Search Results for 'የጤና ሚኒስቴር'

Home Forums Search Search Results for 'የጤና ሚኒስቴር'

Viewing 15 results - 16 through 30 (of 58 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    በአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁ አፈጻጸም ወቅት የታዩ ክፍተቶች አፋጣኝ ማስተካከያ ሊደረግባቸው ይገባል!
    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ)

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ መንግሥት የኮሮና ቫይረስ ‹COVID-19› በኢትዮጵያ ሊያደርስ የሚችለውን ተፅዕኖ ለመቆጣጠርና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ በማሰብ ሚያዝያ 2 ቀን 2012 ዓ.ም የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጅ ቁጥር 3/2012 ማወጁ ይታወሳል። የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁ ከታወጀ ወዲህ በመላው ሀገሪቱ ወጥነት ባለው መልኩ እየተተገበረ ካለመሆኑም በላይ የቫይረሱን ስፋት እና የስርጭት መጠን መሠረት በማድረግ በየጊዜው በአስፈጻሚው አካል የሚወጡ መመሪያዎችም በጥናት ያልተደገፉ እና ለሕግ አስከባሪው ኃይል የተለጠጠ የማስፈጸም ሥልጣን የሚሰጡ ሆነው ታይተዋል። በዚህም ምክንያት የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጁ ከታወጀበት ጊዜ ጀምሮ ባሉት አስር ሳምንታት የታዩት የዐዋጁ አፈጻጸም ሂደቶችም ሆኑ የመመሪያ አወጣጥ ሂደቱ ማሻሻያ ሊደረግባቸው የሚገቡ መሆናቸውን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) በጽኑ ያምናል።

    ዓለም-አቀፉ የጤና ድርጅት እና የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ጤና ሚኒስቴር የኮሮና ቫይረስን አስመልክተው በየጊዜው ይፋ ከሚያደርጓቸው መግለጫዎች ለመረዳት እንደሚቻለው ቫይረሱ ገና በቅጡ ተጠንቶ ያልታወቀ ተለዋዋጭ ባሕርይ ያለው መሆኑ ነው። ከዚህ የተነሣ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት እንዲያስችሉን የምንወስዳቸው እርምጃዎች በበቂ ጥናት ላይ የተመረኮዙ መሆን ይኖርባቸዋል። ቫይረሱ በኢትዮጵያ መገኘቱ ከታወቀበት ጊዜ አንሥቶ ፍ/ቤቶች በከፊል ዝግ ሆነው መቆየታቸው የዜጎች ፍትሕ የማግኘት መብት እንዲገደብ ከማድረጉ በላይ ጉዳያቸው በአፋጣኝ ታይቶ በነጻ መሰናበት እንዲሁም በዋስ መለቀቅ የሚችሉ ዜጎች ያለ አግባበብ በእሥር እንዲቆዩ ምክንያት ሆኗል። በዚሁ ምክንያት አንዳንድ ማረፊያ ቤቶች በመጨናነቃቸው ዜጎች ለቫይረሱ ይበልጥ ተጋላጭ ሆነዋል።

    የዐዋጁ አፈጻጸም ሲገመገም የዜጎችን በሕይወት የመኖር፣ ከማንኛውም ጥቃት ነጻ-የመሆን፣ ፍትሕ የማግኘት፣ እንዲሁም ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብቶች ላይ ያልተመጣጠነ ገደብ ያስቀመጠ በመሆኑ እነዚህ ጉዳዮች አስቸኳይ የማስተካከያ እርምጃዎችን እንዲሁም ዘላቂ መፍትሔዎችን የሚሹ መሆናቸውን ኢሰመጉ በጥብቅ ያምናል። ከዚህም በተጓዳኝ በቀጥታ በዐዋጁ ምክንያት ባይሆንም፤ የቫይረሱ መስፋፋት ባስከተላቸው ማኅበራዊ፣ ሥነ-ልቦናዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጫናዎች የተነሳ በጤና ባለሙያዎች፣ በሴቶች እና ሕጻናት፣ እንዲሁም በድንበር ተሻጋሪ አሽከርካሪዎች ላይ ዓይነተ-ብዙ የመብት ጥሰቶች እየደረሱ በመሆኑ ትኩረት እና መፍትሔ የሚሹ መሆናቸውን ኢሰመጉ ያምናል። እንዲሁም በዐዋጁ አፈጻጸም ወቅት እና በአጠቃላይ ቫይረሱ ከተከሰተ ወዲህ ባሉ ጊዜያት ከታዩት ጉልህ የመብት ጥሰቶች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል፡-

    በትግራይ ክልል ናዕዴር ዓዴት ወረዳ ቀደም ብሎ በክልሉ ታውጆ የነበረውን አስቸኳይ ጊዜ ዐዋጅ ለማስከበር በሚል አንድ የፖሊስ ባልደረባ በወሰደው የኃይል እርምጃ መጋቢት 19 ቀን 2012 ዓ.ም የአንድ ሰው ሕይወት ያለፈ ሲሆን፤ በተመሳሳይ ግንቦት 9 ቀን 2012 ዓ.ም መቐለ ከተማ ሰሜን ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታው 05 ቀበሌ አካባቢ አንድ የፖሊስ ባልደረባ በወሰደው የኃይል እርምጃ የሰው ሕይወት ጠፍቷል፤ ተጨማሪ ሌሎች ሰዎች ደግሞ ቆስለው ሕክምና ላይ ናቸው። በአማራ ክልል በጎንደር ከተማ አንድ የባጃጅ ሹፌር በጸጥታ ኃይሎች በተፈጸመበት ጥቃት አንድ እጁ ላይ በጥይት ጉዳት ደርሶበታል።

    በተለያዩ አካባቢዎች “የአፍ መሸፈኛ ጭምብል አላደረጋችሁም” በሚል ምክንያት ፖሊስ ተመጣጣኝ ባልሆነ እርምጃ በዜጎች ላይ ከፍተኛ እንግልት እና ለቫይረሱ አጋላጭ በሆነ መንገድ የጅምላ እስር ፈጽሟል። “ዐዋጁን ተላልፈዋል” በሚል ምክንያት ንግድ ቤቶች የሚታሸጉበት እና በሰዓት ገደብ እንዲዘጉ የሚደረጉበት ሂደት አንድ ወጥ አለመሆኑ አድሎአዊ እና ሕገ-ወጥ ለሆነ አፈጻጸም አጋልጧል።

    ቫይረሱን ግንባር-ቀደም ሆነው እየተከላከሉ ላሉት የጤና ባለሙያዎች በቂ ራስን የመከላከያ ግብዓቶች እየቀረቡ ባለመሆኑ ሕይወታቸውን አደጋ ላይ በሚጥል መልኩ እንዲሰሩ በመደረጋቸው ለቫይረሱም ተጋላጭ ሆነዋል። በጤና ሚንስቴር ይፋ በተደረጉ መረጃዎች መሠረት እስከአሁን ድረስ ወደ አንድ መቶ የሚጠጉ የጤና ባለሙያዎች እና የጤና ተቋም ሠራተኞች በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጧል። “ንክኪ አላቸው” በሚል በየጊዜው ወደ ለይቶ ማቆያ እንዲገቡ የሚደረጉ የጤና ባለሙያዎች ቁጥርም በየጊዜው እየጨመረ ነው።

    በአዲስ አበባ ቦሌ አየር ማረፊያ በኩል የሀገር ውስጥ በረራ ሊያደርጉ የነበሩ የተለያዩ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና ተወካዮች “ዓለም-አቀፍ በረራ አድርጋችኋል” በሚል ወደ አስገዳጅ ለይቶ ማቆያ ለአስራ ስድስት ቀናት ያህል እንዲገቡ፣ ለተወሰኑ ቀናትም ቤተሰብ ያሉበትን እንዳያውቅ ተደርጓል። ሌሎች ተፎካካሪ የፖለቲካ ድርጅቶችም የቫይረሱን መከላከያ ሥራዎች ሽፋን በማድረግ በአባላትና አመራሮቻቸው ላይ ልዩ ልዩ ተጽዕኖዎች እየደረሱባቸው ነው። ለአብነት፥ ወደ ደቡብ ክልል ቁጫ ወረዳ ሰላም በር ከተማ ለቤተሰባዊ ጉዳይ የሄዱትን አንድ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ፓርቲ አባል ወደ ከተማዋ ለሚገቡ ሌሎች ሰዎች ወጥነት ባለው መልኩ ተግባራዊ በማይሆን አሰራር ከግንቦት 9 – 11 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ለሦስት ቀናት በለይቶ ማቆያ ውስጥ እንዲቆዩ ተደርጎ ተለቀዋል። ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ (ባልደራስ) ፓርቲ ግንቦት 27 ቀን 2012 ዓ.ም በአዲስ አበባ ኮልፌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 አካባቢ ለሚገኙ ዜጎች እርዳታ ለማድረግ ሲንቀሳቀስ ፖሊስ ጣልቃ በመግባት እንዲቆም ተደርጓል።

    የቫይረሱ ስርጭት ባስከተለው ተጽዕኖ የዜጎች የሥራ ዋስትና ጥያቄ ውስጥ ከመውደቁም በላይ፥ አንዳንድ አሰሪዎች ሠራተኞቻቸውን ከሕግ አግባብ ውጪ በሆነ መንገድ ከሥራ ገበታቸው እንዲሰናበቱ እና አስገዳጅ ፈቃድ ያለክፍያ እንዲወጡ ተደርጓል።

    የድንበር ተሻጋሪ አሽከርካሪዎች ማኅበር ይፋ ባደረገው መረጃ በተለይም በጅቡቲ በኩል የሚገቡ አንዳንድ አሽከርካሪዎች ከሚደርስባቸው መገለል በተጨማሪ በአንዳንድ ከተሞች የማደሪያ እና የምግብ አገልግሎት እንዳያገኙ፣ መኪና እንዳያቆሙ ክልክላ ይደረግባቸዋል።

    መንግሥት ቀዳሚ ትኩረቱን በሽታውን በመከላከል እና ተያያዥ ሥራዎች በማድረጉ በሴቶች እና ሕጻናት ላይ የሚደርሱ የቤት ውስጥ ጥቃቶች፣ የአስገድዶ መድፈር ወንጀሎች እና ያለ ዕድሜ ጋብቻን የመሳሰሉት ልማዳዊ ጎጂ ድርጊቶች እየተበራከቱ እና እየተስፋፉ ነው። የአዲስ አበባ ከተማ ሴቶች እና ሕጻናት ቢሮ ብቻ ይፋ ባደረገው መረጃ መሠረት 101 ያህል ህጻናት የመደፈር ጥቃት ደርሶባቸዋል። በተመሳሳይ መልኩ በሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎችም መሰል የመብት ጥሰቶች እንዳሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

    በመሆኑም፥ ዐዋጁን ለማስፈጸም የተቋቋመው የሚኒስትሮች ኮሚቴ እና በየደረጃው ያለው ግብረ-ኃይል ለእነዚህ የመብት ጥሰቶች እና የአፈጻጸም ችግሮች ተገቢውን ትኩረት በመስጠት አስቸኳይ መፍትሔ እንዲያገኙ በትኩረት እንዲሠራ ኢሰመጉ ያሳስባል። መንግሥት በዐዋጁ አፈጻጸም ምክንያት ሊጎዱ ለሚችሉ የጎዳና ተዳዳሪዎች፣ ዝቅተኛ የኢኮኖሚ ደረጃ ላይ ለሚገኙ የሕብረተሰብ ክፍሎች፣ ለድንበር ተሻጋሪ አሽከርካሪዎች፣ በተለያየ ምክንያት ከቤት ንብረታቸው ለተፈናቀሉ ዜጎች አስፈላጊውን የምግብ፣ የንጽህና መጠበቂያ፣ የትራንስፖርት አገልግሎት እርዳታ እና ድጋፍ እንዲያደርግ ኢሰመጉ ጥሪውን ያቀርባል።

    ቫይረሱን ከፊት ሆነው እየተከላከሉ ላሉ የሀገራችን የጤና ባለሙያዎች ቫይረሱ አሁን ካለበትም ደረጃ የከፋ የሚሆንበትም ጊዜ ሳይጠበቅ አስፈላጊ የሆነውን ራስን የመከላከያ ግብዓት በበቂ ሁኔታ በአፋጣኝ እንዲያገኙ መንግስት እና የጤና ሚኒስቴር በትኩረት እንዲንቀሳቀሱ ኢሰመጉ ጥሪውን ያቀርባል። በተጨማሪም በቫይረሱ መያዛቸው ተረጋግጦ በለይቶ ሕክምና ላይ የሚገኙ ዜጎች የምግብ አገልግሎት፣ የመኖሪያ እና የንፅህና መስጫ ስፍራ ጽዳት፣ የአፍ መሸፈኛ ጭምብሎችን ጨምሮ የሌሎች የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁሶች አቅርቦትና የመሳሰሉ የአገልግሎት ችግሮች መኖራቸውን የሚያሳዩ መረጃዎች በመኖራቸው መንግሥት በትኩረት ችግሮቹን እንዲያስተካከል ኢሰመጉ ጥሪ ያቀርባል። በየጊዜው ዐዋጁን በመተላለፍ ተይዘው እንደ ትምህርት ቤት ባሉ መሠረተ ልማቶች ውስጥ የታሰሩ ዜጎች የሚቆዩበት ሥፍራ እንደ ምግብ፣ አልጋ፣ መጸዳጃና የመሳሰሉት መሠረታዊ አገልግሎቶች ለመስጠት በሚያስችል መልኩ መደራጀታቸውን እንዲያረጋግጥ ኢሰመጉ ያሳስባል።

    በዐዋጁ ድንጋጌ መሠረት የመንግስትም ሆነ የግል ትምህርት ተቋማት ተዘግተው ተማሪዎች እና መምህራን በአካል ተገናኝተው ትምህርት የሚሰጥበት ሂደት ተቋርጧል። ሆኖም ተማሪዎች ከቤታቸው ሆነው ትምህርት እንዲከታተሉ እየተደረገበት ያለው መንገድ ጥራቱን በጠበቀ፣ ተማሪዎች ትምህረቱን ለማስተላለፍ የሚረዱትን ነገሮች የማግኘት አቅማቸውን ታሳቢ ያደረገ እና የብሔራዊ ፈተና ተፈታኞችን ፍትሐዊ እድል ለመስጠት በሚያስችል መልኩ እንዲሰጡ መንግሥት እንዲያመቻች ኢሰመጉ ጥሪ ያቀርባል።

    በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተሰየመው የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጅ መርማሪ ቦርድም ሁኔታዎቹን በየጊዜው እየተከታተለ፣ በዐዋጁ ይዘት እና አፈጻጸም ላይ የሚሰጡ አስተያየቶችን በአግባቡ እንዲስተካከሉ ኃላፊነቱን እንዲወጣ እናሳስባለን። መንግሥት ቫይረሱን የመከላከል ሥራዎችን አስመልክቶ በየደረጃው የሚሠሩ ሥራዎች ለሕዝብ ይፋ እንዲሆኑ እና የሲቪል ማኅበረሰቡንም ሌላውን የሕብረተሰብ ክፍል ተሳትፎ በሚጠይቁ ጉዳዮች ላይ እንዲሳተፉ የሚያስችሉ ሁኔታዎችን እንዲያመቻች ኢሰመጉ ጥሪ ያቀርባል።

    ከዚህ በኋላ የሚወጡ መመሪያዎች የበሽታውን ባህርይ ታሳቢ ያደረጉ፣ በበቂ ጥናት እና መረጃ ላይ የተመሠረቱ፣ ለሕግ አስከባሪ ኃይሎች የሚሰጡት ሥልጣን ውስን እንዲሆን፣ ብሎም ክልከላ የተደረገባቸውን ነገሮች በግልጽ የሚያመላክቱ እንዲሆን ኢሰመጉ በጥብቅ ያሳስባል። ዐዋጁን በማስፈጸም ወቅት የፖሊስና ሌሎች የፀጥታ አካላት ሚና የጤና ባለሙያዎችን የማገዝ እንዲሆን ቅጣት እንኳን አስፈላጊ ቢሆን ሕይወትን የማዳን ዓላማ እንጂ የባሰ አደጋ ውስጥ በማይከት ሁኔታ መሆን ስለሚገባው፤ ተጠያቂነትን በሚያሰፍን መልኩ በጥብቅ ዲሲፕሊን እንዲመራ የሚያሳስብ ድንጋጌ በያዘ መልኩ ማሻሻያ እንዲደረግባቸው ኢሰመጉ ያሳስባል።

    በተጨማሪም በአዲስ አበባ ከተማ የሚደረጉ የመሬት ወረራን ታሳቢ አድርገው የሚሠሩ የሕግ ማስከበርና የቤት ማፍረስ እርምጃዎች ያለንበት ወቅት ክረምት እንደመሆኑ እና ዜጎችን ለበሽታውም ስርጭት የበለጠ ተጋላጭ እንዲሆኑ የሚያደርግ በመሆኑ በጥንቃቄ እና ወጥነት ባለው እንዲታዩ ኢሰመጉ ጥሪውን ያቀርባል።

    ሁሉም መብቶች ለሁሉም!!

    ምንጭ፦ ኢሰመጉ

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ)
    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) በኢትዮጵያ የሽግግር ወቅት ቻርተር አንቀጽ 1(ሀ) እና በኢትዮጵያ ፍትሐ-ብሔር ሕግ ቁጥር ከ404-482 በተጻፉት ድንጋጌዎች መሠረት መስከረም 29 ቀን 1984 ዓ.ም.  በአባላት የተመሠረተ የመጀመሪያው መንግሥታዊ ያልሆነ ተሟጋች ተቋም ነው።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ)

    Semonegna
    Keymaster

    የኮቪድ-19 ስርጭት ማሻቀብን ተከትሎ ለአንድ ወር የሚቆይ ሀገር አቀፍ የምርመራ ዘመቻ ይጀመራል – የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሃምሌ 25 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ፥ ኢትዮጵያ ውስጥ በተለይም በአዲስ አበባ ከተማ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ (ኮቪድ-19) ስርጭት እጅግ ማሻቀብን ተከትሎ ለአንድ ወር የሚቆይ ሀገር አቀፍ የምርመራ ዘመቻ ይጀመራል። የጽሕፈት ቤቱ መግለጫ እንደሚከተለው ይነበባል።

    ባለፉት ሁለት ሳምንታት የኮቪድ-19 ስርጭት ማሻቀቡ ይስተዋላል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ሰብሳቢነት ሥራውን የሚከውነው እና ቫይረሱን የመከላከል ሥራዎችን የሚያስተባብረው የሚኒስቴሮች ኮሚቴ፥ ሃምሌ 25 ቀን 2012 ዓ.ም. ከሰዓት በወቅታዊው ሁኔታ ላይ ተወያይቷል። የጤና ሚኒስቴር እና የትምህርት ሚኒስቴር ወረርሽኙ በዓለም አቀፍ እና በሀገር አቀፍ ደረጃ ያለውን አካሄድ በተመለከተ ገለጻ አቅርበዋል።

    የጤና ሚኒስቴር ባቀረበው ሪፖርት መሠረት፥ እስከ አሁን [ሃምሌ 25 ቀን] ድረስ በኢትዮጵያ 17,500 በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች የተገኙ ሲሆን፣ ከእነዚህ ውስጥ 70 በመቶው የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ናቸው። በቫይረሱ ከተያዙት ሰዎች መካከል፣ 84 በመቶው ዕድሜያቸው ከ50 ዓመት በላይ ሲሆን፣ ከመመርመራቸው በፊት በቫይረሱ የመያዝ ምልክቶች አልታዩባቸውም። ይህም ምልክት ሳይታይባቸው ቫይረሱን የሚያስተላልፉ ብዙ ሰዎች መኖራቸውን ያመላክታል።

    የትምህርት ሚኒስቴር የመጀመሪያ፣ የሁለተኛ እና የሦስተኛ ደረጃ ትምህርት ሁኔታዎችን መረጃ አጠቃልሎ አቅርቧል። በዚህም መሠረት፥ ትምህርት ቤቶች [በ2013 ዓ.ም. የትምህርት ዘመን] ተመልሰው ከመከፈታቸው በፊት ሊተኮርባቸው የሚገቡ ቅድመ ሁኔታዎችን አመላክተዋል። ከእነዚህም ውስጥ የቫይረሱ የስርጭት መጠን መቀነስ ዋነኛው ነው።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የምርመራ መጠንን ከፍ ማድረግ የወረርሽኙን አካሄድ ለመረዳት ወሳኝ ተግባር መሆኑን በአጽንዖት ተናግረዋል። ለአንድ ወር የሚቆይ ሀገር አቀፍ የምርመራ ዘመቻ እንዲካሄድም አቅጣጫ ሰጥተዋል።

    ADDIS ABABA (Semonegna) – The Office of Prime Minister – Ethiopia issued a press statement on 1st August 2020 stating that the country will carry out nationwide mass testing of COVID-19 for one month amid the surge of COVID-19 cases in the country, especially in recent weeks. The press statement reads as follows.

    Over the past couple of weeks there has been a noticeable increase in the number of positive COVID-19 cases. The ministerial committee overseeing prevention activities and chaired by Prime Minister Abiy Ahmed, met this afternoon to discuss the current status, where the Ministers of Health and Education presented on the international and domestic trends of the pandemic.

    According to Ministry of Health reports, there are currently 17,500 positive COVID-19 cases confirmed [in the country] as of date with 70% located in Addis Ababa. While 84% of positive cases are above the age of 50 years, 92% of positive cases showed no symptoms prior to testing, which indicates the presence of many silent spreaders.

    The Minister for Education, combining data for primary, secondary and tertiary education, highlighted that a number of issues need to be factored before considering opening schools [for the coming academic year], with declining rate of cases being the key number one factor to enable an opening decision.

    Prime Minister Abiy Ahmed emphasized the critical importance of increased testing to understand the trends better for effective decision making, and gave direction for the launch of a one-month nationwide mass testing.

    የኮቪድ-19 ስርጭት ማሻቀብ

    Anonymous
    Inactive

    የተፈጥሮ ሳይንስ እና ግብርና ኮሌጅ ያላቸው ዩኒቨርሲቲዎች ከመቼውም ጊዜ በላይ ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር መሳካት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ሊያበረክቱ እንደሚገባ ተገለጸ።

    በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በአገራችን አምስት ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ እየተሠራ ይገኛል።

    የከፍተኛ ትምህርትና ስልጠና ተቋማትም ማኅበራዊ ኃላፊነታቸውን ለመወጣት ሰኔ 8 ቀን 2012 ዓ.ም. ዕለት የከፍተኛ ትምህርትና ስልጠና ተቋማት የአረንጓዴ አሻራ ቀን በሚል ችግኝ የመትከል ማዕድ የማጋራትና ደም የመለገስ መርሃ-ግብሮች ተከናውነዋል።

    ኦሮሚያ ክልል ውስጥ በአሰላ ከተማ የሚገኘው አርሲ ዩኒቨርሲቲ በመገኘት መርሃ-ግብሩን ያስጀመሩት የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ እንዳሉት፥ የተፈጥሮ ሳይንስ እና የግብርና ኮሌጅ ያላቸው ዩኒቨርሲቲዎች ከመቼውም ጊዜ በላይ ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር መሳካት የበኩላቸውን ሊወጡ ይገባል።

    በቅድመ ተከላ፣ በተከላ ወቅትና ድኅረ ተከላ መደረግ ያለባቸውን እንክብካቤዎችን እና ጥንቃቄዎችን በማስተማርና እንዲሁም እንደየአከባቢው የአየር ንብረት ሁኔታ ተስማሚ የሆኑትን ችግኞች እንዲባዙ ጥናትና ምርምር ከማድረግና ማማከር በተጨማሪ ከሌላው ጊዜ በበለጠ ችግኞችን አባዝተው ለአከባቢው ማኅበረሰብ ተደራሽ ማድረግም ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።

    አያይዘውም በየአከባቢው ያለው የትምህርትና ስልጠና ተቋማት ማኅበረሰቡ እንዲሁም ሌሎችም ኢትዮጵያውያን የኮሮናቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሸኝን እየተጠነቀቁ በዚሁ ምክንያት ለተቸገሩ ወገኖቻቸው ማዕድ እንዲያጋሩ እና ደም በመለገስም ክቡር የሆነውን የሰው ልጆች ህይወት እንዲታደጉ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    በተጨማሪም የዩኒቨርሲቲውን ሦስቱን ግቢዎች ከዩኒቨርሲቲው አመራሮች ጋር በመሆን የጎበኙ ሲሆን፥ በጉብኝቱ ከሰባ ዓመታት በፊት በስዊድን ድጋፍ የተቋቋመውና በዩኒቨርሲቲው የግብርና ኮሌጅ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ ለማኅበረሰቡ ጠቃሚ የግብርና ምርምር ሥራዎችን እየሠራ እንደሚገኝ እና የጤና ሳይንስ ኮሌጁም የኮሮናቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሸኝን ለመከላከል የሚያመስገን ሥራ እየሠራ መሆኑም ተገልጿል።

    ፕሮፌሰር አፈወርቅ በማዕድ ማጋራት ዩኒቨርሲቲው የሚደግፈውን አፎምያ የአረጋውያን መርጃ ማኅበር የጎበኙ ሲሆን በጉብኝቱ ወቅትም ዩኒቨርሲቲው የዱቄትና ዘይት ድጋፍ አድርጓል።

    ከአረንጓዴ አሻራ ዘመቻ ጋር በተያያዘ፥ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ዑማ ከድምጻውያን ጋር በመሆን በየካ ክፍለ ከተማ በሚገኘው ሚሊኒየም ፓርክ ውስጥ (የካ ተራራ) ችግኞችን ተክለዋል።

    ከንቲባው በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፥ ዓለም-አቀፍ ስጋት የሆንውን የኮሮናቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሸኝን ከመከላከል በተጓዳኝ ነዋሪዎች ርቀታቸውን ጠብቀው ችግኞች እንዲተክሉ አሳስበዋል። ችግኝ ከመትከል ባለፈም ችግኞች በየጊዜው መንከባከብም ያስፈልጋል ብለዋል።

    የኢትዮጵያ የሙዚቃ ዘርፎች ማኅበራት ሕብረት ፕሬዚዳንት አቶ ዳዊት ይፍሩ ሕብረተሰቡ ችግኞች ያላቸውን ዘርፈ ብዙ ጥቅም በመረዳት በራሱ ተነሳሽነት መትከልና መንከባከብ ይገባል ብለዋል። ሕብረቱም የተከላቸውን ችግኞች ለመንከባከብም ቃል ገብተዋል።

    በሥፍራው ተገኝቶ አረንጓዴ አሻራ በማኖሩ ደስተኝነቱን የገለጸውና ተግባሩ መቀጠል አለበት ያለው ድምፃዊ ነዋይ ደበበ ነው።

    ”ንጹህ አየር ለሰው ልጅ አስፈላጊ እንደመሆኑ መጠን ችግኝ መትከል ግዴታ ነው። በዚህም ቦታ ተገኝቼ አረንጓዴ አሻራ በማኖሬ ደስተኛ ነኝ” ሲል የሙዚቃ አቀናባሪ ካሙዙ ካሣ ተናግሯል።

    በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በ አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰባት ሚሊዮን ችግኞች ለመትከል ታቅዷል። በአገር አቀፍ ደረጃ አምስት ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል የታቀደ ሲሆን፤ ከሚተከሉት መካከል ለጥምር ግብርና የሚሆኑ የፍራፍሬ ችግኞች ይገኙበታል።

    ምንጮች፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር/ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አረንጓዴ አሻራ

    Anonymous
    Inactive

    የጤና ሳይንስ ምሩቃን በሀገር ውስጥ ተወዳዳሪ እንዲሆኑና ከሀገር ውጭ ሲወጡ ደግሞ በተማሩበት የሙያ መስክ ጥራት ያለውን ሥራ መሥራት እንዲችሉ የሚያበቃ የሥርዓተ ትምህርት ክለሳና የስልጠና ፕሮግራም ደረጃ ማሳደግ እንደሚገባ ተጠቁሟል።

    በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሰጡ የጤና ሳይንስ ትምህርቶችን ጥራት ለማሳደግ የሚያስችል ውይይት ተካሄደ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር Jhpiego ከተሰኘ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት ጋር የጤና የሰው ኃይል ልማት ማሻሻያ ፕሮግራም (Health Workforce Improvement Program /HWIP/) ላይ የቪዲዮ ውይይት (webinar) አድርጓል።

