Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 76 through 90 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን ) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ
    ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣
    ለሁሉም የኢትዮጵያ የፖለቲካ ኃይሉች፤
    የኢትዮጵያ ጉዳይ ለሚያሳስባችሁ አፍሪካውያን ወንድሞቻችንና ዓለምአቀፍ አጋሮቻችን፤
    በመላው ዓለም ለምትገኙ ሰላም ወዳድ ኃይሎች በሙሉ !

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በሰኔ 26 እና 27 ቀን 2013 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ጥልቅና ዙሪያ መለስ ውይይት በማድረግና፤

    • የሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ፖለቲካ መሠረት ለመጣልና በሕዝብ ይሁንታ ብቻ ሥልጣን የሚይዝ ሥርዓት ለመፍጠር የተደረገውን 6ኛውን ሀገራዊ የምርጫ ሂደት በመገምገም፤
    • የታላቁን የአባይ ግድብን በማጠናቀቅና እንደ ሀገር የተፈጥሮ ፀጋችንን ተጠቅመን የመልማት መብታችንን ለማረጋገጥ በተያያዝነው ጥረት ረገድ የተጋረጡብንን ተግዳሮቶች በመገንዘብ፤
    • ሕዝባችን በሰላምና ደህንነት እጦት፣ በኮቪድ-19 ወረርሽኝና መረን በለቀቀ የኑሮ ውድነት እየደረሰበት ያለውን ምጣኔ ሀብታዊ ድቀት ግምት ውስጥ በማስገባት፤
    • ከሁሉም በላይ ሀገራችን ከውስጥ በከሃዲያንና እኩያን ኃይሎች ቅንጅት፣ ከውጭ በታሪካዊ ጠላቶቻችንና ዓለምአቀፍ አጋሮቻቸው አይዞህ ባይነትና ድጋፍ የተደቀነባትን የህልውና ስጋት ተቀዳሚ ትኩረት በመስጠት፤

    የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ የደረሰባቸውን አቋሞች ለተከበረው ሕዝባችን፣ ለአፍሪካውያን ወንድሞቻችንና በአጠቃላይም ለዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ ለማሳወቅ ይወዳል።

    1. ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ በተመለከተ

    አብን እንደ ድርጅት የመጀመሪያው አብይ የፖለቲካ ተመክሮው በሆነው በ6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ውስጥ ለመሳተፍ ሲያቅድ፥ ገና ከመነሻው ሀገራችን የምትገኝበትን የፖለቲካ አውድ በመገምገም በምርጫው የመሳተፉን ውሳኔ ያደረገው በዋነኝነት ከድርጅታዊ ፋይዳዎች ይልቅ ለሀገራዊ ፖለቲካው መረጋጋትና ለዴሞክራሲያዊ ተመክሮ ግንባታ ከሚኖረው ፋይዳ አንፃር እንደሆነ በይፋ አሳውቋል።

    አብን ሀገራዊ ፓርቲ እንደመሆኑ መጠን የምርጫ ዘመቻውን ስትራቴጂክ ግቦችና ማስፈፀሚያ ስልቶችን በዝርዝር በመንደፍ፣ አማራጭ ፖሊሲዎቹን በማኒፌስቶ በመሰነድና ሙሉ ድርጅታዊ ኃይሉን በማንቀሳቀስ በምርጫ በሚሳተፍባቸው በአማራና ሌሎችም የሀገሪቱ ክፍሎች 510 እጩዎችን በማቅረብ ሰፊውን መራጭ ሕዝብ ለመድረስ ያልተቆጠበ ጥረት አድርጓል።

    በዚህም መሠረት የምርጫ ዘመቻው ከነተግዳሮቶቹ ተጠናቅቆ፣ በሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም ፓርቲያችን በሚወዳደርባቸው ክልሎች ድምፅ ተሰጥቶና በከፊል ጊዜያዊ ውጤት ተገልጾ በድኅረ ምርጫ ሂደት ላይ እንገኛለን።

    ፓርቲያችን በመላ ሀገሪቱ በተወዳደረባቸው አካባቢዎች በምርጫው ሂደት የተፈፀሙትን አበይት ጥሰቶች በማሰባሰብና በዝርዝር ቅሬታዎችን በመሰነድ በህግ አግባብ ለብሄራዊ ምርጫ ቦርድ አቅርቧል። የምርጫ ቦርድ ከተጣለበት ታላቅ ሀገራዊ ኃላፊነት አኳያ ከሰው፣ ከፋይናንስ፣ ከተመክሮና ከሎጂስቲክ አቅም ውሱንነት ቢታይበትም በአጠቃላይ ከቅድመ ምርጫው ጀምሮ አንፃራዊ አዎንታዊነት እንዳሳየ እናምናለን። በቦርዱ የበላይ አመራር የታየው ገለልተኝነት፣ ግልፅነትና ፍትሃዊነት መንፈስ እንደ ተቋም የሚፈተንበት ወቅት እንደሆነም እንገነዘባለን።

    የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ ሕዝባችን ይህንን ሁሉ ጫና ተቋቁሞ በምርጫው ሂደት ውስጥ በመሳተፍ ላሳየው ፅናት ልባዊ አድናቆቱን በመግለፅ፣ የመራጩ ድምፅ እንዲከበር ተገቢውን ሰላማዊና ህጋዊ ጥረት እንደሚያደርግና የሕዝባችንንም ሀቀኛ ውሳኔ ያለማወላወል እንደሚቀበል ለማሳወቅ ይወዳል።

    በሌላ በኩል 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ የሥርዓቱን እውነተኛ ባህርይ በተግባር መፈተንና ማጋለጥ መቻሉን ትልቁ ውጤት አድርጎ መውሰድ ይቻላል። በምርጫው ሂደት የታየው ጎዶሎነትና ክፍተት ከምርጫ ውጤት አኳያ የምንመዝነው ከሆነ የሀገራችንን ተጨባጭ ሁኔታና የሃሳብ ብዝሃነት የማያመለክት መሆኑን መናገር ይቻላል።

    አብን እንደ ድርጅት በምርጫ በመሳተፉ ምን አገኘ፣ አሳካ የሚለውን ስንገመግም አንዳንድ ተስፋ ሰጭ ነገሮች እንዳሉ መካድ አይቻልም። ከሁሉም በላይ የሕዝባችን እውነተኛ ወኪል ስለመሆናችን ሕዝባችን የነበሩትን ጫናዎች ተቋቁሞ በሰጠን የመተማመኛ ድምፅ በቂ ማረጋገጫ አግኝተናል። ይህም የመጪው ዘመን ፓርቲ መሆናችንን ይመሰክራል። በሐገር አቀፍ ድረጃ በተሻለ ሕዝብን የማስተባበር አቅም እንዳለንና ጠንካራ ተገዳዳሪ የፖለቲካ ኃይል መሆናችንን በማያሻማ ሁኔታ አረጋግጠናል።

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ የምርጫው ሂደት አጠቃላይ ድርጅታዊ ቁመናውን የሚፈትሽበት መልካም አጋጣሚ መሆኑንም ይገነዘባል። በቀጣይም ከሂደቱ ያገኛቸውን ተመክሮዎችና ትምህርቶች በማካተትና ሁለገብ የማሻሻያ እርምጃዎች በመውሰድ ለብሔራዊ ፖለቲካችን ሁነኛ ሚና መጫወቱን እንደሚቀጥል አያጠራጥርም።

    1. ብሔራዊ ደህንነትን በተመለከተ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በተለይ በሀገር ሉዓላዊነትና አንድነት፣ በሕዝብ ጥቅምና ክብር፣ በሀገረ መንግሥቱ ቀጣይነት ረገድ ግልፅና የማያሻማ አቋም ያራምዳል። በገዥው ፓርቲ ግልፅ ፍረጃ፣ ወከባና ጥቃት እየደረሰበትም ቢሆን የፖለቲካ ማዕከሉ እንዲረጋጋና በአፍሪካ ረዥሙንና ደም አፋሳሹን የእርስ በርስ ጦርነት ያደረገች ሀገር ተመልሳ ወደ ቀውስ እንዳትገባ ያላሰለሰ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል።

    አብን ወቅታዊው የሀገራችን ብሔራዊ ደህንነት ከጊዜ ጊዜ እየከፋና እጅግ አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን ይገነዘባል። የውጭ ወራሪዎችና የውስጥ ቦርቧሪዎች ከተቻለ ኢትዮጵያን ለየዘውጉ አምበሎች በታትኖ ከዓለም ካርታ ለማጥፋት፤ ካልሆነ ደግሞ ውስጣዊ አንድነት የሌላት፣ ደካማና ፍላጎታቸውን ያለማንገራገር የምትቀበል አድርገው ለማሽመድመድ እየተረባረቡ ይገኛሉ።

    ከዚህ አንፃር የብልጽግና አገዛዝ የሀገሪቱን፣ የዜጎችና የመንግሥቱን ሰላምና ደህንነት፣ ጥቅምና ክብር በማስጠበቅ ረገድ ጉልህ ክፍተቶች እየተስተዋለበት ነው። በአሁኑ ወቅት መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ባደረገው ከፍተኛ ተጋድሎ ከአፈናና ጭቆና መንበሩ የተባረረውና በሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ በአማራ እና አፋር ልዩ ኃይልና ሕዝባዊ ሚሊሺያ ድባቅ የተመታው የትግራይ ሕዝብ ነፃ አውጪ ግንባር (ትህነግ) ተመልሶ በማንሰራራት በብሔራዊ ደህንነታችን ላይ ተቀዳሚ አደጋ ሊሆን በቅቷል።

    አብን ማዕከላዊ መንግሥትና በየደረጃው ያሉ መንግሥታዊ አካላት ሀገሪቱ ከተደቀነባት የህልውና አደጋ ለመታደግ በሚደረገው ርብርብ የራሳቸውን ሚና በግልፅ ከመወሰን አንስቶ ሁሉንም ባለድርሻ አካላት ያካተተ የብሔራዊ ደህንነት እርምጃ እንዲወስዱ ጥሪ ያቀርባል።

    መንግሥት ልዩ የደህንነት ስጋት ያለባቸው አካባቢዎች ላይ ትኩረት እንዲያደርግ፤ በተለይም አሸባሪው የትህነግ ቡድን መልሶ በተቆጣጠረው በትግራይ የተማሪዎችንና የሲቪል ዜጎችን፤ በአጠቃላይም የትግራይን ሕዝብ ደህንነት የማስጠበቅ ኃላፊነቱን እንዲወጣ ይጠይቃል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች በትግራይ ክልል በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ተመድበው ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ የሚገኙ ተማሪዎች ሁኔታ አብንን በእጅጉ ያሳስበዋል። የትግራይ ሕዝብ በመካከሉ ለሚገኙ ተማሪ ልጆቹ አስፈላጊውን ጥበቃና ክብካቤ እንዲያደርግ ጥሪ እናደርጋለን።

    አብን መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ሀገር ወዳድ ዜጎችና በተለይም ወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ሀገራችን ስለገጠማት የብሔራዊ ደህንነት አደጋ ግልፅ ግንዛቤ እንዲኖራቸውና ኢትዮጵያን ለመታደግ በአንድነት እንዲሰለፉ ጥሪ ያደርጋል።

    በወታደራዊ ኃይል የሚገኘው ድል ዳግም በዲፕሎማሲው አውድማ እንዳይነጠቅ መላው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን የሀገራቸው አምባሳደር በመሆን በዓለምአቀፍ የዲፕሎማሲ ትግል እንዲሳተፉ ጥሪ ያቀርባል።

    በተለይም ደግሞ በፀረ – ኢትዮጵያው ጎራ በጠላትነት ተፈርጆ ዘርፈ ብዙ ጥቃት የተሰነዘረበት የአማራ ሕዝብ የሚገኝበትን ወቅታዊ የስጋት ደረጃ በውል ተገንዝቦ የበኩሉን ጥንቃቄና ዝግጅት እንዲያደርግ፣ የአማራ ዲያስፖራ በሕዝባችንና በሀገራችን ላይ የተቃጣውን አደጋ ለመቀልበስ ሁለገብ የሃሳብ፣ የፋይናንስ፣ የዲፕሎማሲ ተሳትፎውን አጠንክሮ እንዲቀጥል ጥሪ ያቀርባል።

    አብን አፍሪካውያን ወንድሞቻችን፣ መላው የኢትዮጵያ ወዳጆችና አጋሮች የጥንታዊ ሥልጣኔ፣ አኩሪ የነፃነት ታሪክ ያላት ሀገር በእኩያን ኃይሎች የተከፈተባትን ወታደራዊ፣ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥቃት ለመመከት ከጎናችን እንዲሰለፉ ጥሪ ያደርጋል። በዚህ ረገድ በአካባቢው ጉዳይ ትኩረት አድርገው የሚንቀሳቀሱ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ዓለምአቀፍ ተቋማት በአፍራሽ የሀሰት ፕሮፓጋንዳ እንዳይደለሉና የችግሩን ዙሪያ ገብ በፍትሃዊነት በመገምገም እንዲንቀሳቀሱ ጥሪ ያቀርባል።

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በሀገራችን ላይ የተደቀነውን ፅኑ የብሔራዊ ደህንነት ስጋት ለመመከትና ከምንም በላይ የቆመለትን የሀገር አንድነትና ሉዓላዊነት፣ የሕዝብ ጥቅምና ክብር እንዲሁም የሀገረ መንግሥቱን ቀጣይነት ለማረጋገጥ የሚጠበቅበትን ሁሉ ድርጅታዊ አስተዋፅኦ ለማድረግ ቁርጠኝነቱን በአፅንኦት ለመግለፅ ይወዳል።

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)
    አዲስ አበባ፣ ሸዋ፣ ኢትዮጵያ
    ሰኔ 28 ቀን 2013 ዓ.ም

    ምንጭ፦ አብን

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ

    Anonymous
    Inactive

    ትግራይ ክልል – የሲቪል ሰዎችን ሁኔታ ለማሻሻል አፋጣኝ እርምጃዎች ሊወሰዱ ይገባል

    አዲስ አበባ (ኢሰመኮ) – የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ሰኔ 21 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. የፌዴራል መንግሥት በትግራይ ክልል የተኩስ አቁም ማወጁን ተከትሎ የግንኙነት መሰመሮች በመቋረጣቸው፣ በክልሉ ነዋሪዎች የሚገኙበት ሁኔታ እንደሚያሳስበውና መንግሥት የነዋሪዎችን ደኅንነት ለማስጠበቅ የሚረዱ እርምጃዎች በአፋጣኝ ሊወስድ እንደሚገባ ገለጸ። በክልሉ የተቋረጡ መሠረታዊ አገልግሎቶችን መመለስና በትግራይ ክልል ስላለው ተጨባጭ የፀጥታ ሁኔታና የሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦት በቂ መረጃ መስጠት፣ በዚህ ረገድ ያሉ ክፍተቶችን ለማረምና የሚመለከታቸውን ባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ትብብር ለመፍጠር ቀዳሚ እርምጃዎች ናቸው።

    ለግጭቱ ሰላማዊ መፍትሔ ለማፈላለግ የሚደረገው ጥረት አስፈላጊነት እንደተጠበቀና በክልሉ ለሚደረጉ የሰብዓዊ እርዳታ አቅርቦቶች ጥበቃና ለተደራሽነቱ ትብብር እንደሚቀጥል መገለጹ የሚበረታታ ሆኖ፣ የሲቪል ሰዎች ደኅንነትና ሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል። በአሁኑ ወቅት በአብዛኛዎቹ የትግራይ አከባቢዎች የመብራት፣ የስልክ እና የውሃ አገልግሎት በመቋረጡ በክልሉ ነዋሪዎች ላይ ከባድ የኑሮ ጫና እያስከተለ ይገኛል። የባንክ አገልግሎት መቋረጥና የጤና አገልግሎት አቅርቦትና ተደራሽነት ውሱንነት ችግሩን አባብሶታል።

    በትግራይ ክልል የሚንቀሳቀሱ ሀገራዊና ዓለምአቀፍ የእርዳታ ድርጅቶች የኤሌክትሪክ እና የስልክ አገልግሎት መቋረጥን ጨምሮ የሌሎች አቅርቦቶች እጥረት የሰብዓዊ ድጋፉን በከፍተኛ ደረጃ እንደጎዳውና በተለያዩ አካባቢዎች የሚኖሩ ነዋሪዎች፣ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች እና ስደተኞች ስለሚገኙበት ሁኔታ ማወቅ አስቸጋሪ እንዳደረገው ይገልጻሉ።

    በአዲስ አበባ ከተማ የትግራይ ክልል ተወላጅ የሆኑ ነዋሪዎችና የሚዲያ ሰዎችን ጨምሮ፣ ሌሎች ከጉዳዩ ጋር ግንኙነት አላቸው በሚል ተጠርጥረው የታሰሩ ሰዎችን ሁኔታ ኮሚሽኑ በመከታተል ላይ ይገኛል። ይህም በነዋሪዎች ላይ ማንነትን በመለየት ለጥርጣሬ እና መድልዎ የሚያጋልጥ ተግባር እንዳይሆን ስጋት የሚያሳድር ነው።

    በተጨማሪም፥ በክልሉ ዩኒቨርሲቲዎች የሚማሩ ወጣቶች ወላጆችና ቤተሰቦች ተማሪዎቹ በአሁኑ ወቅት ስለሚገኙበት ሁኔታ ተገቢው ምላሽ እና ማብራሪያ እንዲሰጣቸው የሚመለከታቸውን የመንግሥት አካላት በመጠየቅ ላይ ይገኛሉ።

    የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ የነዋሪዎችን ደኅንነት ማረጋገጥ ቀዳሚው የመንግሥት ግዴታ መሆኑን አስታውሰው፥ “በክልሉ የሚገኙ ነዋሪዎች ስላሉበት ሁኔታ የተገቢው መረጃ ማነስ ከተለያዩ አቅጣጫዎች ከሚደመጡ ዘገባዎችና ንግግሮች ጋር ተዳምሮ ነዋሪዎችን ስጋት ላይ የሚጥል ነው። የተኩስ አቁሙ በሁሉም በግጭቱ ተሳታፊ በነበሩ ወገኖች ሁሉ በቁርጠኝነት መከበር እና የመሠረታዊ አገልግሎቶች በአፋጣኝ መመለስ፣ አጠቃላይ ሁኔታውን ለማሻሻል፣ በትግራይ ክልል ለተፈጠረው ችግር ዘላቂ መፍትሔ ለማፈላለግ፣ እንዲሁም ሰብዓዊ አቅርቦቱ እንዳይቋረጥ የሚደረገውን ጥረት የሚያግዝ ነው። በተጨማሪም ማንኛውም አይነት እስር ሁልጊዜም ሕጋዊ ሥርዓትን የተከተለ ሊሆን ይገባል” ብለዋል። ዋና ኮሚሽነሩ አክለውም በየትኛውም የሀገሪቱ ክፍል የሚገኙ የመንግሥት እና መንግሥታዊ ያልሆኑ አካላት ሁሉ ሁኔታውን የሚያባብሱ፣ በሕዝቦች መካከል ጥላቻና ጥርጣሬን ሊፈጥሩ ከሚችሉ ንግግሮች እንዲቆጠቡ ጥሪ አቅርበዋል።

