Search Results for 'ጅማ ዩኒቨርሲቲ'

Home Forums Search Search Results for 'ጅማ ዩኒቨርሲቲ'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 30 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    የጅማ እና ዲላ ዩኒቨርሲቲዎች ከ7,390 በላይ ተማሪዎችን አስመረቁ

    ጅማ ዩኒቨርሲቲ በመደበኛ፣ በማታውና በተከታታይ የትምህርት መርሀግብሮች ያሰለጠናቸውን 3,926 ተማሪዎች በደማቅ ሥነ-ሥርዓት ነሐሴ 1 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. አስመርቋል።

    በምርቃ ሥነ-ሥርዓቱ የተገኙት የዕለቱ የክብር እንግዳ የኢፌዲሪ የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል ባስተላለፉት መልዕክት፥ ከሀይማኖትና ብሔር ልዩነት ባለፈ ተዋድደንና ተፈቃቅረን እንደኖርነው ሁሉ፣ አሁንም በአንድነት እጅ ለእጅ ተያይዘን የሀገራችንን ብልጽግና እናረጋግጣለን ብለዋል።

    የኢፌዲሪ የጤና ሚኒስትር ዴኤታና የጅማ ዩኒቨርሲቲ ቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ በበኩላቸው፥ በቀጣይ ዩኒቨርሲቲውን የላቀ የምርምር ማዕከል ለማድረግ የሥራ አመራር ቦርዱ ተግቶ ይሠራል ብለዋል።

    የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት ዶ/ር ጀማል አባፊጣ ባደረጉት ንግግር፥ ከከፍተኛ ትምህርት ተልዕኮዎች መካከል የመጀመሪያው ጥራት ያለው ትምህርት በመስጠት በእውቀት፣ በክህሎት እና በሥነ-ምግባር የዳበረና ሀገር ተረካቢ ዜጋ ማፍራት ነው። ግቡም ተመራቂው ባካበተው የቴክኖሎጂ አቅም ራሱን አብቅቶ ሀገርንና ወገንን መቀየር ሲሆን፥ ጅማ ዩኒቨርሲቲም ይህንኑ ዓላማ እውን ለማድረግ ተግቶ በመሥራት ላይ ይገኛል ብለዋል። ለዚህም ምስክሩ በምርምርና ተቋማዊ አመራር የላቀ ውጤት ማስመዝገቡ ነው በማለት አክልዋል።

    በዕለቱ ከተመረቁት ተማሪዎች መካከል በቅድመ ምረቃ 2,260 ወንድ ሲሆኑ፣ 1234 ሴቶች ተመራቂዎች ናቸው።

    በድኅረ ምረቃ መርሀ ግብር ከተመረቁት 402 ተማሪዎች ውስጥ 318 ወንዶች ሲሆኑ፣ 85 ሴቶች ናቸው፡፡ ከድኅረ ምረቃ መርሀ ግበሩ 18 የሦስተኛ ዲግሪ (ፒ ኤችዲ) ምሩቃን ሲሆኑ፣ በጅማ ዩኒቨርሲቲ ታሪክ ከፍተኛው የሦስተኛ ዲግሪ መርሀግብር ተማሪዎች የተመረቁበት ነው። የሦስተኛ ዲግሪ ተማራቂዎቹ ከሒሳብ፣ ከጤና ግንኙነት (health communication)፣ እና ከኢንፎርሜሽን ሳይንስ ትምህርት ክፍሎች ናቸው።

    በተጨማሪም ጅማ ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያ ዲግሪ መርሀግብር በሶፍትዌር ኢንጅነሪንግና በቪዥዋል አርት (ሥነ-ስዕል) የሰለጠኑ ተማሪዎችን ለመጀመሪያ ግዜ አስመርቋል።

    ከተማሪዎች ምርቃት ጋር በተያያዘ ዜና፥፥ ዲላ ዩኒቨርሲቲ በመደበኛና በሁለተኛ ዲግር እንዲሁም በተከታታይ መርሀግብር ያሰለጠናቸውን ከ3,450 በላይ ተማሪዎችን እሁድ ነሐሴ 2 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. አስመርቋል።

    ዩኒቨርሲቲው ያስመረቃቸው ተማሪዎች 2,101 ወንድና 983 ሴት በድምሩ 3,084 ተማሪዎችን በመጀመሪያ ዲግሪ፤ 317 ወንድና 72 ሴት በድምሩ 384 ተማሪዎችን በሁለተኛ ዲግሪ፤ በአጠቃላይ 3,468 ተማሪዎችን በዕለቱ አስመርቋል።

    የዘንድሮው የዲላ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ምርቃት ለ23ተኛ ጊዜ የተከናወነ ሲሆን፥ ከተመሠረተበት ከ1989 ዓ.ም. ጀምሮ እስካሁን ድረስ ከ71,475 በላይ ተማሪዎችን አሰልጥኖ ለሀገር ኢኮኖሚ የበኩሉን አስተዋጽኦ አበርክቷል። በአሁኑ ወቃትም ከ26ሺህ በላይ የሚሆኑ ተማሪዎችን በመደበኛ እና በተከታታይ የትምህርት መርሀግብሮች እያሰለጠነ  ይገኛል።

    ዩኒቨርሲቲው በዋናው ግቢው ያከናወነው የተማሪዎች ምርቃት ሥነ-ሥርዓት በፋና ቴሌቪዥን በቀጥታ እንደተተላለፈ የዩኒቨርሲቲው የሕዝብ ግንኙነትና ሚዲያ ዘርፍ ዘግቧል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የጅማ እና ዲላ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎችን አስመረቁ

    Semonegna
    Keymaster

    በኢትዮጵያ ስምንት ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል ተብለው ተለዩ

    ጎንደር (ኢዜአ) – በኢትዮጵያ ስምንት የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል (Center of Excellence) በመባል መለየታቸውን የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የጎንደር ዩኒቨርሲቲ በተመረጡ ትምህርት ቤቶች በትምህርት ጥራት ዙሪያ ያካሄደውን የምርምር ግኝቶች ላይ መስከረም 29 ቀን 2013 ዓም ከባለድርሻዎች ጋር ተወያይቷል።

    የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከፍተኛ አማካሪ ዶ/ር ወርቁ ነጋሽ በወቅቱ እንደገለጹት፥ በሀገሪቱ የሚገኙ 46 ዩኒቨርሲቲዎች በምርምር፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ እንዲሁም በአጠቃላይ ትምህርት በሚል በሦስት ደረጃዎች ተለይተዋል።

    ባለፉት ዓመታት በርካታ ችግር ፈቺ የምርምር ውጤቶችን ሲያበረክቱ የቆዩና ወደፊትም አስተዋጽዖ ይኖራቸዋል የተባሉ ስምንት ዩኒቨርሲቲዎች በምርምር ዘርፍ የልህቀት ማዕከል እንዲሆኑ መለየታቸውን ተናግረዋል።

    ጎንደርአዲስ አበባባህር ዳርመቀሌጅማሀዋሳአርባ ምንጭ እና ሐረማያ ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል እንዲሆኑ ተለይተዋል” ብለዋል ዶ/ር ወርቁ።

    ለአንድ ሀገር ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ችግር ፈቺ ምርምር ቁልፍ ሚና እንዳለው የገለጹት ዶ/ር ወርቁ፥ “ያደጉ ሀገሮች የእድገት ምስጢርም ከዚህ የመነጨ ነው” ብለዋል። የምርምር (Research) ዩኒቨርሲቲዎቹ በዓለምአቀፍ ደረጃ ከሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር አቻ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ አቅማቸውን ለመገንባት በትኩረት እንደሚሠራ አመላክተዋል።

    ሌሎች 15 የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ በሳይንስና ቴክኖሎጂ (Science and Technology) ዘርፍ ትምህርትና ስልጠና እንዲሰጡ መለየታቸውን ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ በቂ እውቀትና ክህሎት ያዳበረ ዜጋ ማፍራት እንዲችሉ ተከታታይ ድጋፍ እንደሚደረግላቸው አመላክተዋል።

    ቀሪዎቹ 23 ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ አጠቃላይ ትምህርትና ስልጠና እንዲሰጡ የተለዩ መሆኑን ዶ/ር ወርቁ አስታውቀዋል።

    የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር መርሻ ጫኔ ዩኒቨርሲቲው በርካታ ችግር ፈቺ ጥናትና ምርምር በማካሄድ ለማህበረሰቡ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረጉን ተናግረዋል።

    ላለፉት ሶስት አመታት ጎንደር ከተማን ጨምሮ በሰሜን፣ በማእከላዊና በምዕራብ ጎንደር ዞኖች በተመረጡ 1,343 የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ላይ በትምህርት ጥራት ዙሪያ ጥናትና ምርምር መካሄዱን ገልጸዋል። በምርምር ውጤቶቹ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይትና ምክክር እየተካሄደ መሆኑን አስታውቀዋል።

    “በዩኒቨርሲቲው የሥነ-ትምህርት ኮሌጅ መምህራን የተዘጋጀው የምርምር ውጤት ለፖሊሲ አውጪዎች ጠቃሚ ግብዓት ሆኖ የሚያገለግል ነው” ያሉት ደግሞ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አሥራት አጸደወይን ናቸው።

    ባለፈው ዓመት ዩኒቨርሲቲው ከ200 በላይ የምርምር ሥራዎችን ማካሄዱን ዶ/ር አሥራት አስታውሰዋል፤ ዘንድሮም በተለያዩ ዘርፎች ምርምር ለማካሄድ የሚያስችል ቅድመ ዝግጅት እያካሄደ እንደሚገኝ ፕሬዝዳንቱ ማሳወቃቸውን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዘግቧል።

    ለአንድ ቀን በተካሄደው ውይይት የዩኒቨርሲቲው መምህራንና የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም ከጎንደር ከተማ አስተዳደር የተውጣጡ መምህራንና የትምህርት አመራሮች ተሳትፈዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    የምርምር ልህቀት ማዕከል

    Anonymous
    Inactive

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን መቀበል ከመጀመራቸው በፊት የተቋማቱ ዝግጁነት እንደሚረጋገጥ ተገለጸ

    አዲስ አበባ (የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር) – የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን መልሶ ለመክፈት የሚያስችሉ ሁኔታዎች ላይ መስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም በጅማ ዩኒቨርሲቲ መሰብሰቢያ አዳራሽ ውይይት ተካሂዷል።

    በውይይቱ መጀመሪያ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሙሉ ነጋ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በመከላከል የትምህርትና ስልጠና ተቋማት መልሶ የመክፈት ሂደትና ዝግጅት በሚል ርዕስ ምክረ-ሃሳብ አቅርበዋል።

    በ2012 ዓ.ም የተቋረጠዉን ትምህርት በልዩ ዕቅድ ለማጠናቀቅ በሚሠሩ ሥራዎችና ትምህርት ሲጀመር ሊደረጉ ስለሚገባቸው ጥንቃቄዎች እንዲሁም ቀደም ተብለው በከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ የሚደረጉ ጥንቃቄዎች ምን መምሰል እንዳለባቸው በምክረ-ሃሳባቸው ቀርቦ ውይይት ተካሂዶባቸዋል።

    በጉባኤው የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ በበኩላቸው ‘መቼ እንክፈት?’ ለሚለው ትክክለኛ መልስ እያንዳንዱ ዩኒቨርሲቲ በዓለም የጤና ድርጅት መለኪያ መስፈርት መሠረት ደረጃውን ጠብቆ በተዘጋጀ ዝርዝር በጥልቀት የዝግጅት መጠኑ ተፈትሾ ዝግጁ ሲሆን ብቻ ነው ብለዋል። በዚያ መሠረት የተቋማት ዝግጅት ይፈተሻል፤ በዳሰሳውም መሠረት መቀበል እንደሚችሉ ፍቃድ ይሰጣል ሲሉ አብራርተዋል።

    ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ እንደገለፁት፥ ቅድሚያ ለተመራቂዎች [ቅድሚያ] በመስጠት፣ ተማሪዎችን በመከፋፈል በትንሽ ቁጥር ይጀመራል። ይህም ከሚታዩ ነገሮች እየተማርን የተማሪ ቁጥር ለመጨመር ዕድል ይሰጠናል ብለዋል። ዝርዝር አፈጻጸሙ በምን እንደሚመራ ከጤና ሚኒስቴር ጋር በመሆን ፕሮቶኮል ይዘጋጃልም ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲዎች የለይቶ ማቆያ ማዕከላት እንደመሆናቸው የክልል መንግሥታት ሥራ ይጠበቅባቸዋል። አማራጭ የለይቶ ማቆያ (quarantine) ቦታዎችን ማዘጋጀትም ግድ ስለሚላቸው እዚያ ላይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ይሠራል ብለዋል። ተማሪዎችን በማጓጓዝ ሂደት ችግር እንዳያጋጥም ከትራንስፖርት ሚኒስቴር እና ጤና ሚኒስቴር ጋር በትብብር እንሠራበታለን ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎችን መልሶ ለመቀበል የሚያስችል እቅድ ካሁኑ አዘጋጅተው ከአስተዳደር ሠራተኞችና መምህራን ጋር በመወያየት የጋራ ሊያደርጉ እንደሚገባም አሳስበዋል። የበፊቱን አሠራር ይዘን መቀጠል አንችልም፤ ዝግጅታችንን፣ ተጋላጭነታችንን አውቀን ተማሪ እንቀበላለን። አንድ ብሎክ ወይም አንድ ካምፓስ ኮቪድ-19 ቢያጋጥም ምን እናደርጋለን ከሚለው ጀምሮ በዝርዝር መሥራት እና እያንዳንዱ እቅድ ያለተማሪዎች እገዛ ተፈፃሚ ስለማይሆን ወደእነሱ ለማስረፅ መሥራት የግድ ይለናል ብለዋል።

    ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ እንዳሉት፥ ጊዜው የተማሪዎች ሕብረት ኃላፊነት የሚፈተንበት ነው። የተማሪዎች ሕብረት አባላት የመፍትሄ ሃሳብ ሆናችሁ ለተፈፃሚነቱ ከዩኒቨርሲቲያችሁ ጋር በትብብር እንድትሠሩ ከእናንተ ይጠበቃል። ሰላማችሁን ማስጠበቅና ለደህንነታችሁ ዘብ መቆም ለትምህርታችሁ ቀጣይነት ዋስትና ነው ሲሉ አብራርተዋል። ዩኒቨርሲቲዎች መከፈታቸው ላይ ብቻ ሳይሆን ተመልሰው እንዳይዘጉም ጭምር የተማሪዎች ድርሻ ከፍተኛ እንደሆነም ጠቁመዋል።

    የጥንቃቄ ቁሳቁሶችን አስመልክቶም የትኞቹ በዩኒቨርሲቲዎች ይቅረቡ የትኞቹ በተማሪዎች ይሟሉ የሚለውን ከተጨባጭ ሁኔታ አንፃር ለይቶ መወሰን አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል።

    በውይይቱ ማጠቃለያ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ ውይይቱ ተቋማት የት ላይ እንደሆኑ ለይተን ድጋፍ ለማድረግ የሚያስችል ግንዛቤ ለመያዝ ታስቦ የተካሄደ ነው ብለዋል። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መሪዎች በአሁኑ ጊዜ ቁርጠኝነት የሚፈልግ የለውጥ ሥራ እየሠራን እንደሆነ መገንዘብ እና በዚያው መጠን መፍጠን ያስፈልጋቸዋል ብለዋል። ተማሪዎችን ወደ ትምህርት የመመለስ ሂደት ባለድርሻ አካላትን በተገቢው መንገድ የማቀናጀት ኃላፊነት ተወስዶ መሠራት ያለበት ጉዳይ ነውም ብለዋል።

    ተማሪዎችን ከመመለስና የኮቪድ-19 ለይቶ ማቆያ ቦታዎችን ከማዘጋጀት አንፃር የፌደራልም ሆነ የክልል መንግሥታት እያንዳንዱ የራሱን ኃላፊነት ወስዶ እንዲሠራ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሥራት ያስፈልጋል ሲሉ ገልፀዋል። እንደከፍተኛ ትምህርት ዓለም-አቀፋዊና ሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ ትኩረት እናደርጋለን። ምርምር ላይ የተገኘውን እውቀት ተጠቅመን ለሀገር የሚውል አድርገን መጠቀምም ይገባናል ብለዋል።

    ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ ሥራውን በማስፈፀም ሂደት ኃላፊዎች የግንኙነት (communication) ክፍተት እንዳይኖር በመነጋገር ሊሠሩ እንደሚገባ ጠቁመው አመራር የሁሉ ነገር ቁልፍ እንደመሆኑ በጋራ መሥራት ያስፈልጋል ብለዋል።

    ነገ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በጉዳዩ ላይ እንደሚወያይና ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ይጠበቃል የተባለ ሲሆን፤ ከዚያም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ተቋማቱን ለመክፈት ያበቃሉ ተብለው የተቀመጡ ዝርዝሮችን በመያዝ በዩቨርሲቲዎች በመገኘት ብቁ መሆን አለመሆናቸው ታይቶ አስፈላጊውን መስፈርት ካሟሉ ብቻ እንዲከፍቱ ይደረጋል ብለዋል – ዶ/ር ሳሙኤል።

    ተማሪዎችን መልሶ ለመቀበል በሚደረግ ቅድመ ዝግጅት ወደኋላ የቀራችሁ ዩኒቨርሲቲዎች ካላችሁ ፈጥናችሁ ዝግጅታችሁን አጠናቅቁ ብለው መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን፤ ጉዳዩንም እንደፕሮጀክት ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንዳለባቸው አስበዋል።

    ከተሳታፊዎች የተለያዩ ስጋት ናቸው ተብለው የተነሱ ጉዳዮች ተነስተው ውይይት የተደረገባቸው ሲሆን በሂደት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሆኖ ለመፍታት እንደሚሠራ ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን መቀበል

    Anonymous
    Inactive

    አዲስ አበባ በራሷ ግዛተ-መሬት ላይ የፌዴራል አድያምነት /ክልልነት/ መብት ሊረጋገጥላት ይገባል!
    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ

    የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አወቃቀር በመመዘኛዎቹ ላይ በኢትዮጵያ ተፃራሪ አቋም ባላቸው ልሂቃን ዘንድ ስምምነት ላይ ሊደርስ ቢችል፣ ፌዴራላዊ የመንግሥት አደረጃጀት የፖለቲካ አለመግባባት መንስ ዔ ሊሆን የሚችል አልነበረም። ይህ ጥያቄ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ችግር ዋነኛ መገለጫ ሊሆን የበቃው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ልሂቃን በዚህ ጥያቄ ዙሪያ ላለፉት ሃምሳ ዓመታት ሊግባቡ ባለመቻላቸው ነው። ሊግባቡ ያልቻሉበትም ምክንያት በኢትዮጵያ ሀገረ-መንግሥት የግንባታ ታሪክ ላይ ልዩነታቸውን ማጥበብ ባለመቻላቸው ነው። ይህ ትውልድ ደግሞ በአጼ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት በ1940ዎቹ ዓመታት ተወልዶ በ1950ዎቹ መጨረሻና በ1960ዎቹ መጀመሪያ ላይ ለዩኒቨርሲቲ ደረጃ የደረሰው ትውልድ ነበር። እንደ አጋጣሚ ሆኖ በ1960ዎቹ ሁኔታ ደግሞ ዓለም በሁለት ተፃራሪ የካፒታሊዝምና የሶሻሊዝም ጎራዎች ፉክክር ተቀስፋ ተይዛ የነበረችበት ወቅት ነበር። በ1960ዎቹ ለጉልምስና ከደረሰው ትውልድ ውስጥ አብዛኛው ነው ባይባልም ተራማጅ የሆነ አስተሳሰብ አለኝ ብሎ ያቀነቅን የነበረው የትውልዱን የአመራር ሚና የተጫወተው የማርክሲዝም ሌኒኒዝም (Marxism–Leninism) አስተምህሮ የተቀበለው ነበር።

    ይሁንና የዚህ የ1960ዎቹ የተማሪ አብዮተኞች እና የ እ ነሱ ከፊል ውጤት ሆነው ያቆጠቆጡት የነገድ ድርጅት መሪዎች የኢትዮጵያን ታሪክ በተፃረረና ባልተገናዘበ ሁኔታ የሶቭየት ሕብረትን የኮሚኒስት ፓርቲ መሪ የስታሊንን “የብሔርና የቅኝ ግዛት ጥያቄ” መጽሐፍ ቃል በቃል በመገልበጥ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ዋነኛ ችግር “የጨቋኝና የተጨቋኝ ብሔረሰቦች መስተጋብር ነው” የሚል የሀሰት የታሪክ ትርክት ይዘው ተነሱ። እነዚህ ከተማሪ አብዮተኝነት ወደ ነገድ ድርጅትነት የተሸጋገሩት ከደርግ መንግሥት ጋር ለ17 ዓመታት ጦርነት አድርገው በታሪካዊ የኢትዮጵያ ጠላቶች ያላሰለሰ ድጋፍ በ1983 ዓ.ም በኢትዮጵያ ጦር ላይ ድል ሊቀዳጁ በቁ። አነዚህ ኃይሎች በተጠናወታቸው “የጨቋኝና የተጨቋኝ ብሔረሰቦች” የሀሰት ትርክት ውጤት የሆነውን የመገንጠል መብት ሕገ-መንግሥታዊ መብት ያደረገ፣ ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ ያለመ ቋንቋን መሠረት ያደረገ መንግሥታዊ የፌዴራል አወቃቀር በኢትዮጵያ ላይ አነበሩ።

    በሀገራችን ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ የጐሳና የዘረኝነት ፖለቲካዊ አደረጃጀት የመንግሥት የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ አደረጃጀት ዓይነተኛ መገለጫ ከመሆን አልፎ ይኸው ዓይነት አደረጃጀት  ወደ እምነት ተቋማት ሳይቀር ዘልቆ እንዲገባ ተደረገ። በሀገሪቱ ታሪክ በማይታወቅ ሁኔታ በተረኝነት መንፈስ የተቃኘ ተቋማዊ/መንግሥታዊ ሙስና እና የፍትህ መዛባት የሥርዓት መገለጫ ሊሆን በቃ። ከሕዝቡ ታሪካዊ አሠራር ጋር ባልተገናዘቡ የክልል አደረጃጀቶች ምክንያት በሀገራችን እንግዳ በሆነ መልኩ ማንነትን እና እምነትን መሠረት ያደረጉ ግጭቶች እንዲበራከቱ፣ ሕዝብ የተረጋጋ ሕይወት እንዳይኖረው በፌዴራል መንግሥቱና በክልል መንግሥታት መካከል የኃላፊነትና የተጠያቂነት ጉዳይ አሻሚ በማድረግ፣ የሀገሪቱ ብሔራዊ ስሜት እንዲላሽቅ በምትኩ ጠባብና ክልላዊ አስተሳሰብ እንዲሰፍን ተደረገ። በኢትዮጵያ የዘውግ ፌዴራሊዝም ሥርዓት ችግር ብሔረሰብን ዋነኛው የፌዴራል ሥርዓቱና የሀገር መንግሥት ግንባታ መሠረት ማድረጉ ነው።

    እዚያው ተወልዶ ያደገውና ከአራቱም የኢትዮጵያ ማዕዘናት የመጣውን የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ አንድ ብሔረሰብን እና አንድ ቋንቋ ተናጋሪነትን መሠረት አድርጎ በተዋቀረ ክልል ውስጥ አስገብቶ እንዲተዳደር ማድረግ  ፍትሃዊነት የለውም። የአዲስ አበባ ሕዝብ ጥያቄ ከራሴ ውጭ በእኔ ዕጣ ሌላ ሊወስንብኝ አይገባም የሚል ነው። አዲስ አባባ በኦሮሚያ ምድረ ፅፋዊ (geographic) ክልል ውስጥ በመገኘቷ ብቻ ለአዲስ አበባ ባለቤትነት የመብት መብለጫ፣ ለተፈጠረ ውጥንቅጥ ደግሞ የአዲስ አበባ ሕዝብን መብት ማሳነሻ ማድረግ በምንም መመዘኛ ተገቢነትም ሆነ ተቀባይነት የለውም።

    የኢፌዲሪ ሕገ-መንግሥት በአንቀጽ 69 “የፌዴራሉ መንግሥት ርዕሰ ከተማ አዲስ አበባ ነው። የከተማው አስተዳደር ራሱን በራሱ የማስተዳደር ሙሉ ሥልጣን ይኖረዋል። ዝርዝሩ በሕግ ይወሰናል” ይላል። የአዲስ አበባ ከተማ ራሱን በራሱ የማስተዳደር ሙሉ ሥልጣን እንዳለው ቢታወቅም የህወሓት እና የኦነግ በሆነው ሕገ-መንግሥት ውስጥ “በአዲስ አበባ ከተማ የኦሮሚያ ክልል ልዩ ጥቅም ይኖረዋል” በሚል መካተቱ ችግሩን ሆን ተብሎ እንዲወሳሰብ አድርጎታል።

    በ1989 ዓ.ም የወጣው የአዲስ አበባ ከተማ አስተደደር ማቋቋሚያ ቻርተር መሠረት አዲስ አበባ ራሷን በራሷ እንድታስተዳድር ሲደነገግ፣ በሕገ-መንግሥቱም ሆነ በአዲስ አበባ ከተማ ቻርተር መሠረት የከተማዋ ስምና ስያሜ አዲስ አበባ እንደሆነ ተደንግጓል። ይሁንና ቻርተሩን መሠረት በማድረግ ተዘጋጅቶ የቀረበው ረቂቂ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ የመጽደቅ ሂደቱ በደባ እንዲቀር ተደርጓል። አዲስ አበባ እንደ ዋሽንግተን ዲሲ እና እንደ ካንቤራ (Washington, DC and Canberra) የፌዴራል መንግሥት ግዛት ናት የሚል የሕግ አንቀጽ የለም። ይህ አይደለም እንዳይባል በወንጀልም ሆነ በፍትሀ-ብሔር ጉዳይ በአዲስ አበባ የግዛት ክልል ውስጥ የተፈፀመ ወይም የተከናወነ የሕግ ጥሰት ግን ልክ የፌዴራል መንግሥት ይዞታ አንደሆነችው ዋሽንግተን የመዳኘት ሥልጣንን ለፌዴራል መንግሥቱ ይሆን ዘንድ በሕግ ተለይቶ ተሰጥቷል። ማለትም በተግባር የፌዴራል መንግሥቱ አዲስ አበባን እና ድሬደዋን የራሱ ግዛት አድርጓቸዋል።

