Search Results for 'ኢትዮጵያዊ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያዊ'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 124 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    “የደጋ ሰው” በተሰኘው የሙዚቃ ስብስብ ላይ ሙያዊ ውይይት ተከናወነ

    በኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ የብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደሥላሴ የሥነ-ጥበባት ማዕከል አዘጋጅነት “የደጋ ሰው” በተሰኘው የሙዚቃ ስብስብ ላይ ሙያዊ ውይይት ተካሂዷል።

    በውይይቱ ላይ አጠቃላይ ሙያዊ ትንታኔውን የሙዚቃ ባለሙያና የሙዚቃ ሃያሲ አቶ ሰርጸ ፍሬስብሃት ያቀረቡ ሲሆን፥ የሙዚቃው አቀናባሪና ፕሮዲዩሰር ኢዩኤል መንግሥቱ እና ድምጻዊቷ የማርያም ቸርነት (የማ) የሙዚቃ ስብስቡን ሥራ ታሪክና ውጣ ውረድ አብራርተዋል።

    አቶ ሰርጸ ፍሬስብሃት ሙዚቃው የዓለም ሙዚቃ ዘውግ (World music genre) ላይ የሚመደብ ምርምራዊ ሥራ መሆኑን አመላካች፣ አስረጅ እና ታሪካዊ ዳራዎችን በመጥቀስ ያብራሩ ከመሆኑም ባሻገር፥ እስካሁን በዓለም ሙዚቃ ዘውግ ከተሠሩ የኢትዮጵያዊያን ሙዚቃዎች ውስጥ የቀለለ ዕድል በሌለበት በጥረትና ትጋት የተፈጠረ የጥበብ ሥራ መሆኑን አብራርተዋል።

    ከዚህ አስቀድሞ በየዓለም ሙዚቃ ዘውግ (World music genre) አስቴር አወቀ፣ እጅጋየሁ ሽባባው፣ ምንይሹ ክፍሌ፣ ዣን ስዩም ሔኖክን የመሰሉ ከያንያን በውጭ ሀገር ከመኖራቸውና ለወርልድ ሙዚቃ ካላቸው ተጋላጭነት አንጻር በመመዘንም “የደጋ ሰው” የሙዚቃ ስብስብ በተለየ ሁኔታ በምርጫና በጥረት የተሠራ ሥራ መሆኑን አቶ ሰርጸ አብራርተዋል።

    የሙዚቃ ስብስቡ የአፍሪካ፣ የአውሮፓ እና የሰሜን አሜሪካ ሙዚቀኞች ከኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች ጋር የተጣመሩበት እና በአቀናባሪው ምርጫና ትጋት ወደ እውንነት የተቀየረ መሆኑ ተገልጿል።

    የሙዚቃው አቀናባሪ እና ፕሮዲዩሰር ኢዩኤል መንግሥቱ ሥራው በቦኬ ማኅበረሰብ ሙዚቃ በመሳብ እና ምርምሮችን በማስፋት ሀገር በቀል የሙዚቃ ቅንጣቶችን ከዓለም አቀፍ የሙዚቃ እሳቤዎች ጋር በመቀየጥ የባሕል ውህደትና ቅንብር ለመፍጠር የተሠራ ሥራ መሆኑን የሙዚቃ ስብስቡን ታሪክ አስረድተዋል።

    ድምጻዊቷ የማርያም ቸርነት ከእንግሊዝኛ የሙዚቃ ድምጻዊነት በሽግግር ወደእንዲህ አይነት የባሕል ቅይጥ እና ዓለማቀፋዊ መልክ ወዳለው ሥራ የተሻገረችበትን መልክ ሆኔታዎች አንስታ ገልጻች። “የደጋ ሰው” የሙዚቃ ስብስብ ከሰባት ሀገራት፣ ከሃያ በላይ ሙዚቀኞች የተሳተፉበት ሙዚቃ ስብስብ ሲሆን፥ በሙዚቃ ድርሰት፣ በሁለት የዘፈን ግጥሞች፣ በቅንብር እና በፕሮዲዩሰርነት ኢዩኤል መንግሥቱ፣ ጎላ ጎሕ (የብዕር ስም) ስምንት የሙዚቃ ግጥሞችን በማበርከት፣ አንጋፋው ይልማ ገብረአብ አንድ የሙዚቃ ግጥም ድርሰት በመስጠት የተሳተፉበት ስብስብ ነው።

    በውይይቱ ላይ በርካታ ታዳምያን ተገኝተው ስለሙዚቃ ሥራው የተሰማቸውን ስሜት እና በቀረቡት መነሻ ሃሳቦች ላይ ጥያቄና ማብራሪያ በማቅረብ ጠንካራ ተሳትፎ አድርገዋል።

    በውይይቱም ላይ ከሙዚቃው ድርሰትና ቅንብር በተጨማሪ የተለየ ሆኖ በሀሳብ ላይ ትኩረት አድርጎ ስለመጣው የሙዚቃው ግጥሞች በርካቶች አድናቆታቸውን ሰጥተዋል። በሌላም በኩል ምርምርና የሥነ-ጥበብን ከፍታ ይዘው ለሚመጡ አድካሚና ውድ ሥራዎች አድማጩ ሊሰጠው ስለሚገባው ትኩረት በማንሳት ጠንካራ አስተያየቶች ተሰጥተዋል።

    በዝግጅቱም ላይ ከራያ ማኅበረሰብ የተላኩ ወኪሎች በቦታው ተገኝተው ለድምጻዊቷ፣ ሙዚቃው አቀናባሪና ገጣሚ እንዲሁም በሥራው ላይ ለተሳተፉ ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። ለየማርያም ቸርነትም የራያ ባሕል ልብስ ስጦታ አበርክተዋል።

    የካቲት 2 ቀን፥ 2016 ዓ.ም በ “ነገረ መጻሕፍት” ዝግጅት የገብረሕይወት ባይከዳኝ “ሕዝብና የመንግሥት አስተዳደር” መጽሐፍ የታተመበትን 100ኛ ዓመት በማስመልከት ከፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገዳ ጋር በሚደረገው ውይይት ላይ እንድትገኙ ከወዲሁ የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ጋብዟል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ

    Semonegna
    Keymaster

    የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በወቅታዊ ጉዳይ ላይ የሠጠው መግለጫ

    የአማራ ሕዝብ ከሌሎች ኢትዮጵያዊያን ወንድምና እህት ሕዝቦች ጋር በመሆን የኢትዮጵያን ሕልውና ለማስጠበቅ ያልከፈለው ዋጋ የለም፡፡

    የኢትዮጵያዊ አንድነትን ለማጽናትም ሲል ከመክፈል የሚሰስተው ዋጋ የለም፡፡ በመሆኑም የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥትም ሆነ መላው የክልሉ ሕዝብ በሀገር ሕልውና እና በኢትዮጵያ አንድነት ጉዳይ ላይ ያለው አቋም የጊዜ እና የሁኔታዎች መፈራረቅን ተከትሎ የማይለዋወጥ ጽኑ ሀቅ ስለመሆኑ በታሪክና በዜጎች ህሊና እንዳይፋቅ ሆኖ የተከተበ እውነታ ነው፡፡

    ስለሆነም የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በክልላችን ውስጥ የሚተለሙም ሆነ የሚፈጸሙ ማንኛውም ዓይነት ተግባራት ከዚህ ብሔራዊ መዳረሻ አንጻር የሚቃኙ መሆናቸውን መገንዘብ ያስፈልጋል። ማንኛውም ዓይነት ተቋማዊ መዋቅሮች የሚደራጁበትም አልፋ እና ኦሜጋዊ አመክንዮ ይኸው ነው፡፡

    ከሰሞኑ በሀገር አቀፍ ደረጃ ዋና አጀንዳ ከሆኑት ብሔራዊ ጉዳዮች መካከል አንዱ የሆነውና በሁሉም ክልሎች የሚገኙ የልዩ ኃይል አደረጃጀቶችን መልሶ የማደራጀት ተግባር ዋነኛ እና ብቸኛ ምክንያትም ዓላማው የኢትዮጵያን ሕልውናን የበለጠ የማበርታት የጋራ ግብን ያነገበ፣ በተሟላ ሀገራዊ ጥናት ላይ የተመሠረተ፣ የሕዝቦችን አንድነትንና ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የተተለመ እንዲሁም የጋራ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታን እውን ለማድረግ በሁሉም ክልሎች ታምኖበት የተገባበት ወሳኝ ተግባር ነው።

    የአማራ ክልል ልዩ ኃይል በክልሉ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ከሀገር መከላከያ ሠራዊትና ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በጋራ በመሆን የአማራ ክልልን ሕዝብ ሠላም እና ጸጥታን ለማስከበር በቅንነትና በቆራጥነት አገልግሏል፡፡

    ከክልል አቀፍ ውለታው ባሻገር በኢትዮጵያ ሕልውና ላይ ተጋርጦ የነበረን ከፍተኛ አደጋ ለመቀልበስ ሲል ከሌሎች ኢትዮጵያዊያን ወንድምና እህት ሕዝቦች ጋር በመሆን በኢትዮጵያዊነት የላቀ ሥነ-ልቦናዊ ከፍታ ሁሉንም ዓይነት መስዋዕትነት ከፍሎ ኢትዮጵያና አትዮጵያዊነት ላይ የተቃጣን አደጋ በታማኝነት አምክኗል፡፡ ይህ አኩሪ ገድልና ውለታ ሁልጊዜም በታሪክና በትውልድ ልቦና ውስጥ እየተዘከረና ጽንቶ የሚኖር ታላቅ ተግባር ነው፡፡

    ይህን መሰሉን ብሔራዊ ውለታ የበለጠ ለማጎልበትና ለማስፋት የሚቻልበትን ሁኔታ ለማመቻቸት አማራ ክልል ጨምሮ በሁሉም ክልላዊ መንግሥታት ውስጥ የሚገኙ የልዩ ኃይል አደረጃጀቶችን ያሰባሰበ በጥናት ላይ የተመሠረተ መልሶ የማደራጀት ሥራ በሁሉም ክልሎች በየደረጃው ካለው የፀጥታ አመራር፣ የመንግሥት አመራር፣ የልዩ ኃይል አመራርና አባላት፣ በጉዳዩ ዙሪያ ውይይት የተደረገበትና እየተደረገበት ያለ በሂደት ላይ የሚገኝ የጋራ ሀገራዊ ተግባር ነው።

    ይህ የልዩ ኃይል ፖሊስ አደረጃጀቶችን መልሶ የማደረጃት ወይም የሪፎርም ሥራ በሁሉም የፌደራልና ክልላዊ መንግሥታት መሪዎች የጋራ ስምምነትና እንደ አንድ ሀገር አንድ ጠንካራ የፌደራልና የክልል የፀጥታ መዋቅር እንዲኖረን ታስቦ የተለያዩ አማራጮች ለልዩ ኃይል አባላቶቻችን ያቀረበ እና ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በኩር ያደረገ ሀገር አቀፍ ታሪካዊ ተግባር ነው፡፡ ተግባሩም ለሁሉም ክልል የልዩ ኃይል አደረጃጀቶች የሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ የፌደራልና የክልል መደበኛ ፖሊስ፣ የፌደራልና የክልል የማረሚያ ቤቶችን ፖሊስ አባል እንዲሆኑ አማራጮች ያቀረበ ብሔራዊ ተግባር ነው።

    በቅርቡ በመንግሥት የተጀመረው የልዩ ኃይል ፖሊሶች የሪፎርም ተግባር እውነታዉ ከላይ በተቀመጡት አማራጮች ለሁሉም ክልሎች የልዩ ኃይል አባላት እንደየፍላጎታቸው በቀረቡት አማራጮች እንዲካተቱ ታሳቢ ያደረገ የፌደራልና የክልል የፀጥታ አካላትን የማጠናከር በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተከናወነ የሚገኝ ብሔራዊ ተግባር ነው።

    ይሁን እንጂ እውነታዉ ይሄ ሆኖ ሳለ አንዳንድ አካላት የአማራ ክልል ልዩ ኃይልን አየር ላይ እንዲበተን እየተደረገ ነው የሚል ከእውነት የራቀ ፍፁም በተሳሳተ መንገድ ሀሰተኛ መረጃዎችን በማሰራጨት የአማራን ሕዝብ ውስጣዊ ሰላምና አንድነት የሚያደፈርስ፣ የልዩ ኃይሉን አንድነት የሚረብሽ፣ ባልተገባ መንገድ ጥርጣሬ ውስጥ እንዲገባ የሚያደርጉ እንቅስቃሴ ላይ ተጠምደው ይገኛሉ። ድርጊቱም ሕዝባችንና የልዩ ኃይል አባሎቻችንን በተጨባጭ እየረበሸ ይገኛል።

    ስለሆነም መላው የልዩ ኃይል አባላትና መላው የክልሉ ሕዝብ እንዲገነዘቡት የምንፈልገው መንግሥት ይህንን የመልሶ ማደራጀት ሥራ የሚከውነው የልዩ ኃይላችንን የሰው ኃይል ለበለጠ ፋይዳ ላለው ተልዕኮ መልሶ የማደራጀትና ብቁ የማድረግ ሀገራዊና ክልላዊ ፋይዳ የማዘጋጀት ተግባር እንጅ በመልሶ ማደራጀቱ ሂደት ምንም ዓይነት የሚበተንም ኃይል የሌለ መሆኑን ግንዛቤ ሊያዝበት ይገባል።

    ስለሆነም መላው የአማራ ሕዝብ በአንዳንድ አፍራሽ የሚዲያ ቡድኖች በሚነዛው አሉቧልታ ሳይታለልና ሳይደናገር እንደ አንድ ሕዝብ ያለውን ታሪኩን እና ሥነ ልቦናውን በሚመጥነው የኢትዮጵያዊነት ላዕላዊ ማእቀፍ ጥላ ስር በመሰባሰብ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊ አንድነትን የማጽናት ሂደትን እንዲደግፍ ጥሪ እናቀርባለን፡፡

    የተከበራችሁ የክልላችን ሕዝቦች፥ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የክልሉን ሕዝብ መብትና ጥቅም የሚጋፋ የትኛውንም ዓይነት ውሳኔ ተግባራዊ እንደማያደርግ ሕዝባችን ሊያውቀው ይገባል።

    የተከበራችሁ የክልላችን የልዩ ኃይል ፖሊስ አባላት እንዲሁም መላው ሕዝባችን፥ ለራሳቸው ጥቅምና ፖለቲካዊ ዓላማ ሲሉ ክልላችንን የትርምስ ቀጠና ለማድረግ ከሚሠሩ አካላት ራሳችሁን በመጠበቅ የክልላችን የፀጥታ ኃይል ብቁ ዘቦች ሁናችሁ ሰላምና ፀጥታን በማስጠበቅ ሥራችሁ እንድትተጉ እያሳሰብን የተጀመረውን ልዩ ኃይሉን መልሶ የማደራጀት ሥራ መላው ሕዝባችንንና ልዩ ኃይላችንን በማወያየት እና በመተማመን የሚፈፀም በመሆኑ በየካምፓችሁ ወይም በየተመደባችሁበት የሥራ ቦታ ተረጋግታችሁ በትግስት እንድትጠብቁ የክልሉ መንግሥት ጥሪውን ያስተላልፋል።

    የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት
    መጋቢት 29/2015 ዓም
    ባሕር ዳር፥ ኢትዮጵያ

    ምንጭ፦ የክልሉ ሕዝብ ግንኙነት

    Amhara Regional State የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት

    Semonegna
    Keymaster

    ዲላ ዩኒቨርሲቲ በሥነ-ሕንፃ ምህንድስና፣ በሕክምና እና በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች አስመረቀ

    ዲላ (ዲላ ዩኒቨርሲቲ) – ዲላ ዩኒቨርሲቲ በቴክኖሎጂና ምህንድስና ኮሌጅ ስር በሥነ-ሕንፃ ምህንድስና (አርክቴክቸር) ትምህርት ክፍል፣ በሕክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በሕክምና (ሜዲሲን) ትምህርት ክፍል እንዲሁም በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች መጋቢት 02 ቀን፥ 2015 ዓ.ም አስመርቋል።

    በምርቃቱ ሥነ ሥርዓት ላይ ማቴዎስ ሀብቴ (ዶ/ር) የዲላ ዩኒቨርስቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ተወካይ፤ ለተመራቂ ተማሪዎች፣ ለተመራቂ ወላጆች እንዲሁም ለተማሪዎቹ ለምረቃ መብቃት በተለያየ መልኩ ለተጉ ሁሉ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ዶ/ር ማቴዎስ አክለውም፥ “የዘንድሮ ተመራቂዎች ከትምህርት እና ፈተና ባለፈ በዓለምአቀፍ ደረጃ የተከሰተውን የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ያስከተለውን ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ሥነ-ልቦናዊ ጫናዎች ተቋቁማችሁ ለዚህ የበቃችሁ በመሆናችሁ በራሳችሁ ልትኮሩ ይገባል” ብለዋል።

    ተመራቂዎች ምንም እንኳ ከተቋሙ ተመርቀው ቢወጡም በዩኒቨርሲቲው አሉምናይ (alumni) በኩል ቤተሰባዊ ግንኙነቱ እንደሚቀጥል የገለፁት ዶ/ር ማቴዎስ፥ በቀጣይ ተመራቂዎች በሚሰማሩበት መስክ ሁሉ አምባሳደር ሁነው የዩኒቨርሲቲውን መልካም ስም እንዲያስቀጥሉ የአደራ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

