እርዳታ እንዲደርሰው መንግሥት እስካሁን እያደረገ ያለው ድጋፍ በተጠናከረ መልክ እንዲቀጥልና የዓለምአቀፍ የሰብዓዊ ድርጅቶችም እርዳታና ድጋፋቸውን በመንግሥት በኩል ለሕዝቡ የሚደርስበትን መንገድ እንዲያመቻች እናሳስባለን።

    የኢትዮጵያ መንግሥት ሱዳን መሬታችንን ለቃ እስክትወጣ ድረስ የሱዳንን ትንኮሳ ጥንቃቄ በተሞላበት በሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገድ በመያዝ ከፍጻሜ ለማድረስ ከፍተኛ ትግል ማድረግ ይኖርበታል። ድንበራችን በቋሚነት የሚከለልበትንም መንገድ እንዲያመቻች እናሳስባለን።

    የኢትዮጵያ ሕዝብ የሀገሩን ዳር ድንበር ለማስከበርና የሀገሩን አንድነት ለማስጠበቅ ሊፋለም እንደሚችል ግልጽ መሆን አለበት። ሕዝባችን በተደጋጋሚ እንዳስመሰከረው ሱዳን ከሀገራችን ክልል እስክትወጣ ድረስ አስፈላጊውን መስዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ በመሆን፥ ከመከላከያ ሠራዊታችን ጎን እንደሚቆም አንጠራጠርም። ኢሕአፓም በማንኛውም መንገድ ከሕዝባችን ጎን ዘብ ለመቆም ዝግጁ መሆኑን ያረጋግጣል። አባቶቻችን ስለሀገርና ድንበር ሲነሳ እንደ እግር እሳት ሲያንግበግባቸው፦

    “ከደንበሩ ቆሞ ጌታ ካልመለሰው፥
    መሬትም ይሄዳል እግር አለው እንደ ሰው”

    ይሉ ነበር።

    ኢትዮጵያ በልጆቿ ታፍራና ተከብራ ለዘለዓለም ትኖራለች!
    የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)
    ጥር 29 ቀን፥ 2013 ዓ. ም.

    ሱዳን ያደረገችውን ወረራ

    Anonymous
    Inactive

    በፊትም፣ አሁንም እስትንፋሷ በመሪዋ ላይ ብቻ የሆነባት ሀገር
    (ጋዜጠኛ መላኩ ብርሀኑ)

    እንደአለመታደል ሆኖ የዚህች ሀገር ሰላምና ደህንነት ተጠቃሎ በመሪዎቿ በሰላም ውሎ በሰላም የማደር መዳፍ ውስጥ የገባው ዛሬ አይደለም።

    እንኳን በሰላም ጊዜ ሀገርን መምራት ቀርቶ በጦርነት የማሸነፍና ወጥሮ የመዋጋት ነገር እንኳን የንጉሡን በህይወት መኖር የሚታከክ ነገር ነበር – እዚህ ሀገር። እልፍ ሆኖ ተሰልፎ ድል በእጁ መግባቱን እንኳን እያወቀ ንጉሡ ከተመታ ጦሩ በቀላሉ ይፈታል። ሕዝቡ ንጉሡ ከሌሉ ሀገር የለም እየተባለ ሲሰበክ ነው የኖረው።

    እናቶች ንጉሥ ከሌለ የሚመጣውን መአትና እልቂት በመፍራት ለንጉሡ ረጅም ዕድሜ ከመመኘት በላይ “ከንጉሡ በፊት እኔን አስቀድመኝ” ብለው ይጸልዩም ነበር። ምኒልክ ሲሞቱ የሞታቸው ዜና ለሕዝብ ሳይነገር ስንት ዓመት ፈጀ? መልሱ ይኸው ነው። አጼ ኃይለሥላሴ አንድ ነገር ቢሆኑ ሀገር ያበቃላታል ብለው የሚያምኑ ኢትዮጵያውያን ደርግ በቮልስዋገን ከቤተ መንግሥት ይዟቸው ሲወጣ ሲያዩ ነው ወደሩሃቸው የተመለሱት።

    መንግሥቱ ኃይለማርያም በተራው በኢህአፓ የመግደል ሙከራ ሲደረግበት “ሞተ” ተብሎ አብዮቱ የእልቂት እንዳይሆን (ላይቀርለት ነገር) አደባባይ ወጥቶ ነው እግሩን እጥፍ ዘርጋ እያደረገ ነው “አለሁ” ያለው። መለስ ዜናዊ ሞተ ሲባልም በርካቶች በዚሁ “ሀገር ያበቃላታል” ፍርሃት ውስጥ ነበሩ። እነበረከት አደባባይ ወጥተው “ታጋይ ያልፋል ሀገር ይቀጥላል” ዓይነት ነገር ተናግረው ስጋት ቀንሰዋል።

    የዛሬው መሪ አብይ አህመድ ጉዳይ ግን ከነገሥታቱ በኋላ ካሉት መሪዎች ሁሉ በብዙ ይለያል። ጊዜው ጥቂት ቢሆንም ቅሉ ሃሳቡንና አመራሩን ተቋማዊ ማድረግና ግለሰባዊ ተጽዕኖውን በጥቂቱም ቢሆን ለመቀነስ አልቻለም። ስለዚህ አብይ ተወደደም ተጠላ አሁን ባለው አስተዳደር ውስጥ ብቸኛና መተኪያ የሌለው መሪ ነው።

    አብይ አህመድ እና ጓዶቹ ሲሠሩለት እና ሲያስተዳድራቸው የኖረውን ኢህአዴግ የተባለ ተቋም ከውጭ በነበረ ተቃውሞ ታግዘው ከውስጥ በመፈርከስ ቀንብሩን ከላያቸው ገርስሰው የጣሉ የግለሰቦች ስብስብ እንጂ የተደራጀ ተቋም አልነበሩም። የለውጡ መሪዎች ናቸው የተባሉ ሰዎች በመሃል እየተንጠባጠቡ አብይ ብቻ ሲቀር፣ ቀርቶም ብዙዎች ያደነቁትን ለውጥ እያመጣ ሲቀጥል ብቻውን ገንኖ ወጣ።

    አብይ ከመጣበት ማኅበራዊ መሠረቱ አካባቢ የገጠመው ተግዳሮት አሁን ድረስ በብርቱ ቢገርመኝም በሰሜን አካባቢ ካሉ ሰዎች ዘንድ የተጠላ ሰው መሆኑ ግን አይደንቀኝም። በካልቾ ብሎ ከወንበራቸው ላይ ያባረራቸው ሰዎችና “ገዢነት ካለኛ ለማን!?” ያሉ ጀሌዎቻቸው ሊወዱት አይጠበቅም። ይህም ከዚያ ሰፈር በአብይ ጥላቻ ሳቢያ ሀገር እንድትበተን የሚሠሩና የሚመኙ ድኩማን እንዲፈለፈሉ ምክንያት ሆኗል። መተከል ላይ እየሆነ ባለው “መሪና አቀነባባሪ” ብለው እሱ ላይ ጥርስ የነከሱበት፣ “ወለጋ ላይ ቢገኝ እኔን አያርገኝ” ያሉ የበረከቱበት፣ በመጋቢት መጥቶ በሰኔ ሞቱ የተደገሰለት ሰው ነው አብይ።

    ሰውየው የሀገሪቱን ፖለቲካ ብቻውን እየዘወረ፣ በዚህም በዚያም ሁሉን ነገር ብቻውን እየሠራ፣ አውቆም ይሁን ሳይታወቀው ያለምንም ቀሪ ብቻውን የቆመ፣ የማይካፈል ቁጥር ሆኖ ወጣ። ዛሬ በሰሜን ለተፈጠረውም፣ በደቡብ ላለውም፣ በመሃል ለሆነውም፣ በምዕራብ ለተከሰተውም ችግር ሁሉ ተጠያቂው አብይ ነው የሚል አቋም ባላቸው በርካታ አካላት ሲሰደብ ውሎ የሚያድረው ሰውዬ ወዲህ ጦር እያዘዘ፣ ወዲህ ሀገርና ከተማ እየለወጠ ብቻውን ሲሠራ አጠገቡ የሚተካው ቀርቶ የሚመስለው እንኳን አለማየታችን ፈሪ አድርጎናል።

    [ሰሞኑን] አብይ [ሞተ/ታመመ] ምናምን ሲባል ድንጋጤው የበረታው ከርሱ ሞትም በላይ ነገ ሊሆን የሚችለውን እያሰበ ሁሉም ሰላምና ደህንነቱ ስላስጨነቀው ነው፤ ይህ አለመታደል ነው።

    በግሌ ኢትዮጵያን በከረጢት ውስጥ እንዳለ የተፈጨ ዱቄት፣ አብይን ደግሞ ከረጢቱን የዝቅዝቆሽ አዝሎ ጫፉን በእጁ ጨምድዶ እንደያዘው ተሸካሚ ዓይነት ነው የምመስላቸው። የከረጢቱ ጫፍ ከተለቀቀ ዱቄቱ ከአፈር ይደባለቃል። ይሄ ነው የሚያስፈራኝ።

    አብይን በብዙ የማደንቀው መሪ ቢሆንም በዚህ “the one and only” አካሄዱ ግን ቅሬታ አለኝ። ስለዚህ የእርሱን ደህንነት አጥብቄ የምመኘው በግል ለርሱ ባለኝ ጥሩ ስሜት እና ከፍ ያለ አድናቆት ብቻ ሳይሆን በዋናነት ለዚህች ሀገር ሰላምና መረጋጋት፣ ሲቀጥል ለሕዝቡ በሰላም ወጥቶ በሰላም መግባት፣ ጠበብ ሲል ለቤተሰቤ ደህንንት፣ በጣም ሲጠብ ለራሴ ደህና ወጥቶ ደህና መግባት ብዬ ነው።

    ሰሜኑ አቅሙ ከነሞራሉ ቢደቅቅም ቂሙ ግን ከምንጊዜውም በላይ ጠንኖ ሀገር ብትፈርስ ደስ እንደሚለው በአደባባይ በሚናገርበት፣ ምዕራቡ በፈሪ ዱላ ጫካ ለጫካ እየተሯሯጠ የተሸከመውን መሣሪያ አፍ እያስከፈተ ንጹኃንን በሚረፈርፍበት፣ ከውጭ ግብጽና ሱዳን ቤንዚን በጀሪካን ይዘው እሳታችን ላይ ለመድፋት አጋጣሚ በሚቋምጡበት፣ ብቻ በየትኛውም መስመር ለዚህች ሀገር መልካም የሚመኝ በታጣበት በዚህ ጊዜ አብይ አንድ ነገር ቢሆን ስርዓት ሲናድና ነገር እንዳልነበር ሲሆን ሰዓት የሚፈጅበት አይመስለኝም። ሌሊት እንኳን ቢሆን በርህን ለመስበር እስኪነጋና ከእንቅልፍህ እስክትነቃ እንኳን የሚጠብቅህ የለም!

    በበኩሌ በመሪ ደህንንት ላይ የተንጠለጠለች ሀገር ይዘን ዛሬ ድረስ መኖራችንን ስታዘብ ያለመታደል እለዋለሁ።

    ሰውየውን መደገፍና መቃወም ሌላ ነገር ሆኖ የማንክደው ሃቅ ግን አሁንም ሰላማችን በዚህ ሰው ደህና መሆንና አለመሆን የተወሰነ ሆኖ መዝለቁ ነው። ስለዚህ የተወራበት እንኳን ሀሰት ሆነ! አሹ! ብያለሁ። እንደሰው ሳስብ ደግሞ አብይን ሞት ቀርቶ ጭረት እንዲነካው አልመኝም። [እርሱም ቢሆን] እንደማናችንም የሰላም እንቅልፍ ተኝቶ ማደር አይጠላም። ሀገር ብሎ መሰለኝ የጋለ ምጣድ ላይ የተቀመጠው።

    በግሌ ግን መንግሥት ይሁን አስተዳደር ተቋማዊ ሆነው “ሰዎች ያልፋሉ፣ ሀገር ግን ትቀጥላለች” የምንልበትን ዘመን እናፍቃለሁ።

    ጋዜጠኛ መላኩ ብርሀኑ

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    እስትንፋሷ በመሪዋ ላይ ብቻ የሆነባት ሀገር

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ጋዜጣዊ መግለጫ
    ትግራይና አማራ ክልል፡ የሲቪል ሰዎች ደኅንነትና ከትግራይ ክልል የተፈናቀሉ ሰዎች ሁኔታ ወደ ሰብዓዊ ቀውስ ሊያመራ ይችላል
    አስቸኳይ ሰብዓዊ እርዳታ እና ድጋፍ ሊቀርብ ይገባል

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ/ኮሚሽኑ) ጦርነት በተካሄደባቸው የትግራይ ክልል እና አዋሳኝ አካባቢዎች ያለው ሁኔታ፣ በቦታው ያሉ የሲቪል ሰዎች ደኅንነት እንዲሁም በጦርነቱ ምክንያት ከመኖሪያ ቦታቸው የተፈናቀሉ ሰዎች በአሳሳቢና ወደ ሰብዓዊ ቀውስ ሊያመራ በሚችል ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ ገለጸ። ኮሚሽኑ ከታኅሣሥ 6 እስከ ታኅሣሥ 11 ቀን 2013 ዓ.ም.  በጎንደር እና በዳንሻ በመገኘት እንዲሁም፣ ከታኅሣሥ 22 እስከ ታኅሣሥ 27 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ ደግሞ በትግራይ ክልል፣ ደቡባዊ ዞን፣ ጨርጨር ወረዳ በሚገኙት ኡላጋ እና ቢሶበር መንደሮች በመጓዝ የመንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ አካላት እንዲሁም ተጎጂዎችና ሌሎች የሚመለከታቸውን አካላት በማነጋገር ያደረገውን ክትትል ሪፖርት ይፋ አድርጓል።

    በተጨማሪም የኮሚሽኑ ባለሞያዎች ከጥር 2 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ለተጨማሪ ዙር የመስክ ምልከታ ወደ መቀሌ ከተማ እና ሌሎች የትግራይ ክልል አካባቢዎች በመንቀሳቀስ፥ በግጭቱ ምክንያት የተፈጠረውን የሰብዓዊ ቀውስ እና የሰብዓዊ መብት ጉዳዮች በመመርመር ላይ የሚገኝ ሲሆን ሥራው እንደተጠናቀቀ ተጨማሪ ሪፖርቱን ይፋ የሚደረግ መሆኑን ኮሚሽኑ አክሎ አሳውቋል።

    የአሁኑ ክትትል በዋነኛነት በተካሄደባቸው በዳንሻ፣ በሁመራ፣ በቢሶበር እና በኡላጋ ጦርነቱ የሲቪል ሰዎችን ሞትና አካላዊ ጉዳት አስከትሏል፤ የሲቪል ሰዎችን መኖሪያና የንግድ ቦታዎች ለዝርፊያና ለተለያዩ ጉዳቶች አጋልጧል፤ እንዲሁም በመሠረተ ልማቶች ላይ የደረሰው ውድመትና የኤሌክትሪክ እና የውሃ የመሳሰሉ አገልግሎቶች አለመመለስ፣ በአካባቢዎቹ ነዋሪዎች እና በተፈናቃናዮች ላይ የበለጠ ሰብዓዊ ቀውስ እንዳያስከትል የሚያሰጋ ነው። በቢሶበር እና በኡላጋ  31 ሲቪል ሰዎች ሞተዋል፤ 104 መኖሪያ ቤቶች በከፊል ወይም ሙሉ በሙሉ ተቃጥለዋል፤ እንዲሁም የአካባቢው ትምህርት ቤትና ጤና ጣቢያ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    በተመሳሳይ መልኩ በሁመራ እና በዳንሻ የሲቪል ሰዎች ንብረት የሆኑ መኖሪያ እና ንግድ ቤቶችን ጨምሮ የአካባቢው አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ላይ ውድመት እና ዝርፊያ ደርሷል። ሲቪል ሰዎች በብሔራቸው ምክንያት ወይም በአካባቢዎቹ የፀጥታ መጓደል ምክንያት ለደኅንነታቸው እንደሚሰጉ ለኮሚሽኑ ገልጸዋል። በአጠቃላይ በእነዚህ አራት ከተሞች ያለው የፀጥታ ስጋትና  የፍትህ አካላት ወደ መደበኛ ሥራቸው አለመመለስ፣ የሰዎችን ደኅንነት ለማስጠበቅና የሰብዓዊ መብቶቻቸውን ጥበቃ ለማረጋገጥ አዳጋች አድርጎታል።

