Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 16 through 30 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    በ2014 ዓ.ም የ12ኛ ክፍል ፈተና ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ ውጤት ያስመዘገቡ
    እና የማጠናከሪያ መርሐ ግብር የሚከታተሉ ተማሪዎች ወደ ከፍተኛ ትምህርት እንደሚገቡ ተገለፀ

    አዲስ አበባ (ትምህርት ሚኒስቴር) – የትምህርት ሚኒስቴር የ2014 ዓ.ም 12ኛ ክፍል ፈተና የዉጤት ትንታኔ፣ ወደ ከፍተኛ ትምህርት መግቢያ ውጤትና ተያያዥ ጉዳዮች አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል።

    መግለጫውን የሰጡት የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የተገኘው የፈተና ውጤት ከስርቆትና ከኩረጃ በፀዳ መልኩ በትክክል የተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል።

    በ2014 ዓ.ም ለተሰጠው ፈተና በጠቅላላ የተመዘገቡት ተፈታኞች ቁጥር 985,354 ሲሆኑ፤ ከእነዚህ ውስጥ 92 ከመቶ የሚሆኑት ፈተናውን ወስደዋል። 20,170 ተማሪዎች በፈተናው ከተገኙ በኋላ በተለያዩ የደንብ ጥሰቶች ምክንያት ተባረዋል።

    ከፍተኛ ውጤት የተበመገበበት የትምህርት መስክ — በተፈጥሮ ሳይንስ 666 ከ700 ከፍተኛ ውጤት ሆኖ የተመዘገበ ሲሆን በማህበራዊ ሳይንስ ደግሞ 524 ከ600 ከፍተኛ ውጤት ሆኖ ተመዝግቧል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ፈተናውን ካስፈተኑ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ሰባት ትምህርት ቤቶች ያስፈተኑትን ተማሪዎች 100% አሳልፈዋል ተብሏል።

    በጾታ ደረጃ የወንዶች አማካይ ውጤት 30.2 ከመቶ ሲሆን፤ የሴቶች አማካይ ውጤት ደግሞ 28.1 ከመቶ እንደሆነ፥ ይህም በወንዶች እና በሴቶች መካከል በአሐዛዊ ምልከታ (statistically) የጎልላ ልዩነት እንዳለና፤ ወንዶች ከሴቶች አሐዛዊ ብልጫ (statistically higher) ውጤት እንዳስመዘገቡ አስረድተዋል።

    በክልሎች ደረጃ በዉጤት ደረጃ የጎላ ልዩነት እንደሌለ ገልፀው፤ አዲስ አበባ፣ ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች እንዲሁም የሐረሪ ክልል አሐዛዊ የተሻለ (statistically significantly higher) ውጤት ያስመዘገቡ መሆኑን ፕሮፌሰር ብርሃኑ አብራርተዋል።

    በ2014 ዓ.ም በተሰጠው የ12ኛ ክፍል ፈተና ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሊያስገባ የሚችል ወጤት፥ ማለትም ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ ያስመዘገቡት ተማሪዎች ቁጥር ሲታይ፥ የተፈጥሮ ሳይንስ ፈተና ከወሰዱት አጠቃላይ 339,642 ተማሪዎች መካከል 22,936 (6.8%) ተማሪዎች፣ የማኅበራዊ ሳይንስ ፈተና ከወሰዱት አጠቃላይ 556,878 ተማሪዎች መካከል 6,973 (1.3%) ተማሪዎች ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ አስመዝግበዋል።  የሁለቱም የትምህርት መስኮች በድምር ሲታይ፥ ፈተናውን ከወሰዱት 896,520 ተማሪዎች ውስጥ 29,909 (3%) የሚሆኑት ተማሪዎች 50% እና ከዚያ በላይ ያስመዘገቡ መሆናቸውን ገልፀዋል።

    ከተፈጥሮ ሳይንስ ተፈታኞች የተገኘው አማካይ ውጤት 31.6 ከመቶ ሲሆን፤ ከማኅበራዊ ሳይንስ ተፈታኞች የተገኘው አማካይ ውጤት ደግሞ 27.8 ከመቶ ነው። በሁሉም የትምህርት ዓይነቶች የተፈጥሮ ሳይንስ ተፈታኞች አማካይ ውጤት ከማኅበራዊ ሳይንስ ተፈታኞች አማካይ ውጤት አሐዛዊ ጉልህ (statistically significant) ብልጫ እንዳላቸው ሚኒስትሩ አመላክተዋል።

    በአጠቃላይ ከፍተኛ ውጤት፥ በመላው ሀገሪቱ በማኅበራዊ ሳይንስ  ከ500 በላይ (ከሙሉ 600 ነጥብ) ያስመዘገቡ 10 (አስር) ተማሪዎች ብቻ ሲሆኑ፤ በተፈጥሮ ሳይንስ ከ600 በላይ (ከሙሉ 700 ነጥብ) ያስመዘገቡ ደግሞ 263 (ሁለት መቶ ስድሳ ሦስት) ተማሪዎች ናቸው። ወደፊት ጊዜው ሲደርስ እነዚህን እጅግ ከፍተኛ (great distinction) ላመጡ ተማሪዎች ትምህርት ሚኒስቴር ልዩ እውቅና እንደሚሰጣቸው ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ አስታውቀዋል።

    ፈተናውን ከወሰዱ አጠቃላይ 485,393 ወንድ ተማሪዎች መካከል ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ ያገኙት 20,343 (4.2 በመቶ) ወንድ ተፈታኞች ሲሆኑ፤ ከተፈተኑት አጠቃላይ 411,127 ሴት ተማሪዎች መካከል ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ ያገኙት 9,566 (2.3 በመቶ) ሴት ተፈታኞች ናቸው።

    ወደ ዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት ያላመጡ ተማሪዎች በማጠናከሪያ መርሐግብር (remedial program) እንደ ዩኒቨርሲቲዎቹ የመቀበል አቅም ተማሪዎችን ውጤት መሠረት አድርጎ በሚጸም የምልመላ መስፈርት ለዚህ ዓመት ብቻ ወደ ዩኒቨርሲቲዎች ገብተው በልዩ ሁኔታ በደከሙባቸው የትምህርት ዓይነቶች የተሻለ ዉጤት እንዲያስመዘግቡ የሚያስችል ድጋፍ ተደርጎላቸዉ ፈተና ተፈትነው የሚያልፉ ተማሪዎች የከፍተኛ ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ ይደረጋል ብለዋል። በዚህ የማጠናከሪያ መርሐግብር መሠረት፥ ዩኒቨርሲቲ ከሚቀላቀሉት እና መደበኛ ትምህርት (regular course) ከሚጀምሩ 29,909 ተማሪዎች ውጭ ያሉ ሌሎች ከ100 ሺህ የሚልቁ ተማሪዎች በውጤታቸው ተለይተው እንደ ዩኒቨርሲቲዎች የመቀበል አቅም እየታየ ለአንድ ዓመት የማሻሻያ ትምህርት ወስደው በድጋሚ እንዲፈተኑ ይደረጋል ብለዋል።

    የዚህ ዓመት የ12ኛ ክፍል ፈተና አንድምታ ለዓመታት ሲንከባለል የቆ የበርካታ ችግሮች መገለጫ እና ተሸፋፍኖ የቆየውን እውነተኛ የትምህርት ሥርዓታችን ያለበትን ደረጃ ያመላከተ መሆኑን የሚያሳይ ሲሆን ለዚህም ሁሉም የትምህርት ባለድርሻ አካላት በጋር የሚወስዱት ኃላፊነት በመሆኑ ለቀጣይ ሥራ መረባረብ ይገባል ብለዋል።

    ከዚሁ ጋር በተያያዘ የትምህርት ሚኒስትሩ ከተገኘው የፈተናና የተፈታኞች ውጤት ባሻገር፥ አጠቃላይ ስለ አዲሱ የትምህርት እና ምዘና ሥርዓት አንዳንድ ማብራሪያዎችን ሰጥተዋል። ከዚህ በፊት የነበረው የትምህርት እና ምዘና ሥርዓት በርካታ ብልሹ አሠራሮች እንደነበሩበት ያነሱት ሚንስትሩ፤ የአሁኑ የፈተና ሥርዓት ይህን ብልሹ አሠራር ለማረም የተወሰደ የመጀመሪያ እርምጃ ነው ብለዋል።

    የዚህ ዓመት ውጤት አንድምታ ሲታይ፥ ለዓመታት ከትውልድ ትውልድ ሲንከባለል የተሻገረውን እና ተሸፋፍኖ የቆየውን የትምህርት ሥርዓት ብልሽት የሚያሳይ ነው ብለዋል ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በመግለጫቸው።

    ለዚህም መንግሥት የትምህርት ሥርዓቱን ባለማሻሻል፣ ወላጆች ልጆቻቸውን ባለመከታተልና በሥነ ምግባር ባለመቅረፅ፣ ትምህርት ቤቶች እና ባለሀብቶች በጋራ የወድቀቱ ተጠያቂ ናቸው ብለዋል። ከላይ የተጠቀሱ አካላት ቀጣይ መፍትሄዎች ላይ የአንበሳውን ድርሻ በመውሰድ ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።

    በ2014 ዓ.ም ከተሰጠው ፈተና እና ተፈታኞች የተገኘው ውጤትአስደንጋጭ እንደሆነ እንረዳለን ያሉት ሚኒስትሩ፥ ነገ የተሻለ ትውልድ ለመፍጠር በዚህ ውስጥ ልናልፍ ግድ ይለናል፤ ይህ የማንቂያ ደወል ሊሆን ይገባል ብለዋል። በበጎ ጎን ከተነሱጥ ነጥቦች መካከል፥ ፈተናው ሙሉ ለሙሉ ከስሮቆት የፀዳ እንደነበረም ተነስቷል።

    የፈተናው አሰጣጥ በብዙ ፈተናዎች ውስጥ ያለፈ እንደሆነ አንስተው፤ በስኬት ለመጠናቀቁ አስተዋፅኦ ላበረከቱ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።

    ምንጭ፦ ትምህርት ሚኒስቴር/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የ12ኛ ክፍል ፈተና ውጤት መግለጫ ከትምህርት ሚኒስቴር

    Semonegna
    Keymaster

    በሚደረገው ሀገራዊ ምክክር ዜጎች በንቃት እንዲሳተፉ በቂ አትኩሮት ይሰጠው!
    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተላለፈ ወቅታዊ መልዕክት

    በሀገራችን ኢትዮጵያ በየዘመኑ የነበሩትን፣ ከፖለቲካው ሥርዓት የሚመነጩ ችግሮችን ለመፍታት እና ወደተሻለ ሀገራዊ ሁኔታ ለመሸጋገር የሚያስችል ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለማንበር እቅስቃሴ ማድረግ ከተጀመረ ከሃምሳ ዓመታት በላይ ተቆጥረዋል።

    እነዚህ እንቅስቃሴዎች የሥርዓት ለውጥ ከማምጣት ተሻግረው የዴሞክራሲን ፍሬ ከማፍራት ይልቅ ሀገራዊ ችግሮቻችንን በአይነትና በብዛት እየጨመሩ እና እየተወሰሳሰቡ እንዲመጡ በማድረግ ዛሬ ላይ የኢትዮጵያችን ህልውና እና ቀጣይነት ላይ ከፍተኛ አደጋ ለመደቀን በቅተዋል።

    ምንም እንኳ ሌሎች ዘርፈ ብዙ ችግሮች ቢኖሩም፤ የኢትዮጵያ ህልውና ላይ የተደቀነው አደጋ በዋነኛነት የሚመነጨው፣ ከሀገራዊ የፖለቲካ ሥርዓቱ ነው። ሀገራዊ የፖለቲካ ሥርዓቱ በተለያዩ ፍላጎቶች፣ ጥቅሞች፣ ስሜቶች፣ ተስፋዎች እና ስጋቶች በመወጠሩ፤ እርስ በእርስ አለመተማመን፣ ሰላም ማጣት፣ መፈናቀል፣ አለመረጋጋት . . . ወዘተ ተፈጥሮ መዋቅራዊ ቅራኔ ውስጥ እየዳከርን መገኘታችን የአደባባይ ሀቅ ነው።

    ይህ አደገኛ ሀገራዊ ሁኔታ ሳይረፍድ እና ነገሮች ከቁጥጥር ውጪ ከመውጣታቸው በፊት በጋራ አንድ መፍትሔ ካልተበጀለት፤ እርስ በእርሳቸው እየተሳሳቡ ጫፍ እና ጫፍ የቆሙትን የተለያዩ ፍላጎቶች፣ ጥቅሞች፤ ስሜቶች፤ ቡድኖች እና ድርጅቶች በሙሉ ጠራርጎ፣ ማንኛችንም አሸናፊ ወደማንሆንበት ምድራዊ ሲኦል ውስጥ የመግባት እድል እንዳለን መገንዘብ ይኖርብናል።

    ይህንን ሁላችንም ላይ የተደቀነ ሀገራዊ አደጋ ለማስወገድ፣ ባለፉት ሃምሳ ዓመታት በተለይ በፖለቲካው ሂደት ውስጥ ከተሞከሩት እንዲሁም ሀገራዊ ሁኔታውን ከማባባስ እና ከማወሳሰብ ይልቅ ምንም አይነት መፍትሔ መስጠት ካልቻሉት የፖለቲካ አካሄዶች ውጭ ባለ ሂደት፣ መፍትሔ የማፈላለጉ ጥረት አማራጭ የሌለው አካሄድ መሆኑን መቀበል ያስፈልጋል።

