Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 106 through 120 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    የህወሓቶች እብሪት ― የህወሓቶች ውድቀት ― እንደሀገር፣ እንደዜጋ የሚያስተምረን ትምህርት
    (አቶ ነአምን ዘለቀ)

    ጆርጅ ሳንታያና (George Santayana) የተባለው ፈላስፋ “ታሪክን የማያስተውሱ ታሪክን በመድገም ይረገማሉ” (‘Those who cannot remember the past are condemned to repeat it.’) እንዳለው፥ አምባገነኖች ከሂትለት እሰከ ሳዳም ሁሴን – ካለፈው መማር ሳይችሉ ያንኑ ሲደጋግሙ ኖሩ። የህወሓቶች እብሪት፣ ትእቢት፣ ለኢትዮጵያ ሕዝብ የነበራቸው ንቀት የዚሁ እብሪተኞች ካለፈው ለመማር አለመቻልና የፍትህን ማዕከላዊነት ጥሎ ልከኝነት ረግጦ የመራመድ ቅጥያ ውጤት ነው።

    ለ27 ዓመታት ፍጹም ሊባል በሚችል የበላይነት የመንግሥት፣ የኢኮኖሚ፣ የወታደራዊና የደህንነት ቦታዎች ላይ የአንበሳ ድርሻውን ይዞ የነበረው ህወሓት፥ ከ2018ቱ (እንደ አውሮፓውያን አቆጣጥር) ለውጥ በኋላ በእኩልነት ለመኖር የተሰጠውን ዕድል መቀበል እንዳልቻለ ግልጽ የነበረው የዛሬ ሁለት ወር ተኩል ገደማ በትግራይ በሚገኘው የሰሜን እዝ ሠራዊት አባላት ላይ ያደረሰው መብረቃዊ ጥቃትና ጭካኔያዊ እርምጃ ያን ተከተሎ በተደረገው ሕግን የማስከበር ወታደራዊ ዘመቻ የተጀመረ ሳይሆን ከሁለት ዓመት ተኩል ጀምሮ አንደ ነበር ግልጽ ነው ።

    ያ የነበረውን ሁለንተናዊ የበላይነት ሲያጣ የሞት ሞት ሆነበትና እንዴት ያድርገው!? መላ ቅጡ ጠፋው። ከጅምሩም የያዙትን ስልጣን ለፍትህ፣ በልከኝነት፣ ለሕዝብና ለሀገር ጥቅም ለማስከበር ሳይሆን በሀገርና በሕዝብ ኪሳራ የራሳቸውን፥ አለፍ ሲልም የአንድ ብሔር ሊሂቃን የበላይነት ለማረጋገጥ የተቀሙበት የዘረፋ፣ የዘረኝነትና የመንግሥታዊ ሽብር መሣሪያቸው ነበር። ህወሓቶች ስለራሳቸው ልዩ መሆን፣ ከሌላው ኢትዮጵያዊ የተለየ ጀግንነት፣ ብቃትና ክህሎት ራሳቸው በፈጠሩት የሀሰት ትርክት በእብሪትና በትእቢት የተወጠረው አእምሮአቸው አዲሱን የኢትዮጵያ የለውጥ መንገድ እንዲሁም ከለውጡ ጋር ተከትሎ የመጣውን ነባራዊ እውነታ ሊቀበሉ አልቻሉም።

    እነ ስዩም መስፍን ኢትዮጵያን “ሶርያና የመን እናደርጋታለን” ብለው በአደባባይ አወጁ። እነ ጌታቸው ረዳ “ትግራይ ሀገር መንግሥት መሆን እንዳለባትና እና በቀጣይም ከኢትዮጵያ ጋር ሶማሌላንድ ከሞቃድሾ ጋር እንዳላት ግንኙነት ነው የምንፈልገው” በማለት በድፍረት ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነገሩ። “ተራራን ያንቀጠቀጥን”፣ “የደርግን ሠራዊት የደመሰስን”፣ “ከወርቅ ሕዝብ የተገኘን”፣ “ኢትዮጵያን እንደ አዲስ የሠራን”፣ “የብሔር ብሔረሰቦችን መብት ያረጋገጥን”፣… ብለው ለአስርት ዓመታት የሰበኩት ህወሓቶች የሀሰት ትርክቶቻቸውንም አብጠው አብጠው በአምሮአቸው ውስጥም ተገንብተው፣ ጠጥረውና ደድረው እውነታን ለማየት የማያስችል ግርዶሽ ሆነው ቆዩ። በርካታ የትግራይን ወጣቶችንም በዚሁ ትርክት እወናበዱ። መሬት ላይ ካለው ከነባራዊው እውነታ ጋር ፍጹም በተቃራኑ ቆሙ። እውነታውን ተቀብለው ለመሄድም በትዕቢት፣ በእብሪት፣ በዘረኝነት የተተበተበው ልቦናቸውና ህሊናቸው ፈጽሞ አልፈቅድላቸው አለ።

    በመሆኑም ህወሓቶች ማድባትና መዘጋጀት ጀመሩ። ለሁለት ዓመታት ሲደራጁ፣ ሲዘጋጁ ቆይተው ማዕከላዊ መንግሥቱን ዳግም ለመቆጣጠር፥ ይህ ካልሆነም ኢትዮጵያን አተራምሰውና በታትነው “የትግራይን ሀገር መንግሥት” ለመመሥረት “በመብረቃዊ ጥቃት” በሰሜን እዝ ላይ ክህደትና ጭካኔ የተሞላበት ግፍ ፈጸሙ። በስልጣን ዘመናቸውም ግፍና መከራ ለሕዝብ ሲሰፍሩ ኖሩ። በሰፈሩት ቁና መስፈር አይቀርምና የሚሊዮኖች እምባ፣ የብዙ ሺዎች ደም፣ ዋይታና ሰቆቃ፣ በህወሓቶች ግፍ የተሰደዱ የአስር ሺዎች ኢትዮጵያውያውን መከራ ፈጽሞ ይሆናል ብለው ባልጠበቁትና ባልተዘጋጁበት የበስተርጅና እድሜያቸው፣ በመጦሪያ ዘመናቸው እጅግ የመረረ ዋጋ ጠየቃቸው። በመጨረሻም መራሩን ውድቀትና ውርደት አከናነባቸው። የኢትዮጵያ ሕዝብም ‘አክ እንትፍ!’ እንዳላቸው ሊከሰትላቸው ፈጽሞ ሳይችል ቀርቶ በስተርጅና እድሜያቸው ለውድቀትና ለውርደት፣ ገሚሶቹ ደግሞ በመደምሰስ ፍጻሜያቸው ባጁ።

    የኢትዮጵያ አምላክም በእነዚህ ግፈኞች ላይ መብረቃዊ ጥቃት ያደረሰ ይመስለኛል። ስልጣንና ሀብት ደደብና ደነዝ አድርጎ ለውርደት ከዳረጋቸው ከህወሓቶችና ካለፉ አምባገነኖች ታሪክ ለመማር ያልቻሉ፥ አሁንም በያዙት ስልጣን መከታ በማድረግ በሕዝብ ጫንቃ ለመናጠጥ የሚሞክሩ፣ ፍትህን፣ ሰላምን፣ ለሀገር የሚበጀውን፣ የዜጎችን ህይወት የሚለውጥ ተግባር ላይ ከማተኮርና ከመትጋት ይልቅ ሕዝብን ከሕዝብ የሚከፋፍሉ፣ የብሔር ካርድ ለስልጣን ማጠናከሪያ የሚመዙ፣ የሕዝብ ሰላም የሚያውኩና ሀገሪቱ እንዳትረጋጋ የሚደነፉ፣ በየመድረኩም የሚፎክሩ አፍራሽ በየብሔሩ ስም የተደራጁ ኃይሎችና ቡድኖች በገዢው ፓሪቲ የሚገኙ እንዳንድ መሪ ካድሬዎች ከዚህ ታሪክ ይማሩ ይሆን?

    ከስልጣን ጋር በሚመጣ እብጠትና ማን አለብኝነት ብዙ ርቀት የማያስኬድ መሆኑን ማጤን ትልቅ አስተውሎ ነው። ከፋፋይና ሕዝብን በጭንቀት ውስጥ እንዲኖር ከሚያደርጉ የማኅበራዊ ሚዲያዎችና በየሚዲያው ከሚሰነዘሩ መርዛማና ከፋፋይ አሰተያየቶች ለመሰንዘር ከመሽቀዳደም በጎ በጎውን፣ ለሀገር የሚበጀውን፣ ለሕዝብ ተስፋ የሚሆንውን፣ ለሥራ-አጡ ሥራ የሚፈጥረው፣ ኢትዮጵያን የሚያለማውን፣ ሕዝብ ከሕዝብ የሚያቀራርቡ ተግባራት ላይ ማተኮርና መትጋት በኃላፊነት ላይ ለሚገኙ እነዚህ የገዥው ፓርቲ መሪ ካድሬዎች ቅድሚያ ሊሰጡት ይገባል።

    የሕዝብን ጥቅም ማስቀደም፣ የሕግ የበላይነትና ፍትህን ያማከለ ብሎም ለእያንዳዱ ዜጋ በየትኛውም ክልልና ቦታ ለሚኖር ኢትዮጵያዊ/ት የደህንነት ዋስትናው የሚጠበቅበት፣ ሠርቶ ለፍቶ በሰላም መኖሩ የሚረጋገጥበት፣ የዜጎችን ህይወት የሚቀይሩ እንቅስቃሴዎች ላይ በማተኮር ሕዝብን የሚጠቅም ሥራ ሠርቶ ጊዜው ሲደርስ ስልጣን ማስተላለፍ መሆን ይገባዋል። ስልጣንን ለማቆየት የብሔር ካርድ በየዕለቱ መምዘና ህወሓቶች እንዳደረጉት የሕዝብም አብሮነት የሚሸረሽሩ፣ ብሔር ለብሔር የሚያጋጩ ተግባራት ላይ መጠመድ ዋና ሥራ ሆኖ መቀጠል የለበትም። ከሶማሌ ክልል ፕሬዝዳንት ከሙስጠፋ ኦማርና ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ እና ከሌሎችም ሊማሩ ይገባል።

    ሕዝብ በአግባቡና በቅጡ ማገልገል ቅድሚያ መስጠቱ በህወሓቶች ውድቀትና ውርደት ዋዜማ ትልቁ ትምህርት ይህ እንደሆነ መቀበል ብልህነት ነው ። ለሀገርና ለሕዝብም ብቸኛው መንገድ የሕዝብን ሰላም፣ ደህንነት፣ ፍትህ፣ መብቶችና ጥቅሞች እንዲሁም አስከፊውን ድህነት ለማስወገድ አካታችና ዘላቂ ልማትን ማስቀደም መሆን አለባቸው። የህወሓቶች ውድቀት ዋዜማ እንደ ሀገር ምን እንማራለን ለሚለው አንዱ አስተምሮና አስተውሎ ይህ ይመስለኛል።

    አቶ ነአምን ዘለቀ

    የህወሓቶች እብሪት ― የህወሓቶች ውድቀት

    Anonymous
    Inactive

    መቆሚያ ያጣው በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል ዞን) ያሉ ሰዎች እልቂት!
    አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ (ኢሰመጉ)

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ) በቤንሻንጉል ጉሙዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ መተከል ዞን፣ በቡለን፣ ድባጤ፣ እና ዳንጉር ወረዳዎች ላይ በንጹኃን ሰዎች ላይ የሚፈጸመው ጥቃት አሁንም ተባብሶ መቀጠሉ እጅግ አሳስቦታል።

    ኢሰመጉ ታህሳስ 15 ቀን 2013 ዓ.ም ባወጣው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል ዞን)፣ ቡለን ወረዳ፣ በኩጂ ቀበሌ ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት ከ100 በላይ ንጹኃን ሰዎች መገደላቸውን፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መፈናቀላቸውን እና ለከፍተኛ ችግር የተጋለጡ መሆናቸውን አውግዞ፤ መንግሥት በአካባቢው በተደጋጋሚ ጊዜ የሚከሰተውን የንጹኃን ሰዎች ሰቆቃ ለማስቆም የሚያስችል ፈጣን፣ ተጨባጭ እና ዘላቂ መፍትሔ እንዲያበጅ ማሳሰቡ አይዘነጋም።

    ሆኖም፤ ከሰሞኑ ይኸው ችግር ዳግም ተከስቶ ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውን ተጎጂዎች እና የተጎጂ ቤተሰቦች ለኢሰመጉ ተናግራዋል። ታህሳስ 25 ቀን 2013 ዓ.ም ከቻግኒ ወደ ግልገል በለስ የሚሄድ መኪና ውስጥ የነበሩ ተጓዦች ማንዱራ ከተማ ላይ በታጣቂዎች እንዲወርዱ ተደርጎ አንድ ሰው መገደሉን እና ሁለት ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን ለማወቅ ተችሏል።

    ከጥር 2 እስከ ጥር 3 ቀን 2013 ዓ.ም. በቡለን እና ጉባ ወረዳዎች፣ ኦሜድላ እና አይነሸምስ በተባሉ ቀበሌዎች ላይ ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት ከ50 በላይ ሰዎች መገደላቸውን እና መኖሪያ ቤቶችም መቃጠላቸውን ኢሰመጉ መረጃዎች ደርሰውታል።

    በሌላ በኩል፤ ‹‹በድባጤ ወረዳ፣ ቆርቃ ቀበሌ፣ ዳሌቲ በተባለች መንደር ትላንት ጥር 4 ቀን 2013 ዓ.ም ከሌሊቱ 11፡30 ጀምሮ የኦነግ ሸኔ እና የቤኒን ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት ሰዎች መገደላቸውን፣ እስከአሁን ድረስ እኔ ራሴ ባለሁበት የ82 ሰዎች አስከሬን በፍለጋ መገኘቱን እና የቀብር ቦታዎች እየተዘጋጁ መሆኑን አይቻለሁ›› ሲሉ አንድ የዓይን እማኝ ለኢሰመጉ ተናግረዋል።

    ኢሰመጉ በትላንትናው (ጥር 4 ቀን) ጥቃት ሰለባ የሆኑ ሰዎች ቁጥር ከ100 ሊበለጥ እንደሚችል፣ በአብዛኛው ሴቶችና ህጻናት መሆናቸውን እና ከ24 በላይ የሚሆኑ ሰዎች ቆስለው በጋሊሳ ጤና ጣቢያ እና ቡለን ሆስፒታል ውስጥ ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑን ከአካባቢው ካሰባሰባቸው መረጃዎች ለማወቅ ችሏል።

    በመሆኑም፥ መንግሥት ድርጊቱን የሚፈጽሙ አካላትን በአግባቡ አጣርቶ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወስድ፤ ለዚህ ተደጋጋሚ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ፈጣን፣ ተጨባጭ እና ዘላቂ መፍትሔ ማፈላለጉ ላይ በብርቱ እንዲሠራ ኢሰመጉ ያሳስባል። ኢሰመጉ ይህ ጉዳይ እልባት እንዲያገኝ ሁሉም ግለሰቦች፣ የማኅበረሰብ አንቂዎች፣ መገናኛ ብዙኃን፣ የሲቪል ማኅበራት፣ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ የሀይማኖት ተቋማት እና የሀገር ሽማግሌዎች በመንግሥት ላይ ውትወታ እንዲያደርጉ ጥሪውን ያቀርባል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ)
    ጥር 5 ቀን፥ 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    መቆሚያ ያጣው በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል ዞን) ያሉ ሰዎች እልቂት

