Search Results for 'አዲስ አበባ'

Home Forums Search Search Results for 'አዲስ አበባ'

Viewing 15 results - 61 through 75 (of 495 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    ከትግራይ ክልል ሁኔታ ጋር በተገናኘ የታሰሩ ተጠርጣሪዎች አያያዝ

    አዲስ አበባ (ኢሰመኮ) – የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ እና የኮሚሽኑ ከፍተኛ ባለሙያዎች በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የወንጀል ምርመራ ቢሮ በሚገኘው እስር ቤት የካቲት 27 ቀን 2013 ዓ.ም. በመገኘት በታሳሪዎች አያያዝ ሁኔታ ላይ ክትትል አድርገዋል።

    በጉብኝቱ በትግራይ ክልል ከተፈጠረው ሁኔታ ጋር በተያያዘ ተጠርጥረው የተያዙትን እነ ዶ/ር አብረሃም ተከስተ፣ አምባሳደር አባይ ወልዱ፣ አቶ ስብሀት ነጋ፣ አምባሳደር አባዲ ዘሙ፣ አቶ ቴዎድሮስ ሀጎስ፣ ዶ/ር ሰለሞን ኪዳኔ፣ ዶ/ር አዲስዓለም ባሌማ፣ ሜ/ጀነራል ይርዳው ገብረመድኅን፣ ሜ/ጀነራል ገብረመድኅን ፍቃዱ፣ ወ/ሮ ኬሪያ ኢብራሂም፣ ወ/ሮ ሙሉ ገብረእግዚአብሔር፣ ወ/ሮ ቅዱሳን ነጋን ጨምሮ በአጠቃላይ 21 ታሳሪዎች የሚገኙበትን የእስር ሁኔታ ጎብኝተው ታሳሪዎችን አነጋግረዋል። እንዲሁም ከፖሊስ ኃላፊዎች ጋር ውይይት አድርገዋል።

    በጉብኝቱም ታሳሪዎቹ በጥሩ አካላዊ ደኅንነት ላይ እንደሚገኙ፣ የሚገኙበት አካባቢና ክፍሎች ንፁህ እና ብዙም ያልተጨናነቁ፣ የተፈጥሮና የኤሌክትሪክ ብርሃን ያላቸው መሆኑንና አጠቃላይ ሁኔታው ተቀባይነት ያለው መሆኑን ኮሚሽኑ ተመልክቷል። ሁሉም ከላይ የተጠቀሱት ታሳሪዎች ወደ ፌዴራል ፖሊስ እስር ቤት ከመጡ ወዲህ ተገቢ ያልሆነ የእስር አያያዝ አለመኖሩንና ፖሊሶች በተገቢው የሙያ ሥነ ምግባር የሚሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። የህክምና አገልግሎት ባለው አቅም እያገኙ እንደሆነ፣ ከቤተሰባቸው ተገናኝተው አቅርቦት እንደሚቀበሉ እና ከጠበቆቻቸው ጋር መገናኘት መቻላቸውን አስረድተዋል። የተወሰኑ ታሳሪዎች በመከላከያ ሠራዊት አባላት በትግራይ ክልል በበረሀ ውስጥ ከተያዙበት ጊዜ አንስቶ በሰብአዊ እንክብካቤ መያዛቸውን እና የመከላከያ ሠራዊቱ አመራሮች ከድንገተኛ አደጋና ጥቃት እንደጠበቋቸው ገልጸዋል።

    በሌላ በኩል ከተያዙ በኋላ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ለረጅም ጊዜ መቆየታቸውን፣ በትግራይ ክልል ከመቀሌ ከተማ ሸሽተው ሲሄዱ በተያዙበት ጊዜ ስድብ፣ ድብደባ፣ ማስፈራራት እና ተኩስ እንደነበረና የአካል መቁሰል እንደደረሰባቸው፣ ተይዘው ወደ አዲስ አበባ ሲመጡም ነፃ ሆኖ የመገመት መብታቸውን በሚጋፋ መልኩ በሚዲያ አሰልፎ የማቅረብ እና የማንኳሰስ ሁኔታ እንደነበረ ያነሱ ታሳሪዎች አሉ። አብዛኞቹ ታሳሪዎች የቀረበባቸው ክስ ፖለቲካዊ ነው ብለው እንደሚያምኑ፣ የተጠረጠሩበት ጉዳይ  በተናጠል አለመቅረቡን እና የምርመራ ሂደቱ  በአፋጣኝ አለመታየቱን ገልጸው አቤቱታ አቅርበዋል። ታሳሪዎቹ ከአስተዳደራዊ ጉዳዮች ጋር ተያይዞ ከጠበቆች ጋር የሚገናኙበት ጊዜ ማጠሩን አንስተዋል። በተጨማሪም የተወሰኑ ታሳሪዎች የራሳቸው እና የቤተሰቦቻቸው የባንክ ሒሳብ በመታገዱ ቤተሰቦቻቸው መቸገራቸውን ገልጸዋል።