    ከተመራቂዎቹ በሰሜን ኢትዮጵያ በነበረው ችግር በአክሱም ዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን ይከታተሉ የነበሩ ተማሪዎች እንደሚገኙበት የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) በዘገበው ዜና ገልጿል።

    የዩኒቨርሲቲው የሬጅስትራርና አሉምናይ ዳይሬክተር አቶ ኢሳያስ ይልማ በበኩላቸው፥ በበዕለቱ በድኅረ-ምረቃ መርሃ-ግብር 68 ወንድ እና ዘጠኝ (9) ሴት፤ በድምሩ 77፣ በመደበኛው መርሃ-ግብር በመጀመሪያ ዲግሪ 64 ወንድ እና 24 ሴት በድምሩ 88፣ በተከታታይ የትምህርት መርሃ-ግብር 117 ወንድ እና 30 ሴት፤ በድምሩ 147፣ በአጠቃላይ 249 ወንድ እና 63 ሴት፤ በድምሩ 312 ተመራቂዎች ለምርቃት መብቃታቸውን አብስረዋል።

    በዕለቱ የምርቃት ሥነ-ሥርዓት ከተመራቂ ተማሪዎች መካከል ከሕክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የሕክምና ትምህርት ክፍል ምሩቅ የሆነው ዶ/ር ብርሃን አዳነ አጠቃላይ ውጤት 3.86 ነጥብ በማስመዝገብ የወርቅ ሜዳሊያ ተሸላሚ ሆኗል።

    የማዕረግ ተመራቂው ዶ/ር ብርሃን አዳነ፥ “ከምንም በላይ ፈጣሪዬ ለዚህ ክብር እንድበቃ ስላደረገኝ ክብር ይግባው” ሲል በስኬቱ መደሰቱንና በትምህርቱ ላይ ትኩረት በማድረግ ጠንክሮ በመስራቱ በከፍተኛ ውጤት መመረቁን ጠቅሷል።

    ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ የድንቅ ኪነ-ሕንፃ ጥበብ ባለቤት መሆኗን የምትናገረው የሥነ-ሕንፃ ምህንድስና ትምህርት ክፍል ተመራቂዋ ተማሪ ሴና ኤቢሳ፥ ይሁንና ዘመናዊ ሕንፃዎች የኢትዮጵያን ባህልና ቀለም በማንጸባረቅ ረገድ ውስንነት እንዳለባቸው ተናግራለች። በቀጣይ በሥራ ሕይወቷ በግል ሆነ በቡድን ሀገር በቀል የሥነ-ሕንፃ ጥበብን ከዘመናዊው ጋር በማዋሃድ ኢትዮጵያዊ እሴቶችን ለማስተዋወቅ የድርሻዬን እወጣለሁ ብላለች ።

    የምርቃት ሥነ-ሥርዓቱ የሕክምና ተመራቂዎች ሙያዊ ቃለ-ምሃላ በመፈፀም የተጠናቀቀ ሲሆን፥ በሥነ-ሥርዓቱ የክብር እንግዶች፣ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራር አባላት እና የተመራቂ ቤተሰቦች ተገኝተዋል። የዲላ ዩኒቨርሲቲ የባህል ማዕከልም ልዩ ልዩ ጣዕመ ዜማዎችን በማቅረብ ዝግጅቱን አድምቆታል።

    ምንጭ፦ የዩኒቨርሲቲው ማኅበራዊ ድረ ገጽ

    Semonegna
    Keymaster

    ቦረና ዞን ውስጥ በተከሰተው ድርቅ ተጎጂ ለሆኑ ዜጎች የተሟላ ድጋፍ ለማድረግ በቅንጅት እየተሠራ ነው

    ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ቦረና ዞን በተከሰተው ድርቅ ተጎጂ ለሆኑ ዜጎች በሚፈለገው ደረጃ ድጋፍ ማሠራጨት የሚያስችል የቅንጅት ሥራ እየተሠራ መሆኑን የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ። እስካሁን ከ204 ሺህ በላይ ኩንታል እህል ለተጎጂ ዜጎች መሠራጨቱም ተጠቁሟል።

    የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ደበበ ዘውዴ ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት በቦረና ዞን በድርቅ አደጋ ጉዳት ከደረሰባቸው ዜጎች ውስጥ በ13 ወረዳዎች ውስጥ ለሚገኙ ወደ 604 ሺህ ለሚሆኑ ዜጎች የዕለት ድጋፍ ቀርቦላቸዋል። ካለፉት ሁለት ወራት በ15 ቀናት ውስጥም ለእነዚሁ ወገኖች 204 ሺህ 765 ኩንታል ምግብ ወደ አካባቢው ተልኮ ተሠራጭቷል። ከጉዳቱ አንጻርና የተጎጂዎች ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱ በመንግሥትና በአጋር አካላት ቀጣይ ድጋፍ ማድረግ የሚያስችል የቅንጅት ሥራ እየተሠራ ነው።

    እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ፥ ኮሚሽኑ በተለይ ለአደጋ ተጋላጭ ለሆኑ ሕፃናት፣ ነፍሰ ጡሮች፣ አጥቢ እናቶችና አቅመ ደካሞች የሚሆን 10 ኩንታል አልሚ ምግብ ወደ አካባቢው ተልኳል። ከዚህ በተጨማሪ የአካባቢው ሕብረተሰብ፣ ባለሀብቱ፣ ድጋፍ ሰጪዎችና መንግሥትም በዚሁ መልኩ ለወገኖች ሊደርስ የሚችለውን ድጋፍ እያቀረቡ ይገኛሉ።

    የኦሮሚያ ክልል 800ሺህ ለሚጠጉ ዜጎች የዕለት ድጋፍ መጠየቁን ገልጸው፥ በዚሁ ቁጥር ልክ ድጋፉ እንዲሰጥ ከአጋር አካላት ጋር አብሮ የሚሠራ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

    ድርቅን በሚመለከት በኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ አካባቢዎች ክስተቱ እንዳለ የገለጹት ዳይሬክተሩ፥ ክስተቱ በአንዳንድ ቦታዎች ላይ ጉዳት እያስከተለ ይገኛል ብለዋል።

    በኢትዮጵያ የተፈጥሮ አደጋዎች በሚያጋጥሙበት ጊዜም በሦስት አካላት ድጋፍ እንደሚደረግ ጠቁመው፤ እነዚህም መንግሥት፣ የዓለም ምግብ ፕሮግራም፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። እነዚህም በየአካባቢው ጉዳት ባጋጠመባቸው ስፍራዎች የየድርሻቸውን በመያዝ ምግብና ምግብ-ነክ ያልሆኑ ድጋፎችን ከክልል ጋር በመሆን ለሥርጭት እንዲበቃ ያደርጋሉ ነው ያሉት።

    እንዲህ ዓይነት ችግሮች በሚያጋጥሙበት ጊዜ እንደ ኢትዮጵያ አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን የማስተባበር ሥራን በመሥራት ከሌሎች ሴክተር መሥሪያ ቤቶችና ከክልሎች ጋር አብሮ የሚሠራባቸው ስልቶች እንዳሉ ዳይሬክተሩ አክለው ገልጸዋል። ከእነዚህ ሥራዎች ውስጥም በክልል ደረጃ የአስቸኳይ ጊዜ ማስተባበሪያ ማዕከል ማቋቋም አንዱ እንደሆነና በዞን ደረጃ ብዙ ቁጥር ያላቸው ወገኖች ጉዳት ሲደርስባቸው የአስቸኳይ ጊዜ ኮማንድ ፖስት እንደሚቋቋም ጠቅሰዋል።

    ይህም በክልል የሚመራና ኮሚሽኑ የሚደግፈው የጤና፣ የግብርና፣ የውሃ፣ የትምህርትና ሌሎች ጉዳዮች እንደመኖራቸው ሌሎች ሴክተር መሥሪያ ቤቶችን አስተባብሮ ማስኬድ የሚያስችል ድጋፍ በቅንጅት እየተሠራ እንዳለ አመላክተዋል።

    በዓለም አቀፍ ደረጃ ባሉ ሁኔታዎች ምክንያት በአጋር አካላት የሚደርሰው ድጋፍ ላይ ተጽዕኖ ሊያሳርፉ ይችላሉ ያሉት ዳይሬክተሩ፥ የተበታተነውን ሁኔታ መሰበሰብ የሚያስችል ከሀገር ቤት እስከ ውጭ ያሉ አካላት የሚሳተፉበት ተግባራትም እንዳሉ ጠቁመዋል።

    አምባሳደር ዶክተር ሽፈራው ተክለማርያምን ጨምሮ በየቢሯቸው በመገኘት አጋር አካላትን፣ ኤምባሲዎችን፣ የመንግሥታቱ ኅብረት ተወካዮችን እያነጋገሩ እንዳለ ገልጸዋል። በዚህ መልክ ድጋፉ እንዲጠናከር ይደረጋል ሲሉም አስታውቀዋል።

    ዳይሬክተሩ እንዳሉት፥ በሀገሪቷ ድርቅና ሌሎች ተዛማች ችግሮች አሉ። በመሆኑም እነዚህን ችግሮች ለመቋቋም ከሀገር ውስጥ አቅም ባሻገር የአጋር አካላት አስተዋጽኦ ወሳኝ ነው። ለዚህም አጋር አካላት የራሳቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ ጥረት እየተደረገ ነው። በአሁኑ ወቅትም ድጋፉ እየመጣ ነው፤ ለዚህም በሚፈለገው ደረጃ ማሠራጨት የሚያስችል የቅንጅት ሥራ እየተሠራ ነው።

    ከመንግሥት እንቅስቃሴ በተጨማሪ የተለያዩ ኢትዮጵያውያን እና ኢትዮጵያዊ ተቋማት ቦረና ዞን ውስጥ በተከሰተው ድርቅ ለተጎዱ ወገኖች በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገር የተለያዩ እርዳታዎችን እያሰባሰቡ ይገኛሉ። እርስዎም በዚህ ድጋፍ ለመሳተፍ የሚከተሉትን ማስፈንጠሪያዎች ይጫኑ።

    1. ዓለም አቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያውያን መብት (GARE) በጎፈንድሚ (GoFundMe) በኩል፦ GARE4Borena
    2. በሀገር ውስጥ ደግሞ የጉዞ አድዋ ማኅበር አስተባባሪ ያሬድ ሹመቴ (Yared Shumete) እና መምህር ታዬ ቦጋለ አረጋ “ዓድዋ 127 ለቦረና” በሚል እንቅስቃሴ በመጀመር የተለያዩ ድጋፎችን (ገንዘብ፣ የምግብ ምርቶችን፣ ወዘተ) እያሰባሰቡ ነው። ያግኟቸው፦ http://www.facebook.com/shumeteyared እና http://www.facebook.com/tayebogale.arega

    Semonegna
    Keymaster

    መርገምት፤ ግንድ ግንዱን መገርሰስ
    (ያሬድ ኃይለማርያም)

    በዘመነ ወያኔ የጀመረው ሀገራዊ ክሽፈት በብዙ እጥፍ አቅሙንና ፍጥነቱን ጨምሮ ኢትዮጵያን ቁልቁል እየነዳት እንደሆነ የቅርቡ በእስልምና እምነት ላይ አነጣጥሮ የነበረው ደባና ክፍፍል ጋብ ሲል በሰሞኑ ቆብ ያጠለቁ ነውረኞች ድራማ መተካቱ ጥሩ ማሳያ ነው። ወያኔ ስልጣን ከያዘች ጀምሮ ካደረገችው በርካታ ኢትዮጵያን የማዳከም እኩይ ሥራዎች መካከል የሀገሪቱን እድሜ ጠገብ ተቋማት ማፈራረስ፣ ሕዝቧን ያስተሳሰሩ ማኅበራዊ መስተጋብሮችን መበጣጠስ፣ እድሜ ጠገብ ሀገራዊ ትውፊቶችን ማራከስ እና በማኅበረሰቡ ዘንድ ትልቅ ክብርና ሞገስ ያላቸውን አውራዎች ማዋረድ፣ ማሸማቀቅ እና ሕዝብ እንዲንቃቸው ማድረግ ነበር። በወቅቱ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም ‘ወያኔ ግንድ ግንዱን እየገነደሰች ነው’ ብለው ነበር።

    አንጋፋ የሙያ ማኅበራትን አፍርሶ በተለጣፊ ካድሬዎች መተካት፣ ዓለም ያከበራቸው ምሁራንን በአደባባይ መዝለፍና ማዋረድ፣ ማሰርና ማዋከብ፣ የሀይማኖት ተቋማትን አናታቸውን ጨምድዶ በመያዝ የአፈናው መዋቅር አካል ማድረግና የፖለቲካ ምርኩዝ አድርጎ ምዕመናኑን ለማሸማቀቂያነት መጠቀም፣ ታሪክን በተዛባ ትርክት መቀየርና ጥራዝ-ነጠቅ ትውልድ መፍጠር የተሳካው የወያኔ ትልም ነበር። አንጋፋውን የመምህራን ማኅበር፣ የሠራተኞች ኮንፌደሬሽን፣ የነጻ ጋዜጠኞች ማኅበር እና አከርካሪያቸው ተመትቶ በካድሬዎችና በፖለቲካ ተሻሚዎች እጅ የወደቁትን የትምህርት ተቋማትና የጏይማኖት ቤቶችን ሁኔታ ልብ ይለዋል።

    ይሄ ኢትዮጵያን ለማዋረድ፣ ታሪኳን ለማዛባት፣ ነጻና ጠንካራ ተቋም የሌላት ደካማ ሀገር እንድትሆን እና አዲስ የታሪክ ድርሳን ለመጻፍ በወያኔ የተጀመረው ግንድ ግንዱን የመደርመስ እኩይ ተግባር ዛሬም ወያኔ ባሰለጠነቻቸው መንደርተኛ ካድሬዎች አፍጥጦና አግጥጦ መምጣቱ፣ ምናልባትም እጅግ በከፋና አስፈሪ በሆነ መልኩ መከሰቱ ማንኛውንም ጤነኛና ቅን አሳቢ ኢትዮጵያዊ ሁሉ እንቅልፍ የነሳው ጉዳይ ይመስለኛል።

    ወያኔ ከርክማና ኮትኩታ ያሰለጠነቻቸው የትላንት ጨቅላ ካድሬዎች፣ የዛሬ ሀገር መሪዎች በሰለጠኑበት መንገድ ኢትዮጵያን አውራ ግለስብ እና አውራ ተቋማት የማሳጣት የክሽፈት ምሪታቸውን ምንም ሳይሳቀቁና ያለ ምንም አፍረት ቀጥለውበታል። ኢትዮጵያ ዛሬ ማባሪያ በሌለው በመከራዎች ናዳ ከግራ ቀኝ እየተወገረች ነው።

    ባሳለፍነው ሳምንት እንኳ አጣዬና አካባቢዋ በዘር ፖለቲካ በተመረዙ አክራሪዎች በእሳት ቶን ውስጥ ሲለበለቡና ጥይት ሲያጓራባቸው፤ በተመሳሳይ ቀናት የብዙ ዘመናት ታሪክ ያላትና የጽናት ተምሳሌት የሆነችው ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከጉያዋ በወጡ ባለቆብ ካድሬዎች ስትናጥ ከረመች። ለእኔ አጣዬ ለስንተኛ ጊዜ የተከሰተው በአክራሪ ታጣቂዎች ጥቃት ስር ውላ ለቀናት በእሳት መንደድና የቤተክርስቲያን በተመሳሳይ ጊዜ የተኩላ ለምድ በለበሱ ሰዎች በነገር እሳት መለብለብ ውላቸውም ሆነ ምንጫቸው አንድና አንድ ብቻ ነው። ሀገራዊ የፖለቲካ ክሽፈት ያስከተላቸው ችግሮች ናቸው። መዳረሻ ግባቸውም እንዲሁ አንድ ነው። አክተሮቹም ግብራቸው ቢለያይም፣ ውሏቸውና የተሰማሩበት ግንባር ቢራራቅም ከጀርባ ሆነው ነገሩን ለሚያቀነባብሩትና ለሚመሩት ሰዎች ግን አንድ ግብና አንድ መዳረሻ ነው ያላቸው፤ ኢትዮጵያን ለማፍረስ ግንድ ግንዱን የመገርሰስ ስልቶች አካል ናቸው። ባጭሩ ኢትዮጵያን አዳክሞ የዛሬ ክልሎችን የነገ ራስ-ገዝ ሀገር የማድረግ ጭንጋፍ የሆነ የፖለቲካ ንድፍ ማሳለጫዎች ናቸው።