    Anonymous
    Inactive

    አስር ሞት፤ አቦይ ስብሐት እና በነፍስ የተያዙ የህወሓት አመራሮች
    /
    የአቶ ስብሐት ነጋ በሕይወት መያዝ ከተገደሉት አመራሮች የበለጠ ያለው አንድምታ/

    (ያሬድ ኃይለማርያም*)

    ልክ እንደ አቦይ ስብሐት [ስብሐት ነጋ]* የቀሩትም የህወሓት አመራሮች በህይወት ተገኝተው በሕግ ጥላ ስር እንዲሆኑ እመኛለሁ። በህይወት እንዲገኙ መመኘቴ መቼም ሳይገባችሁ አይቀርም። እነሴኮ ቱሬ ጌታቸው አንድ ሞት ነው የሞቱት። እኔ ለህወሓት አመራሮች አንድ ሞት ስለሚያንሳቸው አስር ሞት ነው የምመኘው። አስር ሞት ደግሞ አንቱ በተባልክበት ቴሌቪዥን ጣቢያ ‘ጁንታው ስብሐት ነጋ ተያዘ’ ከሚለው ይጀምራል። ብዙዎችን በግፍ ወዳሰቃየህበት ቃሊቲ መውረድ ሌላው ሞት ነው። በወንጀል ሊያውም በዓለም አቀፍ ወንጀል ጭምር በሚያስከስስ ወንጀል መከሰስ ደግሞ የሞት ሞት ነው። በየቀኑ ያንን ቢጫ የእስረኞች ቱታ አጥልቀው ይንቁት በነበረው ችሎት ፊት መቅረብ ዘጠነኛው ሞት። በየቀኑ ሱፍና ከረባት አጥልቀህ በምትንጎማለልበት ከተማ እና አስሬ ስምህ በበጎ በሚጠራበት ቴሌቪዥን ላይ ዳኞች ፊት ቀርበህ የፍርድ ቤት ውሎህ እና የወንጀል ታሪክህ ሲዘከዘክ እና መጨረጫም ሲፈረድብህ አስር ሞት ማለት ነው።

    ላለፉት ሰላሳ አመታት በሺዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያንን የገደሉና ያስገደሉ፣ በየእስር ቤቱ  አጉረው ፍጹም ጸያፍ በሆነ መንገድ ያሰቃዩና የደበደቡ፣ ብዙ ሺዎችን ከአገር ያሰደዱ፣ ሚሊዮኖች ከቤት ንብረታቸው እንዲፈናቀሉ ያደረጉ፣ ኢትዮጵያንን በጎጥ ከፋፍለው ሕዝቡን ወደ እርስ በርስ ግጭት የዶሉ፣ የብዙ ሺህ ወጣቶችን ህልም እና ተስፋ ያጨለሙ፣ የሀገር ሀብት የዘረፉ እና ያዘረፉ፣ እጅግ የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን የፈጸሙና ያስፈጸሙ እነዚህ የህወሓት አመራሮች ለፍርድ ቀርበው በጥፋታቸው ልክ ሲቀጡ ማየት የዘወትር ምኞቴ ነበር።

    እነዚህ ሰዎች ሁሉም በጦርነቱ ተደምሰው ቢሆን ኖሩ በብዙ መልኩ ጥሩ እንድምታ አይኖረውም ነበር። ሌላውን ልተወውና የሁሉም መሞት አንዱ መጥፎ እንድምታ እነዚህን ሰዎች ታሪካቸውን በደንብ ካለማወቅ፣ የፈጸሙትን የወንጀል ልክ በቅጡ ካለመረዳት በተወላጅነትም ይሁን በሌላ መልኩ ሲደግፏቸው የኖሩ እና አሁንም የሚደግፏቸው ሰዎች ከምን ዓይነት ሰዎች ጀርባ ወይም ጎን እንዲቆሙ እንዳያውቁ እና ሰዎቹንም እንደ ጀግና ሳይሆን በወንጀል የተዘፈቁ ኃጥአን መሆናቸውንም ይረዳሉ።

    ነጻና ፍትሓዊ በሆነው የፍርድ ሂደት ህወሓት እና አመራሮቿ ከውልደታቸው እስከ ክሽፈታቸው የፈጸሙት ወንጀል በግልጽ ችሎት ፊት ይነገራል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። የሠሯቸው ወንጀሎች ከነማስረጃዎቹ በአግባቡ ተሰንደው ለታሪክም ጭምር ይቆያሉ። ፍትህም ቀና ትላለች። ተበዳዮችም ቢያንስ በሞራል ይካሳሉ። የዛሬዎቹም ሹሞች ከህወሓት ውድቀት ትምህርት ይወስዳሉ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ።

    ለዛሬዎቹ ሹሞች ከዚህ የሚማሩበት ልቦና ይስጣቸው!

    * ማስታወሻ፦
    በሀገራችን ላለፉት 27 ዓመታት የማተራመስ ስትራቴጂ የነደፈ፣ ያስተባበረ እና ያደራጀ በመጨረሻም ጦርነት እንዲቀሰቀስ በማድረግ በሀገራችን ሠራዊት ላይ እጅግ ዘግናኝ ጦርነት በመክፈት ሠራዊቱን ያስጨፈጨፈው የህወሓት ቁንጮ እና ከመሥራቾቹ አንዱ የሆነው  ስብሐት ነጋ (በሥራ ባልደረቦቹ አቦይ ስብሐት በመባል ይታወቃል) መዋሉን ታህሳስ 30 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    አቶ ያሬድ ኃይለማርያም መቀመጫውን ጄኔቭ ከተማ፥ ስዊዘርላንድ ያደረገ ስብስብ ለሰብዓዊ መብቶች በኢትዮጵያ (Association for Human Rights in Ethiopia) የተባለ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የአቶ ስብሐት ነጋ መያዝ

    Anonymous
    Inactive

    ቀጣዩን ሀገር-አቀፍ ምርጫ ባሰብን ጊዜ…
    (የብሔር ፖለቲካ እና መጪው የኢትዮጵያ ምርጫ)
    ጌታሁን ሄራሞ (ኢ/ር)

    በሀገራችን በምርጫ ዲሞክራሲ ሂደት ብሔርን መሠረት ያደረጉ ፓርቲዎችን ተከትሎ ከሚከሰቱ ተቃርኖዎች (paradoxes) ውስጥ አንዱም፥ ተወዳዳሪዎቹ መነሻ ላይ ብሔራቸውን ብቻ ወክለው ካሸነፉ በኋላ በድኅረ-ምርጫው 82 ብሔሮች የሚኖሩባትን ሀገርን ለመምራት መብቃታቸው ነው። ጅምር ላይ የአንድ ብሔር ውክልና ብቻ ያለው ተወዳዳሪ በምን አመክንዮ ነው 82 ወይም ከዚያም በላይ ብሔሮች የሚኖሩባትን ሀገር መምራት የሚችለው?

    ናይጄሪያ ውስጥ የብሔር ፓርቲዎች እንደ አሸን በፈሉበት ወቅት ከላይ የጠቀስኩት ግራ አጋቢ ውክልና አወዛጋቢ በመሆኑ በሂደት ሁለት ቅድመ ሁኔታዎች በፖሊሲ አውጪዎቹ ተቀመጡ። የመጀመሪያው “የትኛውም የብሔር ፓርቲ ሀገራዊ ስሜትን (national sense) የሚያንፀባርቁ አንቀፆችን በፕሮግራሙ ውስጥ በግልፅ ማስቀመጥ አለበት” የሚል ነበር። እናም ፕሮግራሙ ውስጥ የራሱን ጎጥ ጥቅምና ጥያቄ ብቻ የጠቀጠቀ የብሔር ፓርቲ ሀገርን መምራት አይችልም፤ በምርጫ ቦርዱም የመመዝገብ ዕድሉ የለውም። ሁለተኛው ቅድመ ሁኔታ ደግሞ… አንዳንድ የብሔር ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች የመጨረሻ ህልማቸው ትልቋን ናይጄሪያን መምራት ከሆነ በምርጫ ወቅት ከራሳቸው ክልል በዘለለ ሌሎች ብሔሮች በሚኖሩበት ክልሎችም ጭምር እንዲወዳደሩ የሚያስገድድ ነበር። በነገራችን ላይ ናይጄሪያ ብሔርን ከፖለቲካ ለማፋታት የተጠቀመችበት ዘዴ “positive banning” ተብሎ ይጠራል። ሂድ አትበለው ግን እንዲሄድ ግን አድርገው ዓይነት… (ብሔርን ከፖለቲካ ማፋታት ማለት የብሔር ብሔረሰቦች መብት ባህልና ታረክን አለማክበር ማለት እንዳልሆነ እዚህ ጋር ይሰመርልኝ፤ ብዙ ሀገሮች ጎጥ፣ ጎሳና ብሔር ወደ ፖለቲካ ሰፈር ድርሽ ሳይሉ የዜጎቻቸውን ባህልንና ራስን በራስ የማስተዳደር መብትን በአማራጭ የፌዴራል ዲዛይን ተግብረዋል።)

    በምርጫ ወቅት ብሔሩን ወክሎ የማታ ማታ ለሀገር መሪነት የሚበቃ መሪ፦

    1. በሥልጣን ወንበሩ ላይ እንደተቀመጠ ሀገራዊ ስሜትን አንፃባርቆ ሁሉንም ብሔሮች በእኩልነት መምራት ሲጀምር ቀደም ሲል ውክልናውን በሰጠው በገዛ ብሔሩ ዘንድ እንደ ከሀዲ ይቆጠራል።
    2. ሌሎች ብሔሮችን በእኩልነት ከመምራት ይልቅ በመንግሥታዊ ተቋማት ምሥረታና በሌሎች ሲቪክ መሥሪያ ቤቶች መዋቅር ውስጥ የብሔሩን ተወላጆች ብቻ እየመረጠ የሚሾም ከሆነ ደግሞ በሌሎች ብሔሮች ዘንድ “ተረኝነት”ን እንደሚተገብር፣ ወገንተኛና ኢ-ዲሞክራሲያዊ መሪ ሆኖ ይከሰሳል።

    ይህ የብሔር ፓርቲ የሚያስከትለው አዙሪት የፖለቲካ ሳይንትስቶችንም የሚያወዛግብ ነው፤ በካሊፎርኒያ ዩኒቨርሲቲ የአንፃራዊ ፖለቲካ (comparative politics) ሳይንትስት የሆነው ፕሮፈሰር አረንድ ሊፓርት (Arend Lijphart) በብሔር ፖለቲካ የምትመራ ሀገር ካለች በመሪነቱ ሂደት ልዩ ልዩ ሀሳቦችን የሚያንፀባርቁ ልሂቃን በ“grand coalition” አጋዥነት ተሳባስበው በአመራሩ መሳተፍ አለባቸው ያለው ከላይ ያነሳሁትን ተቃርኖ ለመቀነስ በማቀድ ነው፤ እንዲሁም የብሔር ፖለቲካን የሚያራምዱ ሀገራት በየትኛውም መስፈርት መተርጎም ያለባቸው ተመጣጣኝ ውክልናን መሠረት ያደረገ የምርጫን ሥርዓት ነው ያለውም ከዚሁ ተነስቶ ነው። በተመጣጣኝ የውክልና ምርጫ መርህ ቢያንስ ሌሎች ተፎካከሪ ፓርቲዎች ወደ ፓርላማ በመግባት ሚዛኑን ሊያስጠብቁ ይችላሉ።

    ከፕሮፈሰር ሊፓርት በተጨማሪ የሕግና የፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፈሰሩ ዶናልድ ሆሮውዝም (Donald Horowitz) (በብሔር ግጭቶች ጥናት ጥርሱን የነቀለ ሳይንትስት ነው) የብሔር ፓርቲ መዘዝ የሚያመጣውን የአመራር ሳንካ ለመቀነስ “centripetal” ዲሞክራሲን መተግበርን በቅድመ ሁኔታነት ያስቀምጣል። ከላይ ናይጄሪያዎች ጥቅም ላይ እንዳዋሉት ያስቀመጥኩት ጽንሰ-ሀሰብ ባለቤትነቱ የፕሮፈሰር ሆሮውዝ ነው… የአንድ ብሔር ተወካይ የሆነው የምርጫ ተወዳዳሪ ሕልሙ ሁሉም ብሔሮች የሚኖሩባትን ሀገር መምራት ከሆነ መወዳደር ያለበት ከራሱ ቀዬ ባለፈ በሌሎችም ክልሎችም ነው… የሚለው መርህ የሆሮውዝ ነው።

    ከላይ ያነሳሁትን የብሔር ፓርቲን መዘዝ እኛ ኢትዮጵያዊያን ለፖለቲካ ሳይንሱ ባይተዋር ብንሆን እንኳ መሬት ላይ ወርዶ ያየነው እውነት ነው። ህወሓት በቀዬዋ ለምርጫ ተወዳድራ አመሻሽ ላይ ለሀገር መሪነት ስትበቃ የሀገሪቷን ተቋማት ያስወረረችው በራሷ ሰዎች ነበር፤ ሌላው ቀርቶ ክልሎችም ይመሩ የነበሩት በሞግዚትነት በራሷ ተወካዮች ነበር። ለዚህም ነበር በሀገሪቱ የፖለቲካ መዋቅር ውስጥ የ“አንድ ብሔር በላይነት” ስለመስተዋሉ ብዙዎች እሪታቸውን ሲያስደምጡን የነበረው!! የአሁኑ ጠቅላይ ሚኒስትር የሆኑት ዶ/ር አብይም በብሔር ፖለቲካ ባቡር ተሳፍረው ወደ ሥልጣን ከመጡበት ማግስት ጀምሮ ብዙዎች ስለ “ተረኝነት” ስጋት ተሰምቷቸው ድምፃቸውን ማሰማታቸው የአንድ ብሔር ውክልና ከፈጠረው ድባብ የተነሳ ነው። በብሔር ፖለቲካ ቦይ ፈስሶ ለሥልጣን መብቃት ፈተናው ለተሿሚውም ቢሆን ብዙ ነው።