    ኮሚሽኑ ታሳሪዎቹ የሚገኙበት የአያያዝ ሁኔታ በተገቢው ደረጃ መሆኑን በማረጋገጥ፣ በታሳሪዎች የተነሱ አስተዳደር ነክ ጥያቄዎች ላይ ከእስር ቤቱ ኃላፊዎች ጋር ውጤታማ ውይይት አድርጓል። የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ የወንጀል ምርመራውን በተቻለ ፍጥነት ማጠናቀቅ እና የሕግ አግባብ በሚፈቅደው መልኩ በዋስትና ሊለቀቁ የሚገባቸውን ታሳሪዎች መለየት አስፈላጊ መሆኑን አሳስበዋል።

    ምንጭ፦ ኢሰመኮ

    ከትግራይ ክልል ሁኔታ ጋር በተገናኘ የታሰሩ ተጠርጣሪዎች አያያዝ

    Semonegna
    Keymaster

    የምርጫ ክርክር ለማዘጋጀት ፍላጎት ላላቸው የሲቪል ማኅበራት እና ሚዲያዎች የተደረገ ጥሪ

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ 6ተኛው ጠቅላላ ምርጫ ተግባራትን እያከናወነ እንደሆነ ይታወቃል፤ በዚህም መሠረት የተወሰኑ ተቋማት በተወዳዳሪዎች መካከል የምርጫ ክርክር ለማከናወን ከቦርዱ ፍቃድና አቅጣጫ ለማግኘት ጥያቄዎችን አቅርበዋል።

    ይህንን፥ እንዲሁም ሌሎች ልምዶችን መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የእጩዎች ምዝገባ ተጠናቆ ተወዳዳሪ ፓርቲዎች ከታወቁ በኋላ ሀገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ክርክር ሂደትን ለማስተባበር ይፈልጋል። በመሆኑም ከዚህ በፊት ጥያቄ/ ማብራሪያ ያስገባችሁም ሆነ በዚሁ ጉዳይ ላይ ፍላጎት ያላችሁ መንግሥታዊ ያልሆናችሁ ተቋማት እና ሚዲያዎች በተናጠል ወይም በጋራ የምርጫ ክርክር ዝርዝር የፍላጎት መግለጫ ወረቀት (expression of interest) ለቦርዱ እንድታቀርቡ ጥሪ ያቀርባል።

    የፍላጎት መግለጫ ማካተት የሚገባቸው ዋና ዋና ሃሳቦች

    ማንኛውም የምርጫ ክርክር ለማከናወን የሚያስብ ተቋም የሚመለከቱትን ዋና ዋና ነገሮችን ያሟላ የፍላጎት መግለጫ ሊያቀርብ ይገባል።

    • ሊያከናውኑት ያቀዱት የምርጫ ክርክር ግልጽ ዓላማ፣
    • ሊያከናውኑት ያቀዱት ክርክሩ የሚከናወንበት መንገድ (mode of engagement)፣
    • ሊያከናውኑት ያቀዱት የክርክሩ ሥነ-ምግባር ደንብ (code of conduct)፣
    • የክርክሩ ቁጥር ብዛት፣ የተሳታፊዎች ሁኔታ፣ ለሕዝብ የሚቀርብበት ሁኔታ፣
    • የአከራካሪ አመራረጥ ሂደት፣ መስፈርት እና መመዘኛ፣
    • ክርክሩ ለሕዝብ የሚቀርብበት መንገድ፣
    • በጀት እና የገንዘብ ምንጭ፣
    • ክርክሩን የሚከናወንባቸው ቋንቋዎች እና የመሳሰሉት፣

    ከላይ ከተጠቀሱት ዋና ዋና ጉዳዮች በተጨማሪ ምክረ-ሃሳብ የሚያስገቡ ተቋማት አስፈላጊ ነው የሚሉትን ዝርዝር ዕቅድ በምክረ-ሃሳባቸው ውስጥ አካተው ማቅረብ ይችላሉ። ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ክርክሩን በማመቻቸት ብሔራዊ ክርክር መከናወንን ከማመቻቸት በተጨማሪ ለክርክር ዝግጅት የሚሆን የፋይናንስ ድጋፍ አያደርግም።

    የፍላጎት መግለጫ ወረቀት እስከ የካቲት 26 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ (በአምስት የሥራ ቀናት ውስጥ) በቦርዱ ዋና መሥሪያ ቤት በግንባር ወይም በ media@nebe.org.et ኢ-ሜይል አድራሻ ሊቀርብ እንደሚችል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል።

    ከምርጫ ቦርድ መግለጫ ሳንወጣ፥ ቦርዱ ለ6ተኛው አጠቃላይ ምርጫ የእጩዎች ምዝገባን እያከናወነ ባለበት በአሁኑ ወቅት የመጀመሪያ ዙር የእጩ ምዝገባ የሚከናውንባቸው ክልሎች እና የከተማ መስተዳድሮች ማለትም፦

    • የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር
    • የድሬደዋ ከተማ መስተዳድር
    • የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልል
    • የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ብሔራዊ ክልል
    • የጋምቤላ ብሔራዊ ክልል
    • ሃሪሪ ብሔራዊ ክልል ለእጩዎች ምዝገባ የተቀመጠው የጊዜ ገደብ መሠረት የካቲት 08- 21 ድረስ እንደሚከናወን ማሳወቁ ይታወቃል።