    ከዚህ ጋር ተያይዞ በርካታ ጉዳቶች ሊከሰቱ እንደሚችሉ ሲያስረዱ፥ የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ “ምርመራውና ክትትሉ በተካሄደባቸው አካባቢዎች ያለው የፀጥታ ሁኔታ፣ የነዋሪዎቹንም ሆነ ከትግራይ ክልል ወደ አዋሳኝ አካባቢዎች የተፈናቀሉ ሰዎችን ሰብዓዊ እርዳታ ፍላጎት እንዲጨምርና የመቋቋም አቅማቸውን በአስከፊ ሁኔታ እንዲፈተን አድርጓል” ብለዋል። የኮሚሽኑ ምርመራ ቡድን የጎበኟቸው ተጎጂዎች በአብዛኛው በአካባቢው ነዋሪዎች ብቻ እርዳታ የተደረገላቸው አሊያም አንድ ዙር ብቻ እርዳታ የተደረገላቸው መሆኑን በሪፖርቱ እንደተመለከተ ጠቅሰው፥ “በአካባቢዎቹና በሲቪል ሰዎች ላይ የደረሰው ጉዳት የሁሉንም የሚመለከታቸውን አካላት ከፍተኛና አፋጣኝ ርብርብ የሚጠይቅ ነው” በማለት ገልጸዋል።

    ሙሉውን ሪፖርት እዚህ ጋር (ማስፈንጠሪያ) በመጫን ማግኘት ይቻላል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)

    The security situation of civilians and IDPs in Tigray region የሲቪል ሰዎች ደኅንነትና ከትግራይ ክልል የተፈናቀሉ ሰዎች ሁኔታ ወደ ሰብዓዊ ቀውስ ሊያመራ ይችላል ― ኢሰመኮ

    Anonymous
    Inactive

    መቆሚያ ያጣው በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል ዞን) ያሉ ሰዎች እልቂት!
    አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ (ኢሰመጉ)

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ) በቤንሻንጉል ጉሙዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ መተከል ዞን፣ በቡለን፣ ድባጤ፣ እና ዳንጉር ወረዳዎች ላይ በንጹኃን ሰዎች ላይ የሚፈጸመው ጥቃት አሁንም ተባብሶ መቀጠሉ እጅግ አሳስቦታል።

    ኢሰመጉ ታህሳስ 15 ቀን 2013 ዓ.ም ባወጣው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል ዞን)፣ ቡለን ወረዳ፣ በኩጂ ቀበሌ ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት ከ100 በላይ ንጹኃን ሰዎች መገደላቸውን፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መፈናቀላቸውን እና ለከፍተኛ ችግር የተጋለጡ መሆናቸውን አውግዞ፤ መንግሥት በአካባቢው በተደጋጋሚ ጊዜ የሚከሰተውን የንጹኃን ሰዎች ሰቆቃ ለማስቆም የሚያስችል ፈጣን፣ ተጨባጭ እና ዘላቂ መፍትሔ እንዲያበጅ ማሳሰቡ አይዘነጋም።

    ሆኖም፤ ከሰሞኑ ይኸው ችግር ዳግም ተከስቶ ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውን ተጎጂዎች እና የተጎጂ ቤተሰቦች ለኢሰመጉ ተናግራዋል። ታህሳስ 25 ቀን 2013 ዓ.ም ከቻግኒ ወደ ግልገል በለስ የሚሄድ መኪና ውስጥ የነበሩ ተጓዦች ማንዱራ ከተማ ላይ በታጣቂዎች እንዲወርዱ ተደርጎ አንድ ሰው መገደሉን እና ሁለት ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን ለማወቅ ተችሏል።

    ከጥር 2 እስከ ጥር 3 ቀን 2013 ዓ.ም. በቡለን እና ጉባ ወረዳዎች፣ ኦሜድላ እና አይነሸምስ በተባሉ ቀበሌዎች ላይ ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት ከ50 በላይ ሰዎች መገደላቸውን እና መኖሪያ ቤቶችም መቃጠላቸውን ኢሰመጉ መረጃዎች ደርሰውታል።

    በሌላ በኩል፤ ‹‹በድባጤ ወረዳ፣ ቆርቃ ቀበሌ፣ ዳሌቲ በተባለች መንደር ትላንት ጥር 4 ቀን 2013 ዓ.ም ከሌሊቱ 11፡30 ጀምሮ የኦነግ ሸኔ እና የቤኒን ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት ሰዎች መገደላቸውን፣ እስከአሁን ድረስ እኔ ራሴ ባለሁበት የ82 ሰዎች አስከሬን በፍለጋ መገኘቱን እና የቀብር ቦታዎች እየተዘጋጁ መሆኑን አይቻለሁ›› ሲሉ አንድ የዓይን እማኝ ለኢሰመጉ ተናግረዋል።

    ኢሰመጉ በትላንትናው (ጥር 4 ቀን) ጥቃት ሰለባ የሆኑ ሰዎች ቁጥር ከ100 ሊበለጥ እንደሚችል፣ በአብዛኛው ሴቶችና ህጻናት መሆናቸውን እና ከ24 በላይ የሚሆኑ ሰዎች ቆስለው በጋሊሳ ጤና ጣቢያ እና ቡለን ሆስፒታል ውስጥ ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑን ከአካባቢው ካሰባሰባቸው መረጃዎች ለማወቅ ችሏል።

    በመሆኑም፥ መንግሥት ድርጊቱን የሚፈጽሙ አካላትን በአግባቡ አጣርቶ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወስድ፤ ለዚህ ተደጋጋሚ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ፈጣን፣ ተጨባጭ እና ዘላቂ መፍትሔ ማፈላለጉ ላይ በብርቱ እንዲሠራ ኢሰመጉ ያሳስባል። ኢሰመጉ ይህ ጉዳይ እልባት እንዲያገኝ ሁሉም ግለሰቦች፣ የማኅበረሰብ አንቂዎች፣ መገናኛ ብዙኃን፣ የሲቪል ማኅበራት፣ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ የሀይማኖት ተቋማት እና የሀገር ሽማግሌዎች በመንግሥት ላይ ውትወታ እንዲያደርጉ ጥሪውን ያቀርባል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ)
    ጥር 5 ቀን፥ 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    መቆሚያ ያጣው በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል ዞን) ያሉ ሰዎች እልቂት

    Anonymous
    Inactive

    የብሔር ልዩነታችን ላይ መሠረት ባደረገ ፖለቲካዊ የአስተዳደር ሥርዓት የዜጎችን መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቶች ማረጋገጥ አይቻልም
    ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ
    ጋዜጣዊ መግለጫ

    በሀገራችን ኢትዮጵያ በንጹሃን ዜጎች ላይ እየደረሰ ያለ አሰቃቂ ግድያ፣ የአካል መጉደል፣ ለዘመናት ከኖሩበት ስፍራ መፈናቀል፣ እንዲሁም ያፈሩትን ሀብትና ጥሪት በአንድ ጀንበር አጥተው ለተረጅነት መዳረግ በየጊዜው የሚያጋጥም የተለመደ አሳዛኝ ክስተት ሆኗል።

    ይህንን በዜጎች እየደረሰ ያለውን አሰቃቂ ግድያ፣ የአካል መጉደል፣ መፈናቀልና  ሀብትና ንብረታቸውን ማጣት እንዲቆም ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄን ጨምሮ የተለያዩ ተቋማትና ግለሰቦች ደግመው ደጋግመው ቢያወግዙም በተቃራኒው ችግሩ ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሰ ይገኛል።

    እኛ ኢትዮጵያውያን እምነት፤ ባህል፣ ሥነ ልቦና፣ ጋብቻ፣ ሥራ፣ ጉርብትና ሌሎችም መስተጋብሮች ላንለያይ አስተሳስረውን ጠንካራ የአብሮነት ባህል የነበረን ሕዝቦች ነን። ይህ የአብሮነት መስተጋብር በብዙ አጋጣሚዎች ፈተና ላይ የወደቀ ቢሆንም እስከዛሬዋ ቀን ድረስ አብረን እንድንጓዝ አድርጎናል።

    መሠረታዊ የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶች ሳይሸራረፉ በማክበር የሁላችንም መኖሪያ የሆነችውን ሀገር አንድነት በማስጠበቅ፣ በመንግሥት አስተዳደር ሥርዓት ውስጥ ብዝኃነታችንን የሚያስተናግዱ የተለያዩ ፖሊሲዎችንና የሕግ ማእቀፎችን በማዘጋጀት ለጋራ ጥቅም በማዋል፣ እስከዛሬ የነበሩንን ጠንካራ ልምዶች ይበልጥ በማጠናከር ከድክመቶቻችን እና ስህተቶቻችን በመማር ብሎም በማሻሻል በአብሮነት ሁሉም አሸናፊና ተጠቃሚ የሚሆንበት ሥርዓት መዘርጋት ይቻላል ብለን እናምናለን።

    በእኛም ሀገር ይሁን በሌሎች ሀገራት ላይ ለሚከሰቱ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የተለያዩ ምክንያቶች ቢኖሩም በአሁኑ ጊዜ የቆየ አብሮ የመኖር እሴቶቻችንን በመፈታተን በሀገራችን እየተከሰቱ ለምንመለከታቸው ከፍተኛ የንጹሃን ህይወት መቀጠፍ፣ መፈናቀልና የንብረት ውድመት የመብት ጥሰቶች ዋነኛው መንስዔ የሀሰት ትርክት (false narrative) የወለደው ብሔር ተኮር የጥላቻ ፖለቲካ መሆኑ ጥርጥር የሌለው አሳዛኝ ሐቅ ነው።

    አሁንም መንግሥትም ሆነ ሌሎች የሚመለከታቸው የፖለቲካ ባለድርሻ አካላት በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት፣ ሀገራዊ ፍቅርና ቁርጠኝነት የዓለም አቀፍ ሕግጋትን መሠረት ባደረገ መልኩ፥ ያለንበትን 21ኛውን ክ/ዘመን በሚመጥን፣ በሰከነ ስሜት በቅንነት በመነጋገር፥ መሬት ላይ ያለውን ብዙኃኑን ምስኪን የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚመስል የፖለቲካ አስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት እስካልወሰኑ ድረስ በሁሉም የሀገራችን ወሰን ውስጥ ያሉ ዜጎቻችንን መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች በዘላቂነት ማስከበር ከቶውንም አይቻልም።

    ሰብዓዊ መብቶች ባልተከበሩበት፣ የሕግ የበላይነት ባልተረጋገጠበት፣ ሰላም ባልሰፈነበት ሁኔታ የሀገርን እድገትና ለውጥ እውን ለማድረግ ማሰብ እጅግ አዳጋች ነው።

    በአሁኑ ጊዜ እየተስተዋለ ያለው የጥላቻ፣ የመናናቅ፣ ልዩነትን መሠረት ያደረገ የብሔር ፖለቲካ፣ የጨቋኝ ተጨቋኝና የመጤ ሰፋሪ ትርክት ምንአልባትም ከእስካሁኑም ወደከፋ የግጭት አረንቋ ቢከተን ነው እንጂ የዜጎችን ሰው በመሆናቸው ብቻ እና በዜግነታቸው ማግኘት ያለባቸውን መብቶች ማስከበር ፈጽሞ አይቻልም። ችግሩን በፈጠርንበት አስተሳሰብ፣ ችግሩን በፈጠሩት የፓለቲካና የታሪክ ስሁት ትርክቶችን ሳናስተካከል መፍትሔ ማምጣትም ከባድ ነው።

    በሀገራችን በየትኛውም ዘመን እንደሕዝብ ተለይቶ የደላው ወይ ሌላውን የጨቆነ የለም። ይህንንም የተለያዩ የመንግሥት እና የፖለቲካ ድርጅቶች አመራሮች በተደጋጋሚ አስረግጠው የተናገሩት እውነታ ቢሆንም በተቃራኒው በተዛባ የታሪክ አረዳድ ሆን ብለውም ይሁን በስህተት የፖለቲካ አጀንዳ ባደረጉ አካላት ምክንያት የተነሳ ምንም የማያውቁ ንጹሀን ወገኖቻችን ደም እንደጎርፍ እየፈሰሰ ንብረታቸው እየወደመ ይገኛል። ይህም የሀገር ህልውናን አደጋ ላይ በመጣል ወደ ከፍተኛ ግጭት፣ ሞት፣ መፈናቀልና ስደት፣ ብሎም ለውጭ ኃይሎች ወረራና ጥቃት ሊያጋልጠን ይችላል።

    ከአባይ ግድብ ጋር በተገናኘም ሆነ በቀጠናችን ካለ የሽብርተኝነት እንቅስቃሴ ይህ የማይሆንበት ሁኔታ ይኖራል ብለን አንገምትም። ስለሆነም በቅርቡ በእርስ በርስ ግጭት ሕዝባቸውን ለስደትና ሞት ከዳረጉ ሀገራት በመማር ከምን ጊዜውም በላይ ሀገራዊ እና ሕዝባዊ አንድነታችንን ማጠናከር የሚገባን ጊዜ ላይ እንገኛለን።

    መንግሥት ሕግና ሥርዓት እያለ እንኳ በተገቢው መልኩ ማስቀረት ያልቻለውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት በጦርነትና በስደት መካከል ደግሞ ምን ያህል የከፋ ሊሆን እንደሚችልና ለውርደት እንደሚዳርገን ማስተዋል ያስፈልጋል።

    ይህ ፖለቲካው የወለደው የዜጎች ማንነትን መሠረት ያደረገ ጥቃት አይነቱን እየቀያየረ አንድ ጊዜ ሀይማኖትን ሌላም ጊዜ ብሔርን ወይንም አመለካከትንና አቋምን ሰበብ በማድረግ ይብዛም ይነስም ያልደረሰበትና ያልነካው የሕብረተሰብ ክፍል የለም ማለት ይቻላል። የችግሩ ምንጭም የቅርብ ሳይሆን አስርት አመታትን የቆየና አሁን እየባሰ የመጣ ነው።

    በሀገራችን ይህ ሁሉ ቢሆንም እንደ ሕዝብ የሚገድልና እንደሕዝብ የሚያፈናቅል አላየንም። ለዚህም ጥቃት በሚደርስባቸው አካባቢዎች ያሉ ነዋሪዎች ተጠቂዎችን ለማዳን፤ ለማሸሽ እና ለመደበቅ ያደረጉት ወገናዊና ሞራላዊ መልካም ሥራ ማስረጃ ነው።

    የፖለቲካው በቅንነት በመተማመን እና በአንድ ሀገራዊ ስሜት አለመመራት ሁሉንም የሀገሪቱ ዜጎች በየትኛውም ስፍራ በእኩል ዓይን በማየት ለሰብዓዊ እና የዜግነት መብቶቻቸውን በሚያከብር እና በሚያስከብር መልኩ ባለመመራቱ የተነሳ ችግሩን ከማቅለል ይልቅ በማወሳሰብ፡-

    • እጅግ ብዙ ንፁሐን ወገኖቻችን ሕፃናትን፡ ነፍሰጡሮችን፡ አቅመ ደካሞችን ጨምሮ ያለአግባብ በአሰቃቂ ሁኔታ ሕይወታቸው እንዲያልፍ ሆኗል፤
    • የሀገሪቱን የቀድሞ ኤታ ማዦር ሹም ጨምሮ የክልል ከፍተኛ አመራሮችን አጥተናል፤
    • ኢማሞችን እና ቀሳውስትን ጨምሮ የቤተ እምነት አገልጋዮችን ውድ ሕይወት አጥተናል፤
    • በዩንቨርሲቲዎቻችን ለትምህርት የሄዱ ብዙ ወጣቶችን ትርጉም በሌለው ምክንያት ተቀጥፈውብናል፤
    • ለትምህር የሄዱ ሴት ተማሪዎችና የጤና ረዳት ሰራተኞች ታግተው ለስቃይ ተዳርገዋል፤
    • በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች መሠረታዊ አቅርቦቶች ለምሳሌ እንደ ትራንስፖርት፤ መንገድ መዘጋት፤ ምግብ፤ ባንክ፤ ቴሌኮሚኒኬሽን አገልግሎት፣ መድሀኒት ወዘተ አቅርቦት በተደጋጋሚ ረዘም ላሉ ጊዜያት በመቆራረጥ ሰላማዊ ዜጎች ለከፍተኛ ችግር እንዲዳረጉ ሆኗል፤
    • ግምቱ ከፍተኛ የሆነ የሀገር እና የሕዝብ ንብረትና ሀብት እንዲወድም ሆኗል፤
    • ከዚህ ሁሉ በላይ በሰሜን እዝ የመከላከያ ሰራዊት ላይ የደረሰው ጥቃት ችግራችን የደረሰበትን የአሳሳቢነት ደረጃ ፍንትው አድርጎ የሚያሰይ ነው። ለዚህ ጥቃት ዋንኛ መንስኤ ከሀገርና ከሰው ይልቅ ብሔርን ያስቀደመ የማንነት ፖለቲካ ውጤት ሁኖ እናገኘዋለን።

    ይህ አሳዛኝ ሁኔታ ዳግም እንደማይፈጠርስ ምን ማስተማመኛ አለን? ከብሔር፤ ከሀይማኖትና ከፖለቲካ ነጻ የሆነውን የመከላከያ ሠራዊት ከውስጡ የወጡ የራሱ ወገኖች ያጠቁት የብሔር ፖለቲካው ውጤት ነው።

    ይህም በቶሎ በታላቅ መስዋዕትነት በቁጥጥር ባይውል ኖሮ የሀገራችንን ሉዓላዊነትን የሚገዳደርና ከዚህ የከፋ ቀውስ የሚያስከትል እንደነበረ መረዳት አያዳግትም።

    ችግሩ ላይ ብቻ ሳይሆን የችግሩ መንስዔ ላይ አተኩረን ለመሥራት እና ለማስተካከል ከዚህ በላይ ምን ምክንያትና ምቹ ጊዜ እየጠበቅን ነው? ምንስ እስኪፈጠር ነው ለውሳኔ የምንዘገየው?