    በነገራችን ላይ አሁን የታሪክ አጋጣሚ ሆኖ ሀገራችን እየተመራች ያለችው የብሔር ፖለቲካ ውልዶች በሆኑ የፖለቲካ ሰዎች ነው። ምናልባትም በቀጣዩ ምርጫ አሸናፊዎቹ በቦሌም ይሁን በባሌ እነሱ ሊሆኑ ይችላሉ። ሀገራችን ብሔርን ብቻ መንደርደሪያ ካደረገው የፖለቲካ ሥርዓት በተለየ ሌላ ዓይነት የፌዴራል የአስተዳደር መዋቅር እስከሚያጋጥማት ድረስ ገዥው የብልፅግና ፓርቲ ከሀገራችን የፖለቲካ አውድ በሚስማማ መልኩ የነአረንድ ሊፓርትንና የዶናልድ ሆሮውዝን ጽንሰ-ሀሰቦችን ቢያጤን መልካም ነው። የብሔር ፖለቲካ ያመጣብን መዘዝ ሀገር በቀል በሆኑ እሳቤዎች ብቻ እልባት የሚያገኝ አይደለም። ሐኪሞች በሀገር ውስጥ ለማከም የሚያዳግታቸውን በሽታ ከአቅማችን በላይ ነው በማለት እልባት ያገኝ ዘንድ ወደ ውጭ ሀገር “refer” ያደርጉ የለ? እዚህ ጋር ያስቀመጥኳቸው ምስሎች የሚያመለክቱት የኔዜርላንድና የአሜሪካ ጥምር ዜግነት ያለው ፕሮፈሰር ሊፓርት /Lijphart/ ከአራት ዓመታት በፊት ለካናዳ የምርጫ ኮሚቴ ስለ ተመጣጣኝ ምርጫና ስለ ዲሞክራሲ መርሆች ከራሱ ንድፈ ሐሳቦች ጋር በማገናኘት የቪዲዮ ኮንፍረንስ ላይ ሀሳቡን ሲሰጥ ነው። ካናዳዎቹ ለመፍትሔዎቻቸው “ሀገር-በቀል” መፍትሔ ብቻ ያስፈልጋል በሚል ግትር አቋም ሳይወሰኑ ጠቃሚ እስከሆነላቸው ድረስ በዘርፉ ጥናት ካደረጉ ምሁራን ለመማር ያላቸው ተነሳሽነት የቱን ያህል እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል። እንዲያው ለነገሩ እንጂ እኛስ ብንሆን የብሔር ፖለቲካውን የቀዳነው ከቀድሞዋ ሶቪዬት መሪዎች ከአምባገነኑና ጨፍጫፊው ጆሴፍ ስታሊን (Joseph Stalin)ና ሌኒን (Vladimir Lenin) አይደል? የጨፍጫፊውን የስታሊንን እሳቤ ለመቅዳት ያላፈርን የሌሎች የውጭ ሀገራት ምሁራንን ሳይንሳዊ ምክርን ከመስማት ለምን እንታቀባለን? ከሁሉም በላይ እኛ በስታሊናዊ የብሔር ፖለቲካ አንቀፆች ተጣብቀን ቀርተን በተቃራኒው የእሳቤው ምንጭ የነበሩ እነራሺያ የስታሊንን እሳቤ በሀገር በታኝነት ፈርጀው አሽንቀጥረው ከጣሉ ዓመታት እንዳለፉ ገና መረጃው አልደረሰንም ማለት ነው? የብሔር ፖለቲካ የታሪክ ምዕራፉ እስከሚዘጋ የብልፅግና ፓርቲ ቢያንስ የእነ ሊፓርትና የእነ ዶናልድ ሆሮውዝን ምክሮችን በድኅረ ምርጫውም ቢሆን ከሀገራዊ አውድ ጋር አመሳክሮ ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኝነቱን ማሳየት ይጠበቅበታል… ከ“grand coalition” እስከ ተመጣጣኝ የውክልና ምርጫ ተግባራዊ እስከማድረግ ጭምር!

    ጌታሁን ሄራሞ (ኢ/ር)

    የብሔር ፖለቲካ እና መጪው የኢትዮጵያ ምርጫ

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) መግለጫ
    ኦሮሚያ ክልል ― የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ተከስቷል፤ አጥፊዎቹ ሕግ ፊት መቅረብ አለባቸው

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል ልዩ ልዩ አካባቢዎች በተከሰተ የፀጥታ መደፍረስ የተሳተፉ ሰዎችና ቡድኖች በሲቪል ሰዎች ላይ ያደረሷቸው ጥቃቶች በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ባህርያትን የሚያሟሉ መሆናቸውን በምርመራ ሪፖርቱ አመለከተ።

    ኢሰመኮ ከሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በነበሩ ሦስት ተከታታይ ቀናት በኦሮሚያ ክልል የተከሰተውን የፀጥታ መደፍረስና የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት የባለሙያ ቡድኖቹን ወደ 40 የክልሉ አካባቢዎች የላከ ሲሆን፥ የምርመራውን ግኝቶች ታኅሣሥ 23 ቀን 2013 ዓ.ም. ይፋ አድርጓል።

    በ59 ገጽ ሪፖርቱ እንደተመለከተው፥ በዚህ መጠነ ሰፊ ጥቃት የተሳተፉት ብዙ ቁጥር ያላቸው እና ከቦታ ቦታ በቡድን ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሰዎች ሲሆኑ፤ በጩቤ፣ በድንጋይ፣ በእሳት፣ በኤሌክትሪክ ገመድ፣ በዱላ፣ በዶማ፣ በገጀራ እና በመጥረቢያ ተጠቅመው ሰዎችን ደብድበዋል፤ የአካል ጉዳት አድርሰዋል፤ ፍጹም ግፍና ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ በማሰቃየት እና በማረድ ጭምር ሰዎችን ገድለዋል። በጥቃቶቹ የ123 ሰዎች ሕይወት አልፏል፤ 500 ሰዎች የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፤ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተፈናቅለዋል።

    በአብዛኛው በቡድን የተደራጁ ሰዎች ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሱ፣ በብሔርና በሀይማኖታቸው ተለይተው የተመረጡ ሲቪል ሰዎችን፣ ቢያንስ በ40 የተለያዩ ቦታዎች በተስፋፋና ለሦስት ቀናት በቆየ ሁከት ማጥቃታቸው፣ በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል እንደሚያደርገው የኮሚሽኑ ግኝቶች ያመላክታሉ።

    ምንም እንኳን የፀጥታ ኃይሉ በየቦታው የገጠመውን መጠነ ሰፊ የፀጥታ መደፍረስ ችግር እና የፀጥታ አባሎቹንም የሕይወት መስዋዕትነት በሚጠይቅ ሁኔታ በመሰማራታቸው ኃላፊነታቸው እጅግ ፈታኝ የነበረ መሆኑን መገንዘብ ቢቻልም፤ በተወሰኑ ቦታዎች የኃይል አጠቃቀም ተመጣጣኝነት ከፍተኛ ጥያቄ የሚያስነሳ መሆኑን ሪፖርቱ አክሎ ገልጿል። በአንዳንድ አካባቢዎች የፀጥታ ኃይሉ በወሰደው ያልተመጣጠነ እርምጃ፥ ሰልፍ ውስጥ ያልነበሩ፥ በመንገድ ወይም በቤታቸው በር ላይ የተገደሉ፣ ለማሸማገል ጣልቃ የገቡ የአገር ሽማግሌዎችን እና የአዕምሮ ህመምተኛ ጭምር እንዲሞቱ ምክንያት ሆኗል።

    የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ ‘በኢትዮጵያ የሚታየው የግፍና የጭካኔ ወንጀሎች መደጋገም፣ የችግሩን ስር መሠረት ለመፍታት የሚያስችል የተሟላ ብሔራዊ የግፍና ጭካኔ ወንጀል መከላከያ ስትራቴጂ ነድፎ በአፋጣኝ በሥራ ላይ ማዋል እንደሚገባ የሚያሳይ መሆኑን’ ገልጸዋል።

    ሙሉ ሪፖርቱ “መንግስት ያለ አይመስልም ነበር፡ የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በተከሰተው የፀጥታ መደፍረስ ምክንያት የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ምርመራ ሪፖርት” በሚል ርዕስ እዚህ ጋር በመጫን ያገኙታል።

    የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ተከስቷል

    Anonymous
    Inactive

    የብሔር ልዩነታችን ላይ መሠረት ባደረገ ፖለቲካዊ የአስተዳደር ሥርዓት የዜጎችን መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቶች ማረጋገጥ አይቻልም
    ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ
    ጋዜጣዊ መግለጫ

    በሀገራችን ኢትዮጵያ በንጹሃን ዜጎች ላይ እየደረሰ ያለ አሰቃቂ ግድያ፣ የአካል መጉደል፣ ለዘመናት ከኖሩበት ስፍራ መፈናቀል፣ እንዲሁም ያፈሩትን ሀብትና ጥሪት በአንድ ጀንበር አጥተው ለተረጅነት መዳረግ በየጊዜው የሚያጋጥም የተለመደ አሳዛኝ ክስተት ሆኗል።

    ይህንን በዜጎች እየደረሰ ያለውን አሰቃቂ ግድያ፣ የአካል መጉደል፣ መፈናቀልና  ሀብትና ንብረታቸውን ማጣት እንዲቆም ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄን ጨምሮ የተለያዩ ተቋማትና ግለሰቦች ደግመው ደጋግመው ቢያወግዙም በተቃራኒው ችግሩ ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሰ ይገኛል።

    እኛ ኢትዮጵያውያን እምነት፤ ባህል፣ ሥነ ልቦና፣ ጋብቻ፣ ሥራ፣ ጉርብትና ሌሎችም መስተጋብሮች ላንለያይ አስተሳስረውን ጠንካራ የአብሮነት ባህል የነበረን ሕዝቦች ነን። ይህ የአብሮነት መስተጋብር በብዙ አጋጣሚዎች ፈተና ላይ የወደቀ ቢሆንም እስከዛሬዋ ቀን ድረስ አብረን እንድንጓዝ አድርጎናል።

    መሠረታዊ የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶች ሳይሸራረፉ በማክበር የሁላችንም መኖሪያ የሆነችውን ሀገር አንድነት በማስጠበቅ፣ በመንግሥት አስተዳደር ሥርዓት ውስጥ ብዝኃነታችንን የሚያስተናግዱ የተለያዩ ፖሊሲዎችንና የሕግ ማእቀፎችን በማዘጋጀት ለጋራ ጥቅም በማዋል፣ እስከዛሬ የነበሩንን ጠንካራ ልምዶች ይበልጥ በማጠናከር ከድክመቶቻችን እና ስህተቶቻችን በመማር ብሎም በማሻሻል በአብሮነት ሁሉም አሸናፊና ተጠቃሚ የሚሆንበት ሥርዓት መዘርጋት ይቻላል ብለን እናምናለን።

    በእኛም ሀገር ይሁን በሌሎች ሀገራት ላይ ለሚከሰቱ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የተለያዩ ምክንያቶች ቢኖሩም በአሁኑ ጊዜ የቆየ አብሮ የመኖር እሴቶቻችንን በመፈታተን በሀገራችን እየተከሰቱ ለምንመለከታቸው ከፍተኛ የንጹሃን ህይወት መቀጠፍ፣ መፈናቀልና የንብረት ውድመት የመብት ጥሰቶች ዋነኛው መንስዔ የሀሰት ትርክት (false narrative) የወለደው ብሔር ተኮር የጥላቻ ፖለቲካ መሆኑ ጥርጥር የሌለው አሳዛኝ ሐቅ ነው።

    አሁንም መንግሥትም ሆነ ሌሎች የሚመለከታቸው የፖለቲካ ባለድርሻ አካላት በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት፣ ሀገራዊ ፍቅርና ቁርጠኝነት የዓለም አቀፍ ሕግጋትን መሠረት ባደረገ መልኩ፥ ያለንበትን 21ኛውን ክ/ዘመን በሚመጥን፣ በሰከነ ስሜት በቅንነት በመነጋገር፥ መሬት ላይ ያለውን ብዙኃኑን ምስኪን የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚመስል የፖለቲካ አስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት እስካልወሰኑ ድረስ በሁሉም የሀገራችን ወሰን ውስጥ ያሉ ዜጎቻችንን መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች በዘላቂነት ማስከበር ከቶውንም አይቻልም።

    ሰብዓዊ መብቶች ባልተከበሩበት፣ የሕግ የበላይነት ባልተረጋገጠበት፣ ሰላም ባልሰፈነበት ሁኔታ የሀገርን እድገትና ለውጥ እውን ለማድረግ ማሰብ እጅግ አዳጋች ነው።

    በአሁኑ ጊዜ እየተስተዋለ ያለው የጥላቻ፣ የመናናቅ፣ ልዩነትን መሠረት ያደረገ የብሔር ፖለቲካ፣ የጨቋኝ ተጨቋኝና የመጤ ሰፋሪ ትርክት ምንአልባትም ከእስካሁኑም ወደከፋ የግጭት አረንቋ ቢከተን ነው እንጂ የዜጎችን ሰው በመሆናቸው ብቻ እና በዜግነታቸው ማግኘት ያለባቸውን መብቶች ማስከበር ፈጽሞ አይቻልም። ችግሩን በፈጠርንበት አስተሳሰብ፣ ችግሩን በፈጠሩት የፓለቲካና የታሪክ ስሁት ትርክቶችን ሳናስተካከል መፍትሔ ማምጣትም ከባድ ነው።

    በሀገራችን በየትኛውም ዘመን እንደሕዝብ ተለይቶ የደላው ወይ ሌላውን የጨቆነ የለም። ይህንንም የተለያዩ የመንግሥት እና የፖለቲካ ድርጅቶች አመራሮች በተደጋጋሚ አስረግጠው የተናገሩት እውነታ ቢሆንም በተቃራኒው በተዛባ የታሪክ አረዳድ ሆን ብለውም ይሁን በስህተት የፖለቲካ አጀንዳ ባደረጉ አካላት ምክንያት የተነሳ ምንም የማያውቁ ንጹሀን ወገኖቻችን ደም እንደጎርፍ እየፈሰሰ ንብረታቸው እየወደመ ይገኛል። ይህም የሀገር ህልውናን አደጋ ላይ በመጣል ወደ ከፍተኛ ግጭት፣ ሞት፣ መፈናቀልና ስደት፣ ብሎም ለውጭ ኃይሎች ወረራና ጥቃት ሊያጋልጠን ይችላል።

    ከአባይ ግድብ ጋር በተገናኘም ሆነ በቀጠናችን ካለ የሽብርተኝነት እንቅስቃሴ ይህ የማይሆንበት ሁኔታ ይኖራል ብለን አንገምትም። ስለሆነም በቅርቡ በእርስ በርስ ግጭት ሕዝባቸውን ለስደትና ሞት ከዳረጉ ሀገራት በመማር ከምን ጊዜውም በላይ ሀገራዊ እና ሕዝባዊ አንድነታችንን ማጠናከር የሚገባን ጊዜ ላይ እንገኛለን።

    መንግሥት ሕግና ሥርዓት እያለ እንኳ በተገቢው መልኩ ማስቀረት ያልቻለውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት በጦርነትና በስደት መካከል ደግሞ ምን ያህል የከፋ ሊሆን እንደሚችልና ለውርደት እንደሚዳርገን ማስተዋል ያስፈልጋል።

    ይህ ፖለቲካው የወለደው የዜጎች ማንነትን መሠረት ያደረገ ጥቃት አይነቱን እየቀያየረ አንድ ጊዜ ሀይማኖትን ሌላም ጊዜ ብሔርን ወይንም አመለካከትንና አቋምን ሰበብ በማድረግ ይብዛም ይነስም ያልደረሰበትና ያልነካው የሕብረተሰብ ክፍል የለም ማለት ይቻላል። የችግሩ ምንጭም የቅርብ ሳይሆን አስርት አመታትን የቆየና አሁን እየባሰ የመጣ ነው።

    በሀገራችን ይህ ሁሉ ቢሆንም እንደ ሕዝብ የሚገድልና እንደሕዝብ የሚያፈናቅል አላየንም። ለዚህም ጥቃት በሚደርስባቸው አካባቢዎች ያሉ ነዋሪዎች ተጠቂዎችን ለማዳን፤ ለማሸሽ እና ለመደበቅ ያደረጉት ወገናዊና ሞራላዊ መልካም ሥራ ማስረጃ ነው።

    የፖለቲካው በቅንነት በመተማመን እና በአንድ ሀገራዊ ስሜት አለመመራት ሁሉንም የሀገሪቱ ዜጎች በየትኛውም ስፍራ በእኩል ዓይን በማየት ለሰብዓዊ እና የዜግነት መብቶቻቸውን በሚያከብር እና በሚያስከብር መልኩ ባለመመራቱ የተነሳ ችግሩን ከማቅለል ይልቅ በማወሳሰብ፡-