    ምንጭ፦ ኢሰመኮ

    ትግራይ ክልል – የሲቪል ሰዎችን ሁኔታ ለማሻሻል አፋጣኝ እርምጃዎች ሊወሰዱ ይገባል – ኢሰመኮ

    Anonymous
    Inactive

    በ2013 ዓ.ም. ሀገራዊ ምርጫ ድምጽ መስጫ ቀን የተደረገ የሰብዓዊ መብቶች ሁኔታ ክትትል (ቀዳሚ ሪፖርት)
    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)

    በ2013 ዓ.ም. ሀገራዊ ምርጫ የሰብዓዊ መብቶች ሁኔታ ላይ የታዩ ክፍተቶች በተገቢው የሕግ እና የአሠራር ማሻሻያ ሊታረሙ ይገባል

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከሰኔ 12 እስከ ሰኔ 16 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ ምርጫ በተካሄደባቸው በሁሉም ክልሎች በሚገኙ የተመረጡ አካባቢዎች ተንቀሳቃሽ የክትትል ቡድን በማሰማራት ያጠናቀረውን የሰብዓዊ መብቶች ክትትል ሪፖርት ይፋ ሲያደርግ፤ ክትትሉ በተከናወነባቸው የተወሰኑ የምርጫ ጣቢያዎችና አካባቢዎች የተመለከታቸው ክፍተቶች ተገቢው ትኩረት እንዲያገኙና አስፈላጊውን የሕግና የአተገባበር መፍትሔ ሊሰጣቸው እንደሚገባ ገለጸ።

    ኮሚሽኑ ለሀገራዊ ምርጫ 2013 ዓ.ም. ባለ6 ነጥብ የሰብዓዊ መብቶች አጀንዳ ይፋ በማድረግና ለሰብዓዊ መብቶች ትኩረት እንዲሰጥ ከመወትወት በተጨማሪ፥ በቅድመ ምርጫውና በምርጫው ቀን የሰብዓዊ መብቶች ሁኔታ ክትትል ሲያከናውን ቆይቷል። በተለይም ሃሳብን በነፃነት የመግለጽ፣ የመዘዋወር፣ የመሰብሰብ እና ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ መብቶችን በተመለከተና የሴቶችን ተሳትፎ ማሳደግ፣ እንዲሁም ምርጫው የአካል ጉዳተኞችን እና የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን ያሳተፈና ለእነሱ ተደራሽ የሆነ በማድረግ ረገድ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ ክትትል ሲያደርግ ቆይቷል።

    በዚህም መሠረት 94 ባለሞያዎችን ያካተተው ቡድን በአጠቃላይ በአዲስ አበባ፣ በድሬዳዋ ከተሞችና በሁሉም ምርጫ በተካሄደባቸው ክልሎች በሚገኙ 99 የምርጫ ክልሎችና 404 የምርጫ ጣቢያዎች ተዘዋውሮ፥ የአካባቢውን አስተዳደር፣ ነዋሪዎችን፣ የፀጥታ ኃይሎችን እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮችን፣ እጩዎችንና አባላት እንዲሁም የምርጫ አስፈጻሚ አካላትና ሌሎች ባለድርሻዎችን አነጋግሯል። በዋና ጽሕፈት ቤቱ በተመደቡ ባለሞያዎች አማካኝነት በ7037 የስልክ ቁጥሩ ጥቆማዎችንና አቤቱታዎችን ተቀብሎ አስተናግዷል።

    ምርጫው የተካሄደበት አውድ በሀገር ውስጥ የተደራረቡ ችግሮች የገጠሙበት እና በትግራይ ክልል የተከሰተውን ግጭት ጨምሮ በሌሎችም አካባቢዎች የተከሰቱ ግጭቶች ባሉበት፥ በተወሰኑ አካባቢዎች በጸጥታ ችግር ምርጫው እንዲተላለፍ አስገዳጅ በሆነበት፣ የተወሰኑ የፖለቲካ ቡድኖች እራሳቸውን ከምርጫው ሂደት ባገለሉበት፣ ሌሎች የፖለቲካ ቡድን አመራሮች በቀረበባቸው የወንጀል ክስ ምክንያት በእስር በሚገኙበት ወቅት መሆኑ የማይዘነጋ መሆኑንና ከግምት ውስጥ ማስገባት እንደሚገባ ኮሚሽኑ ገልጿል። ይህ ተግዳሮት እንዳለ ሆኖ፤ ኢሰመኮ በምርጫው መዳረሻ ቀናት እና በምርጫው ዕለት ክትትል ባደረገባቸው  አካባቢዎች የተወሰኑ የሰብዓዊ መብቶች አጠባበቅ ክፍተት የታየ ቢሆንም፤ በአብዛኛዎቹ ቦታዎች  የጎላ ወይም የተስፋፋ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እንዳልታየ ገልጾ፤ ክትትል ባደረገባቸው በአብዛኛዎቹ አካባቢዎች የምርጫው ዕለት ሂደት ያለ የጎላ ችግር በሰላም ተጀምሮ የተጠናቀቀና በሰብዓዊ መብቶች አጠባበቅ ረገድ በብዙ መልኩ የተሳካ የድምጽ አሰጣጥ ሂደት እንደነበር አሳውቋል። በተጨማሪም በምርጫው ሂደት በሕጋዊና ሰላማዊ መንገድ ለተሳተፉና አስተዋጽኦ ላደረጉ ወገኖች ሁሉ እውቅና ሰጥቶ፤ በቀሪው ሂደትም በሕጋዊና ሰብዓዊ መብቶችን ባከበረ መንገድ እንዲቀጥሉ ጥሪውን በድጋሚ አቅርቧል።

    እነዚህን አዎንታዊና አበረታች እርምጃዎች እንደተጠበቁ ሆነው፥ በተወሰኑ የምርጫ ክልሎች እና ጣቢያዎች ከምርጫው ዕለት ጥቂት ቀናት በፊት፣ በምርጫው ዕለትና ከምርጫው ቀን በኋላ የደረሰ የሰው ሕይወት መጥፋትና የአካል ጉዳት፣ ተገቢ ያልሆነ እስር፣ በመራጮች ላይ የደረሰ ማስፈራራት፣ በምርጫ ታዛቢዎችና ጋዜጠኞች ላይ ስለደረሰ መጉላላትና ማዋከብ፣ የምርጫው ሂደት ለአካል ጉዳተኛ ሰዎች ያለው ተደራሽነትና የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችን የተሳትፎ መጠን በሚመለከት ባወጣው የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርት አስረድቶ፤ ሊወሰዱ ስለሚገባቸው እርምጃዎች ምክረ ሃሳብ ሰጥቷል።

    በተጨማሪም ጥፋተኛ በሆኑ ሰዎች ላይ በአፋጣኝ ምርመራ በማድረግ ተጠያቂነታቸው እንዲረጋገጥ እና ኮሚሽኑ በሕግ የተሰጠውን በምርጫ ወቅት የሰብዓዊ መብቶች ክትትል የማድረግ ኃላፊነቱንና ተግባሩን በአግባቡ እንዳይወጣ የሚያግዱ፣ የሚገድቡ ወይም የሚያሰናክሉ ሁኔታዎች በተለይም የምርጫ ጣቢዎችን ያለ እንቅፋት የመጎብኘት አስፈላጊነት እና የእስር ቦታዎችን ያለ ቅድሚያ ማስታወቂያ የመጎብኘት አስፈላጊነት በሚመለከት ለወደፊቱ ማናቸውም ዓይነት እንቅፋት እንዳይከሰት ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ተገቢውን እርምጃ እንዲወስዱና ሁሉም ሰዎችና ተቋማት ለኮሚሽኑ ሥራ የመተባበር ግዴታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ አሳስቧል።

    ኢሰመኮ ያወጣውን ሪፖርት እዚህ ጋር በመጫን ያግኙ።

    ምንጭ፦ ኢሰመኮ

    በ6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ድምጽ መስጫ ቀን የተደረገ የሰብዓዊ መብቶች ሁኔታ ክትትል

    Anonymous
    Inactive

    ከባልደራስ ፓርቲ የተሰጠ መግለጫ
    ኢትዮጵያ መቼ ይሆን ነፃ፣ ፍትሀዊና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ የሚኖራት?!

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ከተመሠረተ ጊዜ ጀምሮ ፍትህ እንዲሰፍን ሰላምና መረጋጋት እንዲመጣ፣ አድሎአዊነትና ዘረኝነት እንዲወገድ፣ ሕዝብ ከመፈናቀልና ከድህነት እንዲላቀቀቅ፣ አዲስ አበባ የራስ ገዝ አስተዳደር እንድትሆን እና ሌሎችም ዲሞክራሲያዊ መብቶች እንዲሰፍኑ የሚያስችል ሥርዓት ለማምጣት ጠንክሮ ሠርቷል፤ እየሠራም ነው። የሀገሪቱ መሪ “ከባልደራስ ጋር ግልጽ ጦርነት እንከፍታለን” እያሉ በተናገሩበት ወቅት እንኳን ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ከመታገል ቁርጠኛ አቋሙ ወደ ኋላ አላለም።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) በ6ኛው ሀገር አቀፍ ቅድመ ምርጫ ሂደት (pre-election process) ላይ በተለያዩ ጊዜያት ሳይንሳዊ ጥናቶች አካሂዶ ዝቅተኛውን ዓለም አቀፍ የምርጫ መስፈርት የማያሟላ መሆኑን አረጋግጧል። የምርጫ ሂደቱ የተበላሸ ከሆነ ውጤቱም በተመሳሳይ መንገድ ሊሆን እንደሚችል የሚጠበቅ ቢሆንም ባልደራስ በኢትዮጵያ ሰላም ለማስፈን የበኩሉን አስተዋጽኦ ለማበርከት ሲል በምርጫው የተሳተፈ መሆኑን ለማሳወቅ እንወዳለን።

    ፓርቲያችን ከአራት ወራት በፊት ጀምሮ ባካሄዳቸው ከፍተኛ የምርጫ እንቅስቃሴዎች ወቅት ሕዝብ ከጎኑ መሆኑን በተለያዩ መንገዶች አረጋግጧል። አዲስ አበቤ ለድርጅታችን ባሳየው ደጀንነትም ፓርቲያችን እጅጉን ኮርቷል። ያነሳነውን አዲስ አበባን ራስ ገዝ የማድረግ ጉዞ ሕዝባችን ከጎናችን በመሆን ስለሰጠን ድጋፍ ከልብ እናመሰግናለን። ለሰጣችሁንም ድምፅ ምስጋናችን ከፍ ያለ ነው። ይህንኑ ወደ ፊትም አጠናክረን እንደምንሄድ በዚሁ አጋጣሚ እንገልፃለን ።

    ዓላማችንን ከግብ ለማድረስ ደከመኝ፣ ሰለቸኝ ሳትሉ፥ ዕውቀታችሁን፣ ጊዜያችሁን፣ ገንዘባችሁንና ልዩ ልዩ ቁሳቁሶችን ጭምር የለገሳችሁ የፓርቲው አመራሮች፣ የሕዝብ ተወካዮችና የአዲስ አበባ ምክር ቤቶች እጩዎች፣ የምርጫው የቅስቀሳና የሎጂስቲክስ አካላት፣ የባልደራስ የዴሞክራሲ ማዕዘን በመሆን የምርጫውን ሂደት ከሁለት ቀንና ሌሊት በላይ የተከታተላችሁ ወኪሎቻችን እና በተለያዩ እንቅስቃሴዎቻችን ላይ የተሳተፋችሁ ሁሉ የላቀ ምስጋና የምናቀርብላችሁ በታላቅ ደስታ ነው። በሰሜን አሜሪካ፣ በአውሮፓ እና በሌሎችም ዓለማት የምትኖሩ የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ የድጋፍ ሰጭ ኮሚቴ እና የአማካሪ ቦርድ አባላት ላደረጋችሁት ሁሉን አቀፍ ድጋፍ፣ ምክር እና አስተዋፆኦ ምስጋናችን እጅጉን ከፍ ያለ ነው።

    “አዲስ አበባን ማዳን ኢትዮጵያን ማዳን ነው” በሚል ዓላማ የጀመርነውን ጉዞ ገዥው ፓርቲ መሪዎቻችንን በማሰር ለማሰናከል ጥረት አድርጓል። ነገር ግን ትግሉ የተነሳበትን ዓላማ ይበልጥ ከፍ አድርጎ በመቀጠሉ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች የሚገዙት ሃሳብ ሆኗል። በሀገር ውስጥ ያላችሁ አባላት እና በውጭ ሀገር የምትኖሩ ድጋፍ ሰጭዎች የተሸረበውን ሴራ በጣጥሳችሁ በመውጣት፣ በሰላማዊ ትግሉ ፋና ወጊ የሆኑ መሪዎችን ቀንዲል ከፍ ብሎ እንዲታይ ያደረጋችሁ ናችሁና በድጋሚ የባልደራስ አመራር በእናንተ ደስታና ኩራት እንደሚሰማው ይገልጻል ።

    በባልደራስ ፓርቲ ቅድመ ምርጫ ሂደት ጥናት እንደተረጋገጠው በብዙ ውጥንቅጥ ውስጥ የታጀበው ዝቅተኛውን የምርጫ መመዘኛ ደረጃዎች ያላሟላው የሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. ምርጫ የመጣውን ውጤት ማሳየት ችሏል። እንደሌሎቹ ጊዜዎች ሁሉ የዘንድሮውንም ምርጫ ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ ለማድረግ ከመንግሥት በኩል ምንም ቁርጠኝነት አለመኖሩን ፓርቲያችን ተገንዝቧል።

    ከምርጫው ቀን ዋዜማ ጀምሮ በአዲስ አበባ ነዋሪ ላይ የፍርሃት ድባብ ለመፍጠር በከፍተኛ ደረጃ የታጠቁ የፓሊስ እና የመከላከያ አባላት የጦር መሣሪያቸውን ወድረው በአዲስ አበባ የተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር የሥነ ልቦና ጫና ሲፈጥሩ ሰንብተዋል። ይህም “ሊበሏት ያሰቧትን አሞራ ይሏታል ጅግራ” እንደሚባለው በምርጫው ሰሞን ከነበሩ ኢ-ዲሞክራሲያዊ ትዕይንቶች አንዱ ነበር።

    ምርጫውን ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ ማድረግ ጠቀሜታው በሥልጣን ላይ ላለው መንግሥት እና ተወዳድረው ለማሸነፍ ለሚፎካከሩት ፓርቲዎች ብቻ ሳይሆን ለሚወክሉት ሕዝብ ጭምር መሆኑ ይታወቃል። ምርጫው ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ ሳይሆን ሲቀር የሕዝብ ነፃነት ይገፈፋል፤ ሥርዓት አልበኝነት ይነግሣል። በዜጐች መካከል የደረጃ ልዩነት እና መሰል ችግሮች ተፈጥረው ሕዝብ በፍርሃት አረንቋ ውስጥ ይወድቃል። እነዚህን ችግሮችን ለማስወገድ በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ከፍተኛ ኃላፊነት ያለበት መሆኑ ይታወቃል።

    በ6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ የተከሰቱ ችግሮችን ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ በጥልቀት እየመረመረው ይገኛል። እስካሁን በደረሰበት ሁኔታ ምርጫው ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ አልነበረም የሚል መደምደሚያ ላይ የሚያደርሱ ተግባራት መኖራቸውን ፓርቲያችን ያምናል። ለአብነትም፡-

    1. ድምፅ አሰጣጥን በተመለከተ ግንዛቤ ለመስጠት የተሰየሙት የምርጫ አስፈፃሚዎች የገዢው ፓርቲ እንዲመረጥ የሚረዳ ገለጻ ሲያካሂዱ የፓርቲዎች ወኪሎች እርምት እንዲያደርጉ ቢያስገነዝቡም አስፈፃሚዎች ብልሹ አሠራራቸውን አለማስተካከላቸው በችግርነት የታየ ጉዳይ ነው፤
    2. በመራጮች ምዝገባ ወቅት ያልነበሩ አዳዲስ ንዑስ የምርጫ ጣቢያዎችን ከመክፈት በተጨማሪ ማንነታቸው የማይታወቁ የምርጫ ጣቢያዎች ተከፍተው በድምፅ መስጫ ቀን ድምፅ ሲሰጡባቸው መቆየታቸው፣
    3. አቅመ ደካሞችን፣ በእድሜ የገፉትን እና የአካል ጉዳተኞችን የመንግሥት ካድሬዎች ከምርጫ ሕጉ ውጭ በማገዝ ስም በሚስጥር ድምፅ በሚሰጥባቸው ክፍሎች ይዘዋቸው በመግባት ጫና እየፈጠሩ የሚፈልጉትን ማስመረጣቸው፣
    4. በአንዳንድ የምርጫ ጣቢያዎች የባልደራስን የምርጫ ውጤት ቁጥሮች እየቀነሱ እንዲጻፉ መደረጋቸው፣
    5. ባልደራስ የተመረጠባቸውን ወረቀቶች በስልት ከጥቅም ውጭ እንዲሆኑ ወይም የባከኑ ውጤቶች እንዲሆኑ መደረጋቸው፣
    6. በእያንዳንዱ የምርጫ ጣቢያ ያለው የመራጩ ቁጥር ቀድሞ የሚታወቅ ሆኖ እያለ በብዙ የምርጫ ጣቢያዎች የመራጮች ድምፅ መስጫ ወረቀቶች ከመራጮች ቁጥር እንዲያንስ መደረጉና ወረቀቱ እስኪመጣ መራጮች በፀሐይ፣ በዝናብና በብርድ በርካታ ሰዓታት እንዲቆዩ መሆናቸው የተወሰኑት ሳይመርጡ ወደ የቤታቸው እንዲሄዱ አስገድዷቸዋል።
    7. ለአዲስ አበባ ምክር ቤት ለውድድር የቀረቡ ፓርቲዎች በርካታ በመሆናቸውና በምርጫ ወረቀቱ ላይ በምርጫ አስፈፃሚዎች በቂ እና ግልጽ ማብራሪያ ባለመሰጠቱ የምርጫ ወረቀቱ በውስጡ ምን ያህል እጩዎች እንደያዘ አለመታወቁ ለመራጮች አስቸጋሪ ሁኔታን የሚፈጥር ሆኗል። ይህም መራጩ በግልጽ ድምፅ የመስጠት ነፃነት እንዳይኖረው አድርጓል።በዚህም የድምፅ መስጫ ወረቀቶች እንዲባክኑ ወይም መራጩ ላልፈለገው ድምፅ እንዲሰጥ ሆኗል። ከላይ የተጠቀሱት በምሳሌነት ከሚነሱት ችግሮች እጅግ በጣም ጥቂቶቹ ናቸው።

    የገዥው ፓርቲ በምርጫ ወቅት ለችግረኛ ሰዎች የተለያዩ መደለያዎች በመስጠት የሕዝብን ገንዘብ ለሥልጣን መሸመቻ ማድረጉ በምድር ቀርቶ በፈጣሪ ዘንድ ይቅር የማያሰኝ ተግባር ነው። በሌሎች ጊዜዎች የድሆችን ችግር ለማስወገድ ትኩረት የማይሰጠው ገዥው ፓርቲ በምርጫ ሰዓት ብቻ ማባበያ ይዞ መቅረቡ ነዋሪውን ለመደገፍ ሳይሆን ሥልጣኑን ለማቆየት የተጠቀመበት ዘዴ መሆኑ ግልጽ ነው።