    በየቀኑ ክቡር የሰው ነፍስ በአሰቃቂ ሁኔታ እየተቀጠፈ እያለ የሞተው ወይም ገዳይ ከኛ ነው ከነሱ ነው እያሉ የፖለቲካ ቁማር ከመጫወት ሁላችንንም እንደሀገር ከሰውነት ከፍታ ያወረደንን የጥላቻ ፖለቲካ በመመካከርና በማሻሻል የተሻለ ሥርዓትን ለትውልድ እናቆይ።

    ለፌደራልና ለክልል መንግሥታት አመራሮች፦

    ልዩነታችን ላይ መሠረት ባደረገ የፖለቲካ አስተዳደር ሥርዓት የዜጎችን መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች ማረጋገጥ አይቻልም።

    የፖለቲካ ባለድርሻ አካላት በከፍተኛ ታሪካዊ ሀገራዊ ስሜት በመሞላት በቁርጠኝነት የዓለም አቀፍ ሕግጋትን መሠረት ባደረገ፤ ያለንበትን 21ኛውን ክ/ዘመን በሚመጥን በሰከነ ስሜትና በቅንነት በመነጋገር፤ መሬት ላይ ያለውን በደምና በእምነት ተሳስሮ በሀዘንም በደስታ አብሮ የሚኖረውን ብዙኃኑን ምስኪን የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚመስል የፖለቲካ አስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት እስካልወሰናችሁ ድረስ በሁሉም የሀገራችን ወሰን ውስጥ ያሉ ዜጎቻችንን መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች በዘላቂነት ማስከበር ከቶውንም አትችሉም።

    ሰብዓዊ መብቶች፤ ሰላምና ሕግ ባልተከበረበት ሁኔታ ደግሞ እድገትንና ለውጥን ማሰብ እጅግ አዳጋች ነው። ይህ አካሔድ ደግሞ ለናንተም አይጠቅምም። ከእስካሁኑ ተግዳሮት በጊዜ ትምህር መውሰድ መልካም ነው።

    ችግሩን ለመፍታት እንደሚታሰበውም ቀላል እንዳልሆነ ብንረዳም እንደሚፈራውም ከባድ እንዳልሆነ እናምናለን።

    ከባድ ቢሆንም ደግሞ የእውነትን የአንድነትን የእኩልነትን ሰብዓዊ መብቶች የሚከበሩበትን፤ ለትውልድ ጥላቻን ሳይሆን ፍቅርን የምናወርስበትን መንገድን መርጠን የሚጠይቀውን መስዋዕትነት መክፈል የተሻለ ነው። ተቋማትም እስኪገነቡም ቢሆን የሰው ልጆች ወጥተው መግባት ዜጎች በህይወት የመኖር መብት አላቸው።

    መንግሥት የዜጎቹን ደህንነት ከማረጋገጥ የቀደመ ምን አይነት አጀንዳ ሊኖረው ፈጽሞ አይገባም።

    በመሆኑም፦

    1. መንግሥት ችግሩን ከምንጩ ለአንዴና ለመጨረሻ ለማድረቅ ቁርጠኛ ውሳኔ በመወሰን ጊዜ ባለመስጠት ውይይትና ምክክር ከላይ እስከታች እንዲጀመር እስከዚያውም በከፍተኛ ርብርብ ሕግ የማስከበር ሥራውን እንዲያስፈፅም እንጠይቃለን፤
    2. እስከዛሬም ድረስ በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች የተፈጠሩትን ዘግናኝ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ገለልተኛ ወገን እንዲያጣራ በማድረግ አጥፊዎችና ተባባሪዎች እንደ ተሳትፎዋቸው መጠን ከፍተኛውን ቅጣት እንዲያገኙ ተጎጂዎችም ተመጣጣኝ ካሳ እንዲያገኙ እንዲደረግ እንጠይቃለን፤
    3. እስከዛሬም ድረስ በተፈጠሩ ችግሮች ምክንያት ከሚኖሩበት አካባቢ የተፈናቀሉ ዜጎች ተገቢው ድጋፍ ተደርጎላቸው ወደነበሩበት እንዲመለሱና መደበኛ ኑሯቸውን እንዲጀምሩ በመንግሥት ያለተገደበ ድጋፍ እንዲደረግላቸው እንጠይቃለን።

    ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፦

    እስከዛሬ ድረስ በፖለቲካው ምክንያት በተፈጠሩ ችግሮች ብዙ ዋጋ እየከፈለ እና መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቱን እየተገፈፈ ያለው ንጹህ የሆነው እና አብሮ በሰላም እየኖረ ያለው በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች የሚኖረው ሕዝባችን እንደሆነ ይታወቃል። ያለንን አብሮነት አሁንም በማጠናከር እንደሕዝብም እንደግለሰብም አብረን በመቆም ለልጆቻችን የተሻለች ሀገር እናቆይ።

    ከጥላቻና ከብሔር ወይም ከማናቸውም የማንነት ልዩነት በመውጣት ለፖለቲካ ቁማር የማንመች እንሁን። ካለበለዚያ ከእስካሁኑ በባሰ የመጨረሻ ተጎጂዎች እኛው ነን።

    ምንም እንኳን የተለያየ አመለካከት ቢኖረንም በሰው ልጆች ሰብዓዊ መብቶች እና በሀገር አንድነት ጉዳይ የማንደራደር እንሁን። ሁላችንንም ስደተኞች ረሀብተኞችና ጠፊዎች ያደርገናል እንጂ ሀገር ለአንድ ብሔር፤ ለአንድ ክልል፤ለአንድ ቡድን ወይ ለአንድ ፓርቲ ብቻ ተለይታ አትፈርስም። ለተወሰነ ባለስልጣን ወይ አክቲቪስት ፈርሳ ለሌሎቻችን አትቆምም።

    ከሰሜን እስከደቡብ ከምሥራቅ እስከምእራብ አብረን ስንቆም ችግሮቻችን ከኛ በታች ይሆናሉ። ጥላቻና መጋደል በሕግም ፊት ወንጀል በሞራልም ነውር በእምነቶቻችንም ኃጥያት ነውና በሰከነ መንፈስ ሰብዓዊነትን በማስቀደም ሀገራችንን በማስከበር በብዝኃነት መኖር እንደለመድነው ቃልኪዳናችንን እናድስ።

    ውስጣዊ አንድነታችን በተዳከመ ቁጥር የውጭ ጠላቶቻችን ይደፍሩናል ያጠቁናል የዚያን ጊዜ ብሔር መርጠው አይወጉንም፤ ሁላችንንም ጨለማ ይወርሰናል። ምርጫው በእጃችን ነውና ሳይዘገይብን በይቅርታ መንፈስ እንነሳ።

    ሰው መሆናችን ትልቁ አንድነታችን መሆኑን እናስተውል።የነበሩንን እና ያሉንን መልካም አብሮ የመኖር እሴቶች በማጠናከር ችግሮቻችንን በእርጋታ እየፈታን እንጓዝ። የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች በማንም ይፈጠሩ፤ ማንም ተጎጂ ይሁን ሰው ነውና ወገን ነውና በአንድነት በማውገዝ በአንድነት ፍትህን በመጠየቅ ለሚለያዩን የማንመች እንሁን። ለልጆቻችን ፍቅርን ተስፋን መከባበርንና የሥራ ባህልንና ማውረስ አለብን።

    እናቶች፣ አባቶች፣ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ የሀይማኖት አባቶች፣ ምሁራን፣ የጥበብ ሰዎች፣ የሚድያ አካላት በአጠቃላይ ሁላችሁ ኢትዮጵያውያን በሀገር ውስጥም ይሁን በውጭ ያላችሁ በሙሉ ይህን ከባድ ጊዜ ተያይዘን እንድናልፈው የበኩላችንን አስተዋጽዖ እንድናደርግና የዜጎች ሰብዓዊ መብቶች ሳይሸራረፉ የሚከበሩበት፡ በሕግና በሥርዓት ብቻ ፍትህ የሚጠየቅበትና የሚገኝበት ማንኛውም አካል ከዜጎችና ከሀገር ደህንነት በታች የሚሆንበት መዋቅራዊ የሥርዓት መሻሻል እንዲመጣ በሰላማዊ መንገድ አብረን ጥሪያችንን እንድናሰማ ስንል በታላቅ አክብሮት እንማፀናችኋለን።

    ቅድሚያ ለሰብዓዊነት!
    ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ
    ታህሳስ 22 / 2013
    ​አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    የዜጎችን መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቶች ማረጋገጥ

    Anonymous
    Inactive

    በመተከል፣ በወለጋ፣ በሰገን አካባቢ እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት አጥብቀን እናወግዛለን!
    ከባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ እና የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ጥምረት (ባልደራስ-መኢአድ)  የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    በዓለም ላይ ማንነትን መሠረት አድርጎ የሚፈፀም ግፍ እየጠፋ ነው። ይሁን እንጂ በሀገራችን ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ዜጎች በማንነታቸው ምክንያት እየተገደሉ ነው፤ ግልፅ የሆነ የዘር ፍጅት ወንጀል እየተፈፀመ ነው። በታህሳስ 13 ቀን 2013 ዓ.ም ከ207 በላይ የአማራ ተወላጆች በመተከል አካባቢ ተገድለዋል። ባልደራስ-መኢአድ የተሰማውን መሪር ሐዘን ይገልፃል። ከዚህ በፊት በቤንሻንጉል ጉምዝ አካባቢ በተደጋጋሚ አንድን ዘር መሠረት ያደረገ ተመሳሳይ ግድያ መፈፀሙን ዓለም ያውቃል። የአማራ ተወላጆች በወለጋ፣ በጉራፈርዳ፣ በቤንሻንጉልና በሌሎች አካባቢዎች በማንነታቸው ብቻ ለዘር ፍጅት እየተዳረጉ ነው።

    በሀገራችን ኢትዮጵያ ሌላው የዘር ፍጅት የሚካሄድበት አካባቢ ደግሞ በሰገን ሕዝብ አካባቢ ነው። በደቡብ ኢትዮጵያ የጉማይዴ ነዋሪዎችና የኩስሜ ብሔረሰብ አባላት አካባቢ ወገኖቻችንን እያለቁ ነው። የኩስሜ ብሔረሰብ በቁጥሩ አነስተኛ ሲሆን 40‚000 ሺህ የሚሆኑ ዜጎች ያሉት ነው። የኩስሜ ዜጎች በአነሷቸው የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች፣ የንፁህ ውሃ አገልግሎት ጥያቄዎች ለእልቂት ተዳርገዋል።የኩስሜ ብሔረሰብ አስተዳደር ካሉት 9 አስተዳደር ቀጣናዎች መካከል በ7ቱ ቀጣናዎች ከፍተኛ የሰብዓዊና ቁሳዊ ውድመት የደረሰ ሲሆን በተለይ ቀጣና 1 ሙሉ በሙሉ ወድሞ የኩስሜ ብሔር አባላት ተሰደዋል። በተመሳሳይ በአሁን ሰዓት በምስራቅ ወለጋ ጌዳ ወረዳ፣ በምዕራብ ወለጋ ሳምቦ ወረዳ፣ በሆሮ-ጉድሩ ዞን እየተፈፀመ ያለው ታሪክ ይቅር የማይለው የግፍ ጭፍጨፋ ሊቆም አልቻም። ይህ ሁሉ ሲሆንና ማንነትን መሠረት ያደረገ ጥቃት ሲፈፀም ፌደራል መንግሥትም ሆነ የክልሉ መንግሥት ትኩረት አልሰጡትም። ዛሬ በኩስሜ ብሔር አካባቢ የትምህርት ተቋማት፣ ጤና ጥበቃ ተቋማት፣ ግብርና ወዘተ የመሳሰሉት ተቋማት ፈርሰዋል፤ ሕዝቡ በስደትና በስጋት ቁም ስቅሉን እያየ ነው። በዚሁ በሰገን ሕዝቦች አካባቢ የጉማይዴ ሕዝብ የማያባራ የዘር ፍጅት ወንጀል እየተፈፀመበት ነው። ዛሬ ጉማይዴ ውስጥ በሰላም ውሎ በሰላም መግባት የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። በ100 ሺህ የሚቆጠሩ የጉማይዴ ነዋሪዎች ተሰደዋል። ይህ ሕዝብ በማንነቱ ጥቃት ሲደርስበት የሚከላከልለት ከማጣቱም በላይ በተሰደደባቸው አካባቢዎች የዕለት ደራሽ እርዳታ ማግኘትም አልቻለም። መንግሥት ለዚህ ሕዝብ ሰላምና ፀጥታ መከታ መሆን አለመቻሉም ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን የጎዳው በጥቃቱ የመንግሥት ባለሥልጣናት ቀጥተኛ እጅ መኖሩ ነው። ይህ ሕዝብ የሚደርስበት ግፍ የማያባራው ጥቃቱ በመንግሥት የተደራጀ ኃይል እየተፈፀመ በመሆኑ ነው።

    በሀገራችን ውስጥ እየተፈፀመ ያለውን ማንነት ተኮር የሆነ የዘር ፍጅት ሕዝባችን ለእልቂት ከመዳረጉም በላይ በየጊዜው የሚያልቁ ወገኖቻችን አስከሬናቸው እንኳን በወጉ አያርፍም። በታህሳስ 13 ቀን 2013 ዓ.ም በመተከል የተጨፈጨፉት ከ207 በላይ ወገኖቻችንን መንግሥት በግሪደር አንድ ጉድጓድ ውስጥ እንዲቀበሩ አድርጓል። በዓለም አቀፍ የዘር ፍጅት ጥናት ውስጥ የዘር ፍጅት አንዱ መገለጫ በጅምላ መግደልና በጅምላ መቅበር ነው። በጅምላ መቅበር አንዱ የዘር ፍጅት የመደምደሚያው ወንጀል ነው። መንግሥት ይህንን ወንጀል በገሀድ ፈፅሞታል። ይህ ጉዳይ የሀገራችንን ባህል፣ ሀይማኖትና የቀብር ሥርዓት የጣሰ እና ያላገጠ ሲሆን ሥነ-ልቦናቸውንም ጎድቷል። በመሆኑም መንግሥት ሊጠየቅበት ይገባል። በአጠቃላይ በሀገራችን ውስጥ የዘር ፍጅት ወንጀል በየጊዜው እየተፈመ ሲሆን ፌደራል መንግሥትም ሆነ የክልል መንግሥት ይህንን ወንጀል ለመመከት አልቻሉም፤ ተጠያቂም ናቸው። በዓለም አቀፍ የዘር ፍጅት ወንጀል ክስ ወቅት በየትም ሀገር የዘር ፍጅት ሲፈፀም ተጠያቂው ራሱ መንግሥት ነው።