    ሕገ-መንግሥቱ አዲስ አበባ እራሱን የማስተዳደር ሙሉ ሥልጣን የሰጠው መሆኑ ከላይ የተጠቀሰው የወንጀልና የፍትሀ-ብሔር ጉዳዮችን ለመዳኘት ከተሰጠው ሥልጣን ጋር ሲዳመር አዲስ አበባ ልክ እንደ ዋሽንግተን የፌዴራል ግዛት እንደሆነች ለመረዳት ይቻላል። በተጨባጭ ግን አዲስ አበባ ከተማ የተተወላት የከተማ-ነክ አስተደደርና ከማዘጋጃ ቤት አገልግሎት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን የመዳኘት ሥልጣን ነው። ማለትም ስለ ዳኘነት ሲሆን መሬቱ የፌዴራል መንግሥት፣ ስለ ሌሎች አስተዳደራዊ ጉዳዮች ሲሆን የከተማ መስተዳድሩ ሆኗል።

    አዲስ አበባ ራሷን የማስተዳደር መብት በሕገ-መንግሥቱ የታወቀ ቢሆንም፤ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ጭምር ኢ-ፍትሀዊ በሆነ መንገድ ውክልና የላትም። ሕገ-መንግሥቱ ከሚደነገገው ውጭ ስትደዳደር የቆየችው በህወሓት/ኢህአዴግ፣ አሁን ደግሞ በኦህዴድ/ብልጽግና ነው። በሌሎች ክልሎች ክልሎችን የሚያስተዳድሩ የክልል ፓርቲዎች አሉ /ትግራይ፣ ኦሮሚያ፣ አማራ፣ ደቡብ ወዘተ…/ አዲስ አበባ ላይ ግን የሚወክላት የፖለቲካ ፓርቲ የለም። ገዥ ፓርቲዎች ፍላጎታቸውን የሚጭኑባት ከተማ ናት። ቀደም ሲል ህወሓት/ኢህአዴግ አሁን ደግሞ ኦህዴድ/ብልጽግና ፓርቲ አዲስ አበባን ማስተዳደሩን ቀጥሎበታል። ይህ ሁኔታ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በሕገ-መንግሥቱ የተሰጣቸውን ራሳቸውን የማስተዳደር መብት ፍፁም የሚጥስ ነው።

    አዲስ አበባን እንዲመራ የሚመደበው በገዢው ፓርቲ ውስጥ ከነበሩ ወይም ካሉ የክልል ገዢ ፓርቲዎች እንጂ በከተማው ሕዝብ ነፃ ምርጫ አልነበረም፤ አሁንም አይደለም። አዲስ አበባ ቀደም ሲል ከሁለቱ ክልሎች /ትግራይኦሮሚያ/ አሁን ከ “ለውጡ” ወዲህ ደግሞ ከኦሮሚያ ክልል በሚመጡ ተሹዋሚዎች እንድትደዳደር መደረጉ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ጥቅምና ፍላጎት እንዳይከበር ያደረገ የፖለቲካ ደባ ነው። ከዚህም ባሻገር ከ7 ሚሊዮን የሚልቀውን የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ በኢኮኖሚ እንቅስቃሴው በግብር መልክ በቢሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ለመንግሥት ካዝና የሚያስገባውን ነዋሪ የፖለቲካ ባይተዋር ያደረገ እና በዕጣ ፈንታው ላይ  እንዳይወስን ያደረገ ኢ-ፍትሀዊ የሆነ የፖለቲካ አካሄድ ነው። የአሜሪካን አብዮት እንደቀሰቀሰው /Taxation without Political Representation/ እንደሚለው መፈክር ሠርቶ ግብሩን እየገበረ የፖለቲካ ባይተዋር በማድረግ በዕጣ ፈንታው ላይ እንዳይወስን አድርጎታል። ይህ ፍትሀዊ ያልሆነ የፖለቲካ አካሄድ ከመሆኑም በተጨማሪ በግልጽ የሕገ-መንግሥቱን አንቀጽ 49 እና አንቀጽ 89 ይጥሳል።

    የኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት ትልቁ ወለፈንዲ የአዲስ አበባ ጉዳይ ነው። በአንቀጽ 69 መሠረት የአዲስ አበባ ከተማ የፌዴራሉ ርዕሰ ከተማ እና የከተማው ነዋሪ ሕዝብ እራሱን በራሱ የማስተዳደር መብት ይኖረዋል ሲል ደንግጓል። ማለትም፥ አዲስ አበባ የተወላጆቿና እና የሁሉም ከ80 በላይ የሆኑት የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች በባለቤትነት የሚኖሩባት ከተማ ናት። የአዲስ አበባን አስተዳደር ስንት አማራ፣ ስንት ኦሮሞ፣ ስንት ትግሬ፣ ስንት ጉራጌ፣ ስንት ወላይታ፣ ስንት ሱማሌ፣ ስንት አደሬ፣ ስንት ጋምቤላ፣ ስንት ቤንሻንጉል፣ ስንት ማኦ ወዘተ… እንደሚኖሩባት በተጨባጭ የተረጋገጠ አሃዛዊ መረጃ (statistics) ስለሌለ የአዲስ አበባ ባለቤትነት ሊሰጥ የሚችለው ከሕገ-መንግሥቱ መንፈስ ውጭ ለመላ ቋሚ ነዋሪዎቿ ነው ሊሆን የሚችለው። ይሁንና የአዲስ አበባን ከተማ ባለቤትነት በተመለከተ እንደ ሌሎች የፌዴራል መንግሥት ዋና ከተማዎች እንደሆኑት እንደ ሞስኮ፣ በርሊን፣ ቪየና እና ብራስልስ ለፌዴራል መንግሥት ተጠሪ ያልሆኑ፣ በኢትዮጵያም ከ1983 ዓ.ም ሰኔ ወር ጀምሮ ሕገ-መንግሥቱ ተግባራዊ እስከ ተደረገበት 1987 ዓ.ም ነሐሴ ወር ድረስ ክልል 14 ተብላ የክልልነት ደረጃ የተሰጠበትን ሁኔታ መልሶ ተግባራዊ ማድረግ  ፍትሃዊ እና የነዋሪዎቿን ሕጋዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ነው።

    አዲስ አበባ እንደ ፌዴራል መንግሥት ርዕሰ ከተማነቷ የግዛተ-መሬቷ ባለቤትነትን ለፌዴራል መንግሥቱ ሳይሆን በሽግግር ወቅት እንደነበረው በፌዴራል አድያምነት /በክልልነት/ ደረጃ እንደገና እንድትዋቀር ባልደራስ እውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ለከተማዋ ሕዝብ ጥሪውን ያቀርባል።

    ከሀገራችን ዘመናዊ የታሪክ ጅማሮ ጋር የተሰናሰለ እድሜ ያላት አዲስ አበባ ከተማ፥ በመልክ-ዕምድር አቀማመጧ የሀገሪቱ እምብርት ላይ መገኘቷ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታዋን የጎላ አድርጓታል። ይህ ሁኔታዋ ለሀገራችን ዜጎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ለመስጥ የሚያስችል አቅም ያላት ከተማ እንድትሆን ሰፊ ዕድል ሰጥቷታል። ነገር ግን ከተማዋ ያላትን ሰብዓዊና ቁሳዊ አቅም አሟጣ በመጠቀም ለነዋሪዎቿ ተስፋ መሆን እንዳትችል በሀገራቸን የነበሩ እና ያሉት ገዢዎች አተያይ እና የአመራር ፈሊጥ ትልቅ ተግዳሮት ሆኗል። “በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” እንዲሉ ጎሳን መሠረት ያደረገው የባለፉት 30 ዓመታት የሀገራችን ፖለቲካን ያነበረው ሥርዓት የአዲስ አበባ ከተማን ህልውና የበለጠ ተፈታትኖታል፤ ከባድ አደጋንም የፈጠረ ሆኗል።

    አዲስ አበባ የሀገራችን ርዕሰ መዲና ከመሆኗ ባሻገር፣ የአፍሪካ ሕብረት እና የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ተምሳሌትና መናኸሪያ፣ የትላልቅ ዓለም አቀፍ ተቋማት መታደሚያ ናት። የሀገራችን 65% ምጣኔ-ሀብት በአንበሳ ድርሻነት ይዛለች፤ በሀገሪቱ ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ቤተ-እምነቶች እና የእምነቱ ተከታዮች ተቻችለው የሚኖሩባት የአብሮነት መገለጫ ከተማ ስትሆን፥ የታሪካችን መገለጫ የሆኑ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርስ እና ትውፊት የተመዘገበባት፣ እንዲሁም የተለያዩ ቋንቋዎችና ባህሎች ሕብር ፈጥረው በነፃነት የሚንጸባረቁባት የኢትዮጵያ ብዝሃነት ማሳያ ፈርጥ ናት።

    ከተማችን አዲስ አበባ ባለፉት 3 አስርት ዓመታት ሲመሯት የነበሩት ሁሉ ምን ልጠቀምባት እንጂ ምን ላድርግላት የሚል ኃላፊነት የሚሰማቸው ባለመሆኑ ችግሮቿን የተወሳሰቡ አደርጎታል። እንደ ፓርቲያችን እምነት፥ ለዚህ ችግር በዋነኝነት ያጋለጣት በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ አስተዳድር ተሰይሞ ሊያስተዳድራት አለመቻሉ ጉልህ ስፍራ ይይዛል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርን በከንቲባነት ሲመሩ የቆዩት ግለሰቦች በአብዛኛው የከተማውን ነዋሪ ሥነ-ልቦና በቅጡ ያልተረዱ፣ ራዕይ-አልባ የሆኑ እና ከፍተኛ የብቃት ጉድለት የሚስተዋልባቸው ናቸው።

    አዲስ አበባ ከተማ ራስ ገዝ (በአሁኑ አጠራር ክልል) እንድትሆን መሆኑ እውነተኛ ፌዴራላዊ አስተዳደር በኢትዮጵያ ውስጥ ለማንበር በሚደረገው ጥረት ወሳኝ ሚና እንደሚኖረው ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ያምናል፤ በመሆኑም አዲስ አበባ ራስ ገዝ አስተዳደር እንዲኖረው በላቀ መንገድ መታገል አስፈላጊ ሆኗል።

    የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ ላለፉት ዘመናት በተለይም የህወሓት/ኢህአዴግ ሥልጣን ዘመን ጀምሮ በመረጠው የመተዳደር መብቱን ተነፍጎ፣ ከኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ኦህዴድ በውክልና ተቀብሎ አስተዳድራለሁ በሚል የተረኝነት፣ የሙስና፣ የባህል በአጠቃላይ የዘረኝነት ሰለባ ሆኗል። የተረኛነት ስሜት ነቀርሳ የሆነበት ኦህዴድ/ብልጽግና የአዲስ አበባን ሕዝባዊ አውቃቀር (demography) ከመቀየር ጀምሮ ተጠንቶ የከተማው ሕዝብ ባልመከረበት የትምህርት ሥርዓት ውስጥ ረጅም እጁን ሕገ-ወጥ በሆነ መንገድ በመስደድ፣ የከተማውን መሬት በማስወረር እና ነዋሪው ጥሮ ግሮ ቆጥቦ የሠራውን ቤት አንዴ ለኦሮሚያ የመንግሥት ሠራተኞች በሚል ሌላ ጊዜ ደግሞ የተለየ ምክንያት በመስጠት እየዘረፈ  መሆኑ የከተማዋን ነዋሪ በደል ጫፍ አድርሶታል።

    ዛሬ ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞካራሲ ፓርቲ ይህንን የዘመናት የአዲስ አበባ ሕዝብ ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ መብቱን የሚጠይቅበት ጊዜ ላይ መድረሱን ተገንዝቧል። በኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ፍትህ ማግኘት የሚቻለው የከተማው ነዋሪ ራሱ የመረጠው ሥርዓት ሲዘረጋ መሆኑን በቅርቡ ተረድቷል። አሁን እየደረሰበት ያለው ግፍ መነሻው ለሕዝብ ተጠያቂነት ያለው ትክክለኛ አስተዳደር አለመኖሩና ይህንን ተገን በማድረግ ወደ ዝርፊያ የገቡና ለዚሁ ሁኔታ እንዲያመቻቸው ብቻ የሚሠሩ የውክልና መሪዎች በመሆናቸው ከእነዚህ አስተዳደር ውጭ እንዲሆን ለማስቻል ዴሞክራሲን ለማስፈን እንዲረዳ ነው።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ አዲስ አበባ ከተማ ራስ ገዝ እንድትሆን ብዙ ዜጎች ጥያቄ ሲያነሱ እንደነበረ ያምናል። ይህ የከተማው ነዋሪ ጥያቄም፣ ፓርቲው እንዲመሠረት ገፊ ምክንያት እንደሆነ በመገንዘብ፣ ትላንት ዜጎች ሲያነሱት የነበረው ጥያቄ ወደላቀ ምዕራፍ መሸጋገሩን በማብሰር፤ የአዲስ አበባ ሁለንተናዊ ችግር አስጨንቋቸው እና እንቅልፍ ነስቷቸው ለነበሩ ዜጎች ሁላ ይህ የእናንተ የትላንትና የትግል ጥያቄ በመሆኑ ከፍ ያለ ምስጋና ይገባችኋል። የዜጎች በደልና ጭቆና እንዳንገበገባችህ እናምናለን፤ ይህንንም ለመቅረፍ በጋራ እንድንቀሳቀስ እንጠይቃለን።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ የከተማችንን ነዋሪ የሚመጥን አስተዳደር እንዲዘረጋ የሚያደርገው ጥረት፣ ከአንድ የፖለቲካ ድርጅት ጥያቄ በላይ እንደሆነ ያምናል። በመሆኑም በሀገራችን የምትገኙ የፖለቲካ ኃይሎች፣ ለከተማው ነዋሪ የራሱን ራስ ገዝ አስተዳደር እንዲመሠረት አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍና ትብብር እንድታደርጉለት፤ ምሁራን እና ታዋቂ ግለሰቦችም የሚመሠረተው አስተዳደር የሚያስፈልገውን ድጋፍና አወቃቀር በአግባቡ እንዲይዝ መልክ ለማስያዝ የሚረዳ ልምዳችሁን፣ እውቀታችሁን እንዲሁም ተፅዕኖ የመፍጠር አቅማችሁን እንድታበረክቱ ጭምር አደራ ይላል።

    በዋነኝነት የአዲስ አበባ ራስ ገዝ አስተዳደር ባለቤት ሁሉም የከተማው ነዋሪ እንደሆነ ባልደራስ በጽኑ ያምናል። ይህንንም ለማድረግ የሚያስችል ሕጋዊና ሰላማዊ ትግል በማድረግ የፌዴራል መንግሥት ጥያቄውን እንዲቀበልና በሀገሪቱ አሁን ባለው ሥርዓት መሠረት ሕዝበ-ውሳኔ ተካሂዶ የራስ ገዝ አስተዳደር (ክልል) እንዲሆን እንጠይቃለን። ይህንንም ጥያቄ እውን ለማድረግ እና በሕጉ አግባብ እንዲስተናገድ ለማድረግ የተከማው ነዋሪ የስምምነት ፊርማ የማሰባሰብ ሂደት ውስጥ ተሳታፊ እንዲሆን ጥሪ እናቀርባለን። ጥሪውም በነዋሪ ሕዝቧ ፍላጎት ላይ የተመሠረተ መሆኑን ለማስረገጥ ድጋፉን በፊርማ የሚያቀርብበት የአሠራር ዘዴ ይቀይሳል።

    በመጨረሻም ይህንን የጳጉሜን ሣምንት በግፍ ለታሰሩ የፓርቲያችን መሪ አቶ እስክንድር ነጋ፣ አቶ ስንታየሁ ቸኮል፣ ወ/ሮ ቀለብ ስዩም እና ሌሎች የፓርቲው አባላትና አመራሮች በግፍ ከታሰሩበት እንዲፈቱ በተለያዩ መንገድ ግፊት ለምታደርጉ ወገኖች ምስጋናችንን እያቀረብን፥ መንግሥት በማን አለብኝነት ያለኃጢያታቸው አስሯቸው የሚገኙ ንፁሃን መሪዎቻችንን እና አባላቶቻችንን በአስቸኳይ እንዲፈቱ በድጋሚ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

    መጪው የኢትዮጵያ አዲስ ዓመት፣ ከኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ስጋት ተላቀን በሰላም ወጥተን የምንገባበት፣ ለሀገራችን ዜጎች ሰብዓዊ መብት የሚከበርባት፣ ለተበደሉ ፍትህ የሚሰፍንበት፣ ዴሞክራሲ የሚያብብበት እንዲሆን እንመኛለን፤ ለብሔራዊ መግባባት ሁሉም የፖለቲካ ወገኖች አንድ ላይ ተቀምጠው ስምምነት ላይ የሚያደርስ ተጨባጭ ሥራዎች የምናከናውንበት ዘመን እንዲሆን መልካም ምኞቱን ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ይገልጻል።

    ድል ለእውነተኛ ዲሞክራሲ!
    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ)
    ጳጉሜ 3 ቀን 2012 ዓ.ም

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ

    Anonymous
    Inactive

    ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ድርጅታዊ ህልውና ባገኘባቸው ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ የአማራ ሕዝብ እውነተኛ ድምፅ በመሆን ሕዝባችንን ከህልውና ስጋት ለመታደግ፣ አንድነቱን ለማረጋገጥና ጥቅሞቹን ለማስጠበቅ የተቀጣጠለውን ንቅናቄ ጠንካራና የማይቀለበስ መሠረት በማስያዝ ረገድ የበኩሉን አስተዋጽዖ አድርጓል። የአማራውን ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ምጣኔ ሀብታዊ ጥያቄዎች ከፍ አድርጎ በመያዝና ለነፃነት፣ ለፍትህና ለእኩልነት የሚደረገውን ትግል በመምራት ሕዝባዊ አመኔታን ለማትረፍ ችሏል።

    አብን ጠንካራ ኢትዮጵያዊ ርእይ የሰነቀ ንቅናቄ በመሆኑ በሀገራዊ የሽግግር ሂደት ውስጥ አዎንታዊ ሚና ለመጫወት ከፍተኛ ጥረት አድርጓል። አማራው በታላቅ መስዕዋትነት ያስገኘው ለውጥ መስመሩን እንዳይስት፣ በትግላችን የተንበረከኩ ጠላቶች መልሰው እንዳያንሰራሩ፣ የፈነጠቀው የለውጥ ተስፋ እንዳይጨነግፍና ዳግም የሀገራችንና የሕዝባችን ህልውና አደጋ ላይ እንዳይወድቅ ያላሰለሰ ትግል ሲያደርግ ቆይቷል።

    ይሁን እንጂ ጥረቶቻችን እንደሚጠበቀው ያህል ፍሬ ከማፍራት ይልቅ እየመከኑና የሀገራዊው የፖለቲካ አውድ ከጊዜ ጊዜ ተስፋ አስቆራጭ እየሆነ መምጣቱን የሚጠቁሙ በርካታ ምልክቶችን አስተውለናል። ንቅናቄያችን በዚህ ረገድ በአማራ ሕዝብና በኢትዮጵያ ላይ ያንዣበበውን ጽኑ አደጋ በሚያሳዩ ሦስት አበይት ጉዳዮች ላይ ያለውን አቋም በግልፅ ለማሳወቅ ይሻል።

    1. በአማራ ሕዝብ ላይ የሚፈፀሙ በደሎችና የዘር ጥቃቶችን በተመለከተ፦

    አብን በሀገራችን በየትኛውም ክፍል፣ በማናቸውም ኃይልና በየትኛውም ሕዝብ ላይ የሚፈፀሙ የሽብርና የዘር ጥቃቶችን ያለማመንታት አውግዟል። የጋሞ ተወላጆች በቡራዩ በግፍ ሲጨፈጨፉ፣ የአዲስ አበባ ወጣቶች ታፍሰው ወደ ጦር ካምፕ ሲጋዙ፣ የጌዴዖ ወገኖቻችን ሰብዓዊ እርዳታ ተነፍገው በርሀብ ሲረግፉ፣ ቤተ እምነቶች በእሳት ሲጋዩና አማኞች በጭካኔ ሲታረዱ ድምፃችንን ከፍ አድርገን ለኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝብ እንዲሁም ለዓለም ማኅበረሰብ በማሰማት ዜጎች ከጥቃት እንዲጠበቁና ሰብዓዊ መብቶቻቸው ተከብረው እንዲኖሩ ጥረት አድርገናል።

    በተለይ በኦሮሚያ ክልል በተደጋጋሚ የተከሰቱትን ማንነትና እምነት ተኮር የዘር ማፅዳት፣ የዘር ፍጅትና ሰብዓዊ ወንጀሎችን ለመከላከልና ለማስቆም ሰፊና ያላሰለሰ ትግል አድርገናል። ዜጎች በአማራነታቸው ተመርጠው ቤታቸው ሲፈርስና ሲፈናቀሉ፣ አማራ ተማሪዎች ከኦሮሚያ ክልል ዩኒቨርሲቲዎች በዘር ጥቃት ተገደው ሲለቁና እገታ ሲፈፀምባቸው፣ በኦሮሚያና በሌሎች ክልሎች በሚኖረው ሕዝባችን ላይ የዘር ማጽዳትና ሰብዓዊ ወንጀሎች ሲፈጸሙ ከማውገዝና ማዕከላዊና ክልላዊ መንግሥታት ጥቃቶቹን በአስቸኳይ እንዲያስቆሙ ግፊት ከማድረግ ባለፈ አደጋውን አስቀድሞ መከላከልና ማስቀረት በሚቻልበት መንገድ ላይ ሰፊና የተቀናጁ ጥረቶችን ስናደርግ ቆይተናል።

    በዚህ ረገድ ንቅናቄያችን ካደረጋቸው በርካታ ጥረቶች መካከል ለአብነት ሚያዚያ 29 ቀን 2012 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል የሽብር ኃይሎች ማንነት ተኮርና በተለይም አማራውን ዒላማ ያደረጉ የዘር ጥቃቶች ሊፈፅሙ እንደሚችሉ ከሁኔታዎች ጥናት በመተንበይ ለዚህ ማዕከላዊ መንግሥቱ ልዩ ቅድመ ዝግጅት እንዲያደርግ በአካል ለሀገሪቱ ከፍተኛ መሪዎች ከማስረዳት ባለፈ በመግለጫ ጭምር በአንክሮ ማሳሰቡ ይታወሳል።

    1.1. ከሰኔ 22 ለሊት እስከ ሰኔ 25 ቀን 2012 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል የተደረገው የዘር ማጥፋት፦

    መንግሥት ተቀዳሚ የሆነውን ሰላምና ደኅንነት የማሰከበር ኃላፊነቱን በአግባቡ ሊወጣ ባለመቻሉ የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ሽፋን በማድረግ ጽንፈኛ ኃይሎች ጥምረት ፈጥረውና ተዘጋጅተው በኦሮሚያ ክልል በሚኖሩ በዋነኝነት በአማሮች ላይ፣ በተጓዳኝም በኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ላይ ከሰኔ 22 ሌሊት እስከ ሰኔ 25 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ በሽፋኑም ባስከተለው ሰብዓዊና ቁሳዊ ውድመትም እስከዛሬ ከታየው እጅግ ሰፊና አሰቃቂ የዘር ጥቃት ፈፅመዋል።

    አብን ይህን መረን የለቀቀ የዘር ማጥፋት ድርጊት በወቅቱ ከማውገዝ ባሻገር ጭፍጨፋው በተፈፀመባቸው አካባቢዎች የጥናት ቡድን ልኮ በደረሰው ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳት ላይ ዝርዝር መረጃዎችን በማሰባሰብና በማጠናቀር ሰነድ አዘጋጅቷል። ሰነዱ በአማርኛና በእንግሊዝኛ ቋንቋዎች ተዘጋጅቶ ለሚመለከታቸው የሀገር ውስጥና ዓለማቀፍ አካላት በተለይም ለዲፕሎማቲክ ማህበረሰቡ ፣ ለሰብአዊ መብት ተቋማትና ለአማራ አደረጃጀቶች እየተሰራጨ ሲሆን ፣ ንቅናቄያችን የዘር ፍጅቱ እውቅናና ትኩረት እንዲያገኝና ፍትህ እንዲረጋገጥ ቀጣይ እርምጃዎችን የሚወስድ ይሆናል።

    ሀ. የጥፋቱ አድማስ፦

    ንቅናቄያችን ያደረገው ጥናት በወቅቱ በኦሮሚያ ክልል ከተፈፀመው ሰፊ የዘር ጥቃት ውስጥ በስድስት ዞኖች በሚገኙ በ26 ከተሞችና አካባቢዎች የደረሰውን ያካትታል። በምሥራቅ ሸዋ ዞን ደብረዘይት፣ ናዝሬት፣ መተሐራ፣ ዝዋይ፣ አዳሚ ቱሉ፣ ቡልቡላ፣ መቂ ከተሞችን፤ በምዕራብ አርሲ ዞን ሻሸመኔ፣ አርሲ ነገሌ፣ አሳሳ፣ ዶዶላ ከተሞችን፤ በምሥራቅ ሃረርጌ ዞን ሃረማያ፣ ባቴ፣ ከምቦልቻ፣ ጉርሱም ከተሞችን፤ በሃረማያ ወረዳ ኦዳ በሊናና መልካ ገመቹ አካባቢዎችን፤ በጃርሶ ወረዳ አሌ ከተማን፣ ሚደጋ ቶላ ወረዳን፤ በባቢሌ ወረዳ የተለያዩ ስፍራዎችን፤ እንዲሁም በሃረሪ ክልል ሃረር ከተማን፤ በምዕራብ ሃረርጌ ዞን ጭሮ ወይም አሰበ ተፈሪ፣ ሚኤሶ፣ አሰቦት ከተሞችና አካባቢዎችን፤ በምዕራብ ሸዋ ዞን በተለይም ወሊሶ፤ በጅማ ዞን በጅማ ከተማ የደረሱትን የዘር ጥቃቶች ያካትታል።

    በጥቃቱ ከወደመው ሀብትና ንብረት መካከል 378 መኖሪያ ቤቶች፣ 111 ከብቶችና በርካታ የእርሻ ማሳዎች፣ የእህልና የሸቀጣሸቀጥ ክምችቶች፤ ከ300 በላይ ከአነስተኛ እስከ ከፍተኛ የንግድ ድርጅቶችና ህንፃዎች፣ 189 ሆቴሎችና ፔንሲዮኖች፣ 5 ትምህርት ቤቶች፣ 15 መድሃኒት ቤቶችና የህክምና ተቋማት፣ 8 ባንኮችና የኢንሹራንስ ተቋማት፣ 117 የተለያዩ ተሸከርካሪዎች ተዘርፈዋል፤ ተሰባብረዋል፤ በእሳት ተቃጥለዋል። አብያተ ክርስቲያናት፣ የእምነት መገልገያዎችና ታሪካዊ ቅርሶች ሳይቀር የጥቃቱ ሰለባ ሆነዋል። በተፈፀመው እጅግ ከፍተኛ ጥቃት በብዙ ቢሊዮን ብር የሚገመት ሀብትና ንብረት ወድሟል።