    በውይይቱ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ በሀገራችን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በጤና ሳይንስ የሚመረቁ ምሁራን በሀገር ውስጥ ተወዳዳሪ እንዲሆኑና ከሀገር ውጭ ሲወጡ ደግሞ በተማሩበት የሙያ መስክ ጥራት ያለውን ሥራ መሥራት እንዲችሉ የሚያበቃ የሥርዓተ ትምህርት ክለሳና የስልጠና ፕሮግራም ደረጃ ማሳደግ ይገባል ብለዋል።

    ለዚህም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የትምህርት ጥራት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ገልጸው እንዲህ ዓይነት መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እገዛም አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመዋል። በጤና ዘርፍ በየዓመቱ መሰልጠን ያለባቸውን ቁጥር አጥንቶ መመጠን፣ ኢ-ለርኒንግን (e-learning) ማጠናከር፣ የትምህርት መርሃግብሮች ዕውቅና አሰጣጥ (programs accreditation) ላይ መሥራት፣ የመርሃግብር ደረጃ ማውጣትና ተግባራዊ ማድረግ ከዩኒቨርሲቲዎች ይጠበቃል ብለዋል።

    የተወሰኑ ዩኒቨርሲቲዎች የራሳቸው ሆስፒታል እና የጤና ማዕከላት ሲኖራቸው የሌላቸው ደግሞ ተማሪዎቻቸውን በአከባቢያቸው ከሚገኙ የጤና ማዕከላት ጋር በመቀናጀት ያሰለጥናሉ ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፥ ስለሆነም በጤና ዘርፍ ያሉ አመራሮችን፣ መምህራንን እና የጤና ባለሙያዎችን አቅም መገንባትና ግብዓት ማሟላት ለጥራት የራሱ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመዋል።

    ፕሮጀክቱ የ5 ዓመት መሆኑን እና በጤና ዘርፍ የሚወጡ ተማሪዎች ጥራት እንዲኖራቸው መሥራትና፣ ለጤና ዘርፍ ትምህርት ጥራት የሚያስፈልጉ አስፈላጊ ግብዓቶችንና ቴክኒካዊ ምክረሃሳቦችን በማቅረብ ተግባራዊ እንዲረግ መሥራት ዋና ዓላማቸው መሆኑን የገለፁት የJhpiego ዳይሬክተር ዶ/ር ተግባር ይግዛው የጤና ሳይንስ ትምህርትን ጥራትን ለመደገፍ እንደሚሠሩ ገልጸዋል።

    የ39.5 ሚሊየን ዶላር ፕሮጀክቱን ተግባዊ ለማድረግም በጤና ትምህርት ዘርፍ በሚደረጉ ድጋፎች ላይ ከሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር መሥራት እንደሚፈልጉ ገልጸዋል። በተለይ ለጾታ እኩልነት ቦታ እንደሚሰጡም ጠቁመዋል።

    ዶ/ር ተግባር ፕሮጀክቱ በኢትዮጵያ የጤና ዘርፍ ውስጥ የሚከሰቱትን ወሳኝ የሰው ኃይል ችግሮች ለመቅረፍ የሚያስችሉ መንገዶችን ለማመቻቸት ከጤና ሚኒስቴር ጋር በትብብር ስምምነት የሚሠራ መሆኑን ገልጸው፥ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እና ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ተባብሮ በመሥራትም የኢትዮጵያን የጤና ባለሙያዎች ጥራት፣ የአገልግሎት አሰጣጥና ብቃት ለማሻሻል እና የጤና የሰው ኃይል አስተዳዳሪዎች ችሎታን ለመገንባት በተቋም እና ግለሰቦች አቅም ግንባታ ላይ ትኩረት አድርጎ ይሠራል ብለዋል።

    በውይይቱ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ቅድሚያ ተሰጥቶ ቢሠራበት የሚሏቸውን ሀሳቦች አንስተዋል። በዚህም በሚኒስቴሩ በኩል ከድርጅቱ ጋር በጋራ የሚሠራባቸው መስኮች ተለይተው እና የትግበራ ዕቅድ አውጥተው ወደሥራ እንደሚገቡ ተጠቁሟል።

    በውይይቱ ዩኒቨርሲቲዎችን ዓለምአቀፋዊ ማድረግ ላይ የሚሠራውን ሥራ ለማገዝ ዕውቅና መስጠት (accreditation) መጀመር እንዳለበትና በተለይ የሕክምና ትምህርት ላይ ቀድሞ መጀመር ጥቅሙ ከፍተኛ መሆኑም ተመላክቷል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የጤና ሳይንስ ትምህርት

    Anonymous
    Inactive

    የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከተለያዩ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ጋር በመሆን የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል የሚውል ከሦስት ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ አደረገ

    አዲስ አበባ (ሠ.ማ.ጉ.ሚ.) – ለማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር ይበልጥ ተጋላጭ ለሆኑ የሕብረተሰብ ክፍሎች የኮሮና ቫይረስ (COVID-19) ወረርሽኝን ለመከላከል የሚውል ከሦስት ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ ተደረገ።

    የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር (ሠ.ማ.ጉ.ሚ.) ከኮሮና ቫይረስ ስርጭት ጋር በተያያዘ ከፍተኛ ተጋላጭነት አላቸው ላላቸው አረጋውያንና አካል ጉዳተኞች የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል የሚውል ከሦስት ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ አድርጓል።

    በዚህም ለኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ብሔራዊ ማኅበራት ፌዴሬሽና በስሩ ላሉት ብሔራዊ ማኅበራት ሁለት ሚሊዮን አንድ መቶ ሺህ ብር፣ ለኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ብሔራዊ ማኅበር ሦስት መቶ ሺህ ብር እንዲሁም ለኢትዮጵያ አረጋውያን ብሔራዊ ማኅበር ስድስት መቶ ሀምሳ አንድ ሺህ አንድ መቶ አስራ ሰባት ብር ድጋፍ ተደርጓል።

    የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬ በኢትዮጵያ ከ1.2 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ የአካል ጉዳተኞች እና ከ1.1 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ አረጋውያን እንደሚገኙ ጠቁመው ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ኃላፊነቱን በመወጣት ተጋላጭ የሆኑ የማኅበረሰብ ክፍሎችን ከኮሮና ቫይረስ ለመከላከል የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን እያደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል።

    እነዚህ የማኅበረሰብ ክፍሎች ለኮሮና ቫይረስ ያላቸውን ተጋላጭነት ለመቀነስ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ በአቅም ግንባታ ማዕቀፍ ሲያደርግ የነበረውን የገንዘብ ድጋፍ የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን ለመከላከል እንዲውል መወሰኑን የተናገሩት ሚኒስትሯ፥ ድጋፉ አዲስ አበባንና ክልሎችን ባቀፈ ሁኔታ የምግብ ፍጆታና የንፅህና መጠበቂያ እቃዎች አቅርቦት እንደሚሸፈንበት ተናግረዋል። በቀጣይም ከተለያዩ የልማት ድርጅቶችና የበጎ ፈቃድ ማኅበራት ጋር በመሆን ድጋፉ እንደሚቀጥል ዶ/ር ኤርጎጌ ተናግራዋል።

    በዕለቱ ሌሎች የቁሳቁስ ድጋፎች የተደረጉ ሲሆን የአካል ጉተኞች የእንቅስቃሴ ችግርን ለመቅረፍ አሜሪካን አገር ከሚገኝ አጋፔ ሞቢሊቲ ኢትዮጵያ (Agape Mobility Ethiopia) ጋር በመተባበር ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ በሚገመት ወጪ 183 ዘመናዊ ዊልቸር (wheelchair) ርክክብ የተደረገ ሲሆን ፥ ድጋፉ በሱማሌ፣ ሀረርና ደቡብ ክልሎች ለሚገኙ የእንቅስቃሴ ችግር ላለባቸው አካል ጉዳተኞች የሚውል ይሆናል ተብሏል። በተጨማሪም በአፍሪኮም የቴክኖሎጂ ኩባንያ (AFRICOM Technologies Plc) እና ድርሻዬን ልወጣ የበጎ ፍቃደኞች የንፅህና መጠበቂያ ድጋፍ ተደርጓል።

    በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ለወረርሽኙ ይበልጥ ተጋላጭ የሆኑ የሕብረተሰብ ክፍሎችን መደገፍ ከሁሉም የሕብረተሰብ ክፍል እንደሚጠበቅ የተናገሩት ማኅበራቱ ሚኒስቴር፥ መሥሪያ ቤቱ ላደረገው ድጋፍ ያላቸውን ምስጋና አቅርበዋል።

    እስከ መጋቢት 29 ቀን 2012 ዓ.ም. ኢትዮጵያ ውስጥ በ አጠቃላይ ሰዎች የኮሮና ቫይረስ እንደተገኘባቸው መረጋገጡን የጤና ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ተቋም አስታውቀዋል። በኢትዮጵያ በቫይረሱ የተያዙ ሰዎች መካከል አንድ ግለሰብ በጽኑ ህሙማን ማቆያ ይገኛሉ። አራቱ ያገገሙ ሲሆን፤ ሁለቱ በቫይረሱ ምክንያት ሕይወታቸው አልፏል። ቫይረሱ ከተገኘባቸው መካከል ሌሎች ሁለት ግለሰቦች ደግሞ ወደ ሀገራቸው ተሸኝተዋል።

    ምንጭ፦ ሠ.ማ.ጉ.ሚ./ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የምርጫ 2012 ኦፕሬሽን እቅድ እና የጊዜ ሰሌዳ ላይ የፈጠረውን ችግር ገምግሞ ያሳለፈው ውሳኔ መግለጫ

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በ2012 ዓ.ም የሚካሄደውን አጠቃላይ ምርጫ ለማስፈፀም የቅድመ ምርጫ ዝግጅት ሥራዎች ሲያከናውን ከቆየ በኋላ የምርጫ የጊዜ ሰሌዳውን ይፋ አድርጓል።

    በዚህ የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ መሠረት ምርጫው ነሐሴ 23 ቀን 2012 ዓ.ም. እንዲካሄድ ተወስኖ ቦርዱ በጊዜ ሰሌዳው የተገለጹ ተግባራትን በተያዘላቸው ጊዜ እያከናወነ ለሕዝብ እያሳወቀ እንደቆየ ይታወሳል። በዚህም መሠረት በያዝነው መጋቢት እና በሚመጣው ሚያዝያ ወራት 2012 ዓ.ም. መጠናቀቅ ያለባቸው በርካታ ሥራዎች አሉ። መከናወን ካለባቸው ሥራዎች ዋና ዋናዎቹ የመራጮች ምዝገባ፤ የምርጫ አስፈፃሚዎች ምልመላ፤ ስልጠናና ስምሪት፤ የመራጮች ትምህርት፤ ለመራጮች ምዝገባ የሚያስፈልጉ ቁሳቁስ ስርጭት የመሳሰሉት ናቸው።

    እነዚህን ሥራዎች በጊዜ ሰሌዳው መሠረት ለማከናወን ቦርዱ ተገቢ ጥረት እያደረገ በሚገኝበት ወቅት ባለፉት ሳምንታት በሃገራችን እና በዓለም ላይ የተከሰተው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ እንቅስቃሴዎች እንዲቋረጡ አስገድዷል። ከዚሁ የወረርሽኝ ሥጋት የተነሳ በርካታ ሃገራት ምርጫን ጨምሮ መንግሥታዊ ዕቅዶቻቸውን ለማቋረጥ ተገደዋል። በሃገራችንም መንግሥት ወረርሺኙን ለመከላከል የሰዎች ግንኙነትን የመቀነስ እርምጃዎች እንዲወሰዱ በመወሰኑ የመንግሥት ሠራተኞች አብዛኛውን ሥራ ከቤት ሆነው እንዲሠሩ ተደርጓል፡መንግሥት የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት የተለያዩ ጥብቅ እርምጃዎችን እየወሰደ ሲሆን ከዚህ በተጨማሪም በክልል መንግሥት መስተዳድሮች ደረጃ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ፣ የውስጥና የአገር አቋራጭ የትራንስፓርት ገደቦች፣ የመሰብሰብ ገደቦችን የመሳሰሉ ጥብቅ ክልከላዎች ይፋ ሆነዋል።

    በመንግሥት ከተላለፉ የክልከላ ውሳኔዎች በተጨማሪ ለቦርዱ ድጋፍ የሚያደርጉ ዓለምአቀፍ አጋር ድርጅቶች አብዛኞቹ ሠራተኞቻቸው ከቤት ሆነው እንዲሠሩ ሲደረጉ አንዳንዶቹ ደግሞ ጥቂቶቹን ብቻ በማስቀረት ሠራተኞቻቸው ወደ ሃገራቸው እንዲመለሱ አድርገዋል። ከላይ የተጠቀሱት ድምር ሁኔታዎች በሚያዚያ ሊጀመር በታቀደው የመራጮች ምዝገባ እና ተያያዥ የዝግጅት ሥራዎች ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ አሳድሯል። ከዚህ የሚከተሉት ከችግሩ ማሳያ ከሚሆኑት ጥቂቶቹ ናቸው።

    • በኢትዮጵያ አየር መንገድ መጋዘን የሚገኙ የምርጫ ቁሳቁሶችን የማሸግ ሥራ በሁለት ሳምንት ዘግይቷል፤
    • የቀሪ ህትመት ውጤቶች ግዥ በቫይረሱ ምክንያት በተፈጠረ የአቅርቦት ሰንሰለት መደናቀፍ ምክንያት ተጓቷል፤
    • ለምርጫ አስፈፃሚዎች ስልጠና ቁጥራቸው 1000 /አንድ ሺ/ በላይ የሚሆን አሰልጣኞችን ክክልሎች ወደ አዲስ አበባ በማምጣት የአሰልጣኞች ስልጠና መስጠት አልተቻለም፤
    • ለ150,000 (አንድ መቶ ሃምሳ ሺህ) የምርጫ አስፈፃሚዎች በየክልሎቹ መሰጠት ያለበትን ስልጠና መጀመር አልተቻለም፤
    • ቦርዱ የሚሰጠው የመራጮች ትምህርት ኮቪድ-19 ቫይረስን አስመልክቶ በሚወጡ የማኅበረሰብ ጤና መልእዕቶች ሊዋጡ የሚችሉበት ዕድል ከፍተኛ ሆኖ ተገኝቷል።