    ከምርጫ 97 ወዲህ የምርጫ ጣቢያዎች እንዲበዙ የተደረገባቸው ምክንያቶች ኗሪዎች በረጃጅም ሰልፎች ላይ በመቆየት እንዳይንገላቱ ለማድረግ መሆኑ ይታወቃል። ነገር ግን ዛሬ ምርጫ ጣቢያዎች እንደአሸን እንዲፈሉ በተደረገበት ወቅት መራጮችን ለማሰላቸትና ለማስመረር ይሁን ተብሎ የተከናወኑት ማጓተቶች ድምፅ ሰጭዎች እንዲንገላቱ ማድረጉ የሚያስተዛዝብ ሁኔታን ፈጥሯል። ቀን በፀሐይና በዝናብ፣ በምሽት እና በሌሊት ደግሞ በብርድ እንዲንገላታ የተደረገበትን ደባ ተቋቁሞ የተሰለፈው አዲስ አበቤ ድምፁን ለማን እንደሰጠ ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ ጠንቅቆ ያውቃል ።

    በገዥው ፓርቲና በምርጫ ቦርድ ለማሰላቸት ሆን ተብሎ በተፈጠረው ተስፋ የማስቆረጥ ሂደት ሳትመርጡ ለቀራችሁ፣ ሆን ተብሎ በተሠራ ደባ ካርድ እንዳታወጡ የተደረጋችሁ እና መምረጥ ያልቻላችሁ፣ ጊዜ በማጣት ካርድ ላልወሰዳችሁ፣ እንዲሁም በሀገራችን ሁኔታ ተስፋ በመቁረጥ የዜግነት ግዴታ መወጣት ያልቻላችሁ የእናንተ ድምፅ ሀገራችን ከገባችበት ውጥንቅጥ ችግሮች መውጫ ከፍተኛ ሚና የሚጫወት ሆኖ ሳለ በመቅረቱ በእጅጉ ያስቆጫል።

    የአሁኑ የኦህዴድ/ብልጽግና አባት የሆነው ህወሓት/ኢህአዴግ በምርጫ 2007 የ100% የአሸነፍኩ ጉዞ ከ2 ዓመት በላይ በሥልጣን መቆየት እንዳልቻለ የ3 ዓመት ትውስታችን ነው። በሕዝብ ያልተመረጠ መንግሥት ራሱን ይሸነግል ይሆናል እንጂ ረጅም ርቀት እንደማይጓዝ ከዚሁ ከሀገራችን ታሪክ መረዳት ይቻላል። ለነፃ፣ ፍትሀዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ዳኝነት የሚሰጠው ሕዝብ ነውና።

    6ኛውን ሀገር አቀፍ ምርጫ “ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ አደርጋለሁ” ይል የነበረው ኦህዴድ/ብልጽግና በምርጫው ዙሪያ እየተፈጸሙ ያሉት ድርጊቶች የማያልቅ ሀሰቱ ማሳያዎች ሆነዋል። ዜጎች እየተገደሉ፣ ሰብዓዊ መብታቸው እየተጣሰ፣ ንብረታቸው እየወደመ፣ እየተራቡ እና እየተደፈሩ፣ የውጭ ወራሪ ኃይሎች ድንበር ጥሰው ሀገራችን ውስጥ ገብተው እንደፈለጉ እየሆኑ “ኢትዮጵያ አሸንፋለች፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰላም ሰፍኗል።…” የተሰኙት አባባሎች ዓይናችሁን ጨፍኑ ላሞኛችሁ ከማለት ያለፈ ትርጉም የላቸውም።

    የአዲስ አበባ ሕዝብ ለሰጠን ታላቅ ድጋፍና ፍቅር፣ ክብርና ሞገስ አሁንም ደግመን እናመሰግነዋለን። የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ አመራሮች እና አባላት በሕዝብ ፊት በተግባር ጭምር እየተፈተንን የሰላማዊ ትግል አርበኞች መሆናችንን አስመስክረናል።

    የዴሞክራሲ ኃይሎች ትንንሽ ልዩነቶችን ወደ ጎን በመተው ለማይቀረው የሰላማዊ ትግል ተደጋግፈን ሕዝብን በማስተባበር እንድንታገል ዛሬም እንደቀድሞው ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ ጥሪውን ያቀርባል።

    ብሔራዊ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ሰኔ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. የተካሄደወን የምርጫ ውጤት ይፋ ካደረገ በኋላ ከምርጫው ጋር በተያያዘ በዝርዝር ጉዳዮች ላይ ባልደራስ መግለጫ የሚሰጥ መሆኑን በአክብሮት ይገልጻል።

    የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ
    ድል ለእውነተኛ ዴሞክራሲ!!!
    ሰኔ 18 ቀን 2013 ዓ.ም.

    ምንጭ፦ ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ

    ነፃ፣ ፍትሀዊና ዲሞክራሲያዊ ምርጫ

    Anonymous
    Inactive

    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ መግለጫ
    (ድኅረ ምርጫ 2013)

    ሰኔ 17 ቀን 2013 ዓ.ም

    የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታን መሠረት ለመጣል የሚጠይቀው መስዋዕትነት እጅግ ረጅምና መራር ነው። በተለይም እንደ አፍሪካ ውስጥ ባሉ በበርካታ ውስብስብ አሠራሮች በተተበተቡ አገሮች ውስጥ፣ የፖለቲካ ምህዳሩ ጥበት፣ ከፍተኛ የሥልጣን ጉጉትና የመሳሰሉት እንቅፋቶች የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታውን ቀይደው ይይዙታል። ድህነቱ፣ ኋላቀርነቱ፤ የዜጎች የፖለቲካ አረዳድ ወዘተ ችግሮቹን ይበልጥ ያባብሱታል።

    በተለይም በዘውግና በቋንቋ ላይ የተመሰረተው የሀገራችን የፖለቲካ ትርክት ላለፉት 30 ዓመታት ከአንድነት ይልቅ ልዩነቶቻችንን አግዝፎ በትውልዱ ላይ ቁርሾን ዘርቷል። ዛሬም ከዚህ የማንነት የፖለቲካ አዙሪት ለመላቀቅ አልቻልንም። ከዚህ የችግር አረንቋ ውስጥ ለመውጣት የዜግነት ፖለቲካው ብርቱ ዋጋ የሚያስከፍል ቢሆንም ነገም ብቸኛው አማራጭ መሆኑ ሊታመን ይገባል።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ በታሪኳ በተለያዩ የመንግሥት ቅርጽና የፖለቲካ ፍልስፍና በየጊዜው ሥልጣን ላይ በወጡ ኃይሎች ስትመራ መቆየቷ ይታወቃል። ላለፉት 30 ዓመታት እስከ 6ኛው ዙር ምርጫ ድረስ በምርጫ ብቻ ሥልጣን ለመያዝ የተሞከረው ሒደት ተስፋ ሰጪ ባይሆንም ዜጎች የምርጫ ተሳትፎ ማድረጋቸው አንድ ጥሩ እርምጃ ነው ሊባል ይችላል።

    ሰኔ 14 ቀን 2013 የተደረገው 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ሂደቱ እና ውጤቱ ሙሉ በሙሉ ለሕዝብ የተገለፀ ባይሆንም በብዙ ግልጽ ችግሮች የታጀበ ነበር። ለዚህ ምርጫ ሰላማዊነትና የአገሪቱን የነገን ቀጣይነት በምርጫ ለማረጋገጥ፣ ዜጎች በምርጫው ላይ በንቃት እንዲሳተፉ ኢዜማ የበኩሉን ድርሻ በኃላፊነት ተወጥቷል የሚል የፀና እምነት አለን። ከምንም በላይ ለሀገር መረጋጋትና ለሕዝብ ሰላም ያለውን ቁርጠኝነትም በተግባር አስመስክሯል።

    በመሆኑም ለቀጣይ የኢዜማ መዋቅር አደረጃጀት ለፓርቲያችን ደጋፊዎች፣ አባላትና በየደረጃው ለሚገኙ አመራሮች የሚከተሉትን ማሳወቅ ይኖርብናል።

    1ኛ/ ሰኔ 14 ቀን 2013 የተደረገው የ6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ የመጨረሻ ውጤት እስከሚገለጽ የምንጠብቅ ሲሆን ቅድመ ምርጫና በምርጫ ወቅት ኢዜማ በተወዳደረባቸው በርካታ የምርጫ ክልሎች ያጋጠሙትንና በየሰዓቱ ለምርጫ ቦርድ ያሳወቅናቸው በርካታ ተግዳሮቶችን በአጽንኦት ተመልክቶ ውሳኔ የማይሰጥባቸው ከሆነ ጉዳዩን ወደ ፍትህ አካላት ይዘን የምንሔሄድበትን ሁኔታ ቀድመን ለሕዝብ የምናሳውቅ ይሆናል።

    2ኛ/ ኢዜማ የምርጫ 2013 አጠቃላይ የፓርቲውን የምርጫ እንቅስቃሴ የሚያስተባብር የምርጫ ስትራቴጂክ ማኔጅመንት ኮሚቴ ከአመት በፊት አዋቅሮ ሲንቀሳቀስ እንደነበረ ይታወቃል። ይህ ኮሚቴ አጠቃላይ የምርጫውን ሂደት በተመለከተ ከሚያዘጋጀው የግምገማ አጠቃላይ ሪፖርት፣ በድርጅት በኩል፣ በብሔራዊ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ በተቋቋመ ቡድንና ከፓርቲው ውጪ በተመረጡ ገለልተኛ አካላት ከሚቀርበው ግምገማ ተነስተን አጠቃላይ ሁኔታውን ለኢትዮጵያ ሕዝብ እንገልጻለን።

    3ኛ/ እንደሚታወቀው የፖለቲካ ፓርቲ ሰላማዊ ትግል ቀጣይነት ያለውና ከምርጫ በኋላም ቢሆን ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑ እሙን ነው። በዚህ ረገድ ኢዜማ ጊዜያዊ ፓርቲ ሳይሆን ገና ከመነሻው ከምርጫ ወረዳ ጀምሮ ሲዋቀር ሩቅ ተጓዥና ዘመን ተሻጋሪ ፓርቲ ሆኖ ነው። ከዚህ አንጻር በምርጫው ሒደት ያጋጠሙንን ተግዳሮቶች በሕግ አግባብ እየጠየቅን ከዚህ ምርጫ ማግስት ጀምሮ የድርጅቱን መዋቅር ይበልጥ በማጠናከር ወደ ሥራ የገባን መሆኑን ለማሳወቅ እንወዳለን።

    4ኛ/ ኢዜማ በተቋቋመ በሁለት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ከየትኛውም ተፎካካሪ ፓርቲ በላቀ መልኩ በመላው አገሪቱ 455 የምርጫ ወረዳ መዋቅሮችን አደራጅቶ በጥንካሬ እየተንቀሳቀሰና በምርጫ 2013 ገዢውን ፓርቲ በብርቱ የሞገተ ፓርቲ ነው፤ ሕዝባዊ መሠረቱም ሰፊና ጠንካራ ነው።

    ከዚህ አንጻር የፓርቲው የወረዳ መዋቅሮች በምርጫ ሂደት የተገኘውን ውጤት፣ ልምድ፣ የሰው ኃይል፣ ልዩ ልዩ ግብዓቶች እና ወዘተ የመሳሰሉትን ፓርቲውን ይበልጥ ለማጠናከር መጠቀምና ድርጅቱን በጥንካሬ ለመምራት በየደረጃው የሚገኙ የፓርቲው አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች ከዚህ ምርጫ ማግስት ጀምሮ ብርቱ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉና በቀጣይ ለሚያጋጥሙን ሀገራዊ ጉዳዮችና ሰላማዊ ለሆኑ የትግል እንቅስቃሴዎች ራሳችንን እንድናዘጋጅ የከበረ ጥሪ ማስተላለፍ እንሻለን።

    ኢዜማ ላለፉት ሁለት ዓመታት በተለይም ከምርጫ መቃረብ ጋር ተያይዞ የኢትዮጵያ መፍትሄ ሰጪ ፖሊሲዎችን የነደፈ፣ ማኒፌስቶ አዘጋጅቶ ለሕዝብ ያሳወቀ፣ የምርጫ ቅስቀሳዎችን በሰለጠነ መንገድ ያካሄደ፣ ማኅበራዊ ፍትህ ለማስፈን መሠረቱን ዜግነት ላይ ያደረገ ፓርቲ መሆኑንና መላው የኢትዮጵያ ሕዝብም በእያንዳንዱ እንቅስቃሴ ላይ የራሱን ተሳትፎ እንዳደረገ እናምናለን።

    በመጨረሻም ነገም ኢትዮጵያ ሀገራችን ሉዓላዊ ግዛቷና የሕዝብን ደህንነት ተጠብቆ፣ ለቀጣዩ ትውልድ የምናወርሳት ጠንካራ ሀገር እንድትሆን ኢዜማ ዘመን ተሻጋሪ ፓርቲ ሆኖ በጥንካሬ እንደሚቀጥል እየገለጽን በፀሐይና በዝናብ ወስጥ፤ ቀንና ለሊት ተሰልፋችሁና በብርቱ ጫናና መዋከብ ውስጥ ሆናችሁ ድምጻችሁን ለኢዜማ የሰጣችሁትን ከልብ እያመሰገንን ያልመረጣችሁንንም ውሳኔያችሁን የምናከብር መሆኑን እንገልጻለን።

    ምንጭ፦ ኢዜማ

    ኢዜማ

    Anonymous
    Inactive

    የ6ኛውን ሀገራዊ ምርጫ “ሰላምና ደህንነት” አስመልክቶ ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የተሰጠ መግለጫ

    የተከበርከው የኢትዮጵያ ሕዝብ፥

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን በቅድሚያ ለታሪካዊው 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ እንኳን በሰላም አደረሳችሁ እያለ የምርጫው ሂደት ተጀምሮ አሁን ያለበት ደረጃ እስኪደርስ በጨዋነትና በትዕግስት ላደረጋችሁት ድጋፍና ትብብር የላቀ ምስጋናውን እያቀረበ በቀሪው የምርጫ ሂደትም ምርጫውን የሚያደናቅፉ አጠራጣሪ ጉዳዮች ሲያጋጥሙ እንደተለመደው ሁሉ መረጃ በመስጠትና አስፈላጊውን ድጋፍ ለፀጥታ እና ለደህንነት ኃይሉ በማድረግ የበኩላችሁን ድርሻ እንድትወጡ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

    የተከበራችሁ የሀገራችን ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች፥

    የምርጫ ሕጉንና የሥነ-ምግባር ደንቡን አክብራችሁ እስከ አሁን ለምርጫው ሰላማዊነት የበኩላችሁን ገንቢ አስተዋፅኦ በማበርከታችሁ ኮሚሽኑ ምስጋናውን እያቀረበ በቀጣይም በሚኖረው የምርጫ ሂደት እስከመጨረሻው ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሀገራዊ ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ ኮሚሽኑ አጥብቆ ይጠይቃል።

    የተከበራችሁ የፌዴራልና የክልል የፀጥታና የደህንነት አካላት፥

    መስዋዕትነት በመክፈል ጭምር ፍፁም ገለልተኛ ሆናችሁ ሌት ተቀን እያበረከታችሁት ላላችሁት አስተዋፅኦ ኮሚሽኑ ከልብ እያመሰገነ፤ በቀጣይ ለሚኖረው የድምፅ አሰጣጥና አጠቃላይ ለምርጫው ሂደት ስኬታማነት የተሰጣችሁን ሰላምና ደህንነት የመጠበቅ ኃላፊነታችሁን ልክ እንደቀደመው ጊዜ ሁሉ እንድትወጡ ከአደራ ጭምር ያሳስባል፡፡

    ኮሚሽኑ ሀገራችን ኢትዮጵያ የምትገኝበትን ወሳኝ ምዕራፍ ከግምት ውስጥ በማስገባት የምርጫ ሂደቶች ከሁከትና ብጥብጥ የጸዱ እንዲሆኑ ከፀጥታና የደህንነት መዋቅሩ ጋር የተቀናጀ የምርጫ ደህንነት ዕቅድ በማዘጋጀት፣ በቅድመ ምርጫ፣ በምርጫ ዕለት እና በድኅረ-ምርጫ ወቅት ሊያጋጥሙ የሚችሉ ውስጣዊና ውጫዊ የፀጥታ ሁኔታዎችን በአግባቡ በመተንተን እና በመለየት አስፈላጊውን ዝግጅት በማድረግ ሲሠራ ቆይቷል።

    ከዚህ አንፃር 6ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ በሆነ ሁኔታ ማጠናቀቅ ለሀገራችን ሰላምና መረጋጋት እንዲሁም የሀገራችንን ታላቅነት ለመላው ዓለም የምናሳይበት ታላቅ ኩነት መሆኑንና ለገጽታችን ግንባታ ያለው ጠቀሜታ ከፍተኛ መሆኑን የተረዳው ኮሚሸኑ የውስጥና የውጭ ፀረ-ሰላም ኃይሎች ፀጥታውን ለማናጋት፣ የምርጫውን ሰላማዊነት ለማደፍረስና የሁከትና ብጥብጥ መንስዔ ለማድረግ እንደሚንቀሳቀሱ ከወዲሁ በመረዳት ምንም ዓይነት ሕገ-ወጥ እንቅስቃሴ በየትኛው አካባቢ እንዳይኖር ከፌዴራል እስከ ክልል ያሉ የሀገራችን የፀጥታና የደህንነት መዋቅሮች በከፍተኛ ኃላፊነትና ተጠያቂነት የተሰጣቸውን ሀገራዊ ተልዕኮ በብቃት መወጣት የሚያስችላቸው ሁለንተናዊ አቅም በመገንባት ሙሉ ዝግጅቱን አጠናቆ ወደ ስምሪት ገብቷል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ለሕዝቡ እና ለሥራችን ከፍተኛ እገዛ የሚያደርጉት አስፈላጊ እና ወሳኝ የሆኑት ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶች በምርጫ ወቅት ያለ በቂ ምክንያት እንዳይቋረጡ የሚመለከታቸው አካላት ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ኮሚሽኑ በአንክሮ ያሳስባል፡፡

    በመጨረሻም መላው የሀገራችን ሕዝብ እና የፀጥታ ኃይሉ ከመቼውም ጊዜ በላይ በመቀናጀት ይህንን ታሪካዊ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ እንድንወጣ ጥሪያችንን በከፍተኛ አክብሮት እያቀረብን፥ በድምጽ መስጫ ዕለትና በድኅረ-ምርጫ ወቅት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ሁሉ በሕግ አግባብ ብቻ እንዲሆኑ ኮሚሽን በጥብቅ ያስታውቃል፡፡

    ኮሚሽኑ በድጋሚ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ እንኳን ለ6ኛው ሀገራዊ ምርጫ በሰላም አደረሳችሁ ይላል።

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን
    ሰኔ 12 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ

    ምንጭ፦ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን

    6ኛውን ሀገራዊ ምርጫ -- ከፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የተሰጠ መግለጫ

    Anonymous
    Inactive

    እብለት የሌለበት ምስክርነቴ – ለዶ/ር ብርሀኑ ነጋ

    (የትነበርክ ታደለ /ጋዜጠኛ/*)

    በሀገራችን የዲሞክራሲ ትግል ውስጥ ትልቁ ፈተና ኢ-ዴሞክራሲያዊና አምባገነን መንግሥታት ብቻ አይደሉም፤ የሴራ ምሁራንም ጭምር እንጂ። በገዛ ራሳችን ምሳሌ “ቀና ቀና ያለች ማሽላ አንድም ለወፍ፥ አንድም ለወንጭፍ” እንደ ተባለው የሀገራችን የሴራ ምሁራን ከመካከላቸው ቀና ያለውን በማጥቃት ብዙ ፍሬ ያዘሉ ሰብሎቻችንን አምክነው ኖረዋል። በዚህ ድርጊታቸው ከአምባገነን መንግሥታት በላይ ሀገራችንን መከራ ውስጥ ጨምረዋል። ብርሀኑ ነጋ ለእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የመፍትሄ ምንጭ እንጂ ጸረ-ኢትዮጵያዊ ወይም ጸረ-ኢትዮጵያ ተብሎ ለተከታታይ ዓመታት በአደባባይ የሚዘመትበት ሰው አልነበረም!!

