Search Results for 'የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ'

Home Forums Search Search Results for 'የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 42 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    በሚደረገው ሀገራዊ ምክክር ዜጎች በንቃት እንዲሳተፉ በቂ አትኩሮት ይሰጠው!
    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተላለፈ ወቅታዊ መልዕክት

    በሀገራችን ኢትዮጵያ በየዘመኑ የነበሩትን፣ ከፖለቲካው ሥርዓት የሚመነጩ ችግሮችን ለመፍታት እና ወደተሻለ ሀገራዊ ሁኔታ ለመሸጋገር የሚያስችል ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለማንበር እቅስቃሴ ማድረግ ከተጀመረ ከሃምሳ ዓመታት በላይ ተቆጥረዋል።

    እነዚህ እንቅስቃሴዎች የሥርዓት ለውጥ ከማምጣት ተሻግረው የዴሞክራሲን ፍሬ ከማፍራት ይልቅ ሀገራዊ ችግሮቻችንን በአይነትና በብዛት እየጨመሩ እና እየተወሰሳሰቡ እንዲመጡ በማድረግ ዛሬ ላይ የኢትዮጵያችን ህልውና እና ቀጣይነት ላይ ከፍተኛ አደጋ ለመደቀን በቅተዋል።

    ምንም እንኳ ሌሎች ዘርፈ ብዙ ችግሮች ቢኖሩም፤ የኢትዮጵያ ህልውና ላይ የተደቀነው አደጋ በዋነኛነት የሚመነጨው፣ ከሀገራዊ የፖለቲካ ሥርዓቱ ነው። ሀገራዊ የፖለቲካ ሥርዓቱ በተለያዩ ፍላጎቶች፣ ጥቅሞች፣ ስሜቶች፣ ተስፋዎች እና ስጋቶች በመወጠሩ፤ እርስ በእርስ አለመተማመን፣ ሰላም ማጣት፣ መፈናቀል፣ አለመረጋጋት . . . ወዘተ ተፈጥሮ መዋቅራዊ ቅራኔ ውስጥ እየዳከርን መገኘታችን የአደባባይ ሀቅ ነው።

    ይህ አደገኛ ሀገራዊ ሁኔታ ሳይረፍድ እና ነገሮች ከቁጥጥር ውጪ ከመውጣታቸው በፊት በጋራ አንድ መፍትሔ ካልተበጀለት፤ እርስ በእርሳቸው እየተሳሳቡ ጫፍ እና ጫፍ የቆሙትን የተለያዩ ፍላጎቶች፣ ጥቅሞች፤ ስሜቶች፤ ቡድኖች እና ድርጅቶች በሙሉ ጠራርጎ፣ ማንኛችንም አሸናፊ ወደማንሆንበት ምድራዊ ሲኦል ውስጥ የመግባት እድል እንዳለን መገንዘብ ይኖርብናል።

    ይህንን ሁላችንም ላይ የተደቀነ ሀገራዊ አደጋ ለማስወገድ፣ ባለፉት ሃምሳ ዓመታት በተለይ በፖለቲካው ሂደት ውስጥ ከተሞከሩት እንዲሁም ሀገራዊ ሁኔታውን ከማባባስ እና ከማወሳሰብ ይልቅ ምንም አይነት መፍትሔ መስጠት ካልቻሉት የፖለቲካ አካሄዶች ውጭ ባለ ሂደት፣ መፍትሔ የማፈላለጉ ጥረት አማራጭ የሌለው አካሄድ መሆኑን መቀበል ያስፈልጋል።

    ሀገራዊ ምክክር ያስፈለገውም የሀገራችን አንኳር ችግሮች በመደበኛው የችግር አፈታት ሂደት መፍትሔ ማግኘት በማይቻልበት ደረጃ በመድረሳቸው እና በመቀጠልም፣ የበለጠ እየገዘፉና እየተወሳሰቡ ሄደው ሀገርን የማፍረስ ደረጃ ከመድረሳቸው በፊት ሀገርን ለማዳን እንዲያስችል ነው።

    በኢትዮጵያ ከአንድ ዓመት በፊት ኮሚሽን ተቋቁሞ የተጀመረውን የሀገራዊ ምክክር ሂደት በተመለከተ አሁን በደረስንበት ደረጃ ዋናው ጉዳይ መሆን ያለበት በሀገራችን ህልውና እና ቀጣይነቷ ላይ ያንዣበበውን አደጋ ለአንዴም ለሁሌም እንዲወገድ ማድረግ ነው። ለዚህ ሊረዳን የሚችል ስምምነት ላይ ለመድረስ ደግሞ በምክክሩ ላይ የሚሳተፉ ባለድርሻ አካላትን በሂደቱ ላይ በቀናነት እንዲሳተፉ የማሳመን ሥራ በስፋት ሊከናወን ይገባል።

    የሀገራዊ ምክክሩ ቁልፍና ወሳኝ ባለድርሻዎች ምክክሩን ለመቀበል እና እንዲነቃቁ ለማድረግ፣ በመጀመሪያ መደረግ ያለበት፣ በሀገራዊ ምክክር ምንነትና እና በሀገራችን ሁኔታ ያለውን አስፈላጊነት አስመልክቶ ግልጽ የሆነ አረዳድ እንዲኖር ምቹ ሁኔታ በመፍጠር የተለያዩ ባለድርሻዎች ወሳኝ ሚና እንዳላቸው ማሳየት ነው።

    ሀገራዊ ምክክር በመደበኛ አሰራሮች ሊፈቱ የማይችሉ መዋቅራዊና ጊዜያዊ ቅራኔዎችን በሰላማዊ መንገድ ተነጋግሮ ለመፍታት የሚያስችል በመሆኑ፤ ዘርፈ ብዙ ጥቅም አለው። ሀገራዊ ምክክር በአግባቡ ከተጠቀምንበት ልዩነቶችን በማስታረቅ ሀገራዊ የፖለቲካ ቀውስን ለማስቀረት፤ ፖለቲካዊ አጣብቂኞችን ሰብሮ ለመውጣት እና ውጥረትን ለማርገብ፤ በትጥቅ የታገዘ አመፅ እንዳይፈጠር አስቀድሞ ለመከላከል ያስችላል። በተጨማሪም፤ ብሔራዊ መግባባትን በመፍጠር ከዚህ ቀደም ለተፈፀሙ በደሎች እና ወንጀሎች እንዲሁም የፍትህ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ይረዳል። በውጤቱም ከተፈጠሩ ፖለቲካዊ ቀውሶች ፈጥኖ በማስወጣት በመንግሥት እና በሕዝብ መካከል መተማመንን ይፈጥራል። በፖለቲካዊ ሥርዓቱ ላይ ጥያቄ ለሚያነሱ አካላትም በሀገራዊ ምክክር ላይ በመሳተፋቸው በሀገር ጉዳይ ላይ የባለቤትነት ስሜትን በማጎልበት ልዩነቶችን በሰላማዊ ውይይት የመፍታት ባህል በማዳበር እንዲሁም ሀገራዊ ቀጣይነት እና መረጋጋትን በማረጋገጥ፤ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መደላድሎችን ይፈጥራል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ከዚህ ቀደም በተለያየ መልኩ ሲገልፅ እንደቆየው፤ ሀገራዊ ምክክሩ በዚህ ወቅት ለአጠቃላይ ማህበረሰባዊ ደህንነታችን የሚኖረው አስተዋፅዖ ከፍተኛ ስለሆነ የቅድሚያ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ሀገራዊ አጀንዳ ነው። ነገር ግን የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ለዚህ ሀገራዊ ክንውን እየሰጡት ያለው ትኩረት በጣም አነስተኛ መሆኑ ፓርቲያችንን በእጅጉ አሳስቦታል።

    ከሁሉም በላይ መንግሥት ለሀገራዊ ምክክሩ ስኬታማነት ብዙ እርቀት ተጉዞ አስተዋፅዖ ማድረግ ሲጠበቅበት፤ በምክክሩ ላይ ሊፈቱ የሚገባቸውን ጉዳዮች አስቀድሞ በመወሰን እንዲሁም ግጭቶች እንዲቀንሱ በትጋት ከመስራት ይልቅ በመንግሥታዊ መዋቅሮች ያልተገባ ውሳኔ ምክንያት ተጨማሪ ግጭቶች እየተፈጠሩ መሄዳቸው እንድንሰጋ አድርጎናል። በኢዜማ እምነት መንግሥት አስተባባሪ እንጂ አፍራሽ፤ ጠቃሚ እንጂ ጎጂ፤ ጠንካራ እንጂ ልፍስፍስ፤ ሕግ አስከባሪ እንጂ ሕግ የሚጥስ ሆኖ መገኘት የለበትም። በመንግሥት በኩል የሚከናወኑ አፍራሽ አካሄዶች አደጋቸው ለሁላችንም ነውና ሊወገዱ ይገባል።

    መንግሥት የሀገራዊ ምክክሩን ሂደት የሚያበላሹ ተግባራትን ማከናወኑ እንዲሁም የምክክሩን ሂደት ውጤታማነት ለማረጋገጥ የሚጠበቅበትን ሚና በአግባቡ እስካሁን አለመወጣቱ ትክክል እንዳልሆነ መረዳት ይጠበቅበታል። ለአብነትም፤ ኢዜማ ከዚህ ቀደም ባወጣቸው መግለጫዎች ላይ እንደገለፀው መንግሥት መግባባት ላይ ያልተደረሰባቸውን ሀገራዊ የፖሊሲ ጉዳዮች፤ የሕገ-መንግሥት አንቀፆች፤ አዋጆች እና ሌሎች ውሳኔዎችን ከሀገራዊ ምክክሩ አስቀድሞ መወሰኑ የምክክር ኮሚሽኑን በማቋቋም ያሳየውን በጎ ተስፋ የሚያጨልም ነው።

    ከመንግሥት በተጨማሪም የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ ልሂቃን፤ የሙያ ማኅበራት፤ የሲቪክ ማኅበራት፤ መገናኛ ብዙሃን፤ የሃይማኖት ተቋማት እና ሰፊው ሕዝብ እስካሁን ባለው ሂደት ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚጠበቅባቸውን ሚና በአግባቡ አልተወጡም። ሀገራዊ ምክክር ለተወሰኑ ግለሰቦች ወይም ተቋማት ብቻ የሚተው ሳይሆን የእያንዳንዱን ኢትዮጵያዊ የነገ ህልውና፤ ደህንነት፤ ሰላም፤ ልማት እና ተጠቃሚነት የሚወስን ጉዳይ መሆኑን አለመገንዘብ ሁላችንንም ለውድቀት የሚዳርግ መሆኑን ማሰብ ያስፈልጋል። በሀገር ዕጣፈንታ ላይ የሚወሰንበትን ክንውን ትኩረት አለመስጠት ማኅበራዊ ኪሳራ እንደሆነ እያንዳንዱ ዜጋ ማወቅ አለበት።

    ፓርቲያችን ኢዜማ ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት እንዲሁም መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከፍተኛ ትኩረት እንድትሰጡት እያሳሰበ የሚከተሉት ምክረ ሃሳቦች ተግባራዊ ሊደረጉ ይገባል ብሎ ያምናል።

    1. መንግሥት የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ሊሠራ የሚችላቸውን መሠረታዊ ጉዳዮች በተደጋጋሚ ተላልፎ ምክክሩ ላይ ጫና መፍጠሩን በአስቸካይ እንዲያቆም፤ እንዲሁም ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚጠበቅበትን መንግሥታዊ ሐላፊነት በአግባቡ እንዲወጣ፤
    2. ምክክር ኮሚሽኑ ለዜጎች መድረስ ያለባቸው መረጃዎች በአግባቡ መድረሳቸውን እና በመገናኛ ብዙሃን ላይ ተገቢው ትኩረት እንዲሰጣቸው ማድረግ ላይ በአትኩሮት እንዲሰራ ብሎም ክንውኖቹን፤ እቅዶቹን እና የሀገራዊ ምክክሩን አስፈላጊነት በተመለከተ በመገናኛ ብዙሃን እየቀረበ በአግባቡ መልዕክቶችን ለማኅበረሰቡ ወቅቱን ጠብቆ እንዲያደርስ ራሱን የቻለ የአየር ሰዓት እንዲመደብለት
    3. የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ እምባ ጠባቂ ተቋም እና ምርጫ ቦርድ እንዲሁም ሌሎች የዴሞክራሲ ተቋማት እየሠሩት ያለውን ጅምር በጎ ሥራ ምሳሌ በማድረግ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ በተሰጠው ስልጣን ልክ ተግባሩንና ታማኝነቱን ለኢትዮጵያ ህዝብ ብቻ እንዲያደርግ፤ በኮሚሽኑ ውስጥ የሚያገለግሉ ግለሰቦችም ታማኝነታቸውን ለህሊናቸው እንዲያደርጉ
    4. የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ ልሂቃን፤ የሙያ ማኅበራት፤ የሲቪክ ማኅበራት፤ መገናኛ ብዙሃን፤ የሃይማኖት ተቋማት እና ሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚጠበቅባቸውን ሚና በአዎንታዊነት እንዲወጡ እንዲሁም በጉዳዩ ላይ በንቃት እንዲሳተፉ።

    በአጠቃላይ፤ ሀገራዊ ምክክር እንደስሙ ሀገራዊ መሆን አለበት። ዜጎች በሀገራቸው ጉዳይ ላይ ያለምንም ተጽዕኖ እንዲሳተፍ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተገቢውን ሚና መወጣት ይጠበቅባቸዋል። እንደ ሀገር ያሉንን ልዩነቶች ለማስታረቅ ሁላችንም ከልባችን በእውነተኛነት መስራት አለብን። በጋራ ለአደጋ እንደተጋለጥነው ሁሉ፤ አደጋውንም በጋራ ለመጋፈጥና በጋራ ለመወጣት መትጋት ይጠበቅብናል። በኢዜማ በኩል የሀገራዊ ምክክር አስተባባሪ ኮሚቴ በማቋቋም አባላትን እንዲሁም ማኅበረሰቡን ለማንቃት የሚችለውን ሁሉ እያከናወነ ሲሆን፤ በቀጣይም ለሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማነት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ ማረጋገጥ ይወዳል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
    ጥር 02 ቀን፥ 2015 ዓ.ም.

    Semonegna
    Keymaster

    ፀሐይ ባንክ አ.ማ. ካፒታሉን ወደ አምስት ቢሊየን ብር ለማሳደግ ወሰነ፤ የቦርድ አስመራጭ ኮሚቴንም አስመረጠ።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – የፀሐይ ባንክ አ.ማ. በባለአክሲዮኖች አንደኛ መደበኛና አንደኛ አስቸኳይ ጉባኤ ታኅሳስ 8 ቀን፥ 2015 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ ሆቴል ባካሄደው ስብሰባ የባንኩን የተፈረመ ካፒታል ከብር 2 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ወደ አምስት ቢሊዮን እንዲያድግ ተወሰነ።

    ፀሐይ ባንክ ካፒታሉን ለማሳደግ በምክንያትነት ያቀረበው በዓለም አቀፍ፣ ሀገራዊ እና በፋይናንስ ዘርፉ የታዩ ዓበይት ለውጦች ምክንያት፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ሀገር በቀል ባንኮች ሊኖራቸው የሚገባው ዝቅተኛ የካፒታል መጠን ላይ ማሻሻያ በማድረጉ፤ የውጪ ባንኮች በባንክ ዘርፉ እንዲሳተፉ የሚፈቅድ ፖሊሲ በመውጣቱ እና ወደ የባንኩን ዘርፍ በሚቀላቀሉበት ወቅት በሚፈጠረው ውድድር አሸናፊ ሆኖ ለመውጣት የተሻለ የካፒታል ቁመና ላይ መገኘት አስፈላጊ በመሆኑ ነው ተብሏል።

    በተጨማሪም እጅጉን ተለዋዋጭ በሆነው የፋይናንስ ዘርፍ ምኅዳር ውስጥ አሸናፊ ሆኖ የመሥራች ባለአክሲዮኖች ራዕይ ማሳካት የሚቻለው በቅድሚያ የተፈረመ ካፒታል ቀሪ ክፍያ በአጠረ ጊዜ ውስጥ መሰብሰብ ሲቻል እንደሆነ እና ባንኩ የነደፈውን ስትራቴጂ ለመተግበር እንዲሁም ከግብ ለማድረስ የተፈረመ ካፒታሉን መሰብሰብ አስፈላጊ በመሆኑ እንደሆነ በጉባኤው ላይ ተመልክቷል።

    በዚሁ መሠረትም ቀደም ተብሎ የተፈረመ ካፒታሉ ላይ ያልተሰበሰበ ገንዘብ የመጀመሪያውን ግማስ 37 ነጥብ 5 በመቶ በፈረንጆች አቆጣጠር እስከ ጥር 2023 (January 2023) መጨረሻ ድረስ፤ እንዲሁም ቀሪውን 37 ነጥብ 5 በመቶ እስከ መጋቢት2023 (March 2023) መጨረሻ፤ በመጨረሻም የማጠናቀቂያውን ክፍያ እስከ ሰኔ 2023 (June 2023) መጨረሻ እንዲከፈል ተወስናል።

    የካፒታል ማሳደጉን በተመለከተ አምስት ቢሊዮን ለመሙላት የሚቀረውን 2 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር በፈረንጆች አቆጣጠር በሐምሌ 1 ቀን፥ 2023 (July 1, 2023) ተፈርሞ በዓመቱ ተከፍሎ እንዲጠናቀቅ የተወሰነ ሲሆን፤ የካፒታል እድገት ውስኔው ተግባራዊ የሚደረገው ቀደም ሲል ተፈርመው ያልተከፈሉ የባንኩ አክሰዮኖች ሙሉ በሙሉ ተከፍለው ሲጠናቀቁ መሆኑ ተገልጿል።

    በተጨማሪም የፀሐይ ባንክ አ.ማ. ለቀጣይ ሦስት ዓመታት የሚመሩ የዳይሬክተሮች ቦርድን ለማስመረጥ የሚሠሩ የአስመራጮች ምርጫ የተካሄደ ሲሆን፤ አስር አባላት ተጠቁመው ከፍተኛ ድምጽ ያገኙ አምስት አስመራጮችን ጉባኤው መርጧል።

    ፀሐይ ባንክ አ.ማ ሀምሌ 16 ቀን፥ 2014 ዓ.ም “ፀሐይ ለሁሉ” በሚል መሪ ቃል በይፋ ሥራ የጀመረ ሲሆን፤ በመላ ሀገሪቱ በርካታ ቅርንጫፎች ከፍቶ መደበኛ እና “ፈጅር” የተሰኘ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት ለሕብረተሰቡ በመስጠት ላይ የሚገኝ ባንክ ነው።

    ባንኩ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ የቅርንጫፍ ቁጥሩን ወደ 100 የሚያደርስ ሲሆን፤ በተጨማሪም 15 የኤቴኤም ማሽን በመትከል አገልግሎት እንደሚሰጥና ከ356 ሺህ በላይ ደንበኞችን የማፍራት እቅድ ይዞ በመሥራት ላይ መሆኑ በጉባኤው ላይ ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የባንኩ ፈስቡክ ገጽ

    ፀሐይ ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝበ ውሳኔ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ይከናወናል – የምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – የደቡብ ኢትዮጵያ ክልልነት ጥያቄ ላይ የሚደረገው ሕዝበ ውሳኔ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ እንዲከናወን ቦርዱ በተገቢው መንገድ ኃላፊነቱን ይወጣል ሲሉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ ተናገሩ።

    በደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በሚገኙ የጋሞ፣ ጎፋ፣ ወላይታ፣ ጌዲኦ፣ ኮንሶ፣ እና ደቡብ ኦሞ ዞኖች እንዲሁም የቡርጂ፣ አማሮ፣ ደራሼ፣ ባስኬቶ፣ እና አሌ ልዩ ወረዳዎች የሚካሄደውን ሕዝበ ውሳኔ ጥር 29 ቀን 2015 ዓ.ም እንደሚከናወን ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል።

    የቦርዱ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ በሰጡት መግለጫ፥ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከጊዜ ወደጊዜ አሠራሩንና ደረጃውን እያሳደገ በመሆኑ ሕዝብ ውሳኔውም በተሻለ ሁኔታ እንዲከናወን ያደርጋል ብለዋል። ሕዝብ ውሳኔው ሰላማዊ፣ ነጻና ገለልተኛ በሆነ መንገድ እንዲከናወን ቦርዱ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ይወጣል ሲሉ ዋና ሰብሳቢዋ ተናግረዋል።

    ሕዝበ ውሳኔው ነጻና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ እንዲከናወን ከሚደረጉ ዝግጅቶች መካከል የምርጫ ጣቢያ አስፈጻሚዎች ምልመላ ሥራ እንደሚገኝበት ብርቱካን ሚደቅሳ ገልጸዋል። ለምልመላ በሚቀርቡ እያንዳንዱ የምርጫ ጣቢያ አስፈጻሚ ላይ ቅሬታ አለኝ ያለ አካል ሪፖርት ማድረግ የሚችልበት አሠራር መዘርጋቱን አስረድተዋል። ከዚህ ቀደም በፖለቲካ ፓርቲ፣ በሲቪክ ማኅበራትና በተቋማት ካልሆነ በቀር በግለሰብ ደረጃ በምርጫ አስፈጻሚዎች ላይ ቅሬታ የሚቀርብበት አካሄድ እንዳልነበር አስታውሰዋል። በሕዝብ ውሳኔው ላይ ግን በምርጫ አስፈጻሚዎች ሥነ-ምግባርና ገለልተኝነት ላይ ጥያቄ አለኝ የሚል ማንኛውም ግለሰብ በማስረጃ በተደረፈ መንገድ ቅሬታውን ማቅረብ እንደሚችልም ጠቁመዋል።

    በእስካሁኑ የአስፈጻሚዎች ምልመላ በስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ የተሳተፉ ዘጠኝ ሺህ አስፈጻሚዎች በደቡብ ኢትዮጵያ የሕዝበ ውሳኔ ላይ በድጋሚ ለማገልገል ፍቃደኛ መሆናቸውን ገልጸዋል ያሉት የቦርዱ ሰብሳቢ፥ በአጠቃላይ 18,750 የምርጫ ጣቢያ አስፈጻሚዎች እንደሚያስፈልጉ አስረድተዋል።

    ቀሪዎቹን የምርጫ አስፈጻሚዎች ለመመልመል ቦርዱ የቅጥር ማስታወቂያ እንደሚወጣ ገልጸዋል። እንደ ብርቱካን ሚደቅሳ ከሆነ፥ ከምልመላ ሥራው ባለፈ ለሕዝበ ውሳኔው መሳካት የሚረዱ የውይይት መድረኮች ከሲቪክና ፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ከማኅበረሰቡና ከሚመለከታቸው የጸጥታ አካላት ጋር ተካሂደዋል።

    በእስካሁኑ የዝግጅት ሥራ የሕዝበ ውሳኔው ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት በአርባ ምንጭ ከተማ ተቋቁሟል። በዞንና በልዩ ወረዳዎች መከፈት ያለባቸው 11 ጽሕፈት ቤቶች እስከትናንትናው ዕለት ድረስ አልተከፈቱም ብለዋል። ለዚህ ደግሞ የየአካባቢው አስተዳደሮች በወቅቱ አስፈላጊውን ትብብር ባለማድረጋቸው የተፈጠረ በመሆኑ አስተዳደሮቹ አስፈላጊውን ትብብር በወቅት እንዲያደርጉ ዋና ሰብሳቢዋ ጥሪ አቅርበዋል።

    በደቡብ ብሔሮች ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በሚገኙ ስድስት ዞኖች እንዲሁም አምስት ልዩ ወረዳዎች የሚገኙ ዜጎች ደቡብ ኢትዮጵያ በሚል አዲስ ክልል እንመስርት፤ አሊያም በነበረው የደቡብ ብሔሮች፣ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልልነት እንቀጥል በሚል ሕዝብ ውሳኔውን ያደርጋሉ።

    ለሕዝበ ውሳኔው በመራጭነት ሊመዘገቡ የሚችሉ ግምታዊ መራጮች ሦስት ሚሊዮን 106,585 ሰዎች መሆናቸውን ቦርዱ አሳውቋል። ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለሚያካሂደው ሕዝበ ውሳኔ ማስፈጸሚያ 410.1 ሚሊዮን ብር ከመንግሥት ተፈቅዷል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት 

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ

    Anonymous
    Inactive

     ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የምርጫ ውጤት

    ሰኔ 14 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. የተካሄደው የስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውጤት ይፋ ተደረገ። ይህ ውጤት የሚገለፀው ባገኙት ወንበር ልክ ሲሆን በዚህም መሠረት፦

    • የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር
      – መስተዳድሩ ያለው የተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ: 23
      – ሰኔ 14 ቀን ምርጫ የተከናወነበት የተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልል ብዛት: 23
      □ ብልፅግና ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 22
      □ የግል ተወዳዳሪ ያገኘው መቀመጫ: 1
    • የአፋር ብሔራዊ ክልል
      – ክልሉ ያለው የተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ: 8
      – ሰኔ 14 ቀን ምርጫ የተከናወነበት የተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልል ብዛት: 6
      □ ብልፅግና ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 6
    • የአማራ ብሔራዊ ክልል
      – ብሔራዊ ክልሉ ያለው የተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ: 138
      – ሰኔ ቀን ምርጫ የተከናወነበት የተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልል ብዛት: 125
      □ ብልፅግና ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 114
      □ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 5
      – ድጋሚ ቆጠራ የሚከናወንበት ምርጫ ክልል ብዛት: 1
      – ድጋሚ ምርጫ የሚከናወንበት ምርጫ ክልል ብዛት: 5
    • የቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ብሔራዊ ክልል
      – ብሔራዊ ክልሉ ያለው የተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ: 9
      – ሰኔ 14 ቀን ምርጫ የተከናወነበት የተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልል ብዛት: 3
      □ ብልፅግና ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 3
      – ድጋሚ ምርጫ የሚከናወንበት ምርጫ ክልል ብዛት: 2
    • የድሬዳዋ ከተማ መስተዳድር
      – መስተዳድሩ ያለው የተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ: 2
      – ሰኔ 14 ቀን ምርጫ የተከናወነበት የተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልል ብዛት: 2
      □ ብልፅግና ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 1
      – ድጋሚ ቆጠራ የሚከናወንበት ምርጫ ክልል ብዛት: 1
    • የጋምቤላ ብሔራዊ ክልል
      – ብሔራዊ ክልሉ ያለው የተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ: 3
      – ሰኔ 14 ቀን ምርጫ የተከናወነበት የተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልል ብዛት: 3
      □ ብልፅግና ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 3
    • የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልል
      – ብሔራዊ ክልሉ ያለው የተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ: 178
      – ሰኔ 14 ቀን ምርጫ የተከናወነበት የተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልል ብዛት: 170
      □ ብልፅግና ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 167
      □ የግል ተወዳዳሪዎች ያገኙት መቀመጫ: 3
    • የሲዳማ ብሔራዊ ክልል
      – ብሔራዊ ክልሉ ያለው የተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ: 19
      – ሰኔ 14 ቀን ምርጫ የተከናወነበት የተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልል ብዛት: 19
      □ ብልፅግና ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 19
    • የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ብሔራዊ ክልል
      – ብሔራዊ ክልሉ ያለው የተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ: 104
      – ሰኔ 14 ቀን ምርጫ የተከናወነበት የተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ክልል ብዛት: 85
      □ ብልፅግና ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 75
      □ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ፓርቲ ያገኘው መቀመጫ: 4
      □ የጌዴኦ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ድርጅት: 2
      – ድጋሚ ቆጠራ የሚከናወንበት ምርጫ ክልል ብዛት: 1
      – ድጋሚ ምርጫ የሚከናወንበት ምርጫ ክልል ብዛት: 3

    በዚህ ሐምሌ 3 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ይፋ ባደረገው የምርጫ ውጤት መሠረት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመቀመጫ ብዛት በአጠቃላይ 484 ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ በስልጣን ላይ የሚገኘው ብልፅግና ፓርቲ 410 መቀመጫ አሸንፏል። ይህም ውጤት ፓርቲውን መንግሥት ለመመሥረት ያስችለዋል።

    ይህን የምርጫ ውጤት እና የፓርቲያቸው ማሸነፍን ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ያስተላለፉትን መልዕክት ለማንበብ እዚህ ጋር ይጫኑ

    የምርጫ ክርክር የምርጫ ውጤት

    Anonymous
    Inactive

    “በዚህ ሀገራዊ ምርጫ የፈጠርነው አሸናፊና ተሸናፊን ሳይሆን፣ ጠያቂና ተጠያቂ ያላበት የዲሞክራሲ ሥርዓትን ነው። በዚህ ደግሞ ያሸነፉት በምርጫው የተሳተፉት ሁሉም አካላት ናቸው።” ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ስድስተኛው የስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ውጤትን ያስተላለፉት መልዕክት

    የተከበራችሁ ኢትዮጵያውያን እና ኢትዮጵያውያት፥

    ላለፈው ግማሽ ክፍለ ዘመናት፣ የሀገራችን ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ በነጻ ፈቃዱ የመረጠው መንግሥት እንዲኖረው ብዙ ሙከራዎች ሲደረጉ ቢቆዩም፤ በተለያዩ ምክንያቶች ሲሰናከሉ ነበር። በሂደቱ አያሌ ተማሪዎችና ወጣቶች፣ ገበሬዎችና የቤት እመቤቶች፣ ምሁራንና መለዮ ለባሾች፣ መላው የሀገራችን ሕዝብ ከፍተኛ ዋጋ ከፍሏል። ካለፈ ልምዳችንና ባልተሳኩ ጉዞዎች ጠባሳ ሰበብ፣ የአሁኑም ምርጫ ዴሞክራሲያዊነቱ ተጠብቆ ባይጠናቀቅስ በሚል ስጋት፣ ያለፉትን ወራት እንደ ሀገር በፍርሃት ተወጥረን መክረማችን ሊካድ አይችልም። ኢትጵያውያን ግን ጨዋ ብቻ ሳይሆኑ አርቆ አሳቢ መሆናቸውን ዛሬም አስመስክረዋል። የተሰጋውን ሳይሆን የሚፈልጉትን ማድረግ እንደሚችሉ በግብር አሳይተዋል። ዝናብና ፀሐይ ሳይገድባቸው፣ በረጃጅም ሰልፎች ሳይሰለቹ፣ እስከ እኩለ ሌሊት ታግሰው ፍላጎታቸውን በካርዳቸው ገልጸዋል። እንደ እኛ እምነትም በዚህ ምርጫ አሸናፊ የሆነው ሕዝባችን ነው። ከሕዝባችን በመቀጠል፣ በብዙ ውሱንነቶች ውስጥ አልፈው በዲሞክራሲና በሕዝብ ድምፅ ላይ ባላቸው ጽኑ እምነት፣ ሀሳብና ፖሊሲያቸውን ለሕዝብ አቅርበው ብርቱ ውድድር ያደረጉ ተፎካካሪ ፓርቲዎች የዴሞክራሲያዊ ሂደቱ ድል አድራጊዎች ናቸው።

    ይህንን ምርጫ ልዩና ታሪካዊ የሚያደርጉት ብዙ ጉዳዮች አሉ። በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ ከተጽዕኖዎች በተላቀቀ የምርጫ ቦርድ ዳኝነት ያደረግነው ምርጫ መሆኑ አንደኛው ነው። የምርጫ ቦርድ ዳኝነት እንዲሳካ ደግሞ ቁጥራቸው የበዙ የግልና የመንግሥት ሚዲያዎች፣ የሲቪል ተቋማት፣ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን፣ ፍርድ ቤቶችና ሌሎችም ተቋማት በግልጽ የተከታተሉት መሆኑ ሂደቱን ከመቼም ጊዜ በላይ ተአማኒና ዲሞክራሲያዊነቱ የተጠበቀ ምርጫ ያደርገዋል። ምርጫው ዴሞክራሲን የመትከል ግባችንን አንድ እርምጃ ያስኬደ በመሆኑ፣ ፓርቲያችን ከምንም በላይ ቀዳሚ ድሉ አድርጎ ይቆጥረዋል። በታሪካዊው ምርጫ ተሳታፊ መሆን በራሱ የሚፈጥረው ደስታ እንዳለ ሆኖ፣ ፓርቲያችን በሕዝብ ይሁንታ አግኝቶ ሀገር ለማስተዳደር መመረጡ አስደስቶናል። በውጤቱም ከአሸናፊነት ይልቅ ኃላፊነት፣ ከድል አድራጊነት ይልቅ ታላቅ የሆነ ሀገራዊ አደራ እንዲያድርብን አድርጎናል።

    መንግሥት የሚመሠረተው በሕዝብ በተመረጡ ፓርቲዎች ቢሆንም ሀገርን መምራትና ማስተዳደር ግን ለተመረጡ ፓርቲዎችና መሪዎች ብቻ የሚተው አይደለም። ተፎካካሪ ፓርቲዎችና መሪዎቻቸውም እስከሚቀጥለው ምርጫ በመንግስት አስተዳድርና ሕዝብን በማገልገል ሂደት ውስጥ ሚናቸው ሰፊ ሊሆን እንደሚገባ ለማስታወስ እወዳለሁ። በቀጣይ ወራት ብልጽግና በሚመሠርተው መንግሥት ውስጥ በአስፈጻሚው አካልም ሆነ በፍርድ ቤቶች፣ በሌሎችም የፌደራልና የክልል ተቋማት ላይ ንቁ ተሳትፎ እንዲኖራቸው፣ በዘንድሮው ምርጫ በኃላፊነትና በብቃት የተወዳደሩ የሕዝብ አለኝቶችን ከዚህ በፊት ካደረግነው በእጅጉ ከፍ ባለና አዎንታዊ ለውጥ በሚፈጥር መልኩ እንደምናካትታቸው ለመግለጽ እወዳለሁ። በተጨማሪም እስከሚቀጥለው ምርጫ የበለጠ ተጠናክረውና ተቋማዊ አቅማቸው ደርጅቶ ብርቱ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ ከማድረግ ወደ ኋላ አንልም። በዚህ ምርጫ የፈጠርነው አሸናፊና ተሸናፊን ሳይሆን፣ ጠያቂና ተጠያቂ ያላበት የዲሞክራሲ ሥርዓትን ነው። በዚህ ደግሞ ያሸነፉት በምርጫው የተሳተፉት ሁሉም አካላት ናቸው።

    ውድ የኢትዮጵያ ልጆች፥

    በምርጫ ካርዳችሁ ስትመርጡን በዕቅድና በፖሊሲ የያዝናቸውን የብልጽግና ግቦች እንድናሳካ የድፍረትና የጥንካሬ ስንቅ እንደሚያቀብለን ሁሉ፣ እኛና እናንተን ያስተሳሰረው ቃል ኪዳን ተጠብቆ እንዲቆይ ነገሮች አልጋ በአልጋ እንደማይሆኑን እንገነዘባለን። ቢሆንም ግን ከመቼውም ጊዜ በላይ ትከሻችንን አስፍተን፣ ኢትዮጵያን ከሚወዱ አካላት ጋር ሁሉ በትብብር ዐቅማችን አማጥጠን ለመሥራት ቆርጠን እንደተነሣን ሳበስራችሁ ደስ እያለኝ ነው። በቀጣይ ዓመታት ሀገራችን በእውነትም በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ከፍ የምትልበት ዘመን ይሆናል። ይህ እንዲሳካ የሐሳብና የሞራል ስንቅ እንደምታቀብሉን፣ መንገድ ስንስት እንደምትመልሱን፣ ስናጠፋም እንደምታርሙን ተስፋ በማድረግ ነው።

    በሀገራችን ሁለንተናዊ ብልጽግና እውን እንዲሆን በቀጣዩ አምስት ዓመት ፈር ጠራጊ እንሆናለን የምንለው፣ በዙሪያችን ባሉና ብልጽግና በሚቀላጠፍባቸው አራት ማዕዘኖች መሐል ቆመን ነው። የመጀመሪያው ማዕዘናችን የመሠረተ ልማት ግንባታ ሲሆን፥ ሀገራችን እንድትበለጽግ በኢኮኖሚውም ሆነ በማኅበራዊና ፖለቲካ ዘርፎች ዘላቂ መሠረት የሚሆኑ፣ በፍጥነት የሚጠናቀቁ፣ ጥራታቸው የተጠበቁ፣ ከብክነት ነጻ የሆኑ እና የምንፈጥራቸውን ተቋማት መሸከም የሚችሉ ትውልድ ተሻጋሪ መሠረተ ልማቶችን መገንባታችንን እንቀጥላለን። ጥቂትም ቢሆኑ ባለፉት 3 ዓመታት አመርቂ ሥራዎችን ለመሥራታችን ምስክሮቹ እናንተው ናችሁ።

    ሁለተኛው ማዕዘናችን የተቋማት ግንባታ ሲሆን፣ በጥቂት ግለሰቦችና ነጠላ ተቋማት ላይ ከማተኮር ባለፈ ሀገራችንን በጽኑ መሠረት ላይ የሚያቆሙ ጠንካራ ተቋማት ያስፈልጉናል። ዘመን ተሻጋሪ ሥርዓት ለማጽናት የሚስችሉ ገለልተኛና ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የሚያገለግሉ ተቋማትን መገንባት ላይ ትኩረት ይደረጋል። ይሄ ማሕቀፍ ከፌደራል እስከ ክልል የሚገኙ ተቋማትን የሚያካትት ይሆናል።

    በሦስተኛ ደረጃ እንደ ሀገር የሚያስተሳስሩን የጋራ አመለካከቶችና የጋራ ትርክቶች ላይ ትኩረት ሰጥተን ልንሠራባቸው ይገባል። እርስ በእርስ የሚቃረኑና የሚጠፋፉ ትርክቶች ምን ያህል ለጠላቶቻችን ተመችቷቸው እኛን ደካማ እንዳደረገን ያሳለፍናቸው ዓመታት ሕያው ምስክሮች ናቸው። ስለዚህ ክፍተቶቻችንን በሚደፍን መልኩ ብቻ ሳይሆን እንደ ሀገር አጠንክረው በሚያቆሙን እሴቶች ላይ የተመሰረተ፣ ገዢና ሁላችንንም አሸናፊ የሚያደርግ ትርክት ለመገንባት ጠንክረን እንሠራለን።