    ቦርዱ የእጩዎች ምዝገባ ሂደትን በመገምገም የምርጫ ክልል ቢሮዎች ለመከፈት በመዘግየታቸው፥ የትራንስፓርት መጓተት የተወሰኑ የምርጫ ክልሎች ላይ የምዝገባ ቀንን በማራዘሙ እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲዎች በተለያዩ ምክንያቶች እጩዎችን ለመመዝገብ ችግር ስላጋጠመን ይራዘምልን ብለው ጠይቀዋል። በመሆኑም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከላይ የተጠቀሱትን አሳማኝ ምክንያቶች በማየት የመጀመሪያ ዙር ምዝገባ በጀመሩት ከላይ በተጠቀሱት ክልሎች/የከተማ መስተዳድሮች ላይ የሚካሄደው የእጩዎች ምዝገባ ለ4 ቀናት ያህል እስከ የካቲት 25 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ መራዘሙን አስታወቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

    የምርጫ ክርክር

    Anonymous
    Inactive

    ሱዳን በኢትዮጵያ ላይ ያደረገችውን ወረራ አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) የተሰጠ መግለጫ

    “ከድንበሩ ቆሞ ጌታ ካልመለሰው፥
    መሬትም ይሄዳል እግር አለው እንደ ሰው።”

    የሀገራችን ዳር ድንበር በአባቶቻችንና በእናቶቻችን ደምና አጥንት ተለስኖ የተሠራ የማይነቃነቅ አምድ እንጂ፥ እንደ ሰንበሌጥ አጥር ማንም በፈለገው ጊዜ እየጣሰው የሚገባ ድንበር አይደለም። ሀገሩንና ድንበሩን የማያስከብር ሕዝብ ለባርነት እንደተዘጋጀ ይቆጠራል። ለአንድ ዜጋ ሀገርና ድንበር የክብሩ ከፍተኛ መገለጫው ነውና።

    ኢትዮጵያ ሀገራችን በትግራይ ከአሸባሪው የህወሓት ቡድን እንዲሁም በመተከል በኦሮሚያ ክልል ጽንፈኞችን ለማጽዳት ከፍተኛ ግብግብ በምታደርግበት ወቅት፣ ሱዳን ድንበራችንን ተሻግራ ጦሯን ማስፈሯንና በአካባቢው በነበሩ ኢትዮጵያውን ገበሬዎች ላይ ጥቃት መፈጸሟን የተለያዩ የዜና አውታሮች የዘገቡት ሃቅ ነው። አሁን በቅርቡ ደግሞ በምዕራብ አርማጭሆ በደለሎ የገበሬዎችን የእርሻ ምርት ማቃጠሏን በከፍተኛ ቁጭት ሰምተናል። ይህ የሱዳን ድፍረት ማንኛውንም ኢትዮጵያጵያዊ ዜጋ እጅግ የሚያስቆጣ እርምጃ በመሆኑ ሁላችንንም እንቅልፍ የሚነሳ ድፍረት ነው ይላል ኢሕአፓ።

    የድንበር ውዝግቡ ለረዥም ጊዜ እልባት ሳያገኝ የቆየ መሆኑ ቢታወቅም፥ ኢትዮጵያ አንድም ጊዜ ድንበሯን አልፋ አንድ ጋት መሬት ከሱዳን ፈልጋ አታውቅም። ሱዳን ግን አጋጣሚ እየጠበቀች በተደጋጋሚ ከመተንኮስ ቦዝና አታውቅም። በሰላማዊ ጊዜም ከብቶቿን ወደ ኢትዮጵያ መሬት አሻግራ እንዲግጡ በመድረግ፣ ለእጣን የሚሆን ሙጫ በመሰብሰብ፣ ለቤትና ለማገዶ የሚሆን እንጨት እየቆረጠች በመውሰድ የምትፈጽማቸውን ድርጊቶች ኢትዮጵያውያን ገበሬዎች በመቃወማቸው በተደጋጋሚ ስትጋጭ ኖራልች። ኢሕአፓ በአካባቢው በሚንቀሳቀስበት ጊዜም ይህን ለማስቆም ለሱዳን መንግሥት ገበሬዎቻቸው ድንበራችንን እየተሻገሩ የሚያደርጉትን የጥሬ ሀብት ስብሰባና የከብት ግጦሽ እንዲያስቆሙ በተደጋጋሚ ጠይቆ አሻፈረኝ ስላሉ፤ የአካባቢውን የምዕራብ በጌምድርን (መተማ፣ ቋራ፣ ጫቆ) ሕዝብ አስተባብሮ የሱዳንን ጦር በመውጋት ድል አድርጎ የኢትዮጵያን ድንበር አስከብሮ አንደነበረ የሚታወቅ ነው። በዚህም ምክንያት ሱዳን የነበሩ የድርጅቱ አባሎች ለእስርና እንግልት ተዳርገዋል፤ የተወሰኑትንም ለህወሓት በማስረከብ ለሰቆቃ/ግርፋትና እስር እንዲዳረጉ አድርገዋል። ገዳሪፍ የነበረውን የድርጅቱን ጽሕፈት ቤት በርብረው የድርጅቱን ንብረቶች ወስደዋል። ከህወሓት ጋር በመተባበር ኢሕአፓን ከበው ወግተዋል። ህወሓትንም አጅበው አዲስ አበባ አስገብተው ተመልሰዋል።