    እስኪ በዚህ 30 ዓመት ኢትዮጵያ ውስጥ ያልተዋከበ፣ ያልተዋረደ፣ ክብሩ ያልተገፈፈ፣ በካድሬዎች ጭንጋፍ እሳቤ ያልተጨናገፈ፣ ያልተዘረፈ ተቋም ጥሩልኝ? በጭንጋፍ እሳቤ ሀገር የማጨንገፉ እኩይ ሥራ በብዙ መልኩ ለመሳካቱ የዛሬዋ ኢትዮጵያ ጥሩ ምስክር ነች። እስኪ እንደ ሕዝብና እንደ ሀገር ያልከሸፍንበትን ጎናችንን ንገሩኝ? በትምህርት ጥራት መቀመቅ መውረዳችንን የትምህርት ሚኒስትሩ ትላንት የ12ኛ ክፍል ተማሪዎችን ውጤት ሲናገሩ አብረው አርድተውናል፤ የሀይማኖት ተቋማቶቻችን የጨነገፉ ካድሬዎች መፈንጫ ከሆኑ ዘመናት ተቆጥሯል፤ አንጋፋ የሚባሉ ተቋማትች ገሚሱ ፈርሰዋል፤ የተቀሩት ካለመኖር ባልተሻለ ሁኔታ ተዳክመዋል፤ ለሀገር ትልቅ አስተዋጽዖ ያበረከቱ ምሁራን ከነመኖራቸው ተረስተዋል፤ ምሁራኖቹ ያደራጇቸው የትምህርት ተቋማት ከሳይንሳዊ ምርምር ይልቅ የብሔር ፖለቲካ ሰለባ ሆነዋል፤ የሀገር ባለውለታ የሆኑ አውራዎች ለበጎ ሥራቸው የስድብና የጥላሸት ካባ በላያቸው ተደፍቶ እንዲሸማቀቁ ተደርጓል።

    ዛሬ መከራው በብዙ እጥፍ ቢበረታም ቢያንስ ቁጭ ብለን የሃፍረት፣ የክሽፈት፣ የስጋትና የምሬት እንቆቋችንን እየተጎነጨን የምንቆዝምበት ምርጥ ምርጥ ፖርኮች ተሠርተውልናል። አንድነት በሌላት ሀገር ውስጥ በአንድነት ፖርክ ውስጥ ቁጭ ብለን ለምን አንድነት እንዳጣን ማሰላሰል እንችላለን።

    ለማንኛውም ሀገርን አውራ በማሳጣትና ግንድ ግንዱን እየገነደሱ በደረቅ ጭራሮ ሀገርን ለማቆምና ለማጽናት እንደማይቻል የመጣንበት ረዥም እርቀት ጥሩ ማሳያ ነው። ጭራሮ ተሰብስቦ ቢታሰር እንኳ ችቦ ይሆናል እንጂ ግንድ ሊሆን አይችልም። ሀገር የሚጸናው በጠንካራ ተቋማት፣ በደፋርና እውነተኛ ምሁራን እና ቅን አሳቢና በጎ ራዕይ ባነገቡ የፖለቲካ ልሂቃን ነው። ፖለቲከኛውም፣ ቄሱም፣ ሼሁም፣ ምሁሩም፣ ተማሪውም እኩል በከሸፉበት ሀገር ግን አውራና ግንድ አይኖርም። ጭራሮ ብቻ እንጂ። አውራ ያጣ ሕዝብ ቀፎው ጠፍቶበት እንደተበተነ የንብ መንጋ ነው። ለራሱም ለሌላም ስጋት ነው። ወደ ቀልባችን ቶሎ ተመልሰን አውራዎቻችንን ከፊት ካላስቀደምን፣ ሀገር ጸንታ እንድትቆም ግንድ የሆኑንን ተቋማትና ግለሰቦች ጨርሰው ሳይጠፉ ካልደገፍናቸው እና ሁሉን ነገር ለጭራሮዎች ከተውን እንደ ሀገርም፣ እንደ ሕዝብም ተረት የምንሆንበት ዘመን እሩቅ አይሆንም።

    ያሬድ ኃይለማርያም

    Semonegna
    Keymaster

    በሚደረገው ሀገራዊ ምክክር ዜጎች በንቃት እንዲሳተፉ በቂ አትኩሮት ይሰጠው!
    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተላለፈ ወቅታዊ መልዕክት

    በሀገራችን ኢትዮጵያ በየዘመኑ የነበሩትን፣ ከፖለቲካው ሥርዓት የሚመነጩ ችግሮችን ለመፍታት እና ወደተሻለ ሀገራዊ ሁኔታ ለመሸጋገር የሚያስችል ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለማንበር እቅስቃሴ ማድረግ ከተጀመረ ከሃምሳ ዓመታት በላይ ተቆጥረዋል።

    እነዚህ እንቅስቃሴዎች የሥርዓት ለውጥ ከማምጣት ተሻግረው የዴሞክራሲን ፍሬ ከማፍራት ይልቅ ሀገራዊ ችግሮቻችንን በአይነትና በብዛት እየጨመሩ እና እየተወሰሳሰቡ እንዲመጡ በማድረግ ዛሬ ላይ የኢትዮጵያችን ህልውና እና ቀጣይነት ላይ ከፍተኛ አደጋ ለመደቀን በቅተዋል።

    ምንም እንኳ ሌሎች ዘርፈ ብዙ ችግሮች ቢኖሩም፤ የኢትዮጵያ ህልውና ላይ የተደቀነው አደጋ በዋነኛነት የሚመነጨው፣ ከሀገራዊ የፖለቲካ ሥርዓቱ ነው። ሀገራዊ የፖለቲካ ሥርዓቱ በተለያዩ ፍላጎቶች፣ ጥቅሞች፣ ስሜቶች፣ ተስፋዎች እና ስጋቶች በመወጠሩ፤ እርስ በእርስ አለመተማመን፣ ሰላም ማጣት፣ መፈናቀል፣ አለመረጋጋት . . . ወዘተ ተፈጥሮ መዋቅራዊ ቅራኔ ውስጥ እየዳከርን መገኘታችን የአደባባይ ሀቅ ነው።

    ይህ አደገኛ ሀገራዊ ሁኔታ ሳይረፍድ እና ነገሮች ከቁጥጥር ውጪ ከመውጣታቸው በፊት በጋራ አንድ መፍትሔ ካልተበጀለት፤ እርስ በእርሳቸው እየተሳሳቡ ጫፍ እና ጫፍ የቆሙትን የተለያዩ ፍላጎቶች፣ ጥቅሞች፤ ስሜቶች፤ ቡድኖች እና ድርጅቶች በሙሉ ጠራርጎ፣ ማንኛችንም አሸናፊ ወደማንሆንበት ምድራዊ ሲኦል ውስጥ የመግባት እድል እንዳለን መገንዘብ ይኖርብናል።

    ይህንን ሁላችንም ላይ የተደቀነ ሀገራዊ አደጋ ለማስወገድ፣ ባለፉት ሃምሳ ዓመታት በተለይ በፖለቲካው ሂደት ውስጥ ከተሞከሩት እንዲሁም ሀገራዊ ሁኔታውን ከማባባስ እና ከማወሳሰብ ይልቅ ምንም አይነት መፍትሔ መስጠት ካልቻሉት የፖለቲካ አካሄዶች ውጭ ባለ ሂደት፣ መፍትሔ የማፈላለጉ ጥረት አማራጭ የሌለው አካሄድ መሆኑን መቀበል ያስፈልጋል።

    ሀገራዊ ምክክር ያስፈለገውም የሀገራችን አንኳር ችግሮች በመደበኛው የችግር አፈታት ሂደት መፍትሔ ማግኘት በማይቻልበት ደረጃ በመድረሳቸው እና በመቀጠልም፣ የበለጠ እየገዘፉና እየተወሳሰቡ ሄደው ሀገርን የማፍረስ ደረጃ ከመድረሳቸው በፊት ሀገርን ለማዳን እንዲያስችል ነው።

    በኢትዮጵያ ከአንድ ዓመት በፊት ኮሚሽን ተቋቁሞ የተጀመረውን የሀገራዊ ምክክር ሂደት በተመለከተ አሁን በደረስንበት ደረጃ ዋናው ጉዳይ መሆን ያለበት በሀገራችን ህልውና እና ቀጣይነቷ ላይ ያንዣበበውን አደጋ ለአንዴም ለሁሌም እንዲወገድ ማድረግ ነው። ለዚህ ሊረዳን የሚችል ስምምነት ላይ ለመድረስ ደግሞ በምክክሩ ላይ የሚሳተፉ ባለድርሻ አካላትን በሂደቱ ላይ በቀናነት እንዲሳተፉ የማሳመን ሥራ በስፋት ሊከናወን ይገባል።

    የሀገራዊ ምክክሩ ቁልፍና ወሳኝ ባለድርሻዎች ምክክሩን ለመቀበል እና እንዲነቃቁ ለማድረግ፣ በመጀመሪያ መደረግ ያለበት፣ በሀገራዊ ምክክር ምንነትና እና በሀገራችን ሁኔታ ያለውን አስፈላጊነት አስመልክቶ ግልጽ የሆነ አረዳድ እንዲኖር ምቹ ሁኔታ በመፍጠር የተለያዩ ባለድርሻዎች ወሳኝ ሚና እንዳላቸው ማሳየት ነው።

    ሀገራዊ ምክክር በመደበኛ አሰራሮች ሊፈቱ የማይችሉ መዋቅራዊና ጊዜያዊ ቅራኔዎችን በሰላማዊ መንገድ ተነጋግሮ ለመፍታት የሚያስችል በመሆኑ፤ ዘርፈ ብዙ ጥቅም አለው። ሀገራዊ ምክክር በአግባቡ ከተጠቀምንበት ልዩነቶችን በማስታረቅ ሀገራዊ የፖለቲካ ቀውስን ለማስቀረት፤ ፖለቲካዊ አጣብቂኞችን ሰብሮ ለመውጣት እና ውጥረትን ለማርገብ፤ በትጥቅ የታገዘ አመፅ እንዳይፈጠር አስቀድሞ ለመከላከል ያስችላል። በተጨማሪም፤ ብሔራዊ መግባባትን በመፍጠር ከዚህ ቀደም ለተፈፀሙ በደሎች እና ወንጀሎች እንዲሁም የፍትህ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ይረዳል። በውጤቱም ከተፈጠሩ ፖለቲካዊ ቀውሶች ፈጥኖ በማስወጣት በመንግሥት እና በሕዝብ መካከል መተማመንን ይፈጥራል። በፖለቲካዊ ሥርዓቱ ላይ ጥያቄ ለሚያነሱ አካላትም በሀገራዊ ምክክር ላይ በመሳተፋቸው በሀገር ጉዳይ ላይ የባለቤትነት ስሜትን በማጎልበት ልዩነቶችን በሰላማዊ ውይይት የመፍታት ባህል በማዳበር እንዲሁም ሀገራዊ ቀጣይነት እና መረጋጋትን በማረጋገጥ፤ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መደላድሎችን ይፈጥራል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ከዚህ ቀደም በተለያየ መልኩ ሲገልፅ እንደቆየው፤ ሀገራዊ ምክክሩ በዚህ ወቅት ለአጠቃላይ ማህበረሰባዊ ደህንነታችን የሚኖረው አስተዋፅዖ ከፍተኛ ስለሆነ የቅድሚያ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ሀገራዊ አጀንዳ ነው። ነገር ግን የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ለዚህ ሀገራዊ ክንውን እየሰጡት ያለው ትኩረት በጣም አነስተኛ መሆኑ ፓርቲያችንን በእጅጉ አሳስቦታል።

    ከሁሉም በላይ መንግሥት ለሀገራዊ ምክክሩ ስኬታማነት ብዙ እርቀት ተጉዞ አስተዋፅዖ ማድረግ ሲጠበቅበት፤ በምክክሩ ላይ ሊፈቱ የሚገባቸውን ጉዳዮች አስቀድሞ በመወሰን እንዲሁም ግጭቶች እንዲቀንሱ በትጋት ከመስራት ይልቅ በመንግሥታዊ መዋቅሮች ያልተገባ ውሳኔ ምክንያት ተጨማሪ ግጭቶች እየተፈጠሩ መሄዳቸው እንድንሰጋ አድርጎናል። በኢዜማ እምነት መንግሥት አስተባባሪ እንጂ አፍራሽ፤ ጠቃሚ እንጂ ጎጂ፤ ጠንካራ እንጂ ልፍስፍስ፤ ሕግ አስከባሪ እንጂ ሕግ የሚጥስ ሆኖ መገኘት የለበትም። በመንግሥት በኩል የሚከናወኑ አፍራሽ አካሄዶች አደጋቸው ለሁላችንም ነውና ሊወገዱ ይገባል።

    መንግሥት የሀገራዊ ምክክሩን ሂደት የሚያበላሹ ተግባራትን ማከናወኑ እንዲሁም የምክክሩን ሂደት ውጤታማነት ለማረጋገጥ የሚጠበቅበትን ሚና በአግባቡ እስካሁን አለመወጣቱ ትክክል እንዳልሆነ መረዳት ይጠበቅበታል። ለአብነትም፤ ኢዜማ ከዚህ ቀደም ባወጣቸው መግለጫዎች ላይ እንደገለፀው መንግሥት መግባባት ላይ ያልተደረሰባቸውን ሀገራዊ የፖሊሲ ጉዳዮች፤ የሕገ-መንግሥት አንቀፆች፤ አዋጆች እና ሌሎች ውሳኔዎችን ከሀገራዊ ምክክሩ አስቀድሞ መወሰኑ የምክክር ኮሚሽኑን በማቋቋም ያሳየውን በጎ ተስፋ የሚያጨልም ነው።

    ከመንግሥት በተጨማሪም የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ ልሂቃን፤ የሙያ ማኅበራት፤ የሲቪክ ማኅበራት፤ መገናኛ ብዙሃን፤ የሃይማኖት ተቋማት እና ሰፊው ሕዝብ እስካሁን ባለው ሂደት ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚጠበቅባቸውን ሚና በአግባቡ አልተወጡም። ሀገራዊ ምክክር ለተወሰኑ ግለሰቦች ወይም ተቋማት ብቻ የሚተው ሳይሆን የእያንዳንዱን ኢትዮጵያዊ የነገ ህልውና፤ ደህንነት፤ ሰላም፤ ልማት እና ተጠቃሚነት የሚወስን ጉዳይ መሆኑን አለመገንዘብ ሁላችንንም ለውድቀት የሚዳርግ መሆኑን ማሰብ ያስፈልጋል። በሀገር ዕጣፈንታ ላይ የሚወሰንበትን ክንውን ትኩረት አለመስጠት ማኅበራዊ ኪሳራ እንደሆነ እያንዳንዱ ዜጋ ማወቅ አለበት።

    ፓርቲያችን ኢዜማ ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት እንዲሁም መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከፍተኛ ትኩረት እንድትሰጡት እያሳሰበ የሚከተሉት ምክረ ሃሳቦች ተግባራዊ ሊደረጉ ይገባል ብሎ ያምናል።

    1. መንግሥት የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ሊሠራ የሚችላቸውን መሠረታዊ ጉዳዮች በተደጋጋሚ ተላልፎ ምክክሩ ላይ ጫና መፍጠሩን በአስቸካይ እንዲያቆም፤ እንዲሁም ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚጠበቅበትን መንግሥታዊ ሐላፊነት በአግባቡ እንዲወጣ፤
    2. ምክክር ኮሚሽኑ ለዜጎች መድረስ ያለባቸው መረጃዎች በአግባቡ መድረሳቸውን እና በመገናኛ ብዙሃን ላይ ተገቢው ትኩረት እንዲሰጣቸው ማድረግ ላይ በአትኩሮት እንዲሰራ ብሎም ክንውኖቹን፤ እቅዶቹን እና የሀገራዊ ምክክሩን አስፈላጊነት በተመለከተ በመገናኛ ብዙሃን እየቀረበ በአግባቡ መልዕክቶችን ለማኅበረሰቡ ወቅቱን ጠብቆ እንዲያደርስ ራሱን የቻለ የአየር ሰዓት እንዲመደብለት
    3. የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ እምባ ጠባቂ ተቋም እና ምርጫ ቦርድ እንዲሁም ሌሎች የዴሞክራሲ ተቋማት እየሠሩት ያለውን ጅምር በጎ ሥራ ምሳሌ በማድረግ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ በተሰጠው ስልጣን ልክ ተግባሩንና ታማኝነቱን ለኢትዮጵያ ህዝብ ብቻ እንዲያደርግ፤ በኮሚሽኑ ውስጥ የሚያገለግሉ ግለሰቦችም ታማኝነታቸውን ለህሊናቸው እንዲያደርጉ
    4. የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ ልሂቃን፤ የሙያ ማኅበራት፤ የሲቪክ ማኅበራት፤ መገናኛ ብዙሃን፤ የሃይማኖት ተቋማት እና ሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚጠበቅባቸውን ሚና በአዎንታዊነት እንዲወጡ እንዲሁም በጉዳዩ ላይ በንቃት እንዲሳተፉ።

    በአጠቃላይ፤ ሀገራዊ ምክክር እንደስሙ ሀገራዊ መሆን አለበት። ዜጎች በሀገራቸው ጉዳይ ላይ ያለምንም ተጽዕኖ እንዲሳተፍ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተገቢውን ሚና መወጣት ይጠበቅባቸዋል። እንደ ሀገር ያሉንን ልዩነቶች ለማስታረቅ ሁላችንም ከልባችን በእውነተኛነት መስራት አለብን። በጋራ ለአደጋ እንደተጋለጥነው ሁሉ፤ አደጋውንም በጋራ ለመጋፈጥና በጋራ ለመወጣት መትጋት ይጠበቅብናል። በኢዜማ በኩል የሀገራዊ ምክክር አስተባባሪ ኮሚቴ በማቋቋም አባላትን እንዲሁም ማኅበረሰቡን ለማንቃት የሚችለውን ሁሉ እያከናወነ ሲሆን፤ በቀጣይም ለሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማነት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ ማረጋገጥ ይወዳል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
    ጥር 02 ቀን፥ 2015 ዓ.ም.