    በመሆኑም ለኢትዮጵያ ሕዝብና ለዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ የሚከተሉትን አስቸኳይ ጥሪዎች እናቀርባለን፡-

    1ኛ. የዘር ፍጅት ምልክቶች የሚታዩባቸው አካባቢዎች በፍጥነት ሠራዊታችን በቂ ኃይል እንዲያሰፍር፤
    2ኛ. መላው የሀገራችን ሕዝብ የዘር ፍጅትን በሰላማዊ መንገድ ብቻ ነቅቶና ተግቶ እንዲቃወም፤
    3ኛ. ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች ይህንን ክፉ ወንጀል በመቃወም በአንድነት እንዲቆም፤
    4ኛ. በሀገር ውስጥና በውጪ ያላችሁ የኢትዮጵያ ምሁራን በኢትዮጵያ ውስጥ እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት ወንጀል ወደ ሕግ እንድታቀርቡ፤
    5ኛ. በኢትዮጵያ ውስጥ የምትገኙ የሀገር ውስጥና የውጪ ሀገር ሰብዓዊ መብት ተቋማት በሙሉ ይህንን ወንጀል እንድትቃወሙ እና ወንጀል የፈፀሙት ኃይሎች ወደ ሕግ እንዲቀርቡ እንድትታገሉ፤
    6ኛ. የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትና ወዳጅ ሀገራት በሙሉ የዘር ፍጅት ወንጀልን እንድታወግዙና በመንግሥት ላይ ተገቢውን የዲፕሎማሲ ተፅዕኖ በማሳደር ወንጀሉ እንዲቆም እና ወንጀለኞች ለፍትህ እንዲቀርቡ እንድታደርጉ፤
    7ኛ. መላው የሀገራችን ሕዝብ በዘር፣ በሀይማኖት፣ በብሔር ሳንከፋፈል ከመቼውም ጊዜ በላይ በአንድነት ፀንተን እንድንቆምና የዘር ፍጅት እንድንከላከልና የተባበረችውን ኢትዮጵያችንን በጋራ እንድንገነባ በትህትና እንጠይቃለን።

    የተባበረችውን ኢትዮጵያን እንገነባለን! “አንዲት ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር”!!

    ታኅሣሥ 20 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ
    ባልደራስ-መኢአድ

    ባልደራስ-መኢአድ

    Anonymous
    Inactive

    በመተከል በአማራ ሕዝብ ላይ የቀጠለውን የዘር ፍጅት አስመልክቶ ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ

    የአማራ ሕዝብ እና ሀገራችን ከገጠሟቸው ፈተናዎች ለመውጣት ዘላቂው መፍትሄ ሁሉንም ሕዝብ እና አካላት ባለቤት የሚያደርግ፣ ሀገራዊ መከራንም በጋራ መቀልበስ የሚያስችል ሥርዓትና ስሪት ማቆም መሆኑን ሳናሰልስ ተናግረናል፤ አስገንዝበናል፤ ወትውተናል።

    የፍትህና እኩልነት ሥርዓት ስለማቆም ሳያሰልሱ መወትወትና መታገሉ በመሠረታዊነት አንዳችም ስህተት የሌለበት ቢሆንም ሀገራዊ ፕሮጀክቱ አማራውን ከምድረ ገጽ ለማጥፋት ከሚሠሩ የጥላቻ ኃይሎች ጋር በመሆን ማሳካት እንደማይቻል ግለፅ እየሆነ የመጣ እውነታ ሆኗል።

    ሁሉን አቀፍ በጎ ውጥኖች በተግባር እስኪተረጎሙና የጥፋት ኃይሎችም ልቦና ገዝተው በባለቤትነት ስሜት ጭምር የየራሳቸውን አዎንታዊ አበርክቶ መወጣት ሊጀምሩ ይችላሉ ከሚለው እሳቤ በፊት የሕዝባችን ህልውና የሚቀድም መሆኑን በመረዳት አሳዳጅና ገዳዮቻችን ክላሽ፣ ሜንጫና ቀስታቸውን ጥለው እስኪመጡ ድረስ ለሽግግር የሚሆን የተቀናጀ እርምጃ እንዲወሰድ ዛሬም ለማሳሰብ እንወዳለን።

    የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የመላው አማራ ሕዝብ ወኪል መሆኑን ማረጋገጥ ያለበት ወቅት መሆኑን በመረዳት በትሕነግ ላይ የወሰደውን ዓይነት ህልውናን የማስከበር ታሪካዊ ቁርጥ ውሳኔ በማሳለፍ በመተከል እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት ለማስቆም ተግባራዊ ምላሽ ሊሰጥ ይገባል። በዚህ ረገድ አብን ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ለማድረግ ያለንን ቁርጠኝነትም መግለጽ እንወዳለን።

    የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል መንግሥት በዜጎቻችን ላይ ለሚፈፀመው ጭፍጨፋ ቀዳሚ ተጠያቂ ከመሆኑም በላይ በጭፍጨፋው የተሳተፉ ከክልል እስከ ቀበሌ የሚገኙ አመራሮችን በቸልታ በማለፍ የጥቃቱ ተባባሪ ሆኖ ይገኛል።

    የፌደራል መንግሥትም ኦሮሚያንና ቤንሻንጉል ጉሙዝን ጨምሮ በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች በአማራ ሕዝብ ላይ የሚፈፀመውን ሰፊ የዘር ማጥፋት ወንጀል ማስቆም ካለመቻሉም በላይ ወንጀሉን በስሙ ባለመጥራት በዜጎቻችን ላይ ለሚፈፀመው ጅምላ ፍጅት ተባባሪ በመሆኑ ከተጠያቂነት እያመልጥም።

    በአማራ ሕዝብ ላይ እየተፈፀመ ያለውን የማያባራ የዘር ፍጅት መላው ኢትዮጵያውያን እንድታወግዙና የአማራ ሕዝብ ህልውናውን ለማስቀጠል ከሚያደርገው ትግል ጎን እንድትቆሙም ንቅናቄያችን በአክብሮት ይጠይቃል። ንቅናቄያችን በመተከል በአማራ ወገኖቻችን ላይ የሚፈፀመውን የማያባራ የዘር ፍጅት በጽኑ እያወገዘ፤ ለዘር ፍጅት ሰለባ ቤተሰቦችና ለመላው የአማራ ሕዝብም መጽናናትን ይመኛል።

    አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፥ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ!

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)
    ታኅሣሥ 15 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ፣ ሸዋ፥ ኢትዮጵያ!

    በመተከል በአማራ ሕዝብ ላይ የቀጠለው የዘር ፍጅት

    Anonymous
    Inactive

    አሰቃቂ ጭፍጨፋ በመተከል ዞን ― የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) መግለጫ 

    ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፡ የሰዎች ደኅንነት ማረጋገጥ ቀዳሚው የመንግሥት ግዴታ ነው።

    ታኅሣሥ 13 ቀን 2013 ዓ.ም. በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፥ መተከል ዞን፥ ቡለን ወረዳ፥ በኩጂ ቀበሌ ከለሊቱ 10፡00 ሰዓት ላይ የታጠቁ ኃይሎች በእንቅልፍ ላይ በነበሩ ነዋሪዎች ላይ በለኮሱት እሳት እና በተኩስ ከ100 በላይ ሰዎች መገደላቸው በክልሉ ያለው የሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ በከፍተኛ ሁኔታ እየተዳከመ መሄዱን እንደሚያሳይ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ/ኮሚሽኑ) ገለጸ።

    ኢሰመኮ የጥቃቱን ሂደት በተመለከተ ታኅሣሥ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. ከሚመለከታቸው አካላት እና ከተጎጂዎች ጋር በመነጋገር ሲከታተልና ሲያጣራ ቆይቷል። በኩጂ ቀበሌ ከወረዳው መቀመጫ ከሆነችው ቡለን ከተማ 90 ኪ.ሜ. ርቃ የምትገኝ ሲሆን የሺናሻ፣ የኦሮሞና የአማራ ተወላጆች ይኖሩባታል። ለቀበሌው የተመደበ የፖሊስ ወይም የፀጥታ ኃይል አለመኖሩን ኮሚሽኑ በክትትሉ መሠረት ተረድቷል።

    ኮሚሽኑ ሁኔታውን እስካጣራበት ጊዜ ድረስ በቡለን ሆስፒታል 36 ተጎጂዎች እርዳታ እየተደረገላቸው ሲሆን፥ አብዛኞዎቹ በጥይት ሌሎቹ በቀስት የቆሰሉ መሆናቸውን ኢሰመኮ በምልከታ አረጋግጧል። በተጨማሪም ሰዎች ጥቃት የደረሰባቸውን ሁኔታ የሚያሳዩና የሚረብሹ የፎቶግራፍ ማስረጃዎች ለኮሚሽኑ ደርሰውታል። በሰው ሕይወት እና በአካል ላይ ከደረሰው ጉዳት በተጨማሪ የደረሱ ሰብሎችና የተሰበሰቡ ማሳዎች በእሳት ጋይተዋል። ቢያንስ 18 ያክል ነዶዎች ሲቃጠሉ ማየታቸውን አንድ ተጎጂ አስረድተዋል።

    በጨላንቆ እና ዶሼ ቀበሌዎች ቤቶች እየተቃጠሉ እንደሆነ ከአካባቢው ለኮሚሽኑ የተላኩ መረጃዎች ያመለክታሉ። በድባጤ ወረዳ ዶንበን ቀበሌ ስጋት የገባቸው ነዋሪዎች ከታኅሣሥ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ቀዬአቸውን ጥለው እየተሰደዱ እንደሆነም ኮሚሽኑ ተረድቷል።

    አካባቢውን በቅርበት እንዲጠብቅ የተመደበው ብሔራዊ የመከላከያ ሠራዊት ታኅሣሥ 13 ቀን 2013 ዓ.ም. ለማረጋጋት ተግባር ወደቦታው ተልከው የነበሩ አንድ የፌዴራል እና ሁለት የክልሉ አመራሮችን ለማጀብ በሚል አካባቢውን ለቅቆ መሄዱ ታውቋል። ጥቃቱ የጀመረው ይህንኑ ተከትሎ እንደሆነና ሌሊቱን የጀመረው ጥቃት እስከ ቀኑ አጋማሽ ድረስ መዝለቁንም ለማወቅ ተችሏል። ኮሚሽኑ ያነጋገራቸው ተጎጂዎች እንደሚሉት በጥቃቱ ከሞቱ ሰዎች መካከል አብዛኛው የሺናሻ ተወላጆች ናቸው።

    ከዚህ ቀደም በነበሩ ጥቃቶች ፈጻሚዎቹ ከ”ጫካ” የሚመጡ ሰዎች የነበሩ ቢሆንም፥ በዚህኛው ጥቃት “በስምና በመልክ የሚያውቋቸው” የበኩጂ ቀበሌ ነዋሪዎች ጭምር መሳተፋቸውን ከጥቃቱ የተረፉ ተጎጂዎች ገልጸዋል።

    ኢሰመኮ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ የሚከሰቱ ጥቃቶችን ተደጋጋሚነትና የክልሉን ሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ ሁኔታ አስመልክቶ የፌዴራሉንና የክልሉን መንግሥታት የተጠናከረ ትብብርና ከፍተኛ ትኩረት እንደሚሻ ሲያሳስብ መቆየቱ ይታወሳል፤ ይሁንና ጥቃቶቹ በመልክ እና በስፋት እየተባባሱ መጥተዋል።

    ስለሆነም፣ በጥቃቱ ጉዳት ለደረሰባቸው እና ለተፈናቀሉ ሰዎች የሕክምና እና ሰብዓዊ እርዳታ እንዲቀርብ፣ እንዲሁም ተገቢው ማጣራትና ጥቃቱን ባለመከላከልም ሆነ በሌላ መልኩ ጥቃቱን የፈጸሙና ያባባሱ ሰዎችን ሕግ ፊት የማቅረቡ ሂደት ከወዲሁ እንዲጀመር ኮሚሽኑ ያሳስባል። በአካባቢው የሚገኘውን የፀጥታ ኃይልና መዋቅር የሰዎችን ደኅንነት ሙሉ በሙሉ ለማረጋገጥ በሚያስችል መልኩ በከፍተኛ ደረጃ በአፋጣኝ እንዲጠናከር ኢሰመኮ ጥሪ ያቀርባል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)
    ታኅሣሥ 14 ቀን 2013 ዓ.ም.

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን

    Anonymous
    Inactive

    የአማራ ብልጽግና ፓርቲ ለሀቀኛ የፌዴራሊዝም ሥርዓት ካልታገለ እንደ ብልጽግና መቆም አይችልም!

    የአማራ ብልጽግና ፓርቲ ወቅታዊ አቋም
    ኅዳር 27 ቀን 2013 ዓ.ም.
    ባህር ዳር

    ስናጠፋ የሚገስጸን፣ ስናለማ የሚያግዘን ሕዝብ እንዳለን እናምናለን። በሕዝባችን ስብራት ላይ ተደማሪ ስብራት መሆን ስለማንፈልግ ከሀቀኛ የፌዴራሊዝም ሥርዓት በመነጨ ቅን ልቦናና ፍላጎት የሕዝባችንን ድምጽ ለማክበርና ለማስከበር ተዘጋጅተናል። የብልጽግና ፓርቲ ሲመሠረት የአብዮታዊ ዴሞክራሲን ማቅ እና ድሪት አውልቆ የሕዝብን ሀቀኛ ፍላጎትና እውነተኛ መሻት የሆነውን መካከለኛ አማራጭና የወሳኝ ኩነቶች ወሳኝነት ለሕዝብ ተጠቃሚነት የሚበጀውን የፕራግማቲዝም (pragmatism) ድርና ማግ ተጎናጽፎ ነው። በብልጽግና እምነት ቋሚና የማይለወጥ እውነት የለም፤ ሁሉም ነገር ቋሚ ሊሆን አይችልም። በብልጽግና እምነት የማይለወጥ መሠረታዊና ቁሳዊ የሆነ ነገርም አይኖርም። ከብልጽግና ርዕዮተዓለማዊ እምነት አኳያ ቋሚና የማይለወጥ ነገር አለ ከተባለ እሱም ኅብረብሔራዊ ፌዴራሊዝምና ኢትዮጵያዊነት ብቻ ነው።

    መደመርን መንገዳችን፣ ብልጽግናን መዳረሻችን አድርገን ስንነሳ መደመር የሚፈልጉ ዜጎቻችንን ልንቀንሳቸው አንችልም። ዛሬ በማይካድራ፣ በዳንሻ፣ በዓላማጣ፣ በጥሙጋና በዋጃ ባጠቃላይ በራያ ዋጃ ዓላማጣና ኮረም እንዲሁም በወልቃይት ጠገዴ ሴቲት ሁመራ በተደረገው ሕዝባዊ ሰልፍ ያሰማችሁትን የ‘አማራ ነን’ ድምጽ በአክብሮት የምንቀበለውና በጽናት የታገልንለት ወደፊትም የምንታገልለት የመደመር ኅብረብሔራዊ ፌዴራላዊ ትርጉም ያለው የቆየ ግን በእብሪት የተገፋና መልስ የተነፈገው የዜጎች ጥያቄ ነው።

    ሁሉም የብልጽግና ቤተሰቦችና በሀገር ውስጥም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ የኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባኛል የሚሉ ኃይሎች እንዲረዱት የምንፈልገው ቁምነገር አለ።