    ብርሀኑ…

    ከጽንፈኛ ብሔርተኞችና ከአክራሪ ሀይማኖተኞች በሚወረወርበት ሾተል ጀርባው እየደማ የዜግነት ፖለቲካን የሙጥኝ ያለው ‘በኔ ጉዳት ኢትዮጵያ ትዳን’ ብሎ እንጂ ኢትዮጵያን ስለሚጠላ አይደለም!

    እንዲህም ተባለ እንዲያ ዛሬ ያ መገፋቱ ፍሬ አፍርቶ እነሆ ከሦስት የጭለማ ዓመታት በኋላ ሀገር ኖራ፣ ምርጫም ኖሮ፣ ወደ ፊት ልንሻገር ነው ብለን የምናስብበት የተስፋ ጭላንጭል ላይ ደርሰናል።

    ‘ምርጫ አለ’ ያልነው ብርሀኑ ስላለ ነው! ኢትዮጵያ ያንን ሁሉ መከራ አልፋ ለምርጫ የደረሰችው ብርሀኑ ነጋ በፖለቲካ ስም ሀገር የመናድ የገመድ ጉተታው አካል ስላልነበረ ነው!

    ዶላርና የጥይት አረር ታቅፈው ከውጭ የገቡ ተቃዋሚዎችና ሚሳኤል የታጠቀች ህወሓት “ሕገ-መንግሥቱን ትነኩትና” እያሉ በሚያስፈራሩበት በዚያ የሦስት ዓመት ጭለማ ክረምት ውስጥ ሕዝብ ብርሀኑን ሰምቶ “እውነት ነው፤ ጊዜው የሕገ መንግሥት ጥያቄ ማንሻ አይደለም” ብሎ ጋብ ባይል ኖሮ፤ “ይህ የምንፈልገው ሥርዓት አይደለም፣ ይሁን እንጂ ለሀገራችን ስንል እንደግፈው፣ ከችግሮቹ ይልቅ ጠንካራ ጎኖቹን እያሳየን ወደ ፊት እንግፋው” ብሎ ከመንግሥት ጎን ቆሞ “አለሁ!” ባይል ኖሮ የዛሬው የምርጫ ክርክር ቅንጦት በሆነ ነበር።

    በእውቀቱ ልክ እያሰበ በሀገር ፍላጎት ልክ እየወሰነ ባይራመድ ኖሮ “በለው! በለው! ፍለጠው! ቁረጠው!” ባዮች ጋር በስሜት ጋልቦ ቢሆን ኖሮ… እንኳን አንግቦት የተነሳውን የዜግነት ፖለቲካ ለአካለ ምርጫ ማድረስ ይቅርና፥ ለሀገራችንም ጦስ በሆነ ነበር።

    ይህ ሁሉ ለሕዝብ ግልጽ የሆነ ሀገራዊ አበርክቶው በሴራ ምሁራን ትንታኔ እየታጀለ ቀን ከሌት መዶስኮሩ ሰውዬው በእርግጥም ፍሬ ያዘለ ሰብል መሆኑን ከማሳየቱ በቀር እንደሚሉት ጥላቻ በልቦናው የተሸከመ ጸረ-ሕዝብና ጸረ-ሀገር መሆኑን ፈጽሞ አይመሰክርም!!

    ― ይድረስ ለብርሀኑ ነጋ (ፕሮፌሰር) ―

    የመጨረሻ ውጤቱ፣ ጥራቱና መጠኑ ምንም ይሁን ምን፣ ዴሞክራሲን አዋልደሀል!! ጨቅላውን ዴሞክራሲ አንስቶ መሳም፣ አቅፎ ማሳደግ የኛ ድርሻ ይሆናል! ለዘመናት የተጫነብንን የዘር ፖለቲካ የምናራግፍበትን አንድ ዘዴ የሆነውን የዜጋ ተኮር ፖለቲካ አስተምረህ፣ አዋቅረህ፣ ከምርጫው ኮሮጆ አድርሰህልናል – ያለፈውን ጥፋት ላለመድገምና እንደ ቀሪው ዓለም በሀሳብ ላይ መሠረት ያደረገ ፖለቲካን መምረጥ የኛ ፋንታ ይሆናል። በብዙ መከራዎች መካከል ባለች ሀገር ውስጥ የሰከነ የተቃውሞ ፖለቲካን በማራመድ ሀገርና መንግሥት በፈለጉን ጊዜ አቤት እያልን በቀረው ደግሞ እየተቃወምንና እየተቸን መጓዝ የምንችልበትን የሰለጠን አስተሳሰብ አሳይተኸናል። ይህን መንገድ ተከትሎ ያለጩኸት እና ያለ ወከባ መንግሥት መቀያየርን መልመድ የኛ ተግባር ይሆናል።… በቀረው ደግሞ ምርጫው በሰላም ተጠናቆ ቢሆን በፓርላማው፣ ከዚያም ሲያልፍ በመንግሥት ስልጣን ላይ ሆነህ ቀሪ ህይወትህን ለዚህች ደሀ ሀገራችን የበለጠ እንድትሠራ መልካም ውጤት እመኝልሀለሁ! በቀረው ግን ውለታህ አለብን እንጂ ግዴታችን የሌለብህ ከሚጠበቅብህ በላይ ያገለገልከን ታላቅ ዜጋ ነህና እናከብርሀለን!!!

    * አቶ የትነበርክ ታደለ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚጽፍ ጋዜጠኛ ሲሆን፥ በፌስቡክ ገጹ ሊያገኙትና ጽሁፎቹን ሊከታተሉ ይችላሉ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ዶ/ር ብርሀኑ ነጋ

    Anonymous
    Inactive

    የሰሞኑ “ቃል በተግባር” የተሰኘው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ዘጋቢ /ገላጭ/ ፊልም በሁለት ኢትዮጵያውያን አተያይ
    [ቃል በተግባር ― በዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ እና በአቶ ያሬድ ኃይለማርያም አተያይ]

    • ቃል በተግባር ― ኢትዮጵያን ሀገር ሆና አየኋት
      [በድሉ ዋቅጅራ (/)]

    ኢትዮጵያን እንደሀገር ያገለገልኳት፣ ያፈቀርኳት በ1970ዎቹ መጨረሻ (1976-79) ባለው ጊዜ ነበር፤ በመጀመሪያው ዙር የብሔራዊ ውትድርና አገልግሎት ዘመኔ። ከትምህርት ቤት በግዴታ ታፍሼ የገባሁበት የብሔራዊ ውትድርና ከሀገሬ ጋር ልብ ለልብ አስተዋወቀኝ፤ አፈቀርኳት።

    ግዳጄን ፈጽሜ፣ ዩኒቨርሲቲ ተምሬ፣ በ1983 አ.ም. ወደ ሥራ ስሰማራ ኢትዮጵያን አጣኋት። በብሔር ፖለቲካ ሴራ የተካኑ፣ ስሟን መጥራ የሚዘገንናቸው መሪዎች እጅ ወድቃለች። ለጎሳና ቋንቋ ድንበር ከልላ፣ ባንዲራ [ሰንደቅ ዓላማ] ሰቅላ እሷ ፈዝዛለች።… ለብሔረሰቦችና ለቋንቋዎች እኩልነትና ለሰብዓዊ መብት መከበር ዝም ብዬ አላውቅም፤ እሟገታለሁ። ባንዲራቸው ሲከልላት፣ የምትተነፍሰው አየር ሲያጥራት፣ ኢትዮጵያን ሲረሷት ግን አዝናለሁ፤ ያመኛል።

    ከረዥም ጊዜ በኋላ በትላንትናው ዘጋቢ ፊልም ውስጥ ኢትዮጵያን ሀገር ሆና አየኋት። ዘመንን መስላ፣ ተስፋ አዝላ አነበብኳት። በሦስት ዓመት፣ ያለጥላቻና ግጭት ዜና ነግቶ በማይመሽበት ሀገር፣ ‘የእኔ ሀሳብ ካልሆነ ሀገሬ ትበተን’ በሚል ጽንፍ ረገጥ ፖለቲካዊ መርገምት ውስጥ፣ እንኳን በልዕልና መሥራት፥ በትክክል ማሰብስ ይቻላል ወይ? ያውም ይህ ሁሉ ኃላፊነት ለተጫነበት መሪ?!

    የእያንዳንዳችን አመለካከትና እይታ የሚመነጨው ከቆምንበት ቦታ ነው!

    አዎ፣ ሀገራችን የብሔር ፖለቲካው ካጣባት ደዌ አልተፈወሰችም። አዎ አሜሪካ ማእቀብ ጥላብናለች። አዎ ሱዳን ድንበራችንን ተሻግራ መሬታችንን ይዛለች። አዎ የትግራይ ወገኞቻችን በከፍተኛ ሰብዓዊ ችግር ላይ ናቸው። አዎ የኤርትራ ወታደሮች ከሀገራችን ጨርሶ አልወጡም። አዎ ሸኔና የጁንታው ርዝራዦች በሚሰነዝሩት ጥቃት አሁንም ዜጎች ህይወታቸውን እያጡ ነው። አዎ የኑሮ ውድነት ጣራ ነክቷል።… ሀገራችን ውስጥ በርካታ ችግሮች፣ በርካታ ያልተመለሱ ጥያቄዎች አሉ።

    እነዚህ ሁሉ ችግሮች እያሉ እነዚህ አስደናቂ ፕሮጀክቶች መሠራታቸው አግባብ አይደለም በማለት ሰዎች ለጥላቻቸው የሰበብ ድር ያዳውራሉ። እኔን የሚገርመኝ በዚህ ሁሉ ችግር ውስጥ መሠራት መቻላቸው ነው።

    መሠራት የነበረበት ያልተሠራ አለ። ካልተሠራው የበለጠ የተሠራው የወደፊት መንገዳችንን ያሳያል። ጠቅላይ ሚንስትሩ ከሀገሪቱ ባጀት ሳይነካ፣ የተሸለመውን የግል ገንዘብ ሳይሰስት፣ ወዳጆቹን ለምኖ በሦስት ዓመት፣ ጥላቻና ዘለፋን ቁብ ሳይል ይህንን ሠራ። ባለቤቱ ቀዳማዊ እመቤት ዝናሽ ታያቸው እንዲሁ ከሀያ በላይ ትምህርት ቤቶችን በገጠር ቀበሌዎች ገነባች። ለመሆኑ እነዚህን ሰዎች የማናደንቀው ከእነማን ጋር እያወዳደርናቸው ነው? እንኳን በሦስት ዓመት፣ በሦስት አስርታት ውስጥ የዚህን ግማሽ የሠራ መሪ ኖሮን ያውቃል?

    እንደመሪ እነሱ ይህን ሠሩ፤ ያልመለሷቸው ችግሮችም አሉ። እኛስ! እንደ ዜጋ ባለፉት ሦስት ዓመታት ምን ሠራን? እኛ እንደዜጋ ያለነው የት ነው? የሠሩት በጎ ተግባር ወይስ ያልመለሷቸው ችግሮች አካል ነን? በዋናነት የእያንዳንዳችን አመለካከትና እይታ የሚመነጨው ከቆምንበት ቦታ ነው። ሀገራችን በውስጥና ውጭ ችግር ተተብትባለች፤ ፈተና ላይ እንደሆነችም እናውቃለን። ዋናው፣ እያንዳንዳችን ማወቅ ያለብን ጉዳይ ግን ሀገራችንን የተበተባት ችግር፣ የተጋረጠባት ፈተና አካል አለመሆናችንን ነው። እና እንጠይቅ! እንደዜጋ የቆምነው የት ነው?!

    /ር በድሉ ዋቅጅራ ደራሲና ገጣሚ ሲሆኑ፥ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የሂዩማኒቲስ፤ የቋንቋዎች ጥናት የጆርናሊዝምና የኮሚኒኬሽን ኮሌጅ ውስጥ ደግሞ መምህር ናቸው። ከዚህ ቀደም ለህትመት ከበቁላቸው ሥራዎች ውስጥ የማይፃፍ ገድል፣ የራስ ምስል፣ ያልተከፈለ ስለት፣ የወይራ ስር ጸሎት፣ የማይጻፍ ገድል፣ የተስፋ ክትባት፣ እና ፍካት ናፋቂዎች የጠቀሳሉ። በተጨማሪም በብሔራዊ ቲያትር ቀርቦ በተመልካች ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትን ያገኘውደብተራውየተሰኘው የሁለት ገጸባሕርያት ቲያትር (two-handler theater) ደራሲ ናቸው።

    • ቃል በተግባር ― እያደነቅን ስጋታችንንም እንገልጻለን፤ አቧራው መሬት ላይ ያለ ግፍ፤ ሃሜቱም ሃቅ ነው
      [አቶ ያሬድ ኃይለማርያም]

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በአዲስ አበባ የሠሯቸውን እና እየሠሯቸው ያሉ ድንቅ ነገሮችን አደንቃለሁ። ለዚህ ሥራቸው ሊመሰገኑ ይገባል። ከሠሯቸው ሥራዎቹ አንዱ የሆነውን የእንጦጦ ፖርክን የመጎብኘት ዕድል ገጥሞኛል። የሚያስደምም ድንቅ ሥራ ነው።

    ከትላንት መግለጫቸውም ሁለት ነገር መረዳት ይቻላል። አንደኛው ሀገር ለማልማት ብዙ እቅድ እና ህልም እንዳላቸው ነው። ሁለተኛው ደግሞ ይህን ህልማቸውን እውን ለማድረግ አንባገነን እሰከመሆን የሚሄዱ መሆናቸውን ነው። አገሪቱ አሁን ያለችበትን ውጥንቅጥ እና አሳሳቢ ችግር፣ የተቃዋሚዎቻቸውን ቅሬታ እና በመንግሥታቸው ላይ የሚሰነዘሩ ቅሬታዎችን ‘አቧራ’ በሚል ገልጸውታል። “ሀሜት አቧራ እንጂ አሻራ መሆን አይችልም። አቧራውን ንቀን አሻራ ማኖራችንን እንቀጥላለን” የምትለዋ ንግግራቸው አለቃቸው የነበሩትን መለስን [የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን] አስታወሱኝ። ባጭሩ የመለስን የመታበይ ንግግር ነው የደገሙት። መለስ ‘ውሾቹ ይጮኻሉ፤ ግመሎቹም ጉዟቸውን ይቀጥላሉ’ ነበር ያሉት?

    ታቃዋሚዎቻቸውን ውሻ አድርገው እና ተቋውሟቸውንም እንደ ውሻ ጩኸት ቆጥረው እሳቸው ከጉዟቸው ምንም አይነት ምድራዊ ኃይል እንደማያስቆማቸው ሊያውም በፓርላማ ፎክረው ነበር። የመሠረት ድንጋይ ጥለው ያስጀመሩትን የሕዳሴ ግድብ መጨረሻ ለማየትና ሪባን ለመቁረጥ ግን አልታደሉም። ግመሎቹስ ዛሬ ወዴት አሉ? አብይም ያች በሽታ እየታየችበት ነው። ሀገሪቱ ውስጥ ያለውን ያፈጠጠ እና አሳሳቢ ችግር እንደ አቧራ መቁጠር መጥፎ መታበይ ነው። አቧራው እንዲሰክን የሚቀርቡ ምክርና ወቀሳዎችንም እንደ ሀሜት መቁጠር ሌላው አሳሳቢ የክሽፈት ምልክት ነው።

    ሕዝብ እየተራበ ነው፤ የኑሮ ውድነት ሌላ የቀውስ ምንጭ ነው፤ ያልተረጋጋ ፖለቲካም የልማት ጸር ነው፤ ጦርነትም አውዳሚ ነው፤ የመብት ጥሰቶች መበራከት የአፈና ሥርዓት መሳለጫ ነው። እነዚህ ችግሮች አቧራ አይደሉም። በእነዚህ ጉዳዮች ዙሪያ የሚቀርብብዎት ወቀሳና ነቀፌታዎች ሀሜት አይደለም። ልማቱን ግፉበት፤ መታበይዎን አቁመው ለዲሞክራሲ፣ ለሕግ የበላይነት፣ ለሰብዓዊ መብቶች እና ለፍትህ ቀናዕይ በመሆን እንደ ልማቱ አፋጣኝ መልስ ይስጡ። ካልሆነ ግን መካር እንደሌለው ንጉሥ… ይሆናሉ።

    አቶ ያሬድ ኃይለማርያም መቀመጫውን ጄኔቭ ከተማ፥ ስዊዘርላንድ ያደረገ ስብስብ ለሰብዓዊ መብቶች በኢትዮጵያ (Association for Human Rights in Ethiopia) የተባለ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ቃል በተግባር

    Anonymous
    Inactive

    5ኛው “ሀገረሰባዊ ዕውቀት ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት” ሀገራዊ ዓውደ ጥናት በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተካሄደ

    አርባ ምንጭ (አምዩ) –  የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ (አምዩ) የባህልና ቋንቋ ጥናት ኢንስቲትዩት ከኢፌዴሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 5ኛው “ሀገረሰባዊ ዕውቀት ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት” ሀገራዊ ዓውደ ጥናት ግንቦት 26 ቀን 2013 ዓ.ም. በዩኒቨርሲቲው ተካሂዷል።

    በዓውደ ጥናቱ “የአሪ ብሔረሰብ ባህላዊ የተፈጥሮ ሀብት ዕውቀት፣ እሳቤዎችና ክዋኔዎች፣” “ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴ በጋሞ ዞን ካምባ ወረዳ፣” “ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎች በጋሞ ሕዝብ፡- የኦቾሎ ደሬ ተሞክሮ” እና “ሀገር በቀል ዕውቀት ለብዝሃ ሕይወት ጥበቃ፡- የጋሞ እና ኮንሶ ጥብቅ ደኖች” የሚሉ ሀገር በቀል ዕውቀት፣ ክዋኔና እሳቤዎች ለአካባቢ ጥበቃና ለግጭት አፈታት ያላቸውን ሚና የሚዳስሱ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል። ጥናታዊ ጽሑፎቹ በዩኒቨርሲቲው የባህልና ቋንቋ ጥናት ኢንስቲትዩትና በሶሲዮሎጂና ሶሻል አንትሮፖሎጂ ትምህርት ክፍል መምህራንና ተመራማሪዎች የተሠሩ ናቸው።