    አብን በተጨባጭ መረጃና ማስረጃ ባጠናቀረው ዘገባ ግኝት መሠረት ከሰኔ 22 ለሊት እስከ ሰኔ 25 ቀን 2012 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል የተፈፀመው ጥቃት ዓለምአቀፍ የዘር ማጥፋት መስፈርቶችን የሚያሟላና የማያሻማ የዘር ማጥፋት ድርጊት መሆኑን ያምናል።

    ጥቃቱ በዘርና በእምነት ላይ የተመሠረተ በመሆኑ ‹‹ነፍጠኛ›› እና ‹‹የነፍጠኛ ኃይማኖት›› በሚል የዘር ፍጅት መለያ በዋነኝነት በተጠቀሱት ዞኖች የሚኖሩትን በሚሊዮን የሚቆጠሩ አማሮችን ዒላማ ያደረገ ነው። ሙስሊም አማሮችም የጥቃቱ ሰለባ ሆነዋል። የኦርቶዶክስ ኃይማኖት ተከታይ ኦሮሞዎችና ሌሎችም ኢትዮጵያውያን ለጥቃት ተዳርገዋል።

    በዚህ የዘር ማጥፋት ጥቃት ከ200 በላይ አማሮች በአሰቃቂ ሁኔታ በሜንጫ፣ በዱላና በድንጋይ እየተጨፈጨፉ ሕይወታቸው አልፏል።

    በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ የጥቃቱ ሰለባዎች ከቀላል እስከ ፅኑ አካላዊ ጉዳት ደርሶባቸዋል። በጥቂቱ ከ20 ሺህ የሚበልጡ ወገኖችም አስቸኳይ የእለት እርዳታ ፈላጊ ሆነው ሜዳ ላይ ተጥለዋል።

    የአማሮች ሀብትና ንብረቶች እየተመረጡ በመውደማቸው ጥቃቱ በተፈፀመባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች ሆን ተብሎ የህይወት ዋስትና እንዲያጡ ተደርገዋል። ችግሩ በነዚህ አካባቢዎች ብቻ የሚወሰን ሳይሆን በመላው ኦሮሚያ የሚኖሩ ወደ 15 ሚሊዮን የሚጠጉ አማሮችና ኦርቶዶክስ አማኞችን ለከፍተኛ የህልውና ስጋትና ሥነ-ልቡናዊ ጉዳት ዳርጓቸዋል።

    ለ. የጥፋቱ ተዋንያን፦

    በሁሉም አካባቢዎች ጥቃቱን በተቀናጀ ሁኔታ በመምራት፣ በማስተባበርና በመፈፀም በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል። በተለይ በኦሮሞ ፅንፈኛ የፖለቲካ ቡድኖች፣ ድርጅቶችና ታዋቂ ግለሰቦች ሳይቀር ‹‹ቄሮ›› በሚል ስም የተደራጁ ወጣቶች ዋነኛ የጥቃት ኃይሎች ነበሩ።

    እነዚህ ቡድኖች ከአንዱ ከተማ ወደ ሌላው አቅራቢያ ከተማ ወይም ከገጠር ቀበሌዎች ወደ ከተማ እየተሰማሩ የሚያጠቁ ፣ በከተማው የሚገኙ ዒላማ የተደረጉ ሰዎችን ቤቶችና ንብረቶችን ዝርዝር የያዙ ጠቋሚዎች በቅንጅት የሚሰሩበት ነው። ለንብረቶች ማቃጠያ ቤንዚንና መሰል ግብአቶችንም የሚያቀርቡ ነበሩበት።

    በተለያዩ ደረጃ ያሉ የመንግሥት ኃላፊዎች፣ የክልሉ የፀጥታ መዋቅር አመራሮችና አባላት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በጥቃቱ ከመሳተፋቸውም በላይ ጭፍጨፋውን ለማስቆም ፍላጎት አጥተው ቆመው መመልከታቸውንም ከፍጅቱ የተረፉ እማኞች አስረድተዋል። የፌዴራል መከላከያ ሰራዊት አመራሮችም እንደ ሻሸመኔና አርሲ ነገሌ ባሉ አካባቢዎች ለቀረበላቸው የድረሱልን ጥያቄ ‹‹ከበላይ ትዕዛዝ አልተሰጠንም›› በሚል ለእርዳታ አልተገኙም።

    የዘር ፍጅቱን ተከትሎ የኦሮሚያ ክልልም ሆነ የፌዴራሉ መንግሥት ወንጀሉን በስሙ በመጥራት ወንጀለኞችን ለሕግ ከማቅረብ ይልቅ ድርጊቱን ተራ ግጭት በማስመል ወደ ማስተባበል ገብተዋል። ከዘር ፍጅቱ የተረፉ ተጠቂ ወገኖችንም በተገቢው ሁኔታ በማቋቋም ረገድ ዳተኝነት ይስተዋላል።

    1.2. የአብን አቋም፦

    በአጠቃላይ አብን በጥናቱ ባረጋገጠው መሠረት በኦሮሚያ ክልል የተደረገው የዘር ማጥፋት ተገቢውን ትኩረት ያለማግኘቱና ችግሩን በአጭር ጊዜም ይሁን በዘለቄታ ለመፍታት የሚታየው ዳተኝነት ፓርቲያችንን ክፉኛ ያሳስበዋል። ስለሆነም፦

    ሀ) የተፈፀመው ወንጀል የዘር ማጥፋት መሆኑ ታምኖበት በስሙ እንዲጠራና ለተፈፀመው ወንጀልም ይፋዊ ይቅርታ እንዲጠየቅ፤

    ለ) መንግሥት የተፈፀመውን የዘር ፍጅት የሚያጣራና የሚመረምር ልዩ የምርመራ ኮሚሽንና አቃቤ ሕግ ጽ/ቤት እንዲያቋቁምና ወንጀለኞች የሚዳኙበት ልዩ ችሎት እንዲሰይም፤

    ሐ) መንግሥት በንፁሃን ዜጎች ላይ የተፈፀመውን አሰቃቂ ወንጀል የሚዘክር ቋሚ መታሰቢያ እንዲያቆም፤

    መ) ችግሩን በዘለቄታ ለመፍታት በክልሉ በሚኖሩ የተለያዩ ማህበረሰቦችና ሕዝቦች መካከል የእርቅና የመግባባት ስራዎች እንዲጀመሩ ፤

    ሠ) የኦሮሚያ ክልልም በክልሉ ለሚኖሩ ኦሮሞ ያልሆኑ ማህበረሰቦችና ሕዝቦች ሰብአዊና ህገ መንግሥታዊ መብቶቻቸው የሚከበሩበት ዋስትና እንዲሰጥ ፤

    ረ) መንግሥት የዘር ፍጅቱን በመዘገባቸው ምክንያት ያሰራቸውን የአስራት ሚዲያ ጋዜጠኞች ያለምንም ቅድመሁኔታ በአስቸኳይ እንዲለቅ አብን ይጠይቃል።

    2. በአዲስ አበባ የሚፈፀሙ ወንጀሎችና ብክነቶችን በተመለከተ፦

    ፓርቲያችን አብን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና በፌዴራል መንግሥቱ በከተማዋ ውስጥ የሚፈፅሙትን ወንጀሎች ፣ ሙስናና ብክነቶች የሚመረምር ቡድን በማቋቋም ሰፊ ጥናት እያካሄደ ይገኛል። ከዚህ ጥናት የተገኘ መረጃን መሠረት በማድረግ በከተማዋ ከፍተኛ ሕገ-ወጥ የመሬት ወረራ፣ ተቋማትን በአንድ ብሔር ተወላጆች የመሙላት፣ ሕገ-ወጥ የመታወቂያ እደላና በርካታ ተያያዥ ወንጀሎች እንደተፈፀሙ አረጋግጧል። ይህም በተለይ ከሰኔ 2011 ወዲህ እጅግ የተባባሰ እንደነበር ተገንዝቧል።

    2.1. ሕገ-ወጥ ወረራ፣ ሰፈራና ማፈናቀል

    የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በአንጡራ ሃብታቸው ያቆሙት ጎጇቸውና ድርጅቶቻቸው ያለርህራሄና ያለሕግ አግባብ የሚፈርሱባትና ዜጎች ሜዳ ላይ የሚወረወሩበት፤ ከፊሎች ደግሞ በዘር፣ በፖለቲካ ወገንተኝነትና በጥቅም ትስስር በገፍ መሬት የሚቸራቸው፤ የከተማዋ ነዋሪ ከእለት ጉርሱ ቀንሶ የገነባው የጋራ መኖሪያ ቤት በልዩ መብት የሚታደላቸው ከተማ ሆናለች።

    አብን በከተማዋ የሚፈፅሙትን ሕገወጥነቶች ከማውገዝና በተለያዩ መድረኮችና መገናኛ ብዙሃን አማካኝነት ከማጋለጥ ባሻገር አቅም በፈቀደ መጠን የሰብአዊ ርዳታዎችን በማቅረብ ኢትዮጵያውያን ወገኖችን ለመታደግ ጥረት አድርጓል። መላው ሕዝባችን በተለይም ለሕዝብና ለሀገር ጥቅሞች ፣ መብቶችና ፍላጎቶች ቆመናል የሚሉ የፖለቲካ ኃይሎች ከንቅናቄያችን ሀገርን የማዳን ታሪካዊ ጥሪ ጎን እንዲቆሙ ወትውተናል።

    ከዚህም ባለፈ ንቅናቄያችን ጉዳዩን ትኩረት ሰጥቶ በማጥናት ለሀገሪቱ ከፍተኛ የመንግሥት አካላት በተደጋጋሚ አቤት ብሏል። ታህሳስ 2 ቀን 2011 ዓ.ም በብሔራዊ ቤተመንግሥት በመገኘት ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከታቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አሕመድ ጋር እስከመወያየት ደርሷል። በወቅቱም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ችግሮች መኖራቸውን በማመን አስቸኳይ መፍትሔ እንደሚበጅላቸው ቃል ቢገቡም አንዳችም ሳይደረግ አሁን ካለንበት ሁኔታ ላይ ተደርሷል።

    ሰለዚህም የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ይህ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ በአስቸኳይ መፍትሄ ካላገኘ ፅኑ ብሔራዊ ቀውስ የሚፈጥር በመሆኑ፦

    ሀ) አዲስ አበባ ላይ የተፈፀመውን ሁሉንአቀፍ ወረራ በተመለከተ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ጨምሮ ሌሎች የሚመለከታቸውን ባለድርሻ አካላት ያካተተ አንድ አጣሪ ኮሚቴ እንዲቋቋም፤

    ለ) ባለፉት ሁለት ዓመታት የነበረውን የመሬት አስተዳደርና ማስተላለፍ፣ የመታወቂያ አወጣጥ፣ የቅጥርና ዝውውር እንዲሁም ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን እንዲያጣራ/ኦዲት እንዲደረግ፤

    ሐ) በኦዲት ግኝቱ በሚመጣው መሠረት ጥፋተኛ ሆነው የሚገኙ ሁሉም አካላት ለፍትህ እንዲቀርቡ፤

    መ) በኦዲት ግኝቱ ለተለዩ ጉድለቶች አጣሪ ኮሚቴው በሚያቀርበው ምክረ ሐሳብ መሠረት የማስተካከያ የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ፤ እንዲሁም

    ሠ) ምርጫ ተካሂዶ ቅቡልነት ያለው ሕጋዊ የከተማ አስተዳደር ምክርቤትና ካቢኔ እስኪዋቀር ድረስ አሁን ያለው የሽግግር አስተዳደር ዘላቂ ውጤት ሊኖራቸው ከሚችሉ ውሳኔዎች እንዲታቀብ፤ አብን ጥሪውን ያቀርባል።

    2.2. ሜጋ ፕሮጀክቶችን በተመለከተ፦

    ፓርቲያችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በጠቅላይ ሚኒስቴር ፅ/ቤትና በከተማ አስተዳደሩም በኩል የሚሰሩ ዋና ዋና 15 ሜጋ ፕሮጀክቶችን ሁኔታ በንቃት በመከታተል ስለፕሮጀክቶቹ ዝርዝር መረጃዎችን ሲያሰባስብ ቆይቷል።

    በዚህም መሠረት በጀታቸው/ወጪያቸው የታወቁ ፕሮጀክቶች የገንዘብ መጠን በአጠቃላይ 5.737 ቢሊዮን ዶላር (ወቅታዊ ምንዛሪው ከ212 ቢሊዮን ብር በላይ) እና ተጨማሪ 59.2 ቢሊዮን ብር በአንድ ላይ ወደ 271 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ እንደሆነ ተረድቷል። በጀታቸው ካልታወቁ ጋር ሲደመር ከዚህ ከፍተኛ መሆኑ አያጠራጥርም።

    አዲስ አበባ ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ ከተማ እንድትሆን የሚደረገውን መንግሥታዊ እንቅስቃሴ በመርኅ ደረጃ አብን ይደግፋል።

    ይሁንና የሜጋ ፕሮጀክቶቹ እጅግ የተጋነነ ወጭ የሚወጡባቸው በመሆናቸው (White Elephant Projects)፤ ይኸው ከፍተኛ በጀት ሀገራችን በብድርና እርዳታ የምታገኘው በመሆኑ፤ አንዳንዶቹ ፕሮጀክቶች ሀገራችን አሁን ካለችበት ሁኔታ አንፃር የቅደም ተከተል ችግር ያለባቸው መሆናቸው ፤ ከአዋጭነት፣ ባለድርሻዎችን ከማሳተፍ፣ ከዲዛይንና ግንባታ አካሄድ፣ ከብክነትና ሙስናን ከማስቀረት፣ በግልጽ ጨረታ የግንባታ ኮንትራክተሮችን ከመለየት እንዲሁም በየጊዜው ስለፕሮጀክቶቹ ለሕዝብ ግልጽ መረጃ ከመስጠት አንፃር ክፍተቶች ያሉባቸው መሆናቸውን አብን ያምናል።

    መንግሥት ይህን ያህል ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ ግልጽነት ባልተሞላበትና የቅድሚያ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን አንገብጋቢ ጉዳዮች ባላስቀመጠ መልኩ ማዋሉ ፓርቲያችንን ክፉኛ ያሳስበዋል። ስለሆነም፦

    ሀ) መንግሥት ስለፕሮጀክቶቹ ለሕዝብ ግልፅ ማብራሪያ እንዲሰጥ፤

    ለ) በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት የሀገራችን ኢኮኖሚ ክፉኛ እየተደቆሰ በመሆኑ ቀውሱ ሀገርን ለከፋ አደጋ የሚዳርግ ማኅበራዊ ቀውስ ከማደጉ በፊት አስፈላጊ የኢኮኖሚ ድጋፍ ማእቀፎችን ቀርፆ ወደ ሥራ እንዲገባ፤

    ሐ) የተጋነኑና አንገብጋቢ ያልሆኑ ሜጋ ፕሮጀክቶችን በማጠፍ በጀቱን የነፍስ አድን ርዳታ ለሚፈልጉ ወደ 18 ሚሊዮን ዜጎች ድጋፍ እንዲያውለው፤

    መ) በሀገራችን ያለው የሥራ አጥነት በአስከፊ ሁኔታ ላይ መገኘቱን በማጤን መንግሥት ጊዜውንና አቅሙን ለወጣቶች ሥራ እድል ፈጠራና ለኢኮኖሚ ሽግግር እንዲያውል አብን ጥሪውን ያቀርባል።

    3. ብሔራዊ ውይይትና መግባባትን በተመለከተ፦

    አብን የሀገራችን የፖለቲካ ቀውስ በምርጫ ብቻ እልባት ያገኛል የሚል አቋም የለውም። ስለዚህም ከምርጫ በፊት እንደ ሀገር መደማመጥ፣ መከባበርና መተማመን እንዲቻልና አሁን የተፈጠረው የሽግግር ጊዜም እንዳለፉት ዘመናት እድሎች እንዳይከሽፍ ሁሉን አቀፍ ሀገራዊ የሰለጠነ ውይይት፣ ምክክርና ድርድር እንዲዘጋጅ፤ ለዚህም ግልጽ ማእቀፍ እንዲኖርና ሁሉንም ባለድርሻ አካላት ያሳተፈ የብሔራዊ ውይይት መድረክ እንዲከፈት ወትውቷል።

    መንግሥት ለእውነተኛ የፖለቲካ ድርድርና ብሄራዊ መግባባት ዳተኝነት በማሳየቱ ምክንያት ፅንፈኛ ኃይሎች ሀገር አፍራሽ ድርጊታቸውን በማናለብኝነት እንዲቀጥሉ እድል ሰጥቷቸዋል። በዚህ ረገድ ትሕነግ የሚዘጋጅበት ሕገ-ወጥ ምርጫ በወረራ በተያዙ የአማራ መሬቶች በወልቃይት፣ ጠገዴ፣ ጠለምትና ራያ የሚኖረው ሕዝባችን ላይ የሚያደርሰውን ፅኑ አፈናና ግፍ መንግሥት እንዲያስቆም በተደጋጋሚ ጥሪ አቅርበናል።

    የፌዴሬሽን ም/ቤት ዘግይቶም ቢሆን የወሰነውን ውሳኔ የፌዴራል መንግሥቱ በአስቸኳይ ተግባራዊ እንዲያደርግና ትህነግ በህገወጥ ምርጫ በወልቃይትና ራያ ሕዝባችን ላይ የሚያደርሰውን ሰብአዊ ቀውስ እንዲያስቆም የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ጥሪ ያቀርባል።

    በተጨማሪም ፡-

    ሀ) ሀገርን ወደ ዴሞክራሲ ለማሻገር ሁሉም ባለድርሻ አካላት የማይተካ ሚና እንዳላቸው በማመን መላው የፖለቲካ ኃይሎች የሀገራችን አደገኛ ወቅታዊ ሁኔታ ባጤነ መልኩ በኃላፊነት እንዲንቀሳቀሱ፤

    ለ) መንግሥት በውል የታወቀና የታቀደ ሁሉንአቀፍ ብሔራዊ ውይይት፣ ምክክርና ድርድር የማስተባበርና የማመቻቸት ኃላፊነቱን እንዲወጣ፤

    ሐ) ሁሉም ዜጎች በተለይም ሲቪክ አደረጃጀቶች፣ የሚዲያ ተቋማት፣ ምኁራን፣ የኃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ ወጣቶችና ሴቶች እንዲሁም ባለሀብቶች ለሚደረገው ብሔራዊ ውይይት፣ ምክክርና ድርድር ውጤታማነት የየድርሻቸውን አስተዋፅኦ እንዲኖራቸው፤

    መ) የዓለምአቀፍ ማኅበረሰቡ የሁሉንአቀፍ ብሔራዊ ውይይት፣ ምክክርና ድርድር ሂደት እንዲደግፍና መንግሥት የሚጠበቅበትን ኃላፊነት እንዲወጣም ጫና እንዲፈጥር የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ታሪካዊ ጥሪውን ያስተላልፋል።

    “አንድ አማራ ለሁሉም አማራ ፤ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ!›”
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)
    አዲስ አበባ፣ ሸዋ፤ ኢትዮጵያ!
    ጳጉሜ 2 ቀን 2012 ዓ.ም

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)

    Anonymous
    Inactive

    በኢትዮጵያ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ የታሪክ ዳራ፥ በእኩልነት ላይ የተመሠረተች ሀገር ለመፍጠር የተደረጉ ሙከራዎች፣
    ያጋጠሙን የታሪክ ፈተናዎችና ያመለጡን ዕድሎች በብሔራዊ መግባባት መነፅር ሲታይ

    መረራ ጉዲና (ፕሮፌሰር)
    ለብሔራዊ መግባባት ውይይት የቀረበ ጥናት
    ነሐሴ 2012

    አብዛኛዎቹ የሀገራችን የታሪክ ምሁራን የኢትዮጵያ ታሪክ ከክርስቶስ ልደት በፊት፣ በአስረኛው ምዕተ ዓመት የንግስት ሳባ እና የንጉሥ ሰለሞን ግንኙነት በሚባለው ጊዜ ይጀምራል ይላሉ። ይህ ለአንዳንዶቹ የሚታመን ታሪክ ተደርጎ የሚወሰደው፤ ለሌሎች ደግሞ ተረት እንደነበረ የሚነገረው ክስተት የማስመሰያ ትርክቱ የእስራኤል አምላክ የቀባቸው ገዥዎች ተብሎ በሺዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት ንጉሦቹ ቅቡልነትን አግኝተውበታል። በትርክቱም ሀገሪቷን እስከ 1966 ሕዝባዊ አብዮት ድረስ ያለ ብዙ ጭንቀት ገዝተውበታል።

    የዛሬይቱ ሰፊዋ ኢትዮጵያ እንደ ሕብረ ብሔራዊ የነገሥታት መንግሥት (multi-ethnic empire state) የተፈጠረችው በ2ኛው የ19ኛው ክፍለ ዘመን ግማሽ፤ የዘመነ መሳፍንት ከሚባለው ዘመን በኋላ ስለሆነና ዛሬም በጣም ሰፊ ቀውስ ውስጥ የከተተን ታሪካዊ ዳራም ከዚሁ ጊዜ ጀምሮ ስለሆነ፥ ጽሑፌም ከዘመናዊ ኢትዮጵያ መፈጠር ጋር በተፈጠሩ ችግሮች ላይ ያተኩራል።

    የዘመነ መሳፍንትን ክስተት በመለወጥ የተጀመረው የዛሬዋን ሰሜናዊ ኢትዮጵያን አንድ የማድረግ ሕልም በግማሽ ምዕተ ዓመት ውስጥ ከሦስት እጥፍ በላይ የሰፋች ኢትዮጵያን መፍጠር ችሎዋል። ይህ የታሪክ ክስተት የሦስት ምኞቶች ዉጤት ነበር። እነዚህም፡-

    1ኛ/ ተበታትና የነበረችውን የዛሬዋን ሰሜናዊ ኢትዮጵያ ሕዝቦችን ለማሰባሰብ የታለመ ምኞት፣
    2ኛ/ የኦሮሞና የሶማሌ ሕዝቦችን ጨምሮ ሰፊውን የደቡብ ክፍል የማስገበር ምኞት፣
    3ኛ/ አፍሪካን ለመቀራመት የመጡትን የአውሮፓ ሀገሮች ጋር የመፎካከር ምኞት ነበሩ።

    እነዚህን ሦስት ምኞቶች ለማሳካት የመጀመሪያ የሆነውን ሙከራ የጀመሩት እንደምታውቁት አፄ ቴዎድሮስ ነበሩ። ቴዎድሮስ ሕልሞቹን ለማሳካት ጠንካራና ሰፊ ሠራዊት ማደራጀት ነበረባቸው፤ ለዚህም ሰፊ መሬት የያዙትን ቄሶች መሬት መቀማትና ዘመናዊ መሣሪያን ከክርስቲያን አውሮፓ ለማግኘት ጥረት ማድረግ ነበር። የአዉሮፓ መሪዎችን ማሳመን ሲያቅታቸው ደግሞ ሙያው የሌላቸውን አውሮፓዊያንን ሳይቀር በቤተ መንግሥታቸው ሰብስበው ከባድ የጦር መሣሪያ ውለዱ እስከማለት ደርሰዋል። ይህም ምኞታቸዉ ይሳካ ዘንድ በነበራቸዉ የጦር መሣሪያ የአካባቢ ገዥዎችንም ለማንበርከክ ተንቀሳቅሰዋል።

    ቄሶችን ለመግፋት ያደረጉት ሙከራ እግዚአብሔርን የካዱ ንጉሥ ተብሎ ተሰባከባቸዉ። የአውሮፓውያንን ዘመናዊ መሣሪያ ለማግኘት ገደብ ያለፈ ጉጉታቸው ከእንግሊዘኞች ጋር ያለጊዜ አላተማቸው። የየአከባቢውን ገዥዎች በጉልበት ለማንበርከክ እጅና አንገት በመቁረጥ የገፉበት ሙከራ ከእንግሊዞች ጋር ለመዋጋት የቁርጥ ቀን ሲመጣ፥ የትግራይ፣ የወሎ፤ የጎጃም፣ የሸዋ፣ የጎንደር ገዥዎች ሁሉም በሚባልበት ደረጃ ካዷቸው። በአጭሩ የየአከባቢዉ ገዥዎች በእንግሊዞች እጅ መሞታቸውን ሲሰሙ ከማዘን ይልቅ ተገላገልን ያሉ ይመስላል። ለዚህም ይመስለኛል ዕውቁ የታሪክ ምሁር ፕሮፌሴር ባህሩ ዘውዴ የቴዎድሮስን ሚና በተሻለ የታሪክ ሚዛን ላይ ለማስቀመጥ ሲሞክር፥ “የተወናበዱ የለዉጥ ነቢይ” (“confused prophet of change”) ያላቸዉ።

    በዚህ የቴዎድሮስ የታሪክ ሚና ላይ ብዙ ሰው ልብ የማያደርገውን የታሪክ ማስታወሻ አስቀምጬ ልለፍ። ይኼውም ቴዎድሮስ በጊዜው ለነበሩ የአውሮፓ ኃያላን መንግሥታት በፃፉት ደብዳቤ ውስጥ፥ “አባቶቼ በሠሩት ኃጢአት ምክንያት እግዚአብሔር “ጋሎችን” በሀገሬ ላይ ለቆ፣ እነሱ ጌቶች ሆነው፣ እኛ የእስራኤል ልጆች የነሱ አሽከሮች ሆነን እንኖር ነበር። አሁን እግዚአብሔር ከትቢያ አንስቶኝ የኢትዮጵያ ንጉሥ አድርጎኛል። እናንተ ከረዳችሁኝ በጋራ እየሩሳሌምንም ነፃ ልናወጣ እንችላለን” ማለታቸዉ ነዉ (ትርጉም የኔ ነው)። እዚህ ላይ ሁለት ነገሮችን ልበል፦