    በአራተኛ ደረጃ የሞራል ልዕልናና ግብረገባዊነት ተመጣጣኝ ትኩረት አግኝተው እስካልተሠራባቸው ድረስ በሀገራችን ኃላፊነት የሚሰማቸው ዜጎች ቁጥር እየቀነሰ፣ በተቃራኒው ኢ-ሞራላዊ ድርጊቶች እየተስፋፉ እንዲመጡ በር ይከፍታል። ይኼንን ችግር የመቅረፍ ኃላፊነት መንግሥትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ላይ ብቻ የሚጣል ሳይሆን፣ ከግልና ከቤተሰብ ጀምሮ የሚሠራ ሥራ ነው። ሁሉም አካላት ተረባርቦ ሀገርና ትውልዱን እያቆሸሹ ያሉ መጥፎ ተግባሮችን ጠርጎ ሊጥላቸው ይገባል። በቀጣይ ዓመታት በሞራል ንጽህና የተገነቡ ተቋማትንና መሪዎችን አንጥረን የምናወጣበት እንዲሆን ተስፋ አደርጋለሁ።

    ውድ የሀገሬ ዜጎች፥

    ባለፉት ሦስት ዓመታት በከፍተኛ ጥንቃቄ የቀረጽነው የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለተግባራዊነቱ በጋራ ከተጋን ያለ ጥርጥር ቀጣዩቹ ዓመታት ለሀገራችን ብልጽግና እንደ ወሳኝ የመታጠፊያ ኩርባ ይሆናል። ዕምቅ ዐቅሞቻችን ምንድን ናቸው? ምን ዓይነት የመበልጸግ ዕድል እጃችን ላይ አለ? ምን ብናደርግ ኢኮኖሚያችን መዋቅራዊ ለውጥ ያመጣል? የሚሉትን በሚገባ ፈትሸን ያረቀቅነው ዕቅድ ነው።

    በሀገራችን ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ለነገ የማይባል ጉዳይ ነው። በፍጥነት የምግብ ፍላጎታችንን በማሟላት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከውጭ የምግብ ድጎማ መላቀቅ አለብን። ምግብ ለእኛ ቅንጦት መሆን አይገባም። ጠግቦ መብላት ቅንጦት የሆነበት ሕዝባችንን መርጦ መብላት እንዲጀምር ለማድረግ ቆርጠን መነሳት አለብን። በብዝኃ ዕጽዋትና በብዝኃ እንስሳት የምትታወቅ ሀገራችን የእንስሳት ተዋጽዖና ፍራፍሬዎች ለገበታችን ከቅንጦትነት ወደ አዘቦትነት መለወጥ አለባቸው። ዶሮና ዕንቁላል፣ ወተትና ቅቤ፣ ተርፎን ለገበያ የምናቀርባቸው እንጂ ለዓመት በዓል አይተናቸው የሚሰወሩ የሩቅ እንግዳ መሆናቸው ሊያከትም ይገባል።

    እዚህ ጋር አንድ መታወቅ ያለበት ሀቅ አለ። መንግስትና ሕዝብ እጅና ጓንት ሆነው እስካልሠሩ ድረስ ሕልማችን ይሳካል ማለት ዘበት ነው። በቀጣይ 5 ዓመታት ተባብረን በተለይ በግብርናው ዘርፍ ምርታማነት ለማሳደግ ጠንክረን መስራት አለብን። ከዚህ ቀደም ጀምረናቸው ውጤት እያመጡ ያሉ ተግባራት አሉ። የበጋ ሰብሎችና ፍራፍሬዎች ላይ ለውጥ ለማምጣት ከተጀመሩ አነስተኛ መስኖዎች ባለፈ፣ ዝናብ አጠርነት ለመዋጋት በቴክኖሎጂ አማካኝነት ደመናን ወደ ዝናብ የመቀየር ልምምዳችን እያደገ ይገኛል። በቅርቡም ምርትን የሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመን ችግሮቻችንን ወደ ዕድል መቀየር ጀምረናል።

    አየር ንብረታችንን የሚያስተካክለውና የብዝኃ ዕጽዋትና የብዝኃ እንስሳት ሀብታችንን በእጅጉ ያሳድጋል ተብሎ ተስፋ የተጣለበት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብራችን እንዲሁ ተጠቃሽ ነው። በቁጥር ግንባር ቀደም ያደረጉን የቀንድ ከብቶቻችን ከመቀንጨር ወጥተው ምርታማ እንዲሆኑ ያደርጋል። ወደየጎረቤት ሀገሩ የሸሹ የዱር አራዊትም ተመልሰው፣ ከታሪካዊና ባህላዊ መስህቦች ጋር የተዋደደ ተፈጥሮአዊ መስህብ በመሆን የቱሪስት ፍስትን እንዲጨምርና ኢኮኖሚያችን መስፈንጠር እንዲችል መደላድል ይሆናል ብዬ አምናለሁ።

    የሀገራችን ሕዝብ ሆይ፥

    ባለፉት ጥቂት ዓመታት ትኩረታችንን ሰቅዘው ከያዙት ጉዳዮች መካከል ሌላኛው የሕዳሴ ግድብን የተመለከተ ጉዳይ ነው። የዴሞክራሲ ጥያቄን አንድ ምዕራፍ ለማሳደግ የምርጫችን መሳካት ወሳኝ እንደነበረው ሁሉ፣ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ችግራችንን ለመቅረፍና ለዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች መቀላጠፍ ጉልህ አስተዋጽዖ ከሚያበረክቱ ፕሮጀክቶቻችን መካከል አንዱና ወሳኙ የሕዳሴ ግድብ ግንባታችን እንደሆነ ይታወቃል።

    የሕዳሴ ግድብ አጀንዳ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ከግድብም፣ ከኤሌክትሪክ ኃይል ምንጭነትም በላይ ነው። ከኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ባለፈ ዳግም የመነሣታችን ተምሳሌት ነው። በራስ ዐቅም የመቆም፣ በራስ ፍላጎት የመመራት፣ የሉዓላዊነታችን ምልክት፤ የሀገራዊ አንድነታችን ገመድ ነው። በሕዳሴ ጉዳይ ብዙ አይተናል፣ ብዙ ተፈትነንበታል። በራሳችን ዐቅም መቆማችን የሚያስደነግጣቸው፣ በፍላጎታችን መመራት መጀመራችን የሚቆጫቸው ብዙ ጋሬጣዎችን ሲጥሉብን ነበር። “ሚስማር አናቱን ሲመቱት ይበልጥ ይጠብቃል” እንዲሉ ሆኖ፤ በዓባይ ጉዳይ በገፉን ቁጥር እየቆምን፣ በተጫኑን ቁጥር እየበረታን፣ ባዋከቡን ቁጥር ይበልጥ እየጸናን አሁን የደረስንበት ቦታ ላይ ቆመናል። በቅርቡ ሁለተኛውን ዙር የውኃ ሙሌት አድርገን፣ በምርጫው ስኬት የተደሰትነውን ያህል፣ በሕዳሴያችንም ሐሴት እንደምናደርግ አልጠራጠርም።

    በሕዳሴ ግድብ ላይ ፍትሐዊ ተጠቃሚነታችን እንዲጠበቅልን እንጂ መቼም ቢሆን ሌሎች ሀገራትን የመጉዳት ፍላጎት ኖሮን አያውቅም። አሁንም ለታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ደግመን ማረጋገጥ የምንፈልገው ሐቅ፣ የዓባይ ወንዝ እንደሚያስተሳስራቸው ወንድም ሕዝቦች በእናንተ ላይ ምንም ዓይነት አሉታዊ ተጽዕኖ የመፍጠር ፍላጎት የለንም። ዛሬም ሆነ ወደፊት በጋራ ተጠቃሚነት ዙሪያ ለመመካከር በራችን ክፍት ነው። እኛንም ሆነ እናንተን ነጥሎ ተጎጂ ወይም ተጠቃሚ በሚያደርጉ አካሄዶች ላይ እንድንሳተፍ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን አይፈቅም።

    ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያለንም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ከዚህ ኢትዮጵያዊ ማንነታችን የሚቀዳ ነው። በጋራ ተጠቃሚነት ዙሪያ ለመሥራት ሁሌም ዝግጁዎች ነን። የአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ሰላሙ እንዲጠበቅ፣ የጋራ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ማኅበረሰብ እንዲፈጠር፣ በትብብርና በመግባባት እንድናድግ ኢትዮጵያ ትፈልጋለች፤ ጥሪም ታቀርባለች።

    የተከበራችሁ ተፎካካሪ ፓርቲዎች፥

    የሀገራችን መጻኢ ጊዜ ብሩህ ለማድረግ በተገቢው መወጣት ከሚገቡን የቤት ሥራዎች መካከል አንዱና ዋነኛው ፖለቲካዊ ጉዳዮቻችንን በሠለጠነ መንገድ መምራት ነው። ከላይ በመግቢያዬ እንደገለጽኩት ይኼ ኃላፊነት በመንግሥትና በተመረጠው ፓርቲ ላይ ብቻ የሚጣል አይደለም፤ አንድ አካል ልሥራው ብሎ ቢነሣ እንኳን በአግባቡ የሚወጣው ጉዳይ እንዳልሆነ በተደጋጋሚ አይተናል። እንኳንስ የሠለጠነ የፖለቲካ ሥርዓት መገንባትን የሚያህል ነገር ይቅርና፣ አንድ ዙር ምርጫን ዴሞክራሲያዊ አድርጎ ለማጠነቀቅ ብዙ አካላት መረባረብ እንዳለባቸው ካለፍናቸው ምርጫዎች በሚገባ ተረድተናል። የዘንድሮውንም ምርጫ ካለ እናንተ ድጋፍና ትብብር ፍትሐዊና ዴሞራሲያዊ በሆነ መንገድ ማከናወን ባልተቻለ ነበር።

    በቀጣይም ዓመታት የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ሂደታችን መሬት እንዲረግጥ የተለመደ ትብብራችሁና በየምዕራፉ ያላሰለሰ ድጋፋችሁ እንደሚያሻን ከወዲሁ ለመግለጽ እወዳለሁ። በሀገራችን የብልጽግና ጉዞ ውስጥ የሚኖራችሁ ድርሻ ወሳኝ እንደሆነ እናምናለን።

    የፖለቲካ ልዩነቶቻችን እንዳሉ ሆነው፣ ለሀገርና ለሕዝባችን በሚጠቅሙ ማናቸውም የፖለቲካና ኢኮኖሚያዊ አጀንዳዎች ላይ ከእናንተ ጋር በመግባባት ለመሥራት ዝግጁዎች ነን።

    ምርጫውን ስኬታማ ያደረጋችሁ ውድ የተቋማት አመራሮችና ሠራተኞች፣

    ይህ ምርጫ የተሳካ እንዲሆን የምርጫ ቦርድ አመራሮችና ሠራተኞች፣ እንዲሁም የምርጫ አስፈጻሚዎችና ታዛቢዎች ሁሉ ከደም መሥዋዕትነት በመለስ ያለ ከፍተኛ ዋጋ ከፍላችኋል። ከግራ ከቀኝ የሚመጡትን ጫናዎች ተቋቁማችሁ በውጣ ውረዶች ሳትበገሩ ለሀገራችን የማይደበዝዝ የዴሞክራሲ አሻራ አትማችኋል፤ በዚህም ታሪክ ስማችሁን አድምቆ ይጽፈዋል።

    የጸጥታ አካላት፤ ምርጫው ሰላማዊ እንደሆን ጉልህ ሚና ተጫውታችኋል፤ እናንተ ዕንቅልፍ አጥታችሁ ሥጋቶቻችን ሁሉ እንደ ጉም እንዲተንኑ ስላደረጋችሁ ክብር ይገባችኋል። በተመሳሳይ፣ ፈጣንና ሚዛናዊ መረጃን ወደ ሕዝቡ በማድረስ በኩል የግልና የመንግስት ሚዲያዎች፤ እንዲሁም አጭር የጽሑፍ መልዕልት ስርጭት በኩል የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ሠራተኞች፣ ላበረከታችሁት አስተዋጽዖ ኢትዮጵያ ታመሰግናችኋለች።

    ውድ የፓርቲያችን አመራሮችና አባላት፥

    በዚህ ምርጫ ሕዝቡ ያስተላለፈውን መልእክት በሚገባ መረዳት የወደፊቱን መንገዳችንን ቀና እንደሚያደርገው እናምናለን። ሕዝቡ በአብላጫ ድምጽ እኛን የመረጠው ፓርቲያችን እንከኖች ስለሌሉበት አይደለም፤ ከነስሕቶቻችንን ዕድል ሰጠን እንጂ ድል አላደረግንም። ሕዝብ የመረጠን በአንድ በኩል ያጠፋናቸውን እንድናርም፣ በሌላ በኩል መልካም ጅማሮዎቻችንን እንድናስቀጥል፣ ከሀገር ግንባታ አንጻር በወሳኝ ደረጃ ላይ ያሉ የለውጥ ሥራዎችን በቀጣይ ጊዜያት ፈጽመን እንድናሰረክብ ነው። ሕዝባችን ጉድለቶቻችንን በሚገባ ያውቃል። ከስርቆት ዓመል ያልተላቀቁ፣ ለሰው ነፍስ ግድ የሌላቸው፣ ሕግን የማያከብሩ፣ ኃላፊነታቸውን የማይወጡ አመራሮች በመካከላችን መኖራቸውን ጠንቅቆ ያውቃል። ድምፁን ሲሰጠን ታረሙ፣ ውስጣችሁን አጥሩ እያለን ጭምር ነው። እኛም በተግባር ሆነን ማሳየት አለብን። ይኼን ማድረግ ካልቻልን ከአምስት ዓመት በኋላ በካርዱ እንደሚቀጣን እናውቃለን።

    በአሁኑ ምርጫ መምረጥ ያልቻላሁ ወገኖቻችን በሙሉ፥

    በልዩ ልዩ የጸጥታና የደኅንነት ምክንያቶች፣ እንዲሁም በሎጅስቲክና በተለያዩ ውሱንነቶች ምርጫው በተያዘለት ክፍለ ጊዜ መሠረት ከተቀረው ሕዝብ ጋር አብራቸሁ ድምፅ ባለመስጠታችሁ ታላቅ የሆነ ቅሬታ ፈጥሮብናል። ይኼ የሆነው ባልተጠበቁ ምክንያቶች እንደሆነ ግንዛቤ ትወስዳላችሁ የሚል ግምት አለን። ሁኔታዎች ተስተካክለው የምርጫ ቦርድ በወሰነው ቀን ምርጫው እንደሚደረግ እምነቴ ነው።

    ትግራይን በተመለከተ የትግራይ ሕዝብ በሚፈልገው መንገድ ከተደራራቢ ችግር የሚወጣበትን፣ ተያያዥ ሀገራዊ ችግሮች የሚፈቱበትን እና ሰላምና ደኅንነት የሚረጋገጥበትን የመፍትሔ አቅጣጫ እንከተላለን።

    በመጨረሻም፣ ከለውጡ ጊዜ አንሥቶ እስከ ዛሬ ድረስ ስለ ሀገር አንድነትና ስለ ሕዝባችን ተጠቃሚነት ቀና ቀናውን በማሰብ በመንገዳችን ሁሉ ድጋፍ ሲያደርጉልን የነበሩ አካላትን ከልብ ሳላመሰግን አላልፍም። ኢትዮጵያ በታሪክ ለውጥ ላይ ናት። በዚህ የለውጥ ሂደት ተሳፍረን የተሻለች ሀገር እንገነባለን። በዚህ ምርጫ ኢትዮጵያችን አሸናፊ ስለሆነች በድጋሚ ለመግለጽ እወዳለሁ። ቀጣይ ዘመናችንን ብሩህ ያድርግልን፤ ሁላችንም እንኳን ደስ አለን።

    ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!
    ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ!
    ሐምሌ፣ 2013 ዓ.ም

    • በስድስተኛ ጠቅላላ ሀገራዊ ምርጫ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ብልጽግና ፓርቲ 410 መቀመጫዎችን ማሸነፉን የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሐምሌ 3 ቀን  2013 ዓ.ም. አስታውቋል። ዝርዝሩን ለማንበብ እዚህ ጋር ይጫኑ
    • የስድስተኛው ጠቅላላ ሀገራዊ ምርጫ ውጤት መታወቅን ተከትሎ የኢፌዴሪ ፕሬዝደንት ወ/ሮ ሳህለወርቅ ዘውዴ “ኢትዮጵያ ሀገራችን ተከብራ የምትኖረው ስንቻቻል፣ ስንደማመጥና የሌላውን ሃሳብ ስንቀበል ብቻ ነው” በማለት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
    • ይህ ሀገራዊ ምርጫ በተሳካ ሁኔታ እንዲካሄድ ትልቁን ሚና የተጫወተውን የብሔራዊ ምርጫ ቦርድን የሚመሩት ወ/ት ብርቱካን ሚደቅሳ “ሀገራዊ ምርጫው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ገለልተኝነት በይፋ የታየበት ነው” ብለዋል።

    ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ

    Anonymous
    Inactive

    ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን ) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ
    ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣
    ለሁሉም የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኃይሉች፤
    የኢትዮጵያ ጉዳይ ለሚያሳስባችሁ አፍሪካውያን ወንድሞቻችንና ዓለምአቀፍ አጋሮቻችን፤
    በመላው ዓለም ለምትገኙ ሰላም ወዳድ ኃይሎች በሙሉ !