    ሀገራዊ ምክክር ያስፈለገውም የሀገራችን አንኳር ችግሮች በመደበኛው የችግር አፈታት ሂደት መፍትሔ ማግኘት በማይቻልበት ደረጃ በመድረሳቸው እና በመቀጠልም፣ የበለጠ እየገዘፉና እየተወሳሰቡ ሄደው ሀገርን የማፍረስ ደረጃ ከመድረሳቸው በፊት ሀገርን ለማዳን እንዲያስችል ነው።

    በኢትዮጵያ ከአንድ ዓመት በፊት ኮሚሽን ተቋቁሞ የተጀመረውን የሀገራዊ ምክክር ሂደት በተመለከተ አሁን በደረስንበት ደረጃ ዋናው ጉዳይ መሆን ያለበት በሀገራችን ህልውና እና ቀጣይነቷ ላይ ያንዣበበውን አደጋ ለአንዴም ለሁሌም እንዲወገድ ማድረግ ነው። ለዚህ ሊረዳን የሚችል ስምምነት ላይ ለመድረስ ደግሞ በምክክሩ ላይ የሚሳተፉ ባለድርሻ አካላትን በሂደቱ ላይ በቀናነት እንዲሳተፉ የማሳመን ሥራ በስፋት ሊከናወን ይገባል።

    የሀገራዊ ምክክሩ ቁልፍና ወሳኝ ባለድርሻዎች ምክክሩን ለመቀበል እና እንዲነቃቁ ለማድረግ፣ በመጀመሪያ መደረግ ያለበት፣ በሀገራዊ ምክክር ምንነትና እና በሀገራችን ሁኔታ ያለውን አስፈላጊነት አስመልክቶ ግልጽ የሆነ አረዳድ እንዲኖር ምቹ ሁኔታ በመፍጠር የተለያዩ ባለድርሻዎች ወሳኝ ሚና እንዳላቸው ማሳየት ነው።

    ሀገራዊ ምክክር በመደበኛ አሰራሮች ሊፈቱ የማይችሉ መዋቅራዊና ጊዜያዊ ቅራኔዎችን በሰላማዊ መንገድ ተነጋግሮ ለመፍታት የሚያስችል በመሆኑ፤ ዘርፈ ብዙ ጥቅም አለው። ሀገራዊ ምክክር በአግባቡ ከተጠቀምንበት ልዩነቶችን በማስታረቅ ሀገራዊ የፖለቲካ ቀውስን ለማስቀረት፤ ፖለቲካዊ አጣብቂኞችን ሰብሮ ለመውጣት እና ውጥረትን ለማርገብ፤ በትጥቅ የታገዘ አመፅ እንዳይፈጠር አስቀድሞ ለመከላከል ያስችላል። በተጨማሪም፤ ብሔራዊ መግባባትን በመፍጠር ከዚህ ቀደም ለተፈፀሙ በደሎች እና ወንጀሎች እንዲሁም የፍትህ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ይረዳል። በውጤቱም ከተፈጠሩ ፖለቲካዊ ቀውሶች ፈጥኖ በማስወጣት በመንግሥት እና በሕዝብ መካከል መተማመንን ይፈጥራል። በፖለቲካዊ ሥርዓቱ ላይ ጥያቄ ለሚያነሱ አካላትም በሀገራዊ ምክክር ላይ በመሳተፋቸው በሀገር ጉዳይ ላይ የባለቤትነት ስሜትን በማጎልበት ልዩነቶችን በሰላማዊ ውይይት የመፍታት ባህል በማዳበር እንዲሁም ሀገራዊ ቀጣይነት እና መረጋጋትን በማረጋገጥ፤ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መደላድሎችን ይፈጥራል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ከዚህ ቀደም በተለያየ መልኩ ሲገልፅ እንደቆየው፤ ሀገራዊ ምክክሩ በዚህ ወቅት ለአጠቃላይ ማህበረሰባዊ ደህንነታችን የሚኖረው አስተዋፅዖ ከፍተኛ ስለሆነ የቅድሚያ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ ሀገራዊ አጀንዳ ነው። ነገር ግን የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ለዚህ ሀገራዊ ክንውን እየሰጡት ያለው ትኩረት በጣም አነስተኛ መሆኑ ፓርቲያችንን በእጅጉ አሳስቦታል።

    ከሁሉም በላይ መንግሥት ለሀገራዊ ምክክሩ ስኬታማነት ብዙ እርቀት ተጉዞ አስተዋፅዖ ማድረግ ሲጠበቅበት፤ በምክክሩ ላይ ሊፈቱ የሚገባቸውን ጉዳዮች አስቀድሞ በመወሰን እንዲሁም ግጭቶች እንዲቀንሱ በትጋት ከመስራት ይልቅ በመንግሥታዊ መዋቅሮች ያልተገባ ውሳኔ ምክንያት ተጨማሪ ግጭቶች እየተፈጠሩ መሄዳቸው እንድንሰጋ አድርጎናል። በኢዜማ እምነት መንግሥት አስተባባሪ እንጂ አፍራሽ፤ ጠቃሚ እንጂ ጎጂ፤ ጠንካራ እንጂ ልፍስፍስ፤ ሕግ አስከባሪ እንጂ ሕግ የሚጥስ ሆኖ መገኘት የለበትም። በመንግሥት በኩል የሚከናወኑ አፍራሽ አካሄዶች አደጋቸው ለሁላችንም ነውና ሊወገዱ ይገባል።

    መንግሥት የሀገራዊ ምክክሩን ሂደት የሚያበላሹ ተግባራትን ማከናወኑ እንዲሁም የምክክሩን ሂደት ውጤታማነት ለማረጋገጥ የሚጠበቅበትን ሚና በአግባቡ እስካሁን አለመወጣቱ ትክክል እንዳልሆነ መረዳት ይጠበቅበታል። ለአብነትም፤ ኢዜማ ከዚህ ቀደም ባወጣቸው መግለጫዎች ላይ እንደገለፀው መንግሥት መግባባት ላይ ያልተደረሰባቸውን ሀገራዊ የፖሊሲ ጉዳዮች፤ የሕገ-መንግሥት አንቀፆች፤ አዋጆች እና ሌሎች ውሳኔዎችን ከሀገራዊ ምክክሩ አስቀድሞ መወሰኑ የምክክር ኮሚሽኑን በማቋቋም ያሳየውን በጎ ተስፋ የሚያጨልም ነው።

    ከመንግሥት በተጨማሪም የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ ልሂቃን፤ የሙያ ማኅበራት፤ የሲቪክ ማኅበራት፤ መገናኛ ብዙሃን፤ የሃይማኖት ተቋማት እና ሰፊው ሕዝብ እስካሁን ባለው ሂደት ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚጠበቅባቸውን ሚና በአግባቡ አልተወጡም። ሀገራዊ ምክክር ለተወሰኑ ግለሰቦች ወይም ተቋማት ብቻ የሚተው ሳይሆን የእያንዳንዱን ኢትዮጵያዊ የነገ ህልውና፤ ደህንነት፤ ሰላም፤ ልማት እና ተጠቃሚነት የሚወስን ጉዳይ መሆኑን አለመገንዘብ ሁላችንንም ለውድቀት የሚዳርግ መሆኑን ማሰብ ያስፈልጋል። በሀገር ዕጣፈንታ ላይ የሚወሰንበትን ክንውን ትኩረት አለመስጠት ማኅበራዊ ኪሳራ እንደሆነ እያንዳንዱ ዜጋ ማወቅ አለበት።

    ፓርቲያችን ኢዜማ ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት እንዲሁም መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከፍተኛ ትኩረት እንድትሰጡት እያሳሰበ የሚከተሉት ምክረ ሃሳቦች ተግባራዊ ሊደረጉ ይገባል ብሎ ያምናል።

    1. መንግሥት የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ሊሠራ የሚችላቸውን መሠረታዊ ጉዳዮች በተደጋጋሚ ተላልፎ ምክክሩ ላይ ጫና መፍጠሩን በአስቸካይ እንዲያቆም፤ እንዲሁም ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚጠበቅበትን መንግሥታዊ ሐላፊነት በአግባቡ እንዲወጣ፤
    2. ምክክር ኮሚሽኑ ለዜጎች መድረስ ያለባቸው መረጃዎች በአግባቡ መድረሳቸውን እና በመገናኛ ብዙሃን ላይ ተገቢው ትኩረት እንዲሰጣቸው ማድረግ ላይ በአትኩሮት እንዲሰራ ብሎም ክንውኖቹን፤ እቅዶቹን እና የሀገራዊ ምክክሩን አስፈላጊነት በተመለከተ በመገናኛ ብዙሃን እየቀረበ በአግባቡ መልዕክቶችን ለማኅበረሰቡ ወቅቱን ጠብቆ እንዲያደርስ ራሱን የቻለ የአየር ሰዓት እንዲመደብለት
    3. የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ እምባ ጠባቂ ተቋም እና ምርጫ ቦርድ እንዲሁም ሌሎች የዴሞክራሲ ተቋማት እየሠሩት ያለውን ጅምር በጎ ሥራ ምሳሌ በማድረግ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ በተሰጠው ስልጣን ልክ ተግባሩንና ታማኝነቱን ለኢትዮጵያ ህዝብ ብቻ እንዲያደርግ፤ በኮሚሽኑ ውስጥ የሚያገለግሉ ግለሰቦችም ታማኝነታቸውን ለህሊናቸው እንዲያደርጉ
    4. የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ ልሂቃን፤ የሙያ ማኅበራት፤ የሲቪክ ማኅበራት፤ መገናኛ ብዙሃን፤ የሃይማኖት ተቋማት እና ሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚጠበቅባቸውን ሚና በአዎንታዊነት እንዲወጡ እንዲሁም በጉዳዩ ላይ በንቃት እንዲሳተፉ።

    በአጠቃላይ፤ ሀገራዊ ምክክር እንደስሙ ሀገራዊ መሆን አለበት። ዜጎች በሀገራቸው ጉዳይ ላይ ያለምንም ተጽዕኖ እንዲሳተፍ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተገቢውን ሚና መወጣት ይጠበቅባቸዋል። እንደ ሀገር ያሉንን ልዩነቶች ለማስታረቅ ሁላችንም ከልባችን በእውነተኛነት መስራት አለብን። በጋራ ለአደጋ እንደተጋለጥነው ሁሉ፤ አደጋውንም በጋራ ለመጋፈጥና በጋራ ለመወጣት መትጋት ይጠበቅብናል። በኢዜማ በኩል የሀገራዊ ምክክር አስተባባሪ ኮሚቴ በማቋቋም አባላትን እንዲሁም ማኅበረሰቡን ለማንቃት የሚችለውን ሁሉ እያከናወነ ሲሆን፤ በቀጣይም ለሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማነት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር ሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ ማረጋገጥ ይወዳል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
    ጥር 02 ቀን፥ 2015 ዓ.ም.

    Semonegna
    Keymaster

    “ዱቤ አለ” – ዳሸን ባንክ በቴክኖሎጂ የታገዘ የዱቤ ግብይት አስተዋወቀ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ዳሸን ባንክ በቴክኖሎጂ የታገዙ አገልግሎቶችን በማስተዋወቅ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች የባንክ አገልግሎቶችን በቀላሉ እንዲያገኙ በማድረግ ላይ ይገኛል።

    ባንኩ አዳዲስ አገልግሎቶችን የማስተዋወቅ ጥረቱን በመቀጠል አሁንም ከኢግልላየን ሲስተም ቴክኖሎጂ (EagleLion System Technology) ጋር በመተባበር የቆየውን የአብዛኛው ኢትዮጵያውያን የዱቤ ግብይት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ እና አስተማማኝ የባንክ አሠራር በማገዝ “ዱቤ አለ” የተሰኘና ሸማቾች በዱቤ በፈለጉት ጊዜ ያሻቸውን ገዝተው ቆይተው መክፈል የሚችሉበትን አሠራር እና መተግበሪያ ጥር 02 ቀን 2015 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ ሆቴል አስመርቋል።

    በምረቃ ሥነ- ሥርዓቱ ላይ የዳሸን ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አስፋው ዓለሙን ጨምሮ በርካታ የንግድ ማኅበረሰቡ አባላት ተገኝተዋል።

    ይህ “ዱቤ አለ” ተብሎ የተሰየመው አገልግሎት ዳሸን ባንክ ከተለያዩ የንግድ ተቋማት ጋር በመተባበር ሕብረተሰቡ ቋሚና አላቂ ዕቃዎችንና በርካታ አገልግሎቶችን በ3 ወር፣ በ6 ወርና በ12 ወር በሚመለስ ዱቤ በወለድና ያለወለድ መግዛት የሚያስችል አማራጭ ነው። ይህም የማኅበረሰባችንን የኑሮ ጫና ይቀንሳል፤ በገበያው ውስጥ ምርት እንዲገላበጥ፣ አገልግሎቶችም ይበልጥ ጥቅም ላይ እንዲውሉ እና የንግድ ማኅበረሰቡ ሽያጭ እንዲያድግ ብሎም ኢኮኖሚው እንዲነቃቃ ጉልህ ድርሻ ይኖረዋል።

    “ዱቤ አለ” የምርትና አገልግሎት አቅራቢዎች ለደንበኞቻቸው እጅግ አመቺ የሆነ የዱቤ አገልግሎት በማቅረብ ተመራጭነታቸውን እንዲያሳድጉም ይረዳል።

    ደንበኞች መተግበሪያውን ከጉግል ፕሌይ ስቶር (Google Play Store) ወይም ከአፕ ስቶር (App Store) በማውረድ ለአገልግሎቱ መመዝብ ይችላሉ። ከተመዘገቡ በኋላም ወደ ዳሸን ባንክ ቅርንጫፍ በማምራት የዱቤ ገደብ ማስፈቀድና የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆን ይችላሉ።

