Search Results for 'ፌስቡክ'

Home Forums Search Search Results for 'ፌስቡክ'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 18 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    ይድረስ ለትግራይ ወገኖቼ!
    በአቶ ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ

    የትግራይ ሕዝብ ከባለጌ ልጆቹ በላይ ሀገሩን የሚመርጥበት ጊዜ ደርሷል። በተለይም የትግራይ እናቶች እና አባቶች በራሳቸው ልጆች እኩይ ስምሪት ቀደምቶቻቸው ለአንድነቷ ሰማዕትነትን የተቀበሉላት ኢትዮጵያችን ክብሯ እንዲጎድፍ በዝምታ መተባበራቸውን ይበቃል ለማለት ትክክለኛው ወቅት አሁን መሆኑን ልብ ሊሉ ይገባል።

    የዘመን ተጋሪዬ ለሆናችሁ የትግራይ ወጣቶችም “ጅብም ብሆን የወንዝህ ጅብ ስለሆንሁ፤ ልበላህ መብት አለኝ” የሚሉ ሀገር አጥፊዎችን በመተው ከሀገራችን ኢትዮጵያ እና ወንድሞቻችሁ ጎን እንድትቆሙ ወንድማዊ ጥሪዬን አቀርብላችኋለሁ።

    የሀይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች ጨዋው የትግራይ ሕዝብ በሀገር አፍራሽ፣ ዘር አጥፊና ዘራፊ ብኩኖች በኩል ዘላቂ መብቶቹ፣ ጥቅሞቹና ፍላጎቶቹ እንደማይከበሩለት አውቃችሁ፤ ሁለንተናው ከኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ጋር የተሸመነውን የትግራይ ሕዝብ ታሪክ፣ ክብርና የወደፊት በጎ ተስፋ በሚመጥን ስምሪት እንድትገኙ ዝቅ ብዬ እለምናችኋለሁ።

    ታላቁ የትግራይ ሕዝብ በሌባ አይወከልም! ከዘፍጥረት ጀምሮ እስካሁን ድረስም እናት ኢትዮጵያም ሆነች ወንድሙ የአማራ ሕዝብ ለትግራይ ሕዝብ የክብሩ ምንጭ የደኅንነቱ ደጀኖች እንጂ የስጋቱ ምንጮቹኘች ሆነው አያውቁም፤ አይሆኑምም። እንዴት ሀገር ገንቢው ትግራይ በሀገር አፍራሽ ይወከላል?

    ትግራይ የምታሸንፈው ኢትዮጵያ ስታሸንፍ ብቻ ነው፤ ትግራይ አንገት ደፍታ ኢትዮጵያ አትቃናም። በትግራይ ለቅሶ ፈገግታው የሚደምቅ አንድም ኢትዮጵያዊ አይኖርምም። ሌባና ዘራፊ፤ ባንዳና ሀገር አጥፊ ግን ከየትም ይሁን የትም የጋራ ጠላታችን ነውና በጋራ ልንደመስሰው ይገባናል። በባንዳ ሞት ደረት የሚደቃና ፊት የሚነጭ ሊኖር አይገባም።

    እናም ለተከበራችሁ የትግራይ አባቶቼና እናቶቼ፣ ወንድሞቼና እህቶቼ፥ ስለደማቁ የትናንት ትናንታችን ብቻ ሳይሆን ስለብሩህ ነጋችንም ብላችሁ ለኢትዮጵያችን ኅልውና እንዲሁም ለሕዝባችን ፍትሕ፣ እኩልነትና ነፃነት መረጋገጥ በአንድነት እንድንቆም ስል ጥሪዬን ደግሜ ላቀርብላችሁ እወዳለሁ።

    ሁሉም ችግሮች ከጋራ አቅማችን በታች ናቸው። ስንደማመጥ፣ ስንከባበርና ስንተማመን ከባዱ ቀላል ይሆናል። ኢትዮጵያ ስታሸንፍ ሁላችንም እናሸንፋለን!

    አቶ ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ

    አቶ ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ በፌደራል የጤና ሚኒስቴር፥ የማኅበረሰብ ጤና ኤክስፐርት (public health expert) ሲሆኑ፤ በፖለቲካ እንቅስቃሴአቸው ደግሞ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ናቸው። እርሳቸውን በፌስቡክ ገጻቸው ወይንም በትዊተር ሃንድላቸው ሊያገኟቸው ይችላሉ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    አቶ ክርስቲያን ታደለ

    Anonymous
    Inactive

    እብለት የሌለበት ምስክርነቴ – ለዶ/ር ብርሀኑ ነጋ

    (የትነበርክ ታደለ /ጋዜጠኛ/*)

    በሀገራችን የዲሞክራሲ ትግል ውስጥ ትልቁ ፈተና ኢ-ዴሞክራሲያዊና አምባገነን መንግሥታት ብቻ አይደሉም፤ የሴራ ምሁራንም ጭምር እንጂ። በገዛ ራሳችን ምሳሌ “ቀና ቀና ያለች ማሽላ አንድም ለወፍ፥ አንድም ለወንጭፍ” እንደ ተባለው የሀገራችን የሴራ ምሁራን ከመካከላቸው ቀና ያለውን በማጥቃት ብዙ ፍሬ ያዘሉ ሰብሎቻችንን አምክነው ኖረዋል። በዚህ ድርጊታቸው ከአምባገነን መንግሥታት በላይ ሀገራችንን መከራ ውስጥ ጨምረዋል። ብርሀኑ ነጋ ለእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የመፍትሄ ምንጭ እንጂ ጸረ-ኢትዮጵያዊ ወይም ጸረ-ኢትዮጵያ ተብሎ ለተከታታይ ዓመታት በአደባባይ የሚዘመትበት ሰው አልነበረም!!

    ብርሀኑ…

    ከጽንፈኛ ብሔርተኞችና ከአክራሪ ሀይማኖተኞች በሚወረወርበት ሾተል ጀርባው እየደማ የዜግነት ፖለቲካን የሙጥኝ ያለው ‘በኔ ጉዳት ኢትዮጵያ ትዳን’ ብሎ እንጂ ኢትዮጵያን ስለሚጠላ አይደለም!

    እንዲህም ተባለ እንዲያ ዛሬ ያ መገፋቱ ፍሬ አፍርቶ እነሆ ከሦስት የጭለማ ዓመታት በኋላ ሀገር ኖራ፣ ምርጫም ኖሮ፣ ወደ ፊት ልንሻገር ነው ብለን የምናስብበት የተስፋ ጭላንጭል ላይ ደርሰናል።

    ‘ምርጫ አለ’ ያልነው ብርሀኑ ስላለ ነው! ኢትዮጵያ ያንን ሁሉ መከራ አልፋ ለምርጫ የደረሰችው ብርሀኑ ነጋ በፖለቲካ ስም ሀገር የመናድ የገመድ ጉተታው አካል ስላልነበረ ነው!

    ዶላርና የጥይት አረር ታቅፈው ከውጭ የገቡ ተቃዋሚዎችና ሚሳኤል የታጠቀች ህወሓት “ሕገ-መንግሥቱን ትነኩትና” እያሉ በሚያስፈራሩበት በዚያ የሦስት ዓመት ጭለማ ክረምት ውስጥ ሕዝብ ብርሀኑን ሰምቶ “እውነት ነው፤ ጊዜው የሕገ መንግሥት ጥያቄ ማንሻ አይደለም” ብሎ ጋብ ባይል ኖሮ፤ “ይህ የምንፈልገው ሥርዓት አይደለም፣ ይሁን እንጂ ለሀገራችን ስንል እንደግፈው፣ ከችግሮቹ ይልቅ ጠንካራ ጎኖቹን እያሳየን ወደ ፊት እንግፋው” ብሎ ከመንግሥት ጎን ቆሞ “አለሁ!” ባይል ኖሮ የዛሬው የምርጫ ክርክር ቅንጦት በሆነ ነበር።

    በእውቀቱ ልክ እያሰበ በሀገር ፍላጎት ልክ እየወሰነ ባይራመድ ኖሮ “በለው! በለው! ፍለጠው! ቁረጠው!” ባዮች ጋር በስሜት ጋልቦ ቢሆን ኖሮ… እንኳን አንግቦት የተነሳውን የዜግነት ፖለቲካ ለአካለ ምርጫ ማድረስ ይቅርና፥ ለሀገራችንም ጦስ በሆነ ነበር።

    ይህ ሁሉ ለሕዝብ ግልጽ የሆነ ሀገራዊ አበርክቶው በሴራ ምሁራን ትንታኔ እየታጀለ ቀን ከሌት መዶስኮሩ ሰውዬው በእርግጥም ፍሬ ያዘለ ሰብል መሆኑን ከማሳየቱ በቀር እንደሚሉት ጥላቻ በልቦናው የተሸከመ ጸረ-ሕዝብና ጸረ-ሀገር መሆኑን ፈጽሞ አይመሰክርም!!

    ― ይድረስ ለብርሀኑ ነጋ (ፕሮፌሰር) ―

    የመጨረሻ ውጤቱ፣ ጥራቱና መጠኑ ምንም ይሁን ምን፣ ዴሞክራሲን አዋልደሀል!! ጨቅላውን ዴሞክራሲ አንስቶ መሳም፣ አቅፎ ማሳደግ የኛ ድርሻ ይሆናል! ለዘመናት የተጫነብንን የዘር ፖለቲካ የምናራግፍበትን አንድ ዘዴ የሆነውን የዜጋ ተኮር ፖለቲካ አስተምረህ፣ አዋቅረህ፣ ከምርጫው ኮሮጆ አድርሰህልናል – ያለፈውን ጥፋት ላለመድገምና እንደ ቀሪው ዓለም በሀሳብ ላይ መሠረት ያደረገ ፖለቲካን መምረጥ የኛ ፋንታ ይሆናል። በብዙ መከራዎች መካከል ባለች ሀገር ውስጥ የሰከነ የተቃውሞ ፖለቲካን በማራመድ ሀገርና መንግሥት በፈለጉን ጊዜ አቤት እያልን በቀረው ደግሞ እየተቃወምንና እየተቸን መጓዝ የምንችልበትን የሰለጠን አስተሳሰብ አሳይተኸናል። ይህን መንገድ ተከትሎ ያለጩኸት እና ያለ ወከባ መንግሥት መቀያየርን መልመድ የኛ ተግባር ይሆናል።… በቀረው ደግሞ ምርጫው በሰላም ተጠናቆ ቢሆን በፓርላማው፣ ከዚያም ሲያልፍ በመንግሥት ስልጣን ላይ ሆነህ ቀሪ ህይወትህን ለዚህች ደሀ ሀገራችን የበለጠ እንድትሠራ መልካም ውጤት እመኝልሀለሁ! በቀረው ግን ውለታህ አለብን እንጂ ግዴታችን የሌለብህ ከሚጠበቅብህ በላይ ያገለገልከን ታላቅ ዜጋ ነህና እናከብርሀለን!!!