    • እጅግ ብዙ ንፁሐን ወገኖቻችን ሕፃናትን፡ ነፍሰጡሮችን፡ አቅመ ደካሞችን ጨምሮ ያለአግባብ በአሰቃቂ ሁኔታ ሕይወታቸው እንዲያልፍ ሆኗል፤
    • የሀገሪቱን የቀድሞ ኤታ ማዦር ሹም ጨምሮ የክልል ከፍተኛ አመራሮችን አጥተናል፤
    • ኢማሞችን እና ቀሳውስትን ጨምሮ የቤተ እምነት አገልጋዮችን ውድ ሕይወት አጥተናል፤
    • በዩንቨርሲቲዎቻችን ለትምህርት የሄዱ ብዙ ወጣቶችን ትርጉም በሌለው ምክንያት ተቀጥፈውብናል፤
    • ለትምህር የሄዱ ሴት ተማሪዎችና የጤና ረዳት ሰራተኞች ታግተው ለስቃይ ተዳርገዋል፤
    • በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች መሠረታዊ አቅርቦቶች ለምሳሌ እንደ ትራንስፖርት፤ መንገድ መዘጋት፤ ምግብ፤ ባንክ፤ ቴሌኮሚኒኬሽን አገልግሎት፣ መድሀኒት ወዘተ አቅርቦት በተደጋጋሚ ረዘም ላሉ ጊዜያት በመቆራረጥ ሰላማዊ ዜጎች ለከፍተኛ ችግር እንዲዳረጉ ሆኗል፤
    • ግምቱ ከፍተኛ የሆነ የሀገር እና የሕዝብ ንብረትና ሀብት እንዲወድም ሆኗል፤
    • ከዚህ ሁሉ በላይ በሰሜን እዝ የመከላከያ ሰራዊት ላይ የደረሰው ጥቃት ችግራችን የደረሰበትን የአሳሳቢነት ደረጃ ፍንትው አድርጎ የሚያሰይ ነው። ለዚህ ጥቃት ዋንኛ መንስኤ ከሀገርና ከሰው ይልቅ ብሔርን ያስቀደመ የማንነት ፖለቲካ ውጤት ሁኖ እናገኘዋለን።

    ይህ አሳዛኝ ሁኔታ ዳግም እንደማይፈጠርስ ምን ማስተማመኛ አለን? ከብሔር፤ ከሀይማኖትና ከፖለቲካ ነጻ የሆነውን የመከላከያ ሠራዊት ከውስጡ የወጡ የራሱ ወገኖች ያጠቁት የብሔር ፖለቲካው ውጤት ነው።

    ይህም በቶሎ በታላቅ መስዋዕትነት በቁጥጥር ባይውል ኖሮ የሀገራችንን ሉዓላዊነትን የሚገዳደርና ከዚህ የከፋ ቀውስ የሚያስከትል እንደነበረ መረዳት አያዳግትም።

    ችግሩ ላይ ብቻ ሳይሆን የችግሩ መንስዔ ላይ አተኩረን ለመሥራት እና ለማስተካከል ከዚህ በላይ ምን ምክንያትና ምቹ ጊዜ እየጠበቅን ነው? ምንስ እስኪፈጠር ነው ለውሳኔ የምንዘገየው?

    በየቀኑ ክቡር የሰው ነፍስ በአሰቃቂ ሁኔታ እየተቀጠፈ እያለ የሞተው ወይም ገዳይ ከኛ ነው ከነሱ ነው እያሉ የፖለቲካ ቁማር ከመጫወት ሁላችንንም እንደሀገር ከሰውነት ከፍታ ያወረደንን የጥላቻ ፖለቲካ በመመካከርና በማሻሻል የተሻለ ሥርዓትን ለትውልድ እናቆይ።

    ለፌደራልና ለክልል መንግሥታት አመራሮች፦

    ልዩነታችን ላይ መሠረት ባደረገ የፖለቲካ አስተዳደር ሥርዓት የዜጎችን መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች ማረጋገጥ አይቻልም።

    የፖለቲካ ባለድርሻ አካላት በከፍተኛ ታሪካዊ ሀገራዊ ስሜት በመሞላት በቁርጠኝነት የዓለም አቀፍ ሕግጋትን መሠረት ባደረገ፤ ያለንበትን 21ኛውን ክ/ዘመን በሚመጥን በሰከነ ስሜትና በቅንነት በመነጋገር፤ መሬት ላይ ያለውን በደምና በእምነት ተሳስሮ በሀዘንም በደስታ አብሮ የሚኖረውን ብዙኃኑን ምስኪን የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚመስል የፖለቲካ አስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት እስካልወሰናችሁ ድረስ በሁሉም የሀገራችን ወሰን ውስጥ ያሉ ዜጎቻችንን መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች በዘላቂነት ማስከበር ከቶውንም አትችሉም።

    ሰብዓዊ መብቶች፤ ሰላምና ሕግ ባልተከበረበት ሁኔታ ደግሞ እድገትንና ለውጥን ማሰብ እጅግ አዳጋች ነው። ይህ አካሔድ ደግሞ ለናንተም አይጠቅምም። ከእስካሁኑ ተግዳሮት በጊዜ ትምህር መውሰድ መልካም ነው።

    ችግሩን ለመፍታት እንደሚታሰበውም ቀላል እንዳልሆነ ብንረዳም እንደሚፈራውም ከባድ እንዳልሆነ እናምናለን።

    ከባድ ቢሆንም ደግሞ የእውነትን የአንድነትን የእኩልነትን ሰብዓዊ መብቶች የሚከበሩበትን፤ ለትውልድ ጥላቻን ሳይሆን ፍቅርን የምናወርስበትን መንገድን መርጠን የሚጠይቀውን መስዋዕትነት መክፈል የተሻለ ነው። ተቋማትም እስኪገነቡም ቢሆን የሰው ልጆች ወጥተው መግባት ዜጎች በህይወት የመኖር መብት አላቸው።

    መንግሥት የዜጎቹን ደህንነት ከማረጋገጥ የቀደመ ምን አይነት አጀንዳ ሊኖረው ፈጽሞ አይገባም።

    በመሆኑም፦

    1. መንግሥት ችግሩን ከምንጩ ለአንዴና ለመጨረሻ ለማድረቅ ቁርጠኛ ውሳኔ በመወሰን ጊዜ ባለመስጠት ውይይትና ምክክር ከላይ እስከታች እንዲጀመር እስከዚያውም በከፍተኛ ርብርብ ሕግ የማስከበር ሥራውን እንዲያስፈፅም እንጠይቃለን፤
    2. እስከዛሬም ድረስ በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች የተፈጠሩትን ዘግናኝ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ገለልተኛ ወገን እንዲያጣራ በማድረግ አጥፊዎችና ተባባሪዎች እንደ ተሳትፎዋቸው መጠን ከፍተኛውን ቅጣት እንዲያገኙ ተጎጂዎችም ተመጣጣኝ ካሳ እንዲያገኙ እንዲደረግ እንጠይቃለን፤
    3. እስከዛሬም ድረስ በተፈጠሩ ችግሮች ምክንያት ከሚኖሩበት አካባቢ የተፈናቀሉ ዜጎች ተገቢው ድጋፍ ተደርጎላቸው ወደነበሩበት እንዲመለሱና መደበኛ ኑሯቸውን እንዲጀምሩ በመንግሥት ያለተገደበ ድጋፍ እንዲደረግላቸው እንጠይቃለን።

    ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፦

    እስከዛሬ ድረስ በፖለቲካው ምክንያት በተፈጠሩ ችግሮች ብዙ ዋጋ እየከፈለ እና መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቱን እየተገፈፈ ያለው ንጹህ የሆነው እና አብሮ በሰላም እየኖረ ያለው በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች የሚኖረው ሕዝባችን እንደሆነ ይታወቃል። ያለንን አብሮነት አሁንም በማጠናከር እንደሕዝብም እንደግለሰብም አብረን በመቆም ለልጆቻችን የተሻለች ሀገር እናቆይ።

    ከጥላቻና ከብሔር ወይም ከማናቸውም የማንነት ልዩነት በመውጣት ለፖለቲካ ቁማር የማንመች እንሁን። ካለበለዚያ ከእስካሁኑ በባሰ የመጨረሻ ተጎጂዎች እኛው ነን።

    ምንም እንኳን የተለያየ አመለካከት ቢኖረንም በሰው ልጆች ሰብዓዊ መብቶች እና በሀገር አንድነት ጉዳይ የማንደራደር እንሁን። ሁላችንንም ስደተኞች ረሀብተኞችና ጠፊዎች ያደርገናል እንጂ ሀገር ለአንድ ብሔር፤ ለአንድ ክልል፤ለአንድ ቡድን ወይ ለአንድ ፓርቲ ብቻ ተለይታ አትፈርስም። ለተወሰነ ባለስልጣን ወይ አክቲቪስት ፈርሳ ለሌሎቻችን አትቆምም።

    ከሰሜን እስከደቡብ ከምሥራቅ እስከምእራብ አብረን ስንቆም ችግሮቻችን ከኛ በታች ይሆናሉ። ጥላቻና መጋደል በሕግም ፊት ወንጀል በሞራልም ነውር በእምነቶቻችንም ኃጥያት ነውና በሰከነ መንፈስ ሰብዓዊነትን በማስቀደም ሀገራችንን በማስከበር በብዝኃነት መኖር እንደለመድነው ቃልኪዳናችንን እናድስ።

    ውስጣዊ አንድነታችን በተዳከመ ቁጥር የውጭ ጠላቶቻችን ይደፍሩናል ያጠቁናል የዚያን ጊዜ ብሔር መርጠው አይወጉንም፤ ሁላችንንም ጨለማ ይወርሰናል። ምርጫው በእጃችን ነውና ሳይዘገይብን በይቅርታ መንፈስ እንነሳ።

    ሰው መሆናችን ትልቁ አንድነታችን መሆኑን እናስተውል።የነበሩንን እና ያሉንን መልካም አብሮ የመኖር እሴቶች በማጠናከር ችግሮቻችንን በእርጋታ እየፈታን እንጓዝ። የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች በማንም ይፈጠሩ፤ ማንም ተጎጂ ይሁን ሰው ነውና ወገን ነውና በአንድነት በማውገዝ በአንድነት ፍትህን በመጠየቅ ለሚለያዩን የማንመች እንሁን። ለልጆቻችን ፍቅርን ተስፋን መከባበርንና የሥራ ባህልንና ማውረስ አለብን።

    እናቶች፣ አባቶች፣ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ የሀይማኖት አባቶች፣ ምሁራን፣ የጥበብ ሰዎች፣ የሚድያ አካላት በአጠቃላይ ሁላችሁ ኢትዮጵያውያን በሀገር ውስጥም ይሁን በውጭ ያላችሁ በሙሉ ይህን ከባድ ጊዜ ተያይዘን እንድናልፈው የበኩላችንን አስተዋጽዖ እንድናደርግና የዜጎች ሰብዓዊ መብቶች ሳይሸራረፉ የሚከበሩበት፡ በሕግና በሥርዓት ብቻ ፍትህ የሚጠየቅበትና የሚገኝበት ማንኛውም አካል ከዜጎችና ከሀገር ደህንነት በታች የሚሆንበት መዋቅራዊ የሥርዓት መሻሻል እንዲመጣ በሰላማዊ መንገድ አብረን ጥሪያችንን እንድናሰማ ስንል በታላቅ አክብሮት እንማፀናችኋለን።

    ቅድሚያ ለሰብዓዊነት!
    ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ
    ታህሳስ 22 / 2013
    ​አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    የዜጎችን መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቶች ማረጋገጥ

    Anonymous
    Inactive

    በመተከል፣ በወለጋ፣ በሰገን አካባቢ እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት አጥብቀን እናወግዛለን!
    ከባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ እና የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ጥምረት (ባልደራስ-መኢአድ)  የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    በዓለም ላይ ማንነትን መሠረት አድርጎ የሚፈፀም ግፍ እየጠፋ ነው። ይሁን እንጂ በሀገራችን ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ዜጎች በማንነታቸው ምክንያት እየተገደሉ ነው፤ ግልፅ የሆነ የዘር ፍጅት ወንጀል እየተፈፀመ ነው። በታህሳስ 13 ቀን 2013 ዓ.ም ከ207 በላይ የአማራ ተወላጆች በመተከል አካባቢ ተገድለዋል። ባልደራስ-መኢአድ የተሰማውን መሪር ሐዘን ይገልፃል። ከዚህ በፊት በቤንሻንጉል ጉምዝ አካባቢ በተደጋጋሚ አንድን ዘር መሠረት ያደረገ ተመሳሳይ ግድያ መፈፀሙን ዓለም ያውቃል። የአማራ ተወላጆች በወለጋ፣ በጉራፈርዳ፣ በቤንሻንጉልና በሌሎች አካባቢዎች በማንነታቸው ብቻ ለዘር ፍጅት እየተዳረጉ ነው።

    በሀገራችን ኢትዮጵያ ሌላው የዘር ፍጅት የሚካሄድበት አካባቢ ደግሞ በሰገን ሕዝብ አካባቢ ነው። በደቡብ ኢትዮጵያ የጉማይዴ ነዋሪዎችና የኩስሜ ብሔረሰብ አባላት አካባቢ ወገኖቻችንን እያለቁ ነው። የኩስሜ ብሔረሰብ በቁጥሩ አነስተኛ ሲሆን 40‚000 ሺህ የሚሆኑ ዜጎች ያሉት ነው። የኩስሜ ዜጎች በአነሷቸው የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች፣ የንፁህ ውሃ አገልግሎት ጥያቄዎች ለእልቂት ተዳርገዋል።የኩስሜ ብሔረሰብ አስተዳደር ካሉት 9 አስተዳደር ቀጣናዎች መካከል በ7ቱ ቀጣናዎች ከፍተኛ የሰብዓዊና ቁሳዊ ውድመት የደረሰ ሲሆን በተለይ ቀጣና 1 ሙሉ በሙሉ ወድሞ የኩስሜ ብሔር አባላት ተሰደዋል። በተመሳሳይ በአሁን ሰዓት በምስራቅ ወለጋ ጌዳ ወረዳ፣ በምዕራብ ወለጋ ሳምቦ ወረዳ፣ በሆሮ-ጉድሩ ዞን እየተፈፀመ ያለው ታሪክ ይቅር የማይለው የግፍ ጭፍጨፋ ሊቆም አልቻም። ይህ ሁሉ ሲሆንና ማንነትን መሠረት ያደረገ ጥቃት ሲፈፀም ፌደራል መንግሥትም ሆነ የክልሉ መንግሥት ትኩረት አልሰጡትም። ዛሬ በኩስሜ ብሔር አካባቢ የትምህርት ተቋማት፣ ጤና ጥበቃ ተቋማት፣ ግብርና ወዘተ የመሳሰሉት ተቋማት ፈርሰዋል፤ ሕዝቡ በስደትና በስጋት ቁም ስቅሉን እያየ ነው። በዚሁ በሰገን ሕዝቦች አካባቢ የጉማይዴ ሕዝብ የማያባራ የዘር ፍጅት ወንጀል እየተፈፀመበት ነው። ዛሬ ጉማይዴ ውስጥ በሰላም ውሎ በሰላም መግባት የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። በ100 ሺህ የሚቆጠሩ የጉማይዴ ነዋሪዎች ተሰደዋል። ይህ ሕዝብ በማንነቱ ጥቃት ሲደርስበት የሚከላከልለት ከማጣቱም በላይ በተሰደደባቸው አካባቢዎች የዕለት ደራሽ እርዳታ ማግኘትም አልቻለም። መንግሥት ለዚህ ሕዝብ ሰላምና ፀጥታ መከታ መሆን አለመቻሉም ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን የጎዳው በጥቃቱ የመንግሥት ባለሥልጣናት ቀጥተኛ እጅ መኖሩ ነው። ይህ ሕዝብ የሚደርስበት ግፍ የማያባራው ጥቃቱ በመንግሥት የተደራጀ ኃይል እየተፈፀመ በመሆኑ ነው።