    ህወሓት እና የሱዳን መንግሥት ከመጀመሪያ ጀምረው የጠበቀ ወዳኝነት እንደነበራቸው ይታወቃል። በደርግ ዘመን ህወሓት ጉልበት ያገኘውና የኢትዮጵያን ጦር አሸነፍኩ ያለው ሱዳን ከፍተኛ መከታና ደጀን ሆና ስለረዳቻቸው ጭምር ነው። ለዚህ ውለታ ሱዳኖች ድንበራችን ጥሰው በደለሎ በኩል ገብተው ኢትዮጵያውያን ገበሬዎችን አፈናቆለው ለረዥም ዓመታት ሲያርሱ ኖረዋል። የአካባቢው ገበሬዎች ድርጊቱን በመቃወም ሲከላከሉ፣ የህወሓት ካድሬዎች “መንግሥትና መንግሥት ይነጋገራል እንጂ ገበሬውን አያገባውም” በማለት ኢትዮጵያውያንን ገበሬዎችን ያስሩና ያንገላቱ ነበር። እውነታው ግን ሱዳን እንደፈለገች የኢትዮጵያን መሬት እንድትጠቀም በነአባይ ፀሐዬ የተሸረበ ሤራ መሆኑ ነው። የገበያ ግርግር ለሌባ ያመቻል እንዲሉ፥ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት የህወሓትን አሸባሪ ቡድን ለማፅዳት ጦርነት እያደረገ በነበረበት ወቅት ሱዳን ድንበራችንን ተሻግራ ኢትዮጵያውያን ገበሬዎችን ከማሳቸው ያፈናቀለችው የወዳጇ የህወሓት መመታት ስለከነከናትና በአጋጣሚውም የረጅም ጊዜ ምኞቷን ለማሳካት የወሰደችው እርምጃ ነው።

    ሱዳን ድንበራችንን የጣሰችበት ሌላው ምክንያት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሥራ ለማደናቀፍ እንዲቻል ከሱዳን ጀርባ ተጫማሪ ገፊ ኃይል ሊኖር እንደሚችል መገመት አይቸግርም። ከዚህ በተጨማሪ ህወሓትና የውጭ ደጋፊዎቻቸው ትግራይ ውስጥ የሚደረገውን የሀገር አፍራሹን ቡድን የማጽዳት ዘመቻ ቀጣናዊ መልክ ለማስያዝ የሚጥሩትን እውን ለሜድረግ ሱዳን የጦስ ዶሮ ሆና መቅረቧ አጠራጣሪ አይደለም እንላለን።

    በጦርነቱ ሳቢያ በትግራይ ውስጥ የተጎዳው ሕዝባችን አስፈላጊው እርዳታ እንዲደርሰው መንግሥት እስካሁን እያደረገ ያለው ድጋፍ በተጠናከረ መልክ እንዲቀጥልና የዓለምአቀፍ የሰብዓዊ ድርጅቶችም እርዳታና ድጋፋቸውን በመንግሥት በኩል ለሕዝቡ የሚደርስበትን መንገድ እንዲያመቻች እናሳስባለን።

    የኢትዮጵያ መንግሥት ሱዳን መሬታችንን ለቃ እስክትወጣ ድረስ የሱዳንን ትንኮሳ ጥንቃቄ በተሞላበት በሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገድ በመያዝ ከፍጻሜ ለማድረስ ከፍተኛ ትግል ማድረግ ይኖርበታል። ድንበራችን በቋሚነት የሚከለልበትንም መንገድ እንዲያመቻች እናሳስባለን።

    የኢትዮጵያ ሕዝብ የሀገሩን ዳር ድንበር ለማስከበርና የሀገሩን አንድነት ለማስጠበቅ ሊፋለም እንደሚችል ግልጽ መሆን አለበት። ሕዝባችን በተደጋጋሚ እንዳስመሰከረው ሱዳን ከሀገራችን ክልል እስክትወጣ ድረስ አስፈላጊውን መስዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ በመሆን፥ ከመከላከያ ሠራዊታችን ጎን እንደሚቆም አንጠራጠርም። ኢሕአፓም በማንኛውም መንገድ ከሕዝባችን ጎን ዘብ ለመቆም ዝግጁ መሆኑን ያረጋግጣል። አባቶቻችን ስለሀገርና ድንበር ሲነሳ እንደ እግር እሳት ሲያንግበግባቸው፦

    “ከደንበሩ ቆሞ ጌታ ካልመለሰው፥
    መሬትም ይሄዳል እግር አለው እንደ ሰው”

    ይሉ ነበር።

    ኢትዮጵያ በልጆቿ ታፍራና ተከብራ ለዘለዓለም ትኖራለች!
    የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)
    ጥር 29 ቀን፥ 2013 ዓ. ም.

    ሱዳን ያደረገችውን ወረራ

    Anonymous
    Inactive

    የጥላቻና ዘር ፍጅት ቅስቀሳ በውጤት ደረጃ ሀገርና ሕዝብን የህልውና አደጋ ላይ ይጥላል
    ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ!

    ድርጅታችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በሀገራችን ውስጥ እስካሁን የተካደው ኢትዮጵያዊ ዜግነት ተገቢውን እውቅና እንዲያገኝ፣ ዜግነት የፖለቲካችን ማዕከል እንዲሆን የሚያስችል መሠረታዊ የትርክት ለውጥና የመዋቅር ክለሳ እንዲደረግ በርካታ ጥሪዎችን ሲያደርግ ቆይቷል። ለሀገራችችን የፖለቲካ ምስቅልቅል (crisis) መነሻ የሆነው የጥላቻ ትርክት በሕገ-መንግሥትና በመዋቅሮች መስረፅ ምክንያት መሆናቸውን በመገንዘብ፥ ሕዝባችን ከባድ መስዋዕትነትን የጠየቀ የለውጥ እንቅስቃሴ ሲያደርግ ቆይቷል። በዚህም ቀላል የማይባሉ እመርታዎችን ያስመዘገበ ቢሆንም፥ በዋናነት የአፋኙ ሥርዓት አካልና ወራሽ የሆነ ስብስብ የሕዝባችንን ቅን ልቦና ባጎደፈ መልኩ የጽንፈኝነት ባህሪውን ለጊዜው ደብቆና ስሙን ብቻ ቀይሮ የሕዝባችንን የለውጥ ሂደት አግቶት ይገኛል።

    የአማራ ሕዝብና የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) በትሕነግ ላይ የነበረው አቋም የተፈተሸ፣ የጠራና የነጠረ ስለመሆኑ አስረጅ አያስፈልገውም። አብን ከሁለት ዓመታት በፊት ትሕነግ ሽብርተኛ ድርጅት መሆኑን በመጥቀስ ከሰላማዊ የፖለቲካ ፖርቲዎች ዝርዝር እንዲሰረዝና ጉዳዩ በሕግ የበላይነት ማዕቀፍ እንዲታይ ማሳሰቡ ይታወሳል።  በወቅቱ መንግሥት ከትሕነግ ጋር አብሮ በአንድ ጥምረት ውስጥ ሆኖ የሚሠራበት ነበር። አብዛኛው የሀገራችን የፖለቲካ ኃይሎች በአብን መግለጫ ቢያንስ ተደናግጠው እንደነበር የሚታወስ ሃቅ ነው።

    አብን የአማራ ሕዝብ ሁለንተናዊ ንቅናቄ አካል እንደመሆኑ መጠን ዝቅተኛው የፖለቲካ ስምሪቱ ሀገራችን በጽንፈኛ ኃይሎች ቅንጅት እጅ ዳግም እንዳትወድቅ መከላከል ነው። የኮሮናቫይረስ (COVID-19) ወረርሽኝ ስጋትን ተከትሎ በሀገራዊ የምርጫ መርኃግብር ላይ በታየው የፖለቲካ ችግር ወቅት የወሰድነው አቋም አብን ኢትዮጵያን በተመለከተ ላለው የማያወላዳ አቋም ዓይነተኛ ጠቋሚ መሆኑ አያከራክርም።

    ድርጅታችን አብን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ችግር ሊፈታ የሚችለው መሠረታዊ ለውጦችን በማድረግ እንጅ በስምና በቅብ ለውጥ ሊሆን እንደማይችል በመረዳት ሀገራችን በሽግግር መንግሥት ምሥረታ ሳይሆን በሽግግር ጊዜ ምዕራፍ ማለፍ እንዳለባት አሳውቆ ነበር። በተያያዘ ሁኔታ በሽግግር ጊዜ ውስጥ ዘላቂ እልባት ማስገኘት የሚችሉ አንኳር የለውጥ ተግባራት መፈፀም እንዳለባቸው ገልፆ ጥሪ ማስተላለፉም ይታወሳል። ነገር ግን በጥሬ የስልጣን ግብግብና በጥላቻ ባሕል የተቃኘው የሀገራችን አጠቃላይ የፖለቲካ ስምሪት ዘላቂ ተግዳሮት ሆኖ በመቀጠሉ፥ ተፈላጊው ለውጥ እውን ሊሆን ካለመቻሉም በላይ በሕዝባችን ላይ ተከታታይ የዘር ማጥፋትና የዘር ማፅዳት ጥቃቶች ተፈፅመዋል። የዜሮ ድምር የፖለቲካ ዘይቤን የቀጠለ ሲሆን በሀገራዊ መግባባትና ትብበር መሠራት ያለባቸውን ጉዳዮች በፉክክርና በጥላቻ ለመፍታት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ሊገቱ ባለመቻላቸው ምክንያት የሕዝባችን ትግል ገና ተቀናጅቶና ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተገንዝበናል።

    በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያዊነትን እና የኢትዮጵያዊነትን ትሩፋቶች በብቸኝነት ለመበየንና ለማከፋፈል የቋመጡ ጽንፈኛ መንግሥታዊ አካላት ሀገራችንን ተፈትሾ በወደቀው የሴራ ፖለቲካቸው አዙሪት ውስጥ ለማቆየት ከፍተኛ ርብርብ እያደረጉ ይገኛሉ። በርካታው የሀገራችን ክፍል የደህንነት ስጋት ያንዣበበት ሲሆን፥ የሕዝብ በሰላም የመንቀሳቀስም ይሁን በሕይወት የመኖር መብት በመደበኛነት አደጋ ውስጥ ይገኛል።