    Semonegna
    Keymaster

    ከኢትዮጵያ ዳያስፖራ የተግባር ምክር ቤት የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ተገዳ የገባችበትን የህልውና ጦርነት በጋራ ለመመከት በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊን ከሕዝባቸው ጎን በቆራጥነት በመቆም የሀገርን ሉአላዊነት ለማስከበር በሚደረገው ዘመቻ የዜግነት ግዴታቸውን እንዲወጡ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

    ይህ የህልውና ጦርነት በውጭ ሀገር የምንገኘውን ኢትዮጵያውያን እንቅልፍ የነሳና ሀገራችን እንደ ሀገር እንዳትቀጥል በወያኔ ጁንታ ቡድን፣ በአልሸባብ፣ እና በሸኔ እንዲሁም በውጭ ሀገር የሚገኙ የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች በቅንጅት የከፈቱብን ጦርነት ብሔራዊ ክብራችንና የሚነካ የሀገራችንን ሰላም የሚያውክ በመሆኑ በእጅጉ አሳስቦናል።

    ስለዚህ መንግሥት በሆደ ሰፊነት ቀደም ሲል የወሰዳቸውን ቁርጠኛ የሰላም ፍላጎቶቹን በማድነቅ የሰላም ድርድሩ ውጤታማ እንዲሆን ሙሉ ድጋፍ ስንሰጥ መቆየታችን እንደተጠበቀ ሆኖ፤ በአሸባሪነት የተፈረጀቱ ፀረ-ሰላም ኃይሎች ከሰላም ይልቅ ጦርነትንና እልቂትን መርጠው የከፈቱብንን የአጥፍቶ መጥፋት ጦርነትን በጥብቅ አውግዘን መንግሥት እየወሰደ ያለውን እርምጃ እንደግፋለን።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ የተግባር ምክር ቤት የአሸባሪውን ጁንታ ቡድን እንዲሁም አልሸባብና ሸኔን ማውገዝ ብቻ ሳይሆን ለሀገር ሕልውናና ለሕዝባችን ሰላምና ጥቅም ስንል ከመንግሥትና እንዲሁም ከመከለከያ ሠራዊታች ጎን በመቆም የዜግነት ድርሻችንን ለመወጣት የትግባር ምክር ቤቱ ዝግጁ መሆናችንን እናረጋግጣለን።

    በእርግጥ ዲያስፖራው ዛሬም ነገም ለሀገሩ ለወገኑ ድጋፉን አጠናክሮ እንደቀጠለ ቢሆንም በሀገራችን ውስጥ በተፈጠረው ሀገር የማዳን ዘመቻ በዘር፣ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ እምነት ሳንከፋፈል ከስሜታዊነትና ከኩሪፊያ በመውጣት ለነገዋ ኢትዮጵያ የተሻለ ነገር ለማምጣት፣ የተሻለችውን ኢትዮጵያ ለማየት ትግሉን የሚጠይቀውን ማንኛውንም ድጋፉ እንድናደርግ ምክር ቤታችን በድጋሚ በመላው ዓለም ለሚገኙ የኢትዮጵያዊያንና ለኢትዮጵያ ወዳጆች ሁሉ ጥሪ ያቀርባል።

    መንግሥት ኢትዮጵያን ወደ ተሻለ ከፍታ ለማድረስ፣ ችግሮችን በውይይት በመፍታት፣ ዘላቂ ሰላምን ለማምጣት፣ የሀገራችንን ፖለቲካ ለማዘመን፣ ውስጣዊ ችግሮቻችን በተገቢው መንገድ ለመፍታት ግጭቶችና የጦርነትን ውድመት እንዳይቀጥል በቁርጠኝነት ተነሳስቶ ለሀገረ መንግሥት ግንባታው መሠረት ለመጣል ፖለቲካዊ ችግሮችን በአግባቡ ፈትሾ ሁሉን አቀፍ ውይይትና ድርድር ማድረግ፤ በሀገሪቱ ምክር ቤት በአሸባሪነት የተፈረጁትን ቡድኖች ወደ ዘላቂ ሰላም የጠረንጴዛ ድርድር እንዲቀመጡ ወስዶት የነበረውን የሰላም ጥረት አሁንም ወደፊትም እንዲቀጥል ምክር ቤታችን መደገፉን ይቀጥላል።

    ነገር ግን ከጦርነት በተሻለ ሰላምን መምረጥ ትርፋማነቱ ቢያዋጣም አሸባሪውና ጎጠኛው የጁንታው ቡድን የአማራና አፋርን ሕዝብ በመውረር የትግራይን ሕዝብ አግተው በሰላማዊ ሕዝብና በመሠረተዊ የልማት ተቋማት ላይ ያደረሱትን መጠነ ሰፊ ውድመት መልሰን ለማቋቋም እርብርብ በምናደርግበት ወቅት የሀገርን ሉአላዊነት አደጋ ላይ ለመጣል ለሦስተኛ ዙር የተከፈተብን ታሪክ ይቅር የማይለው ጦርነት በእጅጉ አስቆጥቶናል። ስለዚህ፦

    1ኛ የአማራና የአፋር ክልልን በመውረር ሲዋጉና አመራር ሲሰጡ የነበሩትን እንዲሁም እድሚያቸው ለውትድርና ሞያ ያልደረሱ የትግራይ ህፃናትን በመመልመል ለጦርነት ያሰልፉትን የወያኔ ጁንታ አመራሮች ተለይተው በጦር ወንጀለኝነትና በሀገር ክህደት ክስ ተመሥርቶባቸው በአስቸኳይ ለፍርድ እንዲቀርቡ መንግሥትን እንጠይቃለን።

    2ኛ ሀገራችን በገጠማት የሰላም ማጣት ችግርና ተገዳ ከገባችበት የህልውና ጦርነት በተጨማሪ የሕዝብ ሞትና የሥነ ልቦና ጉዳት ሊያስከትሉ የሚችሉ የሐሀት ቅስቀሳና የፕሮፖጋንዳ ዘመቻ በሚያደርጉ ቅጥረኛ ሚዲያዎች፣ አለአግባብ ለመበልፀግ የኢኮኖሚ አሻጥር በሚፈፅሙ ነጋዴዎች፣ በተለይ የመንግሥት ሙሰኞችና ሌቦች ላይ ያለምንምንም ይቅርታ ጠንካራ እርምጃ መንግሥት እንዲወስድ እናሳስባለን።

    3ኛ መንግሥት የሚቻለው ሁሉ ጥረት በማድረግ ለሀገር ጠቀሜታ ሲል ዘላቂ መፍትሔ የሚያመጡ አካሄዶችና አዳዲስ ስልቶችን (strategies) መንደፍ አለበት። በተለይ ከዲያስፖራው ማኅበረሰብ ጋር እጅ ለእጅ ተያይዞ በጋራ የዓለም አቀፉን ሕብረተሰብ በተሳሳተ ፕሮፖጋንዳ የሚያውኩትን የሚዲያ ተቋማትን ተጠያቂ ለማድረግ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ለድፕሎማቶቹን ጥብቅ መመሪያ እንዲሰጥና ለተግባራዊነቱም ልዩ ክትትል እንዲያደርግ በጥብቅ እናሳስባለን።

    በመጨረሻም ምክር ቤቱ ወደፊት ከሚያደርጋቸው የድጅታል ዲፕሎማሲ ትግል በተጨማሪ ጦርነቱን በአጭር ጊዜ ለመጨረስ በሚደረገው የህልውና ጦርነት የዘማቹ ሠራዊት ደጀን በመሆን ጠንካራ ድጋፍ ለመስጠት ዝግጁ መሆናችንን ለኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት እናረጋግጣለን።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ የተግባር ምክር ቤት (ኢዳተም)

    Semonegna
    Keymaster

    የአማራን ሕዝብ ሰቆቃ እያየ እንዳለየ፣ እየሰማ እንዳልሰማ…
    ጋዜጠኛ አበበ ገላው

    የአማራ ሕዝብ በደለኝ የሚል ካለ ማስረጃውን ይዞ ይቅረብ። አንድም ሰው አይገኝም። የኦሮሞም ይሁን የትግራይ፣ የአፋርም ሕዝብ ይሁን የሲዳማ፣ የጋምቤላም ይሁን የሶማሌ፣ የጉራጌም ይሁን የወላይታ ሕዝብ… ፈጽሞ ማንንም በድለው አያውቁም። የትኛውም ሕዝብ በጅምላ ግለሰቦችንም ይሁን ቡድኖችን ሊበድል ፈጽሞ አይችልም። ስለዚህም ነው በዓለማችን ላይ እጅግ አሰቃቂው ግፍ በተፈጸመበት አውሮፓ ናዚዎች ለፈጸሙት ወንጀል ተጠያቂ አድርጎ ጀርመኖችን እያደነ የሚገድልና የሚያፈናቅል ቡድን ኖሮ አያውቅም። በእኛም ሀገር ሞሶሎኒ በመርዝ ጋዝ ሳይቀር ለፈጸመው ግፍ ንጹኃን የጣሊያን ዜጎችን አሳደንም ይሁን ጨፍጭፈን አናውቅም። እንዲህ ዓይነቱን አስነዋሪ ወንጀል ብንሞክረውም ግፍ እንጂ ፍትሃዊ ሊሆን ፈጽሞ አይችልም።

    በእኛ ሀገር በክፋት ህወሓት በዋነኛነት ከፋፍሎ ለመግዛት እንዲያመቸው መዋቅርና ቅርጽ የሰጠውን ተረት በማንገብ በጥንታዊ ነገሥታትና መንግሥታት ለተፈጸሙ በደሎች መላውን የአማራ ሕዝብ በነፍጠኛነት ፈርጆ ከምንም የሌሉበትን ምሲኪን ድሆች በጅምላ መግደል፣ ማሳደድ፣ ማፈናቀል፣ አፍኖ መውሰድ፣ አካላዊና ስለልቦናዊ ጥቃት መሰንዘር የተለመደ ክስተት ከሆነ አርባ አመታት ተቆጥረዋል። አብዛኛው የአማራ ተወላጅ ሀገሩ እንዳይፈርስ፣ ሕዝብ ለበቀል እንዳይነሳ እና ማለቂያ የሌለው እልቂትና ውድመት እንዳይደርስ በሚል የአስተዋይነት መንፈስና ባህል የሆዱን በሆዱ ይዞ በትዕግስት ህመሙን እና ሀዘኑን አፍኖ በኢትዮጵያዊነት ጨዋነት ከየትኛውም ኢትዮጵያዊ ወገኑ ጋር ተቻችሎና ተከባብሮ ለመኖር የሚቻለውን ሁሉ አድርጓል።

    ይሁንና አሳዛኙ ሃቅ የሕዝቡን ትዕግስት እንደ ፍርሃት የቆጠሩ እኩይ ኃይሎች የአማራን ሕዝብ በጅምላ ዘውትር ከማሸማቀቅ አልፈው የጅምላ ጭፍጨፋ፣ ግፍና ማፈናቀል ያለማቋረጥ እየፈጸሙበት ይገኛሉ። የሕዝቡን ሰላምና ደህንነት የመጠበቅ ኃላፊነትን የተረከበው “የለውጥ” ኃይልና መንግሥትም ከእነ መለስ ዜናዊ ባልተለየ ሁኔታ የአማራን ሕዝብ ሰቆቃ እያየ እንዳለየ፣ እየሰማ እንዳልሰማ… ሕዝቡ በገፍ እያለቀና እየተሰቃየ ባለስልጣናቱ ሌላው ቀርቶ የረባ የሀዘን መግለጫ፣ ማጽናኛም ይሁን የአንዲት ሰከንድ የህሊና ጸሎት ነፍገውታል።

    የዚህ ታጋሽ ሕዝብ ትግስት አልቋል። መንግሥት የሕዝብን ደህንነትና ሰላም በአግባቡ መጠበቅ ካልቻለና የዜጎቹ የጅምላ ሞት፣ ሰቆቃ መፈናቀል፣ የደም ጎርፍና እንባ ግድ የማይለው ከሆነ ሕዝቡ ሰላሙን፣ ደህነንቱና ዜግነታዊ መብቱን ሙሉ በሙሉ የሚያከብርለትና እኩልነትና አንድነትን የሚያረጋግጥለት መንግሥት እንዲመጣ አምርሮ ከመታገል ውጭ አማራጭ እንደማይኖረው ሊታወቅ ይገባል።

    ጋዜጠኛ አበበ ገላው (facebook.com/agellaw)

    [caption id="attachment_41752" align="aligncenter" width="600"] በጀርመን የሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ሰላማዊ ሰልፍ ላይ[/caption]

    Semonegna
    Keymaster

    “የአማራ ባንክ አርሶ እና አርብቶ አደሮች የባንክ አገልግሎት ተጠቃሚ ከማድረግ ባሻገር ባለአክሲዮን እንዲሆኑ አስችሏል” የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ይናገር ደሴ (ዶ/ር)

    አዲስ አበባ (አሚኮ) – የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ይናገር ደሴ (ዶ/ር) አማራ ባንክ መከፈቱንና መይፋ ሥራ መጀመሩን አስመልክተው ለባንኩ ባለድርሻ አካላት እና ለመላው ኢትዮጵያውያን የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት አስተላልፈዋል።

    ዶክተር ደሴ ይናገር አማራ ባንክ አጀማመሩ ከሌሎች ባንኮች የተለየ የሚያደርገው ጉዳዮች እንዳሉት አስረድተዋል። የባንኩ አክሲዮን በስፋት በገጠርም በከተማም የተሸጠ መሆኑ፤ በባለ አክሲዮን ብዛት ትልቅ ባንክ መሆኑ ልዩ ባንክ እንደሚያደርገው ተናግረዋል።

    ዶክተር ይናገር የባንኩ እውን መሆንን ያሳኩ አደራጆች እና የባንኩ የሥራ አመራር ሊመሰገኑ እንደሚገባም ነው የገለጹት። በተለይ የአማራ ባንክ የቦርድ ሊቀመንበር አቶ መላኩ ፋንታ በባንክ ምሥረታ ሂደት አሰልቺውን ጉዞ በተለይም ከተቀመጡት መስፈርቶች አንድ እንኳን ቢጎድል መሳካት የማይችለውን ሂደት በማሳካት ያከናወኑት ሥራ ትልቅ በመሆኑ ሊመሰገኑ ይገባል ነው ያሉት። አቶ መላኩ ከበርካታ የሕይወት ውጣውረድ እና እስር በኋላ ተቋም መርተው ለሕዝብ የሚጠቅም ባንክ ማቋቋም በመቻላቸው እሳቸው እና የሚመሩት አደራጅ እና የሥራ አመራር ቦርዱ ምሥጋና አቅርበዋል።

    በአማራ ባንክ ምሥረታ ላይ ከሀገር ውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ዲያስፖራዎች ያበረከቱት አስተዋጽኦ እና ባንኩ እውን እንዲሆን ያደረጉት ተሳትፎ የሚመሰገን እንደሆነም ነው ዶክተር ይናገር የገለጹት።

    በባንክ ምሥረታ በአንድ ቀን 72 ቅርንጫፍ ለመክፈት ቀን ብቻ ሳይሆን ሌሊትም ተሠርቶ ካልሆነ የማይቻል እንደሆነ የተናገሩት ዶክተር ይናገር ደሴ፥ ለዚህ ውጤት የአማራ ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሄኖክ ከበደ እና የሥራ አጋሮቻቸው ያበረከቱት አስተዋጽኦ ትልቅ በመሆኑ ሊመሰገኑ እንደሚገባም ነው የተናገሩት።

    ኢትዮጵያ ውስጥ የባንክ አቅም ገና ያልተነካ በመሆኑ አሁን የተከፈተውን አማራ ባንክ ጨምሮ አዳዲስ እየተከፈቱ ካሉ ባንኮች በተጨማሪ ከተሳካ የሌሎች ሀገር ባንኮች እንዲገቡ እንደሚደረግ ነው የተናገሩት። ይህም የሀገርን ልማት በማፋጠን የዜጎችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚቻል ነው ያስገነዘቡት። ባልተነካው የሀገሪቱ የንግድ እንቅስቃሴ እና የመዋዕለ ንዋይ ፍሰት የአማራ ባንክ ትልቅ ሚና እንደሚጫወትም ዶክተር ይናገር ያላቸውን እምነት ተናግረዋል።

    አርሶ እና አርብቶ አደሮች የባንክ አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከማድረግ ባሻገር የባንክ ባለአክሲዮን እንዲሆኑ ማስቻል አስፈላጊ በመሆኑ በዚህ ረገድ አማራ ባንክ ሰፊ የአክሲዮን ሽያጭን በገጠር በመሸጥ የሚስተካከለው እንዳልተገኘም ነው የጠቆሙት። ባለአክሲዮኖቹም በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ መሆናቸው ባንኩን ልዩ እንደሚያደርገውም ተናግረዋል። ይህም ባንኩን የመላው ኢትዮጵያዊያን ባንክ እንደሚያደርገው ዶክተር ይናገር አስረድተዋል።