    በሀገራችን ውስጥ እየተፈፀመ ያለውን ማንነት ተኮር የሆነ የዘር ፍጅት ሕዝባችን ለእልቂት ከመዳረጉም በላይ በየጊዜው የሚያልቁ ወገኖቻችን አስከሬናቸው እንኳን በወጉ አያርፍም። በታህሳስ 13 ቀን 2013 ዓ.ም በመተከል የተጨፈጨፉት ከ207 በላይ ወገኖቻችንን መንግሥት በግሪደር አንድ ጉድጓድ ውስጥ እንዲቀበሩ አድርጓል። በዓለም አቀፍ የዘር ፍጅት ጥናት ውስጥ የዘር ፍጅት አንዱ መገለጫ በጅምላ መግደልና በጅምላ መቅበር ነው። በጅምላ መቅበር አንዱ የዘር ፍጅት የመደምደሚያው ወንጀል ነው። መንግሥት ይህንን ወንጀል በገሀድ ፈፅሞታል። ይህ ጉዳይ የሀገራችንን ባህል፣ ሀይማኖትና የቀብር ሥርዓት የጣሰ እና ያላገጠ ሲሆን ሥነ-ልቦናቸውንም ጎድቷል። በመሆኑም መንግሥት ሊጠየቅበት ይገባል። በአጠቃላይ በሀገራችን ውስጥ የዘር ፍጅት ወንጀል በየጊዜው እየተፈመ ሲሆን ፌደራል መንግሥትም ሆነ የክልል መንግሥት ይህንን ወንጀል ለመመከት አልቻሉም፤ ተጠያቂም ናቸው። በዓለም አቀፍ የዘር ፍጅት ወንጀል ክስ ወቅት በየትም ሀገር የዘር ፍጅት ሲፈፀም ተጠያቂው ራሱ መንግሥት ነው።

    በመሆኑም ለኢትዮጵያ ሕዝብና ለዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ የሚከተሉትን አስቸኳይ ጥሪዎች እናቀርባለን፡-

    1ኛ. የዘር ፍጅት ምልክቶች የሚታዩባቸው አካባቢዎች በፍጥነት ሠራዊታችን በቂ ኃይል እንዲያሰፍር፤
    2ኛ. መላው የሀገራችን ሕዝብ የዘር ፍጅትን በሰላማዊ መንገድ ብቻ ነቅቶና ተግቶ እንዲቃወም፤
    3ኛ. ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች ይህንን ክፉ ወንጀል በመቃወም በአንድነት እንዲቆም፤
    4ኛ. በሀገር ውስጥና በውጪ ያላችሁ የኢትዮጵያ ምሁራን በኢትዮጵያ ውስጥ እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት ወንጀል ወደ ሕግ እንድታቀርቡ፤
    5ኛ. በኢትዮጵያ ውስጥ የምትገኙ የሀገር ውስጥና የውጪ ሀገር ሰብዓዊ መብት ተቋማት በሙሉ ይህንን ወንጀል እንድትቃወሙ እና ወንጀል የፈፀሙት ኃይሎች ወደ ሕግ እንዲቀርቡ እንድትታገሉ፤
    6ኛ. የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትና ወዳጅ ሀገራት በሙሉ የዘር ፍጅት ወንጀልን እንድታወግዙና በመንግሥት ላይ ተገቢውን የዲፕሎማሲ ተፅዕኖ በማሳደር ወንጀሉ እንዲቆም እና ወንጀለኞች ለፍትህ እንዲቀርቡ እንድታደርጉ፤
    7ኛ. መላው የሀገራችን ሕዝብ በዘር፣ በሀይማኖት፣ በብሔር ሳንከፋፈል ከመቼውም ጊዜ በላይ በአንድነት ፀንተን እንድንቆምና የዘር ፍጅት እንድንከላከልና የተባበረችውን ኢትዮጵያችንን በጋራ እንድንገነባ በትህትና እንጠይቃለን።

    የተባበረችውን ኢትዮጵያን እንገነባለን! “አንዲት ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር”!!

    ታኅሣሥ 20 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ
    ባልደራስ-መኢአድ

    ባልደራስ-መኢአድ

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እና ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ የዘላቂ አጋርነት ስምምነት ተፈራረሙ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በባለአክሲዮን ብዛት ከቀዳሚ ባንኮች ተርታ የሚመደበው ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ እና በደጋፊ ቁጥር ቀዳሚ የሆነው የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ የዘላቂ አጋርነት ስምምነት ተፈራረሙ።

    ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ እና የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ በሁሉም ዘርፍ በጋራ ለመሥራት የሚያስችላቸውን የጋራ ስምምነት ተፈራርመው ወደሥራ መግባታቸውን ይፋ ያደረጉት ታኅሣሥ 17 ቀን 2013 ዓ.ም በሃያት ሪጀንሲ አዲስ አበባ ሆቴል በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ነው። ስምምነቱ ይፋ በተደረገበት ወቅት እንደተገለጸው፥ ባንኩም ሆነ ክለቡ የሚጋሩት ስም የሁሉም ኢትዮጲያዊ ከመሆኑ ባሻገር ሕዝባዊ መሠረት ያላቸው መሆናቸው አንድ የሚያደርጋቸው የጋራ መለያቸው ነው ተብሏል።

    ስምምነቱ የተፈረመው በቡና ኢንተርናሽናል ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሙሉጌታ አለማየሁ እና በኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ሥራ አስኪያጅ አቶ ገዛኸኝ ወልዴ ሲሆን፥ በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የባንኩና የክለቡ የሥራ አመራር አባላት ተገኝተዋል። በስምምነቱ መሠረትም ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ ለኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ የአምስት ሚሊዮን ብር የአንድ ዓመት ስፖንሰርሺፕ ክፍያ የሚከፍል ሲሆን ስምምንቱም በየዓመቱ የሚታደስ ይሆናል።

    በስምምነቱ መሠረት የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ የባንኩን አርማ በተጫዋቾች ቲሸርትና ላይ በማሳየት ባንኩን ያስተዋውቃል። በተጨማሪም በሜዳውም ይሁን ያለሜዳው ጨዋታ በሚኖረው ወቅት የባንኩ ቢልቦርድ ማስታወቂያ በጨዋታው ሜዳ አካባቢ እንዲቀመጥ ያደርጋል። ክለቡ በተቻለው መጠን የባንኩን ብራንድ እና አገልግሎቶች እንዲያስተዋውቅም በስምምነቱ ተካትቷል።

    ስምምነቱ ከዚህ በተጨማሪ የስፖርት ክለቡ የባንክ ሂሳቡን በባንኩ እንዲከፍት ከማድረግ ጀምሮ የክለቡ አባላትና ደጋፊዎች የባንኩ ደንበኛ እንዲሆኑ ማድረግን የመሳሰሉ የባንክ አገልግሎቶችን ከባንኩ እንዲያገኙ የሚያደርግ ነው ተብሏል።

    እንደስምምነቱ ቡና ባንክ በበኩሉ የስፖርት ክለቡ ደጋፊዎች ማኅበር ወርሃዊ የአባልነት መዋጮአቸውን በዘመናዊ የቴክኖሎጂ አሠራር በመታገዝ በባንኩ በኩል እንዲከፍሉ የሚያስችላቸው አሠራር ይዘረጋል፤ በተለያየ የሀገሪቱ ክፍል ለሚገኙ የክለቡ አባላትም የባንክ አገልግሎት እገዛ እንደሚያደርግ ተገልጿል።

    ቡና ባንክ እና የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እንደስማቸው አንድ መሆን የጋራ እድገት ለማስመዝገብ የሚያስችሉ ሌሎች በርካታ ሥራዎችንም በጥምረት ለመሥራት መስማማታቸውን ነው በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ያበሰሩት።

    ከተመሠረተ 11 ዓመታት የሆነውና ከ13 ሺህ በላይ ባለአክሲዮኖች ያሉት ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ የእግር ኳስ ስፖርቱን በመደገፍና በዓለም አደባባይ አርማውን በማስተዋወቅ ከቀዳሚዎቹ ተርታ የተሰለፈ ባንክ ሆኗል። ባንኩ በ2012 የሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት ከ582 ሚሊዮን ብር በላይ ማትረፉንም በዚያው ሳምንት አሳውቋል። የባንኩ ሀብት በሒሳብ ዓመቱ መጨረሻ ላይ የ4.4 ቢሊዮን ብር ዕድገት ያሳየ ሲሆን፣ ጠቅላላ ሀብቱም ወደ 18.9 ቢሊዮን ብር አድጓል፡፡ ከባንኩ ጠቅላላ ሀብት ውስጥ የተጣራ ብድር 60.9 በመቶውን በመሸፈን ከፍተኛውን ድርሻ ይዟል ሲል ባንኩ የ2012 የሒሳብ ዓመት የሥራ አፈጻጸሙን ይፋ ባደረገበት ጠቅላላ ጉባዔ ላይ አሳውቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ

    ኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እና ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ

    Anonymous
    Inactive

    ኦህዴድ/ ብልጽግና አዲስ አበባን የኦሮሞ ንብረት ለማድረግ የጀመረውን ዘመቻ ያቁም!
    ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ

    ኦህዴድ/ ብልጽግና ቤተ-መንግሥት ከገባ ጀምሮ የመላ ኢትዮጵያውያን ብሎም የአፍሪካ መዲና የሆነችውን አዲስ አበባን በኦሮማዊነት መንፈስ ለመቆጣጠር እንቅስቃሴዎችን እያደረገ ይገኛል።

    ከሰሞኑ ከተማዋን የኦሮሞ ብቻ መዲና ለማድረግ እና ኦሮማዊ ሥነ-ልቦናን ለማላበስ ኦሕዴድ/ ብልጽግና የሕንፃዎች ግንባታ ዘመቻን ጀምሯል። የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በ1.8 ቢሊዮን ብር ወጭ የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሕንፃን፣ በ1.5 ቢሊዮን ብር ወጭ የኦሮሚያ ብዙኃን መገናኛ ድርጅት ሕንፃን፣ በአንድ ቢሊዮን ብር የኦሮሞ ታጋዮች ፋውንዴሽን ሕንፃን እንዲሁም በሰባት መቶ ሚሊዮን ብር ወጭ የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ሕንፃን በአዲስ አበባ ለመገንባት ሥራዎች ጀምሯል። ይህ እንቅስቃሴ ህወሓት ሲያደርግ እንደ ነበርው የሕዝብ ሀብት እየተዘረፈ ለነገድ የፖለቲካ ድርጅቶች እና ለሚመሯቸው የፖለቲካ ኤሊቶች ጥቅም ማስገኛ እንደሚሆን ሳይታለም የተፈታ እውነታ ነው። በሕገ-መንግሥቱ የኦሮሚያ ክልል ዋና ከተማ አዲስ አበባ እንደሆነች ባልተፈቀደበት ሁኔታ ይህ የተወሰደው እርምጃ አዲስ አበባን በኦሮሞ ሥነ-ልቦና ለመሥራት በሚል ሽፋን የኦሮሞ የነገድ ፓለቲካ ኤሊቶች ጥቅም ማጋበሻ እንዲሆኑ የታለሙ መሆናቸውን ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ያምናል። ይህም በ16 እና በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመናት ተቋርጦ የነበረውን የገዳ ሥርዓት ወረራ ለማስቀጠል እየተደረገ ያለ እንቅስቃሴም አካል ነው።

    አቶ ሽመልስ አብዲሳ እንዳሉት ይህ ወረራ አዲስ አበባን ሙሉ በሙሉ ለመዋጥ ወይም ለማጥፋት ያለመ ነው። ‹በረራ› በመባል ትታወቅ የነበረችው ጥንታዊቷ አዲስ አበባ ዳግማዊ ምኒልክ እንደ ገና የዛሬዋን አዲስ አበባ እስከቆረቆሩበት ጊዜ ድረስ ፈርሳ የቆየችው በገዳ ወረራ እንደሆነ ታሪክ ያስረዳል። በ16ኛው እና በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመናት በተካሄደው የገዳ ሥርዓት ወረራ ከ28 በላይ ነባር የኢትዮጵያ ነገዶች መጥፋታቸው በታሪክ የተመዘገበ ነው።

    በመሆኑም በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ከመላ ኢትዮጵያ የተሰበሰቡ ነዋሪዎች ከሚገብሩት ግብር ለክልሎች ፈሰስ ከሚደረገው ድጎማ የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት ለነገድ የፖለቲካ ማራመጃነት እና ለግል ጥቅም ማካበቻ በማን አለብኝነት የሚያባክኑት የሀገር ሀብት ተጠያቂ የሚሆኑበት ሥርዓት እንዲፈጠር መላው የከተማዋ ነዋሪ በሰላማዊ ትግል አድሏዊ ከሆነ የኪራይ ሰብሳቢ አካሄድ እንቅስቃሴያቸው እንዲታቀቡ ባልደራስ በአፅንኦት ያሳስባል።

    ታኅሣሥ 14 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ
    ድል ለዲሞክራሲ!
    ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ

    ኦህዴድ ብልጽግና አዲስ አበባን የኦሮሞ ንብረት ለማድረግ የጀመረውን ዘመቻ ያቁም!