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በሰኔ 26 እና 27 ቀን 2013 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ጥልቅና ዙሪያ መለስ ውይይት በማድረግና፤

    • የሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ፖለቲካ መሠረት ለመጣልና በሕዝብ ይሁንታ ብቻ ሥልጣን የሚይዝ ሥርዓት ለመፍጠር የተደረገውን 6ኛውን ሀገራዊ የምርጫ ሂደት በመገምገም፤
    • የታላቁን የአባይ ግድብን በማጠናቀቅና እንደ ሀገር የተፈጥሮ ፀጋችንን ተጠቅመን የመልማት መብታችንን ለማረጋገጥ በተያያዝነው ጥረት ረገድ የተጋረጡብንን ተግዳሮቶች በመገንዘብ፤
    • ሕዝባችን በሰላምና ደህንነት እጦት፣ በኮቪድ-19 ወረርሽኝና መረን በለቀቀ የኑሮ ውድነት እየደረሰበት ያለውን ምጣኔ ሀብታዊ ድቀት ግምት ውስጥ በማስገባት፤
    • ከሁሉም በላይ ሀገራችን ከውስጥ በከሃዲያንና እኩያን ኃይሎች ቅንጅት፣ ከውጭ በታሪካዊ ጠላቶቻችንና ዓለምአቀፍ አጋሮቻቸው አይዞህ ባይነትና ድጋፍ የተደቀነባትን የህልውና ስጋት ተቀዳሚ ትኩረት በመስጠት፤

    የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ የደረሰባቸውን አቋሞች ለተከበረው ሕዝባችን፣ ለአፍሪካውያን ወንድሞቻችንና በአጠቃላይም ለዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ ለማሳወቅ ይወዳል።

    1. ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ በተመለከተ

    አብን እንደ ድርጅት የመጀመሪያው አብይ የፖለቲካ ተመክሮው በሆነው በ6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ውስጥ ለመሳተፍ ሲያቅድ፥ ገና ከመነሻው ሀገራችን የምትገኝበትን የፖለቲካ አውድ በመገምገም በምርጫው የመሳተፉን ውሳኔ ያደረገው በዋነኝነት ከድርጅታዊ ፋይዳዎች ይልቅ ለሀገራዊ ፖለቲካው መረጋጋትና ለዴሞክራሲያዊ ተመክሮ ግንባታ ከሚኖረው ፋይዳ አንፃር እንደሆነ በይፋ አሳውቋል።

    አብን ሀገራዊ ፓርቲ እንደመሆኑ መጠን የምርጫ ዘመቻውን ስትራቴጂክ ግቦችና ማስፈፀሚያ ስልቶችን በዝርዝር በመንደፍ፣ አማራጭ ፖሊሲዎቹን በማኒፌስቶ በመሰነድና ሙሉ ድርጅታዊ ኃይሉን በማንቀሳቀስ በምርጫ በሚሳተፍባቸው በአማራና ሌሎችም የሀገሪቱ ክፍሎች 510 እጩዎችን በማቅረብ ሰፊውን መራጭ ሕዝብ ለመድረስ ያልተቆጠበ ጥረት አድርጓል።

    በዚህም መሠረት የምርጫ ዘመቻው ከነተግዳሮቶቹ ተጠናቅቆ፣ በሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም ፓርቲያችን በሚወዳደርባቸው ክልሎች ድምፅ ተሰጥቶና በከፊል ጊዜያዊ ውጤት ተገልጾ በድኅረ ምርጫ ሂደት ላይ እንገኛለን።

    ፓርቲያችን በመላ ሀገሪቱ በተወዳደረባቸው አካባቢዎች በምርጫው ሂደት የተፈፀሙትን አበይት ጥሰቶች በማሰባሰብና በዝርዝር ቅሬታዎችን በመሰነድ በህግ አግባብ ለብሄራዊ ምርጫ ቦርድ አቅርቧል። የምርጫ ቦርድ ከተጣለበት ታላቅ ሀገራዊ ኃላፊነት አኳያ ከሰው፣ ከፋይናንስ፣ ከተመክሮና ከሎጂስቲክ አቅም ውሱንነት ቢታይበትም በአጠቃላይ ከቅድመ ምርጫው ጀምሮ አንፃራዊ አዎንታዊነት እንዳሳየ እናምናለን። በቦርዱ የበላይ አመራር የታየው ገለልተኝነት፣ ግልፅነትና ፍትሃዊነት መንፈስ እንደ ተቋም የሚፈተንበት ወቅት እንደሆነም እንገነዘባለን።

    የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ ሕዝባችን ይህንን ሁሉ ጫና ተቋቁሞ በምርጫው ሂደት ውስጥ በመሳተፍ ላሳየው ፅናት ልባዊ አድናቆቱን በመግለፅ፣ የመራጩ ድምፅ እንዲከበር ተገቢውን ሰላማዊና ህጋዊ ጥረት እንደሚያደርግና የሕዝባችንንም ሀቀኛ ውሳኔ ያለማወላወል እንደሚቀበል ለማሳወቅ ይወዳል።

    በሌላ በኩል 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ የሥርዓቱን እውነተኛ ባህርይ በተግባር መፈተንና ማጋለጥ መቻሉን ትልቁ ውጤት አድርጎ መውሰድ ይቻላል። በምርጫው ሂደት የታየው ጎዶሎነትና ክፍተት ከምርጫ ውጤት አኳያ የምንመዝነው ከሆነ የሀገራችንን ተጨባጭ ሁኔታና የሃሳብ ብዝሃነት የማያመለክት መሆኑን መናገር ይቻላል።

    አብን እንደ ድርጅት በምርጫ በመሳተፉ ምን አገኘ፣ አሳካ የሚለውን ስንገመግም አንዳንድ ተስፋ ሰጭ ነገሮች እንዳሉ መካድ አይቻልም። ከሁሉም በላይ የሕዝባችን እውነተኛ ወኪል ስለመሆናችን ሕዝባችን የነበሩትን ጫናዎች ተቋቁሞ በሰጠን የመተማመኛ ድምፅ በቂ ማረጋገጫ አግኝተናል። ይህም የመጪው ዘመን ፓርቲ መሆናችንን ይመሰክራል። በሐገር አቀፍ ድረጃ በተሻለ ሕዝብን የማስተባበር አቅም እንዳለንና ጠንካራ ተገዳዳሪ የፖለቲካ ኃይል መሆናችንን በማያሻማ ሁኔታ አረጋግጠናል።

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ የምርጫው ሂደት አጠቃላይ ድርጅታዊ ቁመናውን የሚፈትሽበት መልካም አጋጣሚ መሆኑንም ይገነዘባል። በቀጣይም ከሂደቱ ያገኛቸውን ተመክሮዎችና ትምህርቶች በማካተትና ሁለገብ የማሻሻያ እርምጃዎች በመውሰድ ለብሔራዊ ፖለቲካችን ሁነኛ ሚና መጫወቱን እንደሚቀጥል አያጠራጥርም።

    1. ብሔራዊ ደህንነትን በተመለከተ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በተለይ በሀገር ሉዓላዊነትና አንድነት፣ በሕዝብ ጥቅምና ክብር፣ በሀገረ መንግሥቱ ቀጣይነት ረገድ ግልፅና የማያሻማ አቋም ያራምዳል። በገዥው ፓርቲ ግልፅ ፍረጃ፣ ወከባና ጥቃት እየደረሰበትም ቢሆን የፖለቲካ ማዕከሉ እንዲረጋጋና በአፍሪካ ረዥሙንና ደም አፋሳሹን የእርስ በርስ ጦርነት ያደረገች ሀገር ተመልሳ ወደ ቀውስ እንዳትገባ ያላሰለሰ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል።

    አብን ወቅታዊው የሀገራችን ብሔራዊ ደህንነት ከጊዜ ጊዜ እየከፋና እጅግ አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን ይገነዘባል። የውጭ ወራሪዎችና የውስጥ ቦርቧሪዎች ከተቻለ ኢትዮጵያን ለየዘውጉ አምበሎች በታትኖ ከዓለም ካርታ ለማጥፋት፤ ካልሆነ ደግሞ ውስጣዊ አንድነት የሌላት፣ ደካማና ፍላጎታቸውን ያለማንገራገር የምትቀበል አድርገው ለማሽመድመድ እየተረባረቡ ይገኛሉ።

    ከዚህ አንፃር የብልጽግና አገዛዝ የሀገሪቱን፣ የዜጎችና የመንግሥቱን ሰላምና ደህንነት፣ ጥቅምና ክብር በማስጠበቅ ረገድ ጉልህ ክፍተቶች እየተስተዋለበት ነው። በአሁኑ ወቅት መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ባደረገው ከፍተኛ ተጋድሎ ከአፈናና ጭቆና መንበሩ የተባረረውና በሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ በአማራ እና አፋር ልዩ ኃይልና ሕዝባዊ ሚሊሺያ ድባቅ የተመታው የትግራይ ሕዝብ ነፃ አውጪ ግንባር (ትህነግ) ተመልሶ በማንሰራራት በብሔራዊ ደህንነታችን ላይ ተቀዳሚ አደጋ ሊሆን በቅቷል።

    አብን ማዕከላዊ መንግሥትና በየደረጃው ያሉ መንግሥታዊ አካላት ሀገሪቱ ከተደቀነባት የህልውና አደጋ ለመታደግ በሚደረገው ርብርብ የራሳቸውን ሚና በግልፅ ከመወሰን አንስቶ ሁሉንም ባለድርሻ አካላት ያካተተ የብሔራዊ ደህንነት እርምጃ እንዲወስዱ ጥሪ ያቀርባል።

    መንግሥት ልዩ የደህንነት ስጋት ያለባቸው አካባቢዎች ላይ ትኩረት እንዲያደርግ፤ በተለይም አሸባሪው የትህነግ ቡድን መልሶ በተቆጣጠረው በትግራይ የተማሪዎችንና የሲቪል ዜጎችን፤ በአጠቃላይም የትግራይን ሕዝብ ደህንነት የማስጠበቅ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ይጠይቃል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች በትግራይ ክልል በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ተመድበው ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ የሚገኙ ተማሪዎች ሁኔታ አብንን በእጅጉ ያሳስበዋል። የትግራይ ሕዝብ በመካከሉ ለሚገኙ ተማሪ ልጆቹ አስፈላጊውን ጥበቃና ክብካቤ እንዲያደርግ ጥሪ እናደርጋለን።

    አብን መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ሀገር ወዳድ ዜጎችና በተለይም ወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ሀገራችን ስለገጠማት የብሔራዊ ደህንነት አደጋ ግልፅ ግንዛቤ እንዲኖራቸውና ኢትዮጵያን ለመታደግ በአንድነት እንዲሰለፉ ጥሪ ያደርጋል።

    በወታደራዊ ኃይል የሚገኘው ድል ዳግም በዲፕሎማሲው አውድማ እንዳይነጠቅ መላው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን የሀገራቸው አምባሳደር በመሆን በዓለምአቀፍ የዲፕሎማሲ ትግል እንዲሳተፉ ጥሪ ያቀርባል።

    በተለይም ደግሞ በፀረ – ኢትዮጵያው ጎራ በጠላትነት ተፈርጆ ዘርፈ ብዙ ጥቃት የተሰነዘረበት የአማራ ሕዝብ የሚገኝበትን ወቅታዊ የስጋት ደረጃ በውል ተገንዝቦ የበኩሉን ጥንቃቄና ዝግጅት እንዲያደርግ፣ የአማራ ዲያስፖራ በሕዝባችንና በሀገራችን ላይ የተቃጣውን አደጋ ለመቀልበስ ሁለገብ የሃሳብ፣ የፋይናንስ፣ የዲፕሎማሲ ተሳትፎውን አጠንክሮ እንዲቀጥል ጥሪ ያቀርባል።

    አብን አፍሪካውያን ወንድሞቻችን፣ መላው የኢትዮጵያ ወዳጆችና አጋሮች የጥንታዊ ሥልጣኔ፣ አኩሪ የነፃነት ታሪክ ያላት ሀገር በእኩያን ኃይሎች የተከፈተባትን ወታደራዊ፣ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥቃት ለመመከት ከጎናችን እንዲሰለፉ ጥሪ ያደርጋል። በዚህ ረገድ በአካባቢው ጉዳይ ትኩረት አድርገው የሚንቀሳቀሱ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ዓለምአቀፍ ተቋማት በአፍራሽ የሀሰት ፕሮፓጋንዳ እንዳይደለሉና የችግሩን ዙሪያ ገብ በፍትሃዊነት በመገምገም እንዲንቀሳቀሱ ጥሪ ያቀርባል።

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በሀገራችን ላይ የተደቀነውን ፅኑ የብሔራዊ ደህንነት ስጋት ለመመከትና ከምንም በላይ የቆመለትን የሀገር አንድነትና ሉዓላዊነት፣ የሕዝብ ጥቅምና ክብር እንዲሁም የሀገረ መንግሥቱን ቀጣይነት ለማረጋገጥ የሚጠበቅበትን ሁሉ ድርጅታዊ አስተዋፅኦ ለማድረግ ቁርጠኝነቱን በአፅንኦት ለመግለፅ ይወዳል።

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)
    አዲስ አበባ፣ ሸዋ፣ ኢትዮጵያ
    ሰኔ 28 ቀን 2013 ዓ.ም

    ምንጭ፦ አብን

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ

    Anonymous
    Inactive

    ከባልደራስ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ
    ኢትዮጵያ መቼ ይሆን ነፃ፣ ፍትሀዊና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ የሚኖራት?!

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ከተመሠረተ ጊዜ ጀምሮ ፍትህ እንዲሰፍን ሰላምና መረጋጋት እንዲመጣ፣ አድሎአዊነትና ዘረኝነት እንዲወገድ፣ ሕዝብ ከመፈናቀልና ከድህነት እንዲላቀቀቅ፣ አዲስ አበባ የራስ ገዝ አስተዳደር እንድትሆን እና ሌሎችም ዲሞክራሲያዊ መብቶች እንዲሰፍኑ የሚያስችል ሥርዓት ለማምጣት ጠንክሮ ሠርቷል፤ እየሠራም ነው። የሀገሪቱ መሪ “ከባልደራስ ጋር ግልጽ ጦርነት እንከፍታለን” እያሉ በተናገሩበት ወቅት እንኳን ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ከመታገል ቁርጠኛ አቋሙ ወደ ኋላ አላለም።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) በ6ኛው ሀገር አቀፍ ቅድመ ምርጫ ሂደት (pre-election process) ላይ በተለያዩ ጊዜያት ሳይንሳዊ ጥናቶች አካሂዶ ዝቅተኛውን ዓለም አቀፍ የምርጫ መስፈርት የማያሟላ መሆኑን አረጋግጧል። የምርጫ ሂደቱ የተበላሸ ከሆነ ውጤቱም በተመሳሳይ መንገድ ሊሆን እንደሚችል የሚጠበቅ ቢሆንም ባልደራስ በኢትዮጵያ ሰላም ለማስፈን የበኩሉን አስተዋጽኦ ለማበርከት ሲል በምርጫው የተሳተፈ መሆኑን ለማሳወቅ እንወዳለን።

    ፓርቲያችን ከአራት ወራት በፊት ጀምሮ ባካሄዳቸው ከፍተኛ የምርጫ እንቅስቃሴዎች ወቅት ሕዝብ ከጎኑ መሆኑን በተለያዩ መንገዶች አረጋግጧል። አዲስ አበቤ ለድርጅታችን ባሳየው ደጀንነትም ፓርቲያችን እጅጉን ኮርቷል። ያነሳነውን አዲስ አበባን ራስ ገዝ የማድረግ ጉዞ ሕዝባችን ከጎናችን በመሆን ስለሰጠን ድጋፍ ከልብ እናመሰግናለን። ለሰጣችሁንም ድምፅ ምስጋናችን ከፍ ያለ ነው። ይህንኑ ወደ ፊትም አጠናክረን እንደምንሄድ በዚሁ አጋጣሚ እንገልፃለን ።

    ዓላማችንን ከግብ ለማድረስ ደከመኝ፣ ሰለቸኝ ሳትሉ፥ ዕውቀታችሁን፣ ጊዜያችሁን፣ ገንዘባችሁንና ልዩ ልዩ ቁሳቁሶችን ጭምር የለገሳችሁ የፓርቲው አመራሮች፣ የሕዝብ ተወካዮችና የአዲስ አበባ ምክር ቤቶች እጩዎች፣ የምርጫው የቅስቀሳና የሎጂስቲክስ አካላት፣ የባልደራስ የዴሞክራሲ ማዕዘን በመሆን የምርጫውን ሂደት ከሁለት ቀንና ሌሊት በላይ የተከታተላችሁ ወኪሎቻችን እና በተለያዩ እንቅስቃሴዎቻችን ላይ የተሳተፋችሁ ሁሉ የላቀ ምስጋና የምናቀርብላችሁ በታላቅ ደስታ ነው። በሰሜን አሜሪካ፣ በአውሮፓ እና በሌሎችም ዓለማት የምትኖሩ የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ የድጋፍ ሰጭ ኮሚቴ እና የአማካሪ ቦርድ አባላት ላደረጋችሁት ሁሉን አቀፍ ድጋፍ፣ ምክር እና አስተዋፆኦ ምስጋናችን እጅጉን ከፍ ያለ ነው።

    “አዲስ አበባን ማዳን ኢትዮጵያን ማዳን ነው” በሚል ዓላማ የጀመርነውን ጉዞ ገዥው ፓርቲ መሪዎቻችንን በማሰር ለማሰናከል ጥረት አድርጓል። ነገር ግን ትግሉ የተነሳበትን ዓላማ ይበልጥ ከፍ አድርጎ በመቀጠሉ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች የሚገዙት ሃሳብ ሆኗል። በሀገር ውስጥ ያላችሁ አባላት እና በውጭ ሀገር የምትኖሩ ድጋፍ ሰጭዎች የተሸረበውን ሴራ በጣጥሳችሁ በመውጣት፣ በሰላማዊ ትግሉ ፋና ወጊ የሆኑ መሪዎችን ቀንዲል ከፍ ብሎ እንዲታይ ያደረጋችሁ ናችሁና በድጋሚ የባልደራስ አመራር በእናንተ ደስታና ኩራት እንደሚሰማው ይገልጻል ።

    በባልደራስ ፓርቲ ቅድመ ምርጫ ሂደት ጥናት እንደተረጋገጠው በብዙ ውጥንቅጥ ውስጥ የታጀበው ዝቅተኛውን የምርጫ መመዘኛ ደረጃዎች ያላሟላው የሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. ምርጫ የመጣውን ውጤት ማሳየት ችሏል። እንደሌሎቹ ጊዜዎች ሁሉ የዘንድሮውንም ምርጫ ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ ለማድረግ ከመንግሥት በኩል ምንም ቁርጠኝነት አለመኖሩን ፓርቲያችን ተገንዝቧል።

    ከምርጫው ቀን ዋዜማ ጀምሮ በአዲስ አበባ ነዋሪ ላይ የፍርሃት ድባብ ለመፍጠር በከፍተኛ ደረጃ የታጠቁ የፓሊስ እና የመከላከያ አባላት የጦር መሣሪያቸውን ወድረው በአዲስ አበባ የተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር የሥነ ልቦና ጫና ሲፈጥሩ ሰንብተዋል። ይህም “ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ይሏታል ጅግራ” እንደሚባለው በምርጫው ሰሞን ከነበሩ ኢ-ዲሞክራሲያዊ ትዕይንቶች አንዱ ነበር።

    ምርጫውን ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ ማድረግ ጠቀሜታው በሥልጣን ላይ ላለው መንግሥት እና ተወዳድረው ለማሸነፍ ለሚፎካከሩት ፓርቲዎች ብቻ ሳይሆን ለሚወክሉት ሕዝብ ጭምር መሆኑ ይታወቃል። ምርጫው ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ ሳይሆን ሲቀር የሕዝብ ነፃነት ይገፈፋል፤ ሥርዓት አልበኝነት ይነግሣል። በዜጐች መካከል የደረጃ ልዩነት እና መሰል ችግሮች ተፈጥረው ሕዝብ በፍርሃት አረንቋ ውስጥ ይወድቃል። እነዚህን ችግሮችን ለማስወገድ በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ከፍተኛ ኃላፊነት ያለበት መሆኑ ይታወቃል።

    በ6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ የተከሰቱ ችግሮችን ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ በጥልቀት እየመረመረው ይገኛል። እስካሁን በደረሰበት ሁኔታ ምርጫው ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ አልነበረም የሚል መደምደሚያ ላይ የሚያደርሱ ተግባራት መኖራቸውን ፓርቲያችን ያምናል። ለአብነትም፡-