    በግፍ ተወረርን እንጂ ማንንም አልወረርንም።

    ክልላዊ ወሰናችንንና ፌዴራላዊ መብታችንን በመጋፋት በግፍ ተጠቃን እንጂ ማንንም አላጠቃንም።

    በጭካኔና ያለርህራሄ የዘር ማጥፋት ወንጀል ተፈጸመብን እንጂ በማንም ላይ የግፍ አጸፋ አልመለስንም። በደም ፍላት ስሜት ተገፍትረው ግፍ ለመፈጸም የቃጡና የሚቃጡ በውስጣችን ያሉ ስሁታንንም ያለርህራሄ ታግለናል፤ እየታገልንም እንገኛለን።

    ከልክ በላይ በተወጠረ እብሪት በትምክህተኝነት ስሜትና በተስፋፊነት ልክፍት ተወጥረው ሕዝባችንን፣ መሬታችንን፣ ታሪካችንን፣ መልካም ስማችንን፣ የ30 ዓመት ሁሉአቀፍ ክልላዊ እድገታችንን፣ እድሜያችንንና ሥነ-ልቦናችንን በግፍ ተዘረፍን እንጂ የማንንም ቅንጣት አልዘረፍንም።

    የወሰን፣ የማንነትና የፍትሀዊ ተጠቃሚነት ጥያቂያችንን በሕግና በሥርዓት አቀረብን እንጂ እንደ ትሕነግ በማን አለብኝነት ‘ዘራፍ’ አላልንም።

    የተገፋን፣ የተበደልንና የተጨፈጨፍን ቢሆንም ለፌዴራል መንግሥቱም ሆነ ለሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱ አደጋ አልፈጠርንም።

    የሀገር መከላከያ ሠራዊትንና የሀገር ሉአላዊነትን ጠብቆ ለማስጠበቅ እስከ አሁኗ ሰዓት ድረስ ቁርጠኛ አጋርነታችንን በክቡር መስዋዕትነት አረጋገጥን እንጂ ሀገራችንና ሕዝባችንን በመካድ አልወጋንም። ሀገርና ሕዝብ ክደው በወገን ላይ የጭካኔ አፈሙዝ ያዞሩትንም የታሪክ ማፈርያዎች እንደሆኑ እንረዳለን።

    በሰላማዊ መንገድ እጅ የሰጡና የተማረኩ የትሕነግ ተዋጊ ኃይሎችን በወንድማማች መንፈስ ቁስላቸውን ጠረግን፣ እንዲያገግሙ በፍቅር ተንከባከብን እንጂ እንደጠላት አልገፋናቸውም። በተለመደው አማራዊ የእንግዳ አቀባበል ሥርዓት እልፍኛችንን ለቀን፣ ከአልጋችን ወርደን የምርኮኛነት ስሜት እንዳይሰማቸው አስተናገድናቸው እንጂ በግፍ አላሸማቀቅናቸውም።

    እብሪተኛው የአፓርታይድ ቡድን በፈጸመብን ሴራ እስከአሁኗ ሰዓት ድረስ በተለያዩ የሀገሪቷ አካባቢዎች በስጋትና በጭንቀት የሚኖረው የአማራ ሕዝብ ነው። በ10ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎቻችን አሁንም በስደት ላይ ይገኛሉ። በቤንሻንጉል ክልል በመተከል ዞን የሚፈሰው የአማራ ደም ዛሬም አልቆመም። በሌሎችም አካባቢዎች የስጋት ጅረት አልተገደበም። በማይካድራና በሁመራ በየቦታው የተጣሉ አስከሬኖች ‘በክብር ቅበሩኝ’ ጥሪ ቢያስተጋቡም የንጹሃኑ በድኖች ግን ዛሬም ድረስ ተለቅመው አላለቁም።

    ይሁን እንጂ የአማራ ሕዝብ ጥንተ ጠላት የሆነው ትሕነግና ጽንፈኛ ወዳጆቻቸው ከትክክለኛው ወቅታዊ አውድ ፍጹም የሚቃረን ሙግትና ትንታኔ ሲሰጡ ልማዳቸው መሆኑን ብናውቅም ለአንድ አንድ የትግል አጋሮቻችንና ደጋፊዎቻችንን ግልጽ መልዕክት ማስተላለፍ እንፈልጋለን።

    1. ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. አረመኔውና የአፓርታይድ ሥርዓት አቀንቃኙ ትሕነግ በሰሜን ዕዝ ላይ የተጠናና የተደራጀ ሁሉ-አቀፍ ጥቃት ሲፈጽም የወራሪነት፣ የተስፋፊነትና የጨፍጫፊነት አድማሱን በማስፋት በ24 ሰዓት ውስጥ በምሥራቅና በምዕራብ የአማራ ክልል አቅጣጫዎች ጎንደርንና ወልድያን የመቆጣጠር ግብ አስቀምጦ ነው። ይህንን እኩይ ዓላማውን ለማሳካት ከ3 ዓመት ያላነሰ ወታደራዊ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቷል። ትሕነግ ያስቀመጠውን የወራሪነት ግብ በመቀልበስ ሀገርና ሕዝብን ለመታደግ በወትሮ ዝግጁነት መፈጸሙ የአማራን ሕዝብ ሊያስመሰግነው ሲገባ፥ በጥርጣሬ እንድንታይ የሚያደርግ በፍጹም አይሆንም። የተከፈተብንን የግፍ ጦርነት ተከላክለንም፣ አጥቅተንም ጦርነቱን መቀልበሳችንና በግፍ ተነጥቀን የነበረውን ተፈጥሯዊ መብታችንን በእጃችን ማስገባታችን (repossession right) የተፈጥሮን ሕግ የሚቃረን ሳይሆን በእብሪተኞች የማይታረቅ ተቃርኖ መቃብር ላይ የተረጋገጠ ድል ነው። ስለሆነም እርስት ለማስመለስ ያልታገለን ይልቁንም ላለፉት 30 ዓመታት ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ጥያቄ ሲያቀርብ የቆየን ሕዝብና መንግሥት እርስት ለማስመለስ እንደተዋጋ አድርጎ ኢ-ሕገ መንግሥታዊና አመክንዮ የጎደለው ድምጽ ማሰማት ነውር ነው እንላለን። በእርግጥ እርስት ማስመለስ የሚለው ትችት ለባለእርስቶች የተወረወረ የበላ-ልበልሀ ክርክር መሆኑ የአማራ ሕዝብን ጥያቄ ፍትሀዊነት ያረጋገጠ ሀቅ በመሆኑ ሀሳቡን ደጋግማችሁ ለተጠቀማችሁ ሁሉ ምስጋና እናቀርብላችኋለን።
    2. እንደ ብልጽግና ፓርቲ የአማራ ሕዝብ ሀቅ ይታወቃል። የአማራ ሕዝብ ሀቅ ዛሬም በአደባባይ በሕዝባዊ ሰልፍ በይፋ እንደሚታየው የማንነት፣ የወሰን፣ በህይወት የመኖርና የአካል ደህንነት ፍትሀዊ ጥያቄ ነበር። ከ500ሺ ሕዝብ በላይ የተፈናቀለባቸው፣ በ10ሺዎች የሚቆጠር ሕዝብ የተገደለባቸው፣ በ10ሺዎች የሚቆጠር ሕዝብ የተሰወረባቸው እነዚህ አካባቢዎች ዛሬም የተረጋገጠ የጅምላ መቃብር የተገኘባቸውና የአፓርታይድ ሥርዓት በተጨባጭ የተፈጸመባቸው የትሕነግ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ጭካኔ ማረጋገጫ የግፉአን መቀበርያ አጽመ እርስቶች ናቸው።

    በግፍ የተጨፈጨፉ የንጹሀን ወገኖቻችን አስከሬኖች ተለቅመው በክብር ባላረፉበት በዚህ ወቅት የባለቤትነት ጥያቄ ማንሳት የወንበዴውን ቡድን ወንጀል ለመደበቅና ለማድበስበስ እየተፈጸመ የሚገኝ ሌላኛው የትሕነግ ሸፍጥ ማምለጫ መንገድ ሲሆን፥ የአካባቢውን ነባራዊ ሀቅ በመረዳትም ሆነ ባለመረዳት የሚራመዱ የተሳሳቱ ሀሳቦች የሞራል ጥያቄ የሚነሳባቸው ናቸው።

    ስለሆነም የሕግ የበላይነት ለማስከበር፣ የሀገር ሉአላዊነት ለማጽናት በተደረገ ሁሉ አቀፍ የትግል ጀብዱ በታሪክ አጋጣሚ ወደባለእርስቱ የገቡ አካባቢዎች (repossessed lands) ላይ የሚነሳውን ማንኛውንም ጥያቄ በሥርዓቱና በአግባቡ በቀጣይ ማየት ይቻላል የሚል እምነት አለን። ግን ደግሞ የትሕነግን የአፓርታይድነት የወንጀል ፈለግ (criminal scene) መፈተሽና መመርመር፣ ለትግራይና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማጋለጥ ከመቸውም ጊዜ በላይ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል የሚል እምነት አለን። ስለሆነም:-

      • ላለፉት 50 ዓመታት የዜጎች ማጎርያና ማሰቃያ የሆኑ ከመሬት በታች የተሰሩ ዋሻዎች (underground torching caves) ለሕዝብ ይፋ መደረግ አለባቸው።
      • ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የጅምላ መቃብሮች ታስሰው ላለፉት 50 ዓመታት እንደ ሕዝብ የተፈጸመብንን ግፍና ጭካኔ ዓለም እንዲያውቀው ማድረግ ታሪካዊ ኃላፊነት እንደሆነ እናምናለን።
    1. በአጠቃላይ የብልጽግና ፓርቲ ተልዕኮ ግፈኛና ግፍን ነቅሎ በአዲስና በተረኛ ግፈኛና ግፈኝነትን ማጽናት አይደለም። ወትሮም ቢሆን የኢትዮጵያ ችግር ከግፈኞች አልነበረም። እንደሀገር ግፈኞችን መቅበር የተለመደ እንጂ አዲስ ነገር አይደለም። በየታሪክ ምዕራፉ ግፈኞችን መቅበር የምትችል ሀገር ግፍን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስወገድ ግን አልቻለችም። ስለሆነም የብልጽግና ፓርቲ ግፈኝነትን በጽናት በሚታገልበት በዚህ ታሪካዊ መድረክ የየበኩላችንን ድርሻ እንድንወጣ እየጠየቅን፥ በእኛ በኩል እብሪተኝነትም ሆነ ግፈኝነት የሕዝባችንን ክብር ዝቅ ስለሚያደርገው በጽናትና በታማኝነት የምንታገለው መሆኑን አበክረን እንገልጻለን።
    2. በሁሉም የክልላችን አካባቢዎች አስተማማኝ ሰላም ለማስፈን የሕግ የበላይነት የምናስከብር መሆኑን እያረጋገጥን፤ በቤንሻንጉል ክልል በሕዝባችን ላይ ተደጋጋሚ ግፍ የሚፈፅሙ የእብሪተኞች ቅሪት ዓላማና ፍላጎት በድል እንደሚቋጭ ሳንጠራጠር የተጀመረውን ሕግ የማስበር ሥራ አጠናክረን መቀጠል ይኖርብናል። ጎን ለጎንም የተፈናቃይ ወገኖቻችንን መሠረታዊና ወቅታዊ ፍላጎት እንዲሟላ ከማድረግ ባሻገር የሕዝባችንን እንቅፋት በሕግ አግባብ ተጠራርጎ መጥፋቱ ከተረጋገጠ በኋላ ዜጎቻችንን ተመልሰው በቀያቸው ላይ እንዲሰፍሩ የሚደረግ መሆኑን በድጋሚ እናረጋግጣለን።

    በመጨረሻም በትሕነግ መራሹ እብሪተኛ አፓርታይድ እርምጃ ዘግናኝ ግፍ የተፈጸመባችሁ ውድ የመከላከያ ሠራዊት አባላትና የማይካድራና የሁመራ ሰማዕታት ሁልጊዜም በሕዝባችን ልብ ውስጥ ዘላለማዊ ክብር አላችሁ።

    የሕግ የበላይነት ለማስከበር በተፈጸመው እልህ አስጨራሽ ግብ ግብ ክቡር መስዋዕትነት የፈጸማችሁ የሀገር መከላከያ ሠራዊት አባላት፣ የአማራ ልዩ ኃይልና ሚሊሻ፣ የአፋር ልዩ ኃይልና ሚሊሻ የአባቶቻችን ልጆች ስለሆናችሁ ኮርተንባችኋል፤ ለዘላለምም እንኮራባችኋለን።

    የኦነግ ሽኔንና የጉሙዝ አማጺ ቡድንን ለመደምሰስ በሁሉም የአገሪቷ አካባቢዎች ስምሪት ወስዳችሁ ታሪካዊ መስዋዕትነት በመክፈል ላይ የምትገኙ የፌዴራል የጸጥታ ኃይሎች፣ የኦሮምያና የቤንሻንጉል ክልል ሀቀኛ የልዩ ኃይልና የሚሊሻ አባላት ጀግንነታችሁን ስንዘክር በአማራ ሕዝብ አክብሮትና ትህትና ነው።

    ድል ከኢትዮጵያና ከአማራ ሕዝብ አብራክ ለተገኙ ታሪካዊ ጀግኖቻችን!!!
    ውርደት በእብሪትና በትዕቢት ተወጥረው ሀገራችንንና ሕዝባችንን ለሚወጉ ጠላቶቻችን!!!
    ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ፈጣሪ አብዝቶ ይጠብቅ!!!
    የአማራ ብልጽግና ፓርቲ

    የአማራ ብልጽግና ፓርቲ

    Anonymous
    Inactive

    ንጹሃን ዜጎችን በማንነታቸዉ በጅምላ ማጥቃት የሽብር እንጂ የፖለቲካ ትግል ሊሆን አይችልም
    ብልጽግና ፓርቲ

    ባለፉት ሁለት ዓመታት ተኩል በሀገራችን እዉነተኛ የዲሞክራሲ ሥርዓት ሽግግር ለማደረግ የፖለቲካ ምህዳሩን ማስፋትን ጨምሮ በርካታ ተግባራዊ እርምጃዎች ሲወሰዱ መቆየታቸዉ ይታወሳል።

    በዚህም በሀገራችን ሕዝቦች ዘንድ ትልቅ ተስፋና መነቃቃት መታየት የጀመረ ሲሆን ሀገራችን በሰላማዊ፣በሰለጠነና በሰከነ የፖለቲካ አስተሳሰብ በሚመራ ነጻ፣ፍትሃዊና ገለልተኛ ምርጫ ወደ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ልትሸጋገር እንደምትችን የተስፋ ብርሃን የታየበት የፖለቲካ ሪፎርም ሲካሄድ መቆየቱ አይዘነጋም።

    ይሁን እንጂ ሰላማዊና የሰለጠነ የፖለቲካ ስርዓት የማይዋጥላቸዉና ግድያን፣ ማፈናቀልን፣ ንብረት ማዉደምንና ንጹሃን ዜጎችን ማሸማቀቅን እንደ ዋነኛ የስልጣን ምንጭ አድርገዉ የሚንቀሳቀሱ የኢትዮጵያን መረጋጋትና የዜጎቿን ሰላም የማይፈልጉ ሃይሎች ቅንጅት በመፍጠር ምንም ዓይነት የፖለቲካ ወገንተኝነት የሌላቸዉን ንጹሃን ዜጎች በማንነታቸዉ ብቻ ኢላማ በማድረግ ጥቃት በማደረስ ላይ ይገኛሉ።

    በዚህ እኩይና ጭካኔ የተሞላበት አረመኔያዊ የጥፋት ተግባራቸዉ ባለፉት አመታት በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የዜጎች ህይወት እንዲጠፋ፣ አካል እንዲጎድል፣ ንብረት እንዲወድምና ዜጎች የሰላም ስሜት እንዳይሰማቸዉ ሲደረግ ቆይቷል።

    በተለይም ሰሞኑን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በመተከል ዞን እና በደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በቤንች ሸኮ ዞን በጉራ ፈርዳ ወረዳ የበርካታ ንጹሃንን ህይወት የቀጠፈ ጨካኝ የሽብር ተግባር ተፈጽሟል።