    1) “ጋሎቹ” የሚባሉት በዘመነ መሳፍንት የጎንደርን ቤተ መንግሥት በበላይነት ሲቆጣጠሩ የነበሩ የየጁ ኦሮሞዎች መሆናቸውና እየሩሳሌም በጊዜው በእስላሞች እጅ የነበረች መሆንዋን ነው።
    2) ከዚህ አንጻር ማስታወስ የሚያስፈልገው ትልቁ ጉዳይ አፄ ቴዎድሮስ የብሔረሰብ (የዘር) ፖለቲካን በግልፅ የተናገሩ የመጀመሪያዉ የኢትዮጵያ መሪ መሆናቸው ነው።

    ከቴዎድሮስ ሞት በኋላ ለሦስት ዓመታት በተክለጊዮርጊስ እና ካሣ (አማቾች የነበሩ ይመስለኛል) ከተካሄደው የሥልጣን ትግል በኋላ በአሸናፊነት የወጡት አፄ ዮሐንስ (ካሣ ምርጫ) ነበሩ። አፄ ዮሐንስ ከሀገር ውስጥ ከወሎ፣ ከጎጃም፣ ከጎንደር፣ ከሸዋ ገዢዎች ጋር እየተጋጩ፥ ከውጭ ደግሞ ከጣሊያኖች፣ ከግብፆችና ከሱዳን መሐዲስቶች (ደርቡሾች ) ጋር ሲዋጉ በመጨረሻ በመሐዲስቶች እጅ ወድቋዋል።

    በአጭሩ ዮሐንስ ለትግራይ ሊሂቃን የኢትዮጵያ ማዕከል ነበርን፤ የአክሱም ሀቀኛ ወራሾች እኛ ነን የሚለውን የፖለቲካ ስሜት መፍጠር ቢችሉም፥ በኢትዮጵያ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ታሪክ ውስጥ የተለየ ሚና መጫወት አልቻሉም።

    በማያሻማ ቋንቋ፥ የዛሬዋ ኢትዮጵያ በዋናነት የተፈጠረችውና የዛሬው የታሪክ ጣጣችንም በዋናነት የተፈጠረው በአፄ ምኒልክ ነው። ምኒልክ ንጉሠ ነገሥት ዮሐንስን የሱዳን መሐዲስቶች እስኪገድሉላቸው ድረስ ከአውሮፓ መንግሥታት፥ በተለይም ከጣሊያን በገፍ ባገኙት የጦር መሣሪያ እነራስ ጎበና የመሳሰሉ የኦሮሞ የጦር መሪዎችን በመጠቀም በጊዜው ጠንካራ የሚባል ግዙፍ ሠራዊት መገንበት ችለዋል። ይህንን ግዙፍ ሠራዊትን ከዮሐንስ ጋር በመዋጋት ከማድከም ይልቅ፥ በአንድ በኩል ዮሐንስን እየገበሩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ያኔ የነበረችውን ኢትዮጵያ ሦስት እጅ እጥፍ የሆነ ሰፊ ግዛት መፍጠር ችሎዋል። በዚህም መጀመሪያ ሳይጠቀለሉ የቀሩትን የሸዋ ኦሮሞዎችን ጠቅልለው ያዙ። ከዚያ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር (እ.አ.አ) በ1876 ጉራጌን ብዙ ሕይወት ከጠየቀ ጦርነት በኋላ አስገበሩ። ብዙ ዝርዝር ውስጥ ሳይገባ የምኒልክን የመስፋፋት ጦርነቶች እንደሚከተለው ማጠቃለል ይቻላል። ይኸውም በምኒልክና ጀኔራሎቹ ብዙ የግዛት መስፋፋት ጦርነቶችን ቢወጉም ሦስቱ ወሳኝ ጦርነቶች ነበሩ።

    አንደኛው በምዕራብ በኩል በእማባቦ (ዛሬ ሆሮ ጉዱሩ በሚባለው ላይ በጎበና መሪነት እ.አ.አ በ1882 የተዋጉት ጦርነት ነበር። ይህ ጦርነት ኦሮሞን ጨምሮ የምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦችን ዕድልና የጎጃም መሪዎች ከሸዋ ጋር የነበራቸውን ፉክክር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የወሰነና የሸዋንም የበላይነት ያረጋገጠ ነበር።

    ሌላው የምኒልክ ጦርነት በአርሲ ላይ እ.አ.አ በ1886 የተደመደመዉ ነው። አርሲዎች ከሌሎች የኦሮሞ አካባቢዎች በተለየ መንገድ ለአምስት ዓመታት በጀግንነት ተዋግተዋል። በመጨረሻም በራሳቸው በምኒልክ በተመራ ጦር የአውሮፓ መሣሪያ በፈጠረው ልዩነት ሊሸንፉ ችለዋል። ተመሳሳይ የመከላከል ጦርነት እንዳይገጥማቸው ይመስላል ምኒልክ ዛሬ አለ፣ የለም የሚባለውን የአኖሌ ዓይነት የጭካኔ በትር በአርሲዎች ላይ አሳርፈዋል። እዚህ ላይ ዛሬ እየተነጋገርንበት ላለው የብሔራዊ መግባባት መሳካት፥ የለም ከሚለው አጉል ክርክር ወጥተን የትናንትናውን የታሪክ ቁስላችንን በሚያክም መልኩ እንድናስተካክል መምከርን እወዳለሁ።

    ሦስተኛው የምኒልክ ትልቁ ጦርነት አሁንም በእሳቸው የተመራውና እ.አ.አ በ1887 የተካሄደው የጨለንቆ ጦርነት ነበር። የዚህ ጦርነት ውጤት በጊዜው የሀብታሟ የሐረር ከተማ መንግሥት (the Harari city-state) ጨምሮ ምስራቅ ኢትዮጵያ ያለ ደረሰኝ ምኒልክ እጅ የገባበት ሁኔታን ፈጥሯል። ከዚህም በኋላ ከፋን፣ ወላይታን፣ ወዘተ ለመያዝ ብዙ ደም የፈሰሰባቸው ጦርነቶች ነበሩ። እንደሚባለው በእንግሊዝ ተስፋፊዎችና በምኒልክ ኢትዮጵያ መካከል የመምረጥ ዕድል የገጠማቸው የቦረና ኦሮሞዎች፥ ‘ማንን ትመርጣላችሁ?’ ሲባሉ፥ የፊታወራሪ ሀብተጊዮርጊስ ፊትን አይተው፥ የእኛኑ ፊት የሚመስለው ይሻላል ብለው በሪፈረንደም (referendum) እየሰፋ በመጣው የኢትዮጵያ መንግሥታዊ ግዛት ውስጥ የተቀላቀሉበት ሁኔታም እንዳለ ይነገራል።

    እ.አ.አ በ1889 አፄ ዮሐንስ በመሐዲስቶች ሲገደሉ፥ ኦሮሞን ጨምሮ አብዛኛው ደቡብን የተቆጣጠሩት ምኒልክ ለሰሜኑ ወንድም መሪዎች ፈረንጆች እንደሚሉት “ካሮትና ዱላን ማስመረጥ” (carrot-and-stick approach) ብቻ በቂ ነበር። የሰሜኑ መሪዎች ምርጫም በማያሻማ መንገድ ካሮት ነበር። ስለካሮቱም በግልፅ ቋንቋ ለማስቀመጥ፥ የኦሮሞ አከባቢዎችን ጨምሮ በደቡብ የተገኘውን እጅግ በጣም ሰፊ ግዛት ዉስጥ በታናሽ ወንድምነት ሹማቶችን መቀራመት ነበር።

    በብሔራዊ መግባባታችን ውይይት አንፃር በምኒልክ በተፈጠረው ሰፊ አፄያዊ ግዛት ጋር የተፈጠሩ ችግሮችን ወደ ማንሳቱ ልለፍ። አንደኛው ችግር ከላይ እንዳነሳሁት፥ በጉልበት የግዛት ፈጠራ ላይ አኖሌን የመሳሰሉ የታሪክ ጠባሳዎች መፈጠራቸው። ሁለተኛውና ዋናው ነገር ግን ከማቅናቱ ጋር የተፈጠረው የፖለቲካል ኤኮኖሚው ነው። ይህም በነፍጥ ላይ የተመሠረተዉ የፖለቲካ ኤኮኖሚ ዛሬም እያወዛገበን ያለው የነፍጠኛ ሥርዓት በሚባለው ላይ የተመሠረተዉ ነዉ። ለማቅናት የተሰማራው የፊውዳሉ ሥርዓት ሠራዊት የገባር ሕዝቦችን ነፃነት ቀምተዋል፤ መሬታቸዉን ዘርፈዋል፤ ሕዝቦችን በገዛ መሬታቸው ላይ ጭሰኛና አሽከር አድርገዋል፤ ቋንቋቸውን አፍነው በ’ስማ በለው’ ገዝቷቸዋል። በአጭሩ፥ እጅግ በጣም ዘግናኝና ጨካኝ የሆነ የፖለቲካ ሥርዓት ጭነውባቸዋል። አንዳንዱ ነፍጠኛ በሃያ ሺዎች የሚቆጠር ጋሻ መሬትም ነበረው። ወረ-ገኑ የመሳሰሉ የቤተ መንግሥት መሬቶች እጅግ በጣም ብዙ ነበሩ። እዚህ ላይ ማስታወስ የሚያስፈልገው የሰሜንና የደቡብ ኢትዮጵያ የመሬት ይዞታም በፍጹም የተለያዩ መሆናቸው ነው። አነሰም በዛ የሰሜኑ ገበሬ የዘር ግንዱን ቆጥሮ መሬት ያገኛል። መሬት አያያዙም የወል ነበር። ሌላው ቢቀር የሚገዛውም በራሱ ቋንቋ ነበር። በደቡቡ ያለው ግን የመሬት ሥርዓቱ የግል ሆኖ፥ ጭሰኝነት እጅግ የተንሠራፋበት ነበር። ሲሶ ለነጋሽ፣ ሲሶ ለቀዳሽ፣ ሲሶ ለአራሽ የሚባለው የኢትዮጵያ ነገሥታት የመሬት ፖሊሲ እጅግ በጣም ዘግናኝ በሆነ ሁኔታ ሥራ ላይ የዋለው በደቡቡ የሀገራችን ክፍል ላይ ነው።

    በ1960ዎቹ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ዘመን “መሬት ላራሹ” እና “የብሔረሰቦች እኩልነት” የተባሉ ሕዝባዊ መፈክሮች የተወለዱት ከዚሁ ጨቋኝ ሥርዓት ነበር። ዛሬ የታሪክ ክለሳ ውስጥ ብንገባም፥ በእውነቱ ከሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብራክ የወጡ ወጣቶች፥ እንዲያውም በወቅቱ ‘አማራ’ ከሚባለው ክፍል የሚበዙ ይመስለኛል፤ መፈክሮቹን በጋራ አስተጋብተዋል።

    ለማንኛውም ከብሔራዊ መግባባታችን አንፃር አንድ ነገር ግልፅ ላድርግ። ‘ነፍጠኛ’ የሚባለው ሥርዓት ገዝፎ የነበረ ሥርዓት መሆኑና፥ ይህም ሥርዓት ከደቡቡ አርሶ አደር የተሻለ ኑሮ የማይኖሩትን፥ ቢፈልጉ እንኳን የደቡቡን ገበሬ ለመዝረፍ አቅሙም ሆነ ዕድሉን ያልነበራቸውን የአማራ አርሶ አደርን አይጨምርም፤ መጨመሩም ጩቡ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ዛሬ አንዳንድ የአማራ ሊሂቃን “እኔም ነፍጠኛ ነኝ” የሚለውን መፈክር ሲያሰሙ፥ ጥቅሙ ኦሮሞን ጨምሮ የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦችን ከአማራ ሕዝብ ጋር ከማጋጨት የዘለለ የፖለቲካ ትርፍ የሚኖረው አይመስለኝም። ስለሆነም የምንችለውን ያክል ሁላችንም ከሁለቱም ጩቡዎች እንጠንቀቅ ዘንድ አደራ እላለሁ።

    ወደ ሌሎች ነጥቦች ከማለፌ በፊት በዋናናት በምኒልክ የተፈጠረችዉ ኢትዮጵያን ለማስተካከል ያቃታቸዉና መሪዎች ማለፍ ያልቻሉት የታሪክ ፈተና ምንድን ነው? የሚለውን ጥያቄ በንጽጽር እንደ ታሪክ ቁጭት ማንሳትን እወዳለሁ። አፄ ቴዎድሮስ የሞቱት እ.አ.አ በ1868 ነበር። ጃፓንን ከታላላቅ የዓለም መንግሥታት ተርታ ያሰለፏት መጅ (Meiji) የሚባሉ የንጉሣውያን ቤተሰብ ወደ ሥልጣን የተመለሱት (The Meiji Restoration) በዚሁ ዓመተ ምኅረት ነበር። የጃፓን ንጉሣዊ ቤተሰቦች በሰላሳ ዓመታት ውስጥ በኢኮኖሚ የበለፀገች ታላቋ ጃፓንን ፈጠሩ። የጃፓኖች የሀገር ፍቅር ግንባታቻውም ባዶ አልነበረም። ትዝ እስከሚለኝ ድረስ አንድ የጃፓን ወታደር ንጉሤ የጃፓንን በሁለተኛው የዓለም ጦርነት መሸነፍ አልነገሩኝም ብሎ ከሃምሳ ዓመታት በኋላ በፊሊፕንስ ይሁን፤ በኢንዲኔዢያ ጫካ ውስጥ ተገኝቷል። ለሀገር ፍቅር ሲባል እራስን በራስ ማጥፋት በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በትናንሽ አይሮፕላኖችን የአሜሪካን መርከቦች ውሰጥ እየጠለቁ አጥፍቶ መጥፋትን የጀመሩት የጃፓን ካሚከዞች (Kamikaze) የሚበሉ ነበሩ። የኢትዮጵያ መሪዎች ግን በተመሳሳይ ጊዜ (እ.አ.አ 1868-1900) ድረስ ሀገሪቷን ከዓለም ጭራነት አላላቀቋትም። በነገራችን ላይ ጃፓንና ኢትዮጵያ በ1868 ላይ ተመሳሳይ የዕድገት ደረጃ ላይ ነበሩ።

    ሌላው ንጽጽሬና የታሪክ ቁጭታችን መሆን ያለበት፥ ታላቋ ጀርመንን የፈጠሩት ቢስማርክ (Otto von Bismarck) እና ምኒልክ የአንድ ዘመን ሰዎች ነበሩ። ምንም ይሁን ምን እነ ቢስማርክ ዓለምን ሁለት ጊዜ ጦርነት ውስጥ መክተት የቻለች ኃያሏን ጀርመን ሲፈጥሩ፥ የኢትዮጵያ ገዥዎች ግን ኋላቀር ኢትዮጵያን ትተውልን ሄደዋል። በነገራችን ላይ ሀገር ትፈርሳለች ተብሎ ስለተሰጋ፥ የምኒልክ ሞት ለሕዝብ ይፋ የሆነው ከዓመታት በኋላ ነበር ይበላል።

    በአጠቃላይ ከብሔራዊ መግባባት ፈጠራችን አንፃር መረሳት የሌለበት ቁመነገር፥ በምኒልክና ጣይቱ የተመራው የአድዋው የጋራ ድል እንኳ ያልፈቱት የሚጋጩ ሦስት አመለካከቶች ዛሬም ከእኛ ጋር መኖራቸዉ ነዉ።

    አንደኛው፥ የሀገራችን ሀገረ-መንግሥት ግንባታ አንድ የነበሩና የተበታተኑ ሕዝቦችን አንድ ላይ መልሶ ያመጣ ነዉ የሚላዉ አመላካከት (reunification)፤
    ሁለተኛው፥ በአንድ ላይ ያልነበሩ ሕዝቦችን ወደ አንድ ማምጣት ነዉ የሚለዉ አመላካከት (unification and/or expansion)፤
    ሦስተኛው፥ ነፃ ሕዝቦችን ጨፍልቆ በኃይል ማቅናት ነዉ የሚላዉ አመላካከት (colonial thesis) ናቸው። የበለጠ ግልፅ ለማድረግ፥ የኢትዮጵያ አንድነት አጥባቂዎች ነን የሚሉ በዋናነት የምኒልክን ኃጢአቶች አይቀበሉም። እንደሚሉት እምዬ ምኒልክ በዓለም ከተደረጉት የሀገር ግንባታዎች ምን የተለየ ነገር ሠራ የሚለውን ሐሳብ ያራምዳሉ። ከዚያም አልፈዉ ምኒልክ የሠራዉ ሥራ ተለያይተዉ የነበሩትን የኢትዮጵያ ግዛቶችን መመለሰ ነበር ይላሉ። በአንፃሩ የኢትዮጵያ አንድነትን የማያጠብቁ ብሔረተኞች ደግሞ የአቶ ሌንጮ ለታን አባባል ለመጠቀም (አሁን አቋማቸዉ ያ መሆኑን አላዉቅም)፥ ሲያንስ “ኢትዮጵያዊ ለመሆን እንደራደራለን ሲበዛ ደግሞ ነፃ መንግሥታትን እስከ መፍጠር ድረስ እንሄደለን” የሚሉ ናቸው። በጥቅሉ እነዚህ አመለካከቶች በፖለቲካችን ለሚጋጩ ሕልሞቻችን መሠረት የሆኑና ካልተገደቡ የሥልጣን ሕልሞች ጋር ተደምሮ የብሔራዊ መግባባት ጥረታችንን የሚያወሳስቡ አመለካከቶች መሆናቸውን በውል መገንዘብ ያስፈልጋል።

    በእነምኒልክ የተፈጠረችዉን ኢትዮጵያን ለማስተካከል የተደረጉ ሙከራዎችና ያመለጡን ዕድሎች፡-

    1) የልጅ ኢያሱ ሙከራ

    ልጅ ኢያሱ የምኒልክ ልጅ ልጅ ሲሆን፥ በእኩልነት ላይ የተመሠረተች ኢትዮጵያን ለመፍጠር ልዩ ዕድል የነበረውና ያንንም ልዩ ዕድል አውቆ ለመጠቀም ሲሞክር በወጣትነት ዕድሜው ላይ የተቀጨ መሪ ነበር። በብሔር ግንዱ ኦሮሞና አማራ የነበረ፣ በሃይማኖት ጀርባዉ ክርስቲያንና ሙስሊም የነበረ ሰዉ ነዉ። ከወሎም በመወለዱ፣ ትግራይንና ሸዋን ለማገናኘት የተሻለ ድልድይ ለመሆን ይችል ነበር። የሚገርመው ግን፥ የልጅ ኢያሱ ወንጀሎች የሚመነጩት እነዚህኑ አዎንታዊ እሴቶችን ለሀገረ-መንግሥት ግንባታ ለመጠቀም መሞከሩ ነበር። ለምሳሌ አንዳንድ የታሪክ ማስታወሻዎች እንደሚያስረዱት፥ አርሲዎች እንደልጃቸው ይመለከቱት ነበር ይባላል። ከሱማሌዎችና ከአፋሮች ጋር ጥብቅ ግንኙነት እንደነበረው በቂ የሆነ የታሪክ ማስረጃ አለ። ከጎጃሙ ራስ ኃይሉና ከወለጋው ደጃዝማች ጆቴ ቱሉ ጋር የጋብቻ ዝምድና እንደነበረው ይታወቃል። ቤተ ክርስቲያንን ለማሠራት የሚጥረውን ያክል (ለምሳሌ የቀጨኔውን መድሃኔዓለምን እሱ ነው ያሠራው ይባላል) መስግዶችን ያሠራ ነበር። ከሥልጣን ላወረዱት የሸዋ ሊሂቃን ግን፤ አንዱና ትልቁ የልጅ ኢያሱ ወንጀል መስጊዶችን ማሠራቱ ነበር። የመጨረሻው ትልቁ ወንጀል ደግሞ ኢትዮጵያን ለመቀራመት ያንዣበቡ የቅኝ ገዥ ኃይሎች ከሰሜንና ምስራቅ ጣሊያን፣ በምዕራብ፣ በደቡብና በምስራቅ እንግሊዝ፣ በምስራቅ ፈረንሳይ የሦስትዮሽ ስምምነት (tripartite treaty) የሚባለውን እ.አ.አ በ1903 ፈርሞ የምኒልክን ሞት ይጠብቁ ከነበሩት መራቅና በአንደኛው የዓለም ጦርነት በአከባቢያችን ግዛት ካልነበራቸው ከነጀርመንና ቱርክ ጋር ለመደጋገፍ መሞከሩ ነበር።

    በጥቅሉ ከሁሉም በላይ ወንጀሎቹ ሰፊዋን ኢትዮጵያን የፈጠርን እኛ ነን የሚሉትን የሸዋ ልሂቃንን መጋፋቱ ነበር። በግልፅ ቋንቋ ለማስቀመጥ፥ የኢያሱ ወንጀሎች የሸዋ ልጅ አለመሆኑ (የኢያሱ አባት ወሎ ነው)፣ ሐቀኛ የክርስቲያን ልጅ አለመሆኑ (አባቱ የግድ ክርስቲያን ከመሆናቸው በፊት መሐመድ ዓሊ ነበሩና) እንዲሁም የአውሮፓ የቅኝ ገዥ ኃይሎችን ማስቀየሙ ናቸው።

    እ.አ.አ በ1916 በመስቀል ቀን ኢያሱን ለማውረድ ሁሉም መሣሪያዎቻቸውን ይዘው ተሰለፉ። ቄሶቹ ኢያሱ ሐቀኛ የክርስቲያን ልጅ አይደለም በማለት በማውገዝ፣ የሸዋ ሊሂቃን ሠራዊታቸውን በመሳለፍ፣ የአውሮፓዊያኑ መንግሥታት ምክርና ጥበባቸውን ይዘው ተሰለፉ። የአውሮፓዊያኑ ጥበብ የሚገርም ነበር፤ ኢያሱ በኢትዮጵያ ባንዲራ ላይ የእስልምና ምልክት የሆነውን ግማሽ ጨረቃ ለጥፎ ለቱርኮች ዲፕሎማት ሲሰጥ የሚያሳይ ፎቶ ሾፕ የሆነ ሥዕል (ፎቶ ሾፕም፣ የባንድራ ፖለቲካም በልጅ ኢያሱ ዘመንም ነበር) መፈንቅለ መንግሥት እንድያከሄዱ የሸዋ ሊሂቃንን መርዳት ነበር። እዚህ ላይ ለታሪክ ትዝብት አንድ ነገር ልብ በሉልኝ። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያን ፖለቲካ ሳስተምር፥ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ችግሮቻችንን በሚመለከት ፈተናም ፈትኜበታለሁ፤ የሸዋው ጦር መሪ የነበሩት ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴ የመፈንቅለ መንግሥቱም መሪ ነበሩ፤ ልጅ ኢያሱን ሲያወርዱ ባስተላለፉት መልዕክት ውስጥ የሚከተለው ይገኝበታል።

    “He claims that he eats flesh of cattle slain by Muslims in order to extend frontiers and to win hearts. But these Somali and Muslims have already been brought to heel [and do not need such diplomacy]”

    በጥሬው ሲተረጎም፥ ግዛትን ለማስፋፋትና ልቦችን ለመሳብ ብዬ በሙስሊም የታረደውን የከብት ሥጋ እባላለሁ ይላል። ነገር ግን እነዚህን ሱማሌዎችና ሙስሊሞችን ቀድሞውኑ ስላንበረከክን እንዲህ ዓይነቱ ዲፕሎማሲ አያስፈልጋቸውም።

    ይህንን የሀብተጊዮርጊስን ንግግር በሚመለከት ሰፊውን ትንተና ለናንተ ትቼ፥ በዚህ ዓይነት የተዛባ አመለካከት ላይ የተገነባችውን ኢትዮጵያን አስተካክሎ በሰፊ መሠረት ላይ የተገነባችውን ኢትዮጵያን ለመፍጠር የተደረገው የመጀመሪያ ሙከራ፥ ልጅ ኢያሱን ለሥልጣን ተብሎ በተጠነሰሰው ሤራ መውረዱን እንዳትረሱት አደራ ማለት እፈልጋለሁ። ያመለጠንን ዕድል ትርጉም ግን ለታሪክ መተውን አመርጣለሁ።

    2) ኢያሱን በወሳኝነት የተኩት ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ

    የሀገራችንን ሀገረ-መንግሥት ግንባታን በተሻለ መሠረት ላይ ለመገንባት ረጅም ጊዜ (ለ60 ዓመታት ገደማ አገሪቷን መርተዋል) በልጅነታቸው የተሻለ የፈረንጅ ዕውቀት የቀመሱና ከማንም የበለጠ ተደጋጋሚ ዕድል ያገኙ ነበሩ። ነገር ግን በእኔ ግምት ታሪክ የሰጣቸዉን ዕድል አልተጠቃሙበትም። ንጉሥ ኃይለ ሥላሴን የተለያዩ ሰዎች በተለያዩ የታሪክ ሚዛን ላይ ቢያስቀጣቸውምና እኔም ቢሆን በዘመናዊ ትምህርትና በመሳሰሉት ላይ የነበራቸውን አሻራ ቀላል ነው ብዬ ባላስብም፥ ንጉሡ ሕይወት ዘመናቸውን በሙሉ የግል ዝናንና ሥልጣንን ማዕከል ማድረጋቸው ኢትዮጵያዉያንን የ20ኛው ክፍለ ዘመን ሕዝቦች ማድረግ አልተቻላቸውም። ስለዘር ግንዳቸው ሀሜቱ እንዳለ ሆኖ፥ ከኢያሱ በተሻለ ደረጃ ኦሮሞም፣ ጉራጌም አማራም ነበሩ። ይህንን ስረ ግንድ አልተጠቀሙም። በተለይ ኦሮሞ ከሚባል ሕዝብ ሲሸሹ እንደኖሩ ብዙ ማስረጃዎች አሉ። ለማንኛዉም፤ አንድንድ ወሳኝ ነገሮችን እንመልከት።

    አምቦ 2ኛ ደረጃ ተማሪ በነበርኩበት ጊዜ የሰማሁት ይመስለኛል፤ አንድ ጋዜጠኛ ካነበቡት መጽሐፍት ዉስጥ የትኛውን እንደሚያደንቁ ሲጠይቃቸው፥ ቀልባቸውን በጣም የሳበውና ብዙ ጊዜ ደጋግመው ያነበቡት በኒኮሎ ማኪያቬሊ (Niccolò Machiavelli) የተፃፈውን “The Prince” የተባለውን እንደነበረ ትዝ ይለኛል። ንጉሡ አብዘኛዉን የሕይወት ዘመናቸዉን የተመሩት በማኪያቬሊ ምክር ነበር ብዬ እጠረጥራለሁ። በማክያቬሊ ትምህርት በመመራትም የሥልጣን ተቀናቃኞቻቸውን አንድ በአንድ አስወግደው ከአስራ አራት ዓመታት በኋላ እ.አ.አ በ1930 ጥቁር ማክያቬሊ ፈላጭ ቆራጭ ንጉሥ ሆነው ወጡ።