    የቫይረሱ ስጋት በቀጣዩ ሀገራዊ ምርጫ በአጠቃላይ በተለይም በአፋጣኝ መፈጸም ባለባቸው የመራጮች ምዝገባ፤ የምርጫ አስፈፃሚዎች ስልጠና፤ የመራጮች ትምህርት ተግባራት አፈፃፀም ላይ ሊኖረው የሚችለውን ተፅዕኖ አስመልክቶ ቦርዱ ከሕግ አውጪው አካል፤ በጉዳዩ ላይ ከሚሠሩ የጤና ሚኒስቴር ከፍተኛ የማኅበረሰብ ጤና ባለሞያዎች፣ ከዓለምአቀፍ አጋሮች እና ከፖለቲካ ፓርቲዎች እና ጋር ተመካክሯል።

    ከፓለቲካ ፓርቲዎች ጋር በተደረገው ውይይት አብዛኞቹ ፓርቲዎች የችግሩን ግዝፈት እና በምርጫ ላይ የሚኖረውን ተጽዕኖ ተገንዝበው ቦርዱ ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር ተመካክሮ አማራጭ የአፈጻጸም ዕቅድ ሊኖረው እነደሚገባ መክረዋል። ይሁን እና በዚህ አግባብ የሚወሰደው እርምጃ ችግሩ ከሚጠይቀው በላይ የሆነ መዘናጋት እንዳያመጣ ቦርዱ በወረርሽኙ አፈጻጸማቸው የማይስተጓጎል ሥራዎችን እንዲያጠናቅቅ አሳስበዋል።

    ቦርዱ ለውሳኔው መሠረት የሚሆነው የዳሰሳ ጥናት በአማካሪ ባለሙያዎቹ ተሠርቶ እንዲቀርብለትም አድርጓል ። የተፈጠረው አጠቃላይ ሁኔታ ከታቀደው የምርጫ ምዝገባና ቀጣይ እርምጃዎች ላይ ሊያሳድር የሚችለውን ተፅዕኖ ባግባቡ ለመዳሰስ ያስችለው ዘንድ በዳሰሳ ጥናቱ ላይ ተመሥርቶ ቦርዱ ሁለት የቢሆን ሁኔታ ግምቶች (scenarios) ተመልክቷል።

    የመጀመሪያው የቢሆን ሁኔታ ግምት መሠረት የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመግታት በኢትዮጵያ መንግሥት እየተወሰዱ ያሉ እርምጃዎች ለአራት ሳምንት ብቻ ማለትም እስከ ሚያዚያ 7 ሊቆይ ይችላል በሚል ግምት ላይ የተመሠረተ ነው። ክልከላው የአራት ሳምንት ብቻ የሚቆይ ከሆነ አሁን ባለው የጊዜ ሰሌዳ ዋና የሆነውን የመራጮች ምዝገባ ቢያንስ በአራት ሳምንት የሚገፋው ሲሆን ምዝገባው ቢከናወን የማኅበረሰቡ ተሳትፎ፣ የምርጫው ተአማኒነት ማግኘትን እና የኦፕሬሽን ድጋፍ የሚያደርጉ ተቋማት ድጋፍን ሙሉ ለሙሉ ማግኘትን በጣም አስቸጋሪ መሆኑን ያሳያል።

    ቫይረሱ በቁጥጥር ስር ካልዋለም የመራጮች ምዝገባን ማካሄድ የማኅበረሰብ ደኅንነትን አደጋ ውስጥ የሚጥል ከመሆኑም በተጨማሪ ከማኅበረሰብ የጤና ደኅንነት ከመጠበቅ አንጻር ጥቂት እንኳን ክልከላዎች የሚኖሩ ከሆነ ይህንን ዕቅድ ወደ ተግባር መለወጥ አስቸጋሪ ያደርገዋል።

    በተጨማሪም በያዝነው ሳምንት መንግሥት ተጨማሪ እርምጃ እየወሰደ መቀጠሉ፣ እንዲሁም ቦርዱ ከጤና ሚኒስቴር ከፍተኛ ባለሙያዎች ጋር ባደረገው ውይይት እስከ ሚያዚያ መጨረሻም ሁኔታው የመሻሻል ዕድል እንደሌለ የተገለጸለት በመሆኑ፣ በዚህ የቢሆን ሁኔታ ግምት በታየው መልኩ የመራጮች ምዝገባን በተያዘለት ጊዜ ማከናወን እንደማይቻል ቦርዱ መረዳት ችሏል።

    የዳሰሳ ጥናቱ ሁለተኛ የቢሆን ሁኔታ ግምት የሚያሳየው ወረርሽኙን ለመቆጣጠር መንግሥት የሚወስዳቸው እርምጃዎች ከሚያዚያ 7 ቀን 2012 ዓ.ም. በኋላ ላልተወሰነ ጊዜ ሊቆዩ ይችላሉ፤ በመሆኑም በመንግሥት የሚደረግ ማንኛውም ከአራት ሳምንት የበለጠ ክልከላ ቢኖር ምርጫውን በተያዘለት ሕገ-መንግሥታዊ የጊዜ ሰሌዳ ማከናወን እንዳይቻል ያደርገዋል፤ ስለዚህም ወረርሽኙን መቆጣጠር በሚቻል ጊዜ ቦርዱ ዕቅዶቹ ላይ የተለያዩ ማሻሻያ ሊደርግ ይገባል የሚል ነው።

    በመሆኑም ቦርዱ እነዚህን የቢሆን ሁኔታ ግምቶች መርምሮ እንዲሁም ከባለድርሻ አካላት ጋር ካደረጋቸው ምክከሮች ያገኘውን ግብአት ታሳቢ በማድረግ የሚከተለውን ወስኗል።

    1. በተፈጠረው ሁኔታ የተነሳ ቦርዱ ባወጣው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ምርጫውን ማካሄድ የማይቻለው መሆኑን በመረዳት ያወጣውን የጊዜ ሰሌዳ በመሰረዝ በሰሌዳው መሠረት መከናወን ያለባቸው ተግባራት ለጊዜው እንዲቆሙ ወስኗል፤
    2. ቦርዱ የወረርሽኙ ሥጋት ተወግዶ ሁኔታዎች ሲመቻቹ እንደገና ግምገማ በማድረግ አዲስ የምርጫ ኦፕሬሽን ዕቅድና ሰሌዳ በማውጣት እንቅስቀሴውን የሚያስጀምር ይሆናል፤
    3. ቦርዱ ባደረጋቸው ምክክሮችና የዳሰሳ ጥናት ላይ በግልጽ የተለዩ፣ በኮቪድ-19 የማይስተጓጎሉ፣ የቦርዱን የምርጫ አፈጻጸም ዝግጁነት የሚጨምሩ፣ ሁኔታው ተቀይሮ ተቋሙ ወደ መደበኛ ተግባሩ ሲመለስ በተገቢው ሁኔታ ምርጫን ለማስፈጸም የሚያሥችል ሁኔታን የሚፈጥሩ ተግባራትን እያከናወነ መቆየት እንዳለበት ወስኗል።
    4. በሕገ መንግሥቱ በተቀመጠው መሠረት በሥራ ላይ የሚገኘው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የስልጣን ጊዜው ከሚያበቃበት አንድ ወር አስቀድሞ ቦርዱ አጠቃላይ ምርጫውን ማድረግ የማይችል መሆኑን ምክር ቤቱ ተገንዝቦ፣ ከዚህ አንጻር የሚሰጠው ውሳኔ ቢኖር ለመነሻነት ያገለግለው ዘንድ ይህ ውሳኔ እንዲሁም ቦርዱ ያደረገው የዳሰሳ ጥናት ሰነድ ለሕዝብ ተወካዮች እንዲተላለፍለት ወስኗል።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ
    መጋቢት 22 ቀን 2012 ዓ.ም

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

    Anonymous
    Inactive

    የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመከላከል የተቋቋመው “ሰው ነኝ ሌሎችንም እረዳለሁ” የተባለው ኮሚቴ፣ በመንግሥት የተቋቋመው የአማካሪ ምክር ቤት እና ኢትዮጵያ ውስጥ በሽታው የተገኘባቸው ሰዎች ያሉበት ሁኔታ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ከተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች የተወጣጡ ግለሰቦች “ሰው ነኝ ሌሎችንም እረዳለሁ” በሚል መሪ ሃሳብ የኮሮናቫይረስ ስርጭትን ለመግታት የሚሠራ ኮሚቴ አቋቋሙ። ኮሚቴው መጋቢት 19 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ የግንዛቤ ማስጨበጥና ሌሎች የእርዳታ ማሰባሰብ ሥራዎች ላይ እንደሚሠራ ነው ያስታወቀው።

    ተነሳሽነቱን ወስዶ ኮሚቴውን ያዋቀሩት ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ (አኢጋን) የተባለው መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት መሥራችና ሊቀመንበር የሆኑት አቶ ኦባንግ ሜቶ “ኮሮናቫይረስ ዘር፣ ቀለምና ሀይማኖት ሳይለይ የሰው ልጅን በስፋት እያጠቃ ይገኛል” ብለዋል።

    ኮሮናቫይረስ የተከሰተባቸው አገሮች በራሳቸው መንገድ ችግሩን ለመፍታት እየተንቀሳቀሱ መሆኑን አስታውሰው፥ ”እኛ ኢትዮጵያውያን የሌሎችን እርዳታ ሳንጠብቅ ስርጭቱን መግታት እንችላለን” ብለዋል አቶ ኦባንግ። “ይህ እውን እንዲሆን ግን ራሳችንን በመጠበቅ አንድ ሆነን መቆም ይገባል” በማለት ጨምረው አስገንዝበዋል።

    ከአካለዊ ንክኪ ርቀን በመንፈስና ተግባር አንድ ሆነን የኮሮናቫይረስ ስርጭትን መግታት ይገባናል ሲሉ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተወጣጡ የኮሚቴው አባላትም ተናግረዋል።

    ሙዚቀኛ ዘለቀ ገሰሰ፥  ወጣቶችን ኮሮና አይዝም የተባለውን የተሳሳተ ግንዛቤ ማሰተካከልን እና ሕብረተሰቡ ሊያውቃቸው የሚገቡ ትክክለኛ መረጃዎች በኪነ-ጥበብ ለሕዝቡ ለማድረሰ እንደሚሠራ አሰታውቋል።

    ከዚሁ ጋር በተያያዘ በጤና ሚኒስቴር የሚመራውን የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የመከላከልና የመቆጣጠር ሥራ ለማጎልበትና ለማፍጠን በጤና ሙያ ማኅበራት የተመሠረተው የአማካሪ ምክር ቤት ሥራ ጀምሯል። ውጤታማ ሥራ ለመሥራትም በስድስት ግብረ ኃይሎች የተዋቀረ ሲሆን እነሱም፦

    1. ማኅበረሰቡን ስለ በሽታው መተላለፊያና መከላከያ መንገዶች በሳይንሳዊ ዘዴ ማስተማርና ማንቃት፣
    2. ጤና ተቋማት የባለሙያውንና የታካሚውን ደኅንነት በጠበቀ መንገድ የሕክምና አገልግሎት እንዲሰጡ ማዘጋጀት፣
    3. የሕክምና መሣሪያዎች መድኃኒቶችና ግባቶች አቅርቦት እንዲሻሻል ማድረግ፣
    4. የወረርሽኝ ስርጭት ቅኝትና በሽታው ከያዛቸው ሰዎች ጋር የተገናኙ ሰዎችን ፈልጎ ማግኘት፣
    5. የወረርሽኙንመጠነስርጭት፣ማንንእንዲሚያጠቃ፣የትበብዛትእንደሚከሰት፣በጊዜሂደትያለውንለውጥናለወረርሽኙአጋላጭሁኔታዎችንማጥናትናበመረጃማጠናቀር፣እና
    6. ከወረርሽኙጋርተያይዘውየሚመጡየአዕምሮጤናእናየሥነ-ልቦናእናማኅበራዊጫናዎችንመፍታትናቸው።

    ከኮሮናቫይረስ ጋር በተያያዘ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በሰጠው ወቅታዊ መግለጫ፥ ማንኛውም ከውጭ ሀገር ወደ ኢትዮጵያ የሚገባ መንገደኛ በሆቴል ውስጥ ለ14 ቀናት ተለይቶ እንዲቆይ በተወሰነው መሠረት እስካሁን ስድስት መቶ ሰላሳ ስድስት (636) መንገደኞች ወደ ሀገራችን የገቡ ሲሆን፥ በተመረጡ አስር ሆቴሎች ማቆያ ውስጥ ይገኛሉ።

    መንገደኞቹ ባሉባቸው ሁሉም ሆቴሎች የጤና ባለሙያዎችን በመመደብ የጤና ክትትል እየተደረገላቸው ይገኛል።

    በሌላ በኩል ከላይ የተገለፀው ውሳኔ ከመተላለፉ በፊት ከተለያዩ ሀገራት ወደ ኢትዮጵያ የገቡ ስምንት መቶ ሰባ ሶስት (873) ሰዎች በቤታቸው ሆነው በስልክ ለ14 ቀን በጤና ባለሙያዎች የጤና ክትትል እየተደረገላቸው ይገኛል። ከዘሁ ጋር በተያያዘ ለ14 ቀናት ክትትል ሲደረግላቸው ቆይተው የበሽታው ምልክት ያልታየባቸው ሁለት ሺ ዘጠና (2,090) ሰዎች ክትትላቸው እንዲረቋጥ ተደርጓል።

    ባለፉት 24 ሰዓት ውስጥ ይህ መረጃ እስከተጠናከረበት ሰዓት ድረስ የኮሮናቫይረስ በሽታ ምልክት ያሳዩ ሰባ ዘጠኝ (79) ሰዎች የላብራቶሪ ምርመራ የተደረገላቸው ሲሆን ሁሉም ከቫይረሱ ነፃ መሆናቸው ተረጋግጧል።