    * አቶ የትነበርክ ታደለ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚጽፍ ጋዜጠኛ ሲሆን፥ በፌስቡክ ገጹ ሊያገኙትና ጽሁፎቹን ሊከታተሉ ይችላሉ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ዶ/ር ብርሀኑ ነጋ

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀ መንበር ብርቱካን ሚደቅሳ መጪውን ሀገራዊ ምርጫ አስመልክተው ያስተላለፉት መልዕክት

    መልካም ዕድል ለተወዳዳሪዎች

    የተከበራችሁ የፓርቲዎች አመራር አባላት፣ የፓርቲ ዕጩ ተወዳዳሪዎች እና በግላችሁ የምትሳተፉ ዕጩዎች፥

    ዛሬ ለ6ኛው አጠቃላይ ምርጫ በዕጩነት ስትመዘገቡ ወይም እንደ ፓርቲ ዕጩዎቻችሁን ስታስመዘግቡ ከፊታችን ያለው መንገድ ከፊል ተስፋ፣ ከፊል ስጋትን አዝሎ እንደሚጠብቃችሁ፣ እንደሚጠብቀን ለሁሉም ግልፅ ነገር ይመስለኛል። ይሁን እና ስጋትን ለመቀነስ፥ ብሎም ወደ መልካም ሁኔታ ለመቀየር የሚያስችለን አቅም እና ዕድል በየፈርጃችን ይዘን ይህን የጋራ ሙከራችንን በዝለት ሳይሆን በጥንካሬ ልንጀምረው ይገባል እላለሁ።

    በቀደሙ ምርጫዎቻችን ባልነበረ ሁኔታ የሂደቱን ዋና ተዋናዮች፥ ማለትም ተፎካካሪዎቹን ግራ ወይም ቀኝ፣ ትንሽ ወይም ትልቅ፣ ሀገራዊ ወይስ ክልላዊ ሳይል፣ በጥረታቸው ሊያግዝ እና ሳንካቸውን ሊፈታ የተዘጋጀ፣ አቅሙን የጨመረ፣ የገለልተኝነቱን መጠን እና ስፋት ከተፅእኖ ሁሉ የሚከላከል የምርጫ ቦርድ ሂደቱን እያስተዳደረ ይገኛል።

    በፍትሃዊነት በተቃኘ በጎ ሀሳብ ሳይሆን በሸፍጥ፣ ሌላውን በማክበር ሳይሆን ማንኛውንም መንገድ ተጠቅሞ በእንፃሩ የቆመውን በማጥፋት ባለመ ሀሳብ፣ የሁሉንም የዜጎችን ሀሳብን የመግለፅ ሰላማዊ ዕድል ሳይሆን ኋላቀር የሆነ ግጭታዊ መስተጋብርን ታሳቢ ያደረገ አቅጣጫን ያሰበ ተወዳዳሪ ቢኖር ይህን ከምርጫ ፖለቲካ ውጪ የሆነ ሥራውን ለአደባባይ አውጥተው ለሰው ዓይን እና ጆሮ ሊያደርሱ የሚችሉ በቁጥር ትንሽ የማይባሉ የሚዲያ አውታሮች እንደ ሀገር ያለን መሆኑም ለተሻለ ሽግግር ወደፊት ለመቀጠል የሚያስችል አንድ በጎ እውነታ ነው።

    የሲቪል ማኅበራቶቻችንንም አናቂ ይባል ከነበረ የሕግ ማእቀፍ ወጥተው ዜጎችን ስለእውነተኛ ምርጫ ሊያሳውቁ፥ እንዲሁም የምርጫ ሂደታችን ጉበኛ /watchman or watchwomen/ ሆኖ በታዛቢነት ለማገልገል በጣት በሚቆጠሩ ሳይሆን በመቶዎች በሚቆጠሩ አደረጃጀቶቻቸው ላይ መሰናዶአቸውን ለማጠናቀቅ ደፋ ቀና ይላሉ።

    የአውሮፓ እና የአሜሪካ ታዛቢዎችም ይህን ለሀገራችን ትልቅ ትርጉም ያለውን ኩነት በእንግድነት ሊታዘቡ ከመንግሥት ግብዣው ደርሷቸው ከእኛው ጋር የሂደቱ አካል ሊሆኑ ዝግጅታቸውን እያጠናቀቁ ነው።

    ብዙ ሌሎች የምርጫ ማሻሻያችን ብዙ ጎኖች መጥቀስ ይቻላል። ሆኖም በዚህ እንደ ብርቱካን ሚደቅሳ በማወጣው የመጀመሪያ የፌስቡክ መልዕክቴ በዝርዝር ላሰለቻችቸሁ አልወደድኩም።

    ለማጠቃለል፥ ዛሬ ፓርቲዎች በሀገራችን የተለያየ አካባቢ ዕጩዎችን በማስመዝገብ፣ በዕጩነት በመመዝገብ የምርጫ ዘመቻውን ምዕራፍ ስትከፍቱ ለሂደቱ የሚጠቅም በጎ እሴት ለመጨመር፣ በችግር ፈቺነት በጋራ ለመሥራት፣ የፖለቲካ ጥቃትን አሮጌ ባህል እለት እለት ለመግደል (old habits die hard ወይም ከክፉ አመል መላቀቅ በቀላሉ አይሆንም የሚለውን ያስቧል)፤ ለዘመናዊ እና ስልጡን ውድድር ራሳችንን ለማደስ፣ ከምንም በላይ የዜጎቻችንን ባለስልጣንነት በማክበር እንዲሆን እያሳሰበኩ፥ በዚህ አስፈላጊ እና ትልቅ ትርጉም ባለው ሥራ የሁላችንንም አብሮነት እና የእያንዳንዳችንን ድርሻ ሳንረሳ በበጎ መንፈስ የምርጫ ውድድሩን እንጀምር ስል ጥሪዬን አቀርባለሁ።

    በድጋሚ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያለበትን ሕጋዊ ኃላፊነት እና ግዴታ እንደሚወጣ፣ እየተወጣም እንደሚገኝ አረጋግጥላችኸዋለሁ።

    መልካም የምርጫ ዘመን!
    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀ መንበር ብርቱካን ሚደቅሳ

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሊቀ መንበር ብርቱካን ሚደቅሳ

    Anonymous
    Inactive

    ዛሬ በይቅርታ ላይ ስናፌዝ ዋልን!
    በድሉ ዋቅጅራ (ዶ/ር)

    የሀገሬ ሰዎች ለይቅርታ (ይቅርታ ለመጠየቅም፣ ይቅርታ ለማድረግም) ንፉግ ናቸው። “ሳላውቅ ያስቀየምኳቸሁ፣…” ብሎ ይቅርታ መጠየቅ። መጀመሪያ እስቲ አውቀን የበደልናቸውን ይቅርታ እንጠይቅ። አውቄ የበደልኩት የለም ለማለት ነው? በየአንዳንዳችን ልብ የበደል ቁልል አለ፤ ያንን ለመናድ መድፈር ነው ይቅርታ። የበደልከውን ሰው፥ “ይህን ስላደረግኩህ ይቅር በለኝ” ብለህ መጋፈጥ። በደለኛነትን ሸሽጎ በይቅርታ መንጻት አይቻልም።

    ይቅርታ በጅምላ አይሆንም። መሪዎች የገደሉትን፣ ያሰሩትን፣ ያፈረሱበትን፣ የወረሱትን፣… ወዘተ በስም እየጠሩ ይቅርታ መጠየቅ አለባቸው – እውን ይቅርታ ከፈለጉ። ጎንደር ላይ ወጣት ሲረሽን የነበረ፣ ተነስቶ የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ የሚጠይቅበት ምክንያት የለም፤ የገደለውን ያስገደለውን በስም እየጠራ፣ የሟች ቤተሰቦች ነው ይቅርታ መጠየቅ ያለበት። ደቡብ አፍሪካ ከአፓርታይድ ስትላቀቅ የተደረገው ይኸውም ነው። በሀገር ላይ የተሠራ በደል ካለ (ለምሳሌ ኢትዮጵያን የባህር በር እንደማሳጣት ዓይነት) ሕዝብ ይቅርታ ይጠየቃል። አንድ ተማሪ የበደለ መምህር ክፍል ገብቶ “ያስቀየምኳችሁ ይቅርታ” ሲል፥ ‘ፐ! ይቅርታ ጠየቀ’ ይባልለታል። በፍጹም፤ ይቅርታ አልጠየቀም!! ስሙን ጠርቶ፣ የበደለውን ገልጾ ነው ይቅርታ መጠየቅ ያለበት።

    ይቅርታ መጠየቅ ነው ወይንስ ማግኘት ቁም ነገሩ? እንዴ ይቅርታችንን ተበዳይ መቀበል አለመቀበሉን ማወቅ የለብንም? ካለብን ከበደልነው ጋር መጋፈጥ የግድ ነው። የጎረቤቴ ልጅ በተገደለ፣ በታሰረ እናት አባቱ እንጂ እኔን ማን ይቅርታ አድራጊ አደረገኝ?

    ደግሞ አንዳንዱ ይገርማል፤ እራሱን ከኢየሱስ መስቀል ላይ ሰቅሎ መሀሪ ይቅር ባይ መሆን ያምረዋል፤ ይቅርታ እኮ ዝቅ ማለት ነው። “ሳላውቅ በድያችኋለሁ፥ ይቅርታ አድርጉልኝ፤ እናንተ ግን አውቃችሁ በድላችሁኛል፥ ይሁንና ይቅር ብያችኋለሁ” ሲባል እኔ ንጹህ፣ እናንተ ኃጢአኞች ማለት እኮ ነው። እስቲ የሚከተለውን ይቅርታ እንመልከት።

    “… እስከዛሬዋ ቀን ድረስ ባለማወቅ ለበደልኩት ለማንኛውም በደል ይቅርታን በትህትና እጠይቃለሁ። እኔንም ለበደሉኝ፣ ያለበደሌ ለከሰሱኝ፣ ያለተግባሬ መጥፎን ስም ሰጥተው ላሳጡኝ፤ ሕዝብን ለማገልገል በምተጋበት ወቅት አላስፈላጊ ጦርነትን በመክፈት ሲያደክሙኝና አላሠራ ሲሉኝ ለነበሩት ሁሉ ከልብ የሆነ ይቅርታን አድርጊያለሁ።

    አሁን እዚህ ውስጥ ምን የይቅርታ መንፈስ አለ? ይቅርታ ጠያቂው፣ አውቆ የበደለው አንድም ነገር የለም። እሱ ላይ የተደረገውን በደል ግን ሆን ተብሎ፣ ታቅዶ እንደተደረገ በዝርዝር ተቀምጧል። ምናለ የእነሱንም፥ ‹‹ሳታውቁ ለበደላችሁኝ›› ብሎ ቢያልፈው? ወይ የእሱንም (እሱ የበደለውንም፣ ያጠፋውንም) ቢዘረዝረው?

    እና እባካችን ያልደረስንበትን እንተወው፤ ቢያንስ ጽንሰ-ሀሳቡ ለልጆቻችን ይቀመጥ፤ እነሱ ይደርሱበት ይሆናል፤ የልጅ ልጆቻቸውም ቢሆኑ።

    በድሉ ዋቅጅራ (ዶ/ር)*

    * በድሉ ዋቅጅራ (ዶ/ር) ደራሲና ገጣሚ ሲሆኑ፥ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የሂዩማኒቲስ፤ የቋንቋዎች ጥናት የጆርናሊዝምና የኮሚኒኬሽን ኮሌጅ ውስጥ ደግሞ መምህር ናቸው። ከዚህ ቀደም ለህትመት ከበቁላቸው ሥራዎች ውስጥ የማይፃፍ ገድል፣ የራስ ምስል፣ ያልተከፈለ ስለት፣ የወይራ ስር ጸሎት፣ የማይጻፍ ገድል፣ የተስፋ ክትባት፣ እና ፍካት ናፋቂዎች የጠቀሳሉ። በተጨማሪም በብሔራዊ ቲያትር ቀርቦ በተመልካች ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትን ያገኘው “ደብተራው” የተሰኘው የሁለት ገጸባሕርያት ቲያትር (two-handler theater) ደራሲ ናቸው። በፌስቡክ ገጻቸው ላይ ሊያገኟቸው ይችላሉ።

    ** ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    በድሉ ዋቅጅራ

    Semonegna
    Keymaster

    ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ መርሀ ግብሮች ያሰለጠናቸውን 7520 ተማሪዎች በበይነ-መረብ አስመረቀ

    (ባሕር ዳር) – ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በድኅረ ምርቃ መርሀ-ግብር በሁለተኛ ዲግሪ በመደበኛውና በተከታታይ መርሀ-ግብር 2254 ተማሪዎች፣ በሦስተኛ ዲግሪ መርሀ-ግብር 40 ተማሪዎች፣ እንዲሁም በስፔሻሊቲ መርሀ-ግብር 41 ተማሪዎች፣ በምስክር ወረቀት መርሀ-ግብር 642 ተማሪዎች በድምሩ 7520 ተማሪዎችን በበይነ-መረብ በመታገዝ ነሐሴ 23 ቀን 2012 ዓ.ም አስመርቋል። ከተመራቂ ተማሪዎቸ መካከል 2345 ሴቶች ሲሆኑ፤ ከእነዚህ ሴት ተመራቂ ተማሪዎች መካከል አምስቱ የሦስተኛ ዲግሪ ተመራቂ ተማሪዎች መሆናቸው ታውቋል።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ድኤታና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ አባል ወ/ሮ ሰሀረላ አብዱላሂ፣ የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ዋና ዳሬክተርና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ አባል ፕ/ር ማስረሻ ፈጠነ፣ እንዲሁም የአማራ መልሶ ማቋቋም ልማት ድርጅት /አመልድ/ ዋና ዳሬክተርና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ አባል ዶ/ር አለማየሁ ዋሴ፣ የዩኒቨርሲቲው የሴኔት አባላት፣ ዲኖችና ዳይሬክተሮች እና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።