    ዳሸን ባንክ ጠንካራ የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት መገንባት የቻለ ሲሆን በቅርቡ በግል ባንኮች ታሪክ የመጀመሪያው ትልቅና ዘመናዊ የሆነውን የመረጃ ማዕከል አስመርቋል። በዚህ ጠንካራ መሠረተ ልማት ላይ ተንተርሶም አሞሌ በተሰኘው የዲጂታል ባንክ አገልግሎቱ ሰፊውን የማኅበረሰባችን ክፍል ተጠቃሚ አድርጓል። በቅርቡም አነስተኛ ቁጠባና ብድር ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በመተባበር መጀመሩ ይታወሳል።

    ዳሸን ባንክ ኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት የግል ባንኮች ቀዳሚና አንጋፋው ሲሆን፣ ሀገር ውስጥ በስፋት ከሚንቀሳቀሱት እንዲሁም እጅግ ትርፋማ ከሆኑት የባንክና ፋይናንሻል ተቋማ አንዱ ነው። ባንኩ በመላው ሀገሪቱ ከ675 በላይ ቅርንጫፎች፣ ዘጠኝ ዓለም አቀፍ የገንዘብ ምንዛሪ አገልግሎት የሚሰጡ ቢሮዎች፣ ከ400 በላይ የገንዘብ ማውጫ ማሽኖች (ATM machines)፣ እና ከ1300 በላይ ፖይንት ኦፍ ሴል ተርሚናሎች (point-of-sale terminals) አሉት።

    Dube Ale ዱቤ አለ

    Semonegna
    Keymaster

    ፀደይ ባንክ ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘቡ 24.5 ቢሊዮን ብር መድረሱን ገለጸ፤ 1.5 ቢሊዮን ብር ማትረፍ ችሏል

    ባሕር ዳር (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ፀደይ ባንክ የባለ አክሲዮኖች 1ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔውን በባሕር ዳር ከተማ ተካሂዷል። የፀደይ ባንክ በ2014 የሒሳብ ዓመት ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘቡ 24.5 ቢሊዮን መድረሱን የባንኩ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ገልጸዋል።

    በ2014 ዓ.ም ባንኩ ከተለያዩ መለኪያዎች አንፃር አበረታች ውጤት እንዳስመዘገበም አቶ ገዱ የተናገሩት። አያይዘውም የባንኩ ተቀማጭ ገንዘብ በ12 በመቶ አድጎ 24.5 ቢሊዮን ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘብ መድረሱንም ገልጸዋል።

    ሰኔ 2020/21 በተደረገ ሪፖርት ባንኩ 38.9 ቢሊዮን ብር ካፒታል እንዳስመዘገበና 9.5 ቢሊዮን ብር ጠቅላላ የተጣራ ካፒታል ማካበቱንም አንስተዋል።

    ባንኩ የቁጠባ መጠኑን 28.1 ቢሊዮን ብር ያደረሰ ሲሆን፤ በ2014 የሒሳብ ዓመት 1.5 ቢሊዮን ብር ጠቅላላ ትርፍም አግኝቷል ብለዋል። ካለፈው የሒሳብ ዓመት ጋር ሲነፃፀር በ29 በመቶ እድገት አሳይቷል የተባለ ሲሆን ለበርካታ ዜጎችም የብድር አገልግሎት መስጠት መቻሉም ተነስቷል።

    አቶ ገዱ በሪፖርታቸው ካቀረባቸው ነጥቦች ዋና ዋናዎቹ፦

    • የፀደይ ባንክ እስከ ፈረንጆቹ ሰኔ 2022 አጠቃላይ ሀብቱ 44 ቢሊዮን ብር ደርሷል።
    • ጠቅላላ ካፒታሉ 11 ቢሊዮን ብር ነው።
    • ጠቅላላ የተከፈለ ካፒታል7 ቢሊዮን ብር ነው።
    • የባንኩ ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘብ5 ቢሊዮን ብር ደርሷል። ይህም ከባለፈው ዓመት ከነበረበት በ12 በመቶ እድገት አሳይቷል።
    • ባንኩ የእቅዱን 94 በመቶ ማሳካት ችሏል።
    • የባንኩ ጠቅላላ የብድር ክምችት6 ቢሊዮን ብር ደርሷል።
    • የብድር መጠኑንም በ29 በመቶ አሳድጓል።
    • ባንኩ በበጀት ዓመቱ ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች1 ቢሊዮን ብር አበድሯል።
    • ፀደይ ባንክ 5 ቢሊዮን ብር ወጭ ማድረጉም በሪፖርቱ ተመላክቷል።
    • በ2014 የሒሳብ ዓመት 5 ቢሊዮን ብር ትርፍም አስመዝግቧል፤ የ2015 የሒሳብ ዓመት ትርፉን ወደ 1.66 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ አቅዷል።
    • ትርፉ ካለፈው የሒሳብ ዓመት ጋር ሲነጻጸር 3 በመቶ ማደጉን የቦርዱ ሰብሳቢ አቶ ገዱ ገልጸዋል።

    ባንኩ በቀጣይ ከ100 በላይ ቅርንጫፎችን በመክፈት የአገልግሎት አድማሱን እንደሚያሰፋ ነው የተገለጸው። ፀደይ ባንክ ሀገር ችግር ውስጥ በገባችበት ወቅት 100 ሚሊየን ብር ወጭ በማድረግ ለወገን ደራሽነቱን አስመስክሯል። እንደሀገር የተከሰተውን የዋጋ ንረት ለመቋቋምም አጥብቆ ይሠራል ነው የተባለው።

    በአጠቃላይ 471 ቅርንጫፎችን በማቀፍ በብድርና ቁጠባ ተቋምነት (የአማራ ብድርና ቁጠባ ተቋም) ሲንቀሳቀስ ቆይቶ በቅርቡ ወደ ባንክ ተቋምነት የተሸጋገረው ፀደይ ባንክ፥ በአሁኑ ሰዓት ከ150 በላይ ቅርንጫፎቹ ውስጥ ከ12,200 በላይ ሠራተኞችን ቀጥሮ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ከዚህ በተጨማሪም አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ 36 ወለሎች ያሉት ዋና ቅርንጫፍ እያስገነባና፥ ግንባታውም በ2015 የሒሳብ ዓመት ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተዘግቧል።

    ንግድና ኢንዱስትሪ ነክ ዜናዎች ― ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ፀደይ ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    ለኢንቨስትመንት ዘርፍ ተጨማሪ አቅም የሚሆነው ሲዳማ ባንክ

    ቀደም ሲል “ሲዳማ ማይክሮፋይናንስ ተቋም” በመባል የሚታወቀው የብድርና ቁጠባ ተቋም “ሲዳማ ባንክ አክሲዮን ማኅበር” ሆኖ በባንክነት ለመደራጀት በሐምሌ ወር 2014 ዓ.ም ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ፈቃድ አግኝቷል።

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – በአንድ ሀገር የምጣኔ ሀብት እንቅስቃሴ ውስጥ የጎላ ሚና ካላቸው ባለድርሻ አካላት መካከል የፋይናንስ ተቋማት በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ። እነዚህ ተቋማት በሀገራዊ የምጣኔ ሀብት እንቅስቃሴ ውስጥ ካላቸው ሚና መካከል አንዱ ለኢንቨስትመንት ተግባራት የፋይናንስ ምንጭ መሆናቸው ነው።

    የብድርና ቁጠባ ተቋማትን ጨምሮ ባንኮችና የመድን (insurance) ድርጅቶች በአነስተኛም ሆነ በትልልቅ የኢንቨስትመንት ተግባራት ላይ ለተሰማሩ ግለሰቦች፣ ማኅበራትና ኩባንያዎች የሥራ ማከናወኛ የገንዘብ ምንጮች እና የንብረት ዋስትናዎች ሆነው ይሠራሉ። ውጤታማ የኢንቨስትመንት ተግባራት አስተማማኝ የፋይናንስ አቅርቦት የሚፈልግ በመሆኑ በኢትዮጵያም ሆነ በሌላው ዓለም ያሉ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ከእነዚህ የገንዘብ ተቋማት ተሳትፎ ውጭ የሚታሰቡ አይደሉም።

    ላለፉት ሁለት አስርት ዓመታት የበርካታ ዜጎችን ሕይወት በበጎ የለወጡት የብድርና ቁጠባ ተቋማት ለአነስተኛና መካከለኛ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ውጤታማነት የነበራቸው ሚና ከፍተኛ እንደሆነ አይዘነጋም። በኢትዮጵያ የብድር እና ቁጠባ ተቋማት ደንበኞች ቁጥር ከባንክ ደንበኞች ቁጥር በብዙ እጥፍ የላቀ ነው። ይህም ለአብዛኛው ሕዝብ የብድር አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙት እነዚህ ተቋማት እንደሆኑ አመላካች ነው። አንጋፋ የሚባሉት የብድርና ቁጠባ ተቋማት የፋይናንስ አቅማቸው ከብዙ አዳዲስ ባንኮች ጭምር የተሻለ ነው። ዛሬ በትልቅ ስምና አቅም የሚታወቁ ብዙ የኢንቨስትመንት ድርጅቶች መነሻቸው እነዚህ የብድርና ቁጠባ ተቋማት ናቸው።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የብድርና ቁጠባ (የማይክሮፋይናንስ) ተቋማት አስተማማኝና ፍትሐዊ በሆነ አሠራር እንዲሠሩና ሕዝባዊ ተዓማኒነት እንዲኖራቸው እንዲሁም ባንክ ሆነው ለመንቀሳቀስ የሚስችላቸው ሕጋዊ ማዕቀፍ እንዲኖራቸው የሚያስችል መመሪያ ከሁለት ዓመታት በፊት ማውጣቱ ይታወሳል። የብድርና ቁጠባ ተቋማቱ ያላቸውን ግዙፍ የደንበኛና የፋይናንስ አቅም ትልልቅ በሆኑና የተሻለ ትርፍ ሊያመጡ በሚችሉ ኢንቨስትመንቶች ላይ እንዲያውሉት የተዘጋጀው ይህ መመሪያ፤ ብዙ የብድርና ቁጠባ ተቋማት ወደ ባንክ እንዲሸጋገሩና ወደ መደበኛ የባንክ ሥራ እንዲገቡ እያስቻለ ነው።

    በዚሁ መመሪያ መሠረት ቀደም ሲል “ሲዳማ ማይክሮፋይናንስ ተቋም” (Sidama Microfinance In­stitution) በመባል የሚታወቀው የብድርና ቁጠባ ተቋም “ሲዳማ ባንክ አክሲዮን ማኅበር” (Sidama Bank S.C.) ሆኖ በባንክነት ለመደራጀት በሐምሌ ወር 2014 ዓ.ም ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ፈቃድ አግኝቷል። ባንኩ 1,988 ባለአክሲዮኖች ያሉት ሲሆን፥ የተፈረመ ካፒታሉ አንድ ቢሊዮን 447 ሚሊዮን ብር ነው። ከዚህ ውስጥ ከ583 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆነው ገንዘብ የተከፈለ ካፒታል ነው።

    የሲዳማ ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀ መንበር አቶ አብርሃም ማርሻሎ ባንኩ ከብሔራዊ ባንክ የሥራ ፈቃድ ማግኘቱን ተከትሎ በባንክ ዘርፍ ተግባራት ላይ ለመሰማራት የሚያስችሉትን የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን እንዳከናወነ ይናገራሉ። አቶ አብርሃም በዚህ ረገድ ስለተከናወኑ ተግባራት ሲገልፁ “የባንኩ የውስጥ አሠራር የሚመራባቸውን መመሪያዎችን የማዘጋጀት፤ በብሔራዊ ባንክ መስፈርት መሠረት ውስጣዊ አደረጃጀቶችን የማሟላት፣ ከባንክ ዘርፉ ወቅታዊ እድገት ጋር የሚጣጣምና ባንኩን ተወዳዳሪ ለማድረግ የሚያስችል የኮር ባንኪንግ ሶፍትዌር ግዢ ለመፈፀምና ባንኩ የሚመራበትን የአምስት ዓመታት ስትራቴጂካዊ እቅድ ለማዘጋጀት ቅድመ ዝግጅት ተግባራትን የማጠናቀቅ፣ የሠራተኞችን አቅም በስልጠና የመገንባትና ተቋሙን በብቁ ሰው ኃይል የማጠናከር፣ በመጀመሪያ ዙር የተሟላ የባንክ አገልግሎት የሚሰጡ 10 ቅርንጫፎችን በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የማዘጋጀት እንዲሁም በብሔራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሬ ሂሳብን ጨምሮ የመጠባበቂያና የክፍያ ሂሳቦችን የመክፈት ተግባራት ተከናውነዋል” ሲሉ ያብራራሉ።

    እንደ እርሳቸው ገለፃ፥ ባንኩ ባለፈው የበጀት ዓመት 142.3 ሚሊዮን ብር ዓመታዊ ገቢ ለመሰብሰብ አቅዶ 177 ሚሊዮን ብር በመሰብሰብ ከእቅድ የበላይ የሆነ አፈፃፀም አስመዝግቧል። ይህም ካለፈው ዓመት የባንኩ አፈፃፀም ጋር ሲነፃፀር የ58 በመቶ ብልጫ እንዲኖረው አድርጓል። 48 ሚሊዮን ብር ለማትረፍ አቅዶ 83 ሚሊዮን ብር በማትረፍ በባንኩ ታሪክ የተሻለ ውጤት ሆኖ ተመዝግቧል። በጠቅላላው 165 ሚሊዮን ብር ተቀማጭ ገንዘብ በመሰብሰብም ከቀዳሚው ዓመት አፈፃፀም የ29 በመቶ እድገት አሳይቷል።