    እንደ ሀብተጊዮርጊስ ዓይነቱን እግዚአብሔር በጊዜ ሲገላገልላቸው፣ እንደ ጎንደሩ ራስ ጉግሳና ባለቤታቸው ንግስት ዘዉድቱን ያስወገዱበት የፖለቲካ ጥበብ፣ በጊዜው በርግጥም አስደናቂ ነበር። ይህ የንጉሡ ጥበብ፤ አርባ ዓመታትን ቆጥራ የአድዋን ሽንፈት ለመበቀል የመጣቸውን ጣሊያንን ለመከላከል አልረዳም። መንግሥታቸዉንም፤ ሀገሪቷንም ለክፉ ቀን አላዘጋጁም።

    አድዋ ላይ ታሪካዊ ድል ያስገኙ ጀግኖችም የሉም። አንድ ለታሪክ የተረፉት ደጀዝማች ባልቻ ሣፎም በንጉሡ ዉሰኔ እስር ቤት ነበሩ። እዚህም ላይ አንድ የታሪክ ትዝብት አስቀምጬ ማለፍ እፈልጋለሁ። ኃይለ ሥላሴ ለሥልጣናቸዉ ብሎ የገፏቸው ብዙ የአከባቢ መሪዎች፥ ከትግራዩ ደጃዝማች ኃይለሥላሴ ጉግሳ ጀምሮ የጎንደር፣ የጎጃም፣ የሸዋ፣ የጅማ፣ የወለጋ ገዥዎች የጣሊያን ባንዳ ሆኑ። ከሚታወቁት ውስጥ ለታሪክ ‘ተፈሪ ሌላ፣ ሀገር ሌላ’ ብለው ሲዋጉ የሞቱት ደጃዝማች ባልቻ ብቻ ነበሩ። በንጉሡ ስህተት ሀገሪቷ ውድ ዋጋ ከፍላለች። ለዚህ ነው ጠቅላይ ሚኒስቴሩን ጨምሮ የብልጽግና ፓርቲ ባለሥልጣናት ጠዋትና ማታ ባንዳ፣ ባንዳ ሲሉ፥ ግብፅ ሱዳንን ይዛ የምር ከመጣች ሰው ያላሰበውን አሳስበው ለኪሳራ እንዳይዳርጉን የሚፈራው።

    ያም ሆነ ይህ፥ ኃይለ ሥላሴ ለጦርነት ያላዘጋጇትን ሀገር በክፉ ቀን ጥለው ሸሹ። ሐረርጌ ላይም የጂቡቲን ባቡር ሲሳፈሩ ከጦር ሜዳ መሸሻቸውን ለመሸፈን፥ ‘የት ይሄደሉ?’ ብሎ ለጠያቀቸዉ የፈንሳይ ጋዜጠኛ፡ “Je ne suis pas né soldat” (“ወታደር አይደለሁም”) ብለው ያለፉት። ለሳቸዉም ፍትሃዊ ለመሆን፥ የአውሮፓ ዲፕሎማቶች ቢክዷቸውም በዓለም መንግሥታት ማኅበር ላይ የሚያስመካ ሥራ ሠርተዋል። ሆኖም ከጦር ሜዳ የመሸሻቸው ጉዳይ እስከ መንግሥታቸው ፍፃሜ ድረስ እንደ ጥቁር ነጥብ ስትከታላቸዉ ኖራለች። የአርበኞችም ሆነ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ዋናው የተቃውሞ መፈክርም ይህች የሽሸት ጉዳይ ነበረች። ከጣሊያን ወረራ በኋላም ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ በሁለት መሠረታዊ ነገሮች ምክንያት፥ ጋዜጣቸውን “አዲስ ዘመን” ብለው እንደሰየሙ፥ በእርግጥም አዲስ ዘመን፤ ለአዲስቷ ኢትዮጵያ ይፈጠራሉ ብሎ የጠበቁ ብዙ መሆናቸውን ብሎ መገመት አስቸጋሪ አይመስለኝም።

    ለአምስት ዓመታት በእንግሊዝ ሀገር በስደት ሲኖሩ ስለራሳቸው ስህተትም ሆነ የሰለጠነው ዓለም ንጉሦች እንዴት ሕዝቦቻቸውን እንደሚመሩና በዚያም ምክንያት በሕዝቦቻቸው ዘንድ ተከብረው እንዴት እንደሚኖሩ ተምረዋል ብሎ መጠበቅ ይቻል ነበር። ከሁሉም በላይ በጣሊያን ወረራ ምክንያት እሳቸውንም ሆነ ሀገራቸውን ከገጠመው ውርደትና ኪሳራ ይማራሉ ተብሎ ይጠበቅም ነበር። ከሁሉም አልተማሩም። በባሰ ሁኔታና ፍጥነት ወደ ድሮአቸው ተመለሱ። ለዓቢይነት፥ አስተዳደራቸውን የተቃወሙ የራያ ገበሬዎችን (ቀዳማይ ወያኔ የሚባለዉ ነዉ) ከየመን በመጡ የእንግሊዝ አይሮፕላኖች አስደበደቡ። የሪፐብሊካን አስተሳሰብ ነበራቸው የሚባሉትን አርበኛ ደጃዝማች ታከለን (ደጃዝማች ታከለ ወልደሀዋርያት) አሰሩ። እኚህ ሰው ከተደጋጋሚ እስር በኋላ በመጨረሻም ሊይዟቸው ከተላኩ የንጉሡ ወታደሮች ጋር ሲዋጉ ሞቱ። ሌላው ስመጥር አርበኛ የነበሩ በላይ ዘለቀንም ያለርህራሄ ሰቀሉ።

    የአምባሳደር ብርሃኑ ድንቄ ግልፅ ደብዳቤ እንኳን (አምባሳደር ብርሃኑ፤ በአሜሪካ አምባሳደር የነበሩና ንጉሡ የገፉበት መንገድ ዉሎ አድሮ ንጉሡንም ሆነ ሀገሪቷን ለዉርደት እንደሚያበቃ የመጀመሪያ የማስጠንቃቂያ ደወል በአደባባይ የሰጡ ባለስልጣን ነበሩ) አሠራራቸውን አላስለወጧቸውም።

    በፖለቲካ ሥርዓታቸው ላይ በተከታታይ ቦንቦች ፈነዱ። የመጀመሪያዉ ትልቁ ቦንብ በራሳቸው ቤተ መንግሥት ውስጥ የፈነዳው የነመንግሥቱ ንዋይ ያውም የእሳቸውን ክብርና ሞገስ ለመጠበቅ ከፈጠሩት የክብር ዘበኛ ጦር ነበር። ንጉሡ ከክስተቱ ከመማር ይልቅ ጀኔራል መንግሥቱ ንዋይን በሞት ቀጡ፤ የታናሽ ወንድማቸውን ሬሳ እኔን ያየህ ተቀጣ በሚመስል መንገድ በስቅላት ቀጡ። የበሉበትን [ወጭት] ሰባሪዎች ናቸው ብለውም በአዝማሪ አዘለፏቸው።

    ማን እንደመከራቸው ባይታወቅም ትልቁን የመንግሥታቸውን የዲፕሎማሲ ውጤትን ያበላሸውና ለትልቅ ኪሳራ ያበቃንን የኤርትራን ፌዴሬሽንን አፈረሱ። ውጤቱም ሁላችንም እንደምናውቀው የኤርትራ ነፃ አውጪ ግንባር መፈጠር ሆነ። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ኦሮሞዎች የሜጫና ቱለማ ልማት ማኅበር በመፍጠራቸው ጠገቡ ተብሎ መሪዎቹ እነ መቶ አለቃ ማሞ መዘምር ተሰቀሉ፤ ኃይለማርያም ገመዳ እስር ቤት ውስጥ በተፈፀመበት ድብዳባ ሞተ። ጀኔራል ታደሰ ብሩ ሞት ተፈርዶባቸው በአማላጅ ወደ ሐረርጌ በግዞት ተላኩ። እኔ እስከ ማውቀው ድረስ ሁሉም በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ጥያቄ አልነበራቸውም። ውጤቱ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)ን መፍጠር ሆነ። በነገራችን ላይ በእነ ኤሌሞ ቅልጡ በኦነግ ስም የመጀመሪያዋ ጥይት የተተኮሰችው ጀኔራል ታደሰ ብሩ የታሰሩበት ሥፍራ ሐራርጌ ዉስጥ ነበር። በዚሁ ጊዜ ሰፋፊ ማኅበራዊ ፍትህን የሚጠይቁ ተከታታይ ጥያቄዎችም መቅረብ ጀመሩ። እ.አ.አ በ1965 የንጉሡ ፊውዳላዊ ሥርዓት የተመሠረተበት ላይ በመሬት ላራሹ ሰልፍ ድንገተኛ የፖለቲካ ቦንብ ፈነዳ። ከአራት ዓመት በኋላ ደግሞ እስከዛሬ ኢትዮጵያን እያመሰ ያለው በእነ ዋለልኝ መኮንን የብሔረሰቦች ጥያቄ ታወጀ። ይህችኛውን ንጉሡና ሥርዓቱ በቀላሉ የተመለከቷት አይመስልም። ንጉሡ የቀ.ኃ.ሥ ዩኒቨርሲቲ፥ የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ማኅበር ፕሬዝደንት የነበረውን ጥላሁን ግዛዉን በማሰገደል “ልጆቼ” ከሚሏቸው ተማሪዎች ጋር ደም መቃባት ዉስጥ ገቡ። በዚህም የታሪክ ጎማው ወደፊት እንዳይሽከረከር ጣሩ።

    አሳዛኙ ጉዳይ መካሪዎቻቸውም ሆኑ እሳቸው አስተዳደራቸው ለሃያኛዉ ክፍለ ዘመን የማይመጥን መሆኑን፣ በጣም እወዳታለሁ የሚሏትም ኢትዮጵያ በታሪክ ፍራሽ ላይ ተኝታ የምትሸሞነሞን ሀገር መሆኗን አልተረዱም። የኤርትራ ግንባሮች ጥይትም ከረጅም ዘመን እንቅልፋቸው አላነቋቸውም። የባሌና የጎጃም ሕዝብ አመፅም አልቀሰቀሳቸውም። ለዓመታት የቆየው የተማሪዎች ንቅናቄ ጩኸትም አላነቃቸውም። ከኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ በቀጥታ የወጡ የመኢሶንና የኢህአፓ የሶሻሊስት አብዮት ደወልም አላነቃቸውም። በመጨረሻም በመቶ ሺዎች የሚቆጠረው የወሎ ሕዝብ እልቂት እንኳን ከእንቅልፋቸዉ አላበነናቸውም።

    በነገራችን ላይ፥ ብልጡ ደርግ በጠዋቱ ሊያወርዳቸው፣ ማታ ያሳየው የወሎ ሕዝብ እልቂት፥ በአንድ በኩል የንጉሡ ውሻ በጮማ ሥጋ ሲጫወት፣ በሌላ በኩል ደግሞ በረሃብ በተረፈረፈ ሕዝብ ውስጥ ሕፃን ልጅ የሞተች እናቷን ጡት ስታጠባ የሚያሳየዉን የጆናታን ዲምበልቢ (Jonathan Dimbleby, “The Unknown Famine”) ፊልም ነበር። ያንን ፊልም ደርግ በቅድሚያ ንጉሡና የኢትዮጵያ ሕዝብን እንዲያዩ ስለጋበዘ ቴሌቪዥን ያልነበረን የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በስድስት ኪሎና አራት ኪሎ አካባቢዎች ያሉትን ቡና ቤቶችን አጣብበን ስንመለከት ነበር። የንጉሡ ደጋፊዎች እንኳ ጃኖሆይ እንዲህ ጨካኝ ነበሩ እንዴ? የሚሉትን ይዘን ወደ ዶርማችን እንደገባን ትዝ ይለኛል። ምናልባት ከእንቅልፋቸው የነቁት በማግስቱ የደርግ አባላቱ በኩምቢ ቮልስዋገን ከቤተ መንግሥታቸው ወደ አራተኛ ክፍለ ጦር ሲወስዷቸው በሠሩባቸው ድራማ ይመስለኛል። ብልጣብልጦቹ ደርጎች የተጠቀሙት ቮልስ መጀመሪያ መስኮቷ ዝግ ነበር ይባላል።

    ንጉሡ ከውጭ ብዙ ሰው ሲጮህ ተመልክተው፥ “እናንተ ልጆች የሚወደን ሕዝባችን ንጉሤን የት እየወሰዳችሁ ነው እያለ ነዉ” ሲሉ፥ ብልጦቹ ደርጎችም መስኮቱን ከፍተው የሕዝቡን ድምፅ ሲያሰሟቸው ጩኼቱ “ተፈሪ ሌባ፤ ተፈሪ ሌባ” የሚለውን ሰምተው፥ “አይ ኢትዮጵያ ይኼን ያክል በድዬሻለሁ እንዴ?” አሉ ይባላል። በዚህ ሽኝታቸው ድሮ ቤተ ክርስቲያን ሲሄዱ ዳቦ የሚጥሉላት ለማኝ ዳቦዋን ስትጠብቅ፥ ‘ንጉሡ ወረዱ፤ ንጉሡ ወረዱ’ ሲባል ሰምታ፥ ‘ለዚህ ያበቃኸኝ አንተ ነህ!’ ብላ በቮልሷ አቅጣጫ የወረወረችው ዳቦ ብቻ ነበር ይባላል። የንጉሡ ሬሳም ከ17 ዓመታት በኋላ ከመንግሥቱ ኃይለማርያም ሽንት ቤት ሥር ተቆፍሮ እንደተገኘ ይታወቃል። እዚህ ላይ ልብ አድርገን ማለፍ ያለብን የፖለቲካ ቁም ነገር ለ60 ዓመታት ገደማ (የአምስት ዓመቱ የጣሊያን ወረራ እንዳለ ሆኖ) በፈላጭ ቆራጭነት ኢትዮጵያን ሲገዙ የሀገረ መንግሥታቸው ግንባታ ፕሮጀክት በአጉል ምክርም ይሁን በራሳቸው ገታራ አቋም ከሽፎ ሽኝታቸው በለማኟ ዳቦ፣ ቀብራቸው ደግሞ በአሳደጓቸው ወታደሮች ሽንት ቤት ሥር መሆኑ ነው።

    3) አብዮቱ እና የደርግ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ሙከራ

    አዲስቷን ኢትዮጵያን ለመፍጠር ሕዝባዊ አብዮቱ ልዩ ዕድል ፈጥሮ ነበር። አብዮቱ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ማኅበረሰቦች የመጡ የአዲሱ ትዉልድ ምሁራን ድጋፍና ተሳትፎ ነበረው። እንደ አብዮቱ መሪ ወደፊት የመጣውን መንግሥቱ ኃይለማርያምም ‘ቪቫ መንግሥቱ፣ ቪቫ መንግሥቱ!’ ብለን ተቀብለን ነበር።

    የኢትዮጵያ አብዮትን አብዮት ያደረገው የጭሰኝነት ሥርዓትን ያስወገደውና የደርግ እርምጃ (ውለታው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ቢሆንም) እስከዛሬ በኢትዮጵያ የሕዝቦች የትግል ታሪክ ውስጥ ልዩ ሥፍራ አለው ብዬ ባምንም፥ ነገሮችን በቶሎ የሚያዩ ወጣቶች “ተፈሪ ማረኝ፤ የደርጉ ነገር አላማረኝ ” ማለት የጀመሩት ብዙዉም ሳይቆዩ ነበር። በአጭሩ ለማስቀመጥ፥ የደርግ የሥልጣን ፍቅር፣ የመኢሶንና የኢህአፓ አሳዛኝ ክፍፍል፣ የኤርትራ ግንባሮችና የህወሓት የተናጠል የፖለቲካ ፕሮጀክቶች በአብዮቱ መፈንዳት የተፈጠረውን ልዩ ታሪካዊ ዕድል አምክኖታል።

    ደርግ መሃይምነትና የሥልጣን ፍቅር ስለተደባለቀበት፥ የሶሻሊስት አብዮቱን እንደሰው ማሰርና መግደል ወሰደው። በዚህ ሶቭዬት ህብረት ድረስ ሄዶ የሌኒን ሐውልት አይተው የመጡት ባለሥልጣኖቹ ስለሶሻሊዝም የተማርነው ከበሰበሰ ከቡርዧ ቤተ መፃሕፍት ሳይሆን ከምንጩ ከሌኒን ሀገር ነው እያሉ ተዘባበቱ። ካደሬዎቻቸው ድንቅ የሶሻሊስት ዕውቀታቸውን ከፍተኛነት ለማሰየት በሚመስል መንገድ የስታሊን ቀይ በትር ሥራ ላይ ይዋል አሉ። ደርግ የሱማሌ ወረራን፣ የኤርትራ ግንባሮችና የህወሓት እንቅስቃሴዎች በኢትዮጵያ አንድነት እንዲነግድ ልዩ ሁኔታ ስለፈጠሩለት “አብዮታዊት እናት ሀገር፥ ወይም ሞት!” አለ።

    ከኤርትራ ግንባሮች እስከ ኢህአፓ እና መኢሶን (ኢጭአት/ ኦነግን ጨምሮ ሌሎች ድርጅቶች እዚህ መሃል ናቸው) የኢትዮጵያ ሕዝቦች የአንድነትና የአብዮት ጠላቶች ሆነው ልዩ ልዩ ስሞች ተለጣፈበቸው። በአጭሩ የኢህአፓና መኢሶን መከፋፈልም ደርግን ብቻኛ የሀገር አንድነትና የአብዮት ተወካይ አደረገው። ሌሎች ዝርዝሮችን ትቼ ለኢትዮጵያ አንድነትና አብዮት ግንባታ ወሳኝ የሆኑ እርምጃዎችን ላንሳ።

    የደርግ የመጀመሪያው ሊቀ መንበር አማን አንዶም የሚባሉ ኤርትራዊ ጀኔራል ነበሩ። የደርግ ሊቀ መንበር ተብሎ ከደርግ ውጭ የተመረጠትም ለኢትዮጵያ አንድነት ብሎ እስከ ሞቃዲሾ ድረስ ሄዶ ካልተዋጋሁ ብሎ ንጉሡን ያስቸገሩ መኮንን ስለነበሩ ነዉ። በወታደሮቹ ዘንድም ተወዳጅ ስለነበረ በራሳቸው በደርግ አባሎቹ ጥያቄ መጀመሪያ መከላከያ ሚኒስቴር፣ ከዚያም ከደርግ ውጭ የደርግ ሊቀ መንበር የሆነው የተመረጡትና በአደባባይ እስከሚታወቀውም በኢትዮጵያ አንደነት ላይም (መቼም በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ልዩ ፍቅር አለን የሚሉ ብዙ ቢኖሩም፥ ፍቅራቸውን የሚለካልን መሣሪያ በሜዲካል ሳይንስ እስካሁን አልተፈጠረልንም) ምንም ዓይነት ጥያቄ ያልነበራቸውና የኤርትራን ችግር በሰላም ለመፍታት አሥመራ ድረስ ሄዶ ሕዝቡን ያወያዩ ነበሩ። ለኢትዮጵያ ልዩ ፍቅር አለኝ የሚሉ እነሻለቃ መንግሥቱ ኃይለማርያም ግን ጠረጠሯቸዉ፤ በታንክ እቤታቸው ውስጥ ገደሉት። በእኔ ግምት ውጤቱ የኤርትራና የኢትዮጵያን አንድነት መግደል ነበር። በዚህም ኤርትራ የደም ምድር ሆነች። ዛሬ እንዲህ ልንሆን የፈሰሰው የሰው ደም ዋጋም ሆነ ለጠፋው ሀብትና ንብረት ሂሳብ ለፈረደበት ታሪክ መተው ይመረጣል።

    የብሔራዊ አንድነት መንግሥትን ልታመጡብኝ ብሎ መንግሥቱ ኃይለማርያም ሁለተኛውን የደርግ ሊቀ መንበር የነበሩትን ጀኔራል ተፈሪ በንቲን ከደጋፊዎቻቸው የደርግ አባላት ጋር ረሸናቸው።

    ኮሎኔል አጥናፉ አባተንም ቅይጥ ኢኮኖሚ ልታመጣብን ነው ብሎ መንግሥቱ ኃይለማርያም በፀረ-አብዮታዊነት ረሸነዉ። በነገራችን ላይ የመጨረሻ ጭንቅ ሲመጣ መንግሥቱ ኃይለማርያም የአጥናፉን ቅይጥ ኢኮኖሚ ላይ ለመንጠላጠል ሞክሮ ነበር።

    በዛሬው የኦሮሞ ፖለቲካ ውስጥ ልዩ ሥፍራ ያላቸው ጀኔራል ታደሰ ብሩ ለሁለተኛ ጊዜ ሞት ተፈርዶባቸው ተረሸኑ። እኔ መከታተል እስከቻልኩ ድረስ ታደሰ ብሩ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ፍጹም ጥያቄ ያልነበራቸው፤ ለኢትዮጵያ ብሎ ከሰላሌ ጫካ እሰካ ሞቃዲሾ ድረስ ተወስደው የታሰሩ እንግሊዞች ኢትዮጵያን ነፃ እናወጣለን ብለው ሲመጡ ከነሱ ጋር እየተዋጉ የመጡ አርበኛ ነበሩ። ከተራ ወታደርነት እስከ ጀኔራል ማዕረግ ድረስ ሀገራቸውን ያገለገሉም ነበሩ። እግር ጥሏቸው አብዮቱ ውስጥ የገቡት መንግሥቱ ኃይለማርያም ያላርህራሄ ገደሏቸዉ። በነገራችን ላይ ከጀኔራል ታደሰ ብሩ ጋር በፀረ አንድነት ክስ የተገደለ፣ ብዙ ሰው የማያስታውሰው መለስ ተክሌ የሚባል በቀ.ኃ.ሥ ዩኒቨርሲቲ ከተማሪ መሪዎች አንዱ የሆነ የትግራይ ተወላጅ ነበር (በጊዜዉ ከነበረዉ አቋም ተነስቼ፥ ይህ ሰው ቢቆይ ኖሮ የትኛው ድርጅት ውስጥ ሊገባ እንደሚችል ዶክተር አረጋዊን ደግሜ መጠየቄን አስታውሳለሁ)። ይህ ሰዉ ሌላ ተከታይ ቢያጣ ለሩብ ምዕተ ዓመት አከባቢ የምኒልክ ቤተ መንግሥትን ተቆጣጥሮ በፈላጭ ቆራጭነት ሀገሪቷን የገዛው ለገሠ ዜናዊ ስሙን አንስቶ ትግራይ በረሃ ገብቷል። ይህም ደርግ በኢትዮጵያ አንድነት ስም ያመጣብን የታሪክ ዕዳ ነው።

    በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ምንም ዓይነት ጥያቄ እንዳልነበራቸው በተሻለ የማውቃቸውን የመኢሶን መሪዎችን ላንሳ። ለሥልጣን ተብሎ በደርግና ብዙ የፖለቲካ ተቀናቃኞቹ ዘንድ እንደ ኦሮሞ ድርጅት፥ በኦሮሞ ደግሞ እንደነፍጠኛ ድርጅት የሚታየው መኢሶን በዘመኑ በየትኛውም ሚዛን የተሻለ ትምህርት የነበራቸው መሪዎች ነበሩት፤ በስብጥራቸውም ኤርትራዊ የዘር ግንድ አላቸው ከሚባሉት ኅሩይ ተድላ እና አበራ የማነአብ እስከ ሲዳማው እሼቱ አራርሶ የነበሩበት ነው። ሽኩሪ የሚባል አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አብረን የነበርነው ልጅ በስተቀር ሰፊ ተሳትፎ እንደልነበራቸዉ የማዉቀዉ የሱማሌ ምሁራንን ብቻ ነበር።

    የመጀመሪያዉ የመኢሶን ሊቀ መንበር የሰሜን ሸዋ አማራ ከሚባለው የተወለዱ፥ ዶ/ር ወርቁ ፈረደ፣ ሁለተኛው ኃይሌ ፊዳ፣ ሦስተኛው የወሎ አማራ ከሚባለው የመጡ ዶ/ር ከበደ መንገሻ ነበሩ። ሕብረ ብሔር ነን፤ ለሀገረ- መንግሥት ግንባታው የተሻለ ግንዛቤም እዉቀትም አለን ለሚሉ የመኢሶን ምሁራንም ደርጎች ርህራሄ አላደረጉም። በተለይ የመጀመሪያው የኦሮሞ የምሁር ትዉልድ የሚባሉት ኃይሌ ፊዳን ጨምሮ አብዱላህ ዩሱፍ፣ ዶ/ር ከድር መሀመድ፣ ዶ/ር ተረፈ ወልደፃዲቅ፣ ዶ/ር መኮንን ጆቴ የመሳሰሉት ሕበረ ብሔር በሚባለው መኢሶን ውስጥ አልቀዋል። በእኔ እምነት ብዙዎች ሊቀየሙኝ ቢችሉም፥ እንደስማቸው በኢትዮጵያ ምድር ሕብረ ብሔር የነበሩ ድርጅቶች መኢሶንና ኢህአፓ ብቻ ነበሩ። አላስፈላጊ ክርክር ዉስጥ ሳልገባ፥ እኔ እስከ ማምነው ድረስ ኢሠፓ የወታደሮች ፓርቲ ነበር። የኢህአዴግን ምንነት ለብልጽግና አበላት እተዋለሁ። የብልጽግናን ምንነት ደግሞ የታሪክ ፈተናዉን ሲያልፍ ብንነጋገርበት የተሻለ ይመስለኛል።

    ደርግ ሕበረ ብሔር ድርጅቶችን በቀላሉ አንድ በአንድ ቀርጥፎ በላቸው። ኢህአፓን ቁርስ አደረገ፤ መኢሶንን ምሳ አደረገ:: ብሔር ሆኖ ለመውጣት ገና ዳዴ የሚሉትን ወዝሊግንና ማሌሪድን እራት አደረጋቸው። ከደርግ ዱላ የተረፉት በደርግ አስተዋጽኦ ጭምር በተሸለ ሁኔታ ኃይል ሆነዉ የወጡት የብሔር ንቅናቄዎች ናቸው። ኢጭአት (የኢትዮጵያ ጭቁኖች አብዮታዊ ትግል) ወደ ኦነግ ተጠቃልሎ ገብቶ ዛሬ የምናውቀው ኦነግን ፈጠረ። የሱማሌ ድርጅቶች ኦብነግ ዓይነትን ፈጠሩ። የሲዳማ አርነት ንቅናቄ ቢያንስ ዋናው ክንፍ ዛሬ ሲአን (የሲዳማ አርነት ንቅናቄ) የሚለው ሆነ። አፋሮችም የአፋር ግራ ክንፍ አርዱፍ እያሉ በሕይወት ያሉ ድርጅቶች አሏቸው። በጣም የተሳካላቸው የብሔር ንቅናቄዎች በኢትዮጵያና ኤርትራ ላይ ደርግን ለሁለት ቀብረው መንግሥታት ሆኑ።