    አማራ ባንክ በአገልግሎት አሰጣጡ እና በፍትሐዊ አሠራሩ ልቆ ከወጣ የውጭ ባንኮች ቢገቡ እንኳን ተወዳዳሪ መሆን ስለሚችል ጠንክሮ መሥራት እንዳለበት ነው ያሳሰቡት። ባንኩ ቁጠባን በማበረታታት ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ እንዳለበት ገልጸዋል፤ ለባንኩ መንግሥት የሚያደርገው እገዛ እንደተጠበቀ ሆኖ ባንኩ ኢትዮጵያዊያንን ሊያገለግል እንዲችል የሞባይል ባንኪንግ አገልግሎትን በስፋት ገቢራዊ ማድረግ እንዳለበት ነው ዶክተር ይናገር የተናገሩት። አማራ ባንክ ዘመኑ የቴክኖሎጅ በመሆኑ በቴክኖሎጅ ዘርፍ ልቆ እንደሚወጣም ያላቸውን እምነት ተናግረዋል።

    ምንጭ፦ አሚኮ

    Anonymous
    Inactive

    የአማራ ብልፅግና ፓርቲ መግለጫ

    አሸባሪው ህወሓት (ትህነግ) የአማራና የአፋር ክልል መሬቶች መውረሩንና በሀገር ላይ እያደረሰ ያለውን ሁለንተናዊ ጥፋትና ሽብር ተከትሎ፥ የአማራ ብልፅግና ፓርቲ የሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ይህንን ይመስላል።

    እምቢ ለባርነት፤ ክተት ለነጻነት!!
    የአማራ ብልፅግና ፓርቲ መግለጫ

    በሁሉም የክልላችን ዞኖች፣ በበርካታ ከተሞች እና ወረዳዎች የህልውና ዘመቻውን ተከትሎ እየተካሄዱ ያሉ መሠረታዊ የውትድርና ስልጠናዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል። ሕዝባችን ህልውናውንና ኢትዮጵያን በደምና በአጥንቱ እንደሚጠብቅ የአባቶቹን ቃል-ኪዳን በማደስ ላይ ይገኛል። በዚህም የወገን ጦር ከፍተኛ መነቃቃት ሲያሳይ በአንጻሩ በቅርብም ሆነ በርቀት ያለው ጠላት በፍርሃት እየተናጠ ይገኛል። አሁን መላ የኢትዮጵያ ብሔር ብሄረሰቦች ለህልውናቸውና ለሉአላዊነታቸው ሲሉ ወታደር መሆን መርጠዋል። የዘመቻው ድጋፍ ይህን ሀቅ ያስረግጣል። በታሪክ ስናየው የኖረው እውነታ ኢትዮጵያ ሊቀብሯት የተነሱትን የውጭና የሀገር ውስጥ ፋሽስቶች ሁሉ በመቅበር ስታሳፍራቸው ኑሯለች።

    አሸባሪው ትህነግ፣ ከታሪክ የመማር አንዳች ፍላጎት የለውም። በለመደ የባንዳ ታሪኩ ከጀርባው የኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶችን ተማምኖ ወክየዋለሁ የሚለውን ሕዝብ ጥይት ማብረጃ ማድረጉን ተያይዞታል። ለባዕድ ሥርዓት የመታመን ልማድ ያለውና የኢትዮጵያ ካንሰር የሆነው ትህነግ አማራን ሊያጠፋ፤ ኢትዮጵያን ሊበትን ቆርጦ መነሳቱን ተከትሎ በአጸፋው የኢትዮጵያ ብሔር ብሄረሰቦችን በቁጭት ስሜት ከዳር እስከ ዳር አነቃንቋል።

    በክልላችን የታወጀውን የክተት ጥሪ ተከትሎ የታየው አስደማሚ ሕዝባዊ ንቅናቄም ጥሪውን ተቀብሎ የመፋለም ጉዳይ “አማራን እና ኢትዮጵያን የመታደግ ጉዳይ ነው” በሚል እምነት ስለመሆኑ በተግባር እየተረጋገጠ ነው። በሁሉም የንቃናቄ መድረኮች የተሰማው ሕዝባዊ ድምጽ አንድና አንድ ነው። “ጦርነቱ የህልውናና ሀገር ማዳን ዘመቻ ነው” ፤ “በአሸባሪው ትህነግ መቃብር ላይ በጠንካራ ወንድማማችንት ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን እንገነባለን!” የሚል ነው።

    ምንም እንኳ አሸባሪው ትህነግ ዕድሜው ከ12 ዓመት ህፃን እስከ 70 ዓመት አዛውንት ሴት፣ ወንድ ሳይለይ ኢትዮጵያን ለመውጋት ያሰለፈና የተነሳ ቢሆንም፥ የዚህ ጦርነት ተደማሪ ግብ የትህነግ አስተሳሰብ ቁራኛ የሆነውን የትግራይ ሕዝብን ነጻ ማውጣትን ይጨምራል። በተለይም ኑሮውን በደሳሳ ጎጆ እየኖረ በድንጋይ ስር አፈር እየገፋ የሚኖረው ጭቁኑ የትግራይ አርሶ አደር፥ አሸባሪውን ትህነግ “ልጆቻችንን የት ጣላችኋቸው ?” ብሎ መጠየቅ የሚጀምርበት ጊዜ ሩቅ አይደለም።

    ጦርነት በባህሪው ከሚፈጥረው የኢኮኖሚ ድቀት በላይ ማኅበዊ ቀውሱ ተሻጋሪ ዕዳ እንደሚያመጣ ከትግራይ አርሶ አደሮች በላይ እውነታውን የሚረዳ የለም። ይህ ጦርነት በግብ የኢትዮጵያ ካንሰር የሆነውን ትህነግ ወደመቃብር ማውረድ ቢሆንም በውጤቱ የወላድ መካን የሆነችው የትግራይ እናትም ነጻ ትወጣበታለች። የኢትዮጵያ የግዛት አንድነት በመንደር ወንበዴዎችና ግልገል ሽብርተኞች አደጋ ላይ እንዲወድቅ የኢትዮጵያ ብሔር ብሄረሰቦች እንደማይፈቅዱ በተግባር እያሳዩ ይገኛል።

    የዚሁ ተግባራዊ ዐቢይ ምዕራፍ አካል የሆነው የክልላችን የህልውና ዘመቻ ዝግጅትና አፈጻጸም በስኬት መጓዙን ቀጥሏል። የክተት ጥሪውና የንቅናቄ መድረኩ ወደመሬት ስራ ወርዷል። የወቅቱ ተልዕኳችንም ከአደባባይ ንቅናቄ ወደግንባር መሰለፍ ሁኗል። የሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ የልዩ ኃይል ምልመላዎች በመካሄድ ላይ ናቸው። አሁንም የነገ ባለአራት ኮከብ ጀኔራሎች የሚገኙት ዛሬ መከላከያ ሠራዊቱን በመቀላቀል ላይ ከሚገኙት ወጣቶች ነውና ምዝገባው ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል። በተመሳሳይ የአማራ ልዩ ኃይል በሰው ኃይል፣ በአደረጃጃት እና በወታደራዊ ዲሲፕሊን የማጠናከሩ እና የማዘመኑ ተልዕኮ የክተት ጥሪውን በተቀበሉ ጀኔራል መኮንኖቻችን በመካሄድ ላይ ነው። ከወታደራዊ መረጃ አኳያ ቁጥሩን በይፋ ለመግለጽ ባይቻልም የልዩ ኃይላችን፣ የሚሊሻችን በጥቅሉ የአማራ ሕዝባዊ ሠራዊታችን አቅም በፍጠነት እያደገ ነው። በተመሳሳይ ተልዕኮ በሁሉም ማዕከላት ተጠባባቂ ኃይል የማፍራት ስራው የህልውና አጀንዳው አካል ሁኗል።

    ይህም ሁኖ ሰብዓዊነቱን ክዶ ለመጣው ጠላት ከዚህም በላይ ዝግጅት ሊካሄድ ይገባል። ከአንድ ወር ወዲህ ያለውን የጠላት ዝግጅት ብንመለከት፡- በትግራይ በሁሉም ወረዳወች በብዙ ሽህዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላ (conscription) ኮታ ተጥሎበታል። ይህ የፌዴራል መንግሥቱ የተናጠል የተኩስ አቁም ካወጀ በኋላ ትህነግ በአማራና አፋር ክልሎች ላይ የከፈተውን ወረራ ተከትሎ የተጣለ ግዳጅ ነው። ከዚህ ግዳጅ በፊት የነበረው ሰልጥኖ የታጠቀው ኃይል አብዛኛው ወደመቃብር የወረደ ሲሆን፤ ይህንኑ የሰው ኃይል ክፍተቱን ለመሙላት በዚህ ወር ብቻ በብዙ ሺህዎች የሚገመት የሳምንታት ስልጠና የወሰዱ ታዳጊዎችን ለወረራ አሰልፏል። ይህ ኃይል ከኢትዮጵያዊነት እሴት የራቀ በመሆኑ እንደአንበጣ በየደረሰበት ያገኘውን የሚወር፣ የሚዘርፍ፣ ሴቶችንና እናቶችን የሚደፍር፣ መሠረተ ልማቶችንም የሚያወድም በጥቅሉ ሰብዓዊነቱን የካደ፤ በአማራና በኢትዮጵያ ጥላቻ ያበደ በመሆኑ በፍጥነት ሊደመመስ ይገባል። እረፍትም ጊዜም ሊሰጠው አይገባም።

    ስለሆነም የህልውና ዘመቻው በጊዜ የለንም መንፈስ ተጠናክሮ ይቀጥላል። መሽቶ በነጋ ቁጥር አሸባሪው ኃይል ወደመቀመቅ የሚወርድበት ጉድጓድ ጥልቀት ይጨምራል። ጠላት በተግባርም ሆነ በአስተሳሰብ ሊቀበር ይገባል።

    ይህ የሽብር ቡድን በተመሳሳይ ሰዓት ከአማራም፣ ከአፋርም እንዲሁም ከጎረቤት ኤርትራ ጋር በአንድ ጊዜ ወደግጭት መግባት ያስፈለገው ግጭት ብቸኛ የዕድሜ ማስቀጠያው እንደሆነ በማመኑ ነው። ባለፉት ሠላሳ ዓመታት በተግባሩም ሆነ በአስተሳሰቡ ለኢትዮጵያ ካንሰር ስለመሆኑ በበቂ ሀገራዊ ኪሳራ ተገምግሟልና አሁን ላይ ለወረራ የተሰለፈባቸው የአማራና የአፋር መሬቶች የአሸባሪው ትሕነግ መቀበሪያ መሆናቸው ይቀጥላል።

    እምቢ ለባርነት፤ ክተት ለነጻነት!!
    የአማራ ብልፅግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት
    ሐምሌ 30 ቀን፥ 2013 ዓ.ም.
    ባህር ዳር፥ ኢትዮጵያ

    የአማራ ብልፅግና ፓርቲ መግለጫ

    Anonymous
    Inactive

    በሀገር አንድነት እና ሰላም ላይ የተደቀነውን አደጋ የመመከት ኃላፊነት በዋነኛነት የፌደራል መንግሥቱ ነው!
    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ መግለጫ

    መንግሥት በትግራይ ያለው ግጭት ቆሞ ለሰብዓዊ ድጋፍ ለማድረስ የተሻለ ሁኔታ ለመፍጠር እና ሌሎች ምክንያቶችን ጠቅሶ የተናጥል ተኩስ አቁም ማወጁን ተከትሎ ሰኔ 26 ቀን 2013 ዓ.ም የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ባወጣው የ‘ቢሆንስ’ ትንተና ሊሆን ይችላል ብለን ያስቀመጥነው ሁለተኛው ቢሆንስ (scenario) መንግሥት በትግራይ ክልል የተናጠል ተኩስ አቁም ካወጀ በኋላ የትግራይ አማጺዎች ግጭቱን ለማስፋት የሚያደርጉት ሙከራ ቀጥሎ ግልፅ አሸናፊ የማይኖርበት ሁኔታ ይከሰታል የሚል ነበር። ይህም ከቀጠለ በክልሉ ሕግና ሥርዓትን ማስከበር አዳጋች መሆኑ የሚፈጥረውን አጋጣሚ በመጠቀም ዘረፋዎች ሊበራከቱ እንደሚችሉ፣ የዕለት እርዳታ የሚያስፈልጋቸው የክልሉ ነዋሪዎች በሚፈለገው ደረጃ እርዳታ ሳያገኙ ቀርተው ለከፍተኛ አደጋ ሊጋለጡ እንደሚችሉ፣ መሰረታዊ ለኑሮ የሚያስፈልጉ አገልግሎቶች እና ግብዓቶች (የውሃ፣ የመብራት፣ ህክምና) ማግኘት የማይቻልበት ሁኔታ ሊፈጠር የሚችልበት ዕድል ከፍተኛ በመሆኑ የክልሉ ሕዝብ ለከፍተኛ ችግር የሚጋለጥበት ሁኔታ ሊበራክት እና ለረጅም ጊዜ ምንም ዓይነት አስተዳደራዊ አገልግሎት ሊያገኝ የማይችልበት ሁኔታ ሊፈጠር እንደሚችል እና የዚህ ዓይነት የማያቋርጥ ግጭት ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ ብዙ ችግሮችን ስቦ በማምጣት (ኢንቬስትመንት ይቀንሳል፤ ቱሪዝም ይቀንሳል፤ በዚህም የሥራ አጥ ቁጥር ይጨምራል) በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎችም አለመረጋጋትን ሊያስከትል ይችላል የሚል ትንተና አስቀምጠን ነበር። በትንተናችን ውስጥ ይህ ቢሆንስ (scenario) የመሆን ዕድሉ ከሌሎቹ የበለጠ መሆኑን ጠቅሰን በክልሉና ባጠቃላይ በሀገራችን ከብሔር ፖለቲካ ጋር ተያይዞ የመጣውን አደጋ በዘላቂነት የማይፈታ፣ ሀገሪቱን ቀስ እያለ ውስጧን እንደሚበላ በሽታ ከመግደሉ በፊት መፍትሄ የሚፈልግ እንደሆነ ገልፀን ነበር። በተጨማሪም በዚህ ሁኔታ ውስጥ መረጋጋትን ማስፈን ስለማይቻል የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ወደ ከፍተኛ ግጭት ማምራቱ እንደማይቀር በትንታኔያችን ውስጥ አስቀምጠን ነበር።

    የፌደራል መንግሥቱ የተናጠል ተኩስ አቁም አውጆ የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት በይዞታው ስር የነበሩ ቦታዎችን ለቆ ከወጣ በኋላ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ያስተዋልነው እንቅስቃሴ በቢሆንስ (scenario) ትንተናችን ውስጥ ከሁሉም የተሻለ የመከሰት ዕድል አለው ብለን ያስቀመጥነው ሁለተኛው ቢሆንስ (scenario) እውን እየሆነ እንደሆነ የሚያመላክት ነው።

    በእርግጥ ከላይ በጠቀስነው ትንተናችን ውስጥ ህወሓት የሚያደርሳቸውን ትንኮሳዎች በኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት እየተመከቱ እና እየከሸፉ ሊሄዱ ይችላሉ የሚል ግምታችንን ብናስቀምጥም በተግባር ያየነው ግን የፌደራል መንግሥት ህወሓት ግጭቱን ለመቀጠል የወሰዳቸውን እርምጃዎች በግንባር ቀደምነት አመራር እየሰጠ ለማክሸፍ ከመሞከር ይልቅ ግጭቱን በክልሎች መካከል ያለ ግጭት እስኪመስል የወሰደው ግልፅ ያልሆነ አቋም እጅግ አስደንጋጭ ሆኖ አግኝተነዋል።

    ከዚህም በላይ ግጭቱን በተመለከተ በፌደራል መንግሥቱ በኩል የሚወሰዱ እርምጃዎች የተጣደፉ እና በቅጡ ያልታሰበባቸው መምሰላቸው በአጭር ጊዜ ከህወሓት የተደቀነውን አደጋ በማንኛውም መንገድ ከማክሸፍ ባለፈ እርምጃዎቹ ለሀገራችን ሰላም እና አንድነት በዘላቂነት የሚኖራቸውን አንድምታን ያልገመገሙ ስለመሆናቸው አመላካች ሆነው አግኝተናቸዋል።

    መንግሥት የሚወስዳቸው እርምጃዎችን በተመለከተ ጊዜውን የጠበቀ እና ትክክለኛ መረጃ ለሕዝብ ባለማድረሱ በሕዝብ ዘንድ ከፍተኛ መደናገጥ ከመፍጠሩም ባለፈ በመንግሥት ላይ ያለው እምነት እንዲሸረሸር ምክንያት ሆኗል። በተጨማሪም ህወሓት ያደረሳቸውን ወንጀሎች እና የሚፈጽማቸውን ኢሰብዓዊ ድርጊቶች ከተራ ክስ ባለፈ በተጨባጭ ማስረጃዎች አስደግፎ ለዜጎች እና ለዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ እንዲደርስ ማድረግ ላይ ከፍተኛ ክፍተት እየተስተዋለ ይገኛል። እነዚህ ክፍተቶች በጊዜ መፍትሄ ካልተበጀላቸው ችግሩን የበለጠ እያባባሱት እንደሚሄዱ እናምናለን።