    የንጹንን ደም በማፍሰስ ስልጣን መያዝን ካልሆነም አገርን መበታተንን ዋነኛ ዓላማቸዉ አድርገዉ ከሚነቀሳቀሱ ቡድኖች መካከል አንዱ የሆነዉ ኦነግ ሸኔ የተባለዉ አሸባሪ ቡድን በሀይል ወደ ስልጣን ለመመለስ ከሚፈልጉ ካልተሳካላቸዉም ኢትዮጵያን ለመበታተን ሌት ተቀን ከሚሰሩ ተቀናጅተዉና በትጥቅ ተደግፈዉ በትናንትናዉ ዕለት ማታ [ጥቅምት 22 ቀን 2013 ዓ.ም] በምዕራብ ወለጋ ዞን ጉሊሶ ወረዳ ጋዋ ጋንቃ በተባለዉ ቀበሌ ባደረሱት ጥቃት የዜጎች ህይወት ያለፈ ሲሆን በርካታ የአካል ጉዳትም ደርሷል።

    ይህ የሽብር ጥቃት ፍጹም ሰላማዊ በሆኑ ንጹሃን ዜጎች ላይ የተቃጣ መሆኑ አጥፊ ቡድኑ የሚከተለዉ መንገድ ምን ያህል ያልሰለጠነ፣ ኋላ ቀርና ጭካኔ የተሞላበት መሆኑን ለአለም ሕዝብ ያጋለጠበት ነዉ።

    በዚህ አረመኔዊ ተግባር ህይወታቸዉን ላጡ ዜጎቻችን የተሰማንን ጥልቅ ሃዘን እየገለጽን ለተጎጂዎች ቤተሰቦችና ወዳጅ ዘመዶች እንዲሁም ለመላዉ ኢትዮጵያዊያን መጽናናትን እንመኛለን።

    መንግሥት እነዚህን ነብሰ ገዳዮች ከያሉበት አድኖ ሕጋዊ እርምጃ የሚወስድ መሆኑን እያረጋገጥን የፓርቲያችን አመራሮች፣ አባላት፣ ደጋፊዎችና መላዉ የሀገራችን ሕዝቦች የንጹሃን ዜጎችን ህይወት ያጠፉና አካል ያጎደሉ ሽብርተኛ ቡድኖችን አድነን እርምጃ በመዉሰድ የህግ የበላይነትን ለማስከበርና ህብረ-ብሄራዊ ፌዴራላዊ አንድነታችንን ለማስቀጠል በምናደርገዉ እርምጃ ዉስጥ ከጎናችን በመሆን አስፈላጊዉን ትብብርና ድጋፍ እንድታደርጉልን ጥሪያችንን እናቀርባለን።

    ብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽ/ቤት
    ጥቅምት 23 ቀን 2013 ዓ.ም

    ንጹሃን ዜጎችን በማንነታቸዉ በጅምላ ማጥቃት

    Anonymous
    Inactive

    ከኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) በወቅታዊ ሀገራዊ ሁኔታዎች ላይ የተሰጠ የአቋም መግለጫ

    የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ሀገራዊ ምክር ቤት አንደኛ ዓመት ሁለተኛ መደበኛ ስብሰባዉን ከመስከረም 29 ቀን እስከ ጥቅምት 1 ቀን  2013 ዓ.ም ሲያካሂድ በወቅታዊ የኢትዮጵ ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና የሰላም መደፍረስ ጉዳዮች ላይ በስፋትና በጥልቀት መክሯል፤ ፓርቲው የሚተገብራቸውን የተለያዩ መመሪያዎች፣ እንዲሁም የ2013-2017 ዓ.ም የፓርቲዉን የአምስት ዓመት ስልታዊ ዕቅድና የ2013 ዓ.ም የአንድ ዓመት ዕቅድ በስፋት እና በጥልቀት በመመርመር ወደተግባር እንዲገቡ በሙሉ ድምጽ ዉሳኔ ካሳለፈ በኋላ የሚከተሉትን የአቋም መግለጫዎች አዉጥቷል።

    1. ሁሉንም ተግባራት ማከናወን የሚቻለዉ በሀገሪቱ አራቱም ማዕዘኖች ሰላም ሲኖርና የሕግ የበይላነት ሲከበር መሆኑ ለሁሉም ግልጽ ነዉ፤ ነገር ግን በመላ ኢትዮጵያ ሀገሪቱን ለ27 ዓመታት ሲዘርፍና የዜጎችን ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች በመንፈግ እንደፈለገ ሲያስር ሲገድልና ሲያኮላሽ የነበረዉ ዘረኛዉ ህወሓት ከጠቅላይ አምባገነንቱ ተባሮ መቀሌ ከመሸገበት እና በዶ/ር ዐቢይ አህመድየሚመራዉ “የለዉጡ ቡድን” መንግሥታዊ ስልጣን ከተቆናጠጠበት ጊዜ ጀምሮ በርካታ ሁነቶች ተከስተዋል። በሀገራችን ኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ሁኔታ እጅግ ዘግናኝ ግድያዎችና የዘር ማጥፋት ወንጀሎች ነፍስ ባላወቁ እምቡጥ ሕፃናት ሳይቀር በጽንፈኛ ብሔርተኞችና እነሱ በሚደግፏቸዉ ታጣቂ ቡድኖች፤ በኦሮሚያ፣ በቤኒሻንጉል ጉምዝ (በተለይ በመተከል በተደጋጋሚ) እንዲሁም በደቡብ ክልሎች እስካሁን ድረስ እየተፈጸሙ ነዉ። ዜጎች በገዛ ሀገራቸዉ እንደሁለተኛ ዜጋ እየታዩ ሀብት ንብረታቸዉ እየተዘረፈና እየወደመ፣ ከመኖሪያ ቀያቸዉ እየተፈናቀሉ ነዉ። ኢሕአፓ ከዚህ በፊት ባወጣቸዉ ተደጋጋሚ አቋሞቹ እንደገለጸዉ፥ መንግሥት የሕግ የበላይነትን ለማስከበር ያሳየዉ ቸልተኝነትና መዘግየት እነዚህ ሁሉ ዘግናኝ ድርጊቶች እንዲፈጸሙ በር እንደከፈተ ያምናል። ስለዚህ ሉዓላዊነታችንንና የሕግ የበላይነትን የማስከበር፣ ሀገራዊ ሰላምን የማረጋገጥ እና የዜጎችን ደህንነነት የመጠበቅ ኃላፊነት ያለባቸዉን የተለያዩ የጸጥታ መዋቅሮች የሚመራዉ መንግሥት ስለሆነ፥ አሁን የጀመረዉን ሕግ የማስከበር ሥራ አጠናክሮ እንዲቀጥል፣ በአጥፊዎችም ላይ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወስድ፣ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በተለይም በቤኒሻንጉልና በኦሮሚያ መሽገው የዜጎችን ህይወት የሚቀጥፉ ሕገ-ወጥ ታጣቂ ቡድኖች ላይ ትጥቅ የማስፈታት እና ወደሕግ የማቅረብ፤ በወንጀል ድርጊት ያልተሳተፉትን አጣርቶ ወደ ሰላማዊ ኑሯቸዉ እንዲመለሱ የማድረግ የማያዳግም እርምጃ እንዲወስድ ይጠይቃል፤ ፓርቲያችን ኢህአፓም ጸረ-ሰላም ኃይሎችን በጽናት ይታገላል።
    2. በሀገራችን ኢትዮጵያ ላለፉት በርካታ ዓመታት የሚፈጸሙት ዘግናኝ የሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች መጣስ መንስዔው በዋነናት የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት ስለመሆኑ በተደጋጋሚ ተገልጧል። ከሁለት ዓመታት በፊት፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ አስተዳደርም ሕገ-መንግሥቱን ለማሻሻል በተደጋጋሚ ቃል ገብቶ እንደነበረ ይታወቃል። ነገር ግን ያ ሁሉ ቃል-ኪዳንና ያ ሁሉ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ወደጎን ተትቶ፥ በፖለቲካ ፓርቲዎች ድርድርና ውይይት ወቅት ይታያል ተብሎ የነበረው ሕገ-መንግሥት ምንም ዓይነት ማሻሻያም ሆነ ማስተካከያ ሳይደረግበት ከሃያ አምስት ዓመታት በላይ ለሰብዓዊና ዲሞክራሲያዊ መብቶች ሁሉ የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ዋነኛው መንስዔ እንደሆነ አለ። ኢሕአፓ ኢትዮጵያ ውስጥ በገዢው ፓርቲና በአጋሮቹ ለሚፈጸሙት ግፎች ሁሉ የመጀመሪያው ተጠያቂ ይህ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥትና ይዘቱ ስለሆነ አስቸኳይ ማሻሻያ እንዲደረግበት መንግሥትን ይጠይቃል።
    3. በተጨማሪም፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አስተዳደር በተደጋጋሚ ይደረጋል እያለ ቃል ሲገባ የነበረው የብሔራዊ ዕርቅና የሀገራዊ መግባባት አጀንዳ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ አጀንዳ እንደሆነ ኢሕአፓ ጽኑ እምነት አለው። በኢትዮጵያ የሚገኙት ሕጋዊና ሰላማዊ የሆኑት የፖለቲካ ኃይሎች በሙሉ የሚሳተፉበት፣ ሀገራዊ መግባባትን ትኩረቱ ያደረገ የፓርቲዎችና የሲቪክ ማኅበራት የጋራ መድረክ አስፈላጊነት ሳይታለም የተፈታ በመሆኑ፥ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ መንግሥት ለዚህ አጀንዳ ቅድሚያ ሰጥቶ የውይይትና የድርድር መድረኩ በአፋጣኝ እንዲካሄድ ኢሕአፓ ጥሪውን ያስተላልፋል።
    4. በያዝነው የ2013 ዓ.ም መጨረሻ ላይ ይካሄዳል የተባለውና የሚጠበቀው 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ሕጋዊና ሰላማዊ ሆኖ እንዲተገበር ኢሕአፓ ከፍተኛ የሆነ ፍላጎት አለው። በመሆኑም፥ ምርጫ የአንድ ቀን ተግባር ሳይሆን የብዙ ወራትን የመደራጀትና የማደራጀት ተግባራት ከእያንዳንዱ የፖለቲካና የሲቪክ ማኅበር የሚጠይቅ ክንውን መሆኑ ግልጽ ነው። ሆኖም ግን ከ5ኛው ሀገራዊ ምርጫ ማግስት ጀምሮ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ መንግሥት ሰላምንና ጸጥታን ማስከበር ተስኖት በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች ውስጥ ሁከትና ብጥብጥ እየተከሰተ ይገኛል። በዚህ ያለመረጋጋትና የሰላም እጦት ውስጥ ሆኖ ምርጫን የሚያክል ከፍተኛ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ማድረግም አጅግ አዳጋች ነው። በመሆኑም መንግሥት ሁሉም ዜጎች በሕግ ፊት እኩል የሚሆኑበትንና የሚዳኙበትን የፖለቲካ-ኢኮኖሚ ምህዳር አስፍቶ የዜጎችን በሕግ የበላይነት ሥር ብቻ የመምረጥና መመረጥ መብታቸውን እንዲያከናውኑ የማድረግ ኃላፊነቱን በተግባር እንዲወጣ ኢሕአፓ ጥሪውን ያስተላልፋል።
    5. በየጊዜዉ እያሻቀበ ያለዉ የዋጋ ግሽበትና በኮቪድ-19 ወረርሽኝ መከሰት ምክንያት በከፍተኛ ደረጃ ቁጥሩ የጨመረዉ ሥራ አጥነት የዜጎችን የእለት ተእለት ኑሮ በሰቆቃ የተሞላ አድረጓል፤ ከዚህ በተጨማሪ ባሳለፍነዉ 2012 ዓ.ም በተከሰቱ ሰው-ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎችም ለከፋ የርሀብ አደጋ ተጋላጭ ሆነዋል። በመሆኑም ኢሕአፓ መንግሥት በረዥም ጊዜ ለዜጎች በተለይም ለወጣቶች በርካታ የሥራ ዕድል መፍጠር የሚችሉ ሀገር በቀል ኢንቨስትመንቶችን እንዲያስፋፋ፣ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ እና ሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን በመቆጣጠር የዋጋ ግሽበቱን ከ2 ዲጂት በታች የሚወርድበትን የኢኮኖሚ አማራጭ እንዲተገበር፣ የአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸዉም ተገቢዉን ድጋፍ በወቅቱ እንዲያቀርብ በአጽንኦት ይጠይቃል።
    6. ከደንቢ ዶሎ ዩኒቨርሲቲ ወደ ትዉልድ ቀያቸዉ ሲመለሱ ታፍነዉ ተወስደዉ እስካሁን ድረስ ደብዛቸዉ የጠፋዉ ተማሪዎች ጉዳይ አሁንም ድረስ የኢሕአፓ የእግር እሳት ነዉ፤ ስለዚህ መንግሥት ልዩ ተኩረት ሰጥቶ ተማሪዎቹ እዉነት በህይወት ካሉ የማስመለስ ሥራ እንዲሠራ፥ አለያም እዉነቱን ለቤተሰቦቻቸዉ፣ ለኢትዮጵያና ለዓለም ሕዝብ እንዲያሳውቅ ኢሕአፓ የዘወትር ጥያቄዉን ዛሬም ያቀርባል።
    7. ኢሕአፓ ሕብረ-ብሔራዊ ፓርቲ እንደመሆኑ በኢትዮጵያ አንድነትና ሉአላዊነት፣ በሕዝቧ ዉህድ ማንንነት የማይጠራጠሩ፣ በሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ትግል ለሚያምኑና በሕጋዊ መንግድ ለተደራጁ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሁሉ ኑ! ሀገራችን ከገባችበት ጽንፈኛ የጎሳ እና የጥላቻ ፖለቲካ ቅርቃር በጋራ እንታደጋት፤ ሀገራዊ ብሔራዊ መግባባትን በመፍጠርና የፖቲካ ቁርሾን በማስወገድ ዘላቂ ሰለማና እድገት የሰፈነባት ሀገር እናድርጋት፤ የሚል የአክብሮት ጥሪዉን ያስተላልፋል።
    8. በሀገር ቤትና በዉጪ ሀገር ለምትገኙ ቀደምት የኢሕአፓ አባላትና መሥራቾች ዘላለማዊ ከሆነዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ህላዌ ጋር በየጊዜዉ እየታደሰ የሚዘልቅ ዘመን ተሸጋሪ ሀሳብ ያነገበዉ ኢሕአፓ ከዉጪ ሀገር ወደ ሀርቤት ከገባ ጊዜ ጀምሮ በሀገሩ ምድር ላይ ትግሉን በጽናትና ቁርጠኝነት እያካሄደ መሆኑን ተገንዝባችሁ ፓርቲያችን ኢሕአፓን በተለያየ መንገድ በመደገፍና በማጠናከር የትግላችሁን ፍሬ ማፍራት እውን ታደርጉ ዘንድ ጥሪዉን ያስተላልፋል።

    ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ!
    ኢሕአፓ ለተሻለ ነገ!

    የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)
    ጥቅምት 5 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ

    የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)

    Semonegna
    Keymaster

    መንግሥት የሰዎችን በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደህነነትና ነጻነት የመጠበቅ እና ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት ይጠብቅ!
    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ – ኢሰመጉ

    • መንግሥት በቤንሻንጉል ክልል የሰዎችን በሕይወት የመኖርና የአካል ደህንነት መብት ይጠብቅ

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 14 ማንኛውም ሰው ሰብዓዊ በመሆኑ የማይደፈርና የማይገሰስ በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደህንነትና ነጻነት መብት እንዳለው በግልጽ ይደግጋል። ይሁንና፥ በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፥ መተከል ዞን፥ ጉባ፣ ዲባጢ፣ ቡለን እና ወንበራ ወረዳዎች ውስጥ ከባለፈው ጳጉሜ ወር ጀምሮ ማንነቸታው ባልታወቁ አካላት ሲደርስ የነበረው ጥቃት፤ መስከረም 14 ቀን 2013 ዓ.ም በዳንጉር ወረዳ፣ በንገዝ ቀበሌ ዳግም ተከስቶ የበርካታ ንጹኃን ሰዎች ሕይወት መጥፋቱን፣ እንዲሁም የአካል ጉዳት መድረሱን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) ከቦታው ካሉ እማኞች ለመረዳት ችሏል። ጥቃቱ እየደረሰባቸው ያሉ ወረዳዎች በኢ.ፌ.ዲ.ሪ መከላከያ ሠራዊት ኮማንድ ፖስት ስር ተይዘው የጸጥታ ማስከበር እርምጃዎች እየተሠሩ ያሉ ቢሆንም፤ አሁንም ግን ተጨባጭ ስጋቶች እንዳሉ ኢሰመጉ ለማወቅ ችሏል።

    በመሆኑም፥ ኢሰመጉ መስከረም 9 ቀን 2013 ዓ.ም ባወጣው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ ይህ መሰሉ ጥቃት ዳግም እንዳይከሰት መንግሥት አስፈላጊና ሕጋዊ የሆኑ የአጭር እና የረዥም ጊዜ እርምጃዎችን በአስቸኳይ እንዲወስድ ማሳሰቡ አይዘነጋም። ስለሆነም፥ በእነዚህ አካባቢዎች ላይ በተደጋጋሚ በንጹኃን ሰዎች ላይ የሚደርሰውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች መንግሥት በከፍተኛ ትኩረት በመመልከት የሰዎችን በሕይወት እና በሰላም የመኖር፣ የአካል ደህነነትና ነጻነት የመጠበቅ ሰብዓዊ መብት በምልዓት እንዲያረጋግጥ ኢሰመጉ ዳግም ጥሪውን ያቀርባል። የችግሩ ስፋት ተባብሶ ከዚህም የባሱ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ከመድረሱ በፊት፥ የፌደራል እና የክልሉ መንግሥት፣ የአዋሳኝ ክልሎች መንግሥታት፣ የሲቪክ ማኅበራት፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና የሀይማኖት አባቶች በአካባቢው ዘላቂ ሰላም ለማስፈን በትኩረት እንዲሠሩ ኢሰመጉ ያሳስባል።

    በተጨማሪም፥ መንግሥት በእስካሁኑ ሕገ-ወጥ ድርጊት የተሳተፉ አጥፊዎችን ለሕግ እንዲያቀርብ፣ ለተጎጂዎች ተገቢውን ካሳ እንዲሰጥ እና የአካባቢውን ሰላም በማስጠበቅ የደረሰውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት መጣራት የሚቻልበት ሁኔታ እንዲያመቻች ኢሰመጉ በጥብቅ ያሳስባል።

    • መንግሥት የዜጎችን ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ ነጻነት ይጠብቅ

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀፅ 32 (1) ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በመረጠው የሀገሪቱ አካባቢ የመዘዋወር መብት እንዳለው በግልጽ ያስቀመጠ ቢሆንም፤ ዜጎች ለሥራ፣ ለትምህርት፣ ለንግድና ለተለያዩ ጉዳዮች ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብታቸው ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ ተገድቧል። ከመስከረም 11 እስከ መስከረም 14 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ ባሉት ቀናት መነሻቸውን ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች አድርገው ወደ አዲስ አበባ ከተማ ሲጓዙ የነበሩ የሕዝብ ማመላለሻ አውቶብሶች ሰበታ፣ ሱሉልታ፣ ጫንጮ እና ገብረ ጉራቻ ከተሞች ላይ ሲደርሱ በኦሮሚያ ክልል ፖሊስ እና ጸጥታ ኃይሎች ታግደው ወደ አዲስ አበባ እንዳይገቡ መደረጋቸውን ኢሰመጉ በየአካባቢዎቹ ከሚገኙ ከመረጃ ምንጮቹ ለመረዳት ችሏል። በእነዚህ ቀናት በነበረው እንቅስቃሴ ወደ አዲስ አበባ ሲጓዙ ከነበሩ የሕዝብ ማመላለሻ አውቶብሶች መካከል አብዛኛዎቹ በአቅራቢያ ወዳሉ ከተሞች ተመልሰው ለማደር በመገደዳቸው፤ ዜጎች ለከፍተኛ እንግልትና ወጪዎች መዳረጋቸውን ኢሰመጉ ለማረጋገጥ ችሏል።

    ይህን መሰሉ ድርጊት፥ ከአሁን ቀደምም ተከስቶ ጥቅምት 01 ቀን 2012 ዓ.ም መነሻቸውን ከተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች ያደረጉ ከ80 በላይ የሆኑ የሕዝብ ማመላለሻ አውቶቡሶች ‹‹ወደ አዲስ አበባ መግባት አትችሉም›› በማለት ወደ ደጀንና ባህር ዳር ከተሞች እንዲመለሱ መደረጋቸው ይታወሳል። ይህን አስመለክቶም፥ ኢሰመጉ በወቅቱ ጥቅምት 07 ቀን 2012 ዓ.ም ዜጎች ለከፍተኛ እንግልት እንየተዳረጉና ከቦታ ቦታ በነጻነት የመንቀሳቀስ መብታቸው አላግባብ እየተጣሰ መሆኑን የሚገልጽ አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ አውጥቶ ነበር። ስለሆነም፤ ከዚህ በኋላ ተመሳሳይ ዓይነት የመብት ጥሰቶች እንዳይከሰቱ፤ ተጨባጭ የጸጥታ እና ደህንነት ጉዳዮች በሚኖሩ ጊዜ አስቀድሞ ለማኅበረሰቡ በግልጽ በማሳወቅ አስፈላጊና ሕጋዊ የሆኑ እርምጃዎችን ከሕብረተሰቡ ጋር በትብብር በመሥራት ሊፈቱ እንደሚገባ ኢሰመጉ ያምናል።

    ከዚህም በተጨማሪ፥ በተለያዩ የሀገሪቱ አከባቢዎች በልዩ ልዩ ምክንያቶች የዜጎችን ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት አላግባብ የሚገድቡ የመንገድ መዝጋት እንቅስቃሴዎችን እና እርምጃዎችን በየደረጃው ያሉ የመንግሥት አካላት በትኩረት ተመልክተው ሕጋዊ እርምጃዎችን እንዲወስዱ ኢሰመጉ ይጠይቃል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ – ኢሰመጉ
    መስከረም 18 ቀን 2013 ዓ.ም

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) በአፍሪካ የሕዝቦችና የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የታዛቢነት ቦታ አለው፤ የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ፌዴሬሽን (FIDH) አባል፣ የዓለም አቀፍ ጸረ-ሥቃይ ድርጅት (OMCT) አባል፣ የምሥራቅና የአፍሪካ ቀንድ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥበቃ ኅብረት (Defend Defenders) መሥራች አባል ነው።

    የሰዎች በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደህነነትና ነጻነት የመጠበቅና ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት ይጠበቅ

    Anonymous
    Inactive

    በወቅታዊ ጉዳዮች ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ መስከረም 9 እና 10 ቀን 2013 ዓ.ም ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ ሕዝባችንን ባጋጠሙት ወቅታዊ ሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎች ላይ ተወያይቶ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፏል።

    1] በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በሕዝባችን ላይ የተፈፀመውን የዘር ጥቃት በተመለከተ፦

    አብን በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በመተከል ዞን ቡለን ወረዳ ከጳጉሜን 1 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት ማንነትን መሠረት አድርገው የተፈፀሙ ጥቃቶችን በተመለከተ ተጨባጭ መረጃዎችን ሲያሰባስብ ቆይቷል። በዚህም ከ160 በላይ ወገኖቻችን በአሰቃቂ ሁኔታ እንደተጨፈጨፉ ተገንዝቧል።

    የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአማራው ሕዝብ ጥንተ ርስቱን ተነጥቆ፣ ሰብዓዊና ዜግነታዊ መብቱ ተገፎ ለሦስት አስርት ዓመታት ለዝርፊያ፣ ለመፈናቀል እና ለተደጋጋሚ የዘር ፍጅት የተጋለጠበት ነው። በተለይም “ለውጥ” እየተባለ በሚጠራው ባለፉት ሁለት ዓመታት ጊዜ ውስጥ በክልሉ ውስጥ ባለው የአማራ ሕዝብ ላይ የሚደረገው የዘር ማጽዳትና ሰብዓዊ ጥቃት ከመቼውም ጊዜ በላይ ተባብሶ ቀጥሏል።

    ንቅናቄያችን ልክ ከሰኔ 22 እስከ 24 ቀን  2012 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በአማራው ሕዝብ ላይ  የደረሰውን ጥቃት አስመልክቶ እንደገለገፀው ሁሉ በቤንሻንጉል ክልል የተፈፀመው ጥቃት ተራ የማኅበረሰቦች ግጭት ወይም የሽፍቶች ድርጊት ውጤት ሳይሆን በአማራ-ጠል ትርክት ላይ የተመሠረተ፣ ስልታዊ የሆነ እና በመንግሥታዊ መዋቅር ጭምር የተደገፈ የሽብርና የዘር ማጥፋት ድርጊት መሆኑን ያምናል።

    በዚህ አሰቃቂ ጥቃት የትህነግ ተቀጥላ የሆኑ በተለያዩ ደረጃዎች የሚገኙ የቤንሻንጉል ክልል መንግሥት ኃላፊዎችን ጨምሮ የአማራ ሕዝብንና የሀገሪቱን ሰላም ለማሳጣት የሚታትሩ ባዕዳንና ውስጣዊ ኃይሎች ያሰማሯቸው የሽብር ቡድኖች እጃቸው እንዳለበት አብን ያምናል።

    የጥቃቱ ፈፃሚዎች ለተከታታይ ቀናት ሕዝባችንን (አማራ/አገው) በማንነታቸው እየመረጡ በአካባቢው ባሉ ትምህርት ቤቶች ውስጥ በኃይል አሰባስበው ለጅምላ ጭፍጨፋ ሲያዘጋጁ የክልሉ መንግሥት መረጃ እና ጥሪ እየቀረበለት ባለመድረሱ፤ የፌዴራል መንግሥቱም ባለው የደኅንነት መረጃ ተመርኩዞ ጥቃቱን ለመከላከል ፈጥኖ እርምጃ ባለመውሰዱ ተጠያቂ መሆን እንዳለባቸው አብን በጥብቅ ያምናል።

    አብን በሕዝባችን ላይ ከእንግዲህ ማናቸውንም ዓይነት ማንነቱን መሠረት አድርገው የሚፈፀሙ ጥቃቶች ሊታገስ የማይችልበት ደረጃ መድረሱን እየገለፀ፤ ለችግሩ አስቸኳይ መፍትሄ ካልተበጀለት ጉዳዩ  ከአማራው አልፎ ታላቅ ብሔራዊ ቀውስ ሊያስከትል እንደሚችል በመገንዘብ፦

    (ሀ) መሣሪያ የታጠቁ ገዳዮችን በመደገፍና እንዳላዩ በማለፍ ለጥቃቱ መዋቅራዊ ከለላ የሰጡና በቀጥታም ሆነ በእጅ አዙር የዘር ማጥፋቱ ተባባሪ የሆኑ የክልሉ ባለሥልጣናት በአስቸኳይ በሕግ ተጠያቂ እንዲሆኑ፤

    (ለ) በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ለሚኖረው ሕዝባችን አስተማማኝ የደህንነት ዋስትና እንዲሰጥ፣ በየአካባቢያቸው የፖሊስና የደኅንነት መዋቅሮች ውስጥ የመሳተፍ መብታቸው እንዲከበር፣ በማኅበረሰብም ደረጃ ደህንነታቸውን የሚያስጠብቁበት አስቸኳይ መፍትኄ እንዲፈለግ፤

    (ሐ) የፌደራል መንግሥቱና ገዥው ብልፅግና ፓርቲ በአማራው ሕዝብ ላይ በሚፈፀሙ የዘር ጥቃቶች ላይ የያዘውን ዳተኝነት እንዲያቆምና ችግሩን ለመከላከልና ከመሠረቱ ለመቅረፍ ተጨባጭ እርምጃ እንዲወስድ፤

    (መ) የአማራ ብልጽግና ፓርቲና የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በአማራ ሕዝብ ላይ በሦስት ወራት ውስጥ ብቻ ሁለት እጅግ አሰቃቂ የዘር ማጥፋት ድርጊቶች ሲፈፀሙ ወንጀሉን በስሙ ከመጥራት ጀምሮ ለችግሩ ዘላቂ መፍትኄ በመፈለግ ረገድ ያሳየው አቅም እና ፍላጎት ከደረጃ በታች መሆኑና ከእንግዲህም ለችግሩ ዘላቂ መፍትሄ ከዚህ አካል ሊመጣ እንደማይችል ሕዝባችን በግልፅ እንዲገነዘበው፤

    (ሠ) ሕዝባችን በተከታታይ ለዘር ማጥፋት እና ዘር ማጽዳት ጥቃቶች የተጋለጠበት የቤንሻንጉል ክልል አማራው ፍጹም ሥነ-ሕዝባዊ አብላጫ እያለው ፖለቲካዊ ውክልና በማጣቱ የተነሳ በመሆኑ ችግሩን በዘላቂነት ለማስወገድ የክልሉ መዋቅር የነዋሪዎቹን መብቶች በሚያረጋግጥ ሁኔታ እንዲከለስ ድርጅታችን አብን ያሳስባል።

    2] በአማራ ክልል የደረሰውን በጎርፍ የመጥለቅለቅ አደጋ በተመለከተ፦

    በአማራ ክልል በዘንድሮ ክረምት ዝናብ ምክንያት በተፈጠሩ የመሬት መንሸራተትና የጎርፍ አደጋዎች በአጠቃላይ በ6 ዞኖች በሚገኙ 36 ወረዳዎች ውስጥ ባሉ 164 ቀበሌዎች በተለያዩ ደረጃዎች የሚገለፁ ጉዳቶች እንዳደረሱ ይታወቃል።

    በተለይ ደግሞ በማዕከላዊ ጎንደር በምሥራቅ ደምቢያ ወረዳ፣ እንዲሁም በደቡብ ጎንደር በሊቦከምከም፣ ደራና ፎገራ ወረዳዎች በከፍተኛ የጎርፍ መጥለቅለቅ በመጠቃታቸው በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወገኖች ከመኖሪያ ቤታቸው ተፈናቅለው በጊዜያዊ መጠለያዎች ይገኛሉ።

    አብን እነዚህ በጎርፍና በመጥለቅለቅ የተፈናቀሉ ወገኖች በአስቸኳይ የእለት እርዳታ እንዲያገኙ የበኩሉን አስተዋፅኦ እንደሚያደርግ እየገለፀ፤ በመላው ዓለም የሚገኙ የድርጅታችን አባላትና ደጋፊዎች፣ መላው የአማራ ሕዝብና ኢትዮጵያውያን ወገኖች ለድጋፍ እጃቸውን እንዲዘረጉ ይጠይቃል።

    በጎርፉ ጉዳት በደረሰባቸው አካባቢዎች ሊነሱ በሚችሉ የወባ እና ሌሎች ውሃ-ወለድ በሽታዎች ሕዝቡ እንዳይጋለጥ ጥንቃቄ እንዲደረግ ይጠይቃል።

    ተጎጂዎች ሰብሎቻቸው እና ንብረቶቻቸው የወደሙባቸው በመሆኑ አፋጣኝ ድጋፍ እና የመልሶ ማቋቋም ተግባራት እንዲከናወኑ፣ ለመጪው ዘመንም የሚያስፈልጋቸውን ሁለገብ እርዳታ የማዘጋጀት ሥራ እንዲሁም ለዘለቄታው በየዓመቱ የክረምት ወቅት ሊከሰቱ ከሚችሉ ተመሳሳይ አደጋዎች ለመጠበቅ ዘላቂ መፍትኄ እንዲፈለግ ይጠይቃል።

    በመጨረሻም በአማራ ሕዝብ ታላቅ መስዋዕትነት የተገኘው ለውጥ አቅጣጫውን በመሳቱ በሕዝባችን ላይ ሥርዓት እና መዋቅር ሠራሽ ጥቃቶቹ ስጋት ደቅነውበት እንደቀጠሉ አብን ይገነዘባል።

    እጅግ ራስ-ወዳድ በሆነው ሰፊ የፖለቲካ ውቅር ውስጥ ጨካኞች እና ያልተገሩ ስብስቦች በአማራው ላይ ጥቃታቸውን ባስቀጠሉበት አግባብ፣ ለኩርፊያቸው እና ለደም ጥማታቸው አማራ ቋሚ ግብር ወይም ማስያዥያ የሚሆንበት የፖለቲካ ድባብ በትግላችን መገፈፍ ይኖርበታል።