    የደረግ ዘመንን ስናጠቃልል መረሳት የሌለባቸው ሦስት ዋና ዋና ጉዳዮች፥ ለሥልጣን ብሎ ደረግ ባካሄዳቸው ጦርነቶች፡-

    የሀገረ-መንግሥት ግንባታውን የበለጠ አወሳስቦ መሄዱን፣
    ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በፃፉት መጽሐፍ በትክክል እንዳስቀመጡት፥ ደርግ ትቶት የሄደው በደም እምባ የታጠበች ሀገር መሆንዋን፣
    በሀገር አንድነት ስም ባካሄደው ትርጉም-የለሽ ጦርነት የባከነው የሀገር ሀብት ብቻ ሳይሆን በዓለም ትልቋ ወደብ-አልባ ሀገር ኢትዮጵያን ትቶ መሄዱን ነዉ።

    ደርግ ለ17 ዓመታት የተጫወተዉ የአጥፍቶ መጥፋት ፖለቲካን እንደ ኑዛዜም፣ እንደ ቁጭትም የደርግ ከፍተኛ ባለሥልጣን የነበሩት ኮሎኔል ፍስሃ ደስታ (ኮ/ል መንግሥቱ ኃይለማርምም ሆነ ሻምበል ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ እድፋቸውን ከታጠቡበት በጣም ይሻላል) በፃፉት መጽሐፍ ልዝጋ።

    የኢህአፓ ወጣቶችን የትግል ስሜት፣ የመኢሶን መሪዎች ዕውቀትና የእኛን የወታደሮቹን የሀገር ወዳድነት ብንጠቀምበት ኖሮ ሀገራችን እንዲህ አትሆንም ማለታቸውን እስር ቤት ሆኜ ማንበቤ ትዝ ይለኛል። ምክራቸው ለጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይም የሚሆን ይመስለኛል። በነገራችን ላይ በታሪክ አጋጣሚ ወደ አስር ወሮች ገደማ በኢህአዴግ እስር ቤት የተኛሁበት አልጋ ኮ/ል ፍስሃ ደስታ ይተኙበት እንደነበረ ሰምቻለሁ።

    4) የኢህአዴግ ዘመን የሀገረ-መንግሥት ግንባታ

    ለአራተኛ ጊዜ የሀገራችን ፖለቲካን ማሰልጠንና የተሻለ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ዕድል ያመለጠን የኢህአዴጉ ዘመን ነው (ይህ የመለስ እና የኃይለማርያም ዘመንን ይጨምራል)። የኢህአዴግ ዘመን ሌላው ቢቀር የብሔረሰቦች ጥያቄን ለሁሉም ሕዝቦች ተቀባይነት ባለው መንገድ ይመልሳል ብሎ (እኔን ጨምሮ) የጠበቁ ብዙ ናቸው። ይህም ለሀገረ-መንግሥት ግንባታ የተሻለ ዕድል ይፈጠራል ተብሎም ተገምቶ ነበር።

    ገና የሽግግር መንግሥቱ ሲመሠረት፥ የኢህአዴግ ባለሥልጣናት እንደግል ሠርጋቸው የፈለጉትን ጠርተው፣ ያልፈለጉትን በመተው የሠሩት የፖለቲካ ቲያትር ጫካ ሆነው ስደግፋቸው ከነበሩት የኢህአዴግ መሪዎች ተለየሁ። እኔም ብቻ ሳልሆን ብዙ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ጓደኞቼ በዚህ ጊዜ የተለዩዋቸዉ ይመስለኛል። ኢህአዴግ መጀመሪያ በጦርኛነት፤ ቀጥሎ ደግሞ በዘመኑ ቋንቋ የሽብርተኝነት ታርጋ እየለጠፈ ለ27 ዓመታት ሕዝብና ሀገርን አመሰ። ዝርዝር ነገሮች ውስጥ ሳልገባ፥ በኦሮሚያ እና በሱማሌ ክልሎች፤ በሲዳማ፣ በሀዲያ፤ በወላይታ፣ በጋምቤላ፣ በአፋር፣ ቁጥራቸውን የኢህአዴግ ባለሥልጣናት እንኳ የማያውቁት ሕይወት ጠፋ። የአፍሪካ መዲና የምትባለው አዲስ አበባ/ፊንፊኔም ሆነች የኢህአፓን ጠበል በቀመሱ ብአዴኖች የሚመራው የአማራ ክልልም ውሎ አድሮ ከኢህአዴግ ዱላ አልተረፉም።

    በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ርዕዮተ ዓለም (ነገርየው መሬት ላይ ሲፈተሽ፥ የአብዮታዊነትም የዴሞክራሲያዊነትም ባህርይ አልነበረውም) የተተበተበው የሞግዚት አስተዳደር እውነተኛ የፌዴራል ሥርዓት ሊሆን አልቻለም። የሕዝቦችን እራስን በራስ ማስተዳደር ጋር ምንም ግንኙነት ያልነበረው፥ ጆርጅ ኦርዌል የእንስሳት እርሻ (George Orwell, “Animal Farm”) በሚለዉ መጽሐፉ ላይ፥ ሁሉም እንስሶች እኩል ናቸው፤ አንዳንድ እንስሶች የበለጠ እኩል ናቸው “All animals are equal, but some are more equal than others” ከሚለው ያለፈ የፖለቲካ ፋይዳ አልነበረውም። ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ተብዬዎቹም ከ97ቱ በስተቀር ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መፍጠር ይቅርና ቅርጫ እንኳ ሊ ሆኑ አልቻሉም። ዉጤቱም ዴሞክራሲያዊ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ዕድል መጨናገፉ ብቻም ሳይሆን ለ27 ዓመታት ውድ የሕይወት ዋጋ ጭምር ሲያስከፍለን ኖሯል። በዚህም ምክንያት የታሪክ ጣጣችንን አስተካክለን በእኩልነት ላይ የተመሠረተ ዴሞክራሲያዊ ፌዴራሊዝም የመፍጠር ተስፋችን ሕልም ሆኖ ቀርቷል።

    5) በማምለጥ ላይ ያለ አዲስ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ሙከራ

    አሁን እየገጠመን ያለውን የታሪክ ፈተናን ለማለፍ፥ ጨክነን በቁርጠኝኘት ብሔራዊ መግባባት ውስጥ መግባት ወይም ኢትዮጵያን እንደ ሀገረ-መንግሥት የምታበቃበት የሚጨምር ቀውስ ውስጥ መግባት ይመስለኛል። እዚህ ላይ የሌሎች ሀገሮችን ፖለቲካ በድኅረ ቅኝ ግዛት ዘመን ብቻ እንኳን በመቀኛት ብጀምር፥ ችግሮቻቸውን ለመፍታት በቁርጠኝነት የሠሩት ተሳክቶላቸዋል። ያንን ያልቻሉት ወይ ፈርሰዋል ወይም አሁንም በቀውስ ውስጥ እየዳከሩ ነዉ። ቅኝታችንን በላቲን አሜሪካ ብንጀምር፥ ቀዉስ ገጥሟቸዉ አነ አርጀንቲና፣ ቺሌ፣ ፔሩ፣ ኒካራጓ፣ ኮሎምቢያ የመሰሰሉ ሀገሮች በተለያየ ደረጃ ፖለቲካቸውን ያስተካከሉ ሀገሮች ናቸው። ከ60 ዓመታት በላይ ለልዕለ ኃያሏ አሜሪካ ሳትበገር በአሜሪካ አፍንጫ ሥር የኖረችው አስደናቂዋ ሶሻሊስት ኩባና በአሜሪካ ጣልቃ ገብነት ምክንያት አሁን በሁለት ፕሬዝዳንቶች የምትገዛዋ ሶሻሊስት ቬኔዙዌላም በዚሁ ክፍለ ዓለም ይገኛሉ። በአውሮፓ ፖርቹጋል፣ ስፓኝ፣ ግሪክ፣ ፖለቲካቸዉን ማስተካከል ችለዋል። ዩጎዚላቪያ ውድ ዋጋ ብትከፍልም ከመፍረስ አልደነችም። ሶቭዬት ህበረትና (ግማሽ አውሮፓ ነች) ቼኮዝላቫኪያ በሰላማዊ መንገድ ፈርሰዋል። በኤዥያ፥ ኔፓል የፓለቲካ ችግርዋን በብሔራዊ መግባባት ስትፈታ፥ፓኪስታን፣ ቬየትናም፣ ካምቦዲያና ላኦስ ደግሞ ችግሮቻቸውን በጦርነት ፈተዋል። አፍጋኒስታን፣ ኢራቅ፣ ሶሪያና የመን አሁንም እየቀወሱ ነው። ወደ አፍሪካችን ስንመጣ፥ ደቡብ አፍሪካና ጋና ከመሳሰሉት በስተቀር አብዘኛዎቹ በይስሙላ ምርጫ ላይ የተመሠረቱ አምባገነን መንግሥታት ሲሆኑ፥ የአፍሪካ ሕብረትም የዲክታተሮች ማኅበር (trade union of dictators) ከመሆን አላለፈም (በኢህአዴግ ጊዜ የተከሰስኩበት አንዱ ወንጀሌ የአፍሪካ መሪዎችን ተሰደብክ የሚል ነበር)። ሱማሊያና ሊቢያ ፈረንጆች የወደቁ መንግሥታት (failed states) የሚሏቸው ሲሆኑ፤ ሩዋንዳ ጊዜውን ጠብቆ የሚፈነዳ ሌላ ቦንብ የምትጠብቅ ይመስለኛል።

    በዚህ የአፍሪካ ፖለቲካ ምስቅልቅል ጉዞ ውስጥ አንዱ የሚገርመኝ ላለፉት 60 ዓመታት ፖለቲካቸውን ማስተካከል አቅቷቸው በቀውስ ሲናጡ የኖሩ ሁለት ሀገሮች፥ በተፈጥሮ ፀጋ እጅግ ሀብታሟ የኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፑቢሊክና የሦስት ሺህ ዓመታት ዕድሜ አለኝ የምትለዋ ድሃዋ ኢትዮጵያ መሆናቸው ነው።  ከንጉሡ ዘመን ጀምሮ ይህንኑ የሀገራችንን የፖለቲካ እንቆቅልሾችን የተከታተለ፣ ያጠና፣ ያስተማረና ብዙ ጽሑፎችን የፃፈበት ጆን ማርካከስ (John Markakis) የሚባል ፈረንጅ፥ የታሪክና ፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፌሴር “Ethiopia: The Last Two Frontiers” (የኢትዮጵያ፥ የመጨረሻዎቹ ሁለት ድንበሮች) ብሎ ፅፏል። ምሳ ጋብዞኝ መፅሐፉን ለዶ/ር ዓቢይ ስጥልኝ ብሎኝ፥ ዶ/ር ዓቢይ ያንብበው አያንብበው ባላውቅም፥ እሳቸውን ማግኘት ለሚችል ለኦፒድኦ ባለሥልጣን ልኬላቸው እንደነበርም አሰታዉሰለሁ። መፅሐፉ በአጭሩ የኢትዮጵያ መሪዎች የሀገረ-መንግሥት ግንባታ የንጉሦቹ ሞዴል (the Imperial model) ፣ የደርግ የሶሻሊስት ሞዴልና የኢህአዴጉ ፌዴራሊስት ሞዴል በሙሉ ከሽፈዋል ይላል። የከሸፉበትም ዋናዉ ምክንያት የባለጊዜ ገዥዎችን ሥልጣን ለማሳካት የተገፋበት መንገድ የኢትዮጵያ ሕዝቦችን እኩልነት ያላጎናፀፈና የልማት ጥማታቸውንም ያላረካ በመሆኑ ነው ይላል።

    ይህ የፈረንጅ ምሁር እንዳለው፥ ፖለቲካችንን ማሰልጠን ባለመቻላችን ሚሊየኖች ሕይወታቸውን አጥተዋል፤ ሚሊዮኖች ከቀዬያቸው ተፈናቅለዋል፤ ሚሊዮኖችም ተሰደዋል። እኔም ከላይ ባነሳሁት ከዚሁ ምሑር ዕይታ ተነስቼ ሀገራችን ስለገባችበት የፖለቲካ ቅርቃርና በብሔራዊ መግባባት አንፃር ከቅርቃሩ ለማውጣት በሌኒን ቋንቋ ምን መደረግ አለበት (What is to be done?) የሚለውን መሠረታዊ ጥያቄ የሀገራችን ፖለቲካ እስከገባኝ ድረስ ልመልስ።

    1. መሠረታዊ ችግራችን በታሪክ አጋጣሚ ሥልጣን ላይ የወጡ መሪዎቻችን ሀገርን የመምራት ሕልማቸው፤ ሥልጣንን ጨምድዶ ከመቆየት ሕልማቸው ጋር ሁሌ ስለሚጋጭባቸው ነው። ለሕዝብ አለን ከሚሉት ፍቅር የሥልጣን ፍቅራቸው ስለሚበልጥባቸው ነው። ለዚህ ነው ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ የሚወደንና (ሕዝቡ ምን ያከል እንደሚወደቸዉ እንዴት እነዳወቁ ባናዉቅም) የምንወደው ሕዝባችን ሲሉ ኖረው ለ60 ዓመታት ገደማ የገዟትን ኢትዮጵያ ለ20ኛዉ ክፍለ ዘመን ሳያበቁ ከዓለም ሀገሮች ጭራ ደረጃ ትተዋት የሄዱት። የሕዝብ ፍቅራቸውንም ደረጃ በረሃብ በመቶ ሺህዎች ያለቀው የወሎ ሕዝብ ይመሰክራል። ይህን የመሳሰሉ የመሪዎቻችን ባዶ የሕዝብና የሀገር ፍቅር፥ የንጉሡ ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ፣ የመንግሥቱ ኃይለማርያም አብዮታዊት እናት ሀገር ወይም ሞት የመለስ ዜናዊ በቀን ሦስት ጊዜ የሚመገቡ ዜጎችን እፈጠራለሁ ወ.ዘ.ተ መሸፈን አይችልም። ለዚህ አሁን ያሉ መሪዎቻችንም ሆኑ ተስፈኛ መሪዎች ይህንን የታሪክ እውነታ በውል እንዲገነዘቡት እፈልጋለሁ።
    2. የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችና የተቀሩት ልሂቃን በተለያየ ደረጃ የሚጋጩ ሕልሞቻቸውን ይዘው መጓዛቸው ነው። ከመኢሶንና ኢህአፓ ዘመን እስከዛሬ ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶቻችንና መሪዎቻቸው ይህንን እውነታ በውል መገንዘብ ይኖርባቸዋል። የሕልሟን ጉዳይ በፈንጆቹ አባባል ከዜሮ ድምር ፖለቲካ (zero-sum game politics) የመውጣቱን ጉዳይና የፖለቲካ ፍላጎቶቻቸዉን በገደብ የማድረጉን ነገር በጥብቅ እንዲያስቡበት እመክራለሁ። ዋና ጉዳያችን ሥልጣን ሆኖ ከፊንፊኔ እስከ መቀሌ ባንዳ፣ ባንዳ እየተባባሉ መካሰሱ ሕዝባችንን ከማደናገር በላይ ብዙ የፖለቲካ ትርፍ የለውም። ዛሬ በአሜሪካና በአውሮፓ በሚደረጉ ሰልፎች ላይ በአንድ እጅ እስክንድር ነጋ ይፈታ፣ በሌላ እጅ ጃዋር ሽብርተኛ ነው የሚሉት መፈክር ዓይነቶቹ ለሀገረ-መንግሥት ግንባታችንም ሆነ ለብሔራዊ መግባባት ሥራችን ብዙ የሚጠቅሙ አይመስሉኝም። በእኔ በኩል እንዲህ ዓይነቱ ጉዳይ ስላስቸገረኝ ነበር በ2008 በፃፍኩት መፅሐፍ ላይ ለቡዳ ፖለቲካችን መላ እንፈልግ ብቻ ሳይሆን የሚጋጩ ሕልሞች ሊታረቁ ወይስ ኢትዮጵያን ሊያፈርሱ በሚል ግልፅ ጥያቄ የደመደምኩኝ። ለእኔ መፍትኼው ለአዲስቷ ኢትዮጵያ ፈጠራ የሚሆን አዲስ ማኅበራዊ ውል (new social contract) ከመፈራረም ውጭ የተሻለ የማጂክ ፎርሙላ ያለን አይመስለኝም። ይህንን እውነታ የምኒልክ ቤተ መንግሥት ያሉ የብልጽግና ወንድሞቻችንም ሆኑ ከአዲስ አበባ/ፍንፍኔም እስከ አውሮፓና አሜሪካ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ግፋ በለው የሚሉ ሁሉ እንዲረዱልኝ አደራ እላለሁ። በቅርብ ጊዜ በተፈጠረው ቀውስ በሁሉም በኩል ላለቁትም የተሻለ የሐዘን መግለጫ የሚሆነውና ዕንባቸውን የሚያብሰው የችግሮቻችን ምንጭ አዉቀን ዘለቂ መፍትኼ ስንፈልግ ይመስለኛል።
    1. ከላይ ካነሳኋቸው ሁለት ነጥቦች ጋር ተያይዞ ሺህ ጊዜ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ እየተባለ በሕዝብ ላይ የሚሠራዉ የፖለቲካ ትያትር መቆም አለበት።
      የንጉሡ ዘመን የምርጫ ትያትሮች፣ የደርግ ዘመን የምርጫ ትያትሮች፣ የኢህአዴግ ዘመን የምርጫ ትያትሮች በግልፅ ቋንቋ ለማስቀመጥ፥ ሲያንሱ በዴሞክራሲ ስም የተቀለዱ  ቀልዶች፣ ሲበዙ ደግሞ በኢትዮጵያ ሕዝቦች ላይ የተሠሩና ታሪክ ይቅር የማይላቸው ወንጀሎች ነበሩ። በሰለጠነው ዓለም የሕዝብን ድምፅ ከመስረቅ በላይ ወንጀል የለም። እዚህ ላይ ሁለት ነገሮችን አስታውሼ ልለፈው። በ“ኢህአዴግ-1” ዘመን አቶ በረከት፥ “ኢህአዴግ ከስድስት ሚሊዮን በላይ አባላት አሉትና በዝረራ ያሸንፋል” ብሎ ሲያስቸግረኝ፤ አቶ በረከት፥ “ኢህአዴግ ሁለት ምርኩዞች አሉት፤ አንደኛው ምርጫ ቦርድ ነው። ሁለተኛው ጠመንጃችሁ ነው። ሁለቱን ምርኩዞቻችሁን አስቀምጣችሁ ተቃዋሚዎችን ካሸነፋችሁ፥ እኔ በግሌ እናንተ የምትሉትን 20 ና 30 ዓመታት ብቻ ሳይሆን ለሃምሳ ዓመታት እንድትገዙን እፈርምልሀለሁ” እንዳልኩት አሰታዉሰለሁ። በ“ኢህአዴግ-2” ጊዜ ደግሞ ዶ/ር ዓቢይ በጠሩት ድንገተኛ ስብሰባ ላይ ገለልተኛ የሆነው ጠቋሚ ኮሚቴ ስምንት ሰዎች አጣርቶ ስላቀረበ አራት ሰዎች መመረጥ ስላለባቸው በተጠቆሙት ሰዎች ላይ አስተያየት ስጡ አሉን። ሌሎች ስብሰባው ላይ የተገኙ የየድርጅት መሪዎች ያሉትን ብለዋል፤ እኔ ጨዋታው ስላላማረኝ፥ “አብዛኛዎቹን ዕጩዎች ብዙዎቻችን አናዉቃቸውምና ከየት እንደመጡ እንኳ ለማወቅ የ24 ሰዓት ጊዜ ስጡኝ” ብዬ አጥብቄ ጠየኩኝ። ዶ/ር አቢይ ‘አይቻልም’ አሉ። ነገ የምናገረው እንዳይጠፋኝና ለታሪክም ቢሆን ተአቅቦ (reservation) መዝግቡልኝ ማለቴ ትዝ ይለኛል። ምስክሮችም አሉኝ። የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መጥቶ የምርጫ ቦርድ ኃላፊዎች የምርጫ ጊዜውን ሰሌዳ ለማስተላለፍ በጠሩት የምክክር ስብሰባ ላይ እንደተናገርኩኝ፥ መለኮታዊ ጣልቃ ገብነት (divine intervention) ነው እንዳልኩኝ ምርጫው ባይተላለፍ ኖሮ የአዲሱ ምርጫ ቦርድ አካሄድ ሌላ ከበድ ቀውስ ሊያስከትል ይችል እንደነበረ ዛሬ ላይ ሆኜ በእርግጠኝነት መናገር እችላለሁ። ይህንኑ ደግም ብዙ ጊዜ በታጋይነቷ ለምናውቃት ክብርት ብርቱካንም ጭምር መናገሬን አስታውሳለሁ።

    ስለሆነም የሚመጣውን ምርጫ አዲስቷን ዴሞክራትክ ኢትዮጵያ እንድትወለድበት ካላደረግን፥ የንጉሥ የማክያቬሊ ምክር፣ የመንግሥቱ ኃይለማርያም፣ የጆሴፍ ስታሊን ቀይ በትር፣ የመለስ ዜናዊ፣ የሊቀ መንበር ማኦ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ውሰት፣ ኢትዮጵያን ለመለወጥ የታሪክ ፈተናውን ለማለፍ እንዳላስቻላቸዉ፥ የዶ/ር ዓቢይም የመደመር የፖለቲካ ቀመር አዛውንቱ የፈረንጅ ምሁር የሚለውን የኢትዮጵያ ፖለቲካ የመጨረሻ ሁለት ድንበሮችን የሚያሻግረን አይመስለኝም። እሱን ካልተሻገርን ደግሞ ሁሌም እንደምለው ለሁላችንም የምትሆን ዴሞክራትክ ኢትዮጵያ የምትፈጠር አይመሰልኝም።

    ከማጠቃለሌ በፊት የብሔረታዊ መግባባቱ የፖለቲካ ጥረታችን ይሳካ ዘንድ መፍትሄ የሚሹ ቁልፍ ጉዳዮች ላስቀምጥ፦

    1. ያለ ሀገራዊ ስምምነት በዋናነት በአንድ ቡድን ሕልምና ፍላጎት (በተለይ የአንድ ቡድን ፍኖተ-ካርታ /road map/) የመመረቱ ጉዳይ ለዉጡን አጣብቂኝ ዉስጥ ማስገበቱን የማወቅ ጉዳይ፤
    2. ለውጡን ለማምጣት በዋናነት የላቀ አስተዋጽኦ ያላቸው ኃይሎች (ለምሳሌ እንደ ኦሮሞ ቄሮ ዓይነቶቹ) ወደ ዳር የመገፋታቸው ጉደይ፤
    3. ለውጡን እየመራ ያለው ከራሱ ከኢህአዴግ የወጣ ቡድን ቢሆንም፥ በለውጡ ምንነት፣ ፍጥነት፣ ስፋትና ጥልቀት ላይ የተለያዩ የኢህአዴግ ክንፎች ስምምነት ማጣታቸውና በዚህም ምክንያት እያመጣ ያለው አደገኛ ሁኔታ፤
    4. በሚጋጩ ሕልሞቻችን ምክንያት ላለፉት 50 ዓመታት መፍትሄ ያላገኘንለት የመከፋፈል ፖለቲካችን (political polarization) ጉዳይ፤
    5. ዴሞክራሲያዊ ለውጡ ለአብዛኛዉ የኢትዮጵያ ሕዝቦችና የፓለቲካ ኃይሎች ተቀባይነት ያለዉ፣ ሰላማዊና የተሳካ እንዲሆን የጋራ ፍኖተ-ካርታ (roadmap) የመቀየስ አስፈላጊነት ጉዳይና፤ የተቀየሰዉን በጋራ ሥራ ላይ የማዋል ጉደይ፤
    6. ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ማለት በእርግጥም በሕዝቦች ይሁንታ ላይ የተመሠረተ የፓለቲካ ጨዋታ መሆኑን የመረዳት ጉዳይ፤
    7. ሀገራችን እዉነተኛ ዲሞክራሲያዊ የፈድራል ሥርዓት ያስልጋታል ስንል፥ ከሕልሞቻችን በሻገር በሕዝቦቻችን ፍላጎት ላይ የተመሠረተ የፖሊቲካ ሥርዓት መሆኑን የማረጋገጥ ጉዳይ፤
    8. ብሔራዊ መግባባቱ በተሻለ መንገድ የሚሳካው፥ በደቡብ አፍሪካ እና ኮሎምቢያ በመሰሰሉት ሀገሮች እንዳየነው የፖለቲካ እስረኞችንና የጫካ አማፅያንን መጨመርን የማስፈለጉ ጉዳይ፤
    9. የተሳካ ብሔራዊ እርቅን ለመምጣት ከሥልጣን በሻገር የምር የፖለቲካ ቁረጠኝነት (political will) የማስፈለጉ ጉዳይ፤
    10. ስለኢትዮጵያ አንድነት ያለን ግንዘቤ ከፊታዉራሪ ሀብተጊዮርጊስ እይታ የሰፋና ለሀገሪቷ ያለን ፍቅርም ገደብ የማድረጉ ጉደይ ናቸዉ።

    በመደምደሚያዬም፥ እዚህ ያደረሰንን የሀገራችንን ፖለቲካ ጉዞ ታሪክ ወደኋላ እያየሁ፥ የወደፊቱን የሀገራችንን ዕጣ ፈንታንም እያማተርኩ ለጠቅላይ ሚኒስትሩም፣ ለሁላችንም የታሪክ የግርጌ ማስታወሻ ልተዉ።

    በቅርብ ቀን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‘ኢትዮጵያ አትፈርስም፤ ኢትዮጵያን የሚያፈርሷት እኛን ቀድሞ ሲያፈርሱ ነው፤ ኢትዮጵያን ለማፍረስ አይፈቀድላቸውም’ ሲሉ አዳምጫለሁ። ሀገርን ለመፍረስ የሚፈልጉ ኃይሎች መጀመሪያኑ ፈቃድ ይጠይቃሉ፤ አይጠይቁም የሚለዉን ክርክር ውስጥ ሳልገባ፥ በጨዋ ቋንቋ ንግግራቸውን አልወደድኩላቸውም። ንግግራቸውንም ተከትሎ የኢሳት ቴሌቪዥን የፖለቲካ ተንታኞች የሚታወቁ የአዛውንት ምሁርን በመጥቀስ (ይህኑን ምሁር መንግሥቱ ሀይለማርያምም ያዉቃል ብለን ስለተሠሩ የንጉሡ ባለስልጣኖች ምክር ጠይቀነዉ፥ ጠመንጃዉ በእናንተ እጅ ነዉ፤ የምን ምክር ትጠይቁናላችሁ ብሎኛል ማለቱን አንብቤአለሁ) ዶ/ር ዓቢይ ጥሩ ይዘዋል፤ ሕጉንም ሰይፉንም እየተጠቀሙ ነው ያሉት የበለጠ ሥጋት ፈጥሮብኛል። እዚህ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ሁላችንም ደጋግመን ማሰብ ያለብን ጨዋታው ከተበላሸ አብዛኛው ዓለምን በሰዓታት ውስጥ ወደ አመድነት የሚለወጥ ወይም ሕይወት-አልባ ሊያደርግ የሚችል የኒዩክሊየርር መሣርያ የታጠቀ፣ ነፍሷን ይማርና የሶቭዬት ህብረት ሠራዊት ዓይኑ እያየ ሀገራቸው መበቷን ነው። የሀገራችንን ፖለቲካ በጋራ አስተካክለን ሁላችንንም በእኩልነት የምታስተናግድ ዴሞክራቲክ ኢትዮጵያን ለመፍጠር እግዚአብሔር ይርዳን እላለሁ።

    ዋቢ መፃሕፍት:

    1. Bahiru Zewde (1991) A History of Modern Ethiopia, 1885 -1991.
    2. Gebru Tareke (1996) Ethiopia: Power and Protest, Peasant Revolts in the Twentieth Century.
    3. John Markakis, (2011) Ethiopia: The Last Two Frontiers.
    4. Merera Gudina, (2002) Ethiopia: Competing Ethnic Nationalisms and the Quest for Democracy, 1960-2000.
    5. Teshale Tibebu, (1995), The Making of Modern Ethiopia, 1896-1974.