    1. ድምፅ አሰጣጥን በተመለከተ ግንዛቤ ለመስጠት የተሰየሙት የምርጫ አስፈፃሚዎች የገዢው ፓርቲ እንዲመረጥ የሚረዳ ገለጻ ሲያካሂዱ የፓርቲዎች ወኪሎች እርምት እንዲያደርጉ ቢያስገነዝቡም አስፈፃሚዎች ብልሹ አሠራራቸውን አለማስተካከላቸው በችግርነት የታየ ጉዳይ ነው፤
    2. በመራጮች ምዝገባ ወቅት ያልነበሩ አዳዲስ ንዑስ የምርጫ ጣቢያዎችን ከመክፈት በተጨማሪ ማንነታቸው የማይታወቁ የምርጫ ጣቢያዎች ተከፍተው በድምፅ መስጫ ቀን ድምፅ ሲሰጡባቸው መቆየታቸው፣
    3. አቅመ ደካሞችን፣ በእድሜ የገፉትን እና የአካል ጉዳተኞችን የመንግሥት ካድሬዎች ከምርጫ ሕጉ ውጭ በማገዝ ስም በሚስጥር ድምፅ በሚሰጥባቸው ክፍሎች ይዘዋቸው በመግባት ጫና እየፈጠሩ የሚፈልጉትን ማስመረጣቸው፣
    4. በአንዳንድ የምርጫ ጣቢያዎች የባልደራስን የምርጫ ውጤት ቁጥሮች እየቀነሱ እንዲጻፉ መደረጋቸው፣
    5. ባልደራስ የተመረጠባቸውን ወረቀቶች በስልት ከጥቅም ውጭ እንዲሆኑ ወይም የባከኑ ውጤቶች እንዲሆኑ መደረጋቸው፣
    6. በእያንዳንዱ የምርጫ ጣቢያ ያለው የመራጩ ቁጥር ቀድሞ የሚታወቅ ሆኖ እያለ በብዙ የምርጫ ጣቢያዎች የመራጮች ድምፅ መስጫ ወረቀቶች ከመራጮች ቁጥር እንዲያንስ መደረጉና ወረቀቱ እስኪመጣ መራጮች በፀሐይ፣ በዝናብና በብርድ በርካታ ሰዓታት እንዲቆዩ መሆናቸው የተወሰኑት ሳይመርጡ ወደ የቤታቸው እንዲሄዱ አስገድዷቸዋል።
    7. ለአዲስ አበባ ምክር ቤት ለውድድር የቀረቡ ፓርቲዎች በርካታ በመሆናቸውና በምርጫ ወረቀቱ ላይ በምርጫ አስፈፃሚዎች በቂ እና ግልጽ ማብራሪያ ባለመሰጠቱ የምርጫ ወረቀቱ በውስጡ ምን ያህል እጩዎች እንደያዘ አለመታወቁ ለመራጮች አስቸጋሪ ሁኔታን የሚፈጥር ሆኗል። ይህም መራጩ በግልጽ ድምፅ የመስጠት ነፃነት እንዳይኖረው አድርጓል።በዚህም የድምፅ መስጫ ወረቀቶች እንዲባክኑ ወይም መራጩ ላልፈለገው ድምፅ እንዲሰጥ ሆኗል። ከላይ የተጠቀሱት በምሳሌነት ከሚነሱት ችግሮች እጅግ በጣም ጥቂቶቹ ናቸው።

    የገዥው ፓርቲ በምርጫ ወቅት ለችግረኛ ሰዎች የተለያዩ መደለያዎች በመስጠት የሕዝብን ገንዘብ ለሥልጣን መሸመቻ ማድረጉ በምድር ቀርቶ በፈጣሪ ዘንድ ይቅር የማያሰኝ ተግባር ነው። በሌሎች ጊዜዎች የድሆችን ችግር ለማስወገድ ትኩረት የማይሰጠው ገዥው ፓርቲ በምርጫ ሰዓት ብቻ ማባበያ ይዞ መቅረቡ ነዋሪውን ለመደገፍ ሳይሆን ሥልጣኑን ለማቆየት የተጠቀመበት ዘዴ መሆኑ ግልጽ ነው።

    ከምርጫ 97 ወዲህ የምርጫ ጣቢያዎች እንዲበዙ የተደረገባቸው ምክንያቶች ኗሪዎች በረጃጅም ሰልፎች ላይ በመቆየት እንዳይንገላቱ ለማድረግ መሆኑ ይታወቃል። ነገር ግን ዛሬ ምርጫ ጣቢያዎች እንደአሸን እንዲፈሉ በተደረገበት ወቅት መራጮችን ለማሰላቸትና ለማስመረር ይሁን ተብሎ የተከናወኑት ማጓተቶች ድምፅ ሰጭዎች እንዲንገላቱ ማድረጉ የሚያስተዛዝብ ሁኔታን ፈጥሯል። ቀን በፀሐይና በዝናብ፣ በምሽት እና በሌሊት ደግሞ በብርድ እንዲንገላታ የተደረገበትን ደባ ተቋቁሞ የተሰለፈው አዲስ አበቤ ድምፁን ለማን እንደሰጠ ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ ጠንቅቆ ያውቃል ።

    በገዥው ፓርቲና በምርጫ ቦርድ ለማሰላቸት ሆን ተብሎ በተፈጠረው ተስፋ የማስቆረጥ ሂደት ሳትመርጡ ለቀራችሁ፣ ሆን ተብሎ በተሠራ ደባ ካርድ እንዳታወጡ የተደረጋችሁ እና መምረጥ ያልቻላችሁ፣ ጊዜ በማጣት ካርድ ላልወሰዳችሁ፣ እንዲሁም በሀገራችን ሁኔታ ተስፋ በመቁረጥ የዜግነት ግዴታ መወጣት ያልቻላችሁ የእናንተ ድምፅ ሀገራችን ከገባችበት ውጥንቅጥ ችግሮች መውጫ ከፍተኛ ሚና የሚጫወት ሆኖ ሳለ በመቅረቱ በእጅጉ ያስቆጫል።

    የአሁኑ የኦህዴድ/ብልጽግና አባት የሆነው ህወሓት/ኢህአዴግ በምርጫ 2007 የ100% የአሸነፍኩ ጉዞ ከ2 ዓመት በላይ በሥልጣን መቆየት እንዳልቻለ የ3 ዓመት ትውስታችን ነው። በሕዝብ ያልተመረጠ መንግሥት ራሱን ይሸነግል ይሆናል እንጂ ረጅም ርቀት እንደማይጓዝ ከዚሁ ከሀገራችን ታሪክ መረዳት ይቻላል። ለነፃ፣ ፍትሀዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ዳኝነት የሚሰጠው ሕዝብ ነውና።

    6ኛውን ሀገር አቀፍ ምርጫ “ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ አደርጋለሁ” ይል የነበረው ኦህዴድ/ብልጽግና በምርጫው ዙሪያ እየተፈጸሙ ያሉት ድርጊቶች የማያልቅ ሀሰቱ ማሳያዎች ሆነዋል። ዜጎች እየተገደሉ፣ ሰብዓዊ መብታቸው እየተጣሰ፣ ንብረታቸው እየወደመ፣ እየተራቡ እና እየተደፈሩ፣ የውጭ ወራሪ ኃይሎች ድንበር ጥሰው ሀገራችን ውስጥ ገብተው እንደፈለጉ እየሆኑ “ኢትዮጵያ አሸንፋለች፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰላም ሰፍኗል።…” የተሰኙት አባባሎች ዓይናችሁን ጨፍኑ ላሞኛችሁ ከማለት ያለፈ ትርጉም የላቸውም።

    የአዲስ አበባ ሕዝብ ለሰጠን ታላቅ ድጋፍና ፍቅር፣ ክብርና ሞገስ አሁንም ደግመን እናመሰግነዋለን። የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ አመራሮች እና አባላት በሕዝብ ፊት በተግባር ጭምር እየተፈተንን የሰላማዊ ትግል አርበኞች መሆናችንን አስመስክረናል።

    የዴሞክራሲ ኃይሎች ትንንሽ ልዩነቶችን ወደ ጎን በመተው ለማይቀረው የሰላማዊ ትግል ተደጋግፈን ሕዝብን በማስተባበር እንድንታገል ዛሬም እንደቀድሞው ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ ጥሪውን ያቀርባል።

    ብሔራዊ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. የተካሄደወን የምርጫ ውጤት ይፋ ካደረገ በኋላ ከምርጫው ጋር በተያያዘ በዝርዝር ጉዳዮች ላይ ባልደራስ መግለጫ የሚሰጥ መሆኑን በአክብሮት ይገልጻል።

    የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ
    ድል ለእውነተኛ ዴሞክራሲ!!!
    ሰኔ 18 ቀን 2013 ዓ.ም.

    ምንጭ፦ ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ

    ነፃ፣ ፍትሀዊና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ

    Anonymous
    Inactive

    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ መግለጫ
    (ድኅረ ምርጫ 2013)

    ሰኔ 17 ቀን 2013 ዓ.ም

    የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታን መሠረት ለመጣል የሚጠይቀው መስዋዕትነት እጅግ ረጅምና መራር ነው። በተለይም እንደ አፍሪካ ውስጥ ባሉ በበርካታ ውስብስብ አሠራሮች በተተበተቡ አገሮች ውስጥ፣ የፖለቲካ ምህዳሩ ጥበት፣ ከፍተኛ የሥልጣን ጉጉትና የመሳሰሉት እንቅፋቶች የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታውን ቀይደው ይይዙታል። ድህነቱ፣ ኋላቀርነቱ፤ የዜጎች የፖለቲካ አረዳድ ወዘተ ችግሮቹን ይበልጥ ያባብሱታል።

    በተለይም በዘውግና በቋንቋ ላይ የተመሰረተው የሀገራችን የፖለቲካ ትርክት ላለፉት 30 ዓመታት ከአንድነት ይልቅ ልዩነቶቻችንን አግዝፎ በትውልዱ ላይ ቁርሾን ዘርቷል። ዛሬም ከዚህ የማንነት የፖለቲካ አዙሪት ለመላቀቅ አልቻልንም። ከዚህ የችግር አረንቋ ውስጥ ለመውጣት የዜግነት ፖለቲካው ብርቱ ዋጋ የሚያስከፍል ቢሆንም ነገም ብቸኛው አማራጭ መሆኑ ሊታመን ይገባል።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ በታሪኳ በተለያዩ የመንግሥት ቅርጽና የፖለቲካ ፍልስፍና በየጊዜው ሥልጣን ላይ በወጡ ኃይሎች ስትመራ መቆየቷ ይታወቃል። ላለፉት 30 ዓመታት እስከ 6ኛው ዙር ምርጫ ድረስ በምርጫ ብቻ ሥልጣን ለመያዝ የተሞከረው ሒደት ተስፋ ሰጪ ባይሆንም ዜጎች የምርጫ ተሳትፎ ማድረጋቸው አንድ ጥሩ እርምጃ ነው ሊባል ይችላል።

    ሰኔ 14 ቀን 2013 የተደረገው 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ሂደቱ እና ውጤቱ ሙሉ በሙሉ ለሕዝብ የተገለፀ ባይሆንም በብዙ ግልጽ ችግሮች የታጀበ ነበር። ለዚህ ምርጫ ሰላማዊነትና የአገሪቱን የነገን ቀጣይነት በምርጫ ለማረጋገጥ፣ ዜጎች በምርጫው ላይ በንቃት እንዲሳተፉ ኢዜማ የበኩሉን ድርሻ በኃላፊነት ተወጥቷል የሚል የፀና እምነት አለን። ከምንም በላይ ለሀገር መረጋጋትና ለሕዝብ ሰላም ያለውን ቁርጠኝነትም በተግባር አስመስክሯል።

    በመሆኑም ለቀጣይ የኢዜማ መዋቅር አደረጃጀት ለፓርቲያችን ደጋፊዎች፣ አባላትና በየደረጃው ለሚገኙ አመራሮች የሚከተሉትን ማሳወቅ ይኖርብናል።

    1ኛ/ ሰኔ 14 ቀን 2013 የተደረገው የ6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ የመጨረሻ ውጤት እስከሚገለጽ የምንጠብቅ ሲሆን ቅድመ ምርጫና በምርጫ ወቅት ኢዜማ በተወዳደረባቸው በርካታ የምርጫ ክልሎች ያጋጠሙትንና በየሰዓቱ ለምርጫ ቦርድ ያሳወቅናቸው በርካታ ተግዳሮቶችን በአጽንኦት ተመልክቶ ውሳኔ የማይሰጥባቸው ከሆነ ጉዳዩን ወደ ፍትህ አካላት ይዘን የምንሔሄድበትን ሁኔታ ቀድመን ለሕዝብ የምናሳውቅ ይሆናል።

    2ኛ/ ኢዜማ የምርጫ 2013 አጠቃላይ የፓርቲውን የምርጫ እንቅስቃሴ የሚያስተባብር የምርጫ ስትራቴጂክ ማኔጅመንት ኮሚቴ ከአመት በፊት አዋቅሮ ሲንቀሳቀስ እንደነበረ ይታወቃል። ይህ ኮሚቴ አጠቃላይ የምርጫውን ሂደት በተመለከተ ከሚያዘጋጀው የግምገማ አጠቃላይ ሪፖርት፣ በድርጅት በኩል፣ በብሔራዊ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ በተቋቋመ ቡድንና ከፓርቲው ውጪ በተመረጡ ገለልተኛ አካላት ከሚቀርበው ግምገማ ተነስተን አጠቃላይ ሁኔታውን ለኢትዮጵያ ሕዝብ እንገልጻለን።

    3ኛ/ እንደሚታወቀው የፖለቲካ ፓርቲ ሰላማዊ ትግል ቀጣይነት ያለውና ከምርጫ በኋላም ቢሆን ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑ እሙን ነው። በዚህ ረገድ ኢዜማ ጊዜያዊ ፓርቲ ሳይሆን ገና ከመነሻው ከምርጫ ወረዳ ጀምሮ ሲዋቀር ሩቅ ተጓዥና ዘመን ተሻጋሪ ፓርቲ ሆኖ ነው። ከዚህ አንጻር በምርጫው ሒደት ያጋጠሙንን ተግዳሮቶች በሕግ አግባብ እየጠየቅን ከዚህ ምርጫ ማግስት ጀምሮ የድርጅቱን መዋቅር ይበልጥ በማጠናከር ወደ ሥራ የገባን መሆኑን ለማሳወቅ እንወዳለን።

    4ኛ/ ኢዜማ በተቋቋመ በሁለት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ከየትኛውም ተፎካካሪ ፓርቲ በላቀ መልኩ በመላው አገሪቱ 455 የምርጫ ወረዳ መዋቅሮችን አደራጅቶ በጥንካሬ እየተንቀሳቀሰና በምርጫ 2013 ገዢውን ፓርቲ በብርቱ የሞገተ ፓርቲ ነው፤ ሕዝባዊ መሠረቱም ሰፊና ጠንካራ ነው።

    ከዚህ አንጻር የፓርቲው የወረዳ መዋቅሮች በምርጫ ሂደት የተገኘውን ውጤት፣ ልምድ፣ የሰው ኃይል፣ ልዩ ልዩ ግብዓቶች እና ወዘተ የመሳሰሉትን ፓርቲውን ይበልጥ ለማጠናከር መጠቀምና ድርጅቱን በጥንካሬ ለመምራት በየደረጃው የሚገኙ የፓርቲው አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ከዚህ ምርጫ ማግስት ጀምሮ ብርቱ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉና በቀጣይ ለሚያጋጥሙን ሀገራዊ ጉዳዮችና ሰላማዊ ለሆኑ የትግል እንቅስቃሴዎች ራሳችንን እንድናዘጋጅ የከበረ ጥሪ ማስተላለፍ እንሻለን።

    ኢዜማ ላለፉት ሁለት ዓመታት በተለይም ከምርጫ መቃረብ ጋር ተያይዞ የኢትዮጵያ መፍትሄ ሰጪ ፖሊሲዎችን የነደፈ፣ ማኒፌስቶ አዘጋጅቶ ለሕዝብ ያሳወቀ፣ የምርጫ ቅስቀሳዎችን በሰለጠነ መንገድ ያካሄደ፣ ማኅበራዊ ፍትህ ለማስፈን መሠረቱን ዜግነት ላይ ያደረገ ፓርቲ መሆኑንና መላው የኢትዮጵያ ሕዝብም በእያንዳንዱ እንቅስቃሴ ላይ የራሱን ተሳትፎ እንዳደረገ እናምናለን።

    በመጨረሻም ነገም ኢትዮጵያ ሀገራችን ሉዓላዊ ግዛቷና የሕዝብን ደህንነት ተጠብቆ፣ ለቀጣዩ ትውልድ የምናወርሳት ጠንካራ ሀገር እንድትሆን ኢዜማ ዘመን ተሻጋሪ ፓርቲ ሆኖ በጥንካሬ እንደሚቀጥል እየገለጽን በፀሐይና በዝናብ ወስጥ፤ ቀንና ለሊት ተሰልፋችሁና በብርቱ ጫናና መዋከብ ውስጥ ሆናችሁ ድምጻችሁን ለኢዜማ የሰጣችሁትን ከልብ እያመሰገንን ያልመረጣችሁንንም ውሳኔያችሁን የምናከብር መሆኑን እንገልጻለን።

    ምንጭ፦ ኢዜማ

    ኢዜማ

    Anonymous
    Inactive

    የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ እና የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በጋራ ለመሥራት የሚያስችል የትብብር ስምምነት ተፈራረሙ
    ባልደራስ እና አብን ትብብርን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ

    የሀገራችን ሕዝብ ለዘመናት በተጫኑበት ኢዲሞክራሲያዊና አምባገነን አገዛዞች የተነሳ፥ በነፃነት እጦት፣በስቃይ እና በመከራ ኑሮውን እንዲገፋ ተደርጓል። ጭቆናን አስወግዶ የሚፈልገውን ፍትህ እና እኩልነት እውን ለማድረግ ከፍትኛ ዋጋ መክፈሉም እሙን ነው።

    ይሁንና የሀገራችን የለውጥ ፍላጎት እና እንቅስቃሴ ጅማሮው ሳይሳካ፥ ለቀጣዩ ዴሞክራሲያዊ ትግል ተስፋ ሊሆን የሚችል መሠረታዊ የትርክትና የመዋቅር ክለሳ እንኳ ሳይደረግ አምባገነንነትና ዘረኝነት የእጅ ለውጥ ብቻ እያደረጉ የሚፈራረቁባት ሆናለች። በዚህ ሁሉ ፈተና ውስጥ ያለፈው ሕዝባችን አሁንም ዲሞክራሲን፣ እኩልነትንና ዘላቂ ሰላምን በመሻት ለነፃነት የሚያደርገውን ትግል አጠንክሮ እንደቀጠለ ይገኛል።

    የዚህ ዓይነት መልክና ይዘት ተላብሶ የተደራጀው የተፎካካሪ ኃይል ለሰርጎ ገቦች የተጋለጠ፣ በተፈጥሮው ደካማና ተሰባሪ ከመሆኑም በላይ የአምባገነኑን ሥርዓት ራዕይ አቀንቃኝ እስከመሆን ደርሶ እንደነበር ይታወሳል። በተጨማሪ የተቃውሞው ጎራ እርስ በርሱ በፍረጃና በሴራ መጠላለፍ ምክንያት በቁርሾ እንዲሞላ በማድረግ የጋራ ሀገራዊ ስምሪት መውሰድ እንዳይችል አድርጎት ቆይቷል።

    በዚህ ሂደት ውስጥ አምባገነኖችን በጋራ መታገል ጥረት ከማድረግ ወርደው በመናኛ ፍላጎቶችና በጥቃቅን ልዩነቶች ዙሪያ ታጥረው ሲሻኮቱ በመካከል የባከነው ጊዜ እና የሰው ህይወት የሚያስቆጭ ነው።