    አብን በዚህ ዓመት በሚካሄደው ሀገራዊ ምርጫ ለመሳተፍ ሲወስን የጥላቻና የሴራ ፖለቲካ ግንባር ቀደም ተጠቂ ድርጅት በሆነበት አግባብ ነው። የምርጫ ትርጉም በአንድ ቀን ውስጥ ተከፍቶ በሚዘጋ ሳጥን ውስጥ በሚጨመሩ ካርዶች የታጠረ እንዳልሆነም ይገነዘባል። በሀገራችን ውስጥ ያለው የቅድመ ምርጫ መደላድል ያለበት ሁኔታ ለሕዝባችን የተሰወረ አይደለም። በተለይም የአማራን ሕዝብ ማገት የፖለቲካ ስልት ሆኖ የቀጠለ እውነታ ነው፤ አብን የአማራ ሕዝብ ሀቀኛና የማያወላዳ እንዲሁም ጸረ-ጭቆናና ጸረ-ዘረኝነት የትግል እንቅስቃሴ በቀጥታ የወለደው ድርጅት በመሆኑ አማራን የሚፈርጁና የሚያጠቁ ጽንፈኞች ዓይናቸውን ለአፍታ እንኳን ዘወር እንደማያደርጉለት ይታወቃል።

    ከአማራ ክልል ውጭ በተለይም በኦሮሚያና በቤኒሻንጎል ክልል ውስጥ ባሉት የአብን መዋቅሮችና አመራሮች ላይ የተለያዩ ጥቃቶች ሲፈፀሙም ቆይተዋል፤ አሁንም ቀጥለዋል። በተለይም የክልሎቹ ባለስልጣናት በሆኑ የብልፅግና ፖርቲ አባላት የሚፈፀሙ ችግሮች መሆናቸውን መነሻ በማድረግ፥ ከፖርቲው ከፍተኛ አመራሮች ጋር በመነጋገር ለመፍታት ጥረት ሲያደርግ ቆይቶ ባለመሳካቱ ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ማመልከቻ አቅርቦ በምርመራ ላይ ይገኛል።

    ጉዳዮቹ በዚህ አግባብ በሚገኙበት ሁኔታ ጭምር “የኦሮሞ ብልፅግና” ከፍተኛ አመራሮች በማኅበራዊ ድረ-ገፅ በአብን፣ በአመራሮቻችን፣ አባላቶቻችን፣ ደጋፊዎቻችን እና በአጠቃላይ በአማራ ሕዝብ ድርጅቶችና አመራሮች ላይ የሀሰት፣ የአፍራሽና የጥቃት ጥሪዎችን በተደጋጋሚ እያስተላለፉ ይገኛሉ። የብልፅግና ፖርቲ እንደተቋም በሚፈፀሙ ጥሰቶች ላይ ምንም ዓይነት ተጨባጭ እርምት ለማድረግ ባለመፈለግ በቀጥታ የተቀበላቸውና የአማራን ሕዝብ በተመለከተ ያለውን አቋም በምግባር፣ በድርጊትና በቸልታ አረጋግጧል።

    ጥር 25 ቀንም በተለያዩ የኦሮሚያ አካባቢዎች በተደረጉ ሰልፎች በዋናነት አብንን የሚያጠለሹና የሚያወግዙ እንዲሁም በሕዝባችን ላይ ቀጣይ ስጋትን የጋረጡ ድምፆች ከፍ ብለው ሲስተጋቡ ተሰምተዋል። አብንን “ከኦነግ ሸኔ” ጋር የሚያመሳስሉ መፍክሮች ተሰምተዋል።

    ስለሆነም፦

    1/ በቅርቡ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ እየተፈፀመ ያለውን ገደብ የለሽ የፖለቲካ ነውረኝነትና የዘረኝነት እንቅስቃሴ ለመቃወም በባልደራስ ፓርቲ ተጠርቶ የነበረውን ሕዝባዊ ሰልፍ በማንአለብኝነት የከለከለ መንግሥት ለፖርቲ ፍጆታ ሲሆን ሰልፍ መጥራቱና መፍቀዱ፤

    2/ በሰልፉ ላይ (ጥር 25 ቀን 2013 ዓ.ም. የተደረገው የብልፅግና ፓርቲ ሰልፍ) የጥላቻና የጥቃት ጥሪዎችን ሲመሩ የነበሩት በስምና በኃላፊነት የሚታወቁ የመንግሥትና የብልፅግና ፖርቲ አመራሮች መሆናቸው፤

    3/ ጥር 25 ቀን 2013 ዓ.ም. በተደረገው የብልፅግና ፓርቲ ሰልፍ ላይ ጎልተው የተሰሙት ድምፆች የክልሉ አመራሮች በማኅበራዊ ድህረ-ገጽ ሲፅፏቸው የነበሩ ኃሳቦች ቀጥተኛ ግልባጭ መሆናቸው፤

    4/ በዚህም በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በአጠቃላይ ያለውን የፖለቲካ አፈና ወደተሟላ እርከን ለማሸጋገር በማሰብ አብን በክልሉ ውስጥ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ለመግታትና በክልሉ የሚኖረውን የአማራ ሕዝብና ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ በጭቆና ቀንበር ስር የማቆየት ዓላማ ያነገበ ተግባር መሆኑ፤