    በብድር አቅርቦት ረገድ ደግሞ ባንኩ የሰጠውን ብድር በ86.6 ሚሊዮን ብር (በ29 በመቶ) በማሳደግ ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች የሰጠውን ብድር 462.5 ሚሊዮን ብር ማድረስ ችሏል። “የባንኩ የተበላሽ ብድር ምጣኔ 3.6 በመቶ ሲሆን፣ ይህም ብሔራዊ ባንክ ካስቀመጠው የአምስት በመቶ ምጣኔ አንፃር ሲታይ የሲዳማ ባንክ የተበላሸ የብድር ምጣኔ ጤናማ እንደሆነ አመላካች ነው” ይላሉ።

    የሲዳማ ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ታደሰ ሐጢያ ባንኩ ማይክሮፋይናንስ ተቋም በነበረበት ጊዜ አነስተኛ ገቢ ያላቸውን የሕብረተሰብ ክፍሎች ሲያገለግል እንደነበር አስታውሰው፤ አገልግሎቱ አዋጭና ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርግ በመሆኑ በብሔራዊ ባንክ ሕጋዊ ማዕቀፍ መሠረት ባንኩ ይህን አገልግሎቱን እንደሚቀጥልም ይናገራሉ። ባንኩ ከሚያከናውናቸው ተግባራት መካከል አንዱ የባንክ አገልግሎትን በገጠርና በከተማ ለሕብረተሰቡ ተደራሽ ማድረግ መሆኑም ይህን አገልግሎቱን የማስቀጠል አካል ነው።

    እርሳቸው እንደሚሉት፥ ተቋሙ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ አድርጓል። ቀደም ካለው ጊዜ ጀምሮ የባንኩን አገልግሎት የሚጠቀሙ በእርሻ፣ በሆቴልና በሌሎችም የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች አሉ። የተቋሙ በባንክ አሠራር መደራጀት ደግሞ ይህን አገልግሎት ለማስፋትና ለማዘመን ተጨማሪ ዕድልና አቅም ይፈጥራል።

    ተቋሙ ወደ ባንክ ሲሸጋገር ብሔራዊ ባንክ ያስቀመጠውን አነስተኛ መነሻ ካፒታል ለማሟላት የአክስዮን ሽያጭ ያከናወነ ሲሆን፣ የተፈረሙ አክሲዮኖች ተከፍለው እንዲጠናቀቁ በማድረግ ከመደበኛ የባንክ ሥራዎች በተጨማሪ ዓለም አቀፍ የባንክ ሥራዎችን ለማከናወን እየሠራ ይገኛል። “ወደ ባንክ ሥራ ስንገባ የጠንካራ የፋይናንስ አቅም ባለቤት መሆን ያስፈልጋል፤ አለበለዚያ አቅም ካላቸው ከሌሎች ባንኮች ጋር ለመወዳዳር አስቸጋሪ ይሆናል። ለትልልቅ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ብድር ማቅረብም ሆነ በፋይናንስ ገበያው ላይ ተፎካካሪ መሆን አይቻልም” ይላሉ። ይህን ለማሳካትም የተፈረሙ አክሲዮኖች እንዲከፈሉና የኮርባንኪንግ (Core Banking) ሥራን ለመጀመር የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሆነ አቶ ታደሰ ያስረዳሉ።

    የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ ገበያ እንዲገቡ መፈቀዱ መልካም ዕድሎችና ፈተናዎች እንደሚኖሩት የሚገልጹት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፥ መልካም ዕድሎችን መጠቀም ከተቻለ ፈተናዎቹን መቀነስና ተወዳዳሪ መሆን እንደሚቻል ነው የተናገሩት። የባንኮቹ መግባት የሀገር ውስጥ ባንኮች ውድድሩን ለመቋቋም ራሳቸውን እንዲያጠናክሩ፣ በዚህም ተገልጋዩ ሕብረተሰብ ተጠቃሚ እንደሚሆን ይገልጻሉ። የኢትዮጵያ ባንኮች በካፒታል አቅምም ሆነ በቴክኖሎጂ አጠቃቀም ረገድ በሚጠበቅባቸውና ወቅቱ በሚፈልገው ልክ እየተንቀሳቀሱ አለመሆናቸውን ተናግረው፥ እነዚህን ክፍተቶች በማስተካከል ለውድድር መዘጋጀትና ለተገልጋዩ እርካታ መሥራት እንዳለባቸው ይመክራሉ። ከዚህ አንፃር ሲዳማ ባንክ ትልቅ አቅም ያላቸውን ባለሀብቶችን እንዲሁም ዳያስፖራውን ማሳተፍን ጨምሮ ያሉትን መልካም አጋጣሚዎች ሁሉ ተጠቅሞ በባንክ ኢንዱስትሪው ዘርፍ ተወዳዳሪ ለመሆን ማቀዱን አቶ ታደሰ ገልፀዋል።

    ሲዳማ ባንክ ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የሚኖረውን አዎንታዊ አስተዋፅኦ በተመለከተም አቶ ታደሰ ሲናገሩ፥ “ገበያው አዋጭ በመሆኑ ባንኩ ለኢንቨስትመንት ሥራዎች የፋይናንስ ምንጭ የመሆን አቅም አለው። ቀደም ሲልም የባንኩን አገልግሎት የሚጠቀሙ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች አሉ። ወደፊትም ባንኩ ይህን ተግባሩን በስፋት አጠናክሮ ይቀጥላል” ብለዋል።

    ሲዳማ ባንክ በማይክሮፋይናንስ ደረጃ ከነበረበት ጊዜ ጀምሮ አነስተኛ ገቢ ያላቸውን የሕብረተሰብ ክፍሎችን ሲያገለግልና ለግለሰቦች እንዲሁም በአነስተኛና ጥቃቅን የንግድና ኢንቨስትመንት ሥራዎች ላይ ለተሰማሩ ማኅበራት የፋይናንስ ምንጭ ሆኖ ቆይቷል። ብዙ ግለሰቦችና ማኅበራትም በተቋሙ የብድርና ቁጠባ አገልግሎት ሥራቸውን አሳድገው ዛሬ ትልልቅ ኢንቨስተሮች ለመሆን በቅተዋል።

    የሲዳማ ክልል የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝደንት አቶ መስፍን ቂጤሳ እንደሚናገሩት፣ ተቋሙ በግል ንግድ ላይ ለተሰማሩ በርካታ ግለሰቦችና ድርጅቶች ባለውለታ ነው። እርሳቸውም ከባንኩ ጋር ያላቸው ደንበኝነት የቆየ መሆኑን አስታውሰው፥ “ከባንኩ የወሰድነው ብድር በጣም ጠቅሞናል፤ ትርፋማ ሆነን እንድንሠራ አግዞናል” በማለት የባንኩ የብድር አገልግሎት ለውጤታማነታቸው አጋዥ እንደሆናቸው አስረድተዋል።

    “አካባቢው በቡና ምርት የታወቀ ስለሆነ ባንኩም ለቡናው ዘርፍ ትልቅ ድጋፍ እያደረገ ነው” የሚሉት አቶ መስፍን፤ ለቡና አብቃዮችና ነጋዴዎች እንዲሁም ለተደራጁ ማኅበራትም የፋይናንስ ዕድል እንደሚያመቻች ይገልፃሉ። በቀጣይም ከባንኩ ጋር ያላቸውን ደንበኝነት አጠናክረው፥ በይርጋለም የተቀናጀ አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ የተፈጠረውን መልካም ዕድል በመጠቀም ቡናን እሴት ጨምሮ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ እቅድ እንዳላቸው ተናግረዋል።

    “ከዚህ ቀደም የነበረው የባንኮች ተደራሽነት ውስን ስለነበር ብድር ለማግኘት ችግሮች ነበሩ። ሲዳማ ባንክ ለኢንቨስትመንት ሥራዎች ብድር በማቅረብ ጥሩ ዕድል ይፈጥራል፤ ለልማት በተለይ ለኢንቨስትመንት ትልቅ አስተዋፅኦ እያደረገ የሚገኝ ባንክ ነው። ጥሩ ተስፋ ያለው ባንክም ነው” በማለት አቶ መስፍን ባንኩ ለኢንቨስትመንት ዘርፍ ስለሚኖረው አስተዋፅዖ ይናገራሉ።

    በግል የንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩት ወይዘሮ አየለች ዱካሞም የባንኩ ደንበኛ ናቸው። “ቀደም ሲል የሲዳማ ማይክሮ ፋይናንስ አገልግሎት ተጠቃሚ ነበርኩ” የሚሉት ወይዘሮ አየለች፥ ተቋሙ ባንክ ከሆነ በኋላ ከባንኩ ብድር መውሰዴ ሥራዬን ሰፋ አድርጌ እንድሠራ አግዞኛል። ብዙ ሰው ከሲዳማ ባንክ ብድር እየወሰደ እየሠራ ነው፤ እየተለወጠም ነው። ከባንክ ጋር መሥራት ጥቅሙ ብዙ ነው” ሲሉ ይገልጻሉ። ሲዳማ ባንክ በጥቃቅንና አነስተኛ የንግድ ሥራዎች ላይ ለተሰማሩ ግለሰቦችና ድርጅቶች ትልቅ ድጋፍ ሲያደርግ እንደነበር አስታውሰው፤ ከባንኩ ብድር ወስደው ከአነስተኛ የንግድ ሥራ ተነስተው ለትልቅ ደረጃ የበቁ ሰዎችን እንደሚያውቁም ነው የጠቀሱት። ወደፊትም ከባንኩ ጋር ብዙ ሥራዎችን የመሥራት እቅድ እንዳላቸው ተናግረዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

    ሲዳማ ባንክ Sidama Bank

    Semonegna
    Keymaster

    በሀገር አቀፍ ደረጃ የተቀናጀ የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ዘመቻ ተጀመረ 

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ከታኅሳስ 13 ቀን እስከ ታኅሳስ 22 ቀን፥ 2015 ዓ.ም በሀገር አቀፍ ደረጀ የሚካሄደው የተቀናጀ የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ዘመቻ የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት፣ የኮቪድ-med19 መከላከያ ክትባት፣ የአጣዳፊ የምግብ እጥረት ልየታ፣ የቫይታሚን ኤ ጠብታ እደላ፣ የሆድ ጥገኛ ትላትል መድኃኒት እደላ፣ የሕፃናት የዞረ እግር ልየታ እንዲሁም በወሊድ ምክንያት የሚከሰት ፊስቱላ ልየታ በቅንጅት የሚሠራበት ዘመቻ ነው።

    በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ሰርጢ ጤና ጣቢያ የማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ላይ የተገኙት የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ እንደገለጹት፥ ለእናቶች እና ለሕፃናት ትኩረት ያደረገው የጤና ፖሊሲ ውስጥ አንዱ እና ባለፉት አራት አስርት ዓመታት በትግበራ ላይ የቆየው የክትባት ፕሮግራም መሆኑን ገልፀው፤ እንደሀገር ከ14 በላይ የሚሆኑ የክትባት ዓይነቶችን በመስጠት ዜጎችን ከህመምና ከሞት መታደግ እንደተቻለ ገልጸዋል።

    በሀገራችን በተወሰኑ አካባቢዎች ተከስተው በነበሩ ሰው ሠራሽና ተፈጥራዊ ችግሮች ምክንያት በሥርዓተ ምግብ እጥረት እና በኩፍኝ በሽታ የሚያዙ ሕፃናት ከፍ ብሎ መታየቱን የገለፁት ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ፥ በዚህ ዘመቻ ዕድሜያቸው ከዘጠኝ ወር እስከ አምስት ዓመት የሆኑ ሕፃናትን የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት፣ የአጣፊ የምግብ እጥረት፣ የዞረ እግር ልየታ እንደሚከናወን እና በወሊድ ምክንያት የሚከሰት ፊስቱላ ልየታም ይካሄዳል።

    ሕፃናት በመደበኛ ክትባት መርሃ-ግብር የሚሰጠውን የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት ካልወሰዱ በቀላሉ በኩፍኝ በሽታ የመያዝና ለከፋ የጤና ችግር የመጋለጥ ዕድላቸው ከፍተኛ  ነው ያሉት የእናቶች እና ሕፃናት ጤና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር መሠረት ዘላለም፥ በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን  ባለፉት 3 ወራት ብቻ የኩፍኝ በሽታ ወረርሽኝ በ6 ክልሎች የታየ ሲሆን፤ በወረርሽኙም ከተያዙ ውስጥ 47 በመቶ  የሚሆኑት ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች የሆኑ ሕፃናት ሲሆኑ፥ ከእነዚህም መካከል 46 በመቶ የሚሆኑት ምንም ዓይነት የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት ያልወሰዱ ናቸው ብለዋል። ለዘመቻው እንቅስቃሴ መሳካት አጋርና ለጋስ አካላት ላደረጉት የተቀናጀ አስተዋጽኦ አመስግነዋል።

    በአዲስ አበባ ከተማ ከ5 ዓመት በታች ለሆናቸው ለ520 ሺህ ሕፃናት ክትባቱ እንደሚሰጥም እና በስድስት የመንግሥት ሆስፒታሎች በ101 የመንግሥት ጤና ጣቢያዎች ከሰኞ አስከ አርብ በሥራ ሰዓት እንደሚሰጥ የገለጹት ደግሞ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ዮሐንስ ጫላ ናቸው።

    ሀገር አቀፍ የተቀናጀ  የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ዘመቻ  የማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ የጤና ሚኒስቴር እና የአዲስ አበባ ከፍተኛ አመራሮች፣ የሀይማኖት አባቶችና የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ተካሂዷል።

    ዘመቻው ለአስር ቀን የሚቆይ ሲሆን ከ15 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ሕፃናት የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ተደራሽ የሚሆን ሲሆን፤ የኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት መርሃ-ግብርም በተያያዘ የሚከናወን ይሆናል። ለዘመቻው ስኬታማነት በየተዋረድ ያሉ የጤናው ዘርፍ ባለሙያዎችና አመራሮች፣ አጋር ድርጅቶችና የየመገናኛ ብዙኃን አካላት ትብብር እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል።