    በሥነ-ሥርዓቱ የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ፍሬው ተገኘ ለተመራቂ ተማሪዎችና ለተመራቂ ቤተሰቦች የእንኳን ደስ ያላችሁ መልክዕት አስተላልፈዋል። በመልዕክታቸውም ዓለምን ባስጨነቀው የኮሮና ወረርሽኝ ተግዳሮት ሳይደናቀፉ የሚጠበቅባቸውን አሟልተው ለተመረቁ ተማሪዎች አድናቆታቸውን ገልፀው ወደ ቀደምት ትልቅነታችን እና ጥበብ ለመመለስ እና አሁን የጀመርናቸውን የአባይ ግድብን ጨምሮ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ለማሳካት የጋራ መድኃኒት ስለሚያስፈልገን ሁላችንም ለሀገራችን ሰላም በጋራ መሥራት እንደሚገባን አሳስበዋል።

    የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን (ኮቪድ-19) ለመከላከል እና ለመቆጣጠር እየተደረገ ባለው እንቅስቃሴ ዩኒቨርስቲዎች ሕይወትን ለመታደግ የእውቀት እና የሕዝብ ተቋምነታቸውን ማስመስከራቸውን ጠቅሰው ለዚህም ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል የሚያስችሉ ቁሳቁሶችን በማምረት እና በርካታ የፈጠራ ሥራዎችን በማበርከት ሕበረተሰቡን ከወረርሽኙ እየታደገ መሆኑን ዶ/ር ፍሬው ገልፀዋል። በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት ተማሪዎች በኮቪድ-19 ምክንያት ሙሉ በሙሉ ከትምህርት እንዳይለዩ በዩኒቨርሲቲው የICT ባለሙያዎች የበለፀገ የትምህርት አስተዳደር ሥርዓት (learning management system) ለአማራ ክልለዊ መንግሥት ትምህርት ቢሮ ማበርከቱን አውስተዋል።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚንስትርና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር ኢ/ር ስለሺ በቀለ እንዳሉት መማር ትርጉም የሚኖረው የሕበረሰተቡን ኑሮ ማሻሻልና ለችግሮቹ መፍቻ የሚሆን አዳዲስ አሠራሮችንና ሀሳቦችን መፍጠር ሲቻል መሆኑን ጠቁመው የሀገራችን ችግር የሚፈታው የችግሮችን ስፋትና ጥልቀት በሚረዱ ምሁራን በመሆኑ የምንግዜም ጠላታችን የሆነውን ድህነትን ለማስወገድ ተመራቂ ተማሪዎች በተመረቁበት መስክ ትኩረት ሰጥተው ለመሥራት ትልቅ ኃላፊነት እንዳለባቸው አሳስበዋል።

    አክለውም፥ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የልሕቀት ማዕከል ለመሆን የሚያደርገውን ትጋት አድንቀው፤ በእምቦጭ ዙሪያ ብዙ ሥራ መሥራት የሚያስችል በመሆኑ ዩኒቨርሲቲው ትኩረት ሰጥቶ በስፋት እንዲሠራ ጥሪ አቅርበዋል። ከአባይ ፏፏቴ ጀምሮ እስከ ሰሜን ብሔራዊ ፓርክ ድረስ ትኩረት በመስጠት የቱሪዝም ኮሪደር ለማድረግ የሚቻልበትን ምርምር በመሥራት መሻሻል የሚገባቸውን ጉዳዮች ማሳየትም ከዩኒቨርሲቲው እንደሚጠበቅ ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ ተናግረዋል።

    የምረቃ ሥነ-ሥርዓቱን ጥቂት ተማሪዎች አዳራሽ ውስጥ በአካል በመገኘት፥ አብዛኛዎቹ ተመራቂ ተማሪዎች ደግሞ በየቤታቸው ሆነው በአማራ ቴሌቪዥን ከጥበብ ህንፃ የመሰብሰቢያ አዳራሽ በቀጥታ ስርጭት፣ በፌስቡክ (Facebook) እና ዩቲዩብ (YouTube) የተላለፈውን ታድመዋል።

    ምንጭ፦ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ

    ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ

     

    Anonymous
    Inactive

    ቁጥጥር ወይ ድርድር! ― አብርሃ ደስታ

    በሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) እና በፌደራል መንግሥት መካከል ውጥረት ነግሷል። የኦሮሚያ ጉዳይም አሳሳቢ ነው። በዚሁ ከቀጠልን የሀገር አንድነት እና የሕዝቦች ደህንነት አደጋ ላይ ይወድቃል።

    ምን መደረግ አለበት?

    ዘርፈ ብዙ ፖለቲካዊ ችግሮች ቢኖርቡንም ለአሁኑ ወቅታዊውና አንገብጋቢው ውጥረት መንስዔ ከምርጫ መራዘም በኋላ የፌደራል መንግሥት ከሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች ጋር መነጋገር/ መወያየት ሲገባው “ሁሉም ነገር በሕግ አግባብ ይፈታል” ብሎ የሕገ መንግሥት ትርጉም ወደ መጠየቅ መጣደፉ ነው።

    መንግሥታዊ ተቋምና መዋቅር (government institutions and structure) እንዲሁም ሁነኛ የመንግሥትቁጥጥር (effective government control) በሌለበት ሀገር ሁሉም ነገር በሕግ አግባብ አይፈታም።

    የፌደራል መንግሥት “የፖለቲካ ውይይት አልቀበልም፤ ስልጣን ልትጋሩኝ ነው” ብሎ ወደ “ሕገ መንግሥት ትርጉም” ሮጦ ብቻውን ባይወስን ኖሮ፥ ብዙ ነገር ቀላል ይሆን ነበር። “ትርጉም” ከመጠየቁ በፊት “ይህን ውሳኔዬን የማይቀበሉ ቢኖሩስ? አመፅ ቢቀሰቀስስ?” ብሎ ማሰብ ነበረበት። በሁሉም አከባቢ “መንግሥታዊ ቁጥጥር” እንደሌለው እያወቀ!? ብቻውን ከመወሰኑ በፊት ከሌሎች ጋር መወያየት ቢችል ኖሮ ብዙ ችግሮቻችን መፍትሔ ያገኙ ነበር።

    አንድ መንግሥት መሥራት ያለበት የመጀመርያ ሥራ በሁሉም አከባቢ መንግሥታዊ መዋቅር ዘርግቶ ሰላምና መረጋጋትን ማስፈን ነው። ለዚህም ጠንካራ እና ገለልተኛ የሆኑ (ለፖለቲካ ፓርቲ የማያዳሉ) መንግሥታዊ ተቋማት በመገንባት ሕዝብ በመንግሥት ላይ እምነት እንዲኖረው ማሳየት አለበት። መንግሥት ይህን ባልሠራበት ወቅት ችግር የሚያጋጥም ከሆነ ግን በውይይት/ እውነተኛ ድርድር ነው መፈታት የሚችለው/ ያለበት።

    መንግሥት “መንግሥት” መሆን ካቃተው ዜጎች ዋስትና ያጣሉ። እናም ራሳቸው በራሳቸው ለመከላከል ይታጠቃሉ። ራሳቸው መልስ ይሰጣሉ፣ ይበቀላሉ። በዚህም ሕዝብ ይጎዳል፤ ሀገር ይፈርሳል። የህወሓት ወታደራዊ ትእይንት የምርጫ ጉዳይ አይደለም፤ በመንግሥታዊ ሥርዓቱ ላይ ዋስትና ማጣት ነው። የኦሮሞ ዓመፅ በመንግሥት ላይ እምነት ማጣት ነው። እንደ ውጤቱም እጅግ ዘግናኝ ክስተቶች አየን።

    ሀገር እንዲፈርስና ሕዝብ እንዲጎዳ አልፈልግም፤ ስለዚህ የፖለቲካ ችግሮቻችን ለመፍታት መደራደር ይኖርብናል። መንግሥት ከስልጣን በላይ የሀገር አንድነትና የሕዝቦች ደህንነት የሚያሳስበው ከሆነ ለእውነተኛ ድርድር ዝግጁ መሆን አለበት። አለበለዚያ ግን ችግሮቻችን ይቀጥላሉ።

    ወይ አልተደራደረ ወይ አልተቆጣጠረ?!

    አብርሃ ደስታ

    * አቶ አብርሃ ደስታ በትግራይ ክልል ውስጥ በዕድሜ አንጋፋነታቸው ሁለተኛ የሆነው ዓረና ትግራይ ለዲሞክራሲ እና ሉዓላዊነት (ዓረና ትግራይ) በመባል የሚጠራው የፖለቲካ ፓርቲ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚታ አባል ናቸው። የፌስቡክ ገጻቸውን እዚህ ጋር ያገኙታል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረ-ገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    Abraha Desta አብርሃ ደስታ

    Anonymous
    Inactive

    [በዚህ ጽሑፍ ላይ አማራ ብዬ የጠቀስኩት ማኅበረሰብ በአሰፋ ጨቦ ትንታኔ መሠረት ሲሆን፥ ዘርን ሳይሆን የአባቶቻችንን ድል እና ኃያልነት የተቀበለውን፣ የማሸነፍ መንፈሱ የማይደረመስ ተራራ የሆነውን፣ በየሄደበት ሁሉ የአባቶቹን ድል አድራጊነት እያሰበ የበታችነትን እንቢ ያለውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ የሚመለከት ነው።]

    አሸናፊን የራሱ የሚያደርግ ብልህ ሕዝብ

    (ሙሉዓለም ጌታቸው)

    የዛሬ አንድ ወይም ሁለት ዓመት ፌስቡክ ላይ በአንድ የኦሮሞ አክቲቪስት ተጽፎ ብዙ ሰው የተለዋወጠው ጽሑፍ ነበር። ጽሑፉ ኦሮሞ ጀግኖቹን አሳልፎ የሚሰጥ ባህል አለው ብሎ ይከራከራል። አማራ* ደግሞ የሌላን ጀግና ሳይቀር የራሱ የማድረግ፣ የማጠጋጋት ባህል አለው ይላል። ይሄ ጽሑፍ ባሰብኩት ጊዜ ሁሉ ይገርመኛል። በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ በየትኛውም ዘርፍ አንቱታን ያተረፉ ጀግኖች አብዛኛው ከኦሮሞ ናቸው፤ ነገር ግን የሚያከብራቸው እና የሚወዳቸው አማራው ወይም ሌላው ብሔር ነው። በተቃራኒው በሕይወት በነበሩበት ዘመን ሳይቀር ከሃዲ፣ የአማራ ተላላኪ እያለ ሲሰድባቸው የነበሩትን ልክ ሲሸነፉ ወይም ሲመቱ የራሱ አድርጎ የመቀበል እና ሞታቸውን የእሱ የማድረግ ባህል ቢያንስ በእኔ ዕድሜ በማውቀው የኦሮሞ ማኅበረሰብ ውስጥ የሰረጸ ባህል ይመስላል።

    ኃይሌ ፊዳ ጎበና እየተባለ መከራውን እንዳየ እንደተሰደበ ደረግ ጭዳ አደረገው። አሁን ደግሞ ለብዙ የኦሮሞ የዘመኑ ጎበዞች ጃዋርን ጨምሮ ኃይሌ ፊዳ የኦሮሞ ጀግና እየተደረገ ሲቀርብ እና ለትግል ማነሳሻ ሲውል መመልከት የተለመደ ሆኗል። “The Ethiopian Revolution and Its Implication” በሚል ርዕስ በአሜሪካው የስለላ ተቋም ሲ.አይ.ኤ. (CIA) እ.ኤ.አ. በማርች 1977 (March 1977) ተዘጋጅቶ በጥብቅ ምስጢርነት ለአሜሪካው የሥራ አስፈጻሚው አካል የቀረበው ሰነድ መንግስቱ ኃይለማርያም ኦሮሞ እንደሆነ ከገለጸ በኋላ፥ በንጉሡ ወዳጆች ከስልጣን የሚፈነቀል ከሆነ “በኦሮሞነቴ” ወይም “ኦሮሞ” ስለሆንኩ ከስልጣን አባረሩኝ ብሎ ዘሩን ሊጠቀምበት እንደሚችል ትንቴውን ያቀርባል። “እንደዚህ ዓይነት አደጋ ካልገጠመው ግን ኦሮሞነቱን የማሳየት (ለስልጣን ሲል ማለቱ ነው) ዝንባሌ አይታይበትም” ይላል የስለላው ሰነድ። ተመልከቱ የሚሸነፍ ከሆነ በኦሮሞ የዘር ጉርጓድ ውስጥ ሊደበቅ ይችላል እያለን ነው (ሽንፈቱን እንጂ ድሉን ለኦሮሞ ለመስጠት ፈቃደኛ አልነበረም ማለቱ ነው)። ይሄ በዘመኑ ሳይቀር በራሳቸው የዓለም ትግል ሲሸነፉ ኦሮሞነታቸውን (ዘራቸውን) ለውድቀታቸው ሰበብ የማቅረብ ዝንባሌ እንዳለ ከማሳየቱ ባሻግር፥ ሲሸነፉ የራሱ የሚያደርጋቸው ማኅበረሰብ እንዳለ ይነግረናል።

    ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከአባታቸው መኮንን ጉዲሳ የተወለዱ ኦሮሞ ናቸው። በዓለም የተደነቁ፣ ዘመናዊ ኢትዮጵያን በዘመናዊ ተቋም የመሠረቱ፣ እጅግ አስደናቂ መሪ ናቸው። ኢትዮጵያ በእሳቸው ጊዜ የነበራትን ዝና ለመመለስ ቢያንስ 100 ዓመት በትንሹ ሊያስፍልጋት ይችላል፤ እሱም ጠንክረን ከሠራን። በርግጥ ፍጹም ሥልጣን የሚወዱ በመሆናቸው ፍጻሜያቸውን ክፉ አደረጉት። ንጉሡን የሚወዳቸው እና የራሱ ያደረጋቸው ግን ማነው? አማራው! በእሳቸው ዘመን ክፉኛ የተጨፈጨፉ ሁለት አመጾች አሉ። አንዱ የቀዳማይ ወያኔ ትግል በትግራይ ሲሆን ሌላኛው የጎጃም አመጽ ነው። የጎጃምን አመጽ ድባቅ የመቱበት ዘግናኝ ክስተት የታሪክ ጸሐፊዎች እንኳ ቃላት ያጡለት ነው። ግን ዛሬ ለሃውልታቸው መሠራት፣ ለስማቸው ክብር የሚቆመው ይሄው አማራው ነው። ምክንያቱም ጀግናን የራሱ የማድረግ ሥነ-ልቦና አለው። ሰቅለው ለገደሉት ለበላይ ዘለቀ እየዘፈነ ፥ ለእሳቸው ክብርና ዝና ዜማ ሲያወርድ ምንም አይጣላበትም። ድንቅ ሥነ-ልቦና። ኦሮሞው ደግሞ የመኮንን ጉዲሳን ሃውልት ሐረር ላይ አፍርሶ፣ ሰው ሀገር ላይ ሎንደን (London) ደግሞ የሳቸውን ያፈርሳል። ምክንያቱም ተሸናፊን እንጂ አሸናፊን የመቀበል ሥነ-ልቦና አላወረሱትም። የተቆረጠ የጡት ሃውልት ለልጆቹ ዘወትር እያሳየ፥ በባዶ እግሩ የሚሄድ ከእሱ በምንም የማይሻለው አማራ አደረገው ይላቸዋል። ልጅ በውስጡ ፍርሃት ይሰርጽበታል። የተሸናፊው ዘር አባል መሆኑ በራሱ የሚፈጥርበት የሥነ-ልቦና ቀውስ ቀላል አይደለም። ከዛ ሕይወቱን በጥላቻ መነጽር መመልከት ይጀምራል። ጥላቻ ደግሞ የሽንፈት ዋስታና ነው።

    በቅርቡ ቤት ውስጥ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በእናቱ አማራ ነው እያለች አንድ ዘመዳችን በደስታ ትፈነድቃለች። ጠቅላዩ ብዙም አልቆየም፤ በOBN ላይ ቀርበው በእናታቸውም በአባታቸውም ኦሮሞ እንደሆኑ ገለጹ። ይሄውልሽ ተሳስተሻል ስላት፥ እሱ ነው የተሳሳተው አለችኝ። ቀጥላም የሰላም ኖቤል ሽልማት ሲቀበል አስተዋዋቂዋ በእናቱ አማራ እንዲሁም በአባቱ ኦሮሞ እያለች የተናገረችውን አሳየችኝ። ይሄ እኮ እሱ የተናገረው ሳይሆን እነሱ በስማ በለው ጽፈው ያቀረቡት ነው። ደግሞ ካስተዋልሽው በእናቱ አማራ ስትል እኮ ሳቀ። ይሄም የሚጠቁምሽ ነገር አለ ስላት፥ “ችግር የለውም እኔ ነው ብያለው፤ ነው!” አለችኝ። ይሄ አሸናፊን፣ ጀግናን የራስ የሚያደርግ፣ የሚቀበል ሥነ-ልቦና እንዲሁ በከንቱ የመጣ አይደለም፤ ሲገነባ የቆየ እንጂ። በእውቀቱ ስዩም ኢትዮጵያውያን ‘እኛ በዚህ ነገር አንደኛ ነን’ የማለት ሥነ-ልቦና አለን ይላል። “ለምሳሌ እኔ የቤቱ ሦስተኛ ልጅ ብሆንም ለሰው ስናገር ግን” ይላል፥ “ከቤታችን ሦስተኛ በመሆን አንደኛ ነኝ ብዬ ነው” በማለት የባህላችንን ራስን ከፍ የማድረግ ድንቅ ሥነ-ልቦና ይገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ነገ ቢገደል ወይም አንድ ነገር ቢያደርጉት ኦሮሞ ስለሆነ ተገደለ ብለው አሁን የምታይዋቸው እሱን የሚቃወሙ የኦሮሞ ጎበዞች የራሳቸው ጀግና ያደርጉታል። እሱም ይሄን ሥነ-ልቦና ጠንቅቆ ስለሚያውቅ ሥልጣኑ ባልጸናበት ወቅት “ከቡራዩ ጠቅላያችን ተነካ ብለው ወጣቶች ሲመጡ፥ ኦሮሞ መምራት አይችልም እያሉ” ምናምን እያለ ሆዳቸውን እያባባው ነበር። በበታችነት ሥነ-ልቦና ትልቅ ሀገር መገንባት እንደማይቻል ጠንቅቆ የሚያውቀው አብይ ይሄን “rhetoric” ብዙ አልገፋበትም። ደካማ አድርጎ ራሱን ዘወትር የሚስል ማንም፥ በዙሪያው ባሉ ሊከበር እንደማይችል ያውቃል’ና፤ በተለይ በፖለቲካ። አብይ ጠንክሮ ሲወጣ፣ ኮስታራ መሪ ሲሆን፣ ቀጥ ለጥ አድርጎ ሲገዛ ሲሰድቡት የነበሩ የአማራ አክቲቪስቶች ሳይቀሩ መልሰው በፍቅሩ እያበዱለት ነው። አማራው የተቀረጸበት እና ያደገበት ሥነ-ልቦና ከጀግንነት እና ከቆራጥነት ጋር እጅግ የተሳሰረ ነው። ባለፉት 30 ዓመታት በኦሮምኛ የተዘፈኑ እና የአማርኛ (በተለይ የባህል) ዘፈኖችን ቁጭ ብላችሁ አነጻጽሩ። አሁን የምናገረው እንደ ጉድ ይታያችኋል።

    ሀጫሉ ሁንዴሳ ከሌላው ዘፈኝ በተለየ ይሄ በጣም የገባው አዋቂ ዘፋኝ ነበር። ኦሮሞ ተገፋ፤ ጡት አስቆረጠ፤ ተኮረኮመ የሚሉ ዘፈኖች እምብዛም የሉትም። የአድዋ ድል ሲመጣ እነ ግርማ ጉተማ ይሄ ድል እኛን አይመለከተንም፤ እነ ጸጋዬ አራርሳ እኛ ለሌላ ቅኝ ግዛት የተዳረግንበት ነው ብለው በድል ቀን ሲያለቃቅሱ ሀጫሉ ግን ፈረሱ ላይ ጉብ ብሎ ባለፉት 28 ዓመታት ባልተለመደ መልኩ ይሄ ድል ከማንም በላይ የኛ ነው እያለ መስቀል አደባባይ ወጣ። የአድዋ ተራራ ሄደን ትግራይ የኛ ናት ያልነው ኦሮሞዎች ነን አለን። ታሪክ ብዙ ነገሩ ተረት ነው። ዋናው ቁም ነገር የሰው ልጅ እጅግ ኢ-ምክንያታዊ ስለሆነ ተረትም ተነገረው ታሪክ ‘አንተ እኮ ልዩ ነህ፤ አሸናፊ ነህ’ ከተባለ የማይፈነቅለው ድንጋይ የለም። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት የአልያንስ ኃይሎች (the Allies) ጀርመንን ወደ አመድነት ከቀየሯት በኋላ አንድ የጀርመን ፖለቲከኛ ለጀርመኖች ያለው ነገር ነበር። “አገራችንን ከፈሏት። ሕንጻዎቻችንን አፈራረሱት። ስልጣኔያችንን አመድ አደረጉት። ጀርመናዊ አዕምሮአችንን ግን ከኛ መውሰድ አልቻሉም” ነበር ያለው። ጀርመን ዛሬ ካፈረሰቻት እንግሊዝ በተሻለ የኢኮኖሚ ቁመና ላይ ትገኛለች። በአውሮፓ ሕብረት በኩል ትልቅ ኢምፓየር ሆና ብቅ ብላለች። እዚህ ላይለመድረስ ከአራት አስርት ዓመታት በላይ አልፈጀባትም። አይሁዶችንም በተመሳሳይ መመልከት ነው። ከናዚ (Nazi) በኋላ የመጡት የጀርመን መሪዎች ብዙዎቻችን እንደምንገምተው በናዚ በተፈጸመ በደል ክፉኛ የሚጸጸቱ አልነበሩም። ይልቁስ ያን ሁሉ ተዓምር ጀርመን መሥራቷ ኩራት የወጠራቸው፣ ድጋሚ ኃያል ሀገር እንደሚሆኑ ለአፍታም ያልተጠራጠሩ ሕዝቦች ነበሩ። Paul Berman የተባለ አሜሪካዊ ጸሐፊ  “Power and the Idealist” ብሎ በጻፈው ድንቅ መጽሐፍ መጸጸት የጀመረ ትውልድ የመጣው ጀርመን በድጋሚ በኢኮኖሚ ከአበበች በኋላ በመጣው ትውልድ ነው ይላል። ዛሬ ለገጠማቸው ከስደተኛ ጋር ለተያያዘ መጠነ ሰፊ ችግር የጸጸት ሥነ-ልቦና ያለውን አስተዋጽኦ ያብራራል። ጄኔቫ (Geneva) እያለው አለቃዬ አይርሻዊ (Irish) ነበር። እንግሊዞች እንደ እኛ የበደሉት የለም ይለኛል። ለብዙ ዘመን እንግሊዝ እንዲህ አደረገን እያልን የተበዳይነት ፖለቲካ (victim politics) ስንሠራ ኖርን። ከእንግሊዝ ተላቀን እንኳ አዕምሮአችን ከእነሱ ነጻ አልወጣም ነበር። የገነቡትን ሃውልት ማፍረስ ሥራችን አደረግን። ወይ መልሰን የራሳችንን ሃውልት አላቆምን። መንገዶቹንም ሃውልቱን በማፍረስ ከትላንት የተሻለ ውብ አላደረግናቸውም፤ አስቀየሙ እንጂ። በኋላ ግን ባነንን አለ። ያኔ ነው ማደግ እና መለወጥ የጀመርነው። ከታሪካችን ጋር ታረቅን። የእንግሊዝን ድል የእኛ ድል አድርገን መቀበል እና መተረክ ጀመርን አለኝ። ከዚያ በብዙ ነገር ለመመንደግ ጊዜ አልፈጀብንም አለኝ።