    በሀገራችን እስካሁን አሥራ ስድስት (16) ሰዎች የኮሮናቫይረስ እንደተገኘባቸው በላቦራቶሪ ምርመራ መረጋገጡ ኢንስቲትዩቱ እና የጤና ሚኒስቴር በመግለጫዎቻቸው ማሳወቃቸውን ተዘግቧል። ከእነዚህ አሥራ ስድስት (16) ታማሚዎች መካከል ሁለቱ ወደ ሀገራቸው የተመለሱ ሲሆን አሥራ አራት (14) ታማሚዎች በለይቶ ሕክምና መስጫ ማዕከል የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው ይገኛሉ። የኮሮናቫይረስ ከተገኘባቸውና የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው ከሚገኙ ታማሚዎች ውስጥ አንድ (1) ታማሚ በድጋሚ በተደረገላቸው የላብራቶሪ ምርመራ ከኮሮናቫይረስ ያገገሙ መሆናቸው የተረጋገጠ ቢሆንም ለጥንቃቄ ሲባል በለይቶ ማቆያ ለ14 ቀናት ተጨማሪ የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው የሚቆዩ ይሆናል።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት/ የጤና ሚኒስቴር/ አኢጋን/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኮሮናቫይረስ

    Semonegna
    Keymaster

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ እና ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን አስመረቁ

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ 34 የሕክምና ዶክተሮችን ጨምሮ ለሁለተኛ ዙር ያሰለጠናቸውን 1233 ተማሪዎቸ መጋቢት 5 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመርቋል።

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ በዋና ግቢው እና በዱራሜ ካምፓስ 6 ኮሌጆች በመጀመሪያ ዲግሪ፣ በሁለተኛ ዲግሪ እና በተከታታይ ትምህርት በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ነው ያስመረቀው።

    በምርቃቱ ሥነ-ሥርዓት ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የሳይንስና እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ፥ ኢትዮጵያ ለእርሷ እና ለዜጎቿ ክብር እና ፍቅር ያለው ባለሙያ ያስፈልጋታል ብለዋል። አክለውም ተመራቂዎች ያገኙትን እውቀት በተገቢው ሁኔታ ለማኅበረሰብ ለውጥ እንዲያውሉት አሳስበዋል።

    ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ መጠናቀቅ ድጋፋቸውን በማጠናከር የአገሪቱን ሉዓላዊነት እንዲያስረግጡም ዶ/ር ሳሙኤል ጠይቀዋል።

    የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሐብታሙ አበበ በበኩላቸው፥ ተመራቂዎች ያገኙትን እውቀት ወደ ተግባር በመቀየር ሙያዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። አሁን ላይ በሀገሪቱ በተለያየ መልኩ ከሚንፀባረቀው የአስተሳሰብ እና የአመለካከት ኋላ ቀርነት በመራቅ ለኅብረተሰብ ዕድገት እና ብልፅግና እንዲረባረቡ ጠይቀዋል።

    በሌላ በኩል ደግሞ ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ለመጀመሪያ ጊዜ በሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም ያሰለጠናቸውን 33 የሕክምና ዶክተሮችን አስመረቀ።

    ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ለመጀመሪያ ጊዜ በሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም (hybrid innovative curriculum) በሕክምና ዶክትሬት ያሰለጠናቸውን 33 ተማሪዎች በተመሳሳይ ቀን አስመርቋል።

    በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ለተማሪዎቹ የሥራ መመሪያ የሰጡት የሳይንስ እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ፥ ተመራቂዎቹ ቃለመሀላ በገቡለት የሕክምና ሥነ-ምግባር በመታገዝ ቅን አገልጋዮች እንዲሆኑ አሳስበዋል። ከዚህም ባለፈ በተግባር በተደገፈው ሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም የቀሰሙትን የሕክምና ትምህርት የሀገሪቱን ብሎም የዓለምን ሕዝብ ስጋት ላይ ከጣሉ ዘመን-ወለድ የጤና ችግሮች ኅብረተሰቡን ለመታደግ ተግባራዊ እንዲያደርጉት ጥሪ አቅርበዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አነጋግረኝ ጋሻው በበኩላቸው፥ ተመራቂዎቹ ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ በውጤት በታገዘው የቅይጥ ፈጠራ-አከል ሥርዓት (ሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም) ለመጀመሪያ ጊዜ ያሰለጠናቸው በመሆናቸው ማኅበረሰቡን ከጤና እክሎች ከመታደግ ባለፈ በምርምር ዘርፍ በመሰማራት ለሀገር ብልፅግና የድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።

    ዩኒቨርሲቲው በዕለቱ 26 የማስተርስ ዲግሪ (ሁለተኛ ዲግሪ) ተማሪዎችንም አስመርቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና የውሃ፣ መስኖ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር የአሜሪካ የግምጃ ቤት ዲፓርትመንት ሴክሬታሪ በየካቲት 21 ቀን 2012 ዓ.ም. (እ.ኤ.አ. በ28 February 2020) የታላቁን የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በተመለከተ ኢትዮጵያ ያልተሳተፈችበትን ስብሰባ ተከትሎ የወጣውን ጋዜጣዊ መግለጫ በከፍተኛ ቅሬታ ተመልክተውታል።

    ስብሰባው የተካሄደው ኢትዮጵያ አስቀድማ ለግብጽ፣ ለሱዳን እና ለአሜሪካ ስብሰባው ለሌላ ጊዜ እንዲተላለፍ አሳውቃ እያለ ነው።

    የግድቡ ባለቤት የሆነችው ኢትዮጵያ በመርሆዎች መግለጫ ስምምነቱ መሰረት የግድቡን ሙሌት ከግንባታው ትይዩ በፍትሐዊ እና ምክንያታዊ አጠቃቀም እና ጉልህ ጉዳት ያለማድረስ መርሆዎች መሠረት የምታከናውን ይሆናል።

    ኢትዮጵያ የግድቡን የመጀመሪያ ሙሌት እና የውሃ አለቃቅ መመሪያ እና ደንብ ለማዘጋጀት የሚደረገው ድርድር ተጠናቋል በሚል የተሰጠውን መግለጫ አትቀበልም።

    በዋሽንግተን ዲሲ የግብጽ ዐረባዊት ሪፐብሊክ ፈርሞበታል የተባለው “ረቂቅ” የሦስቱ ሀገራት የድርድርም ሆነ የሕግ እና ቴክኒክ ቡድኖች ውይይት ውጤት አይደለም። የቴክኒክ ጉዳዮች ድርድሩም ሆነ የሕግ ማዕቀፍ ዝግጅቱ ላይ የሚደረገው ድርድር አልተጠናቀቀም።

    ኢትዮጵያ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የመጀመሪያ ሙሌት እና የውሃ አለቃቅ መመሪያ እና ደንብ የሚዘጋጀው በሶስቱ ሀገራት ብቻ እንደሆነ አቋሟን ቀድማ አሳውቃለች።

    ኢትዮጵያ ግብጽ እና ሱዳን በሚያውቁት እና በተስማሙበት እንዲሁም በመርሆዎች መግለጫ ስምምነት መርህ አንቀጽ ስምንት አድናቆታቸውን በሰጡት ሂደት መሠረት ሁሉንም የግድብ ደህንነት የሚመለከቱ ጉዳዮች በዓለምአቀፍ የባለሙያዎች ቡድን ምክረ ሃሳብ መሰረት የተሰጡትን ምክረ-ሃሳቦች መፈጸሟን ትቀጥላለች።

    የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የመጀመሪያ ሙሌት እና የውሃ አለቃቅ መመሪያ እና ደንብን ለማዘጋጀት ቀሪ መሰረታዊ ልዩነቶችን ለመፍታት ኢትዮጵያ ከግብጽ ዐረባዊት ሪፐብሊክ እና ከሱዳን ሪፐብሊክ ጋር የጀመረችውን ሂደት ለመቀጠል ቁርጠኛ ናት።

    ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተያያዘ፥ የኢትዮጵያ መንግስት ሕዳሴ ግድብን በተመለከተ ብሔራዊ ጥቅምን የሚነካ ድርድር እንደማያደርግ የሚስትሮች ም/ቤት አስታወቀ።

    ታላቁ የሕዳሴ ግድብን የሚመለከት ማንኛውም ነገር የኢትዮጵያን ፍላጎትና ጥቅም በሚጠብቅ መልኩ ብቻ እንደሚከናወን የሚስትሮች ምክር ቤት ገልጿል።

    ምክር ቤቱ በዛሬው ዕለት ባካሄደው ስብሰባ ሕዳሴ ግድብን በተመለከተ ብሔራዊ ጥቅምን የሚነካ ድርድር የኢትዮጵያ መንግስት እንደማያደርግ አስታውቋል።

    በዛሬው ዕለት ባካሄደው 80ኛ መደበኛ ስብሰባው ምክር ቤቱ የኮሮና ቫይረስ መከላከል ስራዎችን የሚከታተል ስድስት አባላት ያሉት ብሔራዊ የሚኒስትሮች ኮሚቴ ማቋቋምን ጨምሮ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል።

    የብሔራዊ የሚኒስትሮች ኮሚቴው ስድስቱ አባላትም የሰላም ሚኒስትር ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚል፣ የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ፣ የገቢዎች ሚኒስትር ወይዘሮ አዳነች አቤቤ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ገዱ አንዳርጋቸው፣ የትራንስፖርት ሚኒስትር ወይዘሮ ዳግማዊ ሞገስ እና የጤና ጥበቃ ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሊያ ታደሰ ናቸው።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    Ethiopian government's statement regarding the negotiations on GERD የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ

    Semonegna
    Keymaster

    ዓለምን እጅግ ያሰጋው የኖቬል ኮሮና ቫይረስ የተጠቂዎች ቁጥር እጅግ አሻቅቧል፤ ቻይና ውስጥ በአንድ ቀን ብቻ 57 በበሽታው የተጠቁ ሰዎች ሞተዋል። የተለያዩ ሀገራት ዜጎቻቸውን ከዉሃን ከተማ ማስወጣት ጀምረዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የዓለም ጤና ድርጅት የኖቭል ኖቬል ኮሮና ቫይረስ በሽታ ከታሕሳስ 21, 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በቻይና ዉሃን (Wuhan) ግዛት የተከሰተ መሆኑን ካሳወቀ ጀምሮ ይህ ዜና እስከተጠናከረበት ሰዓት ደረስ (በኢትዮጵያ ቀንና ሰዓት አቆጣጠር እስከ ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም. ከምሽቱ ሦስት ሰዓት ድረስ) በአጠቃላይ 17,488 ሰዎች በቫይረሱ የተያዙ ሲሆን፥ ከእነዚህ ውስጥ 2,298 (13%) ታማሚዎች በሽታው ክፉኛ የጸናባቸው (in critical conditions) ናቸው። እስካሁን ድረስ በሽታው የተገኘባቸው የሀገራc ቁጥር ቻይናን ጨምሮ 24 የደረሰ ሲሆን፣ በበሽታው የሞቱት ሰዎች ቁጥር 362 ደርሷል (361 የሞቱደርሷል ቻይና ውስጥ ሲሆን፣ አንዱ ብቻ ፊሊፒንስ ውስጥ ነው)። ሰኞ ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም. ብቻ 57 በበሽታው የተጠቁ ሰዎች ቻይና ውስጥ ሞተዋል።

    በሀገረ ቻይና እንዲሁ ቫይረሱ ለመጀመሪያ ጊዜ በተስፋፋባቸው ግዛቶች ምንም ዓይነት የመግባትና የመውጣት አንቅስቃሴ እንዳይደረግ ቢታገድም የስርጭቱ መጠን ከሚታሰበው ባላይ አሳሳቢ አየሆነ እንደመጣ ለማወቅ ተችሏል።

    ይህ መላ ዓለምን እጅግ በሚያሰጋ ሁኔታ እየተስፋፋ እየተሰጨና፣ ብሎም ቻይና ውስጥ በበሽታው የሚሞቱት ሰዎች ቁጥር እያሻቀበ ያለው ኖቬል ኮሮና ቫይረስ ወደ ቻይና የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን (በተለይም የ አየር በረራዎችን) መቆጣጠር ጀምሯል። ከችግሩ አሳሳቢነት አንፃር ብዙ ጎረቤት ሀገራት ከቻይና ጋር የሚያዋስናቸውን ድንበር ለመዝጋት የተገደዱ ሲሆን፤ ሌሎች ሃገራትም ወደቻይና የሚደረጉ ማንኛውም በረራዎችን ለማቆም እንደተገደዱ ነው። ለምሳሌ የጀርመኑ ግዙፍ አየርመንገድ ሉፍታንዛ ወደ ቻይና የሚያደርጋቸውን በረራዎች (ቢያንስ እስከ የካቲት 1 ቀን 2012 ዓ.ም.) ሙሉ ለሙሉ አቁሟል። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች (UAE) ወደ ዋና ከተማ ቤጂንግ ከሚደረጉ በረራዎች በስተቀር ሌሎች ወደ ቻይና የሚደረጉ ሁሉንም በረራዎች እንደምትሰርዝ አስታውቃለች። ካናዳ በበኩሏ ዜግቿን ኖቬል ኮሮና ቫይረስ ለመጀመሪያ ጊዜ ከተነሳባት ሁቤይ (Hubei) ግዛት ከምትገኘው ዉሃን (Wuhan) ከተማ ማስወጣት ጀምራለ፤ ሌሎች ሀገራትም ተመሳሳይ እርምጃ ለመውሰድ እንቅስቃሴ ጀምረዋል።

    ቫይረሱ በሀገራቸው በሚኖሩ ዜጎች ላይ መታያቱን ያረጋገጡት የጂ-7 (G-7) ሀገራትም (ካናዳ፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ጣልያን፣ ጃፓን፣ እንግሊዝ እና አሜሪካ) በችግሩ ላይ በትብብር በመሥራት ምላሽ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን የጀርመን የጤና ሚኒስቴር ጄንስ ፋህን በትላንትናው ጥር 24 ቀን 2012 ዓ.ም. ተናግረዋል።