    በጽሑፎቹ እንደተመለከተው ሀገር በቀል ዕውቀት፣ እሳቤዎችና ክዋኔዎች የተፈጥሮ ሀብትን በመጠበቅና በመንከባከብ እንዲሁም ግጭቶችን በመከላከልና በመፍታት ረገድ ለበርካታ ዘመናት አዎንታዊ ሚና ሲጫወቱ ቆይተዋል። ይሁን እንጂ ዘመናዊነትና ዘመናዊ የመንግሥት አስተዳደር፣ ማኅበራዊና ባህላዊ ለውጦች፣ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች፣ በፌዴራልና በአካባቢ አስተዳደር በቂ ትኩረት አለማግኘትና ሌሎችም ምክንያቶች ለሀገር በቀል እሴቶቹ አደጋ የጋረጡ ሆነዋል። ተመራማሪዎቹ በጥቆማቸው ከመንግሥት አካላት ተገቢው ትኩረትና ዕውቅና እንዲሰጠው፣ ማኅበረሰብ መር የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ እንዲጠናከር እንዲሁም የምርምር፣ የካርታና ዶኪዩሜንቴሽን ሥራዎች እንዲሠሩ ሃሣብ አቅርበዋል።

    የኢፌዴሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚንስትር ዴኤታና የዕለቱ የክብር እንግዳ ወ/ሮ ብዙነሽ መሠረት እንደገለጹት ሀገራችን ኢትዮጵያ በሕክምና፣ በግብርና፣ በግጭት አፈታት፣ በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ እና በሌሎችም በርካታ መስኮች የእምቅ ባህልና ዕውቀት ባለቤት መሆኗ ለማኅበረሰቡ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ሀገር በቀል መፍትሔዎችን ለመስጠት የሚያስችል ነው። በመሆኑም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በመቅረጽ እንዲሁም ምርምሮች እንዲካሄዱ ድጋፍ በማድረግ ሀገር በቀል ዕውቀትና ክዋኔዎች ለሀገር ጥቅም እንዲውሉ በትኩረት ይሠራል።

    ዓውደ ጥናቱ የኢፌዴሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ የክልሉና የዞኑ ባህልና ቱሪዝም ቢሮዎች እንዲሁም አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በጋራ ለመሥራት ያቀዷቸውን ሥራዎች የሚያጠናክር መሆኑን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው የሚገኝበት አርባ ምንጭ እና አካባቢው በርካታ ባህላዊ እሴቶችን ያቀፈ በመሆኑ ለዩኒቨርሲቲው የባህልና ቋንቋ ጥናት ኢንስቲትዩት ውጤታማነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት መሆኑንም ተናግረዋል።

    የዩኒቨርሲቲው የምርምርና ማኅበረሰብ አገልግሎት ም/ፕሬዝደንት ተ/ፕ በኃይሉ መርደኪዮስ በበኩላቸው ሀገር በቀል ዕውቀት ከዘመናዊ ዕውቀት ጋር ተጣምሮ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲሻገርና ለሀገር ልማት እንዲውል ለሀገር በቀል ዕውቀት ያለንን የተሳሳተ ግንዛቤ ማረም ብሎም በምርምር ማገዝ ያስፈልጋል ብለዋል።

    የዩኒቨርሲቲው የባህልና ቋንቋ ጥናት ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር ዶ/ር ሰኢድ አህመድ ኢንስቲትዩቱ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ምርምሮችን ከማካሄድ ባሻገር የሥነ-ጥበብ ዘርፍን ለማሳደግ አበረታች ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ኢንስቲትዩቱ ከዚህ ቀደም ሀገራዊ የትርጉምና የተርጓሚነት ሙያ ጉባዔ ማዘጋጀቱን አስታውሰው መሰል መድረኮች ልምድና ተሞክሮዎችን ለመቅሰም፣ ሀገራዊ መግባባትን ለመፍጠርና ሙያዊ አቅምን ለመገንባት ፋይዳ እንዳላቸውም ተናግረዋል።

    የኢፌዴሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች፣ የክልልና የዞን የሥራ ኃላፊዎች፣ የዩኒቨርሲቲው አመራሮች፣ መምህራን፣ ተመራማሪዎችና የሀገር ሽማግሌዎች በዓውደ ጥናቱ ተሳትፈዋል።

    ምንጭ፦ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት

    ሀገረሰባዊ ዕውቀት ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት ዓውደ ጥናት

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግን ማብራሪያ ጠየቀ

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በቅርቡ የተቋቋመው የአዲስ አበባ ዙሪያ የኦሮሚያ ልዩ ዞን ወረዳ ፍርድ ቤት ሥልጣን እና ተግባራት ላይ ማብራሪያ ይሰጠኝ ሲል የኢፌዴሪ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግን ጠየቀ።

    ኢዜማ ለጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በላከው ደብዳቤ፣ በተለያዩ መንግሥታዊና የግል ሚዲያዎች ‹‹የፊንፊኔ ከተማ ወረዳ ፍርድ ቤት›› በይፋ ተከፍቶ አገልግሎት መስጠት ጀመረ በማለት የተሰሩት ዘገባዎች፣ በሕገ-መንግሥቱ ለአዲስ አበባ ከተማ የተሰጠውን ራስን በራስ የማስተዳደር ሥልጣን የሚጋፋ ሆኖ አግኝቼዋለሁ ብሏል።

    የኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትዎርክ (ኦቢኤን) የአዲስ አበባ ዙሪያ የኦሮሚያ ልዩ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ኩመላ ቡላን ጠቅሶ በሰራው ዘገባ «…በፊንፊኔ ከተማ የሚኖሩ የኦሮሞ ብሄር ተወላጆችም ሕገ-መንግሥታዊ መብታችውን በመጠቀም በዚህ ፍርድ ቤት በቋንቋቸው የመዳኘትና ተደራሽ የሆነ የፍትህ አገልግሎት የማግኘት መብትም ያገኛሉ ብለዋል።» በማለት መዘገቡን ያስታወሰው ኢዜማ፣ ይህንን ዘገባ ተከትሎ አዲስ የተከፈተው ፍርድ ቤት ሥልጣንና ተግባራት ላይ የጠቅላይ ዐቃቤ ሕግን ማብራሪያ ጠይቋል።

    የኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 49 (2 እና 3) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ራሱን በራሱ የማስተዳደር ሙሉ ሥልጣን እንዳለው ተጠሪነቱም ለፌደራል መንግሥት አንደሆነ በግልጽ ደንግጓል ያለው ኢዜማ፥ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ራሱን በራሱ ያስተዳድራል ሲባል ከተማው የራሱ ሕግ አውጭ፣ ሕግ አስፈጻሚ እና ሕግ ተርጓሚ ይኖረዋል ማለት መሆኑን ጠቁሞ፤ ተጠሪነቱ ለፌደራል መንግሥት ነው ማለት ደግሞ በአዲስ አበባ ጉዳዮች ላይ የመጨረሻ የመወሰን ሥልጣን ያለው አካል የፌደራል መንግሥቱ ብቻ ነው ማለት ነው ሲል አመላክቷል።

    የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎችን ለሚገጥማቸው ማናቸውም ጉዳይ የትኛውም ብሔር ጀርባ ቢኖራቸውም የመዳኘት ሥልጣኑ የከተማ መስተዳደሩ ፍርድ ቤቶችና የፌደራል ፍርድ ቤቶች መሆኑን የጠቀሰው ኢዜማ፣ አንድ ክልል የዚህ ብሔር ተወላጆችን ነዋሪነታቸው በአዲስ አበባ ከተማ ቢሆንም የመዳኘት ሥልጣን ይኖረኛል ማለቱ በሕገ-መንግሥቱ ለፌደራል መንግሥቱ የተሰጠውን ሥልጣን የሚጋፋ፤ በአዲስ አበባ ቻርተር አዋጅ ቁጥር 87/1989 እንዲሁም እሱን ያሻሻለው አዋጅ ቁጥር 361/1995 የአዲስ አበባ አስተዳደር ራስ ገዝ ከመሆኑም ባሻገር በፌደራሉ መንግሥት የዳኝነት ፈቃደ ሥልጣን ሥር በማይወድቁ ጉዳዮች ላይ የአዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤቶች አና የቀበሌ ማኅበራዊ ፍርድ ቤቶች ብቻ ሥልጣን እንደሚኖራቸው ተብሎ የተደነገገውን በግልጽ የሚቃረን ሆኖ አግኝቼዋለሁ ብሏል።

    አሁን ለተቋቋመው ፍርድ ቤት የሕግ መሰረት ተደርጎ የተጠቀሰው የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ፍርድ ቤቶች አደረጃጀት ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን የወጣው አዋጅ ቁጥር 216/2011 በአንቀጽ 24 ላይ ከተዘረዘሩት የኦሮሚያ ፍርድ ቤቶች የተሰጣቸው ሥልጣን እና ተግባራት ላይ በአዲስ አበባ የሚኖሩ የኦሮሞ ብሔር ተወላጆችን ጉዳይ የማየት ሥልጣን እንዳላቸው ባልጠቀሰበት ሁኔታ፣ በአዲስ አበባ የሚኖሩ የኦሮሞ ብሔር ተወላጆችን ጉዳይ የማየት የዳኝነት ፈቃደ ሥልጣን የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ፍርድ ቤቶች አላቸው ተብሎ መገለጹ ኢ-ሕገ-መንግሥታዊ እና ምንም ዓይነት የሕግ መሰረት የሌለው ነው ያለው ኢዜማ፣ በአንድ ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ዜጎች የብሔር ማንነታቸው ላይ በመመስረት የተለያየ የዳኝነት መብት ይኖራቸዋል ብሎ ፍርድ ቤት መክፈት የዜጎቸን በሕግ ፊት በእኩልነት የመታየት ሰብአዊና ሕገ-መንግሥታዊ መብትን የሚጥስ ከመሆኑም ባለፈ የዜጎችን ተከባብሮ የመኖር እሴት የሚሸረሽር ነው የሚል እምነት እንዳለው ኢዜማ በደብዳቤው ገልጿል።

    በአንድ ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ዜጎች የብሔር ማንነታቸው ላይ በመመስረት የተለያየ የዳኝነት መብት ይኖራቸዋል ብሎ ፍርድ ቤት መክፈት የዜጎችን በሕግ ፊት በእኩልነት የመታየት ሰብዓዊና ሕገ-መንግሥታዊ መብትን የሚጥስ ተግባር መሆኑን የጠቀሰው ኢዜማ፣ ይህ ዓይነቱ ድርጊት የዜጎችን ተከባብሮ የመኖር ዕሴት ይሸረሽራል ብሎ እንደሚያምን ገልጿል።

    የጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ መሥሪያ ቤት በአፋጣኝ በጉዳዩ ላይ ማብራሪያውን እንዲሰጠው የጠየቀው ኢዜማ፣ ‹‹ጠቅላይ አቃቤ፣ ይህንን ከሕገ-መንግሥት ማዕቀፍ ውጪ የሆነ ኢ-ሕገ-መንግስታዊ ተግባር እንዲያስቆም ሲል ለጠቅላይ አቃቤ ሕግ በላከው ደብዳቤ ጥያቄውን አቅርቧል።

    ምንጭ፦ ኢዜማ

    ኢዜማ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግን ማብራሪያ ጠየቀ

    Anonymous
    Inactive

    ቴሌብር የሞባይል ገንዘብ አ ገልግሎት ምረቃ በተመለከተ የቀረበ ጋዜጣዊ መግለጫ ― ኢትዮቴሌኮም

    ኩባንያችን “ቴሌብር” የተሰኘ፣ ለማኅበረሰባችን ምቹ እና ሁሉን አካታች የሆነ የገንዘብ ማስተላለፊያ እና የመገበያያ ዘዴ የሆነውን፣ የሞባይል ገንዘብ አገልግሎቱን (mobile money service) ለመጀመር አስፈላጊ ዝግጅቶችን አጠናቆ ግንቦት 3 ቀን 2013 ዓ.ም አገልግሎቱ መጀመሩን ሲያበስር በታላቅ ደስታ ነው!

    በሀገራችን በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነውና በኩባንያችን የሚሰጥ የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት ከተደራሽነትና ለአጠቃቀም እጅግ ቀላል ከመሆኑ አኳያ ለማኅበረሰባችን የብስራት ዜና ሲሆን፤ ሕዝባችንን ለማገልገል ካለን ጽኑ ፍላጎት አንጻር ለኩባንያችን ትልቅ ስኬት ነው።

    የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት በሀገራችን ያለውን የፋይናንስ አካታችነት ክፍተት በማጥበብ፣ ዜጎች ባሉበት ሆነው ፈጣንና ቀላል በሆነ ዘዴ እንዲሁም በአነስተኛ የግብይት ወጪ የተሻለ የፋይናንስ አገልግሎት የሚያገኙበት ሁኔታን ያመቻቻል። የፋይናንስ አካታችነት /financial inclusion/ ሁሉንም የፋይናንስ አገልግሎቶች ለሁሉም የኅብረተሰብ ክፍሎች ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል ኢኮኖሚያዊ ፅንሰ ሀሳብ ሲሆን፤ የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት የፋይናንስ አካታችነትን ለማረጋገጥ ዓይነተኛ መፍትሔ ነው። ቴሌብር የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት ጤናማ የገንዘብ ፍሰት ከመፍጠሩም ባሻገር፥ ቁጠባን በማሳደግ፣ ድህነትን በመቀነስ፣ ሥራ ፈጣሪነትንና ኢንቨስትመንትን በማበረታታት እንዲሁም ገንዘብ የሚታተምበትን ወጪ በመቀነስና ኢኮኖሚን በማሳደግ የሕዝባችንን ሁለንተናዊ እድገትና ተጠቃሚነትን ያሳድጋል።

    ኩባንያችን ለቴሌኮም አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ መዋዕለ-ንዋይ በማፍሰስ የዘረጋውን መጠነ ሰፊ መሠረተ ልማት በመጠቀም ወደ ደንበኞቹ ቅርብ ከመሆኑ አኳያ ለኅብረተሰባችን ተጨማሪ እና ከፍተኛ አዎንታዊ ተጽዕኖ የሚፈጥር አገልግሎት ማስጀመሩ በሀገራችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት እንዲሁም ለኅብረተሰባችን የዕለት ተዕለት ኑሮ መሻሻል ጉልህ አስተዋጽዖ ይኖረዋል።

    ኩባንያችን የሞባይል ገንዘብ አገልግሎትና ተያያዥ የዲጅታል ፋይናንስ አገልግሎቶችን ለውድ ደንበኞቹና ለሁሉም ማኅበረሰብ ለማቅረብ የፍቃድ ጥያቄውን ካቀረበበት ወቅት ጀምሮ ሰፊ የዝግጅት ሥራዎችን ያከናወነ ሲሆን፤ በተለይም በኢንዱስትሪው የተመረጠና የተሻለ የሞባይል ገንዘብ ቴክኖሎጂን ሥራ ላይ ለማዋል፣ ተገቢ ፖሊሲዎችን እና አሠራሮችን ለመተግበር፣ ሰፊውን ወኪል ኔትወርክ (ngent network) ለማንቀሳቀስ እና ከቴሌኮም እና ከፋይናንስ ኢንዱስትሪዎች የተሻሉ ልምዶችን በመቀመር በቂ ዝግጅት በማድረግ በዋናነት የባንክ አገልግሎት ማግኘት ያልቻሉ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ዜጎችና በገጠር የሚገኙ ዜጎችን የፋይናንስ አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ ሰፊ ጥረቶችን በማድረግ ለዛሬው ስኬት በቅቷል።

    አገልግሎቱን ለማኅበረሰባችን በማቅረብ ሂደት ውስጥ በርካታ ተቋማት የሚሳተፉ ሲሆን፤ በተለይም በሀገራችን ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ሁሉም የፋይናንስ እና የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት፣ ዓለም አቀፍ ገንዘብ አስተላላፊ ድርጅቶች እንዲሁም አገልግሎቱን ለደንበኞቻችን ቅርብ ለማድረግ የሚያስችሉ ከኩባንያችን ጋር ልዩ ውል ያላቸው ዋና ወኪሎች /master agents/ እና በእነዚህ ዋና ወኪሎች የተመለመሉ እስካሁን ባለው ከ1,600 በላይ ወኪሎች /agents/ ዋነኛ ተሳታፊዎች ናቸው። የአገልግሎት ተደራሽነቱን ለማረጋገጥ የወኪሎችን ቁጥር በየወሩ በማሳደግ በአንድ ዓመት ውስጥ ከ15ሺህ በላይ ለማድረስ እየተሠራ ይገኛል።

    ቴሌብርን በመጠቀም ገንዘብ ከማስተላለፍ፣ ከመቀበልና ከመክፈል በተጨማሪ ግብይት ለመፈጸም የሚያስችል ሁኔታ ለመፍጠር ከተለያዩ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት ጋር አብረን እየሠራን ሲሆን፤ ለአብነት ያህል ውሀና ፍሳሽ፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት፣ ገቢዎች፣ ሱፐር ማርኬቶች፣ ነዳጅ ማደያዎች፣ እርዳታ ድርጅቶች፣ ካፌዎችና ሬስቶራንቶች፣ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጭ ተቋማት፣ የህትመት ሚዲያዎች እና ሌሎችም አገልግሎት ሰጪ ተቋማት የሚገኙበት ሲሆን አገልግሎቱ ክፍያ መቀበልና መፈጸም ያስችላቸዋል።

    ከዚህ በተጨማሪም ደንበኞቻችን ከውጭ ሀገር የሚላክላቸውን ገንዘብ ቴሌብር የሞባይል ገንዘብ አገልግሎትን በመጠቀም በቀላሉና በአነስተኛ ወጪ ለመቀበል የሚያስችላቸው አገልግሎት ለማስጀመር ከዓለም አቀፍ ገንዘብ አስተላላፊ ድርጅቶች ጋር የኢንቴግሬሽን ሥራ እየተከናወነ ሲሆን፤ ኩባንያችን የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት ፈቃድ ካገኘ አጭር ጊዜ ከመሆኑ አኳያ ከድርጅቶቹ ጋር ያሉ ሂደቶችና ፎርማሊቲዎችን አጠናቆ ከጥቂት ሳምንታት በኋላ አገልግሎቱን መስጠት ይጀምራል።

    በቀጣይም ቴሌብር የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት ለማኅበረሰባችን ሁለንተናዊ ለውጥና መሻሻል ከፍተኛ ሚና ያላቸው እንዲሁም የፋይናንስ አገልግሎት ከማግኘት ባሻገር ትርጉም ያለው ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ሊያመጡ የሚችሉ የሞባይል አነስተኛ ብድር፣ የቁጠባ አገልግሎትና ተያያዥ የዲጅታል ፋይናንስ አገልግሎቶችን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበርና አስፈላጊ ቅደመ ሁኔታዎችን በማሟላት የሚያስጀምር ይሆናል።