    ኢትዮጵያኖች ራሳቸውን ከድል አድራጊ እና ከትልቅ ነገር ማጠጋጋት ነበር ታሪካቸው። ይሄ ተራ ጉራ የሚመስለው ሞኝ ይኖራል። በቅርብ ያገኘሁት አንድ ሸምገል ያለ ጥቁር አሜሪካዊ ዳኛ ጋር ስናወራ ለብዙ ጊዜ በራሴ እጠራጠር ነበር አለኝ። ውስጤ ውስጥ “ትችላለህ፣ አትችልም” የሚል ከባድ ትግል ነበር። ብዙ ምሳሌ እና እኔን የሚመስሉ አርአያ የሉኝም። ቀለሜ ያለመቻል ምሳሌ ሆኖ አሜሪካ ውስጥ ቆሟል። ይሄ የውስጥ ትግል ለእኔ አሰልቺ ነበር አለኝ። ኢትዮጵያኖች “ፑሽኪንን” ኢትዮጵያዊ ነው ሲሉ ለኢትዮጵያ ሥነ-ጽሑፍ ያበረከተው ነገር ኖሮ አይደለም። ነገ ለሚወለዱት፣ ከዛም ለሚሰደዱት ልጆቻቸው ‘የትም ሄደክ በሄድክበት ሀገር ካሉ ዜጎች በላይ አንተ የመብለጥ አቅም አለህ፤ አንተ ልዩ ነህ’ የሚል ታሪክ እየነገሩት ነው። ይሄ ትርክት ነው ነገ ልዩ የሚያደርገው። አስጨናቂውን የሕይወት ትግል አሸናፊ የሚያደርገው። የውብሸት ወርቃለማሁ ልጅ ዶ/ር ዳግማዊ ውብሸት በአሜሪካ ውስጥ ካሉ ስምንት ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ በሆነው Cornell University የእንግሊዘኛ ሥነ-ጽሑፍ አስተማሪ ነው። በአንድ ቃለ-መጠይቁ ላይ ወደ አሜሪካ ሲመጣ እንግሊዘኛ ካለመቻሉ በላይ አንብብ ሲባል ተማሪዎቹ በሳቅ ይወድቁ እንደነበረ ይገልጻል። “እነሱ ሲስቁ ጣልያንን ማሸነፋችን ትዝ እያለኝ፥ ‘ምናለ በሉኝ በራሳችሁ ቋንቋ እናንተን ካልበለጥኩ’ እያልኩ ለውስጤ እነገረው ነበር” ይላል። እንዳለውም በCornell University ታሪክ በእድሜ ትንሹ የእንግሊዘኛ ሥነ-ጽሑፍ ፕሮፌሰር ሆነ። ይሄ ተራ ዩኒቨርሲቲ አይደለም። አይደለም አስተማሪ ለመሆን ተማሪ ለመሆን እራሱ አስደናቂ አዕምሮ ሊኖርህ ይገባል። በነገራችን ላይ ከዚሁ ዩኒቨርሲቲ በኮምፒውተር ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በቅርብ በዶክትሬት ዲግሪ የተመረቀች የመጀመሪያዋ ጥቁር፥ ኢትዮጵያዊት ናት። ዶ/ር ረድኤት አበበ ትባላለች። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንደሚባለው የአሜሪካ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ተወዳዳሪ የምክትል ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን (Joe Biden) የሽግግር ካቢኔ መሪ ከታዋቂው ዬል ዩኒቨርሲቲ (Yale University) እና ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ (Harvard University) የተመረቀው ዮሐንስ አብርሃም የተባለ ኢትዮጵያዊ መሆኑን ታውቃላችሁ። ይሄ ማለት ጆ ባይደን ካሸነፈ በዋይት ሀውስ (White House) ውስጥ ካሉት ትልልቅ ስልጣኖች ቁልፉ ቦታን የሚይይዘው ኢትዮጵያዊው ዮሐንስ አብርሃም ይሆናል ማለት ነው። ደግሞም አምናለው በእኛ የእድሜ ዘመን ውስጥ ከኦባማ ቀጥሎ የአሜሪካ ጥቁር ፕሬዝዳንት የሚሆነው ኢትዮጵያዊ ሊሆን ይችላል። ብዙ ድንቅ ኢትዮጵያውያን በሪፖብሊካንም ሆነ በዲሞክራቶች የፓርቲ መስመር የስልጣን መሰላሉን እየወጡ እየተመለከትን ነው።

    ወደ ቀደመ ነገሬ ልመለስ እና – የኦሮሞ ባህል ይሄን ነገር ካልመረመረ የብዙ አቅመ ድኩማን መደበቂያ እና የሽንፈት ታሪክ ወራሽ ልጆች መፈልፈያ ይሆናል። እስቲ ተመልከቱ – ብርሃነመስቀል አበበ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ የአብይ ደጋፊ እና ደንበኛ የኢትዮጵያዊነት አቀንቃኝ ነበር። በአቅም ማነስ ከስልጣን ሲባረር ግን ኦሮሞነቱ ትዝ አለው። የወጣለት የኦሮሞ የመብት አቅንቃኝ ሆነ። ኦሮሞዎቹም ዓይንህን ለአፈር ብለው መስኪድ እንደገባ ውሻ እንዳላባረሩት፥ በአቅም ማነስ ተባሮ ሲመጣ ጀግና አድርገው ተቀበሉት። በተመሳሳይ አማራን እንይ፤ ልክ እንደ ብርሃነመስቀል አበበ ሲባረሩ አማራ ጉያ ውስጥ ለመደበቅ የፈለጉ ሰዎች በቅርብ ታሪካችን ነበሩ። ለምሳሌ ታምራት ላይኔ አንዱ ነው። አማራው ግን ከታምራት ላይኔ ይልቅ መለስ ዜናዊን ይወዳል። በተመሳሳይ ልደቱ አያሌውም ከፖለቲካው መድረክ ሲገለል፥ አማራ ስለሆንኩ ነው ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ የጠላኝ አለ። ዶ/ር ብርሃኑ እኮ የተደነቀ አዋቂ ሰው ነው። ምን ዓይነት ጅል ቢሆን ነው የድጋፍ ማዕከሉ የሆነውን የአማራን ሕዝብ የሚጠላው? የአማራ ሕዝብ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋን እንደሚያፈቅር ለማወቅ በአማራ ክልል እሱ የተገኘባቸውን ሠልፎች እና ስብሰባዎች ማየት ነው። ከልደቱ ይልቅ የአማራው ሕዝብ የብርሃኑ አመለካከት ይስበዋል። ሽንፈት፣ውድቀትን በዘር ቅርፊት ማሳበብ አማራው አምርሮ የሚጸየፈው ነገር ነው። ተሸንፈህ ከመጣ አማራነትህ ይነጠቃል።

    አጼ ቴዎድሮስ በመጀመሪያ በአማራው ሕዝብ እጅግ የተጠላ መሪ እንደነበረ ታሪክን ማገላበጥ ብቻ በቂ ነው። እነ ዮፍታሔ እና ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን ግን ቴዎድሮስን በጀግንነት ካባ አዲስ ሰው አድርገው አቀረበቱ። የቋራ ሰው እየተባለ፣ የኮሶ ሻጭ ሲባል ሲሰደብ የከረመው ቴዎድሮስ ህልሙ እና ጀግንነቱ ለሕዝቡ ተብራርቶ በአዋቂዎች ሲቀርብለት አማራ የሆነው በፍቅር አበደለት። ጀግና እና ዘመን ተሻጋሪ አዋቂን የሱ እንኳ ባይሆን እንደምንም የራሱ የማድረግ ባህል አለውና።

    በምድር ላይ እንደእሱ ዓይነት ጠቢብ የለም ብሎ መጽሐፍ ቅዱስ የሰበከለትን ሰሎሞን የተባለ ሌጀንድ የኢትዮጵያ ጠበብት ሲመለከቱት ጊዜ አላጠፉም። ኢትዮጵያዊ አጋቡት። በዓለም ታሪክ የዓለምን ፖለቲካ በመቀየር ፈጽሞ አቻ የሌለው የPlato “The Republic” መጽሐፍ ድንቅ ሕዝብ እና ታላቅ ሀገር በፈላስፋ ይመራል በሚል አስደናቂውን መጽሐፍ ይዘጋል። አባቶቻችን ይሄን ለመረዳት ከባድ የሆነን መጽሐፍ ያነበቡ ስለነበሩ ፥ በኢትዮጵያ ታሪክ የሚነግሰውን ሁሉ ከፈላስፋው ሰሎሞን ወልደ ዳዊት ጋር ሲያዛምዱት ቆዩ። ኢትዮጵያኖች ልጆቻችሁን አዎ ልዩ ናችሁ እያላችሁ አሳድጓቸው። አንብበው፣ ተመራምረው አዋቂ ሲሆኑ ሁሉን በራሳቸው ይደርሱበታል። እስከዛ ግን ይሄን ሥነ-ልቦና ፈጽማችሁ አትንጠቋቸው። እነሱን እዚህ አሜሪካ እንደሚወለደው ከአንጎላ በመርከብ ከመጣው ጥቁር አሜሪካዊ ጋር የተገዢነት ሥነ-ልቦና አታላብሷቸው። ጥቁሩን ሁሉ ነጻ የሚያወጣው ኢትዮጵያዊው እሱ መሆኑን ከልጅነቱ ጀምራችሁ ስበኩት።

    በመጨረሻም በአንድ አፈ-ታሪክ ምሳሌ ጹሑፌን ልዝጋ። ጅብ አህያን ለብዙ ጊዜ ሲፈራት ይኖር ነበር። ለዚህ ዋናው ምክንያት ደግሞ የአህያ ጆሮ ቀንድ እየመሰለው ነው። አህያ ጅብን መወዳጀት ስለምትፈልግ ለብዙ ጊዜ እንዲቀርባት ትሻ ነበር። አንድ ቀን ግን ለምን እንደሚሸሻት ጨክና ጠየቀችው። እሱም ቀንዶቿን እጅግ እንደሚፈራው ለዛም እንደሚሸሻት ነገራት። በመገረም “ይሄ እኮ ቀንድ አይደለም፤ ጆሮዬ ነው፤ ስጋ እንጂ አይዋጋም አለችው።” ከዚያ ቀን ጀምሮ አባራሪ እና ተባራሪ ቦታ ተለዋወጡ። ኢትዮጵያኖች ታሪኮቻችን፣ ድሎቻችን፣ ሃውልቶቻችን፣ ሃይማኖታችን ጅብ ከሆኑ ጠላቶቻችን መጠበቂያ ጋሻዎቻችን፣ ምሽጎቻችን ናቸው። ይሄን አጥተን ከመኖር ሁላችን ማለቅን መምረጥ ይሻለናል። ጆን ስቱዋርት ሚል (John Stuart Mill) እንዳለው “የተደሰተ አሳማ ከመሆን የተከፋ ሰው መሆን ይሸላል፣ ጅል ሆኖ ከመደሰት ሶቅራጦስን ሆኖ ዕድሜ ልክን ማዘን ይሻላል።” ለልጆቻችን የባርነትን፣ የተሸናፊነትን ሥነ-ልቦናን ከምናወርስ ሁላችን ቀድመን ማለቅ ይሻለናል። አባቴ ጀግና ነው እያለ ካላባት ያደገ ልጅ በፈሪ አባት ካደገ ልጅ በላይ በራስ መተማመኑ ኃያል ነው።

    * በዚህ ጽሑፍ ላይ አማራ ብዬ የጠቀስኩት ማኅበረሰብ በአሰፋ ጨቦ ትንታኔ መሠረት ሲሆን፥ ዘርን ሳይሆን የአባቶቻችንን ድል እና ኃያልነት የተቀበለውን፣ የማሸነፍ መንፈሱ የማይደረመስ ተራራ የሆነውን፣ በየሄደበት ሁሉ የአባቶቹን ድል አድራጊነት እያሰበ የበታችነትን እንቢ ያለውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ የሚመለከት ነው።

    አማራ ብዬ የጠቀስኩት...

    Anonymous
    Inactive

    እናት ባንክ በኢትዮጵያ ምርት ገበያ የግብይት ሥርዓት ውስጥ ለመሳተፍ የሚያስችለውን ዕውቅና አገኘ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– እናት ባንክ አክስዮን ማኅበር በኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለስልጣን የግብይት ሥርዓት ውስጥ ለመሳተፍ የሚያስችለውን ዕውቅና አገኘ።

    የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለስልጣን ለእናት ባንክ በግብይት ሥርዓቱ ውስጥ ለመሳተፍ የሚያስችለውን የዕውቅና ምስክር ወረቀት (certificate) በሰጠበት ወቅት ዋና ዳሬክተሩ ኢንጅነር ኡሌሮ ኡፒየው እንዳሉት፥ ባለስልጣኑ በምርት ገበያው ክፍያ የሚፈጽሙ ተቋማትን አፈጻጸማቸውን የመቆጣጠርና ዕውቅና የመስጠት ስልጣን በአዋጅ የተሰጠው በመሆኑ እናት ባንክ ከምርት ገበያው ጋር የሚያደርገው የኤሌክትሮኒክስ የመረጃ ልውውጥ አስተማማኝ መሆኑ በመረጋገጡ በግብይት ሥርዓቱ ውስጥ ለመሳተፍ የሚያስችል የዕውቅና ምስክር ወረቀት ሊያገኝ ችሏል። በዚህም ባለስልጣኑ ከባንኩ ጋር ለመሥራት የሚያስችለውን የሥራ ውል ስምምነት መፈራረሙን ተናግረዋል።

    እናት ባንክ አክስዮን ማኅበር ከኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለስልጣን የተሰጠውን የዕውቅና ሰርተፍኬት በተረከበበት ወቅት የባንኩ ፕሬዚዳንት አቶ ወንደወሰን ተሾመ እንዳሉት፥ የባንኩን የቴክኖሎጂ አቅም በማሳደግ በኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለስልጣን የግብይት ሥርዓት ውስጥ ለመሳተፍና የፋይናንስ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችላቸውን ዕውቅና ማግኘታቸው እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል።