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ሀገራችንን ለእድሜ ልክ ዝቅታ የዳረጋት የጥላቻ ትርክት፣ ትርክቱን መሠረት አድርገው የተደነገጉ ሕግጋትና የተዘረጉ መዋቅሮች ተከልሰው መላ ኢትዮጵያውያን በእኩልነት፣ በወንድማማችነት፣ በፍትህና በሰላም የሚተዳደሩነት ዘላቂ ሥርዓት በማስፈን በተለምዶ “መንታ ቅኝት” ያለው የትግል እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል። የአብን ስትራቴጂክ ግብ መላውን ኢትዮጵያዊ የፍትሀዊ አማካኝ ተጠቃሚ በማድረግ ሁሉንም አሸናፊ የሚያደርግ የፖለቲካ ማዕቀፍ እንዲፈጠር ሲሆን የድርሻውን ለማበርከት አበክሮ እየሠራ ያለ ንቅናቄ ነው።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ደግሞ የኢትዮጵያዊ ኅብር ዓይነተኛ መገለጫ የሆነችውን የአዲስ አበባ ከተማ ሕዝብ ከከፋፋይና ከጥላቻ ፖለቲካ ነፃ ለማድረግና ሕዝቡ ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብቱ እንዲረጋገጥ ለማስቻል በሚል የተደራጀ ስለመሆኑ በሰፊው የሚታወቅ ነው።

    አዲስ አበባ ከተማ የኗሪዎቿ መሆኗን ለማረጋገጥ የሚያደርጉት የጋራ ትግል መነሻ ዴሞክራሲን፣ ነፃነትን፣ ፍትህንና እኩልነትን በማስፈን ላይ የተመሠረተ ሲሆን፥ አንዳች ቅቡልነት ያለው መርህ ወይም ምክንያት ማጣቀስ የማይችሉ ኃይሎች ከተማዋ የአንድ ንጥል ብሔር ንብረት መሆኗን በይፋ በመግለፅ የማታገያ አጀንዳ በማድረግ ሕዝቡ በነሱ ፍቃድና ይሁንታ መኖር እንዳለበት አድርገው ያወጁት ያልተገራ ፍላጎት የጋረጠበትን የህልውና ስጋት መቀረፍ እንዳለበት አብን እና ባልደራስ የጋራ ፖለቲካዊ አቋም ወሰደዋል።

    የሀገራችን ኢትዮጵያ መድናና የመላ ሕዝቧ ሰላማዊ መኖሪያ ሆና ዘመናትን የተሻገረችው አዲስ አበባ መደበኛና ነባር ምልከታ ሊቸራት ሲገባ ከልቦለድ የመነጨ የዘረኞች “የልዩ ጥቅም”ቀንበር ጊዜ በረዘመ ቁጥር የሕግና የፖለቲካ ቋጠሮው እየጠበቀ መምጣቱና ይዘቱ “በኦሮሚያ ክልል አስተዳደርና በአዲስ አበባ መስተዳደር ስምምነት” እንደሚወሰን በተሻሻለው ቻርተር መደንገጉ ከተማዋንና ሕዝቧን ከአንድ ወገን በተሰባሰበ የፖለቲካ ኃይል ይሁንታ፣ ፍፁም ቁጥጥርና ጥበቃ ስር ለማዋል የተወሰነ መሆኑን ያሳያል። አብን እና ባልደራስ ይሄን አምባገነናዊ፣ ፍትህ አልቦ፣ ዘረኛ፣ አግላይና በመጨረሻም የግጭትና የብሔራዊ ደህንነት አደጋ የሆነ አፍራሽ እንቅስቃሴ በጋራ ተሰልፈው ለመታገል ከስምምነት ላይ ደርሰዋል።

    ትብብሩ በቀጣይ እንዲፈጠርና እንዲጎለብት ለምንፈልገው የሀገራዊ በጎ ኃይሎች ጥምረት እርሾ ሆኖ እንዲያገለግል የታለመ ነው። አስቻይነት የሌለውና በሕግ የተደነገገው የጊዜ ገደብ ጉዳይ በነባራዊ ተግዳሮቶች ምክንያት የተፈጠረ መሆኑን በማረጋገጥ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተመሳሳይ አንድምታ ያላቸውን ጉዳዬች ባስተናገደበት ሁኔታ ትብብሩ ለህጋዊ እውቅና ሲቀርብ በመፍቀድና በመመዝገብ እንዲያፀድቀው የሚቀርብ ይሆናል።

    በዚህ መነሻነት ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን እውን ለማድረግ ለሚደረገው ትግል በመጪው ሀገራዊ ምርጫ የመራጮችን የጋራ ፍላጎትና ራዕይ ለማሳካት የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ /አብን/ እና ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ /ባልደራስ/ በጋራ የምንሠራበት የፖለቲካ ትብብር ፈጥረን ለመሥራት መወሰናችንን ለመላው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን፣ ለመላው አማራ ሕዝብና ለአዲስ አበባ ሕዝብ ስናበስር በታላቅ ደስታ ነው። ሌሎች ፓርቲዎችን ጨምሮ በሁለቱ ፓርቲ አመራሮች መሃከል ለወራት ሲካሄድ የነበረው ረዥምና አድካሚ ድርድር ፍሬ አፍርቶ መጪውን ሀገራዊና ክልላዊ ምርጫ የአብን እና የባልደራስ ትብብር አሸናፊ ሆኖ መውጣት የሚያስችላቸውን የጋራ ስልቶች ቀይሰው በይፋ መንቀሳቀስ ጀምረዋል።

    አብን እና ባልደራስ፣ አጠቃላይ የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ የአማራ ሕዝብ እና የአዲስ አበባ ከተማ ኗሪ ሕዝብ በበደል ውስጥ አምጠው የወለዷቸው የቁርጥ ቀን ልጆቹ እንደመሆናቸው መጠን በተባባረ ክንድ በሕዝባችን ላይ የተጫነውን የመከራ ቀንበር እንዲወርድ ከመቼውም ግዜ በላይ በጋራ ትብብር ለመታገል በቁርጠኝነት ተሰልፈዋል።

    አብን በጽንፈኞች የተሳሳተ ትርክት መነሻነት በአማራ ሕዝብ ላይ በተከታታይ የሚደርሰው ግፍ ድምጽ በመሆን በመጀመሪያው ረድፍ ሆኖ ትግሉን እየመራ ይገኛል። አብን የሀገራችን ኢትዮጵያን ደህንነት ለማረጋገጥና ህልውናዋን ለማስቀጠል አንድ ወሳኝ አምድ የሆነው የአማራ ሕዝብ በልዩ ሁኔታ ተፈርጆ የሚጠቃበትን የፅንፈኞች ስሁት ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ለመግታት የሚያስችል ልዩ ማዕቀፍ ሆኖ የተደራጀ ሲሆን ታሪካዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ስሪቱ በኢትዮጵያዊነት፣ ምልከታውም በወንድማማችነት፣ በፍትህና በዴሞክራሲ የተቃኘ ስለመሆኑ ውሎ ያደረ ጉዳይ ነው።

    ከላይ በሰፊው እንደተመላከተው ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ በአዲስ አበባ ከተማ ሕዝብ ላይ የተጋረጡ የህልውና አደጋዎችን ለመከላከል፣ የከተማዋ ሕዝብም ራሱ በዴሞክራሲያዊ መንገድ በመረጣቸው እንደራሴዎቹ የመተዳደር መብቱን ለማስከበር ባሚያደርገው እልህ አስጨራሽ ትግል ውስጥ በብቃትና በንቃት በነሳተፍ አያሌ መስዋዕቶችን በመክፈል የቀጠለ መሆኑን ራሱ ሕዝቡ በተግባር ኖሮ ያረጋገጠው ሀቅ ነው። ከላይ በተጠቀሱት መሠረታዊ ሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ ግቦች ዙሪያ ሁለቱ ድርጅቶች በፅኑ የሚጋሯቸውን አቋሞች መሠረት በማድረግ ቀጣይ ለሚደረገው ጠንካራና የተቀናጀ የሕዝብ ትግል ወሳኝ የማታገያ አጀንዳ እንዲሆኑ ስምምነት ላይ ደርሰዋል።

    በሀገር አቀፍ ደረጃ ይካሄዳል ተብሎ በሚጠበቀው ምርጫ መላው የሀገራችን ሕዝብ፣ በተለይም የአማራ ሕዝብና የአዲስ አበባ ሕዝብ የተደቀነባቸውን የህልውና አደጋ በትብብር ከመታገል ውጭ ሌላ ተጨባጭ የመፍትሄ አማራጭ እንደሌለ መተማመን ላይ ደርሰዋል።

    ከዚህ ቀደም በጋራ አብረውን ለመሥራት ንግግር ጀምረው ሳለ በተለያዩ ምክንያቶች በትብብሩ ለመዝለቅ ያልቻሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች አሁንም ጊዜው አለመርፈዱን ተገንዝበው በጎ ፍላጎት ካሳዩን ከግማሽ መንገድ ባላይ ተጉዘን ለመቀበል ዝግጁ መሆናችንን በዚህ አጋጣሚ ለማረጋገጥ እንወዳለን።

    የፈጠርነው ትብብር አርአያ መሆን የሚችልና ከትላንት ለተሻለ አዲስ የፖለቲካ ባህል ማሳያ ፈር ቀዳጅ እንደመሆኑ ከምርጫ በኃላም ትብብሩ ጎልብቶ፤ የሀገራችንን ሕዝብ ለዘመናት የቆየ የፍትህ ትግል ዳር ለማድረስ እንዲሁም የመላው ኢትዮጵያዊ የሆነችውን የአዲስ አበባ ከተማን ዓለም አቀፍነት የሚመጥን አመራር ለመስጠት ለመፍጠር ከወዲሁ አብረን መቆም ጀምረናል።

    አብን እና ባልደራስ የአዲስ አበባ ሕዝብ ራስን በራስ የማስተዳደር ዴሞክራሲያዊ መብት አክብረው ከሚቀበሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ትብብር በመፍጠር የከተማዋ ሕዝብ በፌደራል መንግሥቱ ውስጥ ተወክሎ እንደሁሉም ሕዝብ ጥቅሙን ለማስጠበቅ የሚያደርገውን ትግል የማሳለጥ ሚና እንደሚኖረው ለማሳወቅ እንወዳለን።

    አዲስ አበባ በሁሉም ኢትዮጵያውያን ጥረት የተገነባች፣ የአፍሪካ የዲፕሎማሲ ዋና ከተማ ብትሆንም፥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተነሱ ተረኞች ከተማይቷን በልዩ ጥቅም ስም የአንድ ቋንቋ ተናጋሪ ብቸኛ ንብረት ለማድረግ የሚደረገው እንቅስቃሴ በጋራ አጥብቀን እናወግዛለን። በከተማይቱ እና ነዋሪዎቿ ላይ የተደቀነውን ይህ አደጋ ለመከላከል ባልደራስ በዋነኛነት እያካሄደ ያለውን ትግል አብን የሚያድንቅ እና በሙሉ ልብ ከጎኑ እንደሚሰለፍ ቃል ይገባል። በአንጻሩም ባልደራስ ፓርቲ በጽንፈኞች ሴራ ዒላማ እንዲሆን በተደረገው የአማራ ሕዝብ ላይ የሚደርሰውን ግፍ እና በደል ለማስቀረት በቁርጠኝነት አብን ለሚያደርገው ትግል ክብርና እውቅና እንደሚሰጥ ለመግለፅ እንወዳለን፡፡

    ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ስምምነታችን የተበላሸውን የሀገራችንን ፖለቲካ ባሕል በማስተካከል፣ በውይይትና በሰጥቶ መቀበል መርህ ለሕዝብ ጥቅም ሲባል አብሮ መቆም እንደሚገባ ከማሳየት ባሻገር፥ ሌሎች ለተመሳሳይ አላማ ያነገቡ ፓርቲዎችም ይህን ፈለግ ተከትለው የትብብሩ አካል እንዲሆኑ ፅኑ ፍላጎት አለን።

    በመጨረሻም በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች ጽንፈኛ ኃይሎች በሚፈጽሟቸው የሽብር ድርጊቶች ምክንያት እየደረሰ ያለውን ሞት፣ የአካል ጉዳት፣ መፈናቀል እና የንብረት ውድመት ለማስቆም በየእርከኑ ያሉ የፌደራል እና የክልል መንግሥታት ኃላፊዎች ተግተው እንዲሠሩ ጥሪ እናቀርባለን።

    በተለይ ችግሩ ተባብሶ በሚገኝባቸው የኦሮሚያ፣ የቤንሻንጉል እና አንዳንድ የደቡብ ክልል አካባቢዎች የሚገኙ የመንግሥት አስተዳደርና የፀጥታ አካላት ችግሩን የሚመጥን ኃላፊነት በመውሰድ ንፁኃንን ከጥቃት እንዲከላከሉና ወንጀለኞችን ለሕግ እንዲያቅርቡ በአፅንኦት እንጠይቃለን።

    መሠረተ-ቢስ በሆነ ክስ ተወንጅለው ለእስር የተዳረጉትንና የመምረጥና መመረጥ መብታቸውን የተነፈጉ የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ አመራሮች በአስቸኳይ እንዲፈቱ እናሳስባለን። ትህነግ በለኮሰው ጦርነት በትግራይ ክልል ሕግ ለማስከበር እየተካሄደ ባለው ዘመቻ የንጹኃን ዜጎቻችንን ደህንነት እና የሰብዓዊ መብት እንዳይጣስ ልዩ ትኩረት እንዲደረግና የሰብዓዊ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ለማሳሰብ እንወዳለን።

    መጋቢት 9 ቀን 2013 ዓ.ም.
    የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ /ባልደራስ/
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ /አብን/

    ባልደራስ እና አብን በጋራ ለመሥራት

    Semonegna
    Keymaster

    የምርጫ ክርክር ለማዘጋጀት ፍላጎት ላላቸው የሲቪል ማኅበራት እና ሚዲያዎች የተደረገ ጥሪ

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ 6ተኛው ጠቅላላ ምርጫ ተግባራትን እያከናወነ እንደሆነ ይታወቃል፤ በዚህም መሠረት የተወሰኑ ተቋማት በተወዳዳሪዎች መካከል የምርጫ ክርክር ለማከናወን ከቦርዱ ፍቃድና አቅጣጫ ለማግኘት ጥያቄዎችን አቅርበዋል።

    ይህንን፥ እንዲሁም ሌሎች ልምዶችን መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የእጩዎች ምዝገባ ተጠናቆ ተወዳዳሪ ፓርቲዎች ከታወቁ በኋላ ሀገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ክርክር ሂደትን ለማስተባበር ይፈልጋል። በመሆኑም ከዚህ በፊት ጥያቄ/ ማብራሪያ ያስገባችሁም ሆነ በዚሁ ጉዳይ ላይ ፍላጎት ያላችሁ መንግሥታዊ ያልሆናችሁ ተቋማት እና ሚዲያዎች በተናጠል ወይም በጋራ የምርጫ ክርክር ዝርዝር የፍላጎት መግለጫ ወረቀት (expression of interest) ለቦርዱ እንድታቀርቡ ጥሪ ያቀርባል።

    የፍላጎት መግለጫ ማካተት የሚገባቸው ዋና ዋና ሃሳቦች

    ማንኛውም የምርጫ ክርክር ለማከናወን የሚያስብ ተቋም የሚመለከቱትን ዋና ዋና ነገሮችን ያሟላ የፍላጎት መግለጫ ሊያቀርብ ይገባል።

    • ሊያከናውኑት ያቀዱት የምርጫ ክርክር ግልጽ ዓላማ፣
    • ሊያከናውኑት ያቀዱት ክርክሩ የሚከናወንበት መንገድ (mode of engagement)፣
    • ሊያከናውኑት ያቀዱት የክርክሩ ሥነ-ምግባር ደንብ (code of conduct)፣
    • የክርክሩ ቁጥር ብዛት፣ የተሳታፊዎች ሁኔታ፣ ለሕዝብ የሚቀርብበት ሁኔታ፣
    • የአከራካሪ አመራረጥ ሂደት፣ መስፈርት እና መመዘኛ፣
    • ክርክሩ ለሕዝብ የሚቀርብበት መንገድ፣
    • በጀት እና የገንዘብ ምንጭ፣
    • ክርክሩን የሚከናወንባቸው ቋንቋዎች እና የመሳሰሉት፣

    ከላይ ከተጠቀሱት ዋና ዋና ጉዳዮች በተጨማሪ ምክረ-ሃሳብ የሚያስገቡ ተቋማት አስፈላጊ ነው የሚሉትን ዝርዝር ዕቅድ በምክረ-ሃሳባቸው ውስጥ አካተው ማቅረብ ይችላሉ። ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ክርክሩን በማመቻቸት ብሔራዊ ክርክር መከናወንን ከማመቻቸት በተጨማሪ ለክርክር ዝግጅት የሚሆን የፋይናንስ ድጋፍ አያደርግም።

    የፍላጎት መግለጫ ወረቀት እስከ የካቲት 26 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ (በአምስት የሥራ ቀናት ውስጥ) በቦርዱ ዋና መሥሪያ ቤት በግንባር ወይም በ media@nebe.org.et ኢ-ሜይል አድራሻ ሊቀርብ እንደሚችል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል።

    ከምርጫ ቦርድ መግለጫ ሳንወጣ፥ ቦርዱ ለ6ተኛው አጠቃላይ ምርጫ የእጩዎች ምዝገባን እያከናወነ ባለበት በአሁኑ ወቅት የመጀመሪያ ዙር የእጩ ምዝገባ የሚከናውንባቸው ክልሎች እና የከተማ መስተዳድሮች ማለትም፦

    • የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር
    • የድሬደዋ ከተማ መስተዳድር
    • የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልል
    • የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ብሔራዊ ክልል
    • የጋምቤላ ብሔራዊ ክልል
    • ሃሪሪ ብሔራዊ ክልል ለእጩዎች ምዝገባ የተቀመጠው የጊዜ ገደብ መሠረት የካቲት 08- 21 ድረስ እንደሚከናወን ማሳወቁ ይታወቃል።

    ቦርዱ የእጩዎች ምዝገባ ሂደትን በመገምገም የምርጫ ክልል ቢሮዎች ለመከፈት በመዘግየታቸው፥ የትራንስፓርት መጓተት የተወሰኑ የምርጫ ክልሎች ላይ የምዝገባ ቀንን በማራዘሙ እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲዎች በተለያዩ ምክንያቶች እጩዎችን ለመመዝገብ ችግር ስላጋጠመን ይራዘምልን ብለው ጠይቀዋል። በመሆኑም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከላይ የተጠቀሱትን አሳማኝ ምክንያቶች በማየት የመጀመሪያ ዙር ምዝገባ በጀመሩት ከላይ በተጠቀሱት ክልሎች/የከተማ መስተዳድሮች ላይ የሚካሄደው የእጩዎች ምዝገባ ለ4 ቀናት ያህል እስከ የካቲት 25 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ መራዘሙን አስታወቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

    የምርጫ ክርክር

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀ መንበር ብርቱካን ሚደቅሳ መጪውን ሀገራዊ ምርጫ አስመልክተው ያስተላለፉት መልዕክት

    መልካም ዕድል ለተወዳዳሪዎች

    የተከበራችሁ የፓርቲዎች አመራር አባላት፣ የፓርቲ ዕጩ ተወዳዳሪዎች እና በግላችሁ የምትሳተፉ ዕጩዎች፥

    ዛሬ ለ6ኛው አጠቃላይ ምርጫ በዕጩነት ስትመዘገቡ ወይም እንደ ፓርቲ ዕጩዎቻችሁን ስታስመዘግቡ ከፊታችን ያለው መንገድ ከፊል ተስፋ፣ ከፊል ስጋትን አዝሎ እንደሚጠብቃችሁ፣ እንደሚጠብቀን ለሁሉም ግልፅ ነገር ይመስለኛል። ይሁን እና ስጋትን ለመቀነስ፥ ብሎም ወደ መልካም ሁኔታ ለመቀየር የሚያስችለን አቅም እና ዕድል በየፈርጃችን ይዘን ይህን የጋራ ሙከራችንን በዝለት ሳይሆን በጥንካሬ ልንጀምረው ይገባል እላለሁ።