    ምንጭ፦ የጤና ሚኒስቴር

    የኩፍኝ መከላከያ ክትባት

    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና የአዲስ አበባ ከተማ ቤቶች ልማት እና አስተዳደር ቢሮ የ70/30 የማኅበር ቤት ግንባታ ፕሮግራም ይፋ አደረጉ

    • ፕሮግራሙን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈርሟል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና የአዲስ አበባ ከተማ ቤቶች ልማት እና አስተዳደር ቢሮ የ70/30 የማኅበር ቤት (ኮንዶሚኒየም ቤቶች) ግንባታ ፕሮግራም ይፋ አደረጉ። ታህሳስ 10 ቀን 2015 ዓ.ም የተደረገው ስምምነት የከተማ አስተዳደሩ የነዋሪዎችን የቤት ችግር ለመቅረፍ ካቀረባቸው አማራጮች አንዱ በሆነው የጋራ መኖሪያ (ኮንዶሚኒየም) ቤቶች ልማት ፕሮግራም ተጠቃሚ ለመሆን በ2005 ዓ.ም በ20/80 እና በ40/60 ኮንዶሚኒየም ቤቶች ፕሮግራሞች የተመዘገቡና በሕብረት ሥራ ማኅበራት በመደራጀት ቤት ለማልማት ፍላጎት ላላቸው ነዋሪዎች ብድር ለማመቻቸት ያለመ ነው።

    በስምምነቱ መሠረት በማኅበራት የተደራጁ ቤት ገንቢዎች የግንባታ ወጪውን 70 በመቶ ያህል ሲቆጥቡ 30 በመቶውን ደግሞ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በብድር እንዲያገኙ ይደረጋል።

    በስምምነቱ ወቅት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዝዳንት አቶ አቤ ሳኖ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመኖሪያ ቤት ችግርን ለመፍታት በሚያከናውናቸው ተግባራት ባንኩ ድርሻውን በከፍተኛ ደረጃ ሲወጣ መቆየቱን ገልፀዋል።

    አሁን ከተማ አስተዳደሩ ተግባራዊ ለማድረግ ያቀደው የ70/30 የማኅበር ቤት ((ኮንዶሚኒየም ቤቶች) ግንባታ ፕሮግራምም እንዲሳካ ባንኩ ልክ እንደ ከዚህ ቀደሙ በጋራ ይሠራል ብለዋል።

    በምክትል ከንቲባ ማዕረግ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቤቶች ልማት እና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ያስሚን ውሃብረቢ እንዳሉት፥ ቢሮው ባደረገው ጥሪ መሠረት ፍላጎት አሳይተው ከተመዘገቡት ከ12,000 በላይ ቆጣቢዎች ውስጥ 4,580 የሚሆኑት በዳግም ምዝገባው ተገቢውን መረጃ ይዘው የቀረቡ በመሆኑ በመጀመሪያው ምዕራፍ ወደ ትግበራ ይገባሉ።

    በአሁኑ ወቅት የተዘገቡት 4,580 በላይ ቆጣቢዎችን በ57 ሕብረት ሥራ ማኅበራት እንዲደራጁ የመደልደል ሥራ ተጠናቋል ያሉት ወ/ሮ ያስሚን ውሃብረቢ፥ ለአዲሱ ፕሮግራም 30,000 ሄክታር መሬት መዘጋጀቱንም ነው የገለፁት።

    በቤት ልማት ዘርፉ የኢትዮጰያ ንግድ ባንክ ለዓመታት የዘለቀ ድጋፍ ሲያደርግ መቆየቱን የገለፁት ወ/ሮ ያስሚን፥ ባንኩ ሃገራዊ ግዴታውን በመወጣቱ ሊመሰገን ይገባል ብለዋል።

    በቀጣይ ተገቢውን ቅድመ-ሁኔታ አሟልተው ህጋዊ ሰውነት አግኝተው በሕብረት ሥራ ማኅበር ሲደራጁ የፕሮጀክት ሳይት እና የብሎክ እጣ በማውጣት የመሬት ርክክብ ለማኅበራቱ በማድረግ ግንባታ እንደሚጀመር በስምምነቱ ወቅት ተገልጿል።

    ከዚሁ ፕሮግራም ጋር በተያያዘ በርካታ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች መከናወናቸውን፥ ከእነዚህም መካከል የአሠራር ሥርዓት መዘርጋት፣ በከተማ አስተዳደሩ አስፈላጊው የመሬት አቅርቦት ዝግጅት፣የህንፃ ዲዛይን ሥራ፤ ከአዲስ አበባ የሕብረት ሥራ ማኅበር ኤጀንሲ በቀጣይ ሥራ ስምምነት ማመቻቸትን እንደሚያካትት የአዲስ አበባ ከተማ ኮሙኒኬሽን ቢሮ አስታውቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ

    የአዲስ አበባ ከተማ ቤቶች ልማት እና አስተዳደር

    Semonegna
    Keymaster

    ፀሐይ ባንክ አ.ማ. ካፒታሉን ወደ አምስት ቢሊየን ብር ለማሳደግ ወሰነ፤ የቦርድ አስመራጭ ኮሚቴንም አስመረጠ።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – የፀሐይ ባንክ አ.ማ. በባለአክሲዮኖች አንደኛ መደበኛና አንደኛ አስቸኳይ ጉባኤ ታኅሳስ 8 ቀን፥ 2015 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ ሆቴል ባካሄደው ስብሰባ የባንኩን የተፈረመ ካፒታል ከብር 2 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ወደ አምስት ቢሊዮን እንዲያድግ ተወሰነ።

    ፀሐይ ባንክ ካፒታሉን ለማሳደግ በምክንያትነት ያቀረበው በዓለም አቀፍ፣ ሀገራዊ እና በፋይናንስ ዘርፉ የታዩ ዓበይት ለውጦች ምክንያት፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ሀገር በቀል ባንኮች ሊኖራቸው የሚገባው ዝቅተኛ የካፒታል መጠን ላይ ማሻሻያ በማድረጉ፤ የውጪ ባንኮች በባንክ ዘርፉ እንዲሳተፉ የሚፈቅድ ፖሊሲ በመውጣቱ እና ወደ የባንኩን ዘርፍ በሚቀላቀሉበት ወቅት በሚፈጠረው ውድድር አሸናፊ ሆኖ ለመውጣት የተሻለ የካፒታል ቁመና ላይ መገኘት አስፈላጊ በመሆኑ ነው ተብሏል።

    በተጨማሪም እጅጉን ተለዋዋጭ በሆነው የፋይናንስ ዘርፍ ምኅዳር ውስጥ አሸናፊ ሆኖ የመሥራች ባለአክሲዮኖች ራዕይ ማሳካት የሚቻለው በቅድሚያ የተፈረመ ካፒታል ቀሪ ክፍያ በአጠረ ጊዜ ውስጥ መሰብሰብ ሲቻል እንደሆነ እና ባንኩ የነደፈውን ስትራቴጂ ለመተግበር እንዲሁም ከግብ ለማድረስ የተፈረመ ካፒታሉን መሰብሰብ አስፈላጊ በመሆኑ እንደሆነ በጉባኤው ላይ ተመልክቷል።

    በዚሁ መሠረትም ቀደም ተብሎ የተፈረመ ካፒታሉ ላይ ያልተሰበሰበ ገንዘብ የመጀመሪያውን ግማስ 37 ነጥብ 5 በመቶ በፈረንጆች አቆጣጠር እስከ ጥር 2023 (January 2023) መጨረሻ ድረስ፤ እንዲሁም ቀሪውን 37 ነጥብ 5 በመቶ እስከ መጋቢት2023 (March 2023) መጨረሻ፤ በመጨረሻም የማጠናቀቂያውን ክፍያ እስከ ሰኔ 2023 (June 2023) መጨረሻ እንዲከፈል ተወስናል።

    የካፒታል ማሳደጉን በተመለከተ አምስት ቢሊዮን ለመሙላት የሚቀረውን 2 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር በፈረንጆች አቆጣጠር በሐምሌ 1 ቀን፥ 2023 (July 1, 2023) ተፈርሞ በዓመቱ ተከፍሎ እንዲጠናቀቅ የተወሰነ ሲሆን፤ የካፒታል እድገት ውስኔው ተግባራዊ የሚደረገው ቀደም ሲል ተፈርመው ያልተከፈሉ የባንኩ አክሰዮኖች ሙሉ በሙሉ ተከፍለው ሲጠናቀቁ መሆኑ ተገልጿል።

    በተጨማሪም የፀሐይ ባንክ አ.ማ. ለቀጣይ ሦስት ዓመታት የሚመሩ የዳይሬክተሮች ቦርድን ለማስመረጥ የሚሠሩ የአስመራጮች ምርጫ የተካሄደ ሲሆን፤ አስር አባላት ተጠቁመው ከፍተኛ ድምጽ ያገኙ አምስት አስመራጮችን ጉባኤው መርጧል።

    ፀሐይ ባንክ አ.ማ ሀምሌ 16 ቀን፥ 2014 ዓ.ም “ፀሐይ ለሁሉ” በሚል መሪ ቃል በይፋ ሥራ የጀመረ ሲሆን፤ በመላ ሀገሪቱ በርካታ ቅርንጫፎች ከፍቶ መደበኛ እና “ፈጅር” የተሰኘ ከወለድ ነጻ የባንክ አገልግሎት ለሕብረተሰቡ በመስጠት ላይ የሚገኝ ባንክ ነው።

    ባንኩ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ የቅርንጫፍ ቁጥሩን ወደ 100 የሚያደርስ ሲሆን፤ በተጨማሪም 15 የኤቴኤም ማሽን በመትከል አገልግሎት እንደሚሰጥና ከ356 ሺህ በላይ ደንበኞችን የማፍራት እቅድ ይዞ በመሥራት ላይ መሆኑ በጉባኤው ላይ ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የባንኩ ፈስቡክ ገጽ

    ፀሐይ ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    “ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ በሚቀጥሉት አስር ዓመታትም የሚቀጥል ነው – አቶ መላኩ አለበል የኢንዱስትሪ ሚኒስትር

    አዲስ አበባ (ኢፕድ) – “ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ በሚቀጥሉት አስር ዓመታትም ተጠናክሮ የሚቀጥልና ራሱን የቻለ ፕሮጀክት ቢሮ ተቋቁሞለት በጥብቅ ዲስፕሊን እየተመራ እንደሚገኝ ተገለጸ፡፡

    የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል በተለይም ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት (ኢፕድ) እንደገለፁት፥ “ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ እሳቤው በጣም ሰፊ እና በሚቀጥሉት አስር ዓመታትም ተጠናክሮ ይቀጥላል።

    እንደሀገር ለኢትዮጵያ የማምረት ጉዳይ የህልውና ጉዳይ ነው፤ ኢትዮጵያ ማምረት አለባት ያሉት ሚኒስትሩ፥ የለመድነውና ደጋግመን የምንለው መሪ ሀሣብ አለን። ይህም “ኢትዮጵያ ለዘላላም ትኑር” እንላለን፡፡ ኢትዮጵያ ዘላለም መኖር የምትችለው ማምረት ስትችል ነው ብለዋል።

    ‘የምንፈልጋት ጠንካራ ኢትዮጵያ እንድትኖር ለማድረግ ማምረት አለብን፤ ሁሉም ዘርፎችም ማምረት አለባቸው’ ያሉት ሚኒስትሩ፥ “ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ በሚጀምርበት ወቅት የማምረቻ (manufacturing) ኢንዱስትሪ ላይ ያሉትን ነባራዊ ሁኔታዎች ከግምት ውስጥ በማስገባት በሀገር ምርትና ምርታማነት በማተኮር የመነጨ የአንድ ተቋም ሳይሆን የሀገር ሉዓላዊነት አጀንዳም ጭምር መሆኑን አመልክተዋል።

    ለመልፋት፣ ለመድከምና በኢኮኖሚ ጠንካራ ለመሆን መሥራት ያለብንን ባለመሥራታችን ምክንያት ወደ ኋላ ቀርተናል፤ በመሆኑም “ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ የሉዓላዊነት፣ የመኖርና የህልውና እሳቤ ነው። “ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ ከማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ጋር የተያያዘ ፖለቲካውንም፣ ኢኮኖሚውንም ማኅበራዊ ጉዳይንም የሚነካ ነው። በመሆኑም ለጠላት ያልተንበረከከ ጉልበት ለስንዴ መንበርከክና እጁን መዘርጋት እንደሌለበት አስገንዝበዋል።

    “ያለፉትን 6 ወራት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ አፈፃፀም ከፌደራልና ክልል የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት ጋር በአፍሪካ ሕብረት አዳራሽ ዛሬ [ኅዳር 9 ቀን፥ 2015 ዓ.ም] ገምግመናል። በተገኙ አበረታች ውጤቶችና ቀጣይ ትኩረት በሚሹ ጉዳዮች ላይም ተግባብተናል።” የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው

    “ኢትዮጵያ ታምርት” የንቅናቄ አጀንዳ ሆኖ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስጀምረውት እስከ ታች ወረዳ ድረስ አምራቾች ማግኘት የሚገባቸውን ድጋፍ ማግኘት አለባቸው በሚል መነሻ የመጣ ነው ያሉት ሚኒስትሩ፥ ከዚህ አኳያ አንዱ የተሳካው ግብ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ አጀንዳ እንዲሆን ማድረግ እንደነበር ተናግረዋል።

    በተጨማሪም አምራቾች ከእያንዳንዱ የመንግሥት አካልም ማግኘት ያለባቸውን ድጋፍ ማግኘት አለባቸው የሚለው እሳቤ ስኬታማ እየሆነ ነው፤ አጀንዳም ማድረግ ተችሏል ነው ያሉት።