    በተፈፀመው የዘር ማጥፋት ወንጀል ውስጥ ያሉ ተዋንያንንና በቸልተኝነትና በሴራ ተባባሪ የሆኑ አካላትን ጭምር ለማጋለጥ እና በኃላፊነት እንዲጠየቁ ለማድረግ አብን እንደሚሠራ በአፅንዖት ለማስገንዘብ ይወዳል።

    በመጨረሻም አብን በቤንሻንጉል ጉሙዝና በኦሮሚያ ክልሎች በአሰቃቂ ሁኔታ የዘር ጭፍጨፋ ወንጀል ሰለባ ለሆኑ ወገኖቻችን የተሰማንን ጥልቅ ሐዘን ለመግለፅ ለመላው የአማራ ሕዝብና ለሕዝባችን ወዳጆች ከነገ ሰኞ መስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም  ጀምሮ እስከ ማክሰኞ መስከረም 12 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ ለሁለት ቀናት በምናደርገው ጥቁር የመልበስ እና ተያያዥ የሐዘን መግለጫ ሥርዓቶች እንዲካፈሉ አብን የአክብሮት ጥሪውን ያቀርባል።

    አንድ አማራ ለሁሉም አማራ ፥ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ!
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) /NaMA/
    መስከረም 9 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ ፣ ሸዋ ፣ ኢትዮጵያ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)

    Anonymous
    Inactive

    በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል የተከሰተውን ግድያ እና መፈናቀል አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የተሰጠ ይፋዊ መግለጫ

    አሶሳ (ኢሰመኮ) – የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን /ኢሰመኮ/ (ኮሚሽኑ) በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል በአንዳንድ አካባቢዎች እየታዩ ያሉ የፀጥታ መደፍረሶችን ተከትሎ ያጋጠሙ ክስተቶች እጅግ አሳስበውታል።

    ኮሚሽኑ ከክልሉ ከመተከል ዞን፣ ቡለን ወረዳ አጳር ቀበሌ እንዲሁም ከወንበራ ወረዳ መልካን ቀበሌ እጅግ አሳሳቢ መረጃዎች እየደረሱት ነው። ኮሚሽኑ በጳጉሜ 1 ቀን 2012 ዓ.ም. እንዲሁም ከጳጉሜ 2 አስከ መስከረም 3 ቀን 2013 ዓ.ም. መካከል ቢያንስ ሁለት ጥቃቶች ማጋጠማቸውን ከክልሉ መንግሥት ለማረጋጥ ችሏል።

    በቦታው ላይ ከሚገኝ አንድ መንግሥታዊ ምንጭ መረዳት እንደተቻለው፥ ቢያንስ በሁለት ዙር በደረሱ ጥቃቶች ባልታጠቁ ሲቪሎች ላይ ግድያዎች መፈፀማቸውን፤ እንዲሁም በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መፈናቀላቸውን ኮሚሽኑ ማረጋገጥ ችሏል።

    የክልሉ መንግሥት እንደጠቆመው ከተፈናቃዮቹ መካከል 300 ያህል የሚሆኑት ወደ ቀያቸው የተመለሱ ሲሆን፤ የሀገር መከላከያ ሠራዊት እና የፌደራል ፖሊስ ከክልሉ የፀጥታ ኃይሎች ጋር በመተባበር አካባቢውን ለማረጋጋት እየሠሩ ነው።

    ስለሆነም ኮሚሽኑ፡-

    • በክልሉ ባልታጠቁ ሲቪሎች ላይ የደረሱትን ጥቃቶች፣ ግድያዎች እና መፈናቀሎችን ሙሉ በሙሉ ያወግዛል፤
    • በክልሉ ሰላምና መረጋጋት እንዲኖር በመከላከያ ሠራዊት፣ በፌዴራል ፖሊስ እና በክልል የጸጥታ ኃይሎች ሰላምን ለማስጠበቅ እየተደረገ ያለውን ጥረት ያበረታታል፤
    • በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ሕገ-መንግሥትና እንዲሁም ኢትዮጵያ ተቀብላ ባጸደቀቻቸው የቃል ኪዳን ሰነዶች ማለትም፡ በአፍሪካ የሰብዓዊና ሕዝቦች መብቶች ቻርተር፣ በዓለምአቀፍ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች ቃል ኪዳን (ICCPR) እና በሌሎች አግባብነት ባላቸው የሰብዓዊ መብቶች ሰነዶች የተደነገጉትን በህይወት የመኖር መብቶች እንዲከበሩ ይጠይቃል፤
    • በክልሉ ከዚህ ቀደምም ተመሳሳይ ጥቃቶች በተደጋጋሚ ማጋጠማቸውን ከግምት ውስጥ በማስገባት፥ ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው አካላት ገለልተኛ፣ ፈጣን እና ውጤታማ ምርመራዎችን በማካሄድ ግድያው በተከሰተባቸው ሁኔታዎች ላይ የጥፋተኞችን ተጠያቂነት እንዲያረጋግጡ ያሳስባል፤
    • የሚመለከታቸው የክልሉ መንግሥት አካላት ተጎጂዎች እና ቤተሰቦቻቸው ወደ ቀደመ ህይወታቸው የሚመለሱበትን መንገድ እንዲያመቻቹ ጥሪ ያቀርባል፤
    • ኮሚሽኑ በተለይም መሰረታዊ የሆነው በህይወት የመኖር መብት ይረጋገጥ ዘንድ የሚመለከታቸው የክልሉ የመንግሥት አካላት እንዲሠሩ ያሳስባል።

    በአጠቃላይ ኮሚሽኑ ሁሉም የፖለቲካ ቡድኖች እና ባለድርሻ አካላት ገንቢ ውይይት እንዲያደርጉ እና ከማንኛውም ዓይነት የሁከት ድርጊቶች እንዲታቀቡ ጥሪውን ያቀርባል፤ እንዲሁም በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ሕገ-መንግሥት እና ኢትዮጵያ ፈርማ የተቀበለቻቸውን ሌሎች አግባብነት ያላቸውን የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች ውስጥ የተቀመጡ መብቶችን እና ግዴታዎችን እንዲያከብሩ ኮሚሽኑ እየጠየቀ፥ በቀጣይም ጉዳዩን በንቃት እንደሚከታተለው ይገልፃል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን /ኢሰመኮ/

    የሰብዓዊ መብቶች እና ተያያዥ ጉዳዮች ― ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን

    Anonymous
    Inactive

    በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ውስጥ እየደረሰ ያለው የሰላማዊ ሰዎች ጥቃት

    በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ቡለን እና ወንበራ በተባሉ ወረዳዎች ታጣቂዎች በሰላማዊ ሕዝቦች ላይ ጉዳት እያደረሱ አንደሆነ ነዋሪዎችና ጉዳት የደረሰባቸው ቤተሰቦች አመለከቱ። የአማራ እና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች ኃላፊዎች በታጣቂዎች ላይ እርምጃ እየወሰዱ እንደሆነ ይናገራሉ።

    በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ቡለን እና እና ወንበራ ወረዳዎች በሚገኙ አንዳንድ ቀበሌዎች ከቀላል እስከ ከባድ መሳሪያ የታጠቁ ኃይሎች ሰሞኑን በወረዳዉ ነዋሪዎች ላይ ጥቃት በማድረስ ሕብረተሰቡን ለሞት፣ ለስደት እና ለአካል ጉዳት እየዳረጉት እንደሆነ ነዋሪዎቹና ቤተሰቦቻቸው የተጎዱባቸው ግለሰቦች አመልክተዋል። ለሥራ በተንቀሳቀሱበት ባለፈው እሁድ (መስከረም 3 ቀን 2013 ዓ.ም.) ስድስት ዘመዶቻቸው እንደተገደባቸው በአማራ ክልል አዊ ብሔረሰብ አስተዳደር የጓዋንጓ አካባቢ ነዋሪ ለዶይቼ ቬለ ራድዮ አማርኛ ዝግጅት ክፍል በስልክ ተናግረዋል። የግልገል በለስ ነዋሪ የሆኑና ለደህንነታቸው ስማቸውን መጥቀስ ያልፈለጉ ነዋሪ በበኩላቸው፥ “መተከል ዞን ውስጥ ቡለን እና ወንበራ አካባቢዎች የሚፈፀመው ጥቃት እጅግ ዘግናኝና ጭካኔ የተሞላበት ነው” ብለዋል፡፡

    ግጭቱ እንዲባባስ ከመንግሥት መዋቅሩ መረጃ የሚያደርስ አካል ሊኖር እንደሚችል ግምታቸውን የተናገሩት አስተያየት ሰጪዎቹ፥ ለዚህም ምክንያታቸው ታጣቂው ኃይል ባለበት አካባቢ የፀጥታ ኃይሉ ሲንቀሳቀስ ቀድመው ከቦታው እንደሚሰወሩ አብራርተዋል። በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ ተማሪና የአማራ ዴሞክራሲ ኃይሎች ንቅናቄ ሊቀመንበር አቶ ተስፋሁን ዓለምነህ በበኩላቸው “የአማራ ክልላዊ መንግሥት ከክልሉ ውጪ ያሉ የአማራ ክልል ተወላጆችን መብት እያስጠበቀ አይደለም” ሲሉ ይከስሳሉ። የአማራ ክልል የሰላምና ሕዝብ ደህንነት ጉዳዮች ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ገደቤ ኃይሉ እንደገለፁት “ፀረ-ሰላም” ያሏቸውን አካላት ለመደምሰስና በቁጥጥር ስር ለማዋል ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ጋር በጋራ እየተሠራ ነው።  ችግሩ የተፈጠረበትን የመተከል ዞን ዋና አስተዳዳሪና የዞኑን ፀጥታ ዘርፍ ኃላፊዎች ስለጉዳዩ ለማነጋገር ብሞክርም “መረጃ በስልክ አንሰጥም” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል። ከባሕር ዳር ጋዜጠኛ ዓለምነው መኮንን ጉዳዩ የሚመለከታቸውን አነጋግሮ ተከታዩን ዘገባ ለዶይቼ ቬለ ራድዮ አማርኛ ዝግጅት ክፍል ልኳል።

    በቤንሻንጉል ክልል መተከል ዞን የተፈጠረው ምንድን ነው?

    ሰኞ ጳጉሜን 2 ቀን 2012 ዓ.ም መተከል ዞን ቡለን ወረዳ ውስጥ ኤጳር በምትባል ቀበሌ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ኮማንደር ነጋ ጃራ ‘ጸረ-ሰላም’ ያሏቸውኃይሎች (ታጣቂዎች) በአካባቢው ነዋሪዎች ላይ የአፈናና የግድያ ወንጀል ከመፈጸማቸው በተጨማሪ የተለያዩ ጉዳቶችን ማድረሳቸውን ምክትል ኮሚሽነሩ ለቢቢሲ ራድዮ አማርኛ ዝግጅት ክፍል ተናግረዋል።

    ቢቢሲ በበኩሉ የአካባቢው ነዋሪዎችን ጠይቆ እንደተረዳው፥ በተለያዩ ጊዜያት ማንነታቸው ባልታወቁ ሰዎች በሚፈጸመው ጥቃት የተነሳ የዕለት ከዕለት ተግባራቸውን በስጋት ውስጥ ሆነው እንደሚያከናውኑ ተናግረዋል። [ለምሳሌ ያህል፥ ሰኔ 2 ቀን 2011 ዓ.ም.  በክልሉ ዳንጉር ወረዳ ታጣቂዎች በከፈቱት ተኩስ አምስት ሰዎች መገደላቸውን፤ በሌላ ጊዜ ደግሞ ሰኔ 20 ቀን 2011 ዓ.ም. በክልሉ መተከል ዞን ዳንጉር ወረዳ የታጠቁ ኃይሎች ባደረሱት ጥቃት ሕጻናትን ጨምሮ ከ30 ሰዎች በላይ መሞታቸውን የክልሉን ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻዲልን ጠቅሶ የቢቢሲ ራድዮ አማርኛ ዝግጅት ክፍልዘግቦ ነበር።]

    በሚፈጸሙት ጥቃቶችም በሰው ህይወት፣ አካልና ንብረት ላይ ጉዳት እየደረሰ በመሆኑ እንቅስቃሴያቸው መገደቡንና ክስተቱም ሁሉም በነጻነት እንዳይንቀሳቀስ በማድረጉ በአካባቢዎቹ ባለው ሥራ ላይ ችግር እየፈጠረ መሆኑን አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ የወረዳው የመንግሥት ሠራተኛ ተናግረዋል።

    ጥቃት ፈጻሚዎቹ ከአካባቢው ነዋሪዎች በተጨማሪ የጤና እና ግብርና ባለሙያዎችን ለማፈን ከመሞከራቸውም በላይ፥ በመንግሥት መዋቅር ላይ ጥቃት ለማድረስ የሞከሩ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከመካከላቸው አንዳንዶቹ ወደ ሌላ ወረዳ መሸሻቸውን ምክትል ኮሚሽነሩ ገልጸዋል።

    እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት ተከትሎ በወጣው መረጃ መሠረት የአካባቢው ፖሊስ፣ የመከላከያ ሠራዊት እና የክልሉ ልዩ ኃይል በጋራ በመሆን ወደ ወረዳዎቹ በመግባት ጥቃቱን ለማስቆምና ፈጻሚዎቹን ለመቆጣጠር በቅንጅት እየሠሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል።

    እንደ ምክትል ኮሚሽነር ኮማንደር ነጋ ጃራ ገለጻ ከሆነ በወረዳዎቹ ጉዳት እያስከተለ ያለው ጥቃት የሚፈጸመው ስሙን ለጊዜው መጥቀስ ባልፈለጉት “የተቃዋሚ የፖለቲካ ቡድን አባላት” መሆኑንና በቁጥጥር ስር እያዋሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከዚሁ ጋር በተያያዘ እስካሁን የታገቱ እና የሞቱ ሰዎች ቁጥር በተመለከከተ “በቁጥር ደረጃ በዝርዝር አልተለየም” ያሉት ኮማንደር ነጋ፥ መረጃው ተሰባሰቦ ሲያልቅ እንደሚያሳውቁ ገልጸዋል።

    ምክትል ኮሚሽነሩ በክልሉ ባሉ አንዳንድ አካባቢዎች እየተፈጸመ ካለው ጥቃት ጋር በተያያዘ ‘ጸረ-ሰላም’ ያሏቸው ኃይሎች ከውጪ ሀገር ጭምር ድጋፍ እንደሚደረግላቸው መረጃ መገኘቱን ጠቅሰው፥ “ወጣቶችን ለመመልመል እንደሚንቀሳቀሱም” ጨምረው ተናግረዋል። ጥቃት ፈጻሚዎቹ ከቀናት በፊል መልካን በሚባል ቀበሌ 30 ሰዎችን አፍነው የነበረ ሲሆን፥ አሁን እነሱን መልቀቃቸውን አመልክተው፤ የያዟቸውን ሰዎች ቡድኑን እንዲቀላቀሉ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል።

    በተለያዩ ጊዜያት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ማንነታቸው ያልተገጹ ቡድኖች በነዋሪዎች ላይ ጥቃት በመፈጸም በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት ከማድረሳቸው ባሻገር በተደጋጋሚ ሰዎችን እያገቱ እንደሚወስዱ ሲዘገብ ቆይቷል። እየደረሰ ያለውን የሰላማዊ ሰዎች ጥቃት፣ የሰውና የንብረት ጉዳት፣ እንዲሁም ተደጋጋሚ የስዎች መታገት ለማስቆም የክልሉ የጸጥታ ኃይሎች ከሀገሪቱ የመከላከያ ሠራዊት ጋር በመሆን ጥቃት ፈጻሚዎቹን ለመቆጣጠርና ድርጊቱን ለማስቆም እየጣሩ መሆኑ ተገልጿል።

    ምንጮች፦ ዶይቼ ቬለ ራድዮ እና ቢቢሲ ራድዮ የአማርኛ ዝግጅት ክፍሎች

    ቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 16 total)