    የቴሌብር አገልግሎት በሀገራችን የፋይናንስ አገልግሎት ላይ የሚታየውን ውስንነት ወይም የፋይናንስ አካታችነት ክፍተት በማጥበብ ሰፊ ሚና የሚጫወት ሲሆን አሁን ላይ 35% ብቻ የሆነውን የፋይናንስ አካታችነት ወደ 60% ለማሳደግ ግብ አስቀምጠን እየሠራን ሲሆን በተለይም ከኮቪድ-19 ጋር በተገናኘ የገንዘብ ንክኪን ለመቀነስ የቴሌብር አገልግሎት ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል።

    ቴሌብር የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት ዘርፈ ብዙ ትሩፋቶች ያሉት አገልግሎት ሲሆን በተለይም የሀገራችንን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት ላይ ጉልህ ሚና ለመጫወት በዘርፉ ላይ ድርሻና ሚና ያላቸውን አካላት በማሳተፍ ተቀናጅቶ በመሥራት በቀጣይ አምስት ዓመታት ውስጥ ከ40% እስከ 50% ያህሉን ጠቅላላ የሀገራችን የኢኮኖሚ ግብይትና የገንዘብ ፍሰት በቴሌብር እንዲከናወን አቅደን እየሠራን እንገኛለን።

    በዚህ አጋጣሚ ቴሌብር የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት የበለጠ ፍሬ እንዲያፈራና የሀገራችንን የዲጅታል ፋይናንስ ፍላጎት ለማሟላት እና ዲጅታል ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚደረገውን ሀገራዊ ጥረት ከግብ ለማድረስ በኢኮሲስተሙ ሚና ያላቸው ባለድርሻ አካላት በተለይም የፋይናንስ ተቋማት፣ የንግድ ድርጅቶችና አገልግሎት ሰጭ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆናችሁ ተቋማት አብራችሁን እንድትሠሩ ጥሪያችንን በአክብሮት እናቀርባለን።

    ኢትዮቴሌኮም

    ቴሌብር

    Anonymous
    Inactive

    ሚያዝያ 11 ቀን፥ 2013 ዓ.ም.
    አቶ ልደቱ አያሌው
    ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን
    አዲስ አበባ

    ጉዳዩ:- በድጋሚ አቤቱታ ማቅረብን ይመለከታል

    በቅድሚያ በእኔ በአመልካቹ ላይ በተደጋጋሚ እየደረሰ የሚገኘውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት መፍትሄ እንዲያገኝ መሥሪያ ቤታችሁ እያደረገ ስላለው ያልተቋረጠ ጥረት ልባዊ ምስጋናየን አቀርባለሁ። ሆኖም በእኔ ላይ እየተፈፀመ የሚገኘው የሰብዓዊ መብት ጥሰት አሁንም ያልተቋረጠና ለሕይወቴ አስጊ በሆነ ደረጃ ተጠናክሮ የቀጠለ በመሆኑ፥ ይሄንን አቤቱታ በድጋሚ ለማቅረብ ተገድጃለሁ።

    የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በሀገሪቱ የተፈጠረውን የፖለቲካ ቀውስ ሰበብ በማድረግ በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንድውል ከተደረገበት ከሐምሌ 17 ቀን፥ 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በሀገሪቱ ሕግና የሕግ የበላይነት የለም ሊያስብል በሚባል ደረጃ በርካታና ተከታታይ የሰብዓዊ መብት መብት ጥሰት በእኔ ላይ እየተፈፀመ ይገኛል። ለማስታወስ ያህል…

    1. ሕጋዊ ነዋሪነቴ ተመዝግቦ የሚገኘው በአዲስ አበባ ከተማ ሆኖ እያለ፥ እንድታሰር የተደረገው ግን ያለ አግባብ በኦሮሚያ ክልል ነው።
    2. በስልክ ተጠርቼና ለፌደራሉ ፖሊስ ኮሚሽን በእራሴ ፈቃድ እጄን ሰጥቼ በቁጥጥር ስር ከዋልኩ በኋላም በሕጉ መሠረት በ48 ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት እንድቀርብ አልተደረገም።
    3. በቁጥጥር ስር ከዋልኩ በኋላ ያለምንም ፍርድ ቤት ትዕዛዝ በስልክና በኢንተርኔት አማካይነት ያደረኳቸው የግል የመልዕክት ልውውጦች በሕገ-ወጥ መንገድ እንዲበረበሩና በሲዲ እንዲቀዱ ተደርገዋል። የግል ማስታወሻወቼና ረቂቅ የፅሁፍ ሰነዶቸ ሳይቀሩ በፖሊስ ተወስደዋል።
    4. በቁጥጥር ውስጥ ውዬ ገና ክስ እንኳ ባልተመሠረተብኝ ወቅት የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኛ ነን የሚሉ ሰዎች ወንጀለኛ እንደሆንኩ አድርገው ሰፊ የስም ማጥፋት ዘመቻ እንዲያካሂዱብኝ ተደርጓል።
    5. በምርመራ ወቅትና የምርመራ ፋይሌ ከተዘጋ በኋላም የዋስ መብት ተከልክዬና ክስ ሳይመሠረትብኝ በጊዜ ቀጠሮ ሰበብ ከሁለት ወራት በላይ ለሆነ ጊዜ በሕገ-ወጥ መንገድ በእስር ቤት እንድቆይ ተደርጓል።
    6. በፍርድ ሂደቱ ወቅት በግልፅ እንደታየው፥ በቢሾፍቱ ከተማ አመፅ አስነስተሀል፤ ሕገ-ወጥ መሣሪያ ታጥቀህ ተገኝተሀል፤ መንግሥትን በሕገ-ወጥ መንገድ አፍርሰሀል የሚሉ የፈጠራ ክሶች እንዲቀርቡብኝ ተደርጓል።
    7. “መንግሥትን በሕገ-ወጥ መንገድ አፍርሰሀል” በሚል የተከሰስኩበት ወንጀል አዲስ አበባ በሚገኝ የፌደራሉ ፍርድ ቤት መታየት ሲገባው ያለ አግባብ በአዳማ ከተማ የሚገኘው የኦሮሚያ ክልል ጥቅላይ ፍርድ ቤት በውክልና እንዲያየው ተደርጓል። ይህም መሆኑ የፍርድ ሂደቱ በማልናገረው ቋንቋ እንዲካሄድና ብዙ ውጣ ውረድ እንዲደርስብኝ አድርጓል።
    8. በፍርድ ሂደቱ ወቅት ለሁለት ጊዜ ያህል የዋስ መብት በፍርድ ቤት ቢፈቀድልኝም ፖሊስ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ በመጣስ ለሁለት ወራት ያህል በእስር አቆይቶኛል። ከዋስትና መብቴ ጋር በተያያዘም ፍርድ ቤት ለአምስት ጊዜ የሰጣቸው የተለያዩ ትዕዛዞች በፖሊስ እምቢተኝነት ሳይፈፀሙ ቀርተዋል።
    9. ለሕይወት አስጊ የሆነ ከፍተኛ የልብ ህመም ያለብኝ ሰው መሆኔ እየታወቀም የኮቪድ ወረረሽኝ ተጠቂ ከሆኑ ሰዎች ጋር በአንድ ጠባብ ግቢ ውስጥ ታስሬ ለረጅም ጊዜ እንድቆይ ተደርጓል።
    10. ከአምስት ወራት መታሰር በኋላ የዋስ መብቴ ተጠብቆ ከተፈታሁ ከጥቂት ቀናት በኋላም እኔንና የትግል ጓደኞቼን ከሀገሪቱ የፖለቲካ ሂደት ለማግለል ሲባል አባል የሆንኩበት የፖለቲካ ፓርቲ በሕገ-ወጥ መንገድ እንዲሰረዝና ህልውናውን እንዲያጣ ተደርጓል።
    11. ከእስር ቤት ወጥቸ አስቸኳይ የቀዶ ጥገና የሕክምና እርዳታ ለማግኘት ወደ ውጭ ሀገር ለመጓዝ ለሁለት ጊዜ ያደረኩት ሙከራም ምንም አይነት የፍርድ ቤት እገዳ ባልተጣለብኝና እንዲያውም ጉዳዩን ይመለከት የነበረው ፍርድ ቤት ወደ ውጭ ሀገር ሄጀ የመታከሜን አስፈላጊነት በማመን ረዥም ቀጠሮ ሰጥቶኝ እያለ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት መሥሪያ ቤት በሕግ ባልተሰጠው ሥልጣን ባደረገብኝ ሕገ-ወጥ ክልከላ ምክንያት ከሀገር የመውጣት ሕገ- መንግሥታዊ መብቴ ተጥሷል።
    12. ይህ የተጣለብኝ ሕገ-ወጥ እገዳ እንዲነሳልኝ ለማድረግ የተለያዩ ጉዳዩ የሚመለከታቸውን የመንግሥት ባለ ስልጣናት ቀጠሮ ይዤ ለማነጋገር በተደጋጋሚ ብሞክርም ባለስልጣናቱ ሊያናግሩኝ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው ሙከራዬ ሳይሳካ ቀርቷል።
    13. መሥሪያ ቤታችሁ ባደረገው ጥረት ምክንያት የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት መሥሪያ ቤት በእኔ ላይ ምንም ዓይነት የጉዞ ክልከላ እንዳላደረገ የሚክድ ደብዳቤ ለመሥሪያ ቤታችሁ ከፃፈ በኋላም ለሦስተኛ ጊዜ ከሀገር ለመውጣት ያደረኩት ሙከራ የኢሚግሬሽን ዜግነትና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ ክልከላ ስላደረገብኝ ጉዞዬ ሳይሳካ ቀርቷል። የጉዞ ፓስፖርቴም በመሥሪያ ቤቱ ባልደረቦቼ ተወስዶብኛል።
    14. የኢሚግሬሽን መሥሪያ ቤት ለምን የጉዞ ክልከላ እንዳደረገብኝና እንደቀማኝ በማግስቱ ዋናው መሥሪያ ቤት ድረስ ሄጄ ለመጠየቅ ባደረኩት ሙከራ የፌዴራሉ ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ክፍል ባቀረበው ጥያቄ መሠረት በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውዬ ምርመራ እስከሚካሄድብኝ ድረስ የፌደራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የአራዳ ምድብ አንደኛ ችሎት የካቲት 4 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. በዋለው ችሎት ወደ ውጭ እንዳልጓዝ እገዳ የጣለብኝ ስለመሆኑ ተነግሮኛል።

    ከእነዚህ ከዚህ በላይ ከተዘረዘሩት ተደጋጋሚ የመብት ጥሰቶች በግልፅ መረዳት እንደሚቻለውና በእኔ በኩል እንደምገነዘበውም መንግሥት በእኔ ላይ ይህን ሁሉ የመብት ጥሰት እየፈፀመ የሚገኘው የፈፀምኩት ወንጀል ስላለ ሳይሆን መብቴን በሕገ-ወጥ መንገድ በመጣስና በመገደብ ከፖለቲካ ተሳትፎ ውጭ እንድሆን ስለፈለገ ነው።

    እኔ አመልካቹ የአለፈ ታሪኬ እንደሚያሳየው ለሃያ ስምንት ዓመታት በሀገሪቱ ፖለቲካ በነበረኝ ተሳትፎ ስድስት ጊዜ በሕገ-ወጥ መንገድ በፈጠራ ክስ የታሰርኩ ቢሆንም አንድም ጊዜ በወንጀለኝነት ተፈርዶብኝ አያውቅም። የኢትዮጵያ ህዝብ በግልፅ እንደሚያውቀው በዚህ የረጅም ጊዜ የፖለቲካ ተሳትፎዬ ስታገል የኖርኩት በሀገሪቱ ዘላቂ ሰላም፣ እርቅና የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን ሲሆን፤ በአንፃሩም ሕገ-ወጥነትን፣ አመጽንና የኃይል አማራጭን በግልፅና በድፍረት በማውገዝ የምታወቅ ሰላማዊ የፖለቲካ ሰው ነኝ። ሆኖም መንግሥት ከላይ በተገለፀው ሁኔታ በፈጠረብኝ ተከታታይ ሕገ-ወጥ ጫና ምክንያት በአሁኑ ወቅት ከፖለቲካ ተሳትፎዬ ሙሉ በሙሉ ለመገለል የተገደድኩ ሲሆን ከዚያም በላይ ያለብኝን ከፍተኛ የልብ ህመም ወደ ውጭ ሀገር ሄጀ መታከም ባለመቻሌ ምክንያት በህይወት የመኖር ዕድሌ ከፍተኛ አደጋ ላይ ወድቋል። በአጠቃላይም እየደረሰብኝ ባለው ተደጋጋሚ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ምክንያት ለከፍተኛ የጤና መታወክ፣ የሞራል ውድቀት፣ የገንዘብና የጊዜ ብክነት ተዳርጊያለው።

    ይህ ሁሉ በተደጋጋሚ የተፈጸመብኝ በደል አልበቃ ብሎም እኔ አመልካቹ ፈጽሞ ባልተነገረኝና በማላውቀው ሁኔታ፣ ምንም ዓይነት ጥያቄ ባልቀረበልኝና ምርመራ ባልተካሄደበት ሁኔታ፣ ከዚያም በላይ ተፈልጌ የጠፋሁ ወንጀለኛ የሆንኩ በሚያስመስል ሁኔታ የጉዞ እገዳ የተጣለብኝ ስለመሆኑ የአራዳ ፍርድ ቤት ሰጠ የተባለው ትዕዛዝ አሁንም በእኔ ላይ የፈጠራ ክስ እንደገና በመመሥረት እንድታሰርና ሕይወቴ አደጋ ውስጥ እንዲወድቅ እየታሰበና ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ነው።

    በአንድ ሰው የደረሰ የሰብዓዊ መብት ጥሰት በሁሉም ሰው ላይ እንደደረሰ ጥሰት የሚቆጠር መሆኑን ታሳቢ በማድረግና በእኔ ላይ እየተፈፀመ ያለው ተደጋጋሚ መቋጫ ያጣ የሰብዓዊ መብት ጥሰትም የፖለቲካና ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ ሕገ-መንግሥታዊ መብቴን ከመጣስም በላይ በሕይወት ለመኖር ያለኝን የማይገሰስ ሰብዓዊ መብቴን አደጋ ላይ የጣለ መሆኑን ግምት ውስጥ በማስገባት፥ መሥሪያ ቤታችሁ በጉዳዩ ልዩ ትኩረት በመስጠት ምርመራ እንዲያካሂድልኝና አስቸኳይ መፍትሔ እንዳገኝ እንዲያግዘኝ በድጋሚ በአክብሮት እጠይቃለሁ።

    ከሰላምታ ጋር!
    ልደቱ አያሌው

    ግልባጭ፦
    ለመገናኛ ብዙሀን

    አቶ ልደቱ አያሌው ለኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የጻፉት ደብዳቤ

    Anonymous
    Inactive

    ሕዝባችን ከመቼውም ጊዜ በላይ የተጋረጠበትን መንግሥታዊ ሽብር በተደራጀ አግባብ እንዲከላከል ጥሪ እናቀርባለን!
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)

    ድርጅታችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) በአንድ በኩል በሕዝባችን ላይ ለበርካታ አስርተ ዓመታት የቀጠለውን ሕግና መዋቅር ሠራሽ የፖለቲካ ሸፍጥ በዘላቂነት ለመቅረፍ፣ በሌላ በኩል ሕዝባችንና ሀገራችን ከተጋረጠባቸው የኅልውና አደጋዎች ለመታደግ በሚደረገው ሀገራዊ የበጎ ኃይሎች ጥምረት አካል በመሆንና በትጋት በመሥራት ላይ የሚገኝ መሆኑን በሀቅ የሚፈርድ ሁሉ የሚረዳው እውነታ ነው።

    ምንም እንኳን ትጋታችን ለማንም አካል በመታያነት የቀረበ ባይሆንም፥ እጅግ ፈታኝ በሆኑ ሁኔታዎች ውስጥ እንኳ ሆነን “የተሻለ ነገ” ሊመጣ ይችላል የሚል እሳቤን አንግበን እዚህ ደርሰናል።

    ቀደም ሲል በተደጋጋሚ ለመንግሥት እንዳሳሰብነው መሠረታዊ የሆኑ የለውጥ ሀሳቦችን መሬት ለማስረገጥና የተሳሳተውን የማደራጃ ትርክት፣ የተዛነፈውን መዋቅራዊና ሥርዓታዊ ማእቀፍ በማስተካከል ሕዝብን ለዘላቂ ሰላምና ሥልጣን ለማብቃት የበኩላችንን ያልተቋረጠ ጥረት ከማድረግ ጎን ለጎን በተለይ ሀገራችንና ማዕከላዊ ሥርዓቱ እንዳይፈርሱ ለማድረግ በተደረጉ ጥረቶች ሁሉ አብንና የአማራ ሕዝብ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል።

    ሆኖም፦

    1/ መንግሥታዊ ሽብሩን በማባባስ፣ በመደገፍ እና ትእዛዝ በመስጠት ጭምር የሚሳተፉት የሀገራችን ጠቅላይ ሚንስቴርና የሚመሩት የኦሮሞ ብልጽግና ክፍል መንግሥታዊ መዋቅርንና የሀገር ሀብትን በመጠቀም የአማራን ሕዝብ የማሸበር ተግባር አጠናክረው ቀጥለዋል። ሕዝባችንን ለማሸበር የተከፈተው መጠነ-ሰፊ የዘር ፍጅት በመንግሥት መዋቅር በቀጥታ የሚደገፍና የሚመራ መሆኑን አብን ያምናል። ለዚህም የሚከተሉትን ነጥቦች በጉልህ ማሳያነት ማቅረብ ይቻላል።

    ሀ/ በአማራ ሕዝብ ላይ የተቀናጁ የጅምላ ፍጅት ጥቃቶችን የከፈተው በተለምዶ “ኦነግ ሸኔ” ተብሎ በጠቅላይ ሚንስትሩ የሚጠራው አካል ከመነሻው ከነትጥቁ ወደ ሀገር ቤት የገባበትን አሻጥር፤

    ለ/ ከዚያ ቀደም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጭምር እንደገለጹት ከተጠቀሰው ድርጅት ጋር የነበራቸው መረጃን የመለዋወጥ ድብቅ ግንኙነት የሚታወቅ በመሆኑ ከልጅነት እስከ እውቀት አጋር የሆናቸውን ድርጅት አሁንም በልዩ ስልት የማደራጀት፣ የመደገፍ እና የመንከባከብ ሚናቸውን እየተጫወቱ እንደሆነ ንቅናቄያችን በጽኑ ያምናል።

    ሐ/ የ“ኦነግ ሸኔ” ኮር ስትራቴጂክ አመራር በመሀል አዲስ አበባ ውስጥ ተቀምጦ እየመራ ባንኮችን ጭምር በጠራራ ፀሐይ በመዝረፍ ኃይል እንዲያጎለብት የተፈቀደበትና የተመቻቸበት አግባብ መኖሩ፤