    መንግሥት በተጨባጭ ማስረጃዎች ላይ ተመስርቶ ለህወሓት የሚደረግ ማንኛውንም ዓይነት ድጋፍ ለማስቆም እና ተጠያቂነትን ለማስፈን ያለበትን ኃላፊነት ሙሉ በሙሉ የምንደግፍ ቢሆንም በሌሎች የሀገራችን አካባቢዎች ህወሓትን ትደግፋላችሁ በሚል ምክንያት የሚወሰዱ እርምጃዎች ማስረጃ ላይ የተመሰረቱ ከመሆን ይልቅ እንዲሁ በጅምላ የሚወሰዱ መሆናቸው የዜጎችን ሰብዓዊ መብት የሚጋፉ እና በትግራይ ያለውን ችግር የበለጠ የሚያወሳስቡ ድርጊቶች ናቸው። ለአብነት በአዲስ አበባ ከተማ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ ብቻ በተመሳሳይ ወቅት ቢያንስ 60 የንግድ ተቋማት/ሱቆች ከግጭቱ ጋር በተያያዙ ምክንያቶች ታሽገው ላለፉት ሁለት ሳምንታት ተዘግተው ቆይተዋል። ከግጭቱ ጋር በተያያዘ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚደርስ እንግልት፣ ከሕግ አግባብ ውጪ የሆነ እስር እና ጥቃት በአፋጣኝ መቆም እንደሚገባው የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ሐምሌ 8 ቀን 2013 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ መጠየቁ ይታወሳል።

    ከላይ የተጠቀሱትን መሰረት በማድረግ የሚከተሉት ምክረ ሀሳቦች ተግባራዊ እንዲደረጉ እንጠይቃለን፥

    1. በሁሉም የሀገራችን አካባቢዎች የሚገኙ የፀጥታ አስከባሪዎች ህወሓት የደቀነው አደጋን ለማክሸፍ እያደረጉ ያሉትን መረባረብ በከፍተኛ አክብሮት እናደንቃለን። ህወሓት የፌደራል መንግሥቱን በበላይነት ይቆጣጠር በነበረበት ጊዜ ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊያን ላይ በሙሉ ግፍ ሲፈጽም እንደነበረ ሁሉ አሁንም የደቀነው አደጋ በሀገር አንድነት እና ሰላም ላይ እንጂ በአንድ ወይንም በጥቂት ክልሎች ላይ ብቻ ያነጣጠረ እንዳልሆነ በመረዳት አደጋውን ለመከላከል የሚወሰደው እርምጃ አንድ ወጥ የዕዝ ሰንሰለት ኖሮት በፌደራል መንግሥት እና በኢፌደሪ መከላከያ ሠራዊት አመራር ሰጪነት ብቻ እንዲወሰድ፤
    2. በትግራይ ክልል ያለውን ችግር አሁን ከፊታችን ህወሓት ከደቀነው አደጋ እንፃር ብቻ በማየት ህወሓትን ማሸነፍን ብቻ ዓላማ ያደረገ የአጭር ጊዜ ስልት ይዞ ከመንቀሳቀስ ባለፈ በዘላቂነት ክልሉ ወደተረጋጋ ሰላም እና ዜጎች ወደ መደበኛ ሕይወታቸው ሊመለሱ የሚችሉበት እንዲሁም ግጭቱ ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ተቋጭቶ የሀገር ህልውና እና አንድነትን በዘላቂነት ማረጋገጥ የሚቻልበት ስልት የአካባቢውን ተወላጆች በማሳተፍ እንዲነደፍ እና ተግባራዊ እንዲደረግ፤
    3. አሁን ያለው ግጭት ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲያበቃ እና ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ በትግራይ ክልልም ሆነ በሌሎች የሀገራችን አካባቢዎች የምትገኙ የሀገር ሽማግሌዎች እና ሌሎች ልሂቃን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ የምታስፈልጉበት ወቅት ላይ መሆናችሁን ተረድታችሁ የሚጠበቅባችሁን ኃላፊነት እንድትወጡ፤
    4. የሰብዓዊ ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው ዜጎች ድጋፍ እንዲደርሳቸው የሚደረገው ጥረት አሁን ከምን ጊዜውም በላይ ተጠናክሮ እንዲቀጥል እና መንግሥት የሰብዓዊ እርዳታ በክልሉ ለሚኖሩ ዜጎች እንዲዳረስ የሚያደርገውን ጥረት በግልፅ እንዲያሳውቅ፤ እንዲሁም በዚህ ተግባር የሚሳተፉ የሰብዓዊ ድርጅቶች በግልፅነት እንዲንቀሳቀሱ ተገቢው ክትትል እንዲደረግ፤
    5. የተለመዱ መንግሥትን የሚያሞግሱ የፕሮፖጋንዳ ሥራዎችን እየደጋገሙ ሕዝብን ከማሰልቸት ይልቅ መንግሥት የወሰዳቸውን እርምጃዎች በተመለከተ ትክክለኛ እና ወቅታዊ መረጃ ለሕዝብ እንዲደርስ እንዲደረግ እና ህወሓት የሚፈፅማቸውን ኢ-ሰብዓዊ ድርጊቶች እና ታዳጊዎችን በወታደርነት መመልመል እና በጦርነት ማሳተፍን የመሳሰሉ ወንጀሎችን በተገቢው ፍጥነት በተጨባጭ ማስረጃዎች እያስደገፉ ይፋ የማድረግ ሥራ ተገቢውን ትኩረት ተሰጥቶት እንዲሠራ፤
    6. ዜጎች ለህወሓት የሚደረግ ማንኛውም የሞራልም ሆነ ቁሳዊ ድጋፍ በሕዝብ ሠላም፣ በሀገር ደህንነት እና ሕይወቱን ለመሰዋዕትነት አዘጋጅቶ በተሰለፈው የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ላይ የሚደረግ ክህደት መሆኑን በመረዳት ከተመሳሳይ ድርጊቶች እንዲታቀቡ፤
    7. ህወሓትን ደግፋቹኻል በሚል በጅምላ የሚወሰዱ እርምጃዎች ባስቸኳይ እንዲቆሙ እና እስካሁንም በዚህ መልኩ የተወሰዱ እርምጃዎች አፋጣኝ ማጣራት ተደርጎ የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ እንዲሁም አሁን ያለውን ሁኔታ እንደ አጋጣሚ በመጠቀም የግል ጥቅም ለማግኘት ዜጎች ላይ እንግልት የሚፈፅሙ የመንግሥት እና የፀጥታ ሠራተኞች ላይ አስፈላጊው ማጣራት በአስቸኳይ ተደርጎ የማያዳግም ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ፤

    በመጨረሻም የሀገራችን ሰላም እና አንድነት በዘላቂነት ተረጋግጦ የሁሉም ዜጎች መብት እኩል የሚከበርበት እና እኩል ዕድል የሚሰጥበት እውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት ሁላችንም የምንችለውን ሁሉ የምናዋጣበት አሳሳቢ ወቅት ላይ እንዳለን እያስታወስን ሁላችንም ኃላፊነታችንን ከምር ወስደን እንድንወጣ እናሳስባለን።

    ሐምሌ 10 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ

    የፌደራል መንግሥቱ

    Anonymous
    Inactive

    ይድረስ ለትግራይ ወገኖቼ!
    በአቶ ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ

    የትግራይ ሕዝብ ከባለጌ ልጆቹ በላይ ሀገሩን የሚመርጥበት ጊዜ ደርሷል። በተለይም የትግራይ እናቶች እና አባቶች በራሳቸው ልጆች እኩይ ስምሪት ቀደምቶቻቸው ለአንድነቷ ሰማዕትነትን የተቀበሉላት ኢትዮጵያችን ክብሯ እንዲጎድፍ በዝምታ መተባበራቸውን ይበቃል ለማለት ትክክለኛው ወቅት አሁን መሆኑን ልብ ሊሉ ይገባል።

    የዘመን ተጋሪዬ ለሆናችሁ የትግራይ ወጣቶችም “ጅብም ብሆን የወንዝህ ጅብ ስለሆንሁ፤ ልበላህ መብት አለኝ” የሚሉ ሀገር አጥፊዎችን በመተው ከሀገራችን ኢትዮጵያ እና ወንድሞቻችሁ ጎን እንድትቆሙ ወንድማዊ ጥሪዬን አቀርብላችኋለሁ።

    የሀይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች ጨዋው የትግራይ ሕዝብ በሀገር አፍራሽ፣ ዘር አጥፊና ዘራፊ ብኩኖች በኩል ዘላቂ መብቶቹ፣ ጥቅሞቹና ፍላጎቶቹ እንደማይከበሩለት አውቃችሁ፤ ሁለንተናው ከኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ጋር የተሸመነውን የትግራይ ሕዝብ ታሪክ፣ ክብርና የወደፊት በጎ ተስፋ በሚመጥን ስምሪት እንድትገኙ ዝቅ ብዬ እለምናችኋለሁ።

    ታላቁ የትግራይ ሕዝብ በሌባ አይወከልም! ከዘፍጥረት ጀምሮ እስካሁን ድረስም እናት ኢትዮጵያም ሆነች ወንድሙ የአማራ ሕዝብ ለትግራይ ሕዝብ የክብሩ ምንጭ የደኅንነቱ ደጀኖች እንጂ የስጋቱ ምንጮቹኘች ሆነው አያውቁም፤ አይሆኑምም። እንዴት ሀገር ገንቢው ትግራይ በሀገር አፍራሽ ይወከላል?

    ትግራይ የምታሸንፈው ኢትዮጵያ ስታሸንፍ ብቻ ነው፤ ትግራይ አንገት ደፍታ ኢትዮጵያ አትቃናም። በትግራይ ለቅሶ ፈገግታው የሚደምቅ አንድም ኢትዮጵያዊ አይኖርምም። ሌባና ዘራፊ፤ ባንዳና ሀገር አጥፊ ግን ከየትም ይሁን የትም የጋራ ጠላታችን ነውና በጋራ ልንደመስሰው ይገባናል። በባንዳ ሞት ደረት የሚደቃና ፊት የሚነጭ ሊኖር አይገባም።

    እናም ለተከበራችሁ የትግራይ አባቶቼና እናቶቼ፣ ወንድሞቼና እህቶቼ፥ ስለደማቁ የትናንት ትናንታችን ብቻ ሳይሆን ስለብሩህ ነጋችንም ብላችሁ ለኢትዮጵያችን ኅልውና እንዲሁም ለሕዝባችን ፍትሕ፣ እኩልነትና ነፃነት መረጋገጥ በአንድነት እንድንቆም ስል ጥሪዬን ደግሜ ላቀርብላችሁ እወዳለሁ።

    ሁሉም ችግሮች ከጋራ አቅማችን በታች ናቸው። ስንደማመጥ፣ ስንከባበርና ስንተማመን ከባዱ ቀላል ይሆናል። ኢትዮጵያ ስታሸንፍ ሁላችንም እናሸንፋለን!

    አቶ ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ

    አቶ ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ በፌደራል የጤና ሚኒስቴር፥ የማኅበረሰብ ጤና ኤክስፐርት (public health expert) ሲሆኑ፤ በፖለቲካ እንቅስቃሴአቸው ደግሞ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ናቸው። እርሳቸውን በፌስቡክ ገጻቸው ወይንም በትዊተር ሃንድላቸው ሊያገኟቸው ይችላሉ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    አቶ ክርስቲያን ታደለ

    Anonymous
    Inactive

    “በዚህ ሀገራዊ ምርጫ የፈጠርነው አሸናፊና ተሸናፊን ሳይሆን፣ ጠያቂና ተጠያቂ ያላበት የዲሞክራሲ ሥርዓትን ነው። በዚህ ደግሞ ያሸነፉት በምርጫው የተሳተፉት ሁሉም አካላት ናቸው።” ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ስድስተኛው የስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ውጤትን ያስተላለፉት መልዕክት

    የተከበራችሁ ኢትዮጵያውያን እና ኢትዮጵያውያት፥

    ላለፈው ግማሽ ክፍለ ዘመናት፣ የሀገራችን ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ በነጻ ፈቃዱ የመረጠው መንግሥት እንዲኖረው ብዙ ሙከራዎች ሲደረጉ ቢቆዩም፤ በተለያዩ ምክንያቶች ሲሰናከሉ ነበር። በሂደቱ አያሌ ተማሪዎችና ወጣቶች፣ ገበሬዎችና የቤት እመቤቶች፣ ምሁራንና መለዮ ለባሾች፣ መላው የሀገራችን ሕዝብ ከፍተኛ ዋጋ ከፍሏል። ካለፈ ልምዳችንና ባልተሳኩ ጉዞዎች ጠባሳ ሰበብ፣ የአሁኑም ምርጫ ዴሞክራሲያዊነቱ ተጠብቆ ባይጠናቀቅስ በሚል ስጋት፣ ያለፉትን ወራት እንደ ሀገር በፍርሃት ተወጥረን መክረማችን ሊካድ አይችልም። ኢትጵያውያን ግን ጨዋ ብቻ ሳይሆኑ አርቆ አሳቢ መሆናቸውን ዛሬም አስመስክረዋል። የተሰጋውን ሳይሆን የሚፈልጉትን ማድረግ እንደሚችሉ በግብር አሳይተዋል። ዝናብና ፀሐይ ሳይገድባቸው፣ በረጃጅም ሰልፎች ሳይሰለቹ፣ እስከ እኩለ ሌሊት ታግሰው ፍላጎታቸውን በካርዳቸው ገልጸዋል። እንደ እኛ እምነትም በዚህ ምርጫ አሸናፊ የሆነው ሕዝባችን ነው። ከሕዝባችን በመቀጠል፣ በብዙ ውሱንነቶች ውስጥ አልፈው በዲሞክራሲና በሕዝብ ድምፅ ላይ ባላቸው ጽኑ እምነት፣ ሀሳብና ፖሊሲያቸውን ለሕዝብ አቅርበው ብርቱ ውድድር ያደረጉ ተፎካካሪ ፓርቲዎች የዴሞክራሲያዊ ሂደቱ ድል አድራጊዎች ናቸው።

    ይህንን ምርጫ ልዩና ታሪካዊ የሚያደርጉት ብዙ ጉዳዮች አሉ። በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ ከተጽዕኖዎች በተላቀቀ የምርጫ ቦርድ ዳኝነት ያደረግነው ምርጫ መሆኑ አንደኛው ነው። የምርጫ ቦርድ ዳኝነት እንዲሳካ ደግሞ ቁጥራቸው የበዙ የግልና የመንግሥት ሚዲያዎች፣ የሲቪል ተቋማት፣ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን፣ ፍርድ ቤቶችና ሌሎችም ተቋማት በግልጽ የተከታተሉት መሆኑ ሂደቱን ከመቼም ጊዜ በላይ ተአማኒና ዲሞክራሲያዊነቱ የተጠበቀ ምርጫ ያደርገዋል። ምርጫው ዴሞክራሲን የመትከል ግባችንን አንድ እርምጃ ያስኬደ በመሆኑ፣ ፓርቲያችን ከምንም በላይ ቀዳሚ ድሉ አድርጎ ይቆጥረዋል። በታሪካዊው ምርጫ ተሳታፊ መሆን በራሱ የሚፈጥረው ደስታ እንዳለ ሆኖ፣ ፓርቲያችን በሕዝብ ይሁንታ አግኝቶ ሀገር ለማስተዳደር መመረጡ አስደስቶናል። በውጤቱም ከአሸናፊነት ይልቅ ኃላፊነት፣ ከድል አድራጊነት ይልቅ ታላቅ የሆነ ሀገራዊ አደራ እንዲያድርብን አድርጎናል።

    መንግሥት የሚመሠረተው በሕዝብ በተመረጡ ፓርቲዎች ቢሆንም ሀገርን መምራትና ማስተዳደር ግን ለተመረጡ ፓርቲዎችና መሪዎች ብቻ የሚተው አይደለም። ተፎካካሪ ፓርቲዎችና መሪዎቻቸውም እስከሚቀጥለው ምርጫ በመንግስት አስተዳድርና ሕዝብን በማገልገል ሂደት ውስጥ ሚናቸው ሰፊ ሊሆን እንደሚገባ ለማስታወስ እወዳለሁ። በቀጣይ ወራት ብልጽግና በሚመሠርተው መንግሥት ውስጥ በአስፈጻሚው አካልም ሆነ በፍርድ ቤቶች፣ በሌሎችም የፌደራልና የክልል ተቋማት ላይ ንቁ ተሳትፎ እንዲኖራቸው፣ በዘንድሮው ምርጫ በኃላፊነትና በብቃት የተወዳደሩ የሕዝብ አለኝቶችን ከዚህ በፊት ካደረግነው በእጅጉ ከፍ ባለና አዎንታዊ ለውጥ በሚፈጥር መልኩ እንደምናካትታቸው ለመግለጽ እወዳለሁ። በተጨማሪም እስከሚቀጥለው ምርጫ የበለጠ ተጠናክረውና ተቋማዊ አቅማቸው ደርጅቶ ብርቱ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ ከማድረግ ወደ ኋላ አንልም። በዚህ ምርጫ የፈጠርነው አሸናፊና ተሸናፊን ሳይሆን፣ ጠያቂና ተጠያቂ ያላበት የዲሞክራሲ ሥርዓትን ነው። በዚህ ደግሞ ያሸነፉት በምርጫው የተሳተፉት ሁሉም አካላት ናቸው።