    እናት ባንክ በፌስቡክ ገጹ ላይ ያሰፈረው መግለጫ እንዲህ ይነበባል፦

    እንኳን ደስ አለን…
    እናት ባንክ በኢትዮጵያ ምርት ገበያ (ኢ.ሲ.ኤክስ) የክፍያ ፈፃሚ ባንክ በመሆን የክፍያ ሥርዓቱን መጀመር የሚስችለውን የዕውቅና ሰርተፊኬት ከኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለስልጣን የካቲት 17 ቀን 2012 ዓ.ም. በተካሄደው ሥነ-ሥርዓት ተቀበለ። በኢትዮጵያ ምርት ገበያ የምትገበያዩ ደንበኞቻችን በዚሁ አጋጣሚ አገልግሎቱን ማግኘት እንደምትችሉ ስናሳውቅ ደስታ ይሰማናል።

    የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ሥራውን ሲጀምር ዕውቅና ተሰጥቷቸው በግብይት ሥርዓቱ ውስጥ ክፍያ ሲፈጸምባቸው የነበሩ ባንኮች ሁለት ብቻ የነበሩ ሲሆን፥ በሂደት ቁጥራቸው 15 መድረሱን አስታውሰው፥ እናት ባንክ ሲጨመር በድምሩ 16 መድረሳቸውን ተናግረዋል።

    በገበያ ሥርዓቱ ውስጥ የክፍያ መፈጸሚያ ባንኮች ዋና ዋና ተግባራትና ኃላፊነቶች የምርት ገበያው አባላትና ደንበኞች በባንኮቹ ውስጥ ገንዘብ የሚሰባሰብበትን ሁኔታ ማመቻቸት፣ የምርት ገበያው የክፍያ መፈጸሚያ ተቋም በሚሰጠው ትዕዛዝ መሰረት ከግብይት በኋላ ገንዘብ ማዘዋወርና ስለ ወቅታዊ ደንበኞችና የአባላት የባንክ ሂሳብ ከባለስልጣኑ ጋር መረጃ መለዋወጥ መሆኑ ተገልጿል።

    ከግል ባንኮች በርካታ ባለአክሲዮኖችን በመያዝ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሰው እናት ባንክ፥ በ2011 ሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት 231.4 ሚሊዮን ብር እንዳተረፈ፣ የተጣራ ትርፉም 202 ሚሊዮን ብር መሆኑን አስታውቆ ነበር። ባንኩ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች 45 ቅርንጫፎችን ከፍቶ አገልግሎት እየሰጠ ሲሆን፣ ይህንን የቅርንጫፍ ቁጥር በ2012 ሒሳብ ዓመት ወደ 70 ለማሳደግ ዕቅድ መያዙን አምና ኅዳር ወር 2012 ዓ.ም. አስታውቆ ነበር።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    እናት ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) ምክር ቤት የግንባሩ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የመራለትን የፓርቲውን ውህደት አፀደቀ። የምክር ቤቱ ስብሰባ በህዳር 11 ቀን 2012 ዓ.ም. ውሎው ኢህአዴግና አጋር ድርጅቶችን በማዋሃድ አንድ አገር አቀፍ ፓርቲ (የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ) ለመመሥረት በተጀመረው እንቅስቃሴ ላይ ትኩረት አድርጎ ከተወያየ በኋላ ነው ያጸደቀው።

    ኢህአዴግ በሥራ አስፈጻሚ ደረጃ ግንባሩ ከአጋሮቹ ጋር እንዲዋሃድና ህብረ-ብሔራዊ ፓርቲ እንዲሆን ሰሞኑን በአብላጫ ድምጽ በመወሰን ለምክር ቤቱ መምራቱ ይታወሳል። ውህዱ ፓርቲ “የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ” የሚለውን ስያሜ ተሰጥቶት ለኢህአዴግ ምክር ቤት እንዲቀርብ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው ከስምምነት መድረሱም ይታወሳል። ምክር ቤቱም ህዳር 11 ቀን ባካሄደው ስብሰባው ግንባሩና አጋር ድርጅቶቹ እንዲዋሃዱ ውሳኔውን አሳልፏል።

    የኢሕአዴግ ምክር ቤት ዛሬ የፖርቲውን ውሕደት አጽድቋል። በአዲሱ የብልጽግና ፓርቲ አማካኝነት ሁሉም የታላቋ ኢትዮጵያ ዜጎች የሚሳተፉበት ጠንካራ፣ አካታችና እውነተኛ የፌደራል ሥርዓት ለመፍጠር ቆርጠን ተነሥተናል። ጸንተንም እንታገላለን።ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በትዊተር/ፌስቡክ ገጻቸው ላይ

    የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ አባል አቶ ፍቃዱ ተሰማ የህዳር 11 ቀን የምክር ቤቱን ውሎ በማስመልከት ለኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) እንደተናገሩት፥ ምክር ቤቱ በፓርቲው ውህደት ዙሪያ ተወያይቶ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል። አቶ ፍቃዱ እንደገለጹት ምልዓተ ጉባዔው ተሟልቶ ከመከረ በኋላ ውህደቱን በሙሉ ድምጽ ነው ያጸደቀው።

    በውይይቱ ላይ የኢህአዴግ ኦዲትና ቁጥጥር ኮሚሽንም የውህደቱን አስፈላጊነት፣ ሕጋዊ አሠራርና ከደንቡ ጋር የተገናኙ ጉዳዮችን በተመለከተ ዝርዝር ጥናት ማቅረቡን ነው የገለጹት።

    በኮሚሽኑ ጥናት ውጤት መሠረትም ኢህአዴግ አገራዊ ለውጡን ለመምራትና መሠረት ለማስያዝ፣ እንዲሁም ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ የውህደቱ አስፈላጊነት ላይ ከስምምነት ተደርሷል። የውህደቱ ሂደትም ሕገ-ደንቡና ስርዓቱን የተከተለ መሆኑ ተረጋግጦ ምክክር ከተደረገበት በኋላ መጽደቁን አብራርተዋል።

    ምክር ቤቱ በሁለተኛ ደረጃ የተመለከተው የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ መርሀ-ግብርን (ፕሮግራምን) ሲሆን፤ ፓርቲው በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በማኅበራዊና በውጭ ግንኙነት ላይ የሚከተላቸውን አቅጣጫዎች በሰፊው መመልከቱን አብራርተዋል።

    ቀደም ብሎ የኢህአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ፓርቲው በመተዳደርያ ደንቡ ላይ በአገሪቷ ለሚገኙ ቋንቋዎች በሙሉ እውቅና መስጠቱ ይታወሳል። ውህዱ ፓርቲም አማርኛን ጨምሮ አፋን ኦሮሞ፣ ሶማልኛ፣ ትግርኛ እና አፋርኛ ቋንቋዎች ለሥራ ቋንቋነት የተመረጡ መሆኑንም ማስታወቁ ይታወሳል።

    የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ በፕሬዝዳንትና ምክትል ፕሬዝዳንት የሚመራ ሲሆን፤ ይህም ከዚህ ቀደም የነበረውን ሊቀ-መንበርና ምክትል ሊቀ-መንበር የሚሉትን ስያሜዎችን ይተካል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    የኢትዮጵያ ብልጽግና ፓርቲ

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሸን ጋዜጣዊ መግለጫ

    አዲስ አበባ፥ ጥቅምት 13 ቀን 2012 ዓ.ም.
    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ዋና ኮሚሸነር የእስረኞች ጉብኝት በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሸን ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ በፌዴራል ፖሊስ ተይዘው በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሸን ስር በአደራ ቁጥጥር ስር የሚገኙ ተጠርጣሪ ታሳሪዎችን ጥቅምት 10 ቀን 2012 ዓ.ም. ጐብኝተዋል።

    ዋና ኮሚሸነሩ በዚህ ጉብኝታቸው ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በባህር ዳር እና በአዲስ አበባ ከተማ ከተከሰተው የፖለቲካ ግድያ ጋር በተያያዘ እና በሌሎችም ተዛማጅ ጉዳዮች በቁጥጥር ስር ከሚገኙ እስረኞች ውስጥ፥ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) አመራር እና አባሎች ውስጥ እነ አቶ ክርስቲያን ታደለ፣ አቶ በለጠ ካሳን፤ ከባልደራስ ባለአደራ ምክር ቤት ንቅናቄ አባሎች ውስጥ እነ አቶ ኤልያስ ገብሩ፣ አቶ ስንታየሁ ቸኰል እና አቶ መርከብ ኃይሌን፤ ከኢትዮጵስ ጋዜጣ ባልደረቦች አቶ ምሥጋና ጌታቸው እና አቶ አዳሙ ሁጁራን (አቶ አዳሙ በተጨማሪም የባልደራስ ባለአደራ ም/ቤት ንቅናቄም አባል ናቸው)፤ እንዲሁም «የተጠለፈው ትግል›› ከሚለው መጽሐፍ ሕትመት ጋር በተያያዘም በእስር የሚገኙትን አቶ ፍሬው በቀለ፣ አቶ ሳሙኤል በቀለ፣ አቶ መለሰ ማሩ፣ አቶ ጋዲሳ ዳንኤል እና አቶ አማረ ተፈራን፤ በተጨማሪም የሟች ብ/ጄኔራል አሳምነው ጽጌን ባለቤት ወ/ሮ ደስታ አሰፋንና ሌሎች በርካታ ታሳሪዎችን በማነጋገር ጉዳያቸው ያለበትን ደረጃ እና የእስር ሆኔታቸውንም ተመልክተዋል።

    ዋና ኮሚሸነሩ ‹‹የሴቶች እስር ክፍሉ በአንፃራዊነት የተሻለ እና የጽዳት ደረጃው የተጠበቀ ሲሆን በሌላ በኩል ከ300 በላይ ታሳሪዎችን የያዘው የወንዶች እስር ቦታ እጅግ የተጨናነቀ፣ በውሃ መቋራረጥ እና በታሳሪው ብዛትም የጽዳት ደረጃው ዝቅተኛ ነው» ያሉ ሲሆን ታሳሪዎቹ በየእለቱ ከቤተሰብ፣ ወዳጅ እና የሕግ አማካሪዎቻቸው ጋር ለመገናኘት እንደሚችሉም ለማወቅ ችለዋል።

    በሌላ በኩል “ታሳሪዎቹ ከ 3–4 ወር ያህል የፖሊስ ምርመራን ለማጠናቀቅ በሚል በእስር የቆዩና በአሁኑ ወቅት በሕግ የሚፈቀደው የተጨማሪ ምርመራ ጊዜ በአብዛኛው የተጠናቀቀ እና ቀሪውም በመጠናቀቅ ላይ ያለ በመሆኑ ከዚህ በላይ ታሳሪዎቹ በእስር ሊቆዩ ስለማይገባ እንደየአግባቡ በዋስ ወይም ያለዋስትና ከእስር እንዲለቀቁ ወይም ተዓማኒ የሆነ ክስ በመደበኛው የወንጀል ሕግ መሰርት ሊቀርብ ይገባል” በማለት ዋና ኮሚሽነሩ ገልጸዋል።

    “ከአንድ መጽሐፍ ሕትመት ጋር በተያያዘ የመጽሐፉ ፀሐፊ ነው ተብሎ ከተጠረጠረ ግለሰብ አንስቶ፣ የማታሚያ ቤቱ ባለቤት፣ የመጽሐፉ የፊት ገጽ ዲዛይን የሰራ ግለሰብ፣ የመጽሐፉ አከፋፋይ እና የመጽሐፉ የጐዳና ላይ ቸርቻሪ ሻጭ ሳይቀር እንዲሆም ሌሎች ታሳሪዎች ፍርድ ቤት በሚቀርቡበት ጌዜ ፎቶ አንስተሃል በሚል የተያዘ ጋዜጠኛ ጭምር ለዚህን ያህል ጊዜ በእስር መቆየታቸው አሳሳቢ ሁኔታ በመሆኑ አፋጣኝ እልባት እና የዋስትና መብት መከበር ያስፈልገዋል” በማለት ዋና ኮሚሽነሩ ገልጸዋል።

    ክቡር ዋና ኮሚሽነሩ በተጨማሪም ለጉዳዮቹ ሁሉ ሕጋዊ እልባት ለማግኘት ከሚመለከታቸው የስራ ክፍሎች ጋር በመነጋገር ኮሚሽኑ ክትትሉን እየቀጠለ መሆኑን አሳውቀዋል።

    ጉብኝቱ በዓለም ዓቀፍ የእስር ቤቶች ጉብኝት ደረጃ መሠረት ያለ ቅድሚያ ማስታወቂያ የተደረገ ሲሆን የፖሊስ ኮሚሸኑ አመራሮች እና የጥበቃ ክፍል ኃላፊዎች ለዋና ኮሚሸነሩ ጉብኝቱ በማመቻቸት ኃላፊነታቸውን በመወጣታቸው ዋና ኮሚሸነሩ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