    መ/ በአማራ ሕዝብ ላይ እየተፈፀመ ያለውን ተደጋጋሚ የዘር ጥቃት ማስቆም ይቅርና ጅምላ ፍጅቱ በሀገር ደረጃ ለሀዘን መግለጫ እንኳ እንዳይበቃ የተደረገ ከመሆኑም በላይ በሀዘን ድንኳናችን ላይ ቀይ ምንጣፍ አንጥፈው ሕንፃ እና አበባ የሚመርቁበት አስደንጋጭ ማኅበራዊ ስላቅ ሳይቋረጥ መቀጠሉ፤

    ሠ/ በአማራ ሕዝብ ላይ የተከፈተው ዘር-ተኮር ጥቃት የታቀደና የተቀናጀ ሲሆን፥ የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ጭምር የዘር ማጥፍት ወንጀል ለማስፈጸም አመላካች የሆኑ የመግቢያ ንግግሮችን በይፋ ሲያሰሙ መቆይታቸውና ለዚህም ምንም ዓይነት አስተዳደራዊም ይሁን ፖለቲካዊ እርምት አለመሰጠቱ፤

    ጠቅላይ ሚንስትሩና የሚመሩት መንግሥት በዚህ የአማራን ሕዝብ የማሸበርና የዘር ፍጅት እንቅስቃሴ ውስጥ ሚና አላቸው ብሎ ንቅናቄያችን ለማመን ተገዷል።

    2/ የአማራ ክልል መንግሥት ከተፈጥሯዊውና መደበኛው የታዛዥነት መንፈስ አለመውጣቱ፣ ደንታ ቢስነቱና አቅመ ቢስነቱም እየበረቱበት መሆኑ ሕዝባችንን አቻ ለማይገኝለት ማኅበራዊ ውርደት ያበቃ በመሆኑ፤

    አብን የአማራ ሕዝብ ትግል ከተለመደው አካሄድ ተላቆ ኅልውናውን የመታደግና የማስከበር የተቀናጀና የተጠናከረ የትግል ምእራፍ ውስጥ መግባት አለበት የሚል ድምዳሜ ደርሷል። ትግሉንም ለመምራት ንቅናቄያችን ከፊት ይሰለፋል።

    መላው የአማራ ሕዝብም የተከፈተበትን አጠቃላይ የኅልውና አደጋ በመገንዘብ እና ለደኅንነቱ የሚያስብለት መንግሥት እንደሌለው በመረዳት ራሱን የመከላከል ተፈጥሯዊ መብቱን እንዲሠራበት አብን በአጽንዖት ያሳስባል። ሕዝባችንም በዚህ ፈታኝ ወቅትም ወዳጅ መስለው በጠላትነት በቆሙ ቡድኖችና ግለሰቦች ግፊት ፈተና ላይ እንዲወድቅ የሚፈለገውን አንድነቱን አጠናክሮ እንዲጠብቅ እናሳስባለን።

    በሀገር ውስጥም ይሁን በውጭ ሀገራት የምትገኙ ወገን ወዳድ ኢትዮጵያውያን፥ በመሠረቱ ያንዣበበው አደጋ በአማራ ሕዝብ ላይ ብቻ ተወስኖ የሚቆም አለመሆኑን በመገንዘብ በአማራ ሕዝብ ላይ በተቀናጀ ሁኔታ እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት ጥቃት እንድታወግዙና የመልሶ ማቋቋም ሥራዎችን እንድታግዙ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

    በተለያዩ ስምሪቶች በቅንነት ሀገራችሁን የደገፋችሁ መስሏችሁ ለሥርዓቱ እገዛ የምታደርጉ ወገኖች ሂደቱን በመገምገም ጥያቄ እንድታነሱና ከተገፉ ወገኖች ጎን እንደትሰለፉ ጥሪ እናቀርባለን።

    በሀገር ውስጥም ይሁን በውጭ ሀገራት የምትኖሩ የአማራ ተወላጆች በእያንዳንዱ ቀን የአማራ ሕዝብ ደም እንደጅረት የሚፈስበት ሀገር መሆኑን በመረዳት፥ አማራው ለአጠቃላይ የኅልውና አደጋ የተጋለጠ መሆኑን በመቀበልና መሠረተ-ቢስና መናኛ ከሆኑና የሞራልና የታሪክ ተጠያቂነት ከሚያስከትሉ ልማዳዊ የፖለቲካ ዘይቤዎች በአስቸኳይ በመላቀቅ ሰብዓዊ፣ ወገናዊና ሀቀኛ የሆነ የፖለቲካ አቋም በመውሰድ ሕዝብ የመታደግ ድርሻችሁን እንድትወጡ የሚል ታሪካዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

    ኅልውናችንን በትግላችን እናስከበራለን!
    እጣፋንታችንን በራሳችን እጆች እንጽፋለን!
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)

    የፖለቲካ ፓርቲዎች ድምጽ (ኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች)

    ሕዝባችን ከመቼውም ጊዜ በላይ የተጋረጠበትን መንግሥታዊ ሽብር በተደራጀ አግባብ እንዲከላከል ጥሪ እናቀርባለን

    Anonymous
    Inactive

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ) ማኒፌስቶውን ይፋ አደረገ

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ) የምርጫ ማኒፌስቶ ይፋ ማድረጊያ መርሀ ግብር
    የፓርቲው ሊቀመንበር ዶ/ር አብዱልቃድር አደም ያስተላለፉትን መልእክት ሙሉ ቃል

    የተከበራችሁ የነጻነትና እኩልነት ፓርቲ አባላት እና አመራሮች፣
    የተከበራችሁ ጥሪ የተደረገላችሁ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች፣
    የተወደዳችሁ የሚዲያ ተቋማት ተወካዮች፣

    ክቡራት እና ክቡራን፥

    ሀገራችን ኢትዮጵያ እጅግ ፈታኝ እና አስጨናቂ በሆነ የታሪክ ምዕራፍ ውስጥ በማለፍ ላይ ትገኛለች። ያልተቋጨው የሀገር ግንባታ ፕሮጀክት የወለዳቸው ታላላቅ ተቃርኖዎች፣ ለግማሽ ምዕተ-ዓመት በሀገራችን የናኘው የግራ ፖለቲካ፣ በሥርዓት ያልተመራው የሪፎርም ሂደት ስር ከሰደደው ድህነት ጋር ተደርቦ የሕዝባችንን ህይወት በሰቆቃ እና በስጋት የተሞላ አድርጎታል።

    ሀገራችን በዘርፈ ብዙ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና አስተዳደራዊ ችግሮች ውስጥ ተዘፍቃ በርካታ ዘመን አልፏል። የሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች መጨፍለቅ፣ ሙስና እና አድልዎ፣ የፍትህ መዛባት፣ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ የማኅበራዊ አገልግሎቶች መጓደል፣ ሥራ-አጥነት፣ የግጭቶች መበራከት፣ የሰላምና መረጋጋት መጥፋት የሀገራችን መለያ ምልክቶች ሆነዋል። በታሪክ የወረስናቸው ዜጎችን “አንደኛ እና ሁለተኛ” አድርገው የከፈሉ ግልጽ እና ስውር መንግሥታዊ አሰራሮች እና ልማዶች፤ ነጻነት፣ እኩልነት እና ፍትህ የሰፈነበት የመንግሥት ሥርዓት የመመስረት ሀገራዊ ትልማችን እውን እንዳይሆን እንቅፋት ሆነው ቆይተዋል።

    ለበርካታ ኢትዮጵያውያን የእለት ጉርስ የዓመት ልብስ ማግኘት የቀን ህልም ነው። የንጹህ የመጠጥ ውሀ፣ ዳቦ፣ መብራት እና ትራንስፖርት የመሳሰሉ መሠረታዊ አገልግሎቶች ለአብዛኛው የሀገራችን ሕዝብ እንደ ሰማይ የራቁ ናቸው። ሕዝባችን ይህ ሳያንሰው ከቤት በሰላም ወጥቶ መመለስ እጅግ አሳሳቢ ሆኖበታል። በሀገራችን ዜጎች ሀሳባቸውን በነጻነት መግለጽ ብዙ ዋጋ የሚያስከፍል ሆኖ የቆየ ሲሆን፣ ሰፊው የማኅበረሰብ ክፍል ሀሳቡን በነጻነት የመግለጽ መብቱ ተገፎ በርካታ ትውልድ አልፏል።

    መላ የሀገራችን ሕዝቦች ሰላም እና መረጋጋትን የሚያረጋግጥ የፖለቲካ ሥርዓት፣ የዜጎችን ሰብአዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብቶች የሚያስከብር ሕገ-መንግሥታዊ ዋስትና፣ ከአስከፊ ድህነት እና የኑሮ ውድነት የሚያላቅቅ፣ ለዜጎች በተለይም ለወጣቶች በቂ የሥራ ዕድል የሚያስገኝ የኢኮኖሚ ፖሊሲ፣ ዜጎች ራስን በራስ የማስተዳደር መብታቸውን በተግባር የሚያረጋግጥ ጠንካራ እና እውነተኛ የፌደራል ሥርዓት፣ ከጎረቤት ሀገራት እና ከመላው የዓለም ሕዝቦች ጋር ሰላም እና የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ፣ ሕግ እና ሥርዓትን የሚያስከብር፣ በዜጎች ላይ የሚደርስን ጥቃት መመከት የሚችሉ የመከላከያ እና የደህንነት ተቋማት ይሻሉ።

    ዘርፈ ብዙ ታሪካዊ እና ወቅታዊ ችግሮቻችንን አስወግደን ነጻነት፣ እኩልነት፣ ፍትህ፣ ልማት ለማረጋገጥ እና ኅብረ-ብሔራዊ አንድነታችንን ለማጠናከር በሕዝብ የተመረጠ፣ ሕዝብን የሚያገለግል እና ለሕዝብ ተጠያቂ የሆነ መንግሥት ያስፈልጋል።

    የተከበራችሁ ተሳታፊዎች፥

    በሀገራችን ታሪክ ነጻ እና ፍትሀዊ ምርጫ ተካሂዶ አያውቅም – በፍጹም። ባለፉት 25 ዓመታት የተካሄዱት ምርጫዎች ለዚህ ጥሩ ማሳያ ናቸው። የምርጫ ሂደት እና ውጤት ኢዴሞክራሲያዊ የነበሩ፣ የዜጎችን ነጻነት እና የስልጣን ባለቤትነት በግልጽ የካዱና ያዋረዱ፣ አማራጭ ሀሳቦች እንዳይሰሙ የታፈኑበት፣ በግጭት የተሞሉና በርካታ ንጹሀን ዜጎችን ለሞት እና ለአካል ጉዳት የዳረጉ ነበሩ።

    ጠንካራ እና ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዳይፈጠሩ ተቋማዊ እና መዋቅራዊ መሰናክሎችን በመፍጠር እውነተኛ የመድብለ-ፓርቲ ሥርዓት እንዳይፈጠር ተደርጓል። በሀገራችን የተካሄዱ ምርጫዎች በሙሉ አንድ ፓርቲ ከራሱ ጋር ተወዳድሮ የሚያሸንፍበት፣ ከውጭ ኃይላት ድጋፍ ለማግኘት ሲባል የሚካሄድ ትርኢት ነበር።

    6ኛው ሀገር አቅፍ ምርጫ የሚካሄደው በዚህ መራር ታሪካዊ ሀቅ ውስጥ ሆነን ነው።

    የመምረጥ እና መመረጥ መብት ከዴሞክራሲያዊ መብቶች አንዱ እና ዋነኛው ነው። ቀደምት ኢትዮጵያውያን ይህንን መብት ለማግኘት ከፍተኛ መስዋእትነት ከፍለዋል። ከሕዝባችን የዴሞክራሲ ፍላጎት በተቃራኒ የቆሙ ገዥ መደቦች ዜጎች የመምረጥ እና የመመረጥ መብታቸውን በነጻነት እንዳይጠቀሙ ሰፊ የአፈና መዋቅር አደራጅተው መብቱን ነፍገውት ቆይተዋል።

    ባለፉት በርካታ አስርት ዓመታት መላ የሀገራችን ሕዝቦች የብሄር፣ የኃይማኖት እና የፖለቲካ ልዩነታቸውን ወደ ጎን ትተው በጋራ በከፈሉት ከባድ መስዋእትነት ብልጭ ያለው የለውጥ ብርሀን ዘላቂ ይሆን ዘንድ በሕዝብ ይሁንታ ያገኘ መንግሥት ሀገርን ሊያስተዳድር ይገባል።

    ይህንን ተግባራዊ ለማድረግ 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ታሪካዊ አጋጣሚ ነው ብለን እናምናለን። በመሆኑም መላው የሀገራችን ሕዝቦች በዚህ ታሪካዊ ምርጫ በንቃት በመሳተፍ በሀገራችን የነጻነት፣ የእኩልነት እና የፍትህ ዘመን እውን ይሆን ዘንድ የድርሻችንን ልንወጣ ይገባል።

    ደካማ እና አሳፋሪ የምርጫ ታሪካችን በምርጫ ላይ ያለን እምነት እጅጉን እንዲሸረሸር አድርጎታል። ይህ ስሜት ሀገራችን ውስጥ ያለው አሳሳቢ የሰላም እና መረጋጋት ስጋት ታክሎበት 6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ “ነጻ፣ ፍትሀዊ እና ሰላማዊ” ላይሆን ይችላል የሚል ስጋት በበርካታ ወገኖች ዘንድ እንዲፈጠር አድርጓል። ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ ይህ ስጋት ምክንያታዊ እንደሆነ ይረዳል።

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ “ታሪካዊም ሆኑ ወቅታዊ ችግሮቻችንን ለመፍታት ከሚረዱ የፖለቲካ መሣሪያዎች አንዱ ምርጫ ነው።” ብሎ በጽኑ ያምናል። ምርጫ ዜጎች ሉአላዊ የስልጣን ባለቤት መሆናቸውን የሚያረጋግጡበት፣ የፖለቲካ ስልጣን ከሕዝብ የሚመነጭ መሆኑ በተግባር የሚረጋገጥበት ሥርዓት ነው።

    በመሆኑም ይህን የዜግነት መብት አስቸጋሪ በሆነ የፖለቲካ አውድ ውስጥ በሚካሄደው 6ኛው ጠቅላላ ምርጫ ልንጠቀምበት የሚገባ እና በፍጹም ልናሳልፈው የማይገባ የዜግነት መብት መሆኑን ሕዝባችን እንዲገነዘብ እንወዳለን።

    የመምረጥ መብታችንን በተግባር ለማረጋገጥ በአሁኑ ሰአት በመካሄድ ላይ ባለው የመራጮች ምዝገባ ዜጎች በንቃት መሳተፍ፣ በመራጭነት በመመዝገብ የመራጭነት መታወቂያችንን መያዝ ያስፈልጋል። ፈጠነን በመመዝገብ እና ሌሎች እንዲመዘገቡ በማድረግ ታሪካዊ እና ሀገራዊ ኃላፊነታችንን ልንወታ ይገባል።

    ክቡራት እና ክቡራን፥

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ) ለምርጫው ካደረጋቸው ዝግጅቶች አንዱ ብቁ እና ተወዳዳሪ እጩዎችን ማቅረብ ነው። በዚህም ከ600 መቶ በላይ እጩዎችን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና ለክልል ምክር ቤቶች በማቅረብ ለ6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ ከፍተኛ እጩ ካቀረቡ ፓርቲዎች አንዱ ለመሆን ችሏል። ይህ የእጩዎች ቁጥር ነእፓ ከተመሠረተ ጀመሮ ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በሕዝብ ዘንድ ያተረፈውን ከፍተኛ ተቀባይነት እና የፓርቲውን አደረጃጀት በመላ ሀገራችን ለመዘርጋት የተሰራውን ከፍተኛ እና ውጤታማ ሥራ ያሳያል።

    ፓርቲያችን ለምርጫው ካደረጋቸው ዝግጅቶች ውስጥ ሌላው የፓርቲውን የምርጫ ማኒፌስቶ ማዘጋጀት ሲሆን ይህንኑ ከፍተኛ የምርጫ ሰነድ በከፍተኛ ጥንቃቄ እና ትጋት አጠናቀን በዛሬው እለት ለሕዝባቸን ይፋ እናደርጋለን። የነእፓ የምርጫ ማኒፌስቶ ፓርቲያችን በምርጫው የሚያገኘው ውጤት ተንተርሶ በቀጣይ 5 ዓመት ሊሰራቸው ያቀዳቸውን ምጣኔ ሀብታዊ፣ ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ አካባቢያዊ እና የዓለማቀፍ ግንኙነት ዓላማዎች እና ግቦች በዝርዝር ይዟል።

    የነእፓ የምርጫ ማኒፌስቶ ሲያዘጋጅ ብሔራዊ፣ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ሰነዶችን፣ ግቦችን እና ስትራቴጂዎችን በሚገባ ለመከለስ ሞክሯል። በመሆኑም በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት የሀገራችን ማኅበራዊና ምጣኔ ሀብታዊ እድገት በዓለም አቀፍ ደረጃ ከተቀመጡ ግቦች ጋር የተናበበ እንዲሆን ተደርጓል። የአፍሪካ እና ዓለም አቀፍ የፖለቲካ እና ኢኮኖሚያዊ የለውጥ እመርታ ታሳቢ የተደረገ ሲሆን ከፍተኛ፣ የተረጋጋ እና አካታች የኢኮኖሚ እድገት እውን ማድረግን ያለመ ነው።

    ማኒፊስቶው ሲዘጋጅ የሰው ኃይል/ሀብት ልማት፣ አህጉራዊ ተወዳዳሪነት፣ ፈጣን የመረጃና የተግባቦት ቴክኖሎጂ እድገት፣ የአካባቢ ጥበቃ እና ዘላቂ የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀም ከግንዛቤ ውስጥ ገብተዋል። የመንግሥት እና የግል ባለሀብቶች የተቀናጀ ተሳትፎ ይበልጥ በማጠናከር መዋቅራዊ ለውጥ ማረጋገጥ እና ከፍ ወዳለ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ የእድገት ደረጃ ሽግግር ማካሄድ፣ የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ማሻሻል፣ የሀገራችንን ሰላም እና መረጋጋት ማስጠበቅ፣ የዜጎችን ሞት እና መፈናቀል ማስቆም የማኔፌስቶው ቁልፍ ጉዳዮች ናቸው።

    በውጭ ግንኙነታችን ኢትዮጵያ በአካባቢ እና አህጉራዊ ጉዳዮች ያላትን ቦታ እና ተሰሚነት ከፍ ማድረግ፣ በውጭ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ደህነነት፣ ከጎረቤት ሀገሮች እንዲሁም ከሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ሕዝቦች እና መንግሥታት ጋር በሰላም እና በጋራ ጥቅሞች ላይ በትብብር መሥራት የማኒፊስቶው ወሳኝ የትኩረት አቅጣጫዎች ተደርገው ተወስደዋል።

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ ምርጫ አሸንፎ ሀገር የማስተዳደር ኃላፊነት ከተረከበ ማኒፌስቶውን ለመፈጸም የሚረዱ ዓመታዊ እቅዶች እና ዝርዝር የአፈጻጸም ስትራቴጂዎች የሚዘጋጁ ሲሆን ጠንካራ የቁጥጥር እና ክትትል ሥርዓት ይዘረጋል።