    ወደ ሀገራችን ስንመለስ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ከኢፌዴሪ ጤና ሚኒስቴር እና ሌሎች አጋር ድርጅቶች ጋር በመሆን ለኖቬል ኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ዝግጅት በማድረግ ላይ መሆኑን ሰኞ ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል። እንደመግለጫው እየተወሰዱ ካሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ውስጥ ብሔራዊ ታስክ ፎርስ እና በኢንስቲትዩቱ ለኮሮና ቫይረስ ድንገተኛ አደጋዎች ምላሽ የሚሰጠው ማዕከል ሥራ ጀምረዋል። ከኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት፣ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ፣ ከኦሮሚያ ክልል ጤና ቢሮ፣ ከቦሌ አየር መንገድ፣ ከግልና ከመንግስት ጤና ተቋማት ለተውጣጡ ተሳታፊዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ተሰጥቷል። በተመሳሳይ ጥር 25 ቀን 2012 ዓ.ም. ለ200 የሚሆኑ የሆስፒታል አመራሮች እና ባለሞያዎች በጤና ሚኒስተር አማካኝነት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጥቷል። በቦሌ ኢንተርናሽናል ኤርፖርት እና 27 የተለያዩ የድምበር መግቢያ እና መውጫ ኬላዎች ላይ የሚደረገው የማጣራት ምርመራ በተጠናከረ ሁኔታ እየቀጠለ ይገኛል። የማጣራት ምርመራው ከፍተኛ የሙቀት መጠን ያላቸውን ተጓዦች የሚለይ ሲሆን ይሄም የቫይረሱ የበሽታ ምልክት የሚያሳዩትን ለመለየት ይረዳል።

    በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ውስጥ አራት ሰዎች (አንድ ቻይናዊ እና ሦስት ኢትዮጵያውያን) በኖቬል ኮሮና ቫይረስ በሽታ ተጠርጥረው፥ አንድ በአክሱም እና ሦስት በቦሌ ጨፌ በለይቶ ማቆያ ክትትል እየተደረገላቸው ሲሆን፥ ናሙናቸው ተወስዶ ወደ ደቡብ አፍሪካ ለመላክ ዝግጅት ተጠናቋል።

    የኖቬል ኮሮና ቫይረስ አስካሁን ድረስ ምንም አይነት ፈዋሽ መድኃኒት ወይም ክትባት ያልተገኘለት ሲሆን በዋናነት የመተንፈሻ አካላትን በማጥቃት ሰዎችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለሞት የሚዳርግ በሽታ ነው። የኖቬል ኮሮና ቫይረስ እንደአውሮፓውያኑ በ2003 በቻይና ከተከሰተው “ሳርስ” በሽታ ጋር የመተንፈሻ አካልን በማጥቃት በኩል ተመሳሳይ ቢመስልም፤ የስርጭት መጠኑ እና የሚያደርሰው ጉዳት ግን እጅግ ከፍተኛ መሆኑ የሚለየው ጉዳይ ነው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ኖቬል ኮሮና ቫይረስ

    Anonymous
    Inactive

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – የውጭ ጉዲፈቻ በመታገዱ የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻ መጨመሩን የአዲስ አበባ ሴቶችና ሕፃናት ጉዳይ ቢሮ አስታወቀ።

    በቢሮው የሕፃናት ድጋፍ ክብካቤ ቡድን መሪ አቶ ኢያሱ ሳሙኤል በተለይ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደተናገሩት፤ ብሔራዊ የሕፃናት ፖሊሲ ተቀርጾ ከወጣበት ከ2009 ዓ.ም. ጀምሮ የውጭ ሀገር ጉዲፈቻ በመታገዱ የሀገር ውስጡ እየጨመረ መጥቷል።

    ከእገዳው በፊት በተለያየ መንገድ ከሀገር ይወጡ የነበሩት ሕፃናት ቁጥር ከፍተኛ ነበር የሚሉት አቶ ኢያሱ፥ የሀገር ውስጡ ግን በአዲስ አበባ በ2007 ዓ.ም. ስድስት በአደራ ሶስት በጉዲፈቻ እንዲሁም በ2008 ዓ.ም. አምስት በአደራ ብቻ ነበር።

    ከአዋጁ በኋላ ግን በየአመቱ ቁጥሩን በመጨመር በ2009 ዓ.ም. በአደራ 160 በጉዲፈቻ 150፤ በ2010 ዓ.ም. በጉዲፈቻ 148 በአደራ 138 እንዲሁም በ2011 ዓ.ም. በጉዲፈቻ 172 በአደራ 156 ማስተላለፍ መቻሉን ተናግረዋል።

    እንደ አቶ ኢያሱ ገለጻ፥ እገዳው የተደረገው ሕፃናቱ በማያውቁት ባህል፣ ቋንቋና ማኅበረሰብ ውስጥ ማደጋቸው ከማንነት ጋር ተያይዞ የሚነሱባቸው ማኅበራዊና ሥነ ልቦናዊ ቀውሶች ስለሚያጋጥማቸው ነው። ለክትትልና ለቁጥጥር አመቺ ስለማይሆን፣ ብሎም በሀገር ውስጥ መሥራት እየተቻለ ለውጭ መደረጉ በሀገር ገጽታ ላይ የሚያመጣውም ተጽዕኖ በመኖሩ መሆኑን ጠቁመዋል።

    እስካሁንም የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻ ዝቅተኛ ሊሆን የቻለው በአግባቡ ባለመሠራቱና የግንዛቤ ክፍተት ስለነበር ሲሆን፥ በአሁኑ ወቅት ግን ቁጥሩ ከመጨመሩም ባለፈ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እና ባለቤታቸው ወ/ሮ ዝናሽ ታያቸውን ጨምሮ ሌሎች ታዋቂ ሰዎችም በጉዲፈቻ ልጆች ከወሰዱ በኋላ ወሳጅ ቤተሰቦች ወረፋ እስከመጠበቅ መድረሳቸውን ጠቁመዋል።

    አቶ እያሱ ጨምረው እንደተናገሩት፥ ቢሮው አምስቱን የጉዲፈቻ የአደራ፣ የማዋሀድ፣ የማኅበረሰብ አቀፍ ድጋፍና አማራጭ የድጋፍ አገልግሎቶች በመጠቀም ሕፃናትን ከችግር የመታደግና ተጠቃሚ የማድረግ ሥራ ይሠራል።

    ለዚህም በስሩ ያሉትን ቀጨኔ የሴቶች፣ ኮልፌ የወንዶች፣ ክበበ ጸሐይ የጨቅላ ሕፃናት ማቆያና ክብካቤ ማዕከል እንዲሁም በወንጀል ውስጥ ገብተው የተገኙ ታዳጊዎች ተሀድሶ ማዕከላትን ይጠቀማል። በተጨማሪም ሰላሳ የሚደርሱ ከቢሮው ጋር በስምምነት የሚሠሩ እንደ አበበች ጎበና እና ሰላም የሕፃናት መንደር ያሉ በተመሳሳይ ተግባር የተሰማሩ የሕፃናት ማሳደጊያ ተቋማት ጋርም በትብበር የሚሠራ ሲሆን ክትትልና ቁጥጥርም ያደርጋል።

    የሕፃናቱን ደኅንነትና ሥነ ልቦና ለማስጠበቅና ለክትትል እንዲያመች ለወሳጅ ቤተሰቦች መስፈርቶች ተቀምጠዋል የሚሉት አቶ እያሱ፥ ከነዚህም መካከል አዲስ አበባ ነዋሪ መሆን፣ ሙሉ የጤና ምርምራ ማድረግ፣ ገቢው ከአምስት ሺ ብር በላይ የሆነና ቢቻል ሌላ የገቢ አማራጭ ያለው፣ የራሳቸው ቤት ያላቸው ቢሆን ይመረጣል፥ ከወንጀል ነጻ አሻራ የሚያቀርብ፣ የጋብቻ የምስክር ወረቀት (marriage certificate) እና የተጋቢዎች ስምምነት፣ አካባቢው ለሕፃናቱ ምቹ መሆን እንዲሁም ወሳጆቹ ቤተሰቦች ከማኅበረሰቡ ጋር ያላቸው ግንኙነት ሰላማዊ መሆኑ፣ ከእድር፣ ከሃይማኖት ተቋማት፣ ወይንም ከወረዳ ሴቶችና ሕፃናት ቢሮ እንዲያቀርቡ እንደሚደረግም ጠቁመዋል።

    አቶ እያሱ እንዳሉት፤ የሕፃናት ቤተሰብ መገኘት አለመገኘቱን ለማረጋገጥ የፖሊስ ሪፖርት ይዘገያል፤ የጤና ምርመራን በተመለከተም አጠቃላይ ምርመራ ውጤት በጽሁፍ እንዲሰጥ ሲጠየቅ በከተማው ካሉ ጤና ጣቢያዎች ፈቃደኛ ሆኖ የተገኘው አንድ ብቻ ነው። ከሆስፒታሎችም ፈቃደኛ የሚሆኑት ሦስት ብቻ ናቸው፤የምርመራ ውጤት እየሰጡ ያሉት በቃል ብቻ ነው። ይሄ ቢሮውን ብቻ ሳይሆን ቤተሰብንም ለእንግልት እየዳረገ በመሆኑ ከጤና ሚኒስቴር ጋር የመግባቢያ ሰነድ በመፈራረም በየክፍለ ከተሞቹ ለማስቀመጥ በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛሉ።

    በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት አብዛኛው የመራጮች ፍላጎት ሴት በመሆኑ ወንዶች ሳይመረጡ የሚቆይበት ሁኔታ አለ። ይህንንም ለማስተካከል የማግባባት ሥራ እየተሠራ ይገኛል ሲሉ ተናግረዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻ

    Anonymous
    Inactive

    ዲላ ዩኒቨርሲቲ እና መቱ የኒቨርሲቲ በአጠቃላይ ከሰባት ሺህ በላይ ተማሪዎችን አስመረቁ
    —–

    ዲላ/ መቱ – ዲላ ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ ያስተማራቸውን 4 ሺህ 726 ተማሪዎችን አስመረቀ። መቱ የኒቨርሲቲም በበኩሉ በተለያዩ የሙያ መስኮች ያስተማራቸውን 2 ሺህ 323 ተማሪዎችን በመጀመሪያ ዲግሪ አስመርቋል።

    የዲላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ችሮታው አየለ ዩኒቨርሲቲው በተያዘው ዓመት 4 ሺህ 216 ተማሪዎችን በመጀመሪያ ዲግሪ ቀሪዎቹን በሁለተኛ ዲግሪ ለምረቃ ማብቃቱን ተናግረዋል። ከአጠቃላይ ተመራቂ ተማሪዎች ውስጥ 1 ሺህ 561 የሚሆኑት ሴቶች መሆናቸውን አመልክተዋል።

    የማኅበረሰቡን ችግር የሚፈቱና አገራዊ ፋይዳ ያላቸው ከ50 በላይ አነስተኛና 12 መካከለኛ ምርምሮች መካሄዳቸውን አስረድተዋል፤ የጥናት ውጤቶችንም ለማህበረሰቡ ጥቅም ለማዋል ጥረት መደረጉን ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል። በአከባቢው የሚገኘውን የይርጋጨፌ ተፈጥሯዊ ቡና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል የምርምር ማዕከል ለማቋቋም እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል።

    በቀጣዩ የትምህርት ዘመን የቡና ሳይንስና ምጣኔ ሃብት መርሐ ግብር ለመክፈት የሥርዓተ ትምህርት ቀረጻን ጨምሮ ሌሎች ዝግጀት ማጠናቀቁን ተናግረዋል።

    የኢፌዴሪ ሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ “የዛሬ ስኬታችሁ የመጨረሻ ግባችሁ አይደለም” በማለት ምሩቃን ራሳችሁን ለተሻለ ስኬት እንዲያዘጋጁ አሳስበዋል።

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሕዝቡን አኗኗር ለመለወጥ ያበረከቱት አስተዋጽኦ ዝቅተኛ መሆኑን የጠቆሙት ሚኒስትር ዴኤታው፥ የትምህርት ጥራትን ጨምሮ በመስኩ የሚስተዋሉ ድርብርብ ችግሮችን ለመፍታት መንግሥት የሚያደርገውን ጥረት እንዲያግዙ ጠይቀዋል።

    ከተመራቂዎች መካከል ከጤና መኮንን ትምህርት ክፍል በከፍተኛ ማዕረግ የተመረቀችው ጸዮን ሙላት ጊዜዋን በአግባቡ በመጠቀም ውጤታማ መሆኗን አስረድታለች። “የጤና ሙያ ህብረተሰቡን በጥንቃቄ ማገልገልን የሚጠይቅ ነው” ያለችው ተመራቂዋ፣ በምትሰማራበት የሙያ መስክ ሕዝብና መንግስት በታማኝነት ለማገልገል መዘጋጀቷን ገልጻለች።

    በተመሳሳይ መቱ ዩኒቨርስቲ በመቱና በደሌ ካምፓሶች በተለያዩ የሙያ መስኮች ያስተማራቸውን 2 ሺህ 323 ተማሪዎች ትናንትና ሰኔ 23 ቀን 2011 ዓ.ም. በመጀመርያ ዲግሪ አስመርቋል። ከአጠቃላይ ተመራቂዎች መካከል 988 የሚሆኑት ሴት ምሩቃን መሆናቸው ታውቋል።

    የግብርና ሚኒስቴር ዴኤታና የዩኒቨርስቲው የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ሳኒ ረዲ በተጀመረው አገራዊ የለውጥና የእድገት ጉዞ ተመራቂዎች በትምህርት ቆይታቸው የቀሰሙትን ዕውቀት በሚሰማሩበት የሙያ መስክ ወደ ተግባር መቀየር እንዳለባቸው አሳስበዋል።

    በነርሲንግ ትምህርት የተመረቀው አንዋር ታጁዲን እንዳለው በተቀጣሪነትም ይሁን በግል ሥራ ፈጠራ ቀስሞ የወጣውን ዕውቀት ወደ ተግባራ ለመቀየር ተዘጋጅቷል።

    በማኔጅመንት እንፎርሜሽን ሲስተም የትምህርት መስክ የተመረቀው ቴዎድሮስ ፍስሃ፥ ለግል ሥራ ፈጠራ ቅድሚያ እንደሚሰጥ አስረድቷል።

    በሕግ ትምህርት የተመረቀች ፈትያ አብዱልመጂድ በበኩሏ፥ በተማረችበት የሙያ መስክ ኅብረተሰቡን በቅንነት ለማገልገል መዘጋጀቷን ገልጻለች።

    ከተመራቂዎቹ ውስጥ 2 ሺህ 52 የሚሆኑት በመቱ ዋናው ግቢ የተቀሩትን ደግሞ በበደሌ ግብርናና ደን ሳይንስ ኮሌጅ በተፈጥሮና ኮምፒዩቲሽናል ሳይንስ፣በጤና፣ በቢዝነስና ኢኮኖሚክስና በምህንድስና መስኮች ትምህርታቸውን የተከታተሉ ናቸው።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የኢፌዴሪ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ትምህርት የማቆም አድማ ላይ የተሰማሩ የሕክምና ተማሪዎችን በተመለከተ ያወጣው መግለጫ