    ምንጭ፦ የኮሚሽኑ ፌስቡክ ገጽ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሸን

    Semonegna
    Keymaster

    ለጅማ ዩኒቨርሲቲ ለአዲስ አበባ ካምፓስ (Jimma University Addis Ababa Campus) ተማሪዎች የሰጠው መግለጫ

    ጉዳዩ፡- ተገቢነት በሌላቸው ጽሁፎችና መግለጫዎች እንዳትደናገሩ ስለማሳሰብ

    ጅማ (ጅማ ዩኒቨርሲቲ) – ዩኒቨርሲቲያችን መንግሥት የከፍተኛ ትምህርትን ለማዳረስ የሚያደርገውን ጥረት በማሳካት ረገድ ግንባር ቀደም ሚና ያለው መሆኑ ከሁላችሁም የተሰወረ አይደለም። የመንግሥትን የትምህርት ፖሊሲ ተግባራዊነት ከማረጋገጥ አኳያ ዩኒቨርሲቲያችን በተለያዩ ደረጃዎች የሚሰጠውን ትምህርት አድማስ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሰፋ መምጣቱ የቁርጠኝነቱ ዓይነተኛ ማሳያ ነው። ይኸውም ዋና መቀመጫው ጅማ ከተማ ሆኖ በአገሪቱ የተለያዩ ስፍራዎችና ከአገር ውጪም በሐርጌሳ ጭምር ካምፓሶችንና የትምህርት ማዕከሎችን ከፍቶ ትምህርቱን በማስፋፋት ላይ የሚገኘውም በዚሁ አግባብ ነው።

    ሆኖም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዩኒቨርሲቲያችን የሚያደርገውን ሕጋዊ እንቅስቃሴ ለማደናቀፍና ለማስቆም የሚሞክሩ አካላት ያላሰለሰ ጥረት በማድረግ ላይ መሆናቸውን ተገንዝበናል። ይኸውም የከፍተኛ ትምህርት አግባብነትና ጥራት ኤጀንሲ እና ጥቂት የኤጀንሲው የሥራ ኃላፊዎች በኤጀንሲው የፌስቡክ ገጽ እና በግል የፌስቡክ ገጽ በለቀቋቸው መረጃዎች እንዲሁም የፕሬስ ኮንፈረንስ ጠርተው በመገናኛ ብዙኃን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ የዩኒቨርሲቲያችንን ስም ሲያጠፉና ሲያቆሽሹ መቆየታቸው ይታወቃል። አሁን ደግሞ የዩኒቨርሲቲያችንን ስም ከማጥፋት አልፈው በቁጥር 01/መ-4/2688/11 መስከረም 6 ቀን 2012 ዓ.ም. በተፃፈ ደብዳቤ በአዲስ አበባው ካምፓሳችን (Jimma University Addis Ababa Campus) በመማር ላይ ለሚገኙ ተማሪዎች ጥሪ በማድረግ ወደ ሌላ ተቋም እንደሚያዛውሯቸው በኤጀንሲው የፌስቡክ ገጽ መረጃ ለቀዋል።

    ነገር ግን ዩኒቨርሲቲያችን የአዲስ አበባውን ካምፓስ (Jimma University Addis Ababa Campus) የከፈተውም ሆነ ላለፉት ሰባት ዓመታት ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ ትምህርት ሲሰጥ የቆየው ዩኒቨርሲቲውን እንደገና ለማቋቋም በወጣው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 240/2003 አንቀጽ 2(1) እና አንቀጽ 3 መሠረት ራሱን የቻለ የሕግ ሰውነት ያለው የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ሆኖ ስለተቋቋመ እና ዋና ግቢው ጅማ ከተማ ሆኖ በሌሎች ቦታዎች የትምህርት ክፍሎች እና የምርምርና የማሕበረሰብ አገልግሎት ማዕከሎችን የማቋቋም መብት በሕግ ስተሰጠው ነው። የድጋፍ አገልግሎት ከሚሰጥ የግል ተቋም ጋር ሕጋዊ ስምምነት ተፈራርሞ ለትምህርቱ የሚያስፈልጉ የአገልግሎት ግብአቶችን በማግኘት ላይ ያለው ደግሞ በከፍተኛ ትምህርት አዋጅ ቁጥር 650/2001 አንቀጽ 93(1) ስር ማንኛውም የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ድጋፍ ሰጪ አገልግሎቶችን በሌሎች አገልግሎት አቅራቢዎች እንዲሰጥ ለማድረግ የሚያስችል ሕጋዊ መብት እንዳለው በተደነገገው መሠረት ነው። ይህም ሆኖ በሕግ ድንጋጌዉ ላይ የጠቅላይ አቃቤ ሕግ ትርጓሜ እንዲሰጥ ተጠይቆ ዉጤቱን እየተጠባበቅን ባለንበት ወቅት ሁከት ለመፍጠር የሚደረገዉ እንቅስቃሴ አግባብነት የጎደለዉ ነዉ።

    በሌላ በኩል ደግሞ የከፍተኛ ትምህርት አግባብነትና ጥራት ኤጀንሲ ሥልጣንና ተግባር ኤጀንሲው በተቋቋመበት የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 261/2004 አንቀጽ 6 እና በከፍተኛ ትምህርት አዋጅ ቁጥር 650/2001 አንቀጽ 89 ስር የተዘረዘረ ሲሆን በሁለቱም ሕጎች ኤጀንሲው ተማሪዎችን ከአንድ የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ነጥቆ ለሌላ ተቋም ለመስጠትም ሆነ አንድን ካምፓስ ለመዝጋት የሚያስችል ሥልጣንና ኃላፊነት አልተሰጠውም። ስለሆነም ኤጀንሲውንና የሥራ ኃላፊዎቹ በዩኒቨርሲቲያችን ዙሪያ የሚያደርጓቸው ማናቸውም እንቅስቃሴዎች በሙሉ ተገቢነት የሌላቸዉ እና በሌላቸው ስልጣን የተፈፀሙ በመሆናቸው በሕግ የሚያስጠይቁ ናቸው።

    ውድ ተማሪዎቻችን! ዩኒቨርሲቲያችን በአዲስ አበባ ካምፓስ ከፍቶ ለተማሪዎች ትምህርት ሲሰጥ የቆየው በሕጋዊ መንገድ መሆኑን እያረጋገጥን ይህንኑ በሕግ የተሰጠውን ሥልጣን በመጋፋት ኤጀንሲውና የሥራ ኃላፊዎቹ በማድረግ ላይ ያሉት አግባብ የሌለዉ እንቅስቃሴ ሕዝብና መንግሥት እንዳይረጋጋ የሚያደርግ በመሆኑ በፅኑ የምናወግዘው ነው። ዩኒቨርሲቲያችን እስከ አሁን ድረስ በኤጀንሲው በበላይ የሥራ ኃላፊዎች ሲፈፀሙ የነበሩትን አግባብነት የሌላቸዉን ተግባራት በትዕግስትና በሰከነ መንፈስ ሲከታተልና መፍትሄ ሲያፈላልግ የቆየ ሲሆን፤ የአሁኑ ተግባር ግን የዩኒቨርሲቲውን ህልውና የሚፈታተንና የኤጀንሲውን የስልጣን እና ኃላፊነት ገደብ የጣሰ በመሆኑ፣ ዩኒቨርሲቲያችን ጉዳዩን ከሚመለከታቸው የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ጋር በመወያየት መፍታትን ጨምሮ ሌሎች አስፈላጊ ተግባራትን ለመፈፀም ቁርጠኛ አቋም የያዘ መሆኑን እየገለፅን፤ በኤጀንሲው ጥሪ ሳትረበሹና ሳትሳሳቱ ዩኒቨርሲቲዉ ከተማሪ እና ከወላጅ ተወካዮች ጋር ባደረገዉ ዉይይት መሠረት ጉዳዩን ለመፍታት እየሠራ መሆኑን አዉቃችሁ በትዕግስት እንድትጠብቁን እናሳስባለን።

    ምንጭ፦ ጅማ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    Jimma University Addis Ababa Campus


    Semonegna
    Keymaster

    ከዴሞክራሲና ከነጻነት ጋር የተቆራኙ እሴቶች
    (ነአምን ዘለቀ)

    ከዴሞክራሲና ከነጻነት መብቶች ጋር ተያያዥነት ያላቸው እሴቶችና ከእነዚህ ጋር የተገናኙ ንድፈ ሃሳቦች ከፍልስፍና አኳያ መነሻቸው አንዱ የሰው ልጅ ክቡርነትና የግለሰብ ሉዓላዊነት መከበር ጋር የተጋመዱና የተያያዙ መሆናቸው ነው። ዴሞክራሲም ሆነ ነጻነት የሰው ልጆችን ክብር፣ የእያንዳንዱን ሰው ሰብዓዊ ክቡርነት (dignity) ከልብ ካልተቀበለ፣ አንዱ ሌላውን ሰው እንደመጠቀሚያ፣ ለአንድ ግብ ማስፈጸሚያ መሣሪያ (means to an end/instrument) የሚመለከት ከሆነ፥ ለምሳሌ በፓለቲካም ሆነ በሌላ “እገሌን ለዚህ ጉዳይ ተጠቀምኩበት” እንደሚባለው ከሆነ ስር የሰደደ የእሳቤው፣ የእሴቶች፣ እንዲሁም የፍልስፍናው ግንዛቤ ላይ ከፍተኛ እጥረት አለ ማለት ነው። ይህንንም በጥልቀት በንድፈ ሃሳብ (theory)፣ እንዲሁም በጽንሰ ሃሳብ (concept) ደረጃ በጥልቀት ማወቅ ቢቻልም፣ ከልባችን ጋር አልተዋሃደም (internalized አልሆነም) ማለት ነው።

    ሰዎችን የግብ ማስፈጸሚያ አድርጎ ማየት ብዙ ጊዜ የግራም ሆነ የቀኝ ርዕዮትን ያነገቡ በጣም ጨካኝና ጠቅላይ ከሆኑ (totalitarian) ርዕዮቶች/ፍልስፍናዎች ፣ የነዚህ ውላጅ ከሆኑ የፓለቲካ ስርዓቶችም የሚመነጭ ነው። በምዕራባውያኑ ዘንድ በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ በሰፊው የተጻፈበትና ልዩ ልዩ አመለካከቶች ያሉ ቢሆንም ከሊበራሊዝም አኳያ በርሊን፣ ከፕራግማቲዝም ሪቻርድ ሮርቲ (Richard Rorty)፣ ከሰብዓዊነት ላይ የተመሠረተ የማርክሳዊ ፍልስፍና አመለካከቶች እንደ ኤሪክ ፍሮም (Erich Fromm) እንዲሁም ሌሎችም ፈላስፎችና ሃያሲዎች የእነዚህ ጠቅላይ ርዮተ ዓለሞች ቅድመ መነሻ/መሠረት ከጥንታዊ ግሪክ ከፕሌቶ ፍልስፍና መሆኑን ተንትነውበታል። ነገር ግን የምዕራባዊ ስልጣኔና አካል ባልሆኑ፣ የእኛንም ማኅበረሰብ ጨምሮ ይህ አመለካከት በቅድመ ዘመናይ (pre-modern) ስርዓተ መንግሥታት የፓለቲካ፣ የባህልና ፣ ማኅበራዊ ግንኙነቶች ውስጥም ሰፍኖ የነበረ መሆኑ ግልጽ ነው።

    በርካታና እጅግ አንገብጋቢ ሃገራዊ ጉዳዮች ቢኖሩም ቅሉ፣ አንዱ የችግሮቻችን ምንጭ ከአስተሳሰብ ጋር፣ ከአመለካከቶች ጋር የተያያዙ ጎጂ የአስተሳሰቦችና እሴቶች (values) መሆናቸው ቀላል ግምት የሚሰጠው አይደለም። የሰው ልጅ ውስብስብ ፍላጎቶች ያለን ፍጥረቶች ነንና ወደ ውስጥ መመልከትና የትኛው ፍላጎት ለምን አላማ የሚለውን ራስን መሞገት ወደ ተሻለ በበጎ የሞራል እሴቶች ላይ የተመሠረተ የፓለቲካ ማኅበረሰብ ለማጠናከር የራሱ አስተዋጽኦ ያደርጋል። የፓለቲካ ጉዳይ ከስልጣን ጋር የተያያዘ መሆንና፣ በዴሞክራሲም ሆነ ዴሞክራሲያዊ ባልሆኑ የፓለቲካ ስርዓቶች ውስጥ ስልጣን (power) የሰው ልጆችን ‘ኮራፕት’ [corrupt] (በጥቅም ብቻ ሳይሆን ስልጣን ላይ ያሉትንም ሆነ ወደ ስልጣን የሚመጡትን ሰዎች የሞራል እሴቶን በማዳከም ጭምር) የማድረግ አቅሙ በጣም ከፍተኛ መሆኑ ቢታወቅም፥ ፍትህ፣ ዴሞክራሲና ነጻነት በሀገራችን እንዲመጣ ከልብ ከተፈለገ ደግሞ ከነዚህ ዓይነት አመለካከቶች ለመጽዳት መሞከር አንዱ የቤት ሥራ መሆን አለበት ማለት ነው።