    Anonymous
    Inactive

    በመተከል በአማራ ሕዝብ ላይ የቀጠለውን የዘር ፍጅት አስመልክቶ ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ

    የአማራ ሕዝብ እና ሀገራችን ከገጠሟቸው ፈተናዎች ለመውጣት ዘላቂው መፍትሄ ሁሉንም ሕዝብ እና አካላት ባለቤት የሚያደርግ፣ ሀገራዊ መከራንም በጋራ መቀልበስ የሚያስችል ሥርዓትና ስሪት ማቆም መሆኑን ሳናሰልስ ተናግረናል፤ አስገንዝበናል፤ ወትውተናል።

    የፍትህና እኩልነት ሥርዓት ስለማቆም ሳያሰልሱ መወትወትና መታገሉ በመሠረታዊነት አንዳችም ስህተት የሌለበት ቢሆንም ሀገራዊ ፕሮጀክቱ አማራውን ከምድረ ገጽ ለማጥፋት ከሚሠሩ የጥላቻ ኃይሎች ጋር በመሆን ማሳካት እንደማይቻል ግለፅ እየሆነ የመጣ እውነታ ሆኗል።

    ሁሉን አቀፍ በጎ ውጥኖች በተግባር እስኪተረጎሙና የጥፋት ኃይሎችም ልቦና ገዝተው በባለቤትነት ስሜት ጭምር የየራሳቸውን አዎንታዊ አበርክቶ መወጣት ሊጀምሩ ይችላሉ ከሚለው እሳቤ በፊት የሕዝባችን ህልውና የሚቀድም መሆኑን በመረዳት አሳዳጅና ገዳዮቻችን ክላሽ፣ ሜንጫና ቀስታቸውን ጥለው እስኪመጡ ድረስ ለሽግግር የሚሆን የተቀናጀ እርምጃ እንዲወሰድ ዛሬም ለማሳሰብ እንወዳለን።

    የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የመላው አማራ ሕዝብ ወኪል መሆኑን ማረጋገጥ ያለበት ወቅት መሆኑን በመረዳት በትሕነግ ላይ የወሰደውን ዓይነት ህልውናን የማስከበር ታሪካዊ ቁርጥ ውሳኔ በማሳለፍ በመተከል እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት ለማስቆም ተግባራዊ ምላሽ ሊሰጥ ይገባል። በዚህ ረገድ አብን ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ለማድረግ ያለንን ቁርጠኝነትም መግለጽ እንወዳለን።

    የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል መንግሥት በዜጎቻችን ላይ ለሚፈፀመው ጭፍጨፋ ቀዳሚ ተጠያቂ ከመሆኑም በላይ በጭፍጨፋው የተሳተፉ ከክልል እስከ ቀበሌ የሚገኙ አመራሮችን በቸልታ በማለፍ የጥቃቱ ተባባሪ ሆኖ ይገኛል።

    የፌደራል መንግሥትም ኦሮሚያንና ቤንሻንጉል ጉሙዝን ጨምሮ በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች በአማራ ሕዝብ ላይ የሚፈፀመውን ሰፊ የዘር ማጥፋት ወንጀል ማስቆም ካለመቻሉም በላይ ወንጀሉን በስሙ ባለመጥራት በዜጎቻችን ላይ ለሚፈፀመው ጅምላ ፍጅት ተባባሪ በመሆኑ ከተጠያቂነት እያመልጥም።

    በአማራ ሕዝብ ላይ እየተፈፀመ ያለውን የማያባራ የዘር ፍጅት መላው ኢትዮጵያውያን እንድታወግዙና የአማራ ሕዝብ ህልውናውን ለማስቀጠል ከሚያደርገው ትግል ጎን እንድትቆሙም ንቅናቄያችን በአክብሮት ይጠይቃል። ንቅናቄያችን በመተከል በአማራ ወገኖቻችን ላይ የሚፈፀመውን የማያባራ የዘር ፍጅት በጽኑ እያወገዘ፤ ለዘር ፍጅት ሰለባ ቤተሰቦችና ለመላው የአማራ ሕዝብም መጽናናትን ይመኛል።

    አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፥ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ!

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)
    ታኅሣሥ 15 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ፣ ሸዋ፥ ኢትዮጵያ!

    በመተከል በአማራ ሕዝብ ላይ የቀጠለው የዘር ፍጅት

    Anonymous
    Inactive

    አሰቃቂ ጭፍጨፋ በመተከል ዞን ― የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) መግለጫ 

    ቤኒሻንጉል ጉሙዝ፡ የሰዎች ደኅንነት ማረጋገጥ ቀዳሚው የመንግሥት ግዴታ ነው።

    ታኅሣሥ 13 ቀን 2013 ዓ.ም. በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፥ መተከል ዞን፥ ቡለን ወረዳ፥ በኩጂ ቀበሌ ከለሊቱ 10፡00 ሰዓት ላይ የታጠቁ ኃይሎች በእንቅልፍ ላይ በነበሩ ነዋሪዎች ላይ በለኮሱት እሳት እና በተኩስ ከ100 በላይ ሰዎች መገደላቸው በክልሉ ያለው የሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ በከፍተኛ ሁኔታ እየተዳከመ መሄዱን እንደሚያሳይ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ/ኮሚሽኑ) ገለጸ።

    ኢሰመኮ የጥቃቱን ሂደት በተመለከተ ታኅሣሥ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. ከሚመለከታቸው አካላት እና ከተጎጂዎች ጋር በመነጋገር ሲከታተልና ሲያጣራ ቆይቷል። በኩጂ ቀበሌ ከወረዳው መቀመጫ ከሆነችው ቡለን ከተማ 90 ኪ.ሜ. ርቃ የምትገኝ ሲሆን የሺናሻ፣ የኦሮሞና የአማራ ተወላጆች ይኖሩባታል። ለቀበሌው የተመደበ የፖሊስ ወይም የፀጥታ ኃይል አለመኖሩን ኮሚሽኑ በክትትሉ መሠረት ተረድቷል።

    ኮሚሽኑ ሁኔታውን እስካጣራበት ጊዜ ድረስ በቡለን ሆስፒታል 36 ተጎጂዎች እርዳታ እየተደረገላቸው ሲሆን፥ አብዛኞዎቹ በጥይት ሌሎቹ በቀስት የቆሰሉ መሆናቸውን ኢሰመኮ በምልከታ አረጋግጧል። በተጨማሪም ሰዎች ጥቃት የደረሰባቸውን ሁኔታ የሚያሳዩና የሚረብሹ የፎቶግራፍ ማስረጃዎች ለኮሚሽኑ ደርሰውታል። በሰው ሕይወት እና በአካል ላይ ከደረሰው ጉዳት በተጨማሪ የደረሱ ሰብሎችና የተሰበሰቡ ማሳዎች በእሳት ጋይተዋል። ቢያንስ 18 ያክል ነዶዎች ሲቃጠሉ ማየታቸውን አንድ ተጎጂ አስረድተዋል።

    በጨላንቆ እና ዶሼ ቀበሌዎች ቤቶች እየተቃጠሉ እንደሆነ ከአካባቢው ለኮሚሽኑ የተላኩ መረጃዎች ያመለክታሉ። በድባጤ ወረዳ ዶንበን ቀበሌ ስጋት የገባቸው ነዋሪዎች ከታኅሣሥ 14 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ቀዬአቸውን ጥለው እየተሰደዱ እንደሆነም ኮሚሽኑ ተረድቷል።

    አካባቢውን በቅርበት እንዲጠብቅ የተመደበው ብሔራዊ የመከላከያ ሠራዊት ታኅሣሥ 13 ቀን 2013 ዓ.ም. ለማረጋጋት ተግባር ወደቦታው ተልከው የነበሩ አንድ የፌዴራል እና ሁለት የክልሉ አመራሮችን ለማጀብ በሚል አካባቢውን ለቅቆ መሄዱ ታውቋል። ጥቃቱ የጀመረው ይህንኑ ተከትሎ እንደሆነና ሌሊቱን የጀመረው ጥቃት እስከ ቀኑ አጋማሽ ድረስ መዝለቁንም ለማወቅ ተችሏል። ኮሚሽኑ ያነጋገራቸው ተጎጂዎች እንደሚሉት በጥቃቱ ከሞቱ ሰዎች መካከል አብዛኛው የሺናሻ ተወላጆች ናቸው።

    ከዚህ ቀደም በነበሩ ጥቃቶች ፈጻሚዎቹ ከ”ጫካ” የሚመጡ ሰዎች የነበሩ ቢሆንም፥ በዚህኛው ጥቃት “በስምና በመልክ የሚያውቋቸው” የበኩጂ ቀበሌ ነዋሪዎች ጭምር መሳተፋቸውን ከጥቃቱ የተረፉ ተጎጂዎች ገልጸዋል።

    ኢሰመኮ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ የሚከሰቱ ጥቃቶችን ተደጋጋሚነትና የክልሉን ሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ ሁኔታ አስመልክቶ የፌዴራሉንና የክልሉን መንግሥታት የተጠናከረ ትብብርና ከፍተኛ ትኩረት እንደሚሻ ሲያሳስብ መቆየቱ ይታወሳል፤ ይሁንና ጥቃቶቹ በመልክ እና በስፋት እየተባባሱ መጥተዋል።

    ስለሆነም፣ በጥቃቱ ጉዳት ለደረሰባቸው እና ለተፈናቀሉ ሰዎች የሕክምና እና ሰብዓዊ እርዳታ እንዲቀርብ፣ እንዲሁም ተገቢው ማጣራትና ጥቃቱን ባለመከላከልም ሆነ በሌላ መልኩ ጥቃቱን የፈጸሙና ያባባሱ ሰዎችን ሕግ ፊት የማቅረቡ ሂደት ከወዲሁ እንዲጀመር ኮሚሽኑ ያሳስባል። በአካባቢው የሚገኘውን የፀጥታ ኃይልና መዋቅር የሰዎችን ደኅንነት ሙሉ በሙሉ ለማረጋገጥ በሚያስችል መልኩ በከፍተኛ ደረጃ በአፋጣኝ እንዲጠናከር ኢሰመኮ ጥሪ ያቀርባል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)
    ታኅሣሥ 14 ቀን 2013 ዓ.ም.

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቡታጅራ ከተማ ወስጥ ያስገነባውን የባንኩ ዲስትሪክት ህንፃ ሳይጠናቀቅ በመተው
    ወደ ሌላ አካባቢ እንዲዛወር መደረጉ አግባብነት የሌለው ነው ተባለ

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የጉራጌ ማኅበረሰብን ነዋሪዎችን እና አጎራባች ከተሞችን ታሳቢ በማድረግ በቡታጅራ ከተማ አስተዳደር የባንኩን ዲስትሪክት ለመክፈት ከውሳኔ ደረሶ ግንባታውን ለማጠናቀቅ ከጫፍ ሲደርስ ዲስትሪክቱን ወደሌላ አካባቢ ማዛወሩ ተገቢ አለመሆኑ ተገለፀ።

    የጉራጌ ማኅበረሰብ ከጥንት ጀምሮ እሴቱ የሆነውን የቁጠባ ባህል ፍላጎት እና የልማት ተነሳሽነት ተከትሎ የቡታጅራ ከተማ ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በከተማዋ መሀከል ላይ ዋናውን መስመር ተከትሎ ባንኩ ቅርንጫፍ እንዲከፍት ቦታውን አመቻችቶ ባቀረበው መሠረት ቅርንጫፉን ከፍቶ አሁን አራት አድርሷል።

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቡታጅራ ከተማ ቅርንጫፍ ባለበት ስፍራ ለጉራጌ ማኅበረሰብ በዞኑ ለሚኖሩ ማኅበረሰቦች እና ለአጎራባች ከተሞች የሚያገለግል የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዲስትሪክት ለመክፈት ከውሳኔ በመድረስ፥ ህንፃም ገንብቶ ለማጠናቀቅ ከጫፍ ባደረሰበት ሰዓት ማዕከሉን ወደ ሌላ አካባቢ ማዛወሩ ተገቢ አለመሆኑን በመግለጽ ማኅበረሰቡ ቅሬታውን እያቀረበ ይገኛል።

    የባንኩ ማኔጅመንት ባስቀመጣቸው ቅድመ ሁኔታዎች መሠረት ለጉራጌ እና ለአካባቢው ከተሞች በማዕከልነት የባንኩ ዲስትሪክት አስፈላጊ እንደሆነ ታምኖበት ውሳኔ በማሳለፍ በቡታጅራ ከተማ አስተዳደር የጀመረውን የዲስትሪክት መቀመጫነት ወደ ሌላ አካባቢ ማዛወሩ የአካባቢውን ማኅበረሰብ የማይመጥን ውሳኔ መሆኑን ማኅበረሰቡ ያነሳል።

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የአመራር (ማኔጅመንት) አባላትም የመጀመሪያ ውሳኔያቸውን በማጽናት በቡታጅራ ከተማ አስተዳደር የባንኩን ዲስትሪክት በማስቀጠል ባለበት የማያጸኑ ከሆነ የዞኑን ማኅበረሰብ በባንኩ ላይ ያለውን ደንበኝነት የሚሸረሽርና ደንበኝነታቸው ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንደሚያሳድርም ከግምት ውስጥ ያላስገባ ውሳኔ መሆኑን ማኅበረሰቡ ይገልፃል።

    ባንኩ የራሱ የሆነ አሠራር አለው በማንኛውም ዓይነት በፖለቲካም ሆነ በኢኮኖሚ ጣልቃ ገብነት ውሳኔውን በመሻር ዲስትሪክቱን ማዛወሩ ቅቡልነት የሌለው አሠራር መሆኑን በማስገንዘብ፤ ባንኩ በመጀመሪያው (በቀደመው) ወሳኔው ፀንቶ በተጀመረበት ስፍራ ማስቀጠል እንደሚገባም በመግለጽ ማኅበረሰቡ ያሳስባል።

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፤ የጉራጌና የአካባቢዋ ማኅበረሰብም የኢትዮጵያ አንድ አካል ነው፤ ልማትም ይሻል፤ የዚህን ማኅበረሰብ ስሜት ከግምት ውስጥ ባለማስገባት የተጀመረና ለማጠናቀቅ ከጫፍ የደረሰን ልማት ማዛወር በምንም ዓይነት አስተሳሰብም ሆነ አመለካከት ተቀባይነት የሌለው ውሳኔ መሆኑ ሊታወቅ ይገባል ሲል ማኅበረሰቡ ይገልጻል።

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በቡታጅራ ከተማ

    Anonymous
    Inactive

    በሀገር ላይ የፈጸሙ ወንጀሎች ስለሚያስከትሉት ቅጣት የወንጀል ሕግ ምን ይላል?

    “የሀገር መከላከያ ኃይልን መጉዳት ከአምስት እስከ 25 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት፣ እንዲሁም ነገሩ እጅግ ከባድ በሆነ ጊዜ
    በእድሜ ልክ ጽኑ እስራት ወይም በሞት ያስቀጣል።”    

    መንግሥት የሕዝቦቹን ሰላም እና ደህንነት የመጠበቅ እንዲሁም ሕግን የማስከበር ኃላፊነት የሚወጣ ቢሆኑም በተለያዩ ሁኔታዎች በሀገር ላይ ወንጀሎች ሊፈጸሙ ይችላሉ። የእነዚህ ወንጀሎች መፈፀም በአጠቃላይ በማኅበረሰቡ ሰላም፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ህይወት ላይ ጉዳት ማስከተሉ አይቀሬ በመሆኑም መንግሥት የሀገርን ደህንነት አደጋ ላይ የሚጥሉ ወንጀሎች እንዳይፈጸሙ አስቀድሞ የመከላከል፤ ተፈጽመው ሲገኙም ሕግን የማስከበር ኃላፊነት አለበት። በሀገር ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች በኢ.ፌ.ዲ.ሪ የወንጀል ሕግ ሦስተኛ መፅሐፍ በመንግሥት፣ በሀገርና በዓለም አቀፍ ጥቅሞች ላይ የሚደረጉ ወንጀሎች በሚል ስር ተካቶ ይገኛል።

    በዚህ አጭር የንቃተ ሕግ ፅሁፍ በሀገር ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች እና የሚያስከትሉትን የወንጀል ቅጣት እንዳስሳለን። በሕገ-መንግሥትና በሕገ-መንግሥት ሥርዓት ላይ የሚደረጉ ወንጀሎች በ1996 ዓ.ም በወጣው የወንጀል ሕግ አንቀፅ 238 ስር እንደተደነገገው ማንም ሰው በኃይል፣ በዛቻ፣ በአድማ ወይም ሕገ-ወጥ በሆነ ማናቸውም መንገድ የፌደራሉን ወይም የክልልን ሕገ-መንግሥት ያፈረሰ፣ የለወጠ ወይም ያገደ እንደሆነ ወይም በፌደራሉ ወይም በክልል ሕገ-መንግሥት የተቋቋመውን ሥርዓት ያፈረሰ ወይም የለወጠ እንደሆነ ከሦስት ዓመት እስከ 25 ዓመት ለመድረስ በሚችል ጽኑ እስርት ይቀጣል። ወንጀሉ ሲፈፀም በሕዝብ ደህንነት ወይም ኑሮ ላይ ከፍተኛ ቀውስ ደርሶ እንደሆነ አድራጊው በዕድሜ ልክ እስራት ወይም በሞት ይቀጣል።