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forumsላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    በኢትዮጵያ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ የታሪክ ዳራ… መረራ ጉዲና (ፕሮፌሰር)

    Semonegna
    Keymaster

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ እና ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን አስመረቁ

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ 34 የሕክምና ዶክተሮችን ጨምሮ ለሁለተኛ ዙር ያሰለጠናቸውን 1233 ተማሪዎቸ መጋቢት 5 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመርቋል።

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ በዋና ግቢው እና በዱራሜ ካምፓስ 6 ኮሌጆች በመጀመሪያ ዲግሪ፣ በሁለተኛ ዲግሪ እና በተከታታይ ትምህርት በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ነው ያስመረቀው።

    በምርቃቱ ሥነ-ሥርዓት ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የሳይንስና እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ፥ ኢትዮጵያ ለእርሷ እና ለዜጎቿ ክብር እና ፍቅር ያለው ባለሙያ ያስፈልጋታል ብለዋል። አክለውም ተመራቂዎች ያገኙትን እውቀት በተገቢው ሁኔታ ለማኅበረሰብ ለውጥ እንዲያውሉት አሳስበዋል።

    ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ መጠናቀቅ ድጋፋቸውን በማጠናከር የአገሪቱን ሉዓላዊነት እንዲያስረግጡም ዶ/ር ሳሙኤል ጠይቀዋል።

    የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሐብታሙ አበበ በበኩላቸው፥ ተመራቂዎች ያገኙትን እውቀት ወደ ተግባር በመቀየር ሙያዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። አሁን ላይ በሀገሪቱ በተለያየ መልኩ ከሚንፀባረቀው የአስተሳሰብ እና የአመለካከት ኋላ ቀርነት በመራቅ ለኅብረተሰብ ዕድገት እና ብልፅግና እንዲረባረቡ ጠይቀዋል።

    በሌላ በኩል ደግሞ ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ለመጀመሪያ ጊዜ በሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም ያሰለጠናቸውን 33 የሕክምና ዶክተሮችን አስመረቀ።

    ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ለመጀመሪያ ጊዜ በሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም (hybrid innovative curriculum) በሕክምና ዶክትሬት ያሰለጠናቸውን 33 ተማሪዎች በተመሳሳይ ቀን አስመርቋል።

    በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ለተማሪዎቹ የሥራ መመሪያ የሰጡት የሳይንስ እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ፥ ተመራቂዎቹ ቃለመሀላ በገቡለት የሕክምና ሥነ-ምግባር በመታገዝ ቅን አገልጋዮች እንዲሆኑ አሳስበዋል። ከዚህም ባለፈ በተግባር በተደገፈው ሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም የቀሰሙትን የሕክምና ትምህርት የሀገሪቱን ብሎም የዓለምን ሕዝብ ስጋት ላይ ከጣሉ ዘመን-ወለድ የጤና ችግሮች ኅብረተሰቡን ለመታደግ ተግባራዊ እንዲያደርጉት ጥሪ አቅርበዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አነጋግረኝ ጋሻው በበኩላቸው፥ ተመራቂዎቹ ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ በውጤት በታገዘው የቅይጥ ፈጠራ-አከል ሥርዓት (ሀይብሪድ ኢኖቬቲቭ ካሪኩለም) ለመጀመሪያ ጊዜ ያሰለጠናቸው በመሆናቸው ማኅበረሰቡን ከጤና እክሎች ከመታደግ ባለፈ በምርምር ዘርፍ በመሰማራት ለሀገር ብልፅግና የድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።

    ዩኒቨርሲቲው በዕለቱ 26 የማስተርስ ዲግሪ (ሁለተኛ ዲግሪ) ተማሪዎችንም አስመርቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    አዳማ ሪፈራል ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ የሕክምና ዶክተሮችን አስመረቀ
    ጅማ ዩኒቨርሲቲ 3ሺህ 185 ተማሪዎችን መተመሳሳይ ዕለት አስመርቋል

    አዳማ (ኢዜአ) – አዳማ ሪፈራል ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ የውስጥ ደዌና ከፍተኛ የቀዶ ሕክምና ስፔሻልስቶችን ጨምሮ በተለያዩ ሙያዎች ያሰለጠናቸውን 140 ዶክተሮችን የካቲት 14 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመረቀ። ከተመራቂዎቹ መካከል ደቡብ ሱዳን የሕክምና ስፔሻልስቶች ይገኙበታል።

    በምረቃው ሥነ ሥርዓት የተገኙት የኦሮሚያ ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ነጋሽ ስሜ እንደገለጹት፥ በክልሉ ከተሞችና ገጠራማ አካባቢዎች ካንሰርና ስኳርን ጨምሮ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች (noncommunicable diseases) እየተስፋፉ መጥተዋል። በክልሉ በሚገኙ የመጀመሪያና ሪፌራል ሆስፒታሎች የሕክምና መሣሪያና መድኃኒትን ጨምሮ የውስጥ ደዌና የቀዶ ሕክምና ሐኪሞች እጥረት መኖሩንም ተናግረዋል።

    ለዚህም አዳማ ሪፈራል ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ግንባር ቀደም መሆኑን ጠቅሰው ኮሌጁ የሰው ሕይወት ለማዳን የሚያስችል እውቅትና ክህሎት ለማስታጠቅ ተግባር ተኮር ስልጠናና ምርምር ሥራዎችን ማከናወን እንደሚገባው አቶ ነጋሽ ጠቁመዋል። ሰልጣኞቹ በቆይታቸው ያገኙትን እውቀት ወደ ተግባር በመተርጎም ማህበረሰቡን በማገልገል ምሳሌ መሆን አለባቸው ብለዋል።

    የአዳማ ሪፈራል ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር መኮንን ፈይሳ በማህፀን፣ በውስጥ ደዌ፣ በህፃናትና በከፍተኛ ቀዶ ሕክምና እንዲሁም በጠቅላለ ሐክም ስፔሻልስቶችን እያሰለጠነ ነው፤ ዛሬ ለምረቃ የበቁት 140 የሕክምና ዶክተሮች አሁን በስፋት የሚስተዋለውን አጣዳፊና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመከላከል አስተዋጽኦ እንደሚኖራቸው ተናግረዋል።

    በተለይ በክልሉ የመጀመሪያ፣ ስፔሻላይዝድና ሪፌራል ሆስፒታሎች የሚታዩትን የማህፀን፣በውስጥ ደዌ፣ የህፃናትና ከፍተኛ ቀዶ ሕክምና ያለው የከፍተኛ ሙያተኞች እጥረት የሚፈታ ነው ብለዋል – ዶ/ር መኮንን።

    ሰልጣኞቹ በቆይታቸው ለህብረተሰቡ የጠቅላላ ሕክምና አገልግሎት፣ መካከለኛና ከፍተኛ የቀዶ ጥገና ሕክምና በመስጠት ሙያዊ ብቃታቸውን በተግባር ያስመሰከሩ በማለት አስረድተዋል።

    አዳማ ሪፈራል ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ከ400 በላይ አልጋ ያለው፣ ማስፋፊያ ግንባታ፣ የጥናትና ምርምር ማዕከላት፣የተማሪዎች መኖሪያና መመገቢያ ህንፃዎች ከአንድ ቢሊዮን 300 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በመገንባት ለአገልግሎት ዝግጁ አድርጓል።

    ከተመራቂዎቹ መካከል በከፍተኛ ማዕረግ የተመረቀችው ዶ/ር አያንቱ በቀለ በሰጠችው አስተያየት በአሁኑ ወቅት በሀገራችን አሳሳቢ እየሆነ ያለው ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች እንደሆነ ገልጻ ባገኘሁ እውቀት የድርሻዬን እወጣለሁ በማለት ተናግራለች።

    ከከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች ምርቃት ጋር በተያያዘ፥ ጅማ ዩኒቨርሲቲ 3ሺህ 185 ተማሪዎችን መተመሳሳይ ዕለት አስመርቋል። የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዘዳንት ዶ/ር ጀማል አባፊጣ በምረቃው ሥነ ሥርዓቱ ወቅት እንደተናገሩት “ዛሬ ከጅማ ዩኒቨርሲቲ ተመራቂዎች ሀገራችሁ ከእናንተ ከምንግዜውም በላይ እንድታገለግሏት ትፍልጋለች” ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲው ያስመረቀው ከስድስት ኮሌጆች፣ ሁለት ኢንስቲትዩቶች እና ድኅረ ምረቃ ትምህርት ቤት በተለያዩ ሙያዎች ስልጠናቸው ነው። ከተመራቂዎቹ መካከል 834 ሴቶች እንዲሁም 11 የሱማሌላንድና የሩዋንዳ ዜጎች ይገኙበታል። ዩኒቨርሲቲው ከተለያዩ የዓለም ሀገራት የተወጣጡ አንድ መቶ ስልሳ ስምንት ሰዎችን እያስተማረ እንደሚገኝም ተመልክቷል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አዳማ ሪፈራል ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ

    Semonegna
    Keymaster

    በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሥር ከሚገኙት ተቋማት መካከል አንዱ የሆነው የጎንደር ዩንቨርሲቲ በርካታ ቁሳዊና መንፈሳዊ እሴት የያዙ መጻህፍት ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲሸጋገሩ ለማድረግ ሥርዓተ ትምህርት (curriculum) ተቀርጾና መምህራን ተቀጥረው የግእዝ ቋንቋን ለማስተማር መዘጋጀቱን አስታውቋል።

    ጎንደር ዩንቨርሲቲ የግእዝ ቋንቋ በመጀመሪያ ዲግሪ መስጠት ሊጀምር ነው

    ጎንደር (ኢዜአ) – ጎንደር ዩንቨርሲቲ የመጥፋት አደጋ የተጋረጠበትን የግእዝ ቋንቋ ለመታደግ በአዲሱ የትምህርት ዘመን በመጀመሪያ ዲግሪ የቋንቋ ትምህርት ለመስጠት መዘጋጀቱን አስታወቀ።

    የጎንደር ዩንቨርሲቲ የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዘዳንት ዶ/ር ካሳሁን ተገኘ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደተናገሩት ኢትዮጵያ የግእዝ ቋንቋ ባለቤት ብትሆንም ለቋንቋው ማደግና መስፋፋት የተሰጠው ትኩረት አነስተኛ ነው። “በዚህም ሳቢያ ቋንቋው የመጥፋት አደጋ የተጋረጠበት ከመሆኑም በላይ በግእዝ ቋንቋ የተጻፉ በርካታ የብራና መጻፍትን ለጥናትና ምርምር ስራ ለማዋል አልተቻለም “ብለዋል።

    ዘመናት የተሻገሩና በቋንቋው የተጻፉ ለዘመናዊ ሕክምና ሙያ የሚያግዙ፣ ምጣኔ ሀብታዊ፣ ባህላዊና ታሪካዊ ፋይዳ ያላቸው በርካታ መጻሕፍት በኃይማኖት ተቋማትና ገዳማት ተወስነው መኖራቸውን አመልክተዋል።

    ዩንቨርሲቲው እነዚህን ቁሳዊና መንፈሳዊ እሴት የያዙ መጻህፍት ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲሸጋገሩ ለማድረግ ሥርዓተ ትምህርት (curriculum) ተቀርጾና መምህራን ተቀጥረው የግእዝ ቋንቋን ለማስተማር መዘጋጀቱን አስታውቀዋል።

    በትምህርት ዘመኑ 50 ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር ዝግጅት መደረጉን ያመለከቱት ዶክተር ካሳሁን፥ ትምህርቱ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚሰጠውም በኤክስቴንሽንና በክረምት መርሃ ግብሮች መሆኑን አስረድተዋል። ትምህርቱ ሰፊ ተቀባይነት እያገኘ ሲሄድ መደበኛ ተማሪዎችን ጭምር በቀጣይ በግእዝ ቋንቋ አሰልጥኖ ለማስመረቅ መታቀዱን አመልክተዋል።

    በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሥር ከሚገኙት ተቋማት መካከል አንዱ የሆነው የጎንደር ዩንቨርሲቲ፥ በአጠቃላይ 87 የመጀመሪያ ዲግሪ፤ 158 ሁለተኛ ዲግሪና 29 የሦስተኛ ዲግሪ የትምህርት ፕሮግራሞች እንዳሉት ተገልጿል። በመደበኛ፣ በተከታታይና በክረምት መርሃ ግብሮች ትምህርታቸውን የሚከታታሉ ከ45ሺ በላይ ተማሪዎች በዩንቨርሲቲው ይገኛሉ።

    ምንጭ፦ ኢዜአ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    —–
    ተመሳሳይ ዜናዎች

    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በኢትዮጵያ ― ዜናዎችና ጠቃሚ መረጃዎች


    Semonegna
    Keymaster

    ለጅማ ዩኒቨርሲቲ ለአዲስ አበባ ካምፓስ (Jimma University Addis Ababa Campus) ተማሪዎች የሰጠው መግለጫ

    ጉዳዩ፡- ተገቢነት በሌላቸው ጽሁፎችና መግለጫዎች እንዳትደናገሩ ስለማሳሰብ

    ጅማ (ጅማ ዩኒቨርሲቲ) – ዩኒቨርሲቲያችን መንግሥት የከፍተኛ ትምህርትን ለማዳረስ የሚያደርገውን ጥረት በማሳካት ረገድ ግንባር ቀደም ሚና ያለው መሆኑ ከሁላችሁም የተሰወረ አይደለም። የመንግሥትን የትምህርት ፖሊሲ ተግባራዊነት ከማረጋገጥ አኳያ ዩኒቨርሲቲያችን በተለያዩ ደረጃዎች የሚሰጠውን ትምህርት አድማስ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሰፋ መምጣቱ የቁርጠኝነቱ ዓይነተኛ ማሳያ ነው። ይኸውም ዋና መቀመጫው ጅማ ከተማ ሆኖ በአገሪቱ የተለያዩ ስፍራዎችና ከአገር ውጪም በሐርጌሳ ጭምር ካምፓሶችንና የትምህርት ማዕከሎችን ከፍቶ ትምህርቱን በማስፋፋት ላይ የሚገኘውም በዚሁ አግባብ ነው።

    ሆኖም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዩኒቨርሲቲያችን የሚያደርገውን ሕጋዊ እንቅስቃሴ ለማደናቀፍና ለማስቆም የሚሞክሩ አካላት ያላሰለሰ ጥረት በማድረግ ላይ መሆናቸውን ተገንዝበናል። ይኸውም የከፍተኛ ትምህርት አግባብነትና ጥራት ኤጀንሲ እና ጥቂት የኤጀንሲው የሥራ ኃላፊዎች በኤጀንሲው የፌስቡክ ገጽ እና በግል የፌስቡክ ገጽ በለቀቋቸው መረጃዎች እንዲሁም የፕሬስ ኮንፈረንስ ጠርተው በመገናኛ ብዙኃን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ የዩኒቨርሲቲያችንን ስም ሲያጠፉና ሲያቆሽሹ መቆየታቸው ይታወቃል። አሁን ደግሞ የዩኒቨርሲቲያችንን ስም ከማጥፋት አልፈው በቁጥር 01/መ-4/2688/11 መስከረም 6 ቀን 2012 ዓ.ም. በተፃፈ ደብዳቤ በአዲስ አበባው ካምፓሳችን (Jimma University Addis Ababa Campus) በመማር ላይ ለሚገኙ ተማሪዎች ጥሪ በማድረግ ወደ ሌላ ተቋም እንደሚያዛውሯቸው በኤጀንሲው የፌስቡክ ገጽ መረጃ ለቀዋል።

    ነገር ግን ዩኒቨርሲቲያችን የአዲስ አበባውን ካምፓስ (Jimma University Addis Ababa Campus) የከፈተውም ሆነ ላለፉት ሰባት ዓመታት ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ ትምህርት ሲሰጥ የቆየው ዩኒቨርሲቲውን እንደገና ለማቋቋም በወጣው የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 240/2003 አንቀጽ 2(1) እና አንቀጽ 3 መሠረት ራሱን የቻለ የሕግ ሰውነት ያለው የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ሆኖ ስለተቋቋመ እና ዋና ግቢው ጅማ ከተማ ሆኖ በሌሎች ቦታዎች የትምህርት ክፍሎች እና የምርምርና የማሕበረሰብ አገልግሎት ማዕከሎችን የማቋቋም መብት በሕግ ስተሰጠው ነው። የድጋፍ አገልግሎት ከሚሰጥ የግል ተቋም ጋር ሕጋዊ ስምምነት ተፈራርሞ ለትምህርቱ የሚያስፈልጉ የአገልግሎት ግብአቶችን በማግኘት ላይ ያለው ደግሞ በከፍተኛ ትምህርት አዋጅ ቁጥር 650/2001 አንቀጽ 93(1) ስር ማንኛውም የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ድጋፍ ሰጪ አገልግሎቶችን በሌሎች አገልግሎት አቅራቢዎች እንዲሰጥ ለማድረግ የሚያስችል ሕጋዊ መብት እንዳለው በተደነገገው መሠረት ነው። ይህም ሆኖ በሕግ ድንጋጌዉ ላይ የጠቅላይ አቃቤ ሕግ ትርጓሜ እንዲሰጥ ተጠይቆ ዉጤቱን እየተጠባበቅን ባለንበት ወቅት ሁከት ለመፍጠር የሚደረገዉ እንቅስቃሴ አግባብነት የጎደለዉ ነዉ።

    በሌላ በኩል ደግሞ የከፍተኛ ትምህርት አግባብነትና ጥራት ኤጀንሲ ሥልጣንና ተግባር ኤጀንሲው በተቋቋመበት የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 261/2004 አንቀጽ 6 እና በከፍተኛ ትምህርት አዋጅ ቁጥር 650/2001 አንቀጽ 89 ስር የተዘረዘረ ሲሆን በሁለቱም ሕጎች ኤጀንሲው ተማሪዎችን ከአንድ የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ነጥቆ ለሌላ ተቋም ለመስጠትም ሆነ አንድን ካምፓስ ለመዝጋት የሚያስችል ሥልጣንና ኃላፊነት አልተሰጠውም። ስለሆነም ኤጀንሲውንና የሥራ ኃላፊዎቹ በዩኒቨርሲቲያችን ዙሪያ የሚያደርጓቸው ማናቸውም እንቅስቃሴዎች በሙሉ ተገቢነት የሌላቸዉ እና በሌላቸው ስልጣን የተፈፀሙ በመሆናቸው በሕግ የሚያስጠይቁ ናቸው።

    ውድ ተማሪዎቻችን! ዩኒቨርሲቲያችን በአዲስ አበባ ካምፓስ ከፍቶ ለተማሪዎች ትምህርት ሲሰጥ የቆየው በሕጋዊ መንገድ መሆኑን እያረጋገጥን ይህንኑ በሕግ የተሰጠውን ሥልጣን በመጋፋት ኤጀንሲውና የሥራ ኃላፊዎቹ በማድረግ ላይ ያሉት አግባብ የሌለዉ እንቅስቃሴ ሕዝብና መንግሥት እንዳይረጋጋ የሚያደርግ በመሆኑ በፅኑ የምናወግዘው ነው። ዩኒቨርሲቲያችን እስከ አሁን ድረስ በኤጀንሲው በበላይ የሥራ ኃላፊዎች ሲፈፀሙ የነበሩትን አግባብነት የሌላቸዉን ተግባራት በትዕግስትና በሰከነ መንፈስ ሲከታተልና መፍትሄ ሲያፈላልግ የቆየ ሲሆን፤ የአሁኑ ተግባር ግን የዩኒቨርሲቲውን ህልውና የሚፈታተንና የኤጀንሲውን የስልጣን እና ኃላፊነት ገደብ የጣሰ በመሆኑ፣ ዩኒቨርሲቲያችን ጉዳዩን ከሚመለከታቸው የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ጋር በመወያየት መፍታትን ጨምሮ ሌሎች አስፈላጊ ተግባራትን ለመፈፀም ቁርጠኛ አቋም የያዘ መሆኑን እየገለፅን፤ በኤጀንሲው ጥሪ ሳትረበሹና ሳትሳሳቱ ዩኒቨርሲቲዉ ከተማሪ እና ከወላጅ ተወካዮች ጋር ባደረገዉ ዉይይት መሠረት ጉዳዩን ለመፍታት እየሠራ መሆኑን አዉቃችሁ በትዕግስት እንድትጠብቁን እናሳስባለን።

    ምንጭ፦ ጅማ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    Jimma University Addis Ababa Campus


    Semonegna
    Keymaster

    ኤ.ቢ.ኤች. ፓርትነርስ (ABH Partners) የከፍተኛ ትምህርት አግባብነትና ጥራት ኤጀንሲ እና አምስት የሥራ ኃላፊዎቹ ላይ ጉዳት አድርሰውብኛል በሚል በመሠረተው የ174.6 ሚሊዮን ብር ክስ ነሐሴ 29 ቀን 2011 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ቀረቡ።

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን ጋዜጣ) – የከፍተኛ ትምህርት አግባብነትና ጥራት ኤጀንሲ (HERQA) እንዲሁም አምስት የሥራ ኃላፊዎቹ በድርጅቱ ላይ ላደረሱትና ለሚደርሰው ጉዳት የ174.6 ሚሊዮን ብር ተከፍሎ እስከሚያልቅ ከሚታሰብ ሕጋዊ ወለድ ጋር ክስ እንዳቀረበባቸውና ነሐሴ 29 ቀን 2011 ዓ.ም. ረፋድ ላይ ፍርድ ቤት እንደቀርቡ ኤ.ቢ.ኤች. ፓርትነርስ (ጥምረት ለተሻለ ጤና) /ABH Partners/ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል አማካሪ ድርጅት አስታወቀ።

    የድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር ማርቆስ ፈለቀ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለጹት፥ ጉዳዩ ወደ ፍርድ ቤት ከማምራቱ በፊት ኤጀንሲው የድርጅቱን መልካም ሥምና ዝናን በማጠልሸቱ ይቅርታ እንዲጠይቅና ችግሩን እንዲያርም ቢጠየቅም ፈቃደኛ ሊሆን አልቻለም።

    በዚህም ድርጅቱ ነሐሴ 23 ቀን 2011 ዓ.ም. በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፍትሐ-ብሔር ስድስተኛ ምድብ ችሎት የመዝገብ ቁጥር 241863 ክስ ለመመሥረት ተገዷል። የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር አንዱዓለም አድማሴን ጨምሮ አምስት የሥራ ኃላፊዎችም ተከሰዋል።

    ኤጀንሲው ጅማ ዩኒቨርሲቲ ከኤ.ቢ.ኤች. ፓርትነርስ (ABH Partners) ጋር በጥምረት የሚሠሩትን ሥራ እንደማያውቀው ቢያስተባብልም፤ ሁለቱ ተቋማት ውል ተፈራርመው ሥራውን ሲጀምሩ በወቅቱ የነበሩት የከፍተኛ ትምህርት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ በቦታው ተገኝተው መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ቃል ገብተው እንደነበር ዶ/ር ማርቆስ አስታውሰው፤ “ይህም መንግሥት አያውቀውም የሚለውን ሐሳብ ትክክል እንዳልሆነ አመላካች ነው። ከወራት በፊት ትምህርት የሚሰጥበትን ቦታ ተገኝተው የጎበኙ የሣይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታዎች ግን ‘ሥራው የዩኒቨርሲቲውን አቅም ለማዳበር ያገዘ ነው’ ሲሉ አሞካሽተውታል። ለጅማ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ተጨማሪ የገቢ ምንጭ በመስጠት የመምህራን ፍልሰት እንዲቀንስ አዎንታዊ አስተዋፅዖ ማበርከቱንና ለትምህርት ጥራት እንዲተጋ የሚያግዙ ሁኔታዎች መመቻቸታቸውንም ሚኒስቴሩ ምስክርነቱን በደብዳቤ ሰጥቷል” ብለዋል።

    ሚኒስቴሩ፥ የዚህ መሰል የግሉ ዘርፍና የመንግሥት አጋርነት ለትምህርት ጥራትም ሆነ ተደራሽነት ሚናው የላቀ መሆኑን በመግለጽ፥ ለዚህ ሊበረታታ ለሚገባው ድርጅት አገራዊ ፋይዳውን በማየት የግንባታ መሬት በመስጠት ትብብር እንዲደረግላቸው ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማ የትብብር ደብዳቤ እንደፃፈላቸውም ጠቁመዋል።