    በቀደሙ ምርጫዎቻችን ባልነበረ ሁኔታ የሂደቱን ዋና ተዋናዮች፥ ማለትም ተፎካካሪዎቹን ግራ ወይም ቀኝ፣ ትንሽ ወይም ትልቅ፣ ሀገራዊ ወይስ ክልላዊ ሳይል፣ በጥረታቸው ሊያግዝ እና ሳንካቸውን ሊፈታ የተዘጋጀ፣ አቅሙን የጨመረ፣ የገለልተኝነቱን መጠን እና ስፋት ከተፅእኖ ሁሉ የሚከላከል የምርጫ ቦርድ ሂደቱን እያስተዳደረ ይገኛል።

    በፍትሃዊነት በተቃኘ በጎ ሀሳብ ሳይሆን በሸፍጥ፣ ሌላውን በማክበር ሳይሆን ማንኛውንም መንገድ ተጠቅሞ በእንፃሩ የቆመውን በማጥፋት ባለመ ሀሳብ፣ የሁሉንም የዜጎችን ሀሳብን የመግለፅ ሰላማዊ ዕድል ሳይሆን ኋላቀር የሆነ ግጭታዊ መስተጋብርን ታሳቢ ያደረገ አቅጣጫን ያሰበ ተወዳዳሪ ቢኖር ይህን ከምርጫ ፖለቲካ ውጪ የሆነ ሥራውን ለአደባባይ አውጥተው ለሰው ዓይን እና ጆሮ ሊያደርሱ የሚችሉ በቁጥር ትንሽ የማይባሉ የሚዲያ አውታሮች እንደ ሀገር ያለን መሆኑም ለተሻለ ሽግግር ወደፊት ለመቀጠል የሚያስችል አንድ በጎ እውነታ ነው።

    የሲቪል ማኅበራቶቻችንንም አናቂ ይባል ከነበረ የሕግ ማእቀፍ ወጥተው ዜጎችን ስለእውነተኛ ምርጫ ሊያሳውቁ፥ እንዲሁም የምርጫ ሂደታችን ጉበኛ /watchman or watchwomen/ ሆኖ በታዛቢነት ለማገልገል በጣት በሚቆጠሩ ሳይሆን በመቶዎች በሚቆጠሩ አደረጃጀቶቻቸው ላይ መሰናዶአቸውን ለማጠናቀቅ ደፋ ቀና ይላሉ።

    የአውሮፓ እና የአሜሪካ ታዛቢዎችም ይህን ለሀገራችን ትልቅ ትርጉም ያለውን ኩነት በእንግድነት ሊታዘቡ ከመንግሥት ግብዣው ደርሷቸው ከእኛው ጋር የሂደቱ አካል ሊሆኑ ዝግጅታቸውን እያጠናቀቁ ነው።

    ብዙ ሌሎች የምርጫ ማሻሻያችን ብዙ ጎኖች መጥቀስ ይቻላል። ሆኖም በዚህ እንደ ብርቱካን ሚደቅሳ በማወጣው የመጀመሪያ የፌስቡክ መልዕክቴ በዝርዝር ላሰለቻችቸሁ አልወደድኩም።

    ለማጠቃለል፥ ዛሬ ፓርቲዎች በሀገራችን የተለያየ አካባቢ ዕጩዎችን በማስመዝገብ፣ በዕጩነት በመመዝገብ የምርጫ ዘመቻውን ምዕራፍ ስትከፍቱ ለሂደቱ የሚጠቅም በጎ እሴት ለመጨመር፣ በችግር ፈቺነት በጋራ ለመሥራት፣ የፖለቲካ ጥቃትን አሮጌ ባህል እለት እለት ለመግደል (old habits die hard ወይም ከክፉ አመል መላቀቅ በቀላሉ አይሆንም የሚለውን ያስቧል)፤ ለዘመናዊ እና ስልጡን ውድድር ራሳችንን ለማደስ፣ ከምንም በላይ የዜጎቻችንን ባለስልጣንነት በማክበር እንዲሆን እያሳሰበኩ፥ በዚህ አስፈላጊ እና ትልቅ ትርጉም ባለው ሥራ የሁላችንንም አብሮነት እና የእያንዳንዳችንን ድርሻ ሳንረሳ በበጎ መንፈስ የምርጫ ውድድሩን እንጀምር ስል ጥሪዬን አቀርባለሁ።

    በድጋሚ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያለበትን ሕጋዊ ኃላፊነት እና ግዴታ እንደሚወጣ፣ እየተወጣም እንደሚገኝ አረጋግጥላችኸዋለሁ።

    መልካም የምርጫ ዘመን!
    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀ መንበር ብርቱካን ሚደቅሳ

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀ መንበር ብርቱካን ሚደቅሳ

    Anonymous
    Inactive

    በብልፅግና ሰልፎች ላይ ፓርቲዎች የሚመሩባቸው ሥነ ምግባሮች ተጥሰዋል
    ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተሰጠ መግለጫ

    ጥር 25 ቀን 2013 ዓ.ም. በተለያዩ የኦሮሚያ ከተሞች ለብልፅግና ፓርቲ ድጋፍ ለማሳየት የተለያዩ ሰልፎች መካሄዳቸው ይታወቃል። እነዚህን ሰልፎች ተከትሎ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) “ፓርቲያችን ያለአግባብ ተወንጅሏል፤ ይህም ፓርቲዎች የፈረሙትን የጋራ የሥነ ምግባር ደንብ የጣሰ ነው” ሲል አቤቱታውን ለቦርዱ አቅርቧል። ብሔራዊ ምርጫ ቦርድም ከአቤቱታው በተጨማሪ በዕለቱ የተደረጉ የተለያዩ ሰልፎችን በሚዲያ ክትትል ክፍሉ አማካኝነት ክትትል በማድረግ በአሜሪካ ድምጽ፣ በዋልታ፣ በፋና፣ በኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትወርክ እንዲሁም በእነዚሁ ሚዲያዎች የማኅበራዊ ሚዲያ ገጾች በቀጥታ የተላለፉ መልእክቶችን በማየት፦

    • ሠልፎቹ በዋልታ ቴሌቪዥን እና በኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትወርክ በቀጥታ መተላለፋቸውን እንዲሁም የመንግሥት አመራር አካላት፣ የብልፅግና ፓርቲ አመራሮች እና ደጋፊዎች መሳተፋቸውን ተረድቷል፤
    • ከሚዲያዎቹ በቀጥታ ከመተላለፉም በተጨማሪ የተለያዩ የመንግሥት አመራር አባላት በሰልፎቹ ላይ ያደረጓቸውን ንግግሮች ተመልክቷል፤
    • በሰልፎቹ የተለያዩ መፈክሮች፣ በተወሰኑ የመንግሥት የዞን፣ የከተማ አስተዳድር አመራር አካላት እና ብልፅግናና ፓርቲ ኃላፊዎች ንግግሮች በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተመዘገቡ እና የምርጫ ምልክቶቻቸውን የመረጡ ፓርቲዎች በአሉታዊ መልኩ መነሳታቸውን ተገንዝቧል።

    እነዚህ ሰልፎች ላይ የተነሱ ንግግሮች እና መፈክሮች በሕጋዊነት ተመዝግበው፣ በፖለቲካ ፓርቲነት የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎችን ማለትም አማራ ብሔራዊ ንቅናቄባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ እና የኦሮሞ ነጻነት ግንባር በአመፃ ተግባር በመሳተፍ ከምርጫ ቦርድ ከተሰረዘው ጁንታ በማለት ከሚጠሩ ህወሓት ፓርቲ ጋር አንድ በማድረግ፣ የኢትዮጵያ ጠላት ናቸው ብሎ በመፈረጅ እና ሕገ ወጥ ናቸው በማለት የምርጫ፣ ፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ እና ሥነ ምግባር ሕግ 1162/2011 ላይ ያሉ ድንጋጌዎችን ጥሰዋል።

    ቦርዱ ሰልፎቹ ላይ የተንጸባረቁት ንግግሮች እና መፈክሮች በአዋጁ አንቀጽ 132 ንዑስ 2(ሀ) ላይ የተጠቀሰውን ስም የሚያጠፋ ንግግርን ክልከላ ድንጋጌ አንዲሁም በዚሁ ሕግ አንቀጽ 143 (2) ላይ የተጠቀሰውን ሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች ሀሳባቸውን በነጻነት እንዳያሰራጩ ስጋት እና ፍርሀት የመፍጠር የሥነ ምግባር ጥሰት ፈጽሞ አግኝቶታል። ከዚህም በተጨማሪ ከላይ ስማቸው የተጠቀሱት የፖለቲካ ፓርቲዎች እና ገዥው ፓርቲ በጋራ ተስማምተው በፈረሙት የቃልኪዳን ሰነድ አንቀጽ 8 ንዑስ አንቀጽ 1 ላይ የተጠቀሰውን “የሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች በየትኛውም ጉዳይ ላይ ሊኖር የሚችል የዓላማ፣ የሃሳብ ወይም የዘር ልዩነትን፣ ወይም ሌላ ምክንያት መሠረት በማድረግ የሌሎች ፓርቲዎችን መብቶች የሚፃረሩ ወይም የሚያጣብቡ ድርጊቶችን ከመፈፀም የመቆጠብ ግዴታ አለባቸው” የሚለውን አንቀጽ የሚጥስ ተግባር ነው።

    ይህ ተግባር በተለይ ቦርዱ የመጨረሻ የጊዜ ሰሌዳ አውጥቶ የምርጫ ተግባራት በይፋ መፈጸም ከጀመረ በኋላ በምንገኝበት የምርጫ ወቅት መከሰቱ በምርጫ ውድድር ላይ ፓርቲዎች በእኩልነት የመወዳደር መብታቸውን ችግር ላይ የሚጥል በመሆኑ ቦርዱን በእጅጉ አሳስቦታል። በመሆኑም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በየደረጃው ያሉ የገዥው ፓርቲ አመራሮች እና በየአስተዳደር እርከኑ ያሉ የመንግሥት ኃላፊዎች በተመሳሳይ ተግባራት ከመሳተፍ እንዲቆጠቡ ያሳውቃል።

    ለወደፊትም በተመሳሳይ በምርጫ፣ ፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ እና ሥነ ምግባር ሕግ 1162/2011 እና ተያያዥ መመሪያዎች መሠረት የፓርቲዎች የቅስቀሳ የንግግር እና ሌሎች ለሕዝብ የሚያሰራጯቸውን መልዕክቶች ላይ ክትትል በማድረግ አስፈላጊውን እስከእጩ መሠረዝ የሚደርስ አስተዳደራዊ እርምጃ ሊወስድ እንደሚችል ያሳውቃል።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ
    ጥር 26 ቀን 2013 ዓ.ም.

    በብልፅግና ሰልፎች ላይ ፓርቲዎች የሚመሩባቸው ሥነ ምግባሮች ተጥሰዋል ― ምርጫ ቦርድ

    Anonymous
    Inactive

    የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) የአመራሮች ክፍፍልን አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተሰጠ መግለጫ

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በተቋቋመበት አዋጅ 1133/2011 በምርጫ በፖለቲካ ፓርቲዎች እና በሥነ ምግባር አዋጅ 1162/2011 በተሰጠው ስልጣን መሠረት ፖለቲካ ፓርቲዎች ድጋፍ እና ቁጥጥር የሚያደርግ ተቋም ነው። በዚህም መሠረት በኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ፓርቲ አመራሮች መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት ሕጋዊ እና ተደጋጋሚ ጥረቶችን ሲያደርግ እንደነበር ይታወሳል።

    በዚህም መሠረት፦

    1. የፓርቲው የተወሰኑ የሥራ አስፈጻሚ አባላት ነሐሴ 01 ቀን 2012 ዓ.ም. በተጻፈ እና በድርጅቱ ምክትል ሊቀ-መንበር በተፈረመ ደብዳቤ የድርጅቱን ሊቀ-መንበር መታገዳቸውን ለቦርዱ አሳውቀው እንደነበር፤ ከዚህም በተጨማሪ የድርጅቱ አመራር ላይ ተከታታይ አቤቱታዎች አስገብተው እንደነበር ይታወሳል። በሌላ በኩል የድርጅቱ ሊቀ-መንበር መስከረም 02 ቀን 2013 ዓ.ም. ድርጅቱ ብሔራዊ ምክር ቤት ስብሰባ አድርጎ የፓርቲውን ምክትል ሊቀ-መንበር፣ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላትን እንዲሁም የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት እስከሚቀጥለው የድርጅቱ ጠቅላላ ጉባዔ ድረስ ከኃላፊነታቸው ታግደው እንዲቆዩ እንደወሰነ ለቦርዱ አሳውቀዋል።
    2. ፖለቲካ ፓርቲ አባላት መካከል አለመግባባት ሲከሰት እና ለቦርዱ አቤቱታ ሲቀርብለት በአዋጅ ቁጥር 1162/11 አንቀፅ 74 ንዑስ አንቀፅ 6 መሠረት ጉዳዩን ተመልክቶ የውሳኔ ሃሳብ የሚያቀርብ የባለሙያዎች ጉባዔ ለማቋቋም በተሰጠው ስልጣን መሠረት በማድረግ የሁለቱንም ቡድኖች ደብዳቤዎች እና አቤቱታዎች፣ እንዲሁም የውስጥ ሕጎች የሚያይ የባለሞያዎች ኮሚቴ ለማቋቋም ውሳኔ አሳልፎ እንደነበርም ይታወሳል። በዚህም መሠረት በእነ አቶ አራርሶ በኩል ባለሞያ ቢመድቡም፥ በእነ አቶ ዳውድ በኩል ባለሞያ ለመመደብ ፍቃደኛ ካለመሆናቸውም በላይ የፓርቲው የውስጥ ደንብ መሠረት መጠናቀቅ ያለበት ጉዳይ ነው በማለት መልስ በመስጠታቸው የባለሙያዎች ጉባዔ ማቋቋም ሳይሳካ ቀርቷል።
    3. በኦነግ አመራር መካከል የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት የተደረገው የመጀመሪያው የቦርዱ ጥረት ባለመሳካቱ ጉዳዩን ከባለሞያዎች ጉባዔ ይልቅ በራሱ ሊያየው ተገድዷል። በዚህም መሠረት ከሁለቱም ወገን የገቡትን እገዳዎች በማየት እና የገቡ ሰነዶችን በመመርመር፥ እንዲሁም ከሁለቱም ቡድን አመራሮች ጋር እንዲሁም ከሥነ ሥርዓት እና ቁጥጥር ኮሚቴ አመራር አባላት ጋር ሰፊ ውይይት አድርጓል። በውይይቱም ወቅት ፓርቲው አመራር ቀውስ ውስጥ እንደገባ፣ ለአባላቱ አመራር መስጠት የሚችልበት ሁኔታ ላይ እንዳልሆነ፣ በተለይም ደግሞ ሁለቱም ቡድኖች ያቀረቧቸው እገዳዎች ሕጋዊ እንዳልሆኑ ቦርዱ ወስኗል። በዚህም መሠረት የሁለቱም ወገን እገዳ የቀረበባቸው አባላት በነበራችው ሕጋዊ ኃላፊነት ላይ እንደሚቆዩ ወሰነ።

    በተጨማሪም ሁለቱም አካላት ሕጋዊ ሂደቱ የተሟላ ሰነድ ባለማቅረባቸው፣ ፓርቲው ያለበት የአመራር ቀውስ ለመፍታት አለመቻላቸውን በመረዳት ቦርዱ የአመራር መከፋፈሉን  ጠቅላላ ጉባዔ በማከናወን የፓርቲው አባላት መሪዎቻቸውን እንዲመርጡ ታኅሣሥ 08 ቀን 2013 ዓ.ም. ባደረገው ስብሰባ ከመወሰኑም በተጨማሪ፥ የጠቅላላ ጉባዔውን ለማመቻቸት ኃላፊነቱንም እንደሚወስድ አሳውቆ እንደነበር ይታወሳል።

    1. ከላይ በተጠቀሰው ውሳኔ መሠረት ለሁለቱም አመራር ቡድኖች ቦርዱ ውሳኔ በደብዳቤ ደርሷቸው የመጀመሪያውን ውይይት በቦርዱ አመቻችነት በጋራ ለማከናወን የመጀመሪያውን የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ አባላት ጥሪ ቢደረግላቸውም በድርጅቱ ምክትል ሊቀመንበር አቶ አራርሶ የሚመራው የሥራ አስፈጻሚ ቡድን ቦርዱ በጠራው ስብሰባ ላይ ሲገኝ፥ በአቶ ዳውድ የሚመራው ቡድን ግን “ቦርዱ ይህንን የማመቻቸት ሕጋዊ ሚና የለውም” በማለት በውይይቱ ላይ አልገኝም በማለታቸው በቦርዱ የተደረገው ጥረት አሁንም ሊሳካ አልቻለም።
    2. ይህ ሂደት በዚህ ላይ እንዳለ ሁለቱም ወገኖች የተለያዩ አስተዳደራዊ ጉዳዮችን ሚመለከቱ ማመልከቻዎችን ለቦርዱ ማቅረባቸውን ቀጥለዋል።
    3. የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጥር 19 ቀን 2013 ዓ.ም. ባደረገው የቦርድ አመራር አባላት ስብሰባ በኦነግ ሥራ አስፈጻሚ መከፈልን አስመልክቶ እስከአሁን የተደረጉ ጥረቶችን እና ለመፍታት የወሰዳቸውን እርምጃዎች በዝርዝር መርምሯል። በዚህም መሠረት ቦርዱ እጁ ላይ ባሉት የሕግ እና የአስተዳደር መሣሪያዎች በመጠቀም ሊያግዝ የሚችልበት ተጨማሪ አሠራር አለመኖሩን ተረድቷል።
    4. በዚህም መሠረት የኦሮሞ ነጻነት ግንባር አባላት፣ የተለያዩ የድርጅቱ መዋቅሮች እና አመራሮች ለችግሩ መፍቻ ሊሆን የሚችለውን ጠቅላላ ጉባዔ እንዲያደርጉ ቦርዱ ማሳሰብ እንደሚገባው ወስኗል። በመሆኑም ፓርቲው በመሀከሉ ያለውን አለመግባባት በሥራ አስፈጻሚ አመራሮቹ ሊፈታ ባለመቻሉ የተለያዩ የድርጅቱ መዋቅሮች እና አባላት አውቀው ጠቅላላ ጉባዔ እነዲከናወን የሚያደርጉባቸውን ማንኛውንም መንገዶች እንዲጠቀሙ ቦርዱ በጥብቅ ያሳስባል።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ
    ጥር 27 ቀን 2013 ዓ.ም.

    የኦሮሞ ነፃነት ግንባር የአመራሮች ክፍፍልን አስመልክቶ ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተሰጠ መግለጫ

    Anonymous
    Inactive

    የጥላቻና ዘር ፍጅት ቅስቀሳ በውጤት ደረጃ ሀገርና ሕዝብን የህልውና አደጋ ላይ ይጥላል
    ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ!

    ድርጅታችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በሀገራችን ውስጥ እስካሁን የተካደው ኢትዮጵያዊ ዜግነት ተገቢውን እውቅና እንዲያገኝ፣ ዜግነት የፖለቲካችን ማዕከል እንዲሆን የሚያስችል መሠረታዊ የትርክት ለውጥና የመዋቅር ክለሳ እንዲደረግ በርካታ ጥሪዎችን ሲያደርግ ቆይቷል። ለሀገራችችን የፖለቲካ ምስቅልቅል (crisis) መነሻ የሆነው የጥላቻ ትርክት በሕገ-መንግሥትና በመዋቅሮች መስረፅ ምክንያት መሆናቸውን በመገንዘብ፥ ሕዝባችን ከባድ መስዋዕትነትን የጠየቀ የለውጥ እንቅስቃሴ ሲያደርግ ቆይቷል። በዚህም ቀላል የማይባሉ እመርታዎችን ያስመዘገበ ቢሆንም፥ በዋናነት የአፋኙ ሥርዓት አካልና ወራሽ የሆነ ስብስብ የሕዝባችንን ቅን ልቦና ባጎደፈ መልኩ የጽንፈኝነት ባህሪውን ለጊዜው ደብቆና ስሙን ብቻ ቀይሮ የሕዝባችንን የለውጥ ሂደት አግቶት ይገኛል።

    የአማራ ሕዝብና የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) በትሕነግ ላይ የነበረው አቋም የተፈተሸ፣ የጠራና የነጠረ ስለመሆኑ አስረጅ አያስፈልገውም። አብን ከሁለት ዓመታት በፊት ትሕነግ ሽብርተኛ ድርጅት መሆኑን በመጥቀስ ከሰላማዊ የፖለቲካ ፖርቲዎች ዝርዝር እንዲሰረዝና ጉዳዩ በሕግ የበላይነት ማዕቀፍ እንዲታይ ማሳሰቡ ይታወሳል።  በወቅቱ መንግሥት ከትሕነግ ጋር አብሮ በአንድ ጥምረት ውስጥ ሆኖ የሚሠራበት ነበር። አብዛኛው የሀገራችን የፖለቲካ ኃይሎች በአብን መግለጫ ቢያንስ ተደናግጠው እንደነበር የሚታወስ ሃቅ ነው።

    አብን የአማራ ሕዝብ ሁለንተናዊ ንቅናቄ አካል እንደመሆኑ መጠን ዝቅተኛው የፖለቲካ ስምሪቱ ሀገራችን በጽንፈኛ ኃይሎች ቅንጅት እጅ ዳግም እንዳትወድቅ መከላከል ነው። የኮሮናቫይረስ (COVID-19) ወረርሽኝ ስጋትን ተከትሎ በሀገራዊ የምርጫ መርኃግብር ላይ በታየው የፖለቲካ ችግር ወቅት የወሰድነው አቋም አብን ኢትዮጵያን በተመለከተ ላለው የማያወላዳ አቋም ዓይነተኛ ጠቋሚ መሆኑ አያከራክርም።

    ድርጅታችን አብን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ችግር ሊፈታ የሚችለው መሠረታዊ ለውጦችን በማድረግ እንጅ በስምና በቅብ ለውጥ ሊሆን እንደማይችል በመረዳት ሀገራችን በሽግግር መንግሥት ምሥረታ ሳይሆን በሽግግር ጊዜ ምዕራፍ ማለፍ እንዳለባት አሳውቆ ነበር። በተያያዘ ሁኔታ በሽግግር ጊዜ ውስጥ ዘላቂ እልባት ማስገኘት የሚችሉ አንኳር የለውጥ ተግባራት መፈፀም እንዳለባቸው ገልፆ ጥሪ ማስተላለፉም ይታወሳል። ነገር ግን በጥሬ የስልጣን ግብግብና በጥላቻ ባሕል የተቃኘው የሀገራችን አጠቃላይ የፖለቲካ ስምሪት ዘላቂ ተግዳሮት ሆኖ በመቀጠሉ፥ ተፈላጊው ለውጥ እውን ሊሆን ካለመቻሉም በላይ በሕዝባችን ላይ ተከታታይ የዘር ማጥፋትና የዘር ማፅዳት ጥቃቶች ተፈፅመዋል። የዜሮ ድምር የፖለቲካ ዘይቤን የቀጠለ ሲሆን በሀገራዊ መግባባትና ትብበር መሠራት ያለባቸውን ጉዳዮች በፉክክርና በጥላቻ ለመፍታት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ሊገቱ ባለመቻላቸው ምክንያት የሕዝባችን ትግል ገና ተቀናጅቶና ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተገንዝበናል።

    በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያዊነትን እና የኢትዮጵያዊነትን ትሩፋቶች በብቸኝነት ለመበየንና ለማከፋፈል የቋመጡ ጽንፈኛ መንግሥታዊ አካላት ሀገራችንን ተፈትሾ በወደቀው የሴራ ፖለቲካቸው አዙሪት ውስጥ ለማቆየት ከፍተኛ ርብርብ እያደረጉ ይገኛሉ። በርካታው የሀገራችን ክፍል የደህንነት ስጋት ያንዣበበት ሲሆን፥ የሕዝብ በሰላም የመንቀሳቀስም ይሁን በሕይወት የመኖር መብት በመደበኛነት አደጋ ውስጥ ይገኛል።

    አብን በዚህ ዓመት በሚካሄደው ሀገራዊ ምርጫ ለመሳተፍ ሲወስን የጥላቻና የሴራ ፖለቲካ ግንባር ቀደም ተጠቂ ድርጅት በሆነበት አግባብ ነው። የምርጫ ትርጉም በአንድ ቀን ውስጥ ተከፍቶ በሚዘጋ ሳጥን ውስጥ በሚጨመሩ ካርዶች የታጠረ እንዳልሆነም ይገነዘባል። በሀገራችን ውስጥ ያለው የቅድመ ምርጫ መደላድል ያለበት ሁኔታ ለሕዝባችን የተሰወረ አይደለም። በተለይም የአማራን ሕዝብ ማገት የፖለቲካ ስልት ሆኖ የቀጠለ እውነታ ነው፤ አብን የአማራ ሕዝብ ሀቀኛና የማያወላዳ እንዲሁም ጸረ-ጭቆናና ጸረ-ዘረኝነት የትግል እንቅስቃሴ በቀጥታ የወለደው ድርጅት በመሆኑ አማራን የሚፈርጁና የሚያጠቁ ጽንፈኞች ዓይናቸውን ለአፍታ እንኳን ዘወር እንደማያደርጉለት ይታወቃል።

    ከአማራ ክልል ውጭ በተለይም በኦሮሚያና በቤኒሻንጎል ክልል ውስጥ ባሉት የአብን መዋቅሮችና አመራሮች ላይ የተለያዩ ጥቃቶች ሲፈፀሙም ቆይተዋል፤ አሁንም ቀጥለዋል። በተለይም የክልሎቹ ባለስልጣናት በሆኑ የብልፅግና ፖርቲ አባላት የሚፈፀሙ ችግሮች መሆናቸውን መነሻ በማድረግ፥ ከፖርቲው ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመነጋገር ለመፍታት ጥረት ሲያደርግ ቆይቶ ባለመሳካቱ ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ማመልከቻ አቅርቦ በምርመራ ላይ ይገኛል።

    ጉዳዮቹ በዚህ አግባብ በሚገኙበት ሁኔታ ጭምር “የኦሮሞ ብልፅግና” ከፍተኛ አመራሮች በማኅበራዊ ድረ-ገፅ በአብን፣ በአመራሮቻችን፣ አባላቶቻችን፣ ደጋፊዎቻችን እና በአጠቃላይ በአማራ ሕዝብ ድርጅቶችና አመራሮች ላይ የሀሰት፣ የአፍራሽና የጥቃት ጥሪዎችን በተደጋጋሚ እያስተላለፉ ይገኛሉ። የብልፅግና ፖርቲ እንደተቋም በሚፈፀሙ ጥሰቶች ላይ ምንም ዓይነት ተጨባጭ እርምት ለማድረግ ባለመፈለግ በቀጥታ የተቀበላቸውና የአማራን ሕዝብ በተመለከተ ያለውን አቋም በምግባር፣ በድርጊትና በቸልታ አረጋግጧል።

    ጥር 25 ቀንም በተለያዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች በተደረጉ ሰልፎች በዋናነት አብንን የሚያጠለሹና የሚያወግዙ እንዲሁም በሕዝባችን ላይ ቀጣይ ስጋትን የጋረጡ ድምፆች ከፍ ብለው ሲስተጋቡ ተሰምተዋል። አብንን “ከኦነግ ሸኔ” ጋር የሚያመሳስሉ መፍክሮች ተሰምተዋል።

    ስለሆነም፦

    1/ በቅርቡ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ እየተፈፀመ ያለውን ገደብ የለሽ የፖለቲካ ነውረኝነትና የዘረኝነት እንቅስቃሴ ለመቃወም በባልደራስ ፓርቲ ተጠርቶ የነበረውን ሕዝባዊ ሰልፍ በማንአለብኝነት የከለከለ መንግሥት ለፖርቲ ፍጆታ ሲሆን ሰልፍ መጥራቱና መፍቀዱ፤

    2/ በሰልፉ ላይ (ጥር 25 ቀን 2013 ዓ.ም. የተደረገው የብልፅግና ፓርቲ ሰልፍ) የጥላቻና የጥቃት ጥሪዎችን ሲመሩ የነበሩት በስምና በኃላፊነት የሚታወቁ የመንግሥትና የብልፅግና ፖርቲ አመራሮች መሆናቸው፤

    3/ ጥር 25 ቀን 2013 ዓ.ም. በተደረገው የብልፅግና ፓርቲ ሰልፍ ላይ ጎልተው የተሰሙት ድምፆች የክልሉ አመራሮች በማኅበራዊ ድህረ-ገጽ ሲፅፏቸው የነበሩ ኃሳቦች ቀጥተኛ ግልባጭ መሆናቸው፤

    4/ በዚህም በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በአጠቃላይ ያለውን የፖለቲካ አፈና ወደተሟላ እርከን ለማሸጋገር በማሰብ አብን በክልሉ ውስጥ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ለመግታትና በክልሉ የሚኖረውን የአማራ ሕዝብና ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ በጭቆና ቀንበር ስር የማቆየት ዓላማ ያነገበ ተግባር መሆኑ፤

    5/ በተለይም ጥር 25 ቀን 2013 ዓ.ም. በተደረገው የብልፅግና ፓርቲ ሰልፍ ላይ በአማራ ሕዝብ ላይ በተደጋጋሚ የዘር ፍጅት ለመፈፀም ጽንፈኛ ኃይሎች መንደርደሪያ አድርገው የሚጠቀሙበት “ነፍጠኛ” የሚለው ቃል በሰፊው ሲገለፅ የነበረና በግልፅም “ነፍጠኛ ይውጣ” የሚል ሀሳብ ሲሰማ የነበረ መሆኑ፣

    6/ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያሉ ኃላፊነት የጎደላቸው ጽንፈኛ አመራሮች በአማራ ሕዝብ ላይ እየደረሰ ላለው ጥቃት ሽፋን በመስጠትና በቀጥታ በመሳተፍ እንደሚያስፈፅሙ የተረጋገጠ ጉዳይ ሆኖ እያለ፥ በታየው ደረጃ የተላለፈውን የጥላቻና የጥቃት ጥሪ የመንግሥት ሚዲያዎች መዘገባቸው እና የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትርም እርምት መስጠት እየተገባቸው፥ ‘ቡራኬ’ መስጠታቸው እጅግ አሳዛኝ የሆነና በቀጣዩ የሀገራችን የፖለቲካ ሂደት ላይም ከፍተኛ ስጋትን እንደሚፈጥር መረዳት ይቻላል።

    በአጠቃላይ የሀገራችንን የፖለቲካ እንቅስቃሴ የተለየ ፖለቲካዊ እይታ የማስተናገድ ዝንባሌና ቀጣዩን ምርጫ በተመለከተ በመንግሥት በኩል እየታየ ያለው አቋምና አፍራሽ እንቅስቃሴ በአስቸኳይ እንዲቆም እየጠየቅን፥ የአብን የብሔራዊ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ጉዳዩን በቀጥታ ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድና በግልባጭ ለሚመለከታቸው አካላት በደብዳቤ አሳውቋል።

    በመጨረሻም መላው ኢትዮጵያውያን፥ በተለይም የአማራ ሕዝብ፥ የብልፅግና ፓርቲ ሰልፍ ላይ የተስተጋባው የጥላቻና ዘር ፍጅት ቅስቀሳ በውጤት ደረጃ ሀገርና ሕዝብን ለህልውና አደጋ የሚጥል መሆኑን በመረዳት የተፈፀመውን አስነዋሪ ድርጊት በጽኑ እንዲያወግዝና አብን ከሚያደርጋቸው የፍትህ፣ እኩልነትና ነፃነት ትግሎች ጎን እንዲሰለፍ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

    የሴራ ፖለቲካ ምዕራፍ የሚዘጋበት፣ የጥላቻና የፍረጃ ፖለቲካ ላንቃ የሚዘጋበት ጊዜው አሁን ነው!

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)
    ጥር 25 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፤ ሸዋ፤ ኢትዮጵያ!

    የጥላቻና ዘር ፍጅት ቅስቀሳ በውጤት ደረጃ ሀገርና ሕዝብን የህልውና አደጋ ላይ ይጥላል

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ለምርጫ አስፈፃሚነት ከተመለመሉት ሰዎች መሀከል ጥያቄ ያነሳባቸውን ለምርጫ ቦርድ አመለከተ

    ‘የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለምርጫ አስፈፃሚነት የመለመላቸው የምርጫ አስፈፃሚዎች ገለልተኛ ናቸው ወይስ አይደሉም?’ የሚለውን ለማጣራት ለሁሉም ፖለቲካ ፓርቲዎች የአስፈፃሚዎቹን ስም ዝርዝር በመላክ ማጣራት እያካሄደ ነው። ቦርዱ አስፈጻሚዎችን ከመለመለ በኋላ የተመለመሉትን አስፈጻሚዎች ስም ዝርዝር ለፖለቲካ ፓርቲዎች በመላክ ፓርቲዎች ገለልተኝነታቸው ላይ አስተያየታቸውን እንዲሰጡ እንደሚያደርግ መናገሩ የሚታወስ ነው። በዚህም መሠረት በመጀመሪያው ዙር ወደ 750 ምርጫ አስፈጻሚዎች ስም ዝርዝር የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ደርሶታል።

    የተላኩላቸውን ምርጫ አስፈጻሚዎች የፓርቲውን መዋቅር በመጠቀም ገለልተኝነታቸውን ለማጣራት ሙከራ እንዳደረጉ ለዜጎች መድረክ የገለፁት የኢዜማ ድርጅት ጉዳይ ኃላፊ አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ፥ ዜጎች መድረክ ከዚህ ቀደም የምርጫ አስፈፃሚዎቹን ስም ዝርዝር ይዞ ለማጣራት አቅም አላችሁ ወይ ብላ ጥያቄ አንስታላቸው እንደነበር አስታውሰው፤ የፓርቲውን መዋቅር በመጠቀም ምርጫ ቦርድ የመለመላቸውን ምርጫ አስፈጻሚዎች ገለልተኝነት ማጣራት መቻላቸውን ተናግረዋል። በማጣራት ሂደቱም አንዳንዶቹ የምርጫ አስፈፃሚዎች ከዚህ ቀደም የኢሕአዴግ አባል የነበሩ አሁን ደግሞ የብልፅግና አባል መሆኑን እንደደረሱበትና ይህንንም በማስረጃ በማስደገፍ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መላካቸውን ለዜጎች መድረክ አስታውቀዋል።

    “የእኛ መዋቅሮችም የብልፅግና አባል የሆኑትን ሰዎች አጣርተው ከእነ ስም ዝርዝራቸውና ከመቼ ጀምሮ የብልፅግና አባል እንደሆነ ጠቅሰው ስማቸውን ልከውልናል። አንዳንዶቹ ሰዎች ለብልፅግና ፓርቲ የአባልነት መዋጮ የከፈሉበትን ደረሰኝ ጭምር አያይዘው ልከውልናል። ይህንንም ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ገቢ አድርገናል” ብለዋል።

    ምርጫ ቦርድ በሁለተኛ ዙር የሌሎች ሰዎችን ስም ዝርዝር የላከላቸው መሆኑን የጠቀሱት ድርጅት ጉዳይ ኃላፊው፥ ይህንንም የሚያጣሩ መሆናቸውንና ተገቢውን ማጣራት ካደረጉ በኋላ ለቦርዱ ምላሻቸውን እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።

    አንዳንድ ቦታዎች ላይ በምርጫ አስፈጻሚነት እየተሳተፉ ያሉ ሰዎች በግልፅ ወገንተኝነት የታየባቸው ናቸው ያሉት ዋሲሁን ተስፋዬ፣ ዋናው የአስፈጻሚነት ሚና ገለልተኝነት መሆኑን ጠቅሰው፥ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምርጫ አስፈፃሚዎችን ገለልተኝነትን በጥንቃቄ ሊመረምረው ይገባል ብለዋል። ቦርዱ፣ ፓርቲያቸው የገለልተኝነት ጥያቄ ያነሳባቸውን ሰዎች ዝርዝር በመመልከት ሌሎቹ አስፈጻሚዎች እንዴት ነው የተመለመሉት የሚለውን ያጣራል ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ገልፀዋል።

    ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፥ ለምርጫ አስፈጻሚነት የመለመላቸውንና ገለልተኝነታቸው ላይ ጥያቄ ያነሳንባቸውን እነዚህን ሰዎች በሌሎች ሰዎች ይቀይራል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፤ መቀየርም ይኖርበታል ብለዋል አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ።

    ኢዜማ በገለልተኝነታቸው ላይ ጥያቄ ያነሳባቸውና ስም ዝርዝራቸው ለምርጫ ቦርድ የተላከው የምርጫ አስፈፃሚዎች፣ ሲፈርሙባቸው የነበሩ የደሞዝ መክፈያ ሰነድና የብልፅግና አባል መሆናቸውን የሚያሳይ የአባልነት መዋጮ የከፈሉበት ደረሰኝ በማያያዝ ለምርጫ ቦርድ ገቢ ማድረጉን ለማወቅ ተችሏል።

    ሰነድ ማስረጃ ያልተገኘባቸው ደግሞ የሰው ማስረጃ በማቅረብ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጥር 19 ቀን 2013 ዓ.ም. በደብዳቤ እንዲደርሰው መደረጉን የፓርቲው መጽሔት “የዜጎች መድረክ” መረዳት ችላለች።

    ኢዜማ፥ በመንግሥት ሥር ያሉ እንደ ሥራ ፈጠራ ኮሚሽን ዓይነት ተቋማት፣ ምርጫ አስፈጻሚ መሆን የምትፈልጉ ሰዎች መመዝገብ ትችላላችሁ የሚል ማስታወቂያ ለጥፎ ምልመላ ሲያካሄዱ ደርሶበት ይህንን ከእነ ሰነድ ማስረጃው ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በማቅረብ፣ ከቦርዱ ውጪ የትኛውም አካል ምርጫ አስፈፃሚዎችን የመመልመል ስልጣን እንደሌለው ማስታወቁ አይዘነጋም።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)

    ኢዜማ ለምርጫ ቦርድ ያመለከተው

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 42 total)