    የሰውን ልጅ ክቡርነት (dignity) ከልብ ማመን፣ ይህ እሴት እንዲዋሀደን ማድረግ፣ ለዲሞክራሲያዊ ባህል መስፈን፣ ፍትሃዊና ሰብአዊነት የነገሰበት ስርዓት እውን እንዲሆን ለማድረግ በጣም ወሳኝ ከሆኑ እሴቶች አንዱና ዋነኛው ነው። ቅዱሳን መጻህፍትም የሚሉት ‘በአንተ ላይ ሊደረግ የማትፈልገውን በሌላው ሰው ላይ አታድርግ’ ይመስለኛል። ፓለቲካው በርካታና አስፈላጊ የሞራልና የስነ-ምግባር እሴቶች ያስፈልጉታል የሚለው ዋናው ጭብጥ ነው – በተለይ በፓለቲካ ልሂቃን (political elites)። በቀጣይነት ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮች ይኖራሉ። በቸር ይግጠመን።

    አቶ ነአምን ዘለቀን ፌስቡክ ገጻቸው ላይ ይከተሏቸው (Like ያድርጓቸው)፦ Neamin Zeleke
    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ከዴሞክራሲ እና ከነጻነት ጋር የተቆራኙ እሴቶች


    Semonegna
    Keymaster

    ዋትስአፕ (WhatsApp) ሰኞ፣ ግንቦት 5 ቀን 2011 ዓ.ም. ይፋ እንዳደረገው፥ ጥቃቱ የተመረጡ የዋትስአፕ ተጠቃሚዎችን (“select number” of users) ዒላማ ያደረገ ነበር፤ የተቀነባበረውም የላቀ ችሎታ ባላቸው ሀከሮች ነው ተብሏል።

    አዲስ አበባ (ኢመደኤ)– የኮምፒውተር መረጃ መዝባሪዎች (ሀከርስ) የዋትስአፕ መተግበሪያን (WhatsApp app) ተጠቅመው ስልኮችና ሌሎችም የኤሌክትሮኒክስ መገልገያዎች ላይ መሰለያ ጭነው እንደነበረ ተረጋገጠ።

    መሰለያውን የጫኑት የዋትስአፕ መተግበሪያ ላይ ያለ ክፍተትን ተጠቅመው ነው ተብሏል።

    በዓለም ላይ 2.3 ቢሊዮን ሰዎችን ተጠቃሚ በማድረግ ቀዳሚ ማኅበራዊ ሚዲያ (social media) በሆነው ፌስቡክ (Facebook) ስር የሚተዳደረው ዋትስአፕ ይፋ እንዳደረገው፥ ጥቃቱ የተመረጡ የዋትስአፕ ተጠቃሚዎችን (“select number” of users) ዒላማ ያደረገ ነበር፤ የተቀነባበረውም የላቀ ችሎታ ባላቸው ሀከሮች ነው ተብሏል።

    የለንደኑ ዓለም አቀፍ ጋዜጣ ፋይናንሽያል ታይምስ እንደዘገበው፥ ጥቃቱ የተሰነዘረው ‘ኤንኤስኦ ግሩፕ’ (NSO Group) በተባለ የእስራኤል የደኅንንት ተቋም ነው። ባለፈው ሀሙስ (ግንቦት 1 ቀን 2011 ዓ.ም.) ዋትስአፕ የተፈጠረውን ችግር ማስተካከል ችያለሁ ብሏል።

    ጥቃቱ እንደተሰነዘረ የታወቀው በያዝነው ወር መባቻ ላይ ሲሆን፥ ሰኞ ዕለት (ግንቦት 5 ቀን 2011 ዓ.ም.)  ዋትስአፕ 1.5 ቢሊየን ተጠቃሚዎቹ የተሻሻለውን መተግበሪያ እንዲጭኑ (‘update’ እንዲያደርጉ) ጠይቆ ነበር።

    መሰለያ የጫኑት አካሎች በዋትስአፕ መሰለል ወደሚፈልጉት ግለሰብ ይደውላሉ። ከዛም መሰለያውን ይጭናሉ። ግለሰቡ ስልኩን ባያነሳም እንኳን መሰለያውን ከመጫን አያግዳቸውም ተብሏል። ፋይናንሽያል ታይምስ እንዳለው ከሆነ ጥሪ ያደረገው አካል ማንነት ከደዋዮች ዝርዝር (call log) ይጠፋል።

    ዋትስአፕ ለቢቢሲ እንዳሳወቀው፥ ለመጀመርያ ጊዜ ይህ ክፍተት መፈጠሩን ያስተዋለው የድርጅቱ የደኅንነት ክፍል (security team) ነበር። ወዲያው ለሰብአዊ መብት ተሟጋች ቡድኖች እንዲሁም ለአሜሪካ የፍትህ ቢሮ (Department of Justice) አሳውቀዋል።

    “ጥቃቱ ከግል ድርጅት መሰንዘሩን የሚያሳይ ምልከት አለ። ከመንግሥት ጋር በመሆን ያልተፈለገ የስለላ ሶፍትዌር (spyware) በመጠቀም ስልክ መቆጣጠር የሚያስችል ነው” ሲሉ የዋትስአፕ ባለስልጣናት ለመገናኛ ብዙኀን ገልጸዋል።

    ‘ኤንኤስኦ ግሩፕ’ ከመንግሥት ፍቃድ የተሰጣቸው ተቋማት ወንጀልን ለመከታከልና የሽብር ጥቃት እንዳይደርስ ለማድረግ እንዲያውሉት አልሞ የሠራው ነው። ሆኖም አሠራሩ ያላግባብ ጥቅም ላይ ውሎ ከሆነ ምርመራ ይደረጋል ተብሏል።

    ዋትስአፕ ምን ያህል ሰዎች ጥቃቱ እንደደረሰባቸው ለማወቅ ጊዜው ገና ነው ብሏል።

    ከዚህ ቀደም በ’ኤንኤስኦ ግሩፕ’ ጥቃት ደርሶብኝ ነበር ያለው የመብት ተከራካሪው አምነስቲ ኢንተርናሽናል (Amnesty International)፤ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች መሰል ጥቃት ሊደረስባቸው እንደሚችል ስጋት ነበረን ብሏል።

    የአምነስቲ ኢንተርናሽናል የቴክኖሎጂ ክፍል ዳይሬክተር ዳና ሌግሌተን (Danna Ingleton) እንዳሉት፥ ታዋቂ የመብት ተሟጋቾችና ጋዜጠኞችን ለመቆጣጠር በመንግሥታት ጥቅም ላይ የሚውል አሠራር ነው።

    የእስራኤል መከላከያ ሚንስትር የ’ኤንኤስኦ ግሩፕ’ን ፍቃድ እንዲቀማ ለመጠየቅ በአምነስቲ ኢንተተርናሽናል የተመራ የፊርማ ስብስብ ቴል አቪቭ ፍርድ ቤት ይቀርባል።

    ምንጭ፦ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ (ኢመደኤ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዋትስአፕ


    Anonymous
    Inactive

    ዋቸሞ ዩኒቨረሲቲ ዘሬ ቅዳሜ የካቲት 02-2011 ዓ/ም በዩኒቨርሲቲው ታሪክ የመጀመሪያ የሆኑትን የህክምና ዶክተሮች አሰመረቀ፡፡
    —–

    ክብርት ፕሮፌሰር ሂሩት ወ/ማርያም የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሳይነስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ፣ፕሮፌሰር ላጲሶ ጌ. ድሌቦ ፣የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የስራ አመራር ቦርድ አባላት፣ የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የሴኔት አባላት፣ የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ስራ ሃላፊዎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ፣ የዩኒቨርሲቲው ማህበረስብ እና ውድ የተመራቂ ቤተሰቦች በተገኙበት በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ታሪክ የመጀማሪያ የሆኑትን የህክምና ዶክተሬት ተማሪዎችን በደማው ሁኔታ አስመረቀ፡፡

    በህ/ጤ/ሳይ/ኮሌጅ፤
    – በቅድመ-ምረቀ በ3 ት/ት መሽኮች በህክምና ዶክተሬት ወንድ 26 ሴት 8 (ድምር 24)፣ በህ/ሰብ ጤና ወንድ 37 ሴት 15 (ድምር 52)፣ በሰርጂካል ነርስ ስፔሻሊቲ ወንድ 11 ሴት 7 (ድምር 18)፣ እና በድህረ ምረቃ በህብረተሰብ ጤና ወንድ 2 ሴት 1 (ድምር 3) በአጠቃላይ ወንድ 76 ሴት 31 (በድምሩ 96) ተማሪዎች፣
    – በግ/ሳ/ኮሌጅ በቅድመ ምረቃ በክረምት መረሃ ግብር በ2 ትምህርት መስኮች በተፈጥሮ ሀብት አያያዝና በዕጽዋት ሳይንስ ወንድ85 ሴት 8 (በድምሩ 93) ተማሪዎች፣
    – ቢዚነስ እና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ በድህረ ምረቃ በአካውንቲንግና ፋናንስ በመደበኛ መርሃ ግብ 4 ተማሪዎች፣

    በአጠቃላይ በውድመ ምረቃ እና በድህረ ምረቃ በመደበኛ እና በክረምት መርሃ ግብር ሰለጠኑ ወንድ 165 ሴት 39 በድምሩ 204 ተማሪዎችን አሰመርቋል፡፡

    በምረቃውም በሁላቱም ጾታ አመረቂ ውቴት የመጡ ተማሪዎች የተሸለሙ ሲሆን ከ ሴቶች ዶ/ር ጋዲሴ ሰስፋ ከወንዶች ዶ/ር ዋክሹም ፌጠነ የሰርትፍኬት እና የብር ሽልማት ተሸለመዋል፡፡ ዶ/ር ዋክሹም ፌጠነ በአጠቀላይ የሜዳሊያ ተሸላሚ ነው፡፡

    ምንጭ፦ ከዩኒቨርሲቲው ፌስቡክ ገጽ

    Anonymous
    Inactive

    የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ዱራሜ ካምፓስ ለአቅመ-ደካሞች ቤት ሠራ!

    የሣይንስና ከፍተኛ ት/ት ሚኒስተር ባስቀመጠው “አንድ ቀን ለሕዝቤ” መርሃ-ግብር መሰረት ፣ ዛሬ በ25/05/2011 ዓ.ም. “የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የዱራሜ ካምፓስ ለሕዝቤ” በሚል መሪ ቃል ለሁለት የደሃ ደሃ ቤተሠቦች ማለትም ለአቶ አማን መሐመድ ከቀርጭቾ ቀበሌ እና ለአቶ አባቶ መኬቦ ከ ጠዛ አጋራ ቤት መልሶ የመገንባት ስራ በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የዱራሜ ካምፓስ በጎ ፈቃደኛ አስተዳደር ሠራተኞች፣ መምህራን ፣ ተማሪዎችና ሌሎች የግቢው ማህበረሰብ አባላት ተሰርቷል።

    ከቤቱ በተጨማሪ ፣ለእያንዳንዳቸው አባወራዎች ስፓንጅ ፍራሽና ብርድልብስ ተበርክቶላቸዋል።

    በመጨረሻም፣የቤቱ ባለቤቶችና በቦታው የነበሩ ጎረቤቶቻቸው አስተያየታቸውን ተጠይቀዋል። የተሰማቸውን ሲገልፁም÷ ” ይህ በጎ ተግባር መቀጠል አለበት፣ አቅመ-ደካሞችን ከመርዳቱም በላይ ማህበረሰቡ ስለ ተቋሙ መልካም አመለካከት ከመቼውም በላቀ ሁኔታ እንዲኖረው ያደርጋል፤ ተቋሙንም እንደ ዐይኑ ብሌን እንዲጠብቅ የባለቤትነት ስሜት ያሳድርበታል” ብለዋል።

    ምንጭ፦ ከዩኒቨርሲቲው ፌስቡክ ገጽ

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 18 total)