    ውድ የኢትዮጵያ ልጆች፥

    በምርጫ ካርዳችሁ ስትመርጡን በዕቅድና በፖሊሲ የያዝናቸውን የብልጽግና ግቦች እንድናሳካ የድፍረትና የጥንካሬ ስንቅ እንደሚያቀብለን ሁሉ፣ እኛና እናንተን ያስተሳሰረው ቃል ኪዳን ተጠብቆ እንዲቆይ ነገሮች አልጋ በአልጋ እንደማይሆኑን እንገነዘባለን። ቢሆንም ግን ከመቼውም ጊዜ በላይ ትከሻችንን አስፍተን፣ ኢትዮጵያን ከሚወዱ አካላት ጋር ሁሉ በትብብር ዐቅማችን አማጥጠን ለመሥራት ቆርጠን እንደተነሣን ሳበስራችሁ ደስ እያለኝ ነው። በቀጣይ ዓመታት ሀገራችን በእውነትም በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ከፍ የምትልበት ዘመን ይሆናል። ይህ እንዲሳካ የሐሳብና የሞራል ስንቅ እንደምታቀብሉን፣ መንገድ ስንስት እንደምትመልሱን፣ ስናጠፋም እንደምታርሙን ተስፋ በማድረግ ነው።

    በሀገራችን ሁለንተናዊ ብልጽግና እውን እንዲሆን በቀጣዩ አምስት ዓመት ፈር ጠራጊ እንሆናለን የምንለው፣ በዙሪያችን ባሉና ብልጽግና በሚቀላጠፍባቸው አራት ማዕዘኖች መሐል ቆመን ነው። የመጀመሪያው ማዕዘናችን የመሠረተ ልማት ግንባታ ሲሆን፥ ሀገራችን እንድትበለጽግ በኢኮኖሚውም ሆነ በማኅበራዊና ፖለቲካ ዘርፎች ዘላቂ መሠረት የሚሆኑ፣ በፍጥነት የሚጠናቀቁ፣ ጥራታቸው የተጠበቁ፣ ከብክነት ነጻ የሆኑ እና የምንፈጥራቸውን ተቋማት መሸከም የሚችሉ ትውልድ ተሻጋሪ መሠረተ ልማቶችን መገንባታችንን እንቀጥላለን። ጥቂትም ቢሆኑ ባለፉት 3 ዓመታት አመርቂ ሥራዎችን ለመሥራታችን ምስክሮቹ እናንተው ናችሁ።

    ሁለተኛው ማዕዘናችን የተቋማት ግንባታ ሲሆን፣ በጥቂት ግለሰቦችና ነጠላ ተቋማት ላይ ከማተኮር ባለፈ ሀገራችንን በጽኑ መሠረት ላይ የሚያቆሙ ጠንካራ ተቋማት ያስፈልጉናል። ዘመን ተሻጋሪ ሥርዓት ለማጽናት የሚስችሉ ገለልተኛና ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የሚያገለግሉ ተቋማትን መገንባት ላይ ትኩረት ይደረጋል። ይሄ ማሕቀፍ ከፌደራል እስከ ክልል የሚገኙ ተቋማትን የሚያካትት ይሆናል።

    በሦስተኛ ደረጃ እንደ ሀገር የሚያስተሳስሩን የጋራ አመለካከቶችና የጋራ ትርክቶች ላይ ትኩረት ሰጥተን ልንሠራባቸው ይገባል። እርስ በእርስ የሚቃረኑና የሚጠፋፉ ትርክቶች ምን ያህል ለጠላቶቻችን ተመችቷቸው እኛን ደካማ እንዳደረገን ያሳለፍናቸው ዓመታት ሕያው ምስክሮች ናቸው። ስለዚህ ክፍተቶቻችንን በሚደፍን መልኩ ብቻ ሳይሆን እንደ ሀገር አጠንክረው በሚያቆሙን እሴቶች ላይ የተመሰረተ፣ ገዢና ሁላችንንም አሸናፊ የሚያደርግ ትርክት ለመገንባት ጠንክረን እንሠራለን።

    በአራተኛ ደረጃ የሞራል ልዕልናና ግብረገባዊነት ተመጣጣኝ ትኩረት አግኝተው እስካልተሠራባቸው ድረስ በሀገራችን ኃላፊነት የሚሰማቸው ዜጎች ቁጥር እየቀነሰ፣ በተቃራኒው ኢ-ሞራላዊ ድርጊቶች እየተስፋፉ እንዲመጡ በር ይከፍታል። ይኼንን ችግር የመቅረፍ ኃላፊነት መንግሥትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ላይ ብቻ የሚጣል ሳይሆን፣ ከግልና ከቤተሰብ ጀምሮ የሚሠራ ሥራ ነው። ሁሉም አካላት ተረባርቦ ሀገርና ትውልዱን እያቆሸሹ ያሉ መጥፎ ተግባሮችን ጠርጎ ሊጥላቸው ይገባል። በቀጣይ ዓመታት በሞራል ንጽህና የተገነቡ ተቋማትንና መሪዎችን አንጥረን የምናወጣበት እንዲሆን ተስፋ አደርጋለሁ።

    ውድ የሀገሬ ዜጎች፥

    ባለፉት ሦስት ዓመታት በከፍተኛ ጥንቃቄ የቀረጽነው የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለተግባራዊነቱ በጋራ ከተጋን ያለ ጥርጥር ቀጣዩቹ ዓመታት ለሀገራችን ብልጽግና እንደ ወሳኝ የመታጠፊያ ኩርባ ይሆናል። ዕምቅ ዐቅሞቻችን ምንድን ናቸው? ምን ዓይነት የመበልጸግ ዕድል እጃችን ላይ አለ? ምን ብናደርግ ኢኮኖሚያችን መዋቅራዊ ለውጥ ያመጣል? የሚሉትን በሚገባ ፈትሸን ያረቀቅነው ዕቅድ ነው።

    በሀገራችን ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ለነገ የማይባል ጉዳይ ነው። በፍጥነት የምግብ ፍላጎታችንን በማሟላት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከውጭ የምግብ ድጎማ መላቀቅ አለብን። ምግብ ለእኛ ቅንጦት መሆን አይገባም። ጠግቦ መብላት ቅንጦት የሆነበት ሕዝባችንን መርጦ መብላት እንዲጀምር ለማድረግ ቆርጠን መነሳት አለብን። በብዝኃ ዕጽዋትና በብዝኃ እንስሳት የምትታወቅ ሀገራችን የእንስሳት ተዋጽዖና ፍራፍሬዎች ለገበታችን ከቅንጦትነት ወደ አዘቦትነት መለወጥ አለባቸው። ዶሮና ዕንቁላል፣ ወተትና ቅቤ፣ ተርፎን ለገበያ የምናቀርባቸው እንጂ ለዓመት በዓል አይተናቸው የሚሰወሩ የሩቅ እንግዳ መሆናቸው ሊያከትም ይገባል።

    እዚህ ጋር አንድ መታወቅ ያለበት ሀቅ አለ። መንግስትና ሕዝብ እጅና ጓንት ሆነው እስካልሠሩ ድረስ ሕልማችን ይሳካል ማለት ዘበት ነው። በቀጣይ 5 ዓመታት ተባብረን በተለይ በግብርናው ዘርፍ ምርታማነት ለማሳደግ ጠንክረን መስራት አለብን። ከዚህ ቀደም ጀምረናቸው ውጤት እያመጡ ያሉ ተግባራት አሉ። የበጋ ሰብሎችና ፍራፍሬዎች ላይ ለውጥ ለማምጣት ከተጀመሩ አነስተኛ መስኖዎች ባለፈ፣ ዝናብ አጠርነት ለመዋጋት በቴክኖሎጂ አማካኝነት ደመናን ወደ ዝናብ የመቀየር ልምምዳችን እያደገ ይገኛል። በቅርቡም ምርትን የሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመን ችግሮቻችንን ወደ ዕድል መቀየር ጀምረናል።

    አየር ንብረታችንን የሚያስተካክለውና የብዝኃ ዕጽዋትና የብዝኃ እንስሳት ሀብታችንን በእጅጉ ያሳድጋል ተብሎ ተስፋ የተጣለበት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብራችን እንዲሁ ተጠቃሽ ነው። በቁጥር ግንባር ቀደም ያደረጉን የቀንድ ከብቶቻችን ከመቀንጨር ወጥተው ምርታማ እንዲሆኑ ያደርጋል። ወደየጎረቤት ሀገሩ የሸሹ የዱር አራዊትም ተመልሰው፣ ከታሪካዊና ባህላዊ መስህቦች ጋር የተዋደደ ተፈጥሮአዊ መስህብ በመሆን የቱሪስት ፍስትን እንዲጨምርና ኢኮኖሚያችን መስፈንጠር እንዲችል መደላድል ይሆናል ብዬ አምናለሁ።

    የሀገራችን ሕዝብ ሆይ፥

    ባለፉት ጥቂት ዓመታት ትኩረታችንን ሰቅዘው ከያዙት ጉዳዮች መካከል ሌላኛው የሕዳሴ ግድብን የተመለከተ ጉዳይ ነው። የዴሞክራሲ ጥያቄን አንድ ምዕራፍ ለማሳደግ የምርጫችን መሳካት ወሳኝ እንደነበረው ሁሉ፣ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ችግራችንን ለመቅረፍና ለዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች መቀላጠፍ ጉልህ አስተዋጽዖ ከሚያበረክቱ ፕሮጀክቶቻችን መካከል አንዱና ወሳኙ የሕዳሴ ግድብ ግንባታችን እንደሆነ ይታወቃል።

    የሕዳሴ ግድብ አጀንዳ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ከግድብም፣ ከኤሌክትሪክ ኃይል ምንጭነትም በላይ ነው። ከኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ባለፈ ዳግም የመነሣታችን ተምሳሌት ነው። በራስ ዐቅም የመቆም፣ በራስ ፍላጎት የመመራት፣ የሉዓላዊነታችን ምልክት፤ የሀገራዊ አንድነታችን ገመድ ነው። በሕዳሴ ጉዳይ ብዙ አይተናል፣ ብዙ ተፈትነንበታል። በራሳችን ዐቅም መቆማችን የሚያስደነግጣቸው፣ በፍላጎታችን መመራት መጀመራችን የሚቆጫቸው ብዙ ጋሬጣዎችን ሲጥሉብን ነበር። “ሚስማር አናቱን ሲመቱት ይበልጥ ይጠብቃል” እንዲሉ ሆኖ፤ በዓባይ ጉዳይ በገፉን ቁጥር እየቆምን፣ በተጫኑን ቁጥር እየበረታን፣ ባዋከቡን ቁጥር ይበልጥ እየጸናን አሁን የደረስንበት ቦታ ላይ ቆመናል። በቅርቡ ሁለተኛውን ዙር የውኃ ሙሌት አድርገን፣ በምርጫው ስኬት የተደሰትነውን ያህል፣ በሕዳሴያችንም ሐሴት እንደምናደርግ አልጠራጠርም።

    በሕዳሴ ግድብ ላይ ፍትሐዊ ተጠቃሚነታችን እንዲጠበቅልን እንጂ መቼም ቢሆን ሌሎች ሀገራትን የመጉዳት ፍላጎት ኖሮን አያውቅም። አሁንም ለታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ደግመን ማረጋገጥ የምንፈልገው ሐቅ፣ የዓባይ ወንዝ እንደሚያስተሳስራቸው ወንድም ሕዝቦች በእናንተ ላይ ምንም ዓይነት አሉታዊ ተጽዕኖ የመፍጠር ፍላጎት የለንም። ዛሬም ሆነ ወደፊት በጋራ ተጠቃሚነት ዙሪያ ለመመካከር በራችን ክፍት ነው። እኛንም ሆነ እናንተን ነጥሎ ተጎጂ ወይም ተጠቃሚ በሚያደርጉ አካሄዶች ላይ እንድንሳተፍ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን አይፈቅም።

    ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያለንም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ከዚህ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን የሚቀዳ ነው። በጋራ ተጠቃሚነት ዙሪያ ለመሥራት ሁሌም ዝግጁዎች ነን። የአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ሰላሙ እንዲጠበቅ፣ የጋራ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ማኅበረሰብ እንዲፈጠር፣ በትብብርና በመግባባት እንድናድግ ኢትዮጵያ ትፈልጋለች፤ ጥሪም ታቀርባለች።

    የተከበራችሁ ተፎካካሪ ፓርቲዎች፥

    የሀገራችን መጻኢ ጊዜ ብሩህ ለማድረግ በተገቢው መወጣት ከሚገቡን የቤት ሥራዎች መካከል አንዱና ዋነኛው ፖለቲካዊ ጉዳዮቻችንን በሠለጠነ መንገድ መምራት ነው። ከላይ በመግቢያዬ እንደገለጽኩት ይኼ ኃላፊነት በመንግሥትና በተመረጠው ፓርቲ ላይ ብቻ የሚጣል አይደለም፤ አንድ አካል ልሥራው ብሎ ቢነሣ እንኳን በአግባቡ የሚወጣው ጉዳይ እንዳልሆነ በተደጋጋሚ አይተናል። እንኳንስ የሠለጠነ የፖለቲካ ሥርዓት መገንባትን የሚያህል ነገር ይቅርና፣ አንድ ዙር ምርጫን ዴሞክራሲያዊ አድርጎ ለማጠነቀቅ ብዙ አካላት መረባረብ እንዳለባቸው ካለፍናቸው ምርጫዎች በሚገባ ተረድተናል። የዘንድሮውንም ምርጫ ካለ እናንተ ድጋፍና ትብብር ፍትሐዊና ዴሞራሲያዊ በሆነ መንገድ ማከናወን ባልተቻለ ነበር።

    በቀጣይም ዓመታት የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ሂደታችን መሬት እንዲረግጥ የተለመደ ትብብራችሁና በየምዕራፉ ያላሰለሰ ድጋፋችሁ እንደሚያሻን ከወዲሁ ለመግለጽ እወዳለሁ። በሀገራችን የብልጽግና ጉዞ ውስጥ የሚኖራችሁ ድርሻ ወሳኝ እንደሆነ እናምናለን።

    የፖለቲካ ልዩነቶቻችን እንዳሉ ሆነው፣ ለሀገርና ለሕዝባችን በሚጠቅሙ ማናቸውም የፖለቲካና ኢኮኖሚያዊ አጀንዳዎች ላይ ከእናንተ ጋር በመግባባት ለመሥራት ዝግጁዎች ነን።

    ምርጫውን ስኬታማ ያደረጋችሁ ውድ የተቋማት አመራሮችና ሠራተኞች፣

    ይህ ምርጫ የተሳካ እንዲሆን የምርጫ ቦርድ አመራሮችና ሠራተኞች፣ እንዲሁም የምርጫ አስፈጻሚዎችና ታዛቢዎች ሁሉ ከደም መሥዋዕትነት በመለስ ያለ ከፍተኛ ዋጋ ከፍላችኋል። ከግራ ከቀኝ የሚመጡትን ጫናዎች ተቋቁማችሁ በውጣ ውረዶች ሳትበገሩ ለሀገራችን የማይደበዝዝ የዴሞክራሲ አሻራ አትማችኋል፤ በዚህም ታሪክ ስማችሁን አድምቆ ይጽፈዋል።

    የጸጥታ አካላት፤ ምርጫው ሰላማዊ እንደሆን ጉልህ ሚና ተጫውታችኋል፤ እናንተ ዕንቅልፍ አጥታችሁ ሥጋቶቻችን ሁሉ እንደ ጉም እንዲተንኑ ስላደረጋችሁ ክብር ይገባችኋል። በተመሳሳይ፣ ፈጣንና ሚዛናዊ መረጃን ወደ ሕዝቡ በማድረስ በኩል የግልና የመንግስት ሚዲያዎች፤ እንዲሁም አጭር የጽሑፍ መልዕልት ስርጭት በኩል የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ሠራተኞች፣ ላበረከታችሁት አስተዋጽዖ ኢትዮጵያ ታመሰግናችኋለች።

    ውድ የፓርቲያችን አመራሮችና አባላት፥

    በዚህ ምርጫ ሕዝቡ ያስተላለፈውን መልእክት በሚገባ መረዳት የወደፊቱን መንገዳችንን ቀና እንደሚያደርገው እናምናለን። ሕዝቡ በአብላጫ ድምጽ እኛን የመረጠው ፓርቲያችን እንከኖች ስለሌሉበት አይደለም፤ ከነስሕቶቻችንን ዕድል ሰጠን እንጂ ድል አላደረግንም። ሕዝብ የመረጠን በአንድ በኩል ያጠፋናቸውን እንድናርም፣ በሌላ በኩል መልካም ጅማሮዎቻችንን እንድናስቀጥል፣ ከሀገር ግንባታ አንጻር በወሳኝ ደረጃ ላይ ያሉ የለውጥ ሥራዎችን በቀጣይ ጊዜያት ፈጽመን እንድናሰረክብ ነው። ሕዝባችን ጉድለቶቻችንን በሚገባ ያውቃል። ከስርቆት ዓመል ያልተላቀቁ፣ ለሰው ነፍስ ግድ የሌላቸው፣ ሕግን የማያከብሩ፣ ኃላፊነታቸውን የማይወጡ አመራሮች በመካከላችን መኖራቸውን ጠንቅቆ ያውቃል። ድምፁን ሲሰጠን ታረሙ፣ ውስጣችሁን አጥሩ እያለን ጭምር ነው። እኛም በተግባር ሆነን ማሳየት አለብን። ይኼን ማድረግ ካልቻልን ከአምስት ዓመት በኋላ በካርዱ እንደሚቀጣን እናውቃለን።