    በተወሰኑ ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙ የመጨረሻ ዓመት (intern) ተማሪዎችና ስፔሻሊቲ (resident) ተማሪዎች ላነሱዋቸው የተለያዩ ጥያቄዎች ክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ከሴክተሩ ባለሙያዎች እና ተማሪዎች ጋር ሲወያዩ ተማሪዎች ላነሷቸው ጥያቄዎች በሰጡት አመራር የተለያዩ እርምጃዎች ተወስደዋል።

    በዚሁ መሠረት፦

    1. የመጀመሪያ ዲግሪ ተማሪዎችን በተመለከተ የሕክምና ተማሪዎች እንደ ሌሎች ተማሪዎች የወጣባቸውን ትክክለኛ ወጪ እንዲጋሩ (cost sharing) እና ከዚህ በፊት አምስት መቶ ሺህ (500,000) ብር ይፈርሙ የነበሩት እንዲቀር መደረጉ፤
    2. የተግባር ትምህርት አተገባበርን በተመለከተ የአዳርና ለረዥም ጊዜ በሥራ ላይ መቆየት ጋር ተያይዞ የሥርዓተ ትምህርት ፍተሻ እንዲደረግና የውሳኔ ሃሳብ እንዲቀርብ፤
    3. የማስተማርያ ሆስፒታሎችን ለሥራ ምቹ ማድረግንና ተያያዥነት ያላቸውን ጥያቄዎች በተመለከተ ተቋማት ባላቸው አቅም በፍጥነት እርምጃ እንዲወስዱ እየተደረገ መሆኑን በተለያዩ አካላት መገለጫ መሰጠቱ ይታወሳል።

    በተጨማሪም እነዚህንና ሌሎች ጉዳዮችን በዝርዝር አጥንቶ ዘላቂ መፍትሔ ለመሰጠት አራት ግብረ ሃይል ተቋቁመው ወደ ሥራ ገብተዋል። ይህ እንዳለ ሆኖ በጥቂት ዩኒቨርሲቲዎች ትምህርት ያቋረጡ ተማሪዎች ተስተውለዋል። ይህ በፍጹም ተቀባይነት የሌለው መሆኑን ተገንዝበው ተማሪዎቹ በፍጥነት ወደ ትምህርት ገበታቸው እንዲመለሱ እያልን ከሰኞ ግንቦት 11 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ ትምህርታቸው የማይመለሱትን ተማሪዎች ተቋማት ባላቸው የመማር ማስተማር (academic) ሕግ ቀጣይ እርምጃ እንዲወስዱ መመሪያ የተላለፈ መሆኑን እንገልጻለን።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የሕክምና ተማሪዎችን


    Semonegna
    Keymaster

    መንግሥት ሆይ፥ የጤና ባለሙያውን ጥያቄ ከልብህ አድምጥና መፍትሄ ስጥ
    (ዶ/ር አክሊሉ ደበላ)

    አሁን ነገሮች ወዴት እያመሩ እንደሆነ ሁሉም እያየው ነው። አነሰም በዛ መንግሥትም በዚህ ምክንያት መጨነቁ አልቀረ። በዚህ ችግር የሚነካካ አካል ብዙ እንደሆነም አምናሁ። የጤና ባለሙያው፣ መንግሥትና ሕዝብ ሳይወዱ በግድ ባለጉዳዮች ናቸው። የባለሙያው ጥያቄ ግልጽ ሆኖ ቀርቧል። በዚህ ጥያቄ ላይ የተለያየ አስተያየት ያላቸው ሰዎች አሉ። የሚሰጡትም አስተያየቶች ነገሩን የከፋ እንዳያደርጉ መጠንቀቅ ከሁሉም ይጠበቃል።

    የሐኪሙ ጥያቄ ዛሬ የበቀለ የሚመስላቸው ተሳስተዋል። ጥያቄውም ሆነ ተግባር ያልታየበት የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር መልስ ሲንከባለሉ ቆይተው ዛሬ ወደ አደባባይ የወጡ ናቸው። “እስከዛሬ የት ነበራችሁ?” ማለት ቢቻልም በጥልቅ ሲታሰብ ልክ አይሆንም። የመቶ ዓመት ጥያቄ እንኳን ቢሆን የሆነ ጊዜ በሥርዓቱ መመለስ አለበት። ችግሮቹን የፈጠረ የዶ/ር አቢይ መንግሥት ነው ያለ የለም፣ መመለስ ያለበት ግን አሁን እሱ ነው። ሕዝቡ በደፈናው በሐኪሙ ላይ መጥፎ አስተያየት ከመስጠቱ በፊት ነገሩን አዙሮ አዟዙሮ ቢያስብ መልካም ነው። ዛሬ ገንፍሎ የወጣው ጩኸት የፖለቲካ ሁኔታ ምቹ ስለሆነ ብቻ አይደለም (መሆኑ አንድ ነገር ቢሆንም)፤ ይልቅስ እየተባባሰ የመጣው የችግሩ ተፈጥሮ ራሱ የመገንፈል ልክ ላይ ደርሶ ነው እንጂ። እዚህ ላይ የደረሰውን ጉዳይ ሁሉም በጥንቃቄ ካልያዘ ጉዳቱ ከተፈጥሯዊነት ይልቅ ሰው-ሠራሽ አንዳናደርገው።

    ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የተጠየቀውን ነገር ለመመለስ ምን ያህል እምነት የሚጣልበት አካል እንደሆነ አላውቅም። ነገሮችን እየመለሰ ያለበት አኳኋን ግን መልካም አይደለም። እስከሚገባኝ ድረስ በውይይቱም ላይ ለመመለስ ቃል የገባባቸው ጉዳዮች ራሱ ሲፈጽም የነበረ ሕግን የጣሰ አሠራር ነው። የሀገሪቷን ሕግ ጥሶ ወጪ መጋራትን (cost-sharing) ቢያስተካክል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሲሠራ የነበረውን የወንጀል ሂሳቡን አወራረደ ይባላል እንጂ የሐኪሙን ጥያቄ መለሰ ተብሎ ለዜና የሚቀርብ ጉዳይ አልነበረም። ወሃ የማይቋጥር ጥቃቅን ነገሮች አስር ጊዜ እንደሰበር ዜና የሚለጥፍበት መንፈስ ግን አስቂኝ ነው። ስጠረጥር ግን ባለሙያውን ንዴት ውስጥ በመክተት ይበልጥ እንዲገፉበት የፈለገም ይመስለላል። ከሳምንታት በፊት ሰምተን ያለቀውን ጉዳይ ዛሬ በሰበር ዜና ባገኘው ሚዲያ ሁሉ ማስተጋባት የቅንነት ልቡን የሚታመን አያደርገውም። ጊዜያዊ ስሜቱን ማብረድም ሆነ ዘላቂ መፍትሄውን በሰከነ መንገድ መመለስ ይጠበቅበታል እንጂ የብልጣብልጥነት ጨዋታ በመገናኛ ብዙሃን (ሚዲያ) በኩል መጫወት አይጠቅምም።

    ሌላው ከዶ/ር አቢይ ጋር ተያይዞ፡- እንደሚታወቀው ባለፈ ከሕክምና ማኅበረሰብ ጋር ያደረገው ውይይት ብዙዎችን አስከፍቷል። በዚህም የተነሳ የብዙ ሐኪሞች የሥራ ሞራል ወርዷል፣ የብዙዎች ስሜት ቀዝቅዟል። በዚህ ብቻም የተነሳ ብዙ ህመምተኞች ይጎዳሉ፤ ተጎድተዋል። ይህ እንግዲህ ከጥያቄዎቻቸው ጋር ቀጥተኛ ተዛምዶ የሌለው ተጨማሪ ችግር ነው። የአንድ አገር መሪ በተናገረው ነገር የሚበላሸው ብዙ ነገር እንደሆነ ግልጽ ነው። የዚህንም ፍሬ አይተነዋል። ለዚህ ትክክለኛው መድኃኒት እርምት ነው። ስለ ባለሙያው ክብርም ባይሆን ስለሚበደሉቱ ህመምተኞች ሲባል፣ የተነገረውም በአደባባይ ስለሆነ፣ የዶ/ር አቢይ መንግሥት በአደባባይ ይቅርታ ቢጠይቅ አገር ትጠቀማለች።

    ሌላው ከሕክምና ስነምግባርና ሀገሪቱ ካለችበት ሁኔታ አንጻር የተለያየ አስተያየት የሚሰጡ ሰዎች አሉ። እርግጥ ነው ሀገሪቷ ገና አልተረጋጋችም፤ እርግጥ ነው የሐኪሞቹን ጥያቄ ለራሳቸው የፖለቲካ አጀንዳ ሊያውሉ የሚፈልጉ አካላት ሊኖሩ ይችላሉ። ይህን ለማስቀረት ኃላፊነት ያለበት ደግሞ ጠያቂው ሐኪም ብቻ ሳይሆን ተጠያቂው መንግሥትና ተመልካቹ ማኅበረሰብም ጭምር ነው። መመለስ ባለበት መንገድ ካልተመለሰ ባልተፈለገ መንገድም ሊወድቅ ይችላል፤ ስጋቱ የሁሉም ነው። ይህን ተፈጥሯዊ ዕጣውን በመዘንጋት ከየአቅጣጫ ጠያቂውን ብቻ መውቀስ ተገቢ አይደለም፤ ጥያቄውንም ማራከስ ይሆናል። እርግጥ ነው ሕክምና በተቻለው መጠን ሁሉ ህመምተኛን ማስቀደምን ይጠይቃል። ይህን ጠያቂዎቹም ያውቃሉ። ይሁንና የሕክምና ሥራ የሚሠራው ሰው ሆኖ መኖር ከተቻለ ብቻ መሆኑን መዘንጋት የለብንም። በብዙ ቦታዎች ያለው እውነታ ደግሞ የደኅንነት ስጋት ጉዳይ ስለሆነ ከሁሉም ይቀድማል– ከሕክምናም። ይህን ችግር ግን ብዙ ሰው የተረዳው አይመስለኝም። ብዙዎቹ ጥያቄዎች ደግሞ ቀጥታ ለህሙማኑ ጥቅም የሚውሉ ናቸው። በአሠራር ብልሹነት መሥራት አልቻልንም ማለት እንደ አገር ቢታሰብ ትልቅ ችግር ነው እንጂ የሕክምና ባለሙያ ጥያቄ ብቻ ተደርጎ ባልተወሰደ ነበር።

    ከማኅበራዊ ድረ-ገጾች ጩኸት እስከ ሥራ ማቆም ተደርሷል። ነገሮች በዚሁ የሚሄዱ ከሆነ ደግሞ ሥራ ማቆሙ እየተስፋፋ ሄዶ የብዙዎቹ ሕይወት እስከ መቅጠፍ ሊደርስ ይችላል። ማኅበራዊ ቀውስ ሊያስከትል የሚችል ጉዳይም ሊሆን ይችላል እና ሁሉም ቆሞ ቢያስብበት ሸጋ ነው። “መንግሥትስ በዚህ አስቸጋሪ ጊዜ ላይ ሆኖ የሕክምና ባለሙያን ጥያቄ መመለስ ይችላል ወይ?” ከተባለ “አዎ ይችላል።” ምናልባትም ጊዜ የሚፈልጉ አንዳንድ ከባድ ጥያቄ የሆኑበትም ካሉ አመላለሱን ያማረ በማድረግ መተማመንን መፍጠር ይችላል። አሁን እየሄደ ባለበት መንገድ ግን አይደለም። ለዚህም ነው “መንግሥት ሆይ፥ የጤና ባለሙያውን ጥያቄ ከልብህ አድምጥና መፍትሄ ስጥ!” የምንለው።

    አክሊሉ ደበላ (የሕክምና ዶ/ር)
    ——
    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    መንግሥት የጤና ባለሙያዎች ጥያቄ


    Semonegna
    Keymaster

    መንግስት በሀገር ውስጥ የተለያዩ የሥራ ዕድሎችን በማስፋፋት ለሥራ ፈላጊ ዜጎች አስፈላጊውን ጥቅም ለማዳረስ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። መሥራት ለሚችሉ ዜጎች ሁሉ በሀገር ውስጥ ላሉ የሥራ ዕድሎች ቅድሚያ በመስጠት ሠርተው የሚለወጡበትን ሁኔታዎች በማመቻቸት ዜጎችን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ ይገኛል።

    ኢትዮጵያ ውስጥ ሠርቶ ለመኖር በርካታ መልካም አጋጣሚዎች አሉ። ለዚህም ምሳሌ የሚሆኑ በሀገራቸው ሠርተው የተለወጡ በርካታ ወጣቶችን መጥቀስ ይቻላል።

    ከዚህ ባለፈ ወደ ውጭ ሀገራት ለሥራ መሄድ የሚያስቡ ዜጎች እራሳቸውን ከአቻ ግፊትና ከሕገ-ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ሊጠብቁ ይገባል። ዜጎች ስለሚሄዱበት ሀገር ስላለው እውነታ ያላቸው ግንዛቤና መረጃ ውስንና የተዛባ በመሆኑ ከመሄዳቸው በፊት ስለሚሄዱበት ሀገር ባህል፣ ወግና ልማድ መረዳትና እና የዜጎችን መብት ደህንነትና ክብር ለማስጠበቅ ሲባል በኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የወጣውን አዋጅ ቁጥር 923/2008 ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል።

    ለጉዞ ከመነሳታችን በፊት ምን ማወቅ ይጠበቅብናል?