    5/ በተለይም ጥር 25 ቀን 2013 ዓ.ም. በተደረገው የብልፅግና ፓርቲ ሰልፍ ላይ በአማራ ሕዝብ ላይ በተደጋጋሚ የዘር ፍጅት ለመፈፀም ጽንፈኛ ኃይሎች መንደርደሪያ አድርገው የሚጠቀሙበት “ነፍጠኛ” የሚለው ቃል በሰፊው ሲገለፅ የነበረና በግልፅም “ነፍጠኛ ይውጣ” የሚል ሀሳብ ሲሰማ የነበረ መሆኑ፣

    6/ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያሉ ኃላፊነት የጎደላቸው ጽንፈኛ አመራሮች በአማራ ሕዝብ ላይ እየደረሰ ላለው ጥቃት ሽፋን በመስጠትና በቀጥታ በመሳተፍ እንደሚያስፈፅሙ የተረጋገጠ ጉዳይ ሆኖ እያለ፥ በታየው ደረጃ የተላለፈውን የጥላቻና የጥቃት ጥሪ የመንግሥት ሚዲያዎች መዘገባቸው እና የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትርም እርምት መስጠት እየተገባቸው፥ ‘ቡራኬ’ መስጠታቸው እጅግ አሳዛኝ የሆነና በቀጣዩ የሀገራችን የፖለቲካ ሂደት ላይም ከፍተኛ ስጋትን እንደሚፈጥር መረዳት ይቻላል።

    በአጠቃላይ የሀገራችንን የፖለቲካ እንቅስቃሴ የተለየ ፖለቲካዊ እይታ የማስተናገድ ዝንባሌና ቀጣዩን ምርጫ በተመለከተ በመንግሥት በኩል እየታየ ያለው አቋምና አፍራሽ እንቅስቃሴ በአስቸኳይ እንዲቆም እየጠየቅን፥ የአብን የብሔራዊ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ጉዳዩን በቀጥታ ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድና በግልባጭ ለሚመለከታቸው አካላት በደብዳቤ አሳውቋል።

    በመጨረሻም መላው ኢትዮጵያውያን፥ በተለይም የአማራ ሕዝብ፥ የብልፅግና ፓርቲ ሰልፍ ላይ የተስተጋባው የጥላቻና ዘር ፍጅት ቅስቀሳ በውጤት ደረጃ ሀገርና ሕዝብን ለህልውና አደጋ የሚጥል መሆኑን በመረዳት የተፈፀመውን አስነዋሪ ድርጊት በጽኑ እንዲያወግዝና አብን ከሚያደርጋቸው የፍትህ፣ እኩልነትና ነፃነት ትግሎች ጎን እንዲሰለፍ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

    የሴራ ፖለቲካ ምዕራፍ የሚዘጋበት፣ የጥላቻና የፍረጃ ፖለቲካ ላንቃ የሚዘጋበት ጊዜው አሁን ነው!

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)
    ጥር 25 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፤ ሸዋ፤ ኢትዮጵያ!

    የጥላቻና ዘር ፍጅት ቅስቀሳ በውጤት ደረጃ ሀገርና ሕዝብን የህልውና አደጋ ላይ ይጥላል

    Anonymous
    Inactive

    የብልፅግናው ታዬ ደንደዓ … ስለማያወቀው ታሪክ የሚጽፈው ነገርስ ምን ይሉታል?
    (ጋዜጠኛ ፋሲል የኔዓለም)

    ለታላቋ ኢትዮጵያ ተብሎ ዝም ቢባል አሁንስ በዛ። ታዬ ደንደዓ፣ የብልፅግናው ባለስልጣን፣ ስለማያውቀው ታሪክ እየጻፈ የአብይ አህመድን መንግሥት አጣብቂኝ ውስጥ እየከተተው ነው። አብይ አህመድ ህወሓት የቀደዳትን ኢትዮጵያን እንቅልፉን አጥቶ ለመስፋት ይሞከራል፤ ታዬ ደንደዓ እና መሰሎቹ ደግሞ በጎን ይተረትራሉ።

    አብይ አህመድን ለማመስገን የኢትዮጵያን ታሪክ ማጠልሸት አይስፈልግም። አብይ በተደጋጋሚ እንዳለው ነው፤ ኢትዮጵያ ከሱ በፊት በነበሩ መሪዎች እየተገነባች እዚህ የደረሰች አገር ናት።

    ታዬ ደንደዓ ስለ ቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተወልድ የተሳሳተ ታሪክ ጻፈ። በዚህ ስህተቱ ሳያፍር ቀጥሎ ደግሞ የዛግዌንና የዶ/ር አብይን መንግሥት አወዳድሮ ሌላ የማይሆን ታሪክ ጫረ። “ሞኝ ባያፍር፣ የሞኝ ዘመድ ያፍር” ነው ነገሩ።

    ታዬ ከዛገዌ መጨረሻ እስከ አፄ ኃይለሥላሴ ዘመን የነበረውን የነገሥታቱን ዘመን ምንም ሥራ እንዳልሠራ አድርጎ ረገመው። በአጭሩ የደርግን ፕሮፓጋንዳ ደገመው። ዓላማው እነሱ የአማራ መንግሥት የሚሉት የሰሎሞናዊው መንግሥት ምንም እንዳልሠራ በማሳየት አማራን መወረፍ ነው።