    ክቡራት እና ክቡራን፥

    6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ካለፉት ስህተቶች የጸዳ እንዲሆን ከምርጫ በፊት፣ በምርጫ ወቅት እና ድህረ-ምርጫ ነጻ፣ ፍትሀዊ እና ሰላማዊ እንዲሆን መላ የሀገራችን ሕዝቦች በምርጫው ሂደት በንቃት በመሳተፍ የዜግነት ግዴታችንን ልንወጣ ይገባል። ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ 6ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ ሰላማዊ፣ ሂደቱ እና ውጤቱ በመራጩ ሕዝብ፣ በተፎካካሪ ፓርቲዎች እና በታዛቢዎች ተቀባይነት ያለው እንዲሆን አቅሙ የሚፈቅደለትን ሁሉ ያደርጋል።

    መላው የፓርቲያችን አባላት እና ደጋፊዎች የፓርቲያችንን የምርጫ ስነ-ምግባር ደንብ እና አግባብነት ያላቸውን የሀገሪቱን ህጎች ጠብቀን ለምርጫው ሰላማዊነት የበኩላችንን አስተዋጾ እንድናበረክት አደራዬ ከፍ ያለ ነው።

    በመጨረሻም፥

    ይህ ማኒፌስቶ ሲዘጋጅ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ኤክስፐርቶች ተካፍለዋል። በመንግሥት እና መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች፣ በአለም-ዓቀፍ ተቋማት፣ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት እና በግል አማካሪነት በመሥራት ላይ የሚገኙት እኚህ ኤክስፐርቶች በየሙያ ዘርፋቸው ለማኒፌስቶው ዝግጅት መነሻ ጥናታዊ ጽሁፎችን አቅርበዋል። በመላው የነጻነትና እኩልነት ፓርቲ አመራር እና አባላት ስም ላደረጉት አስተዋጽኦ ከፍተኛ ምስጋና አቀርባለሁ።

    የተከበራችሁ የሀገራችን ወጣቶች፣ ሴቶች፣ አርሶ አደሮች እና አርብቶ አደሮች፣ የንግዱ ማኅበረስብ አባላት፣ ተማሪዎች፣ አካል ጉዳተኞች፣ አረጋውያን፣ ህጻናት እንዲሁም ልዩ እንክብካቤ የሚያስፈልጋችሁ ዜጎች ነእፓ ለሁላችሁም የሚሆን አማራጭ ፖሊሲዎችን እና ፕሮግራሞችን “በሚዛናዊነት” እና “አብሮ ማሸነፍ” የትግል ዘይቤ ይዞ ይቀርቧል።

    ነጻነት፣ እኩልነት እና ፍትህ በተግባር እንዲረጋገጥ፣ በታማኝነት እና በእውነተኛ የሀገር ፍቅር ስሜት መላውን የሀገራችን ሕዝቦች ለማገልገል ነእፓ ከፍተኛ ዝግጅት በማድረግ አድርጓል።

    በመሆኑም ድምጽዎን ለቅን ልቦች እና ለታማኝ እጆች ይስጡ፣ ነእፓን ይምረጡ፣ ብእርን ይምረጡ።

    “እኩልነት በተግባር”
    አመሰግናለሁ

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ

    Anonymous
    Inactive

    የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ እና የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በጋራ ለመሥራት የሚያስችል የትብብር ስምምነት ተፈራረሙ
    ባልደራስ እና አብን ትብብርን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ

    የሀገራችን ሕዝብ ለዘመናት በተጫኑበት ኢዲሞክራሲያዊና አምባገነን አገዛዞች የተነሳ፥ በነፃነት እጦት፣በስቃይ እና በመከራ ኑሮውን እንዲገፋ ተደርጓል። ጭቆናን አስወግዶ የሚፈልገውን ፍትህ እና እኩልነት እውን ለማድረግ ከፍትኛ ዋጋ መክፈሉም እሙን ነው።

    ይሁንና የሀገራችን የለውጥ ፍላጎት እና እንቅስቃሴ ጅማሮው ሳይሳካ፥ ለቀጣዩ ዴሞክራሲያዊ ትግል ተስፋ ሊሆን የሚችል መሠረታዊ የትርክትና የመዋቅር ክለሳ እንኳ ሳይደረግ አምባገነንነትና ዘረኝነት የእጅ ለውጥ ብቻ እያደረጉ የሚፈራረቁባት ሆናለች። በዚህ ሁሉ ፈተና ውስጥ ያለፈው ሕዝባችን አሁንም ዲሞክራሲን፣ እኩልነትንና ዘላቂ ሰላምን በመሻት ለነፃነት የሚያደርገውን ትግል አጠንክሮ እንደቀጠለ ይገኛል።

    የዚህ ዓይነት መልክና ይዘት ተላብሶ የተደራጀው የተፎካካሪ ኃይል ለሰርጎ ገቦች የተጋለጠ፣ በተፈጥሮው ደካማና ተሰባሪ ከመሆኑም በላይ የአምባገነኑን ሥርዓት ራዕይ አቀንቃኝ እስከመሆን ደርሶ እንደነበር ይታወሳል። በተጨማሪ የተቃውሞው ጎራ እርስ በርሱ በፍረጃና በሴራ መጠላለፍ ምክንያት በቁርሾ እንዲሞላ በማድረግ የጋራ ሀገራዊ ስምሪት መውሰድ እንዳይችል አድርጎት ቆይቷል።

    በዚህ ሂደት ውስጥ አምባገነኖችን በጋራ መታገል ጥረት ከማድረግ ወርደው በመናኛ ፍላጎቶችና በጥቃቅን ልዩነቶች ዙሪያ ታጥረው ሲሻኮቱ በመካከል የባከነው ጊዜ እና የሰው ህይወት የሚያስቆጭ ነው።

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ሀገራችንን ለእድሜ ልክ ዝቅታ የዳረጋት የጥላቻ ትርክት፣ ትርክቱን መሠረት አድርገው የተደነገጉ ሕግጋትና የተዘረጉ መዋቅሮች ተከልሰው መላ ኢትዮጵያውያን በእኩልነት፣ በወንድማማችነት፣ በፍትህና በሰላም የሚተዳደሩነት ዘላቂ ሥርዓት በማስፈን በተለምዶ “መንታ ቅኝት” ያለው የትግል እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል። የአብን ስትራቴጂክ ግብ መላውን ኢትዮጵያዊ የፍትሀዊ አማካኝ ተጠቃሚ በማድረግ ሁሉንም አሸናፊ የሚያደርግ የፖለቲካ ማዕቀፍ እንዲፈጠር ሲሆን የድርሻውን ለማበርከት አበክሮ እየሠራ ያለ ንቅናቄ ነው።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ደግሞ የኢትዮጵያዊ ኅብር ዓይነተኛ መገለጫ የሆነችውን የአዲስ አበባ ከተማ ሕዝብ ከከፋፋይና ከጥላቻ ፖለቲካ ነፃ ለማድረግና ሕዝቡ ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብቱ እንዲረጋገጥ ለማስቻል በሚል የተደራጀ ስለመሆኑ በሰፊው የሚታወቅ ነው።

    አዲስ አበባ ከተማ የኗሪዎቿ መሆኗን ለማረጋገጥ የሚያደርጉት የጋራ ትግል መነሻ ዴሞክራሲን፣ ነፃነትን፣ ፍትህንና እኩልነትን በማስፈን ላይ የተመሠረተ ሲሆን፥ አንዳች ቅቡልነት ያለው መርህ ወይም ምክንያት ማጣቀስ የማይችሉ ኃይሎች ከተማዋ የአንድ ንጥል ብሔር ንብረት መሆኗን በይፋ በመግለፅ የማታገያ አጀንዳ በማድረግ ሕዝቡ በነሱ ፍቃድና ይሁንታ መኖር እንዳለበት አድርገው ያወጁት ያልተገራ ፍላጎት የጋረጠበትን የህልውና ስጋት መቀረፍ እንዳለበት አብን እና ባልደራስ የጋራ ፖለቲካዊ አቋም ወሰደዋል።

    የሀገራችን ኢትዮጵያ መድናና የመላ ሕዝቧ ሰላማዊ መኖሪያ ሆና ዘመናትን የተሻገረችው አዲስ አበባ መደበኛና ነባር ምልከታ ሊቸራት ሲገባ ከልቦለድ የመነጨ የዘረኞች “የልዩ ጥቅም”ቀንበር ጊዜ በረዘመ ቁጥር የሕግና የፖለቲካ ቋጠሮው እየጠበቀ መምጣቱና ይዘቱ “በኦሮሚያ ክልል አስተዳደርና በአዲስ አበባ መስተዳደር ስምምነት” እንደሚወሰን በተሻሻለው ቻርተር መደንገጉ ከተማዋንና ሕዝቧን ከአንድ ወገን በተሰባሰበ የፖለቲካ ኃይል ይሁንታ፣ ፍፁም ቁጥጥርና ጥበቃ ስር ለማዋል የተወሰነ መሆኑን ያሳያል። አብን እና ባልደራስ ይሄን አምባገነናዊ፣ ፍትህ አልቦ፣ ዘረኛ፣ አግላይና በመጨረሻም የግጭትና የብሔራዊ ደህንነት አደጋ የሆነ አፍራሽ እንቅስቃሴ በጋራ ተሰልፈው ለመታገል ከስምምነት ላይ ደርሰዋል።

    ትብብሩ በቀጣይ እንዲፈጠርና እንዲጎለብት ለምንፈልገው የሀገራዊ በጎ ኃይሎች ጥምረት እርሾ ሆኖ እንዲያገለግል የታለመ ነው። አስቻይነት የሌለውና በሕግ የተደነገገው የጊዜ ገደብ ጉዳይ በነባራዊ ተግዳሮቶች ምክንያት የተፈጠረ መሆኑን በማረጋገጥ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተመሳሳይ አንድምታ ያላቸውን ጉዳዬች ባስተናገደበት ሁኔታ ትብብሩ ለህጋዊ እውቅና ሲቀርብ በመፍቀድና በመመዝገብ እንዲያፀድቀው የሚቀርብ ይሆናል።

    በዚህ መነሻነት ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን እውን ለማድረግ ለሚደረገው ትግል በመጪው ሀገራዊ ምርጫ የመራጮችን የጋራ ፍላጎትና ራዕይ ለማሳካት የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ /አብን/ እና ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ /ባልደራስ/ በጋራ የምንሠራበት የፖለቲካ ትብብር ፈጥረን ለመሥራት መወሰናችንን ለመላው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን፣ ለመላው አማራ ሕዝብና ለአዲስ አበባ ሕዝብ ስናበስር በታላቅ ደስታ ነው። ሌሎች ፓርቲዎችን ጨምሮ በሁለቱ ፓርቲ አመራሮች መሃከል ለወራት ሲካሄድ የነበረው ረዥምና አድካሚ ድርድር ፍሬ አፍርቶ መጪውን ሀገራዊና ክልላዊ ምርጫ የአብን እና የባልደራስ ትብብር አሸናፊ ሆኖ መውጣት የሚያስችላቸውን የጋራ ስልቶች ቀይሰው በይፋ መንቀሳቀስ ጀምረዋል።

    አብን እና ባልደራስ፣ አጠቃላይ የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ የአማራ ሕዝብ እና የአዲስ አበባ ከተማ ኗሪ ሕዝብ በበደል ውስጥ አምጠው የወለዷቸው የቁርጥ ቀን ልጆቹ እንደመሆናቸው መጠን በተባባረ ክንድ በሕዝባችን ላይ የተጫነውን የመከራ ቀንበር እንዲወርድ ከመቼውም ግዜ በላይ በጋራ ትብብር ለመታገል በቁርጠኝነት ተሰልፈዋል።

    አብን በጽንፈኞች የተሳሳተ ትርክት መነሻነት በአማራ ሕዝብ ላይ በተከታታይ የሚደርሰው ግፍ ድምጽ በመሆን በመጀመሪያው ረድፍ ሆኖ ትግሉን እየመራ ይገኛል። አብን የሀገራችን ኢትዮጵያን ደህንነት ለማረጋገጥና ህልውናዋን ለማስቀጠል አንድ ወሳኝ አምድ የሆነው የአማራ ሕዝብ በልዩ ሁኔታ ተፈርጆ የሚጠቃበትን የፅንፈኞች ስሁት ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ለመግታት የሚያስችል ልዩ ማዕቀፍ ሆኖ የተደራጀ ሲሆን ታሪካዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ስሪቱ በኢትዮጵያዊነት፣ ምልከታውም በወንድማማችነት፣ በፍትህና በዴሞክራሲ የተቃኘ ስለመሆኑ ውሎ ያደረ ጉዳይ ነው።

    ከላይ በሰፊው እንደተመላከተው ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ በአዲስ አበባ ከተማ ሕዝብ ላይ የተጋረጡ የህልውና አደጋዎችን ለመከላከል፣ የከተማዋ ሕዝብም ራሱ በዴሞክራሲያዊ መንገድ በመረጣቸው እንደራሴዎቹ የመተዳደር መብቱን ለማስከበር ባሚያደርገው እልህ አስጨራሽ ትግል ውስጥ በብቃትና በንቃት በነሳተፍ አያሌ መስዋዕቶችን በመክፈል የቀጠለ መሆኑን ራሱ ሕዝቡ በተግባር ኖሮ ያረጋገጠው ሀቅ ነው። ከላይ በተጠቀሱት መሠረታዊ ሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ ግቦች ዙሪያ ሁለቱ ድርጅቶች በፅኑ የሚጋሯቸውን አቋሞች መሠረት በማድረግ ቀጣይ ለሚደረገው ጠንካራና የተቀናጀ የሕዝብ ትግል ወሳኝ የማታገያ አጀንዳ እንዲሆኑ ስምምነት ላይ ደርሰዋል።

    በሀገር አቀፍ ደረጃ ይካሄዳል ተብሎ በሚጠበቀው ምርጫ መላው የሀገራችን ሕዝብ፣ በተለይም የአማራ ሕዝብና የአዲስ አበባ ሕዝብ የተደቀነባቸውን የህልውና አደጋ በትብብር ከመታገል ውጭ ሌላ ተጨባጭ የመፍትሄ አማራጭ እንደሌለ መተማመን ላይ ደርሰዋል።

    ከዚህ ቀደም በጋራ አብረውን ለመሥራት ንግግር ጀምረው ሳለ በተለያዩ ምክንያቶች በትብብሩ ለመዝለቅ ያልቻሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች አሁንም ጊዜው አለመርፈዱን ተገንዝበው በጎ ፍላጎት ካሳዩን ከግማሽ መንገድ ባላይ ተጉዘን ለመቀበል ዝግጁ መሆናችንን በዚህ አጋጣሚ ለማረጋገጥ እንወዳለን።

    የፈጠርነው ትብብር አርአያ መሆን የሚችልና ከትላንት ለተሻለ አዲስ የፖለቲካ ባህል ማሳያ ፈር ቀዳጅ እንደመሆኑ ከምርጫ በኃላም ትብብሩ ጎልብቶ፤ የሀገራችንን ሕዝብ ለዘመናት የቆየ የፍትህ ትግል ዳር ለማድረስ እንዲሁም የመላው ኢትዮጵያዊ የሆነችውን የአዲስ አበባ ከተማን ዓለም አቀፍነት የሚመጥን አመራር ለመስጠት ለመፍጠር ከወዲሁ አብረን መቆም ጀምረናል።

    አብን እና ባልደራስ የአዲስ አበባ ሕዝብ ራስን በራስ የማስተዳደር ዴሞክራሲያዊ መብት አክብረው ከሚቀበሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ትብብር በመፍጠር የከተማዋ ሕዝብ በፌደራል መንግሥቱ ውስጥ ተወክሎ እንደሁሉም ሕዝብ ጥቅሙን ለማስጠበቅ የሚያደርገውን ትግል የማሳለጥ ሚና እንደሚኖረው ለማሳወቅ እንወዳለን።

    አዲስ አበባ በሁሉም ኢትዮጵያውያን ጥረት የተገነባች፣ የአፍሪካ የዲፕሎማሲ ዋና ከተማ ብትሆንም፥ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተነሱ ተረኞች ከተማይቷን በልዩ ጥቅም ስም የአንድ ቋንቋ ተናጋሪ ብቸኛ ንብረት ለማድረግ የሚደረገው እንቅስቃሴ በጋራ አጥብቀን እናወግዛለን። በከተማይቱ እና ነዋሪዎቿ ላይ የተደቀነውን ይህ አደጋ ለመከላከል ባልደራስ በዋነኛነት እያካሄደ ያለውን ትግል አብን የሚያድንቅ እና በሙሉ ልብ ከጎኑ እንደሚሰለፍ ቃል ይገባል። በአንጻሩም ባልደራስ ፓርቲ በጽንፈኞች ሴራ ዒላማ እንዲሆን በተደረገው የአማራ ሕዝብ ላይ የሚደርሰውን ግፍ እና በደል ለማስቀረት በቁርጠኝነት አብን ለሚያደርገው ትግል ክብርና እውቅና እንደሚሰጥ ለመግለፅ እንወዳለን፡፡

    ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ስምምነታችን የተበላሸውን የሀገራችንን ፖለቲካ ባሕል በማስተካከል፣ በውይይትና በሰጥቶ መቀበል መርህ ለሕዝብ ጥቅም ሲባል አብሮ መቆም እንደሚገባ ከማሳየት ባሻገር፥ ሌሎች ለተመሳሳይ አላማ ያነገቡ ፓርቲዎችም ይህን ፈለግ ተከትለው የትብብሩ አካል እንዲሆኑ ፅኑ ፍላጎት አለን።

    በመጨረሻም በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች ጽንፈኛ ኃይሎች በሚፈጽሟቸው የሽብር ድርጊቶች ምክንያት እየደረሰ ያለውን ሞት፣ የአካል ጉዳት፣ መፈናቀል እና የንብረት ውድመት ለማስቆም በየእርከኑ ያሉ የፌደራል እና የክልል መንግሥታት ኃላፊዎች ተግተው እንዲሠሩ ጥሪ እናቀርባለን።

    በተለይ ችግሩ ተባብሶ በሚገኝባቸው የኦሮሚያ፣ የቤንሻንጉል እና አንዳንድ የደቡብ ክልል አካባቢዎች የሚገኙ የመንግሥት አስተዳደርና የፀጥታ አካላት ችግሩን የሚመጥን ኃላፊነት በመውሰድ ንፁኃንን ከጥቃት እንዲከላከሉና ወንጀለኞችን ለሕግ እንዲያቅርቡ በአፅንኦት እንጠይቃለን።

    መሠረተ-ቢስ በሆነ ክስ ተወንጅለው ለእስር የተዳረጉትንና የመምረጥና መመረጥ መብታቸውን የተነፈጉ የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ አመራሮች በአስቸኳይ እንዲፈቱ እናሳስባለን። ትህነግ በለኮሰው ጦርነት በትግራይ ክልል ሕግ ለማስከበር እየተካሄደ ባለው ዘመቻ የንጹኃን ዜጎቻችንን ደህንነት እና የሰብዓዊ መብት እንዳይጣስ ልዩ ትኩረት እንዲደረግና የሰብዓዊ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ለማሳሰብ እንወዳለን።

    መጋቢት 9 ቀን 2013 ዓ.ም.
    የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ /ባልደራስ/
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ /አብን/

    ባልደራስ እና አብን በጋራ ለመሥራት

Viewing 15 results - 76 through 90 (of 730 total)