    ወደ ውጭ ሀገር ሄደን ለመሥራት በምናስብበት ወቅት ጊዜ ሰጥቶ ማሰብ ይገባል። ለምን እንደምንሄድ፣ ከሄድን በኋላ የሚያጋጥሙንን መልካምና መጥፎ አጋጣሚዎች እንዴት መቋቋምና ማለፍ እንደሚገባን፣ የምንሄድበትን ሀገር ባህል፣ ወግ፣ ልማድና ስርዓት እንዴት ተላምደን መኖር እንደምንችል፣ የሠራንበትን ገንዘብ ወደ ሀገራች እንዴት መላክና መቆጠብ እንደምንችል፣ ኮንትራታችንን ጨርሰን መቼ ወደ ሀገራችን መመለስ እንዳለብን አስቀድመን ማቀድ ያስፈልጋል።

    በአዋጅ ቁጥር 923/2008 መሠረት በውጭ አገር ለሥራ የሚሰማሩ ዜጎች እድሜያቸው ከ18 አመት በላይ የሆኑ፣ 8ኛ ክፍል ያጠናቀቁ (ወደ 9ኛ ክፍል የተዛወሩ)፣ በሚሄዱበት የሥራ መስክ ስልጠና ወስደው የብቃት ማረጋገጫ ያገኙ፣ የቅድመ ጉዞ ስልጠና ወስደው ሰርተፊኬት የያዙ፣ የጤና ኢንሹራንስ የተገባላቸው፣ ሙሉ የጤና ምርምራ ያደረጉና ከወንጀል ነጻ ሊሆኑ ይገባል።

    ይህን ያሟሉ ዜጎች በአስቀጣሪ ኤጀንሲ በኩል ወይም በራሳቸው አማካኝነት ሥራውን በማፈላለግ ማለትም በቀጥታ ቅጥር አስፈላጊውን የቅጥር ፎርማሊቲ በማሟላት ቪዛውን አግኝተው መሄድ ይችላሉ። ብዙ ጊዜ በቀጥታ ቅጥር የሚጓዙ ሠራተኞች መደበኛ ስልጠና የወሰዱና ከቤት ሠራተኝነት ውጭ በልዩ ልዩ ሙያዎች የሰለጠኑ ሲሆን የሚሠሩትም በካምፓኒና በልዩ ልዩ አነስተኛ የቢዝነስ ተቋማት ውስጥ ነው። ከዚህ በፊት በውጭ ሀገር ሠርተው የተመለሱ ልምድ ይኖራቸዋል ተብሎ ስለሚታሰብ መረጃ ማቅረብ የሚችሉ ከሆነ ስልጠናውን መውሰድ ግዴታ ባይሆንም የብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ማቅረብ ይኖርባቸዋል።

    ለሥራ የት ሀገር ነው መሄድ የሚቻለው?

    ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በቤት ሠራተኝነት የሚሄድ ከሆነ ሊጓዝ የሚችለው በኤጀንሲዎች አማካኝነት ብቻ መሆኑን ሊረዳ ይገባል። የሥራ ስምሪት ማድረግ የሚችለውም አገሪቷ የሁለትዮሽ ስምምነት ወደተፈራረመችባቸው ሀገራት ብቻ ነው። የሁለትዮሽ ስምምነት የተፈፀመባቸው መዳረሻ ሀገራት ለጊዜው ሳውዲ አረቢያ፣ ኳታርና ጆርዳን ሲሆኑ ከሌሎች አገሮች ጋር የሚደረገው ስምምነትም በሂደት ይቀጥላል።

    ስምምነት በተፈፀመባቸው ሀገሮች የደመወዝ መጠን ስንመለከት ከኳታር መንግስት 1200 ለቤት ሠራተኛና 1300 ለእንክብካቤ (care giver) የኳታር ሪያል፣ ከጆርዳን መንግስት ለጀማሪ 225 ዶላር፣ ልምድ ላላው 250 ዶላር፣ ከሳውዲ አረቢያ መንግሰት ጋር 1000 የሳውዲ ሪያል እንዲሆን ስምምነት ላይ ተደርሷል።

    በሠራተኞችና በአሠሪዎች የሚሸፈኑ ወጪዎች

    አንድ ሠራተኛ በሥራ ለመሰማራት አስፈላጊውን መስፈርት ካሟላና ብቁ ከሆነ በአዋጁ የተደነገጉ የቅጥርና ምልመላ መንገዶችን በመከተል አስፈላጊውን መፈጸም እና ወጪዎችን መሸፈን ይገባል።

    1. አሠሪው ወይንም ኤጀንሲው የሚሸፍናቸው ወጪዎች

    በአሠሪው የሚሸፈኑ ወጪዎች ሠራተኛውን ወደ ተቀባይ አገር ለማድረስ፣ በተቀባይ አገር ያለችግር እንዲቆይና እንዲሠራ ለማድረግ፣ እንዲሁም በሥራ ላይ ደህንነቱ የተጠበቀ እንዲሆን የሚወጡ ወጪዎች ናቸው።

    እነርሱም የተቀባይ አገር የመግቢያ ቪዛ፣ የደርሶ መልስ መጓጓዣ፣ የሥራ ፍቃድ፣ የመኖሪያ ፍቃድ፣ የሥራ ውል ማጽደቂያ ክፍያዎች፣ የመድህን ዋስትና ሽፋን እንዲሁም በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገኝ የተቀባይ አገር ኤምባሲ ወይም ቆንስላ ጽህፈት ቤት የሚከፈል ከቪዛና ከሰነድ ማረጋገጥ ጋር የተያያዘ ማናቸውም ወጪዎች ናቸው።

    1. በሠራተኛው የሚሸፈኑ ወጪዎች

    አንድ ሠራተኛ ለሥራ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ሀገራት በሚጓዝበት ወቅት የሚያወጣው ወጪ በአብዛኛው በህይወት ዘመኑና በማህበራዊ ህይወቱ ውስጥ የትኛውም ሰው ስለሚጠቀምባቸው የሚያወጣቸው ወጪዎች ናቸው።

    እነርሱም ለልደት ሰርተፊኬት፣ ለፓስፖርት፣ ለክትባት፣ ለህክምና ምርመራ፣ ለሙያ ብቃት ማረጋገጫ፣ ከወንጀል ነፃ ማስረጃ ማረጋገጫ ወጪዎች ናቸው። እነኝህ ክፍያዎች በሙሉ አገልግሎቱን ለሰጡ ሌሎች መሥሪያ ቤቶችና ተቋማት የሚከፈል እንጂ ምልመላውን ለሚያከናውነው ኤጀንሲ የሚከፈል አይደለም። ኤጀንሲው ምንም አይነት ክፍያ ከሠራተኛው ቢጠይቅ ህገወጥ ያደርገዋል።

    ይሁን እንጂ ለሥራ ወደ ውጭ አገር ለመሄድ አስፈላጊ ሁኔታዎች ተጠናቀው ያለበቂ ምክንያት ሠራተኛው ወደ ሥራ ባይሰማራ ከቅጥሩ ጋር በተያያዘ አሠሪው ያወጣውን ወጪ ሠራተኛው እንዲከፍለው ሊጠይቅ ይችላል። በተመሳሳይ መንገድ በተራ ቁጥር 2 ላይ የተጠቀሱትን ወጪዎች ሠራተኛው አውጥቶ በራሱ ጉድለት ባልሆነ ምክንያት በሥራ ላይ ካልተሰማራ ኤጀንሲው ወይም አሠሪው የሠራተኛውን ወጪ የመተካት ግዴታ ይኖርበታል።

    ለውጭ አገር ለሥራ ስምሪት የሚሰጡ ስልጠናዎችና ማሰልጠኛ ተቋማቱ

    ለውጭ አገር ሥራ ስምሪት የሚሰጡ ስልጠናዎች ሶስት ሲሆኑ እነሱም በቤት አያያዝ (Household Service) በቤት ውስጥ ሥራ (Domestic Help) እና በእንክብካቤ ሥራ (Care Giving) ናቸው።

    የእነዚህ ሙያዎች የስልጠና መሳሪያዎች፣ የሙያ ደረጃ፤ ሥርዓተ ትምህርት እና የብቃት ማረጋገጫ ምዘና መሳሪያዎች ሲዘጋጁ ለማንኛውም ዜጋ እንዲያገለግል ሲሆን ወንድም ሆነ ሴት በፍላጎቱ ሊሰለጥን ይችላል። ሠልጣኞች ስልጠናውን በግላቸው ሊሠሩበት፣ በአገር ውስጥ ሊቀጠሩበት እንዲሁም ወደውጭ አገር ሊሰማሩበት እንደሚችሉ ሊገነዘቡና በምልመላ ወቅትም ሊነገራቸው ይገባል። በተጨማሪም በስልጠናው የተሳተፈ ሁሉ የብቃት ምዘናውን ያልፋል ማለት አይደለም፣ የብቃት ምዘናውን ያለፈ ሁሉ ቀጣሪ ያገኛል ማለትም አይደለም። በመሆኑም በተጠቀሱት ሙያ እንዲሰለጥኑ የተደረጉ ሁሉ ወደአረብ ሀገር መሄድን እንደመብት ሊያዩት አይገባም።

    ይሁን እንጂ ወደአረብ አገር መሄድ የሚፈልጉ ሰልጣኞች ከላይ በተጠቀሱት ሦስት ሙያዎች ከሰለጠኑ በኋላም የብቃት ምዘና ማረጋገጫ ተፈትነው ማለፍና ሰርተፊኬት መያዝ ይኖርባቸዋል። ስልጠናው በየክልላቸውና በአቅራቢያቸው በሚገኙ በተመረጡ ማሰልጠኛ ተቋማት ይሰጣል። ስልጠናው በየክልላቸውና አቅራቢያቸው የመሰጠቱ ጠቀሜታም የሠራተኞች ምልመላ በየክልላቸው የሚካሄድ በመሆኑ፣ አስፈላጊ መረጃዎችን ለማጣራትና ለማረጋገጥ፣ የዜጎችን ደህንነትና ክብር በቅርብ ለመከታተል እና ከስልጠና፣ ከምልመላ ጋር ተያይዞ ለአላስፈላጊ ወጪና የመብት ጥሰቶች እንዳይጋለጡ ያግዛል።

    ስልጠናን በተመለከተም፣ የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት ትምህርቱን በነፃ የሚሰጡ ሲሆን ማንኛውም ሰልጣኝ በክልሉ በሚገኝ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ወይም በየዞኑና ክፍለ ከተማው ወይም ወረዳዎች በሚገኙ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ጽህፈት ቤቶች በመመዝገብ ለየማሰልጠኛዎቹ በመላክ እንዲሰለጥኑ ይደረጋል።

    በተጨማሪም የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት የተደራሽነትና የአቅም ውስንነት ስላለባቸው በፌደራልና በክልል በሚገኙት የቴ/ሙ/ት/ስ/ኤጀንሲ ቢሮዎች ለግል ማሰልጠኛ ተቋማት ፍቃድ በመስጠት በማሰልጠን ሥራው እንዲሳተፉ ተደርጓል። በመሆኑም የግል ማሰልጠኛ ተቋማት የስልጠና ጥራታቸው ላይ ጥንቃቄ በማድረግና አስፈላጊ የስልጠና ቁሳቁሶችን በማሟላት የትምህርቱን ጥራት እንዲጠብቁ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን። ፍቃድ ሰጪ አካላትም የጀመሩትን ክትትል፣ ቁጥጥርና ድጋፍ በማጠናከር እገዛ እንዲያደርጉ እንጠይቃለን።

    በየክልሉ የተመረጡ የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት ዝርዝር

    በመንግስት የተመረጡ 66 ማሰልጠኛ ተቋማት ሲሆኑ ስልጠናውም በሁሉም ክልል በነፃ ይሰጣል።

    የማሰልጠኛ ተቋማት ዝርዝር በየክልሉ፡-

    አማራ ክልል

    1. ባህርዳር ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    2. ወልድያ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    3. ደሴ ወ/ሮ ስህን ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    4. ከሚሴ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ
    5. ደ/ብርሃን ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    6. ጎንደር ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    7. እንጂባራ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    8. ቡሬ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ
    9. ደብረታቦር ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    10. ደብረ ማርቆስ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    11. ሠቆጣ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ

    ደቡብ ክልል

    1. አዋሳ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    2. አርባ ምንጭ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    3. ሶዶ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    4. ዱራሜ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    5. ሆሳዕና ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    6. ወራቤ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    7. ወልቂጤ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    8. ቡታጅራ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    9. ሀላባ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    10. ይርጋለም ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    11. ዲላ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ

    ትግራይ ክልል

    1. መቀሌ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    2. ዶ/ር ተወልደ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ
    3. አክሱም ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    4. ዶ/ር አርዕያ ካሳ ኮሌጅ
    5. ውቅሮ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    6. (ማይጨው) ጥላሁን ይግዛው ፖሊቴክኒክ
    7. አላማጣ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ

    አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

    1. እንጦጦ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና (ቴ/ሙ/ት/ስልጠና) ኮሌጅ
    2. ጄነራል ዊንጌት ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ
    3. ንፋስ ስልክ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ
    4. ምሥራቅ አጠቃላይ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ
    5. የካ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    6. ልደታ ማኒፋክቸሪንግ ኮሌጅ
    7. አዲስ ከተማ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    8. ቂርቆስ ማኒፋክቸሪንግ ኮሌጅ
    9. አቃቂ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ

    ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር

    1. መለስ ዜናዊ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ

    ኦሮሚያ ክልል

    1. ሀሮማያ ቴክኒክና ሙያ
    2. አሰላ ቴክኒክና ሙያ
    3. ሻሸመኔ ቴክኒክና ሙያ
    4. መርቲ ፖሊ ቴክኒክ
    5. ቢሾፍቱ ቴክኒክና ሙያ
    6. ጂማ ቴክኒክና ሙያ
    7. መቱ ቴክኒክና ሙያ
    8. መቱ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ
    9. ነቀምት ቴክኒክና ሙያ
    10. ነቀምት ጤና ሳይንስ ኮሌጅ
    11. ባቱ ተራራ ቴክኒክና ሙያ
    12. ዶና ባርበር ቴክኒክና ሙያ
    13. ፍቼ ቴክኒክና ሙያ
    14. መርቲ ፖሊ ቴክኒክ
    15. አዳማ ፖሊ ቴክኒክ
    16. አብቦ ፖሊ ቴክኒክ
    17. ሰበታ ፖሊ ቴክኒክ
    18. ወሊሶ ፖሊ ቴክኒክ
    19. አጋሮ ፖሊ ቴክኒከ
    20. አደላ ፖሊ ቴክኒክ
    21. ቡሌ ሆራ ፖሊ ቴክኒክ
    22. ጨርጭር ፖሊ ቴክኒክ
    23. ደደር ፖሊ ቴክኒክ
    24. አርሲ ነገሌ ፖሊ ቴክኒክ
    25. ሀሰሳ ፖሊ ቴክኒክ
    26. ጊምቢ ፖሊ ቴክኒክ
    27. ወንጂ ፖሊ ቴክኒክ

    ምንጭ፦ የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ለሥራ ወደ መካከለኛው


Viewing 15 results - 16 through 30 (of 58 total)