    አላዋቂነት የወለደው ድፍረትና ስልጣን የወለደው ትዕቢት ታዬን እያቅበዘበዘው ነው።

    ከዛገዌ በኋላ ሸዋ ላይ የተመሠረተው ታላቅ ስልጣኔ በማን እንደፈረሰ ታዬ የሚያውቅ አይመስልም። አክሱም፣ ዛግዌና የሰሎሞናዊው ስርወ-መንግሥት ስልጣኔዎች የማይነጣጠሉ፣ ተያያዥነትና ተደጋጋፊነት ያላቸው የኢትዮጵያ ታሪኮች መሆናቸውን ለማወቅ የልብ ብርሃን ያስፈልጋል።

    ደግሞ የታሪክ ሒሳብ ማወራረድ ውስጥ ከተገባ በማን እንደሚከፋ ታዬና ቢጤዎቹ ያወቁትም ያሰቡበትም አይመስልም። ደርግ እንዳስወራውና ታዬ እንደደገመው ሳይሆን፥ የኢትዮጵያ ነገሥታት ለእደ ጥበብ ሰዎች አክብሮት ነበራቸው። በሄዱበት ሁሉ ይዘዋቸው ከሚዞሩ ሰዎች መካከል የእደ ጥበብ ባለሙያዎች ይገኙበት ነበር። የኢትዮጵያ ነገሥትታና የሙስሊም ነጋዴዎች ቁርኝት በታሪክ ተመዝግቦ የሚገኝ ነው። ይህ ሲባል እንከን አልነበረም ማለት አይደለም፤ እንኳንስ ትናንት ዛሬም ብዙ እንከኖች አሉ።

    የመካከለኛው ዘመን ነገሥታት የሠሩትን ሥራ ለማወቅ እኮ የዛሬዋን አዲስ አበባ ቆፈር ቆፈር ማድረግ ነው። አንቶን ዲ አባዲ የተባለው ፈረንሳዊው አሳሽ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የቆመበት ቦታ ላይ የነበረውን በመካከለኛው ዘመን የተሠራውን የቤተ ክርስቲያን ፍርስራሽ ዓይቶ አግራሞቱን እንዲህ ሲል ገልጾ እንደነበር Abba Emile Foucher እንዲህ ሲል ጽፏል፦

    Who could have been the architect of such a building? … People who constructed such a building with well-cut stone, linked with mere clay, must have been of another type of civilizations.

    የረርን፣ በራራን፣ ፈጠጋርን፣ ጋሞን፣ ጉራጌን በአጠቃላይ የሸዋን የጥንት ታሪክ ያጠና ሰው፣ የኢትዮጵያ ነገሥታት የኢትዮጵያን ሕዝብ አንድነት ለማጥናት እየዘመቱ፣ በጎን ደግሞ ታላቅ ስልጣኔ ገንብተው እንደነበር ይረዳል። ያው እነዚህ ስልጣኔዎች እንዴት እና በእነማን እንደፈረሱ ዝርዝር ውስጥ አልገባም። ታሪካችን ስለሆነ ከመቀበልና ወደፊት ከመጓዝ ውጭ በታሪክ ‘እኘኘ…’ ስንል አንገኝም። እንደ ታዬ ደንደዓ ዓይነት አምቦጫራቂዎች ከበዙ ግን እውነቱን ከመናገር ወደ ኋላ አንልም።

    ታዬ የዛግዌ መንግሥትን ከአብይ አህመድ መንግሥት ጋር ሲያነጻጻር በተዘዋዋሪ መንገድ የአብይን መንግሥት የኦሮሞ መንግሥት አድርገን እንድንቀበለው እየነገረን ነው። አብይን የሚደግፈው አብዛኛው ሰው የአብይን መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት እንጅ የኦሮሞ መንግሥት አድርጎ አያየውም። ከተሳሳትኩ እታረማለሁ። እንዲህ ከሆነማ አንዳንዶች “ተረኝነት አለ!” የሚሉት ትክክል ነው ማለት ነው።

    አብይ አህመድ የራሱን መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት እንጂ የኦሮሞ መንግሥት ብሎ ሲጠራው ወይም ተራው የኦሮሞ ነው በሚል አስተሳሰብ ስልጣን እንደያዘ ሲናገር ሰምቼ አላውቅም። አብይን የደገፉት ሰዎች ሁሉ አብይን በኢትዮጵያዊነት እንጂ በኦሮሞነት የሚስሉትም አይመስለኝም። አብይ ከኦሮሞ ነገድ ቢወጣም፥ ስልጣን የያዘው በኢትዮጵያዊነቱ እንጂ የስልጣን ተራው የኦሮሞ ስለሆነ አይደለም። ስልጣን በብሔር ተራ ተከፋፍሎ ከሆነማ ኦሮሞ በየትኛው የዕጣ ድልድል ነው ከሶማሌ፣ ከአፋር፣ ከጋምቤላ፣ ከአማራ ወይም ከጉራጌ ቀድሞ ስልጣን የያዘው? እስኪ ዕጣው መቼ እንደወጣና እንዴት እንደወጣ ንገሩን?

    የእነ ታዬ ደንደዓ አመለካከት በጣም አደገኛ የሚሆነው በምርጫ ቢሸነፉ