    “በየትኛውም ሀገር ላይ ኢንዱስትሪዎች ጠንካራ የፖሊሲ ድጋፍ የሚያደርጉ መንግሥታት ውጤት ናቸው” ያሉት አቶ መላኩ አለበል፥ የክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች ኢንዱስትሪዎች የገጠሟቸው ማነቆዎች እንዲፈቱ በማድረግ ትልቅ አስተዋፅኦ አበርክተዋል። በዚህም የቆሙ ኢንዱስትሪዎች ችግራቸው ተፈትቶ ወደ ሥራ ተመልሰዋል፤ አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች ወደ ዘርፉ ገብተዋል፤ ያለአግባቡ የባከኑ መንግሥትና የሕዝብ ሀብቶች እንዲመለሱ ማስቻሉን አብራርተዋል።

    በኢትዮጵያ ትልቁ ሀብት መሬት ነው። ያለአግባብ መሬት ከያዙት በመቀበል ለአልሚዎች ተላልፏል። ችግሮችን በመለየት እስከታችኛው መዋቅር ድረስ ችግሮቻቸውን ለመፍታት አቅም ሰጥቷል፤ የአደረጃጀት ችግሮችም ተፈትተዋል። በመሆኑም “ኢትዮጵያ ታምርት” የሚለው ንቅናቄ ትልቅ ውጤት አስገኝቷል። ይህም የአንድ ዓመት ዘመቻ ሳይሆን በዘላቂነት የሚሠራ ነው። የፖሊሲ ማሻሻያዎችን በማድረግ፥ ያለውን ፖሊሲ በመተግበርና አማራጮችን በመመልከት የሚስተካከሉ ጉዳዮች መኖራቸውንም አስገንዝበዋል።

    ባለፈው ዓመት (የ2014 በጀት ዓመት) የአስር ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርቱን ለኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረበበት ጊዜ፥ በበጀት ዓመቱ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ውጤት ማምጣቱን ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ገልጾ ነበር

    ምንጭ፦ ኢፕድ

    ኢትዮጵያ ታምርት

    Semonegna
    Keymaster

    በኢትዮ-ኬንያ የኃይል ማስተላለፊያ መስመር በይፋ የኤሌክትሪክ ሽያጭ ተጀመረ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢትዮ-ኬንያ ባለ 500 ኪሎ ቮልት የኃይል ማስተላለፊያ መስመር እና የኮንቨርተር ማከፋፈያ ጣቢያ ኅዳር 8 ቀን፥ 2015 ዓ.ም በይፋ የኤሌክትሪክ ሽያጭ መጀመሩን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አስታወቀ።

    በማስተላለፊያ መስመሩ ላይ ኃይል የማስተላለፍ የሙከራ ሥራ ከጥቅምት 29 ቀን 2015 ዓ/ም ጀምሮ ሲከናወን መቆየቱንም ኩባንያው አስታውሷል።

    ኅዳር 8 ቀን፥ 2015 ዓ.ም በይፋ ኃይል ማስተላለፍ የጀመረው የኢትዮ-ኬንያ ባለ 500 ኪሎ ቮልት (500 kilovolt) የማስተላለፊያ መስመር በዓመት እስከ አንድ መቶ ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ማስገባት አቅም ያለው ሲሆን፤ ከኬንያ አልፎ ከታንዛኒያ እስከ ደቡብ አፍሪካ ላሉት ሀገራት እስከ ሁለት ሺህ ሜጋ ዋት (2000 MW) ኤሌክትክ የማስተላለፍ አቅም አለው፡፡

    የኢትዮ-ኬንያ የኃይል ማስተላለፊያ መስመርና ኮንቨርተር ጣቢያ ፕሮጀክት ለአማካሪ ድርጅቱ፣ ለካሳ ክፍያና የተሰረቁ መሰረተ ልማቶችን ለመተካት የወጣውን ወጪ ጨምሮ ወደ አምስት መቶ ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር ወጪ ተደርጎበታል፡፡

    ከዚህ ውስጥ 214 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዶላሩ ለኮንቨርተር ስቴሽኑና ለግራውንድ ኤሌክትሮድ መስመር የግንባታ ሥራ እንዲሁም 120 ሚሊዮን ዶላሩ ደግሞ ለማስተላለፊያ መስመሩ የዋለ ነው፡፡

    የኢትዮ-ኬንያ ባለ 500 ኪሎ ቮልት የማስተላለፊያ መስመር የግንባታ ሥራ “China Electric Power Equipment and Technology Co. Ltd (CET)” በተሰኘ የቻይና ኩባንያ የተከናወነ ሲሆን፤ የኮንቨርተር ማከፋፈያ ጣቢያውና የግራውንድ ኤሌክትሮድ መስመሩ ደግሞ ሲመንስ (Siemens AG) በተሰኘው የጀርመን ኩባንያ ተከናውኗል፡፡

    በኢትዮጵያ በኩል የተዘረጋው የማስተላለፊያ መስመር እና የፕሮቴክሽንና የዳታ ኮሙዩኒኬሽን መስመር (ኦፕቲካል ግራውንድ ፋይበር) 440 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ሲሆን 994 የከፍተኛ ኃይል ተሸካሚ የብረት ታወሮች አሉት።

    ኢትዮጵያ የምታስተላልፈው ኃይል ያልተቆራረጠና አስተማማኝ እንዲሆን የሚያግዙ ተግባራትን ያጠናቀቀች ሲሆን በኬንያ በኩል ተመሳሳይ ሥራዎች ተሰርተው በቅርቡ ወደተግባር እንደሚገባ ይጠበቃል፡፡

    የማስተላለፊያ መስመሩ ከደቡብ ህዝቦች ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የወላይታ፣ ጋሞ እና ኮንሶ ዞን እንዲሁም ከኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የቦረና ዞን አቋርጦ ነው ወደ ኬንያ ኃይል የሚያስተላልፈው።

    ኢትዮጵያ ቀደም ሲል ከሱዳን እና ከጅቡቲ ጋር የኃይል ሽያጭ እያካሔደች ሲሆን ከሶማሌ ላንድ፣ ታንዛኒያ፣ ደቡብ ሱዳን እና ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጋር የኤሌክትሪክ ኃይል ሽያጭ ለማከናወን የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርማለች።

    ባለፈው ዓመት ለሱዳን እና ለጅቡቲ ኤክስፖርት ከተደረገው የኤሌክትሪክ ኃይል 95 ነጥብ 4 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ተገኝቷል፡፡

    በኢትዮ-ኬንያ የኃይል ማስተላለፊያ መስመር በይፋ የኤሌክትሪክ ሽያጭ ተጀመረ

    Semonegna
    Keymaster

    ናሽናል አቭዬሽን ኮሌጅ የአቭዬሽንና የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ቀጣይነትን ለማረጋገጥ እየሠራ ነው

    ናሽናል አቭዬሽን ኮሌጅ በአገራችን በፍጥነት እያደገ የመጣውን የአቭዬሽንና የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ቀጣይነት ለማረጋገጥና ተወዳዳሪነቱን ለማሳደግ የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራት እየሠራ እንደሆነ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አሰግድ ጌታቸው ተናገሩ። ኮሌጁ ያሰለጠናቸውን 277 ተማሪዎች ኅዳር 3 ቀን፥ 2015 ዓ.ም አስመርቋል።

    የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አሰግድ ጌታቸው ኅዳር 3 ቀን በተካሄደው የተማሪዎች ምረቃ ሥነ-ሥርዓት ላይ እንደገለጹት፥ ኢትዮጵያ የተለያዩ የተፈጥሮ ሀብቶች፣ ብዛት ያለው የሰው ኃይል፣ አኩሪ ታሪክና ባህል ያላት ውብ ሀገር ናት። እነዚህን ገፀ-በረከቶች ወደ ውጤት በመቀየር የሀገራችን ሕዝቦች ካሉባቸው ዘርፈ ብዙ ችግሮች መታደግ ወቅቱ የሚጠይቀው ነው። ከዚህ አኳያ የተለያዩ ክህሎቶችና ዕውቀቶች የቀሰሙ ተመራቂዎች ኢትዮጵያን ለማበልጸግ በሚደረገው ጥረት ጉልህ ሚና መጫወት ይጠበቅባቸዋል።

    ኮሌጁ በሀገሪቷ የተማረ የሰው ኃይል ለማፍራት በሚደረገው ሀገራዊ ጥረት የራሱን ኃላፊነት እየተወጣና በትምህርት አሰጣጥ ሂደት ጥራትን መሠረት አድርጎ እየሠራ የሚያስመስግነው ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ተመራቂ ተማሪዎቹ ያገኙትን ዕውቀትና ክህሎት በሚሠሩበት የሥራ መስክ ኃላፊነት በተሞላበት መንገድ ለሀገራቸውና ለሕዝቦቿ እንደሚያበረክቱ የፀና ዕምነት አለኝ ብለዋል።

    ኮሌጁ ካናዳ ከሚገኘው ዓለም አቀፉ የአየር ትራንስፖርት ማኅበር (IATA) እና እንግሊዝ አገር ከሚገኘው ኢንስቲትዩት ኦፍ ኮሜርሽያል ማኔጅመንት (ICM) ባገኘው ዕውቅና መሠረት ከአቭዬሽን፣ ቱሪዝምና ሆቴል ሙያ ጋር በተገናኘ ደረጃውን ያሟላ ዓለም አቀፍ ስልጠና እየሰጠ እንደሚገኝ ተጠቅሷል። ኮሌጁ ለዘጠነኛ ጊዜ በአቭዬሽን፣ በቱሪዝም፣ በሎጀስቲክስና ቢዝነስ በሁለተኛና በመጀመሪያ ዲግሪ እንዲሁም በሰርተፍኬት ያሰለጠናቸውን 277 ተማሪዎችን በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ECA) አዳራሽ በልዩ ሥነ-ሥርዓት አስመርቋል።

    ናሽናል አቭዬሽን ኮሌጅ የናሽናል አየር መንገድ እህት ኩባንያ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ በአየር ትራንስፖርት ዘርፍ ከሚንቀሳቀሱ የግል አየር መንገዶች መካከል ግንባር ቀደም መሆኑንም የኩባንያው ምክትል ሥራ አስፈጻሚ አቶ ገዛኸኝ ብሩ ገልጸዋል።

    አየር መንገዱ በሀገራችን በፍጥነት እያደገ የመጣውን የአቭዬሽንና የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ቀጣይነት ለማረጋገጥና ተወዳዳሪነቱን ለማሳደግ ቁልፍ የሆነውን የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራት ናሽናል አቭዬሽን ኮሌጅን በማቋቋም የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን አቶ ገዛኸኝ ተናግረዋል።

    በአሁኑ ጊዜም መንግሥት የያዘውን የትኩረት አቅጣጫ በመከተል ግንባር ቀደም የስልጠና ተቋም በመሆን ለበለጠ ስኬት ራሱን አዘጋጅቶ እየሠራ እንደሚገኝ አመልክተው፥ ናሽናል አቭዬሽን ኮሌጅ ከተመሠረተበት ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ከአራት ሺ በላይ ምሩቃንን ከሀገር አልፎም ለዓለም አበርክቷል ብለዋል።

    ናሽናል አቭዬሽን ኮሌጅ የሚሰጣቸው የትምህርት ዘርፎች በአሁኑ ወቅት ሀገራችን በምታካሄደው የልማት የትኩረት አቅጣጫ ጋር ተጣጥሞ የሚሄድ እና ዓለም አቀፍ ንግድ፣ ኢንዱስትሪ እና ቱሪዝም በሚፈልገው ደረጃ የተወጠነ በመሆኑ የኮሌጃችን ፍሬ የሆኑት ተመራቂዎች በሄዱበት ሁሉ ስኬትማ እንደሆኑ ተገልጿል።

    ኮሌጁ በአሁኑ ወቅት የአገር ግንባታ እየተሳተፈ ቢሆንም ብቻውን በሚያደርጋቸው ጥረቶች የተፈለገውን ውጤት ለማምጣት አዳጋች መሆኑን ገልጸው፥ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ለኢንዱስትሪው ዕድገት የበኩላቸውን አስተዋጽዖ ቢያደርጉ የሚፈለገው ግብ ላይ መድረስ እንደሚቻልም አመልክተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት (አዲስ ዘመን)

    ናሽናል አቭዬሽን ኮሌጅ

    Semonegna
    Keymaster

    ተሰርዞ የነበረው የ20/80 እና 40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ወጣ ((የዕድለኞች ስም ዝርዝር))

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከዚህ ቀደም ተሰርዞ የነበረውን የ20/80 እና የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ዕጣ አወጣ። የ14ኛዉ ዙር የ20/80 እና 3ኛዉ ዙር የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች (condominium houses) ዕጣ የማውጣት ሥነ-ሥርዓት ህዳር 6 ቀን 2015 ዓ.ም ተካሂዷል።

    በዕጣ ማውጣት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ አዳነች አቤቤን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች ተወካዮች በታዛቢነት ተገኝተዋል።

    በዕጣው የ20/80 የቤት ልማት ፕሮግራም 18,930 ቤቶች፣ በ40/60 ደግሞ 6,843 ቤቶች እንዲሁም ተጨማሪ 18 ስቱዲዮ ቤቶች በድምሩ 25,791 ቤቶች በዕለቱ ዕጣ ወጥቶባቸዋል።

    የጋራ ቤቶች (condominium houses) ዕጣ ሐምሌ 01 ቀን 2014 ዓ.ም ወጥቶ የነበረ ቢሆንም በዕጣው ማውጣት ሂደት በገጠመ ችግር ምክንያት ዕጣው በመሰረዙ ነው አሁን በድጋሚ የዕጣ ማውጣት ሂደት የተከናወነው።

    የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዕጣ ማውጣት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንዳሉት፥ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ከግንባታ እስከ ዕጣ ማውጣት ሂደት ባለፉት ጊዜያት ከውስጥም ሆነ ከውጭ በርካታ ችግሮች አስተናግዷል። ከዚህ አንፃር ዛሬ የወጣው የ20/80 እና 40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ በርካታ ችግሮችን በማለፍ በስኬት መከናወኑን አንስተዋል።

    በተለይ በለውጡ ዋዜማ የሥራ ተቋራጮች ሥራውን አቋርጠው የመጥፋት፣ የመሠረተ ልማት ዝርፊያ የግንባታ ጥራት ችግር፣ የፋይናንስ እጥረትን ጨምሮ ዘርፉ የተወሳሰበ ሂደት ውስጥ ለማለፍ ተገድዷል ነው ያሉት።

    የከተማ አስተዳደሩ እነዚህን ውስብስብ ችግሮች ለመፍታት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ21 ቢሊዮን ብር በላይ በመበደር ጥረት ሲያደርግ መቆየቱንም እንዲሁ አስታውቀዋል።

    ሆኖም ከዚህ በፊት ዕጣ የወጣባቸውን የጋራ ቤቶች ለተጠቃሚዎች ለማድረስ የተደረገው ሙከራ በተለያዩ የሌብነት ተግባራት ምክንያት ሳንካ ገጥሞት እንደነበርም ጠቅሰዋል። ይህ ደግሞ ለረጅም ዓመታት በትዕግስት ሲጠባበቅ ለነበረው ሕዝብ አሳዛኝ ዜና እንደነበር አውስተዋል።

    በዕጣ ማውጣት ሂደቱ ከተፈጠረው ችግር ጀርባ የቤት ልማት መርሃ-ግብርን ለግል ጥቅም ማካበቻ ከማድረግ ባለፈ በመንግሥትና በሕዝብ መካከል አለመተማመን ለመፍጠር ያለመ ሴራም እንደነበር ነው የተናገሩት። የከተማ አስተዳደሩ የገጠመውን ችግር ለሕዝብ በግልፅ ይፋ በማድረግ በአጥፊዎች ላይ ተጠያቂነትን ማስፈኑን ጠቅሰዋል።

    ተዓማኒነቱ የተረጋገጠ አዲስ የዕጣ ማውጫ ሥርዓት በማልማትም ከዚህ ቀደም ተሰርዞ የነበረው የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ አሁን (ህዳር 6 ቀን 2015 ዓ.ም) በድጋሚ እንዲወጣ መደረጉን ተናግረዋል። የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ በድጋሚ እንዲወጣ ያለመታከት ጥረት ያደረጉ ሰራተኞችና አመራሮችን አመስግነው ባለእድለኞችንም እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።

    ዛሬ የጋራ መኖርያ ቤት ዕጣ ለደረሳችሁ 25,791 ባለ እድለኞች እንኳን ደስ አላችሁ!!
    ለዘመናት በትዕግስት ስትቆጥቡና ስትጠባበቁ የነበራችሁ የ14ኛ ዙር የ20/80 እንዲሁም የ3ኛ ዙር የ40/60 የጋራ መኖርያ ቤት ባለ እድለኞች በሙሉ እንኳን ደስ አላችሁ ለማለት እወዳለሁ!!
    ከዚህ ቀደም በቤት የዕጣ አወጣጥ ሂደት በገጠመን የማጭበርበር ችግሮች ምክንያት የእጣ አወጣጥ ሂደቱ ቢዘገይና እክል ቢገጥመውም የህዝብን ሃብት ለማዳን ያደረግነውን ጥረት በመረዳት ከጎናችን ስለሆናችሁና በከፍተኛ የሃላፊነት ስሜት የህግ የበላይነት እንዲከበር በትዕግስትና በማስተዋል እገዛችሁ ላልተለየን የከተማችን ነዋሪዎች በሙሉ ምስጋናችን ላቅ ያለ ነው፡፡
    እንዲሁም ለዚህ ስራ ስኬት በትጋት የተሳተፋችሁ ፤በየደረጃው የምትገኙ የስራ ሃላፊዎች፣ አመራሮች ፣ሰራተኞች፣ ባለሙያዎችና የፌደራል ተቋማት ስላበረከታችሁት ታላቅ አስተዋፅኦ በከተማ አሳተዳደሩ ስም ልባዊ ምስጋናዬን ለማቅረብ እወዳለሁ!!
    አሁንም የጀመርነውን ከተማችንን እንደ ስሟ ውብና ደማቅ ለነዋሪዎቿ የምትስማማ የማድረግ ስራ ቃላችንን ጠብቀን በመቀጠል ከተማችንን ተወዳዳሪ ብቁና የቱሪስት መዳረሻ የማድረግ ስራ አጠናክረን የምንቀጥል ይሆናል፡፡
    ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን አብዝቶ ይባርክ!!
    ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ

    የ14ኛ ዙር የ20/80 የጋራ መኖርያ ቤት ባለ ዕድለኞችን ለማየት ተከታዩን የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) ቴሌግራም ማስፈንጠሪያ ይጫኑ – EBC Telegram Link

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት

    የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ወጣ

    Semonegna
    Keymaster

    ኢሰመኮ የሴቶችና የሕፃናት ሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ዓመታዊ ሪፖርት ይፋ አደረገ
    የኮቪድ ወረርሽኝ፣ ድርቅ፣ ጦርነትና ግጭት ሳቢያ በሴቶችና ሕፃናት መሰረታዊ መብቶች ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደራቸውን ኮሚሽኑ ገልጿል

    አዲስ አበባ (ኢሰመኮ) – የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከመስከረም 2014 ዓ.ም. እስከ ነሐሴ 2014 ዓ.ም. ያለውን ጊዜ የሚሸፍን የሴቶችና የሕፃናት ሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ዓመታዊ ባለ 36 ገጽ ሪፖርት ይፋ አድርጓል።

    ይህ ዓመታዊ የሴቶችና የሕፃናት መብቶች የዘርፍ ሪፖርት ኢሰመኮ ሐምሌ 1 ቀን 2014 ዓ.ም. ይፋ ካደረገው አጠቃላይ የኢትዮጵያ ዓመታዊ የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ሪፖርት በተጨማሪነት በተለይ የሴቶችና የሕፃናት ሰብአዊ መብቶች አያያዝ ላይ በዝርዝር በማተኮር ኮሚሽኑ የለያቸውን አበረታች እመርታዎችን፣ ዋና ዋና አሳሳቢ ጉዳዮችን እና ምክረ-ሃሳቦችን አካቷል፡፡ ኮሚሽኑ ሪፖርቱን ያዘጋጀው ባከናወናቸው ክትትሎች፣ ምርመራዎችና የመስክ ምልከታዎች፣ ባስተናገዳቸው የግለሰቦች አቤቱታዎች፣ የሕግና የፖሊሲ ግምገማዎች፣ ጥናቶች እና ምክክሮች፣ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮች እንዲሁም የውትወታ እና ሌሎች ሥራዎቹ ላይ በመመስረት ነው።

    የሴቶችና የሕፃናት ሰብአዊ መብቶችን ከማስጠበቅ እና ከማስፋፋት አንፃር በሕግ ረገድ የታዩ ክፍተቶች፣ የሴቶችና የሕፃናት ከጥቃት እና ከብዝበዛ የመጠበቅ፣ ፍትሕ እና ውጤታማ መፍትሔ የማግኘት፣ ሕዝባዊ ተሳትፎ የማድረግ፣ በፍትሕ ሥርዓት ውስጥ ያለው አያያዝ፣ የቤተሰብ መብቶች እንዲሁም የሴት ሠራተኞች ሁኔታ ሪፖርቱ ትኩረት ያደረገባቸው ርዕሰ ጉዳዮች ናቸው።

    በኢትዮጵያ በተከሰቱት ሰው ሠራሽ እና ተፈጥሯዊ ችግሮች ምክንያት ሕፃናት ከመንግሥት፣ ከማኅበረሰብ እና ከቤተሰብ ማግኘት ያለባቸው ጥበቃ በመጓደሉ ለተደራራቢ የመብቶች ጥሰት መጋለጣቸው እና ሴቶች በተፈጸሙባቸው ጾታዊ መድሎዎችና ጥቃቶች ምክንያት መሰረታዊ መብቶቻቸውን የሚጥሱ፣ ነጻነቶቻቸውን የሚገድቡ እንዲሁም ሰብአዊ ክብራቸውን የሚያጎድፉ በደሎች እንደደረሱባቸው በሪፖርቱ ተገልጿል። በተጨማሪም በብሔራዊ የሕግ ማዕቀፍ ውስጥም ለሕፃናትና ለሴቶች ሰብአዊ መብቶች በቂ የሕግ ከለላ በመስጠት ረገድ የተለያዩ ክፍተቶች መስተዋላቸው ተጠቅሷል።

    በኢትዮጵያ የሰሜኑ ክፍል በተነሳው ጦርነትና ቀጥሎም በየመሀሉ ማገርሸቱ በሴቶች እና በሕፃናት ላይ መጠነ-ሰፊ ጥቃቶች፤ በአንዳንድ ሁኔታዎች ለጦርነት ዓላማ ስልታዊ በሆነ መልኩ ጭምርም መፈጸማቸውን ተዘግቧል። ይሁን እንጂ ለተፈጸሙ ጥቃቶች ውጤታማ ፍትሕ እና መፍትሔ የሚያስገኝ የወንጀልና የፍትሐ-ብሔር የሕግ ማዕቀፍ አለመኖር፣ ዓለም አቀፍ መመዘኛዎችን ያሟላ የወንጀል ምርመራና የክስ አመሰራረት መጓደል በሪፖርቱ ከተዘረዘሩት ዋና ዋና አሳሳቢ ጉዳዮች መካከል ናቸው። በሌላም በኩል በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በሶማሌ፣ በአፋር፣ በኦሮሚያ፣ በጋምቤላ፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ፣ በደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልሎች በተለያየ ወቅት በተነሱ ግጭቶችም ሴቶችና ሕፃናት ለተለያዩ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች መጋለጣቸው ተጠቅሷል።

    ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሴቶችና ሕፃናት ከመኖሪያቸው መፈናቀላቸው፣ በተፈናቃይ መጠለያ ጣቢያዎች ውስጥም ለጾታዊ ጥቃቶች እና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ተጋላጭ መሆናቸውና ልዩ ፍላጎታቸውን መሰረት ያደረጉ የሰብአዊ ድጋፎች አለማግኘታቸው ተደራራቢ የመብቶች ጥሰትን አስከትሏል። በሀገሪቱ በተከሰቱ የኮቪድ ወረርሽኝ፣ ድርቅ፣ ጦርነትና ግጭት ሳቢያ የትምህርት እና የጤና አገልግሎቶች በመቋረጣቸው፣ ወይም የተለያዩ ገደቦች መኖራቸው በሴቶችና ሕፃናት ትምህርትና ጤና የማግኘት መሰረታዊ መብቶች ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደራቸውን ኮሚሽኑ ገልጿል። እንዲሁም ሴቶችና ሕፃናት ለሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር እና ለብዝበዛ መጋለጥ፣ በኢንደስትሪ ፓርኮች የሚሠሩ ሴት ሠራተኞች መሰረታዊ መብቶች ጥሰቶች መቀጠል እና በእነዚህ የመብቶች ጥሰት ረገድ የቁጥጥርና የተጠያቂነት መላላት ሌላው አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑ በሪፖርቱ ።

    በሕዝባዊ ጉዳዮች ላይ ከመሳተፍ መብት ጋር በተያያዘም፣ ሕፃናት በማናቸውም ጉዳይ ላይ ሃሳባቸውን በነፃ የመግለጽና በሚመለከታቸው ጉዳዮች ላይ ተሳትፎ የማድረግ መብታቸውን ለመተግበር የሚያስችል ሕግ አለመኖር፤ ሴቶችም በምርጫና በፖለቲካ ውስጥ ውጤታማ ተሳትፎ እንዳያደርጉ የአመለካከት ችግሮች እና ጾታን መሰረት ያደረጉ ጥቃቶች እክል መፍጠራቸው፤ እንዲሁም በሰላም ግንባታ እና በሀገራዊ ምክክር እና ሌሎች የሕዝባዊ ውይይት መዋቅሮች ውስጥም ጾታዊ አካታችነት በእጅጉ ውስን በመሆኑ፣ የሴቶች ተሳትፎ ተገድቧል፡፡

    ከወንጀል ጉዳይ ጋር በተያያዘ በፍትሕ ሥርዓት ውስጥ የሚያልፉ ልጆች አያያዝ ከሕፃናት ፍትሕ መርሆዎችና መመዘኛዎች ውጪ መሆን፣ በወንጀል ተጠርጥረው የታሰሩ ሴቶች ሁኔታ ከመሰረታዊ የሴት እስረኞች አያያዝ መስፈርቶች ጋር አለመጣጣም፣ ከእናቶቻቸው ጋር በእስር ቤት የሚቆዩ ሕፃናት ትምህርትና አማራጭ እንክብካቤ የማግኘት መብቶች መጓደል፣ በወንጀል ፍትሕ አስተዳደር ሥርዓት ውስጥ ያሉ ክፍተቶች በሪፖርቱ ከተለዩ ጉድለቶች መካከል ናቸው። ከዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች መስፈርቶች ጋር በተጣጣመ ሁኔታ ለሕፃናት ነፃና ለሁሉ ተደራሽ የሆነ የልደት ምዝገባ አሠራር በሀገር አቀፍ ደረጃ በሕግ አለመደንገጉ እንዲሁም በተወሰኑ ክልሎች ደግሞ የቤተሰብ ሕግ አለመውጣቱ ከተስተዋሉት የሕግ ክፍተቶች መካከል ተጠቃሽ ናቸው።

    በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የደኅንነት ሥጋቶች መቀጠላቸው የሴቶችን እና ሕፃናትን ሁኔታ በሚፈለገው ቅርበት እና ፍጥነት ለመከታተል እንዳይቻል እንቅፋት የፈጠረ መሆኑ፣ በእነዚህ አካባቢዎች የሚሠሩ የሲቪል ማኅበራት እና አጋሮች አቅምም መዳከሙና በኮሚሽኑ የሚሰጡ ምክረ ሃሳቦችን ተግባራዊ ከማድረግ አኳያ በቅንጅት ለመሥራት የሚያስችል ጠንካራ የጋራ መድረክ አለመኖር ፈታኝ ሁኔታ መፍጠሩም ተጠቁሟል፡፡

    የኢሰመኮ የሴቶችና የሕፃናት መብቶች ኮሚሽነር መስከረም ገስጥ የሴቶችንና የሕፃናት መብቶችን በተመለከተ ኮሚሽኑ ባከናወናቸው ክትትሎች፣ ምክክሮች እና የተለያዩ ክንውኖች ትብብር በማድረግ እና ግብዓት በመስጠት ኃላፊነታቸውን ለተወጡ መንግሥታዊም ሆነ መንግሥታዊ ያልሆኑ አካላት ምስጋናቸውን አቅርበው በኢትዮጵያ ለሚገኙ ሕፃናትና ሴቶች ከግጭት፣ ከጥቃትና ከመድልዎ ነፃ የሆነ፤ ዘላቂ ሰላምና እኩልነት የሰፈነበት ሕይወትን እውን ለማድረግ በሪፖርቱ የተካተቱትን ምክረ-ሃሳቦች በመፈጸምና በማስፈጸም የተቀናጀ ጥረት እና ርብርብ እንዲያደርጉ አሳስበዋል፡፡

    ኮሚሽነር መስከረም አክለውም “ሰብአዊ መብቶችን ማክበር፣ ማስጠበቅ እና ማሟላት የመንግሥት ዋነኛ ግዴታ በመሆኑ የሕግ ማዕቀፎችን፣ ተቋማትን እና አሠራሮችን በማሻሻል፣ ፍትሕን ተደራሽ በማድረግ፣ በግጭቶች የወደሙ የትምህርትና የጤና ተቋማትን እና ሌሎች መሰረተ-ልማቶችን መልሶ በመገንባት እና ለተጎጂዎች ሁለንተናዊ ተሐድሶን በማመቻቸት የሕፃናትንና የሴቶችን ሰብአዊ መብቶች የማሻሻል ኃላፊነቱን መወጣት አለበት። በተጨማሪም መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ፣ እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላትና ጠቅላላ ማህበረሰቡ በሰብአዊ መብቶች ማዕቀፍ በተቀመጠው አግባብ በሀገሪቱ የሴቶችና የሕፃናት መብቶች አፈጻጸምን በማረጋገጥ ረገድ የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ጥሪ አቀርባለሁ” ብለዋል።

    ሙሉ ሪፖርቱ እዚህ ተያይዟል

    [caption id="attachment_53773" align="aligncenter" width="600"]የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ሪፖርት የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ሪፖርት[/caption]

    Semonegna
    Keymaster

    ቡራዩ የተሰጥኦ ማበልፀጊያ መዕከል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ተመርቆ 500 ተማሪዎችን ለመቀበል ተዘጋጅቷል

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በቡራዩ ከተማ የተገነባውን የተሰጥኦ ማበልፀጊያ ትምህርት ቤት (ቡራዩ የተሰጥኦ ማበልፀጊያ መዕከል ) መርቀው መክፈታቸው ተገለጸ፡፡

    በመደበኛ ትምህርት ቤቶች፣ በዩኒቨርሲቲዎች፣ በማሰልጠኛ ተቋማትና ሌሎች ተመሳሳይ ድርጅቶች የወጣቶችን ተሰጥኦ የማጎልበት ሥራ ማከናወን አስፈላጊ ነው።

    አሁን ባለው እውነታ ወጣቶቹ ተሰጧቸውን አበልጽገው ወደምርትና አገልግሎት ለመቀየር ከፈለጉ የትምህርት ሥርዓቱ የሚፈልገውን ቆይታ ማጠናቀቅ ግድ ይሆንባቸዋል።

    ወጣቶቹ የሚያጋጥማቸውን ውጣ ውረድ ማለፍ ሲሳናቸው ደግሞ ተሰጥኦዋቸውን ለመረዳት፣ ለማውጣትና ለመተግበር ስለሚቸገሩ ባክነው የሚቀሩበት ዕድል ሰፊ ነው።

    በመሆኑም ከመደበኛው መማር ማስተማር ሳይለዩ ተሰጧቸውን ያለጊዜ ገደብ ወደ ምርትና አገልግሎት እንዲለወጡና አገር እንዲጠቅሙ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑ ይነገራል።

    የተገነባው ማዕከልም በሀገራዊ ለውጥ ምክንያት በነበሩ ጫናዎች ውስጥ ሆኖ መጠናቀቁና የአካባቢው ሕዝብ በግንባታ ሂደቱ ንብረት እንዳይጠፋና እንዳይባክን ጠብቆ ለምረቃ ያበቃው መሆኑ ተገልጿል።

    የአካባቢው ነዋሪ ከመሬት ስጦታ እስከ ጉልበት ያለምንም ካሳ አስተዋጽኦ ያደረገበት በመሆኑ ሕዝብ ከተባበረ ምንም ነገር ማሳካት እንደሚቻል ያሳየ መሆኑም ተመልክቷል።

    የማዕከሉ መገንባት አዲስ ከተማ ከመፍጠር ባለፈ ከትምህርት፣ ከሰው ኃይል ልማትና ከሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ከሳይንስ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ልማትና ምርምር አኳያ መሠረት ይጥላል ተብሏል።

    በአንድ ጊዜ 1 ሺህ ባለተሰጥኦ ወጣቶችን ተቀብሎ ማስተናገድ የሚችለው ትምህርት ቤቱ በመጀመሪያው ምዕራፍ 500 ሰልጣኞችን የሚያስተናግድ ይሆናል።

    የፕሮጀክቱ ተጨማሪ ማስፋፊያ ሲገነባ በ10 ሄክታር መሬት ላይ የሚያርፍ ሲሆን አሁን የተመረቀው በ4.3 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ መሆኑ ታውቋል።

    በአፍሪካ ደረጃ የመጀመሪያ ነው የተባለው ማዕከል የመመገቢያ አዳራሽ፣ የአስተዳደር ሕንጻ፣ የሕክምና ማዕከል፣ የመማሪያ ክፍሎችና የጋራ መማሪያ አዳራሽ እንዲሁም ቤተ ሙከራን የያዘ ዘጠኝ ብሎክ ህንፃ ያለው መሆኑ ታውቋል።

    በተጨማሪም ኤሌክትሮ መካኒካል፣ የኬሚካልና ዲጅታል፣ ወርክሾፖች፣ ቤተ መጻሕፍት እና ተጨማሪ አገልግሎት የሚሰጡ ክፍሎችን ያሟላ መሆኑም ተገልጿል፡፡ ለትምህርት ቤቱ የተሟሉት ቁሳቁሶቹ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁና የጥራት ደረጃቸው ከፍተኛ እንደሆኑም ተመልክቷል።

    ፕሮጀክቱ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ጠንሳሽነት የተጀመረና በእርሳቸው ጥብቅ አመራር የተፈጸመ መሆኑ ታውቋል።

    በዚሁ አጋጣሚ ለአካባቢው ሕዝብ አገልግሎት የሚውሉ 2 ኪሎ ሜትር መንገድ፣ የጎዳና እና የውስጥ ለውስጥ መብራትና የውሃ አገልግሎት ማቅረብ ማስቻሉም ተመላክቷል፡፡

    የፕሮጀክቱ ግንባታ በጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ መሠረቱ ተጥሎ ሥራው የተጀመረው በ708 ሚሊዮን 693 ሺህ ብር መሆኑ ታውቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ቡራዩ የተሰጥኦ ማበልፀጊያ መዕከል

    Semonegna
    Keymaster

    የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝበ ውሳኔ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ይከናወናል – የምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – የደቡብ ኢትዮጵያ ክልልነት ጥያቄ ላይ የሚደረገው ሕዝበ ውሳኔ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ እንዲከናወን ቦርዱ በተገቢው መንገድ ኃላፊነቱን ይወጣል ሲሉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ ተናገሩ።

    በደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በሚገኙ የጋሞ፣ ጎፋ፣ ወላይታ፣ ጌዲኦ፣ ኮንሶ፣ እና ደቡብ ኦሞ ዞኖች እንዲሁም የቡርጂ፣ አማሮ፣ ደራሼ፣ ባስኬቶ፣ እና አሌ ልዩ ወረዳዎች የሚካሄደውን ሕዝበ ውሳኔ ጥር 29 ቀን 2015 ዓ.ም እንደሚከናወን ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል።

    የቦርዱ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ በሰጡት መግለጫ፥ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከጊዜ ወደጊዜ አሠራሩንና ደረጃውን እያሳደገ በመሆኑ ሕዝብ ውሳኔውም በተሻለ ሁኔታ እንዲከናወን ያደርጋል ብለዋል። ሕዝብ ውሳኔው ሰላማዊ፣ ነጻና ገለልተኛ በሆነ መንገድ እንዲከናወን ቦርዱ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ይወጣል ሲሉ ዋና ሰብሳቢዋ ተናግረዋል።

    ሕዝበ ውሳኔው ነጻና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ እንዲከናወን ከሚደረጉ ዝግጅቶች መካከል የምርጫ ጣቢያ አስፈጻሚዎች ምልመላ ሥራ እንደሚገኝበት ብርቱካን ሚደቅሳ ገልጸዋል። ለምልመላ በሚቀርቡ እያንዳንዱ የምርጫ ጣቢያ አስፈጻሚ ላይ ቅሬታ አለኝ ያለ አካል ሪፖርት ማድረግ የሚችልበት አሠራር መዘርጋቱን አስረድተዋል። ከዚህ ቀደም በፖለቲካ ፓርቲ፣ በሲቪክ ማኅበራትና በተቋማት ካልሆነ በቀር በግለሰብ ደረጃ በምርጫ አስፈጻሚዎች ላይ ቅሬታ የሚቀርብበት አካሄድ እንዳልነበር አስታውሰዋል። በሕዝብ ውሳኔው ላይ ግን በምርጫ አስፈጻሚዎች ሥነ-ምግባርና ገለልተኝነት ላይ ጥያቄ አለኝ የሚል ማንኛውም ግለሰብ በማስረጃ በተደረፈ መንገድ ቅሬታውን ማቅረብ እንደሚችልም ጠቁመዋል።

    በእስካሁኑ የአስፈጻሚዎች ምልመላ በስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ የተሳተፉ ዘጠኝ ሺህ አስፈጻሚዎች በደቡብ ኢትዮጵያ የሕዝበ ውሳኔ ላይ በድጋሚ ለማገልገል ፍቃደኛ መሆናቸውን ገልጸዋል ያሉት የቦርዱ ሰብሳቢ፥ በአጠቃላይ 18,750 የምርጫ ጣቢያ አስፈጻሚዎች እንደሚያስፈልጉ አስረድተዋል።

    ቀሪዎቹን የምርጫ አስፈጻሚዎች ለመመልመል ቦርዱ የቅጥር ማስታወቂያ እንደሚወጣ ገልጸዋል። እንደ ብርቱካን ሚደቅሳ ከሆነ፥ ከምልመላ ሥራው ባለፈ ለሕዝበ ውሳኔው መሳካት የሚረዱ የውይይት መድረኮች ከሲቪክና ፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ከማኅበረሰቡና ከሚመለከታቸው የጸጥታ አካላት ጋር ተካሂደዋል።

    በእስካሁኑ የዝግጅት ሥራ የሕዝበ ውሳኔው ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት በአርባ ምንጭ ከተማ ተቋቁሟል። በዞንና በልዩ ወረዳዎች መከፈት ያለባቸው 11 ጽሕፈት ቤቶች እስከትናንትናው ዕለት ድረስ አልተከፈቱም ብለዋል። ለዚህ ደግሞ የየአካባቢው አስተዳደሮች በወቅቱ አስፈላጊውን ትብብር ባለማድረጋቸው የተፈጠረ በመሆኑ አስተዳደሮቹ አስፈላጊውን ትብብር በወቅት እንዲያደርጉ ዋና ሰብሳቢዋ ጥሪ አቅርበዋል።

    በደቡብ ብሔሮች ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በሚገኙ ስድስት ዞኖች እንዲሁም አምስት ልዩ ወረዳዎች የሚገኙ ዜጎች ደቡብ ኢትዮጵያ በሚል አዲስ ክልል እንመስርት፤ አሊያም በነበረው የደቡብ ብሔሮች፣ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልልነት እንቀጥል በሚል ሕዝብ ውሳኔውን ያደርጋሉ።

    ለሕዝበ ውሳኔው በመራጭነት ሊመዘገቡ የሚችሉ ግምታዊ መራጮች ሦስት ሚሊዮን 106,585 ሰዎች መሆናቸውን ቦርዱ አሳውቋል። ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለሚያካሂደው ሕዝበ ውሳኔ ማስፈጸሚያ 410.1 ሚሊዮን ብር ከመንግሥት ተፈቅዷል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት 

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ሰብሳቢ ብርቱካን ሚደቅሳ

Viewing 15 results - 16 through 30 (of 730 total)