    በአሁኑ ምርጫ መምረጥ ያልቻላሁ ወገኖቻችን በሙሉ፥

    በልዩ ልዩ የጸጥታና የደኅንነት ምክንያቶች፣ እንዲሁም በሎጅስቲክና በተለያዩ ውሱንነቶች ምርጫው በተያዘለት ክፍለ ጊዜ መሠረት ከተቀረው ሕዝብ ጋር አብራቸሁ ድምፅ ባለመስጠታችሁ ታላቅ የሆነ ቅሬታ ፈጥሮብናል። ይኼ የሆነው ባልተጠበቁ ምክንያቶች እንደሆነ ግንዛቤ ትወስዳላችሁ የሚል ግምት አለን። ሁኔታዎች ተስተካክለው የምርጫ ቦርድ በወሰነው ቀን ምርጫው እንደሚደረግ እምነቴ ነው።

    ትግራይን በተመለከተ የትግራይ ሕዝብ በሚፈልገው መንገድ ከተደራራቢ ችግር የሚወጣበትን፣ ተያያዥ ሀገራዊ ችግሮች የሚፈቱበትን እና ሰላምና ደኅንነት የሚረጋገጥበትን የመፍትሔ አቅጣጫ እንከተላለን።

    በመጨረሻም፣ ከለውጡ ጊዜ አንሥቶ እስከ ዛሬ ድረስ ስለ ሀገር አንድነትና ስለ ሕዝባችን ተጠቃሚነት ቀና ቀናውን በማሰብ በመንገዳችን ሁሉ ድጋፍ ሲያደርጉልን የነበሩ አካላትን ከልብ ሳላመሰግን አላልፍም። ኢትዮጵያ በታሪክ ለውጥ ላይ ናት። በዚህ የለውጥ ሂደት ተሳፍረን የተሻለች ሀገር እንገነባለን። በዚህ ምርጫ ኢትዮጵያችን አሸናፊ ስለሆነች በድጋሚ ለመግለጽ እወዳለሁ። ቀጣይ ዘመናችንን ብሩህ ያድርግልን፤ ሁላችንም እንኳን ደስ አለን።

    ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!
    ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ!
    ሐምሌ፣ 2013 ዓ.ም

    • በስድስተኛ ጠቅላላ ሀገራዊ ምርጫ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ብልጽግና ፓርቲ 410 መቀመጫዎችን ማሸነፉን የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሐምሌ 3 ቀን  2013 ዓ.ም. አስታውቋል። ዝርዝሩን ለማንበብ እዚህ ጋር ይጫኑ
    • የስድስተኛው ጠቅላላ ሀገራዊ ምርጫ ውጤት መታወቅን ተከትሎ የኢፌዴሪ ፕሬዝደንት ወ/ሮ ሳህለወርቅ ዘውዴ “ኢትዮጵያ ሀገራችን ተከብራ የምትኖረው ስንቻቻል፣ ስንደማመጥና የሌላውን ሃሳብ ስንቀበል ብቻ ነው” በማለት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
    • ይህ ሀገራዊ ምርጫ በተሳካ ሁኔታ እንዲካሄድ ትልቁን ሚና የተጫወተውን የብሔራዊ ምርጫ ቦርድን የሚመሩት ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ “ሀገራዊ ምርጫው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ገለልተኝነት በይፋ የታየበት ነው” ብለዋል።

    ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ

    Anonymous
    Inactive

    ህወሓት ጠቡ ከኢትዮጵያ እና ከኢትዮጵያዊነት ጋር ነው

    በአቶ ዮሐንስ መኮንን

    “ከማዕከላዊው የመንግሥት የሥልጣን ማማ ተገፍቼያለ” ብሎ ያኮረፈው የህወሓት ቡድን ከሦስት ዓመታት በፊት የጦርነት ዳርዳርታ በጀመረ ሰሞን መገዳደል ማንንም አትራፊ ስለማያደርግ የጦርነት ጉሰማውን እንዲተው በሀገር ሽማግሌዎች፣ በልኂቃንም ሆነ በተራ ዜጎች ሳይቀር ተለምኖ ነበር። የህወሓት ሰዎች ግን “ጦርነት ባህላዊ ጨዋታችን ነው” እያሉ ያፌዙ እንደነበር ኢትዮጵያውያን ሁላችንም የምናስታውሰው የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው።

    የጦርነት ጉሰማው ድንበሩን አልፎ “የ45 ደቂቃ መብረቃዊ ጥቃት” ሲሉ በራሳቸው አንደበት በነገሩን አረመኔያዊ የክህደት እርምጃ ወገናቸው በሆነው የሀገር መከላከያ ላይ የፈጸሙት ጥቃት እና በማይ ካድራ ንጹሐን ላይ የፈጸሙት ጭፍጨፋ ለህወሓት ሰዎች እና ደጋፊዎቻቸው ዛሬ ላይ “ጀብድ” ይምሰላቸው እንጂ የፈጸሙት ተግር በታሪክ ፊት አንገታቸውን የሚያሰደፋ የነውር ጥግ ነበር።

    ይህንኑ የህወሓት አረመኔያዊ ተግባ ተከትሎ የመከላከያ ሠራዊታችን በወሰደው የአጸፋ እርምጃ ዋንኛው ዓላማ ህወሓትን ከነመዋቅሯ መደምሰስ ቢሆንም ጦርነቱ በንጹሓን ዜጎች ይልቁኑም በሴቶች እና በሕጻናት ላይ ያደረሰው ጉዳት የሚያሳዝነን እና የሚያሳፍረን ክስተት ነበር።

    ዛሬ ላይ የኢትዮጵያ መንግሥት በውጪ መንግሥታት ተጽእኖም ይሁን በጦርነቱ አክሳሪነት የተነሳ “የጽሙና ጊዜ ለመስጠት” የተናጥል የተኩስ አቁም ውሳኔ አሳልፎ ከክልሉ ሠራዊታችን ማስወጣቱ ተገቢ እርምጃ ነው። ይህ ማለት ግን “ትግራይን የራሱ ሉዓላዊት ሀገር አካል መሆኗ አበቃ” ማለት አይደለም። በግልጽ ቋንቋ ለመግለጥ “ህወሓት ይሻለናል” ለሚሉ አባላቶቿ ደጋፊዎቿ “ዕድል ለመስጠት ያለመ” መሆኑን እገነዘባለሁ።

    ይሁን እንጂ መንግሥት ተገፍቶ ሕግ ወደማስከበር ጦርነት ሲገባም ሆነ አሁን ትግራይን ለቅቆ ሲወጣ ጉዳዩን ያየዘበት መንገድ ሌላ ዘላቂ ሀገራዊ ችግር ተክሎብን እንዳያልፍ ሊጠነቀቅባቸው የሚገቡ ጉዳዮች እንዳሉ ይሰማኛል። በምክንያት ላስረዳ፡

    ህወሓት ያኮረፈውም ሆነ የተጣላው ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር እንጂ ከአንድ ሕዝብ ጋር እንዳልነበረ የሚስተው ያለ አይመስለኝም። ጦርነቱ እንደተጀመረ ተደራጅቶ በቅርብ ርቀት ላይ ገኝ የነበረው የአማራ ልዩ ኃይል ቀድሞ የህወሓትን ተስፋፊ ጦር መመከቱ የሚያስመሰግነው ተግባር መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ በሂደት ግን በዓለም ዓቀፉ ማኅበረሰብም ሆነ በአንዳንድ “ልኂቃን” ጭምር የህወሓት ጠብ “ከአማራ ልዩ ኃይል” ጋር አስመስለው መግለጻቸው ተገቢ ካለመሆኑም በላይ የአንድን ጠባብ ቡድን የእብሪት ጦርነት በሁለት ሕዝቦች መካከል የተደረገ ጦርነት አስመስሎ ማቅረቡ ጉዳቱ ውሎ አድሮ የሚያመረቅዝ ቁስል እንዳተርፈን ያሳስበኛል። በእርግጥ የመከላከያ ሠራዊታችን ከሁሉም ብሔሮች የተውጣጣ ጦር መሆኑ እየታወቀ ተደጋግሞ “አማራ ልዩ ኃይል” የጦርነቱ ፊት አውራሪ ተደርጎ መሳሉ የህወሓት ጠብ ከአንድ ሕዝብ ጋር አስመስሎታል።

    በቀደም እለት ጠቅላይ ሚንስትሩ በፓርላማ ባደረጉት ንግግርም “የአማራ ሕዝብ ለህወሓት አይንበረከክም” የሚለው ንግገራቸው ምንም እኳን ሕዝቡን ለማጀገን እንደተጠቀሙበት ብረዳውም የአማራ ልዩ ኃይል ለሀገር አንድነት የከፈለውን መስዋእትነት ክልሉን ለመከላከል እንደተከፈለ መስዋእትነት አሳንሶ ወደማየት እንዳይተረጎም ያሳስበኛል።

    ዛሬ ደግሞ የጀርመኑ ዶቼቬሌ ሂውማን ራይት ዎችን ጠቅሶ እንደዘገበው ህወሓት “በአማራ ክልል ልዩ ኃይሎች ተይዘውብኛል” የሚላቸውን አካባቢዎች መልሶ ለመንጠቅ በርካታ ታጣቂዎቹን እያንቀሳቀሰ መሆኑን ሰምተናል። እንደዘገባው ከመጠለያ ካምፖች ሳይቀር ወጣቶችን በገፍ እየመለመለች ነው። (ህወሓት ሰንአፌ በረሃ አርቅቃ ኢትዮጵያ ላይ የጫነችውን “ሕገመንግሥት” ሳይቀር በተቃረነ መንገድ የአማራ ገበሬዎችን በማፈናቀል በወረራ የቀማቻቸውን ወልቃይት እና ሁመራን የመሳሰሉ ለም መሬቶች በግፍ መንጠቋ ይታወሳል)

    የህወሓትን ትፍራፊ ጦር እንደ አመጣጡ ለመመለስ የአማራ ልዩ ኃይል የሚያንስ ባይሆንም ትንኮሳውን ማስቆም ያለበት ዋንኛው ፊትአውራሪ ጦር ግን የሀገር መከላከያ ኃይል ነው ብዬ በጽኑ አምናለሁ። የልዩ ኃይል ተሳፎ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝም የአማራ ብቻ ሳይሆን የሁሉም ክልሎች ልዩ ኃይሎች በመከላከያ ሠራዊት ሥር ታቅፈው ስምሪት ሊሰጣቸው ይገባል።

    “ኢትዮጵያን ሳላፈርስ እንቅልፍ አይወስደኝም” ብሎ የማለውን የህወሓት ትርፍራፊ ጦር መመከት እና አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝም መደምስ የሁሉም ኢትዮጵያውያን የቅድሚያ ቅድሚያ ኃላፊነት ነው። ምክንያቱም የህወሓት ጸብ ከኢትዮጵያ እና ከኢትዮጵያዊነት ጋር ነው!

    በአቶ ዮሐንስ መኮንን

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ህወሓት ጠቡ ከኢትዮጵያ እና ከኢትዮጵያዊነት ጋር ነው

    Anonymous
    Inactive

    እብለት የሌለበት ምስክርነቴ – ለዶ/ር ብርሀኑ ነጋ

    (የትነበርክ ታደለ /ጋዜጠኛ/*)

    በሀገራችን የዲሞክራሲ ትግል ውስጥ ትልቁ ፈተና ኢ-ዴሞክራሲያዊና አምባገነን መንግሥታት ብቻ አይደሉም፤ የሴራ ምሁራንም ጭምር እንጂ። በገዛ ራሳችን ምሳሌ “ቀና ቀና ያለች ማሽላ አንድም ለወፍ፥ አንድም ለወንጭፍ” እንደ ተባለው የሀገራችን የሴራ ምሁራን ከመካከላቸው ቀና ያለውን በማጥቃት ብዙ ፍሬ ያዘሉ ሰብሎቻችንን አምክነው ኖረዋል። በዚህ ድርጊታቸው ከአምባገነን መንግሥታት በላይ ሀገራችንን መከራ ውስጥ ጨምረዋል። ብርሀኑ ነጋ ለእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የመፍትሄ ምንጭ እንጂ ጸረ-ኢትዮጵያዊ ወይም ጸረ-ኢትዮጵያ ተብሎ ለተከታታይ ዓመታት በአደባባይ የሚዘመትበት ሰው አልነበረም!!

    ብርሀኑ…

    ከጽንፈኛ ብሔርተኞችና ከአክራሪ ሀይማኖተኞች በሚወረወርበት ሾተል ጀርባው እየደማ የዜግነት ፖለቲካን የሙጥኝ ያለው ‘በኔ ጉዳት ኢትዮጵያ ትዳን’ ብሎ እንጂ ኢትዮጵያን ስለሚጠላ አይደለም!

    እንዲህም ተባለ እንዲያ ዛሬ ያ መገፋቱ ፍሬ አፍርቶ እነሆ ከሦስት የጭለማ ዓመታት በኋላ ሀገር ኖራ፣ ምርጫም ኖሮ፣ ወደ ፊት ልንሻገር ነው ብለን የምናስብበት የተስፋ ጭላንጭል ላይ ደርሰናል።

    ‘ምርጫ አለ’ ያልነው ብርሀኑ ስላለ ነው! ኢትዮጵያ ያንን ሁሉ መከራ አልፋ ለምርጫ የደረሰችው ብርሀኑ ነጋ በፖለቲካ ስም ሀገር የመናድ የገመድ ጉተታው አካል ስላልነበረ ነው!

    ዶላርና የጥይት አረር ታቅፈው ከውጭ የገቡ ተቃዋሚዎችና ሚሳኤል የታጠቀች ህወሓት “ሕገ-መንግሥቱን ትነኩትና” እያሉ በሚያስፈራሩበት በዚያ የሦስት ዓመት ጭለማ ክረምት ውስጥ ሕዝብ ብርሀኑን ሰምቶ “እውነት ነው፤ ጊዜው የሕገ መንግሥት ጥያቄ ማንሻ አይደለም” ብሎ ጋብ ባይል ኖሮ፤ “ይህ የምንፈልገው ሥርዓት አይደለም፣ ይሁን እንጂ ለሀገራችን ስንል እንደግፈው፣ ከችግሮቹ ይልቅ ጠንካራ ጎኖቹን እያሳየን ወደ ፊት እንግፋው” ብሎ ከመንግሥት ጎን ቆሞ “አለሁ!” ባይል ኖሮ የዛሬው የምርጫ ክርክር ቅንጦት በሆነ ነበር።

    በእውቀቱ ልክ እያሰበ በሀገር ፍላጎት ልክ እየወሰነ ባይራመድ ኖሮ “በለው! በለው! ፍለጠው! ቁረጠው!” ባዮች ጋር በስሜት ጋልቦ ቢሆን ኖሮ… እንኳን አንግቦት የተነሳውን የዜግነት ፖለቲካ ለአካለ ምርጫ ማድረስ ይቅርና፥ ለሀገራችንም ጦስ በሆነ ነበር።

    ይህ ሁሉ ለሕዝብ ግልጽ የሆነ ሀገራዊ አበርክቶው በሴራ ምሁራን ትንታኔ እየታጀለ ቀን ከሌት መዶስኮሩ ሰውዬው በእርግጥም ፍሬ ያዘለ ሰብል መሆኑን ከማሳየቱ በቀር እንደሚሉት ጥላቻ በልቦናው የተሸከመ ጸረ-ሕዝብና ጸረ-ሀገር መሆኑን ፈጽሞ አይመሰክርም!!

    ― ይድረስ ለብርሀኑ ነጋ (ፕሮፌሰር) ―

    የመጨረሻ ውጤቱ፣ ጥራቱና መጠኑ ምንም ይሁን ምን፣ ዴሞክራሲን አዋልደሀል!! ጨቅላውን ዴሞክራሲ አንስቶ መሳም፣ አቅፎ ማሳደግ የኛ ድርሻ ይሆናል! ለዘመናት የተጫነብንን የዘር ፖለቲካ የምናራግፍበትን አንድ ዘዴ የሆነውን የዜጋ ተኮር ፖለቲካ አስተምረህ፣ አዋቅረህ፣ ከምርጫው ኮሮጆ አድርሰህልናል – ያለፈውን ጥፋት ላለመድገምና እንደ ቀሪው ዓለም በሀሳብ ላይ መሠረት ያደረገ ፖለቲካን መምረጥ የኛ ፋንታ ይሆናል። በብዙ መከራዎች መካከል ባለች ሀገር ውስጥ የሰከነ የተቃውሞ ፖለቲካን በማራመድ ሀገርና መንግሥት በፈለጉን ጊዜ አቤት እያልን በቀረው ደግሞ እየተቃወምንና እየተቸን መጓዝ የምንችልበትን የሰለጠን አስተሳሰብ አሳይተኸናል። ይህን መንገድ ተከትሎ ያለጩኸት እና ያለ ወከባ መንግሥት መቀያየርን መልመድ የኛ ተግባር ይሆናል።… በቀረው ደግሞ ምርጫው በሰላም ተጠናቆ ቢሆን በፓርላማው፣ ከዚያም ሲያልፍ በመንግሥት ስልጣን ላይ ሆነህ ቀሪ ህይወትህን ለዚህች ደሀ ሀገራችን የበለጠ እንድትሠራ መልካም ውጤት እመኝልሀለሁ! በቀረው ግን ውለታህ አለብን እንጂ ግዴታችን የሌለብህ ከሚጠበቅብህ በላይ ያገለገልከን ታላቅ ዜጋ ነህና እናከብርሀለን!!!

    * አቶ የትነበርክ ታደለ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚጽፍ ጋዜጠኛ ሲሆን፥ በፌስቡክ ገጹ ሊያገኙትና ጽሁፎቹን ሊከታተሉ ይችላሉ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ዶ/ር ብርሀኑ ነጋ

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 124 total)