    የሕገ-መንግሥታዊ ሥልጣንን ተግባራዊነት ማሰናከል ሌላው በወንጀል ሕጉ የወንጀል ድርጊት ተብሎ የተፈረጀ ተግባር ሲሆን ማንም ሰው በኃይል ሥራ፣ በዛቻ፣ ወይም ሕገ-ወጥ በሆነ ሌላ ማናቸውም መንገድ በፌደራል ወይም በክልል ሕገ-መንግሥት ስልጣን የተሰጠውን አካል ወይም ባለስልጣን ተግባሩን እንዳያከናውን ያደናቀፈ፣ የከለከለ ወይም አስገድዶ ውሳኔ እንዲሰጥ ያደረገ እንደሆነ ከ15 ዓመት በማይበልጥ ጽኑ እስራት ይቀጣል።

    የጦር መሣሪያ ይዞ በማመፅ፣  ወይም የእርስ በርስ ጦርነት በማስነሳት በመንግሥት ላይ የሚደረግ ወንጀል (የወንጀል ሕግ አንቀፅ 240) — ማንም ሰው አስቦ በሕገ-መንግሥት በተቋቋሙት አካላት  ወይም ባለስልጣናት ላይ ሕዝብ፣ ወታደሮች ወይም ሽፍቶች የትጥቅ አመፅ እንዲያነሱ ያደራጀ ወይም የመራ እንደሆነ ወይም ዜጎችን ወይም በሀገር ነዋሪ የሆኑትን በማስታጠቅ ወይም አንዱ ወገን በሌላው ላይ የጦር መሣሪያ እንዲያነሳ በማነሳሳት የእርስ በእርስ ጦርነት እንዲነሳ ያደረገ እንደሆነ ከ10 ዓመት እስከ 25 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ይቀጣል።እንዲሁም ድርጊቱ በሕዝብ ደህንነት ወይም ኑሮ ላይ ከፍተኛ ቀውስ ይስከተለ እንደሆነ በእድሜ ልክ ጽኑ እስራት ወይም በሞት ይቀጣል።

    የሀገሪቱን የፖለቲካ የግዛት አንድነት በመንካት የሚደረግ ወንጀል (የወንጀል ሕግ አንቀጽ 241) — ማንም ሰው በኃይል ወይም በሌላ ማናቸውም ሕገ-መንግሥትን የሚፃረር መንገድ፣ በቀጥታ ወይም በእጅ አዙር፣ የሀገሪቱን ሕዝቦች አንድነት እንዲፈርስ ወይም ፌዴሬሽኑ እንዲከፋፈል ወይም ከፌዴሬሽኑ ግዛት ከፊሉ እንዲገነጠል የሚያደርግ ተግባር የፈፀመ እንደሆነ ከ10 ዓመት እስከ 20 ዓመት ለመድረስ በሚችል ጽኑ እስራት ወይም ነገሩ ከባድ በሆነ ጊዜ በእድሜ ልክ እስራት ወይ በሞት ይቀጣል።

    የሀገሪቱን መንግሥት እንዲሁም የሀገሪቱን ምልክቶችና በመንግሥት የታወቁ ሌሎች ምልክቶችን መድፈር — ማንም ሰው በንግግር ወይም በአድራጎት ወይም በማናቸውም ሌላ አኳኋን በአደባባይ የሀገሪቱን መንግሥት ያዋረደ፣ የሰደበ፣ ስሙን ያጠፋ ወይም በሀሰት የወነጀለ እንደሆነ ከሦስት ወር በማያንስ ቀላል እስራት ወይም ከ500 ብር በማያንስ መቀጮ ይቀጣል (የወንጀል ሕግ አንቀፅ 244/1)። እንዲሁም በተንኮል፣ በንቀት ወይም ይህንን በመሳሰለ በማናቸውም ሀሳብ በግልጽ የታወቀውን አንድ የሀገር ምልክት፥ ማለትም የፌደራላዊት ኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማን ወይም አርማን እንዲሁም የክልላዊ መንግሥት ሰንደቅ ዓላማን ወይም አርማን በአደባባይ የቀደደ፣ ያቃጠለ፣ ያጠፋ፣ ያበላሸ፣ የሰደበ ወይም በማናቸውም ሌላ አኳኋን ያዋረደ እንደሆነ ከሦስት ወር በማያንስ ቀላል እስራት ወይም በመቀጮ ይቀጣል (የወንጀል ሕግ አንቀፅ 244/2)። በሀገር ነፃነት ላይ የሚደረግ ወንጀል ማንም ሰው፡-

    • የሀገሪቱን ነፃነት አደጋ ላይ ለመጣል ወይም ሀገሪቱ ሉአላዊቷን እንድታጣ፣
    • የሀገሪቱን ነፃነት አደጋ ላይ ለመጣል የውጪ መንግሥት ጣልቃ እንዲገባ በመገፋፋት፣ ወይም
    • የውጪ መንግሥት የጠላትነት ድርጊት በሀገሪቱ ላይ እንዲፈጽም ወይም ከውጪ ሀገር መንግሥት ጋር ጦርነት እንድትዋጋ ወይም የጠላትነት ድርጊት እንድትፈጽም፣ በጠላትነት እንድትከበብ ወይም እንድትያዝ በማሰብ ማናቸውም ድርጊት ያደረገ እንደሆነ ከአምስት ዓመት እስከ 25 ዓመት ለመድረስ በሚችል ጽኑ እስራት፤ ወይም ነገሩ ከባድ ሲሆን በእድሜ ልክ ጽኑ እስራት ወይም በሞት ይቀጣል (የወንጀል ሕግ 246)።

    የሀገር መከላከያ ኃይልን መጉዳት (የወንጀል ሕግ አንቀፅ 247/ሀ/ለ/እና መ) የሀገር መከላከያ ኃይልን መጉዳት በሀገር ላይ ከሚፈጸሙ ወንጀሎች አንዱ ሲሆን ማንም ሰው አስቦ፡-

    ሀ/ ወታደራዊ ፀባይ ያለውን ወይም ለሀገር መከላከያ እንዲሆን የታቀደውን ማናቸውንም የኢኮኖሚ ድርጅት፣ የመከላከያ ሥራ ተቋም ወይም ሥፍራ፣ የመገናኛ ወይም የመጓጓዣ ዘዴ፣ ሥራ፣ ማከማቻ፣ የጦር መሣሪያ ወይም ቁሳቁስ አሳልፎ በመስጠት፣ በማፍረስ፣ የተንኮል ሥራ በመፈፀም ወይም ለአገልግሎት እንዳይውል በማድረግ፣

    ለ/ ጠላት ለሆነ ለውጪ ሀገር መንግሥት ወታደሮች በማቅረብ ወይም የኢትዮጵያ ዜጎች ለዚሁ ለጠላት ሀገር በወታደርነት እንዲያገለግሉ በመመልመል ወይም በማግባባት ወይም ራሱ ዜግነቱ ኢትዮጵያዊ ሆኖ ለዚሁ ዓይነት የጠላት ሀገር መንግሥት በመሰለፍ፣

    ሐ/ የጦር ወታደሩ የጦር አገልግሎት ከመፈፀም እምቢተኛ እንዲሆን፣ ወታደራዊ አመፅ እንዲያስነሳ ወይም እንዲከዳ በግልፅ በማነሳሳት ወይም የጦር ወታደርነት ግዴታ ያለበት ሰው ከእነዚህ ወንጀሎች አንደኛውን እንዲፈፅም በመገፋፋት ወይም እንዲነሳሳ በማድረግ፣ ወይም

    መ/ ለሀገር መከላከያ የሚያገለግሉትን ወታደራዊ የጥንቃቄ እርምጃዎች በማሰናከል፣ በማበላሸት ወይም በማናቸውም ሌላ ዘዴ የተንኮል ድርጊት በመፈፀም በኢትዮጵያ የመከላከያ ኃይል ላይ ጉዳት ያደረሰ እንደሆነ ከአምስት ዓመት እስከ 25 ዓመት ለመድረስ በሚችል ጽኑ እስራት ወይም ነገሩ እጅግ ከባድ በሆነ ጊዜ በተለይም በጦርነት ወይም ጦር አስጊ በሆነበት ጊዜ እንደሆነ በእድሜ ልክ ጽኑ እስራት ወይም በሞት ይቀጣል።

    ምንጭ፦ የኢፌዲሪ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ

    ከመንግሥታዊ ተቋማት የሚወጡ ሰሞነኛ ዜናዎችና መግለጫዎች

    በሀገር ላይ የፈጸሙ ወንጀሎች ስለሚያስከትሉት ቅጣት የወንጀል ሕግ ምን ይላል?

    Anonymous
    Inactive

    የአማራ ብልጽግና ፓርቲ ለሀቀኛ የፌዴራሊዝም ሥርዓት ካልታገለ እንደ ብልጽግና መቆም አይችልም!

    የአማራ ብልጽግና ፓርቲ ወቅታዊ አቋም
    ኅዳር 27 ቀን 2013 ዓ.ም.
    ባህር ዳር

    ስናጠፋ የሚገስጸን፣ ስናለማ የሚያግዘን ሕዝብ እንዳለን እናምናለን። በሕዝባችን ስብራት ላይ ተደማሪ ስብራት መሆን ስለማንፈልግ ከሀቀኛ የፌዴራሊዝም ሥርዓት በመነጨ ቅን ልቦናና ፍላጎት የሕዝባችንን ድምጽ ለማክበርና ለማስከበር ተዘጋጅተናል። የብልጽግና ፓርቲ ሲመሠረት የአብዮታዊ ዴሞክራሲን ማቅ እና ድሪት አውልቆ የሕዝብን ሀቀኛ ፍላጎትና እውነተኛ መሻት የሆነውን መካከለኛ አማራጭና የወሳኝ ኩነቶች ወሳኝነት ለሕዝብ ተጠቃሚነት የሚበጀውን የፕራግማቲዝም (pragmatism) ድርና ማግ ተጎናጽፎ ነው። በብልጽግና እምነት ቋሚና የማይለወጥ እውነት የለም፤ ሁሉም ነገር ቋሚ ሊሆን አይችልም። በብልጽግና እምነት የማይለወጥ መሠረታዊና ቁሳዊ የሆነ ነገርም አይኖርም። ከብልጽግና ርዕዮተዓለማዊ እምነት አኳያ ቋሚና የማይለወጥ ነገር አለ ከተባለ እሱም ኅብረብሔራዊ ፌዴራሊዝምና ኢትዮጵያዊነት ብቻ ነው።

    መደመርን መንገዳችን፣ ብልጽግናን መዳረሻችን አድርገን ስንነሳ መደመር የሚፈልጉ ዜጎቻችንን ልንቀንሳቸው አንችልም። ዛሬ በማይካድራ፣ በዳንሻ፣ በዓላማጣ፣ በጥሙጋና በዋጃ ባጠቃላይ በራያ ዋጃ ዓላማጣና ኮረም እንዲሁም በወልቃይት ጠገዴ ሴቲት ሁመራ በተደረገው ሕዝባዊ ሰልፍ ያሰማችሁትን የ‘አማራ ነን’ ድምጽ በአክብሮት የምንቀበለውና በጽናት የታገልንለት ወደፊትም የምንታገልለት የመደመር ኅብረብሔራዊ ፌዴራላዊ ትርጉም ያለው የቆየ ግን በእብሪት የተገፋና መልስ የተነፈገው የዜጎች ጥያቄ ነው።

    ሁሉም የብልጽግና ቤተሰቦችና በሀገር ውስጥም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ የኢትዮጵያ ጉዳይ ያገባኛል የሚሉ ኃይሎች እንዲረዱት የምንፈልገው ቁምነገር አለ።

    በግፍ ተወረርን እንጂ ማንንም አልወረርንም።

    ክልላዊ ወሰናችንንና ፌዴራላዊ መብታችንን በመጋፋት በግፍ ተጠቃን እንጂ ማንንም አላጠቃንም።

    በጭካኔና ያለርህራሄ የዘር ማጥፋት ወንጀል ተፈጸመብን እንጂ በማንም ላይ የግፍ አጸፋ አልመለስንም። በደም ፍላት ስሜት ተገፍትረው ግፍ ለመፈጸም የቃጡና የሚቃጡ በውስጣችን ያሉ ስሁታንንም ያለርህራሄ ታግለናል፤ እየታገልንም እንገኛለን።

    ከልክ በላይ በተወጠረ እብሪት በትምክህተኝነት ስሜትና በተስፋፊነት ልክፍት ተወጥረው ሕዝባችንን፣ መሬታችንን፣ ታሪካችንን፣ መልካም ስማችንን፣ የ30 ዓመት ሁሉአቀፍ ክልላዊ እድገታችንን፣ እድሜያችንንና ሥነ-ልቦናችንን በግፍ ተዘረፍን እንጂ የማንንም ቅንጣት አልዘረፍንም።

    የወሰን፣ የማንነትና የፍትሀዊ ተጠቃሚነት ጥያቂያችንን በሕግና በሥርዓት አቀረብን እንጂ እንደ ትሕነግ በማን አለብኝነት ‘ዘራፍ’ አላልንም።

    የተገፋን፣ የተበደልንና የተጨፈጨፍን ቢሆንም ለፌዴራል መንግሥቱም ሆነ ለሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱ አደጋ አልፈጠርንም።

    የሀገር መከላከያ ሠራዊትንና የሀገር ሉአላዊነትን ጠብቆ ለማስጠበቅ እስከ አሁኗ ሰዓት ድረስ ቁርጠኛ አጋርነታችንን በክቡር መስዋዕትነት አረጋገጥን እንጂ ሀገራችንና ሕዝባችንን በመካድ አልወጋንም። ሀገርና ሕዝብ ክደው በወገን ላይ የጭካኔ አፈሙዝ ያዞሩትንም የታሪክ ማፈርያዎች እንደሆኑ እንረዳለን።

    በሰላማዊ መንገድ እጅ የሰጡና የተማረኩ የትሕነግ ተዋጊ ኃይሎችን በወንድማማች መንፈስ ቁስላቸውን ጠረግን፣ እንዲያገግሙ በፍቅር ተንከባከብን እንጂ እንደጠላት አልገፋናቸውም። በተለመደው አማራዊ የእንግዳ አቀባበል ሥርዓት እልፍኛችንን ለቀን፣ ከአልጋችን ወርደን የምርኮኛነት ስሜት እንዳይሰማቸው አስተናገድናቸው እንጂ በግፍ አላሸማቀቅናቸውም።

    እብሪተኛው የአፓርታይድ ቡድን በፈጸመብን ሴራ እስከአሁኗ ሰዓት ድረስ በተለያዩ የሀገሪቷ አካባቢዎች በስጋትና በጭንቀት የሚኖረው የአማራ ሕዝብ ነው። በ10ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎቻችን አሁንም በስደት ላይ ይገኛሉ። በቤንሻንጉል ክልል በመተከል ዞን የሚፈሰው የአማራ ደም ዛሬም አልቆመም። በሌሎችም አካባቢዎች የስጋት ጅረት አልተገደበም። በማይካድራና በሁመራ በየቦታው የተጣሉ አስከሬኖች ‘በክብር ቅበሩኝ’ ጥሪ ቢያስተጋቡም የንጹሃኑ በድኖች ግን ዛሬም ድረስ ተለቅመው አላለቁም።