    ሚኒስቴሩ ለዩኒቨርሲቲውና ለድርጅቱ ምስክርነት በመስጠት ከመንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያገኙ ሲያደርግ፥ ኤጀንሲው ደግሞ የከፍተኛ ትምህርት አዋጅ ቁጥር 650/2001 ከሰጠው ሥልጣን ውጪ “ዩኒቨርሲቲው ከዋናው ግቢ ውጪ በአዲስ አበባ የሚሰጠው ትምህርት ዕውቅና የለውም፤ ሕጋዊም አይደለም” በማለት እግድ ማስተላለፉ “ባለፉት ሰባት ዓመታት የት ነበረ?” የሚል ጥያቄንም የሚጭር እንደሆነ ዶ/ር ማርቆስ አብራርተዋል።

    ጅማ ዩኒቨርሲቲ የማስተማር ሥራውን ሊሰራ፤ አማካሪ ድርጅቱ ደግሞ አስተዳደራዊ ድጋፍ ሊሰጥ በገቡት ስምምነት መሠረት ዩኒቨርሲቲው አዲስ አበባ ባለው ካምፓስ ምንም ዓይነት የመንግሥት ድጋፍ ሳይደረግለት ኤ.ቢ.ኤች. ፓርትነርስ ሙሉ ድጋፍ በማድረግ ለመማር-ማስተማሩ አስፈላጊ ግብዓቶችን አሟልቶ በውሉ መሠረት ግዴታውን ሲወጣ መቆየቱንም ተናግረዋል።

    ዩኒቨርሲቲው ከዋናው ግቢ ውጪ ማስተማርም ሆነ ከሌሎች አካላት ጋር በትብብር መሥራት እንደማይችል ኤጀንሲው ቢገልጽም፣ በዩኒቨርሲቲው እንደገና ማቋቋሚያ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 240/2003 ግን ዩኒቨርሲቲው ዋናው ግቢ ከሚገኝበት ጅማ ከተማ ውጪ በሌሎች ቦታዎች የትምህርት ክፍሎችን እንዲሁም የምርምርና የማኅበረሰብ አገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ሊያቋቁም እንደሚችል ተደንግጓል።

    በተመሳሳይ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አዋጅ ዩኒቨርሲቲዎች ተልዕኳቸውን ለማሟላት ድጋፍ ሊሰጣቸው ከሚችል ከማንኛውም ተቋም ጋር መሥራት እንደሚችሉ ይደነግጋል። በዚህም በአዋጁ ያልተከለከለን ሥልጣን ኤጀንሲው በደብዳቤ መሻሩ ተገቢነት እንደሌለው ዶ/ር ማርቆስ ገልፀዋል። በመሆኑም ለቀጣይ የትምህርት ዘመን አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት እያደረጉ መሆናቸውንና ተማሪዎችና የተማሪ ወላጆች በሁኔታው መደናገጥ እንደማይገባቸው ተናግረዋል።

    የከፍተኛ ትምህርት አዋጅ (ቁጥር 650/2001) አንቀጽ 93፣ ንዑስ አንቀጽ አንድ አገልግሎት በሌሎች ወገኖች እንዲሰጥ ስለማድረግ ይደነግጋል። በዚህም ማንኛውም የመንግሥት ተቋም ተገቢና ተግባራዊ ሊደረግ የሚችል ሆኖ ሲያገኘው የድጋፍ ሰጪ አገልግሎቶችን በሌሎች አገልግሎት አቅራቢዎች እንዲሰጥ ሊያደርግ እንደሚችል አስቀምጧል።

    በተመሳሳይ በጅማ ዩኒቨርሲቲ እንደገና ማቋቋሚያ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ (ቁጥር 240/2003) በአንቀጽ ሦስት መሠረት የዩኒቨርሲቲው ዋናው ግቢ ጅማ ከተማ ሆኖ በሌሎች ቦታዎች የትምህርት ክፍሎችን፣ የምርምርና የሕብረተሰብ አገልግሎት ማዕከሎችን ሊያቋቁም እንደሚችል ተቀምጧል።

    ባለፉት 15 ቀናት ኤጀንሲው “የትብብር ሥልጠና ትክክል ባለመሆኑ እንዲያቆሙ” በሚል ሚኒስቴሩ በደብዳቤ ማሳወቁን መግለጹ ይታወሳል። በዚህ መልኩ ሲሠሩ የነበሩ የጅማየደብረ ማርቆስየባህር ዳር እና የሐረማያ ዩኒቨርሲቲዎች እንደታገዱ አሳውቋል።

    ሆኖም ጅማ ዩኒቨርሲቲ እና ኤ.ቢ.ኤች. ፓርትነርስ ሥራቸውን በመቀጠላቸው “አደብ ሊገዙ ይገባል” ብሎም ነበር። ከዚህ በተጨማሪም ኤጀንሲው በተቋማቱ በመማር ላይ ያሉትን ተማሪዎች ዝርዝር እንዲላክለት የጠየቀ ሲሆን፤ ተመርቀው የወጡ ተማሪዎች ዕጣ ፈንታ ግን ቀጣይ ውይይት እንደሚያስፈልገው አሳውቆ ነበር።

    ምንጭ፦ አዲስ ዘመን ጋዜጣ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ABH Partners vs HERQA brawl


    Semonegna
    Keymaster

    ክበቡ የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል እንዲሁም ተዛማጅ እሴቶችን በማስተዋወቅ ቀደም ሲል በኢትዮጵያ የነበረውን ፍቅር፣ ሰላምና አብሮ የመኖር እሴት ለመጪው ትውልድ ለማስረከብ ጠንክሮ እንደሚሠራ እምነታቸው መሆኑን የድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ተናግረዋል።

    ድሬ ዳዋ (ሰሞነኛ) – “ቋንቋችንን፣ ባህላችንን፣ እሴቶቻችንንና ታርካችንን ጠብቀን ለመጪው ትውልድ ማስረከብ የአሁኑ ትውልድ ግዴታ ነው።” በሚል መሪ ቃል የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል ማበልፀጊያ ክበብ በድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ ተቋቁሟል። በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል ክበብ ምሥረታ ቀደም ብለው ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡት የድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ያሬድ ማሞ፣ የኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል ክበብ ፕሬዝዳንት ተማሪ ገሊማ፣ የተማሪዎች ህብረት ፕሬዝዳንት ተማሪ ጥበቡ ሙሉጌታ እንዲሁም የ2011 ዓ.ም የተማሪዎች ምረቃ ኮሚቴ ሰብሳቢ ተማሪ ቢቅላ ጋሮምሳ የክበቡን መመሥረት በማብሰር መርሃ ግብሩን ይፋ አድርገዋል።

    ክበቡ የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ እና ባህልን በማስተዋወቅ ቀደም ሲል በኢትዮጵያ የነበረውን ፍቅርና ሰላም እንዲሁም አብሮ የመኖር እሴት ለመጪው ትውልድ ለማስረከብ ጠንክሮ እንደሚሠራ እምነታቸው መሆኑን የድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ያሬድ ማሞ ተናግረዋል። ዶ/ር ያሬድ አያይዘውም ክበቡ ለሌላ ዓላማና እኩይ ተግባር እንደማይውል ሙሉ እምነታቸው መሆኑን በመግለጽ፤ ግንባር ቀደም ክበብ በመሆኑ ሌሎች ብሔሮችም ተመሳሳይ ጥያቄ ይዘው ቢመጡ ክበቡ እነሱን የማገዝ ሃላፊነት እንዳለበት አሳስበዋል። በመጨረሻም ዶ/ር ያሬድ ተማሪዎቻችን ከተለያዩ ብሔር ብሔረሰብ በመምጣታቸው የራሳቸውን ቋንቋና ባህል ለማስተዋወቅ ክበብ ለመመሥረት ቢፈልጉ ዩኒቨርሲቲው እኩል ድጋፍ እንደሚያደርግም ገልፀዋል።

    በምስረታው ላይ ታዋቂ ሰዎች፣ አባገዳዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፎበታል። የኦሮሞን ባህል ከማስተዋወቅ አንጻርም የኦሮሞ ባህላዊ ምግቦች ቅምሻ ሥነ-ስርዓትና የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች አለባበስ ትዕይንትም ተካሂዷል። በእለቱ የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ፣ ባህልና ታርክ ላይ የተመሠረተ ጥናታዊ ጽሁፍ በዶ/ር ተሾሜ ኤጌሬ የጅማ ዩኒቨርሲቲ የኦሮሞ ገዳ እንስቲትዩት ኤክስክዩቲቭ ዳይሬክተር፡ በአፋን ኦሮሞ ቋንቋና ታርክ ጥናታዊ ጽሁፍ አቅርቦ በተሳታፊዎች ሰፊ ውይይት ተካሂዶበታል።

    የዩኒቨርሲቲው የአፋን ኦሮሞ ቋንቋና ባህል ክበብ ፕሬዝዳንት እና መሥራች ተማሪ ገልማ ብዱ እንደተናገረው ክበቡ ኃይማኖት ተኮር ነገሮችን ከማንፀባረቅና ከማንኛውም የፖለቲካ አመለካከት የፀዳመሆኑን በመግለጽ የኦሮሞን ቋንቋ እና ባህል ከሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች ጋር በማዋሀድ ልምድ ልውውጥ በማድረግ በልዩነታችን ውስጥ ውበት አንድነታችን የሚጠናከርበትና የሚካሄድበት ክበብ ነው ብሏል። በክበቡም የሌሎች ብሄር ብሄረሰቦች ተወላጆች አባል ሆነው መሳተፍና አኩሪ የኢትዮጵያዊነት መልካም ባህላቸውን ማበልጸግ እንደሚችሉ ተናግረዋል።

    በዩኒቨርሲቲው የተማሪዎች ህብረት ስር ክበባትን ማደራጀት በሚፈቅደው መመሪያ መሰረት የኦሮምኛ ቋንቋና ባህልን ለማበልፀግ እንደ አንድ ክበብ የኦሮምኛን ቋንቋና ባህል ክበብ ሚያዝያ 5 ቀን 2011 ዓ.ም. ተመሥርቷል። የክበቡም ምሥረታ በአፍራን ቀሎ ባንድ ጣዕመ ዜማ፣ መነባነብ በገጣሚ እና ደራሲ ሲሳይ ዘለገሃሬ እና በዩኒቨርሲቲያችን ተማሪዎች ቀርቧል። በዩኒቨርሲቲያችን እስታዲየም ከአዲስ አበባ በተጋበዙ ታዋቂ የኦሮምኛ ዘፋኞች፣ የቀድሞ የአፍራን ቀሎ መሥራቾችና ዘፋኞች ተገኝቷል። እንዲሁም የማነቃቂያ ንግግሮች፣ የዕውቅና እና የስጦታ ሥነ-ስርዓቶችም ተካሂዷል።

    ምንጭ፦ ድሬ ዳዋ ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኦሮሞ ቋንቋ እና ባህል


    Anonymous
    Inactive

    መቐለ 70 እንደርታ የ2011 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አሸናፊ ሆነ
    —–

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – መቐለ 70 እንደርታ በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ 30ኛ ሳምንት ዛሬ ድሬ ዳዋ ከነማን 2ለ1 በመርታት ዋንጫ አንስቷል።

    ከስሑል ሽረ ጋር የተገናኘው ፋሲል ከነማ 1ለ1 በሆነ አቻ ግብ ሲለያይ መቐለ 70 እንደርታ ድሬ ዳዋን 2ለ1 በሆነ ልዩነት በመርታት ነው አሸናፊ የሆነው።

    መቐለ 70 እንደርታ ከድሬ ዳዋ ከነማ ጋር ባደረጉት ጨዋታ ጎሎቹን ያስቆጠሩት ለመቐለ 70 እንደርታ ኦሴይ ማውሊ (በጨዋታው የመጀመርያ የመጠናቀቂያ ደቂቃ ላይ በፍፁም ቅጣት ምት) እና አማኑኤል ገብረሚካኤል (በሀምሳ አራተኛው ደቂቃ ላይ በፍፁም ቅጣት ምት) ሲሆኑ፤ ለድሬ ዳዋ ከነማ ብቸኛዋን ጎል ያስቆጠረው ኤልያስ ማሞ (በሰባ ዘጠነኛው ኛው ደቂቃ ላይ) ነበር።

    መቀመጫውን መቐለ ከተማ ያደረገውና ራሱን በአዲስ መልክ በ2000 ዓ.ም. ካዋቀረ በኋላ በ 2010 ዓ.ም. ፕሪምየር ሊጉን የተቀላቀለው መቐለ 70 እንደርታ የእግር ኳስ ክለብ የፕሪምየር ሊጉን ዋንጫ ሲያሸንፍ ለመጀመርያ ጊዜው ነው።

    በፕሪምየር ሊጉ ማጠናቀቂያ ዕለት (ሰኔ 30 ቀን 2011 ዓ.ም.) በተካሄዱ ጨዋታዎች ደደቢትን ያስተናገደው ሀዋሳ ከተማ 5ለ2 በሆነ ሰፊ ልዩነት ረቷል። ሲዳማ ቡና ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ 3 ለ0፣ ኢትዮጵያ ቡና ከመከላከያ 3ለ4፣ ጅማ አባጅፋር ከደቡብ ፖሊስ 3ለ2 እና አዳማ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ 0ለ3 ተለያይተው የ2011 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ተጠናቋል።

    https://semonegna.com/wp-content/uploads/2019/07/Mekelle-70.jpg

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    Semonegna
    Keymaster

    የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎቻቸውን አስመርቀዋል
    —–

    አዲስ አበባ – የተለያዩ የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠኗቸውን ተማሪዎቻቸውን ሰኔ 22 ቀን 2011 ዓ.ም. አስመርቀዋል።

    በዕለቱ ተማሪዎቻቸውን ካስመረቁ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥም የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ፣ ጅማ ዩኒቨርሲቲ፣ ወለጋ ዩኒቨርሲቲ፣ መቱ ዩኒቨርሲቲ፣ ዲላ ዩኒቨርሲቲ እና አሶሳ ዩኒቨርሲቲ ይገኙበታል።

    የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በተለያየ የትምህርት መስክ ያሰለጠናቸውን 1 ሺህ 313 ተማሪዎቹን በዕለቱ አስመርቋል። ከተመረቁት ውስጥም 1 ሺህ 112 በቅድመ ምረቃ መርሃ ግብር (በመጀመሪያ ዲግሪ) ያስመረቀ ሲሆን፥ 201 ተማሪዎችን ደግሞ በድህረ ምረቃ መርሃ ግብር ነው ያስመረቀው።

    ጅማ ዩኒቨርሲቲም በዕለቱ በመጀመሪያ ዙር ዩኒቨርሲቲ በተለያየ የትምህርት መስክ ያሰለጠናቸውን 2 ሺህ 683 ተማሪዎቹን አስመርቋል። ከእነዚህም ውስጥ 341 በድህረ ምረቃ ሲሆን፥ 1 ሺህ 11 ደግሞ ሴቶች መሆናቸው ታውቋል።

    በተመሳሳይ ዲላ ዩኒቨርሲቲም በተለያዩ የትምህርት መስኮች ያሰለጠናቸውን 4 ሺህ 726 ተማሪዎቹን በዕለቱ አስመርቋል። በዲላ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች የምረቃ በዓል ላይ የተገኙት የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስተር ዲኤታ ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ፥ በዘንድሮው ዓመት በመላው ሀገሪቱ ከ175 ሺህ በላይ ተማሪዎች እንደሚመረቁ አንስተዋል። ተመራቂ ተማሪዎች ለሀገራቸው የሚሰሩ ሊሆኑ እንደሚገባም ፕሮፌሰር አፈወርቅ መልእክት አስተላልፈዋል። ዲላ ዩኒቨርሲቲ በዕለቱ ካስመረቃቸው ተማሪዎቹ ውስጥ 500 ተማሪዎችን በሁለተኛ ዲግሪ ነው ያስመረቃቸው።

    ወለጋ ዩኒቨርሲቲም በዕለቱ በተለያየ የትምህርት መስክ ያሰለጠናቸውን 3 ሺህ 682 ተማሪዎቹን በዕለቱ አስመርቋል። ከተመረቁት ተማሪዎች ውስጥ 2 ሺህ 139 ሴቶች ሲሆኑ 1 ሺህ 543 ደግሞ ወንዶች መሆናቸው ተገልጿል። በተጨማሪም ዩኒቨርሲቲው 295 ተማሪዎችን በሁለተኛ ዲግሪ ያስመረቀ2 ሲሆን፥ 8 ተማሪዎችን ደግሞ በ3ኛ ዲግሪ ወይም በዶክትሬት ዲግሪ አስመርቋል።

    መቱ ዩኒቨርሲቲም በተለያየ የትምህርት መሰኮች ሲያሰለጥናቸው የነበረውን ከ2 ሺህ 300 በላይ ተማሪዎቸ በዛሬው ዕለት አስመርቋል። በምረቃ ሥነ-ስርዓት ላይ የተገኙት ግብርና ሚኒስተር ዲኤታና የመቱ ዩኒቨርሰቲ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ሳኒ ሬዲ መንግስት ለሰው ሀብት ልማት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥው እየሠራ ባለበት መመረቃቸውንና ከተመራቂ ተማሪዎች የሚጠበቀው ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን ጠቅሰዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ተካልኝ ቃጄላ በበኩላቸው፥ ዩኒቨርሲቲው በዚህ ዓመት ብዙ ፈታኝ የሆኑ የውስጥና የውጭ ተግዳሮቶችን አልፎ ለዚህ መብቃቱን አስታውሰዋል።

    በተመሳሳይ አሶሳ ዩኒቨርሲቲ 2 ሺህ 714 ተማሪዎችን በተለያዩ የትምህርት መርሓ ግብሮች አስመርቋል። ከነዚህ ውስጥ 930 ሴት ተመራቂዎች መሆናቸው ታውቋል። ዩኒቨርሲቲው አሁን ለ6ኛ ጊዜ እያስመረቀ ሲሆን ከተመሰረተበት ከ2004 ዓም ጀምሮ አጠቃላይ 12 ሺ 450 ተማሪዎችን አስመርቋል። በዕለቱ በተካሄደው የምረቃ ሥነ-ስርዓት ላይ የሳይንስ እና የከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ፕሮፌሰር ሂሩት ወልደማርያምን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች ተገኝተዋል። ፕሮፌሰር ሂሩት ኢትዮጵያ ካለችበት ሁኔታ እንድትወጣ የተማረው ሀይል ዋነኛ አካል ነው ብለዋል።

    ምንጭ፦ ኤፍ.ቢ.ሲ

    Semonegna
    Keymaster

    ‹‹የንባብ ባህላችንን እናዳብር፤ ምክንያታዊ ትውልድ እንፍጠር›› በሚል መሪ-ቃል የመጽሐፍት ሽያጭ፣ ዓወደ-ርዕይና ሲምፖዚየም አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ተማሪዎች፣ መምህራን፣ ሠራተኞችና ሌሎች እንግዶች በተገኙበት ተካሂዷል።

    አርባ ምንጭ (AMU) – በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ቤተ-መጽሐፍትና መረጃ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት አዘጋጅነት “የንባብ ባህላችንን እናዳብር፤ ምክንያታዊ ትውልድ እንፍጠር” በሚል መሪ-ቃል የመጽሐፍት ሽያጭ፣ ዓወደ-ርዕይና ሲምፖዚየም ለመጀመሪያ ጊዜ ከሰኔ 3 ቀን እስከ ሰኔ 8 ቀን 2011 ዓ.ም. ተካሂዷል።

    የዝግጅቱ ዓላማ በዩኒቨርሲቲውና በአካባቢው ማኅበረሰብ ዘንድ በንባብ ባህል ዙሪያ ሰፊ ግንዛቤ በመፍጠር እውቀት እንዲስፋፋ እና ልምድ እንዲዳብር ለማድረግ እንዲሁም ማኅበረሰቡ የመጽሐፍትን ጥቅም ተረድቶ ከሌሎች ወጪዎች በመቀነስ የመግዛት ልምድ እንዲቀስም ለማስቻል መሆኑን በዩኒቨርሲቲው የቤተ-መጽሐፍትና መረጃ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ዓለምሰገድ ካሣሁን ገልፀዋል።

    የዕለቱ የክብር እንግዳ ገጣሚ፣ ደራሲና መምህር ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ የንባብ ጅማሮ፣ ጥቅምና የመምህራን ሚናን አስመልክቶ ባቀረቡት አንኳር ሀሳብ ንባብ ሊለካ የሚችለው በአንባቢው ላይ በሚያመጣው ዘርፈ ብዙ ለውጥ እንደሆነ ገልጸዋል። ንባብ የተለያየ ነገር ግን የተዋሀደ ይዘት ያለው እንደመሆኑ ማኅበራዊ ተግባቦት እንዲጨምር፣ ተአማኒ እውቀት እንዲዳብር ብሎም ባልኖርንበት ዘመንና ቦታ በምናብ እንድንኖር የሚያደርግ ጥልቅ ምስጢር አለው ብለዋል።

    ጥሩ አንባቢ የአፃፃፍ ስልትና የቃላት አመራረጥን ከመረዳት ባለፈ በሚያነበው ጉዳይ ራሱን የሚመለከትና የሚፈትሽ እንዲሁም የሌሎችንም ስሜት መረዳት የሚችል እንደሆነ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ ተናግረዋል። ለዚህም መምህራን ከመጽሐፍት ምርጫ አንስቶ መልካም ልምዶችን ለትውልዱ በማካፈል በመረጃ የዳበረና ያወቀ ማኅበረሰብ እንዲፈጠር የበኩላቸውን መወጣት እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ በበኩላቸው ለአንድ ማኅህበረሰብ እድገት የተማረ ማኅበረሰብ መፍጠር ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደመሆኑ ላለፉት በርካታ ዓመታት በአገሪቱ ከመሠረተ ትምህርት ጀምሮ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ዘርፍ ጥረት ሲደረግ መቆየቱን አውስተዋል።

    ማንበብና መጻፍ ከግለሰብ ባለፈ ለማኅበረሰብ ሁለንተናዊ እድገት ወሳኝ ናቸው ያሉት ፕሬዝደንቱ፥ የንባብ ባህል እንዲዳብር አስፈላጊውን ቁሳቁስ በማሟላት፣ አቅምና ጊዜ በተገቢው በመጠቀም፣ ተፈላጊውን የአዕምሮና የአስተሳሰብ ለውጥ በማምጣት እንዲሁም ምክንያታዊ ትውልድ በመፍጠር ከግለሰብና ከማኅበረሰብ ባለፈ ለአገር ዕድገት አስተዋጽዖ ማበርከት እንደሚቻል ገልፀዋል። በመሆኑም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለንባብ ባህል መዳበር አጽንዖት ሰጥተው ሊሠሩ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።

    የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝደንት ዶ/ር የቻለ ከበደ በበኩላቸው በአገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ ምንም እንኳ ጥንታዊ የሆኑና የተለያየ ዘውግ ያላቸው የስነ-ጽሑፍ ውጤቶች እንዲሁም ወቅታዊ አዕምሯዊ ውጤት የሆኑ የህትመት ውጤቶች ቢኖሩም ከጊዜ ወደ ጊዜ የሚታየው የንባብ ባህል መቀዛቀዝ በመረጃ የበለጸገና ምክንያታዊ የሆነ ዜጋ ከመፍጠር አኳያ እንደ አገር ከፍተኛ ተጽዕኖ የሚያሳድር እንደሆነ ተናግረዋል። በአገሪቱ ለንባብ የሚውለው ጊዜ በዓለም አንባቢ ዜጋ ካላቸው አገራት አንጻር በሣምንት ለንባብ ከሚያውሉት አማካይ ጊዜ በእጅጉ መራቁን የተለያዩ ዓለም አቀፍ ጥናቶች እንደሚያስረዱም ዶ/ር የቻለ ገልፀዋል።

    በማኅበረሰቡ ዘንድ መጽሐፍትን ገዝቶ ከማንበብ ይልቅ የማኅበራዊ ድረ-ገጽ ምርኮኛ መሆን፣ የወረቀትና የህትመት ዋጋ መጨመርና ሌሎችም ለችግሩ መባባስ በምክንያትነት ይጠቀሳሉ። ይሁን እንጂ የንባብ ባህል መዳበር ወሳኝ ጉዳይ በመሆኑ ባህሉ እንዲያንሰራራና መሻሻሎች እንዲመጡ ጠንከር ያለ ጥረትን ይጠይቃል።

    በንባብና ሚዲያ ቴክኖሎጂ ዙሪያ የሚያጠነጥን የውይይት መነሻ ጽሑፍ የዶክትሬት (PhD) ተማሪ በሆኑት አቶ ተመስገን ካሣዬ ቀርቦ ከተሳታፊዎች ጋር ሰፊ ውይይት ተደርጓል። በዚህም ዘመኑ የቴክኖሎጂና የመረጃ ከመሆኑ ባሻገር የሚዲያ ተግባቦት ባህሎችን ከሌላው ጋር የመቀየጥ አቅም ከፍተኛ እየሆነ መምጣቱ ተገልጿል።

    ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት ንባብ የአንድ ወቅት ሂደት ስላልሆነ በየደረጃው ያለው ሁሉም ማኅበረሰብ ከዋና ሥራው ጎን ለጎን መጽሐፍት ማንበብን ልምድ በማድረግ ከራሱ አልፎ ለሌሎችም መትረፍ የሚያስችል አቅም ማጎልበት እንደሚገባው ገልጸዋል። በተለይም በአገራችን ያሉ ደራሲያን መጽሐፍት ስነ-ጽሑፋዊ ይዘታቸውን ሳይለቁ፣ ታሪክን ሳያዛቡ እንዲሁም በሥነ-ምግባር ረገድ የተሻለ አቀራረብ እንዲይዙ በማድረግ ንቁ ማኀበረሰብ በመፍጠር ለአገራዊ ለውጥ የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ አስተላልፈዋል።

    በመጽሐፍት አውደ ርዕይና ሲምፖዚየሙ የዩኒቨርሲቲው አመራሮች፣ መምህራንና ተማሪዎች እንዲሁም ከአርባ ምንጭ ከተማ እና ከአዲስ አበባ የመጡ የቤተ-መጽሐፍት ባለሙያዎችና የመጽሐፍት ሽያጭ መደብሮች ተሳታፊ ሆነዋል።

    ምንጭ፦ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የንባብ ባህል


Viewing 15 results - 1 through 15 (of 30 total)