    ይሁን እንጂ የአማራ ሕዝብ ጥንተ ጠላት የሆነው ትሕነግና ጽንፈኛ ወዳጆቻቸው ከትክክለኛው ወቅታዊ አውድ ፍጹም የሚቃረን ሙግትና ትንታኔ ሲሰጡ ልማዳቸው መሆኑን ብናውቅም ለአንድ አንድ የትግል አጋሮቻችንና ደጋፊዎቻችንን ግልጽ መልዕክት ማስተላለፍ እንፈልጋለን።

    1. ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. አረመኔውና የአፓርታይድ ሥርዓት አቀንቃኙ ትሕነግ በሰሜን ዕዝ ላይ የተጠናና የተደራጀ ሁሉ-አቀፍ ጥቃት ሲፈጽም የወራሪነት፣ የተስፋፊነትና የጨፍጫፊነት አድማሱን በማስፋት በ24 ሰዓት ውስጥ በምሥራቅና በምዕራብ የአማራ ክልል አቅጣጫዎች ጎንደርንና ወልድያን የመቆጣጠር ግብ አስቀምጦ ነው። ይህንን እኩይ ዓላማውን ለማሳካት ከ3 ዓመት ያላነሰ ወታደራዊ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቷል። ትሕነግ ያስቀመጠውን የወራሪነት ግብ በመቀልበስ ሀገርና ሕዝብን ለመታደግ በወትሮ ዝግጁነት መፈጸሙ የአማራን ሕዝብ ሊያስመሰግነው ሲገባ፥ በጥርጣሬ እንድንታይ የሚያደርግ በፍጹም አይሆንም። የተከፈተብንን የግፍ ጦርነት ተከላክለንም፣ አጥቅተንም ጦርነቱን መቀልበሳችንና በግፍ ተነጥቀን የነበረውን ተፈጥሯዊ መብታችንን በእጃችን ማስገባታችን (repossession right) የተፈጥሮን ሕግ የሚቃረን ሳይሆን በእብሪተኞች የማይታረቅ ተቃርኖ መቃብር ላይ የተረጋገጠ ድል ነው። ስለሆነም እርስት ለማስመለስ ያልታገለን ይልቁንም ላለፉት 30 ዓመታት ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ጥያቄ ሲያቀርብ የቆየን ሕዝብና መንግሥት እርስት ለማስመለስ እንደተዋጋ አድርጎ ኢ-ሕገ መንግሥታዊና አመክንዮ የጎደለው ድምጽ ማሰማት ነውር ነው እንላለን። በእርግጥ እርስት ማስመለስ የሚለው ትችት ለባለእርስቶች የተወረወረ የበላ-ልበልሀ ክርክር መሆኑ የአማራ ሕዝብን ጥያቄ ፍትሀዊነት ያረጋገጠ ሀቅ በመሆኑ ሀሳቡን ደጋግማችሁ ለተጠቀማችሁ ሁሉ ምስጋና እናቀርብላችኋለን።
    2. እንደ ብልጽግና ፓርቲ የአማራ ሕዝብ ሀቅ ይታወቃል። የአማራ ሕዝብ ሀቅ ዛሬም በአደባባይ በሕዝባዊ ሰልፍ በይፋ እንደሚታየው የማንነት፣ የወሰን፣ በህይወት የመኖርና የአካል ደህንነት ፍትሀዊ ጥያቄ ነበር። ከ500ሺ ሕዝብ በላይ የተፈናቀለባቸው፣ በ10ሺዎች የሚቆጠር ሕዝብ የተገደለባቸው፣ በ10ሺዎች የሚቆጠር ሕዝብ የተሰወረባቸው እነዚህ አካባቢዎች ዛሬም የተረጋገጠ የጅምላ መቃብር የተገኘባቸውና የአፓርታይድ ሥርዓት በተጨባጭ የተፈጸመባቸው የትሕነግ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ጭካኔ ማረጋገጫ የግፉአን መቀበርያ አጽመ እርስቶች ናቸው።

    በግፍ የተጨፈጨፉ የንጹሀን ወገኖቻችን አስከሬኖች ተለቅመው በክብር ባላረፉበት በዚህ ወቅት የባለቤትነት ጥያቄ ማንሳት የወንበዴውን ቡድን ወንጀል ለመደበቅና ለማድበስበስ እየተፈጸመ የሚገኝ ሌላኛው የትሕነግ ሸፍጥ ማምለጫ መንገድ ሲሆን፥ የአካባቢውን ነባራዊ ሀቅ በመረዳትም ሆነ ባለመረዳት የሚራመዱ የተሳሳቱ ሀሳቦች የሞራል ጥያቄ የሚነሳባቸው ናቸው።

    ስለሆነም የሕግ የበላይነት ለማስከበር፣ የሀገር ሉአላዊነት ለማጽናት በተደረገ ሁሉ አቀፍ የትግል ጀብዱ በታሪክ አጋጣሚ ወደባለእርስቱ የገቡ አካባቢዎች (repossessed lands) ላይ የሚነሳውን ማንኛውንም ጥያቄ በሥርዓቱና በአግባቡ በቀጣይ ማየት ይቻላል የሚል እምነት አለን። ግን ደግሞ የትሕነግን የአፓርታይድነት የወንጀል ፈለግ (criminal scene) መፈተሽና መመርመር፣ ለትግራይና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማጋለጥ ከመቸውም ጊዜ በላይ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል የሚል እምነት አለን። ስለሆነም:-

      • ላለፉት 50 ዓመታት የዜጎች ማጎርያና ማሰቃያ የሆኑ ከመሬት በታች የተሰሩ ዋሻዎች (underground torching caves) ለሕዝብ ይፋ መደረግ አለባቸው።
      • ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የጅምላ መቃብሮች ታስሰው ላለፉት 50 ዓመታት እንደ ሕዝብ የተፈጸመብንን ግፍና ጭካኔ ዓለም እንዲያውቀው ማድረግ ታሪካዊ ኃላፊነት እንደሆነ እናምናለን።
    1. በአጠቃላይ የብልጽግና ፓርቲ ተልዕኮ ግፈኛና ግፍን ነቅሎ በአዲስና በተረኛ ግፈኛና ግፈኝነትን ማጽናት አይደለም። ወትሮም ቢሆን የኢትዮጵያ ችግር ከግፈኞች አልነበረም። እንደሀገር ግፈኞችን መቅበር የተለመደ እንጂ አዲስ ነገር አይደለም። በየታሪክ ምዕራፉ ግፈኞችን መቅበር የምትችል ሀገር ግፍን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስወገድ ግን አልቻለችም። ስለሆነም የብልጽግና ፓርቲ ግፈኝነትን በጽናት በሚታገልበት በዚህ ታሪካዊ መድረክ የየበኩላችንን ድርሻ እንድንወጣ እየጠየቅን፥ በእኛ በኩል እብሪተኝነትም ሆነ ግፈኝነት የሕዝባችንን ክብር ዝቅ ስለሚያደርገው በጽናትና በታማኝነት የምንታገለው መሆኑን አበክረን እንገልጻለን።
    2. በሁሉም የክልላችን አካባቢዎች አስተማማኝ ሰላም ለማስፈን የሕግ የበላይነት የምናስከብር መሆኑን እያረጋገጥን፤ በቤንሻንጉል ክልል በሕዝባችን ላይ ተደጋጋሚ ግፍ የሚፈፅሙ የእብሪተኞች ቅሪት ዓላማና ፍላጎት በድል እንደሚቋጭ ሳንጠራጠር የተጀመረውን ሕግ የማስበር ሥራ አጠናክረን መቀጠል ይኖርብናል። ጎን ለጎንም የተፈናቃይ ወገኖቻችንን መሠረታዊና ወቅታዊ ፍላጎት እንዲሟላ ከማድረግ ባሻገር የሕዝባችንን እንቅፋት በሕግ አግባብ ተጠራርጎ መጥፋቱ ከተረጋገጠ በኋላ ዜጎቻችንን ተመልሰው በቀያቸው ላይ እንዲሰፍሩ የሚደረግ መሆኑን በድጋሚ እናረጋግጣለን።

    በመጨረሻም በትሕነግ መራሹ እብሪተኛ አፓርታይድ እርምጃ ዘግናኝ ግፍ የተፈጸመባችሁ ውድ የመከላከያ ሠራዊት አባላትና የማይካድራና የሁመራ ሰማዕታት ሁልጊዜም በሕዝባችን ልብ ውስጥ ዘላለማዊ ክብር አላችሁ።

    የሕግ የበላይነት ለማስከበር በተፈጸመው እልህ አስጨራሽ ግብ ግብ ክቡር መስዋዕትነት የፈጸማችሁ የሀገር መከላከያ ሠራዊት አባላት፣ የአማራ ልዩ ኃይልና ሚሊሻ፣ የአፋር ልዩ ኃይልና ሚሊሻ የአባቶቻችን ልጆች ስለሆናችሁ ኮርተንባችኋል፤ ለዘላለምም እንኮራባችኋለን።

    የኦነግ ሽኔንና የጉሙዝ አማጺ ቡድንን ለመደምሰስ በሁሉም የአገሪቷ አካባቢዎች ስምሪት ወስዳችሁ ታሪካዊ መስዋዕትነት በመክፈል ላይ የምትገኙ የፌዴራል የጸጥታ ኃይሎች፣ የኦሮምያና የቤንሻንጉል ክልል ሀቀኛ የልዩ ኃይልና የሚሊሻ አባላት ጀግንነታችሁን ስንዘክር በአማራ ሕዝብ አክብሮትና ትህትና ነው።

    ድል ከኢትዮጵያና ከአማራ ሕዝብ አብራክ ለተገኙ ታሪካዊ ጀግኖቻችን!!!
    ውርደት በእብሪትና በትዕቢት ተወጥረው ሀገራችንንና ሕዝባችንን ለሚወጉ ጠላቶቻችን!!!
    ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ፈጣሪ አብዝቶ ይጠብቅ!!!
    የአማራ ብልጽግና ፓርቲ

    የአማራ ብልጽግና ፓርቲ

    Anonymous
    Inactive

    ማይካድራ ውስጥ ሲቪል ሰዎች ላይ የተደረገው ጭፍጨፋ የግፍና ጭካኔ ወንጀል ነው ― ኢሰመኮ

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) መግለጫ
    ትግራይ፡ የማይካድራ ሲቪል ሰዎች ጭፍጨፋ የግፍና ጭካኔ ወንጀል ነው
    የተጎዱትን ማቋቋም እና የአጥፊዎችን ተጠያቂነት ማረጋገጥ ይገባል

    በትግራይ ክልል ምዕራባዊ ዞን በምትገኘው ማይካድራ ከተማ ጥቅምት 30 ቀን 2013 ዓ.ም. በወቅቱ በስልጣን ላይ በነበረው የአካባቢው መስተዳድር የጸጥታ መዋቅርና ሳምሪ በተባለ ኢ-መደበኛ የወጣቶች ቡድን የተፈጸመው ጥቃት፤ ግድያ፣ ጉዳትና ውድመት፤ ጠቅላላ ድርጊቱና ውጤቱ ግፍና ጭካኔ የተሞላበት በሲቪል ሰዎች ላይ  የተፈጸመ የጭፍጨፋ ወንጀል (atrocious crime of massacre against civilians) መሆኑን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ገለጸ።

    ይህ የተገለጸው ኮሚሽኑ ከሕዳር 5 እስከ ሕዳር 9 ቀን 2013 ዓ.ም. ድረስ ማይካድራ ከተማ እንዲሁም በአብርሀ ጅራ፣ በሳንጃ፣ በዳንሻ፣ በሁመራ እና በጐንደር ከተሞች ተዘዋውሮ ባደረገው ምርመራ የደረሰበትን ግኝቶች ይፋ ባደረገበት የመጀመሪያ ደረጃ ቀዳሚ ሪፖርት ነው። ይህ ከፍተኛ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል (crimes against humanity) እና የጦር ወንጀል (war crime)  ሊሆን እንደሚችል የሚያመለክት ስለሆነ፥ ኮሚሽኑ ዝርዝር ማስረጃዎቹን እና ወንጀሉን የሚያቋቁሙትን የሕግና የፍሬ ነገር ትንተና በሙሉ ሪፖርቱ ላይ በዝርዝር አጣርቶ የሚያቀርብ መሆኑን አሳውቋል።

    በቀዳሚ ሪፖርቱ እንደተመለከተው፥ በአካባቢው የነበረው የሚሊሽያና የፖሊስ ጸጥታ መዋቅር በፌዴራሉ ሀገር መከላከያ ሠራዊት እርምጃ ሸሽቶ አካባቢውን ለቅቆ ከመውጣቱ በፊት ሳምሪ ከተባለ መደበኛ ያልሆነ የትግራይ ወጣቶች ቡድን ጋር በማበርና በመተባበር በተለይ “አማሮችእና ወልቃይቴዎች” ያሏቸውን የአካባቢው ነዋሪ ሲቪል ሰዎች ከቤት ቤት እየዞሩና በየጐዳናው ላይ በገመድ በማነቅ፣ በስለት በመጥረቢያ በዱላ በመደብደብ ገድለዋል፤ የአካል ጉዳት አድርሰዋል፤ እንዲሁም ንብረት አውድመዋል። ኢሰመኮ ከአካባቢው ምንጮች እስከ አሁን ባገኘው መረጃ በአነስተኛ ግምት እስከ 600 ሰዎች የተገደሉ ሲሆን ትክክለኛው ቁጥር ከዚህ ሊበልጥም እንደሚችል በሪፖርቱ ተመልክቷል።

    ሳምሪ የሚባለው የትግራይ ወጣቶች ቡድን በዚህ ከባድ ወንጀል ላይ ቢሰማራም፤ በአንጻሩ የትግራይ ብሔረሰብ ተወላጅች የሆኑ ሌሎች የአካባቢው ነዋሪዎች አጥቂው ቡድን ሲያሳድዳቸው የነበሩ ሲቪል ሰዎችን በቤታቸው፣ በቤተ ክርስቲያን እና በእርሻ ቦታ ደብቀው በመሸሸግ ሕይወታቸውን እንዳተረፉላቸው ኢሰመኮ ያነጋገራቸው ምስክሮች አረጋግጠዋል።

    የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዳንኤል በቀለ (ዶ/ር) “በማይካድራ ከተማ በአነስተኛ ጽንፈኛ ቡድን የተፈጸመው በብሔር ማንነት ላይ የተመሠረተ እጅግ ዘግናኝ ኢ-ሰብዓዊ ወንጀል ልብ ሰባሪ ቢሆንም፤ በአንጻሩ ኢትዮጵያውያን በብሔር ሳይለያዩ አንዱ የሌላው ጠባቂ ሆነው መታየታቸው ልብ ይጠግናል፤ ስለ ወደፊት በሰላም አብሮ መኖርም ተስፋ ይሰጣል” ብለዋል። አክለውም “የተጐዱ ሰዎችን እና አካባቢዎችን መልሶ ከማቋቋምና ከመጠገን በተጨማሪ፥ በዚህ ከባድ የሰብዓዊ መብቶች ወንጀል በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ የተሳተፉ በየደረጃው ያሉ ጥፋተኞችን በሕግ ፊት ተጠያቂነት ማረጋገጥ ያስፈልጋል” ብለዋል።

    የኮሚሽኑን የመጀመሪያ ደረጃ ቀዳሚ ሪፖርትን እዚህ ጋር በመጫን ማግኘት ይቻላል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)
    ኅዳር 15 ቀን 2013 ዓ.ም.

    ማይካድራ ጭፍጨፋ

Viewing 15 results - 106 through 120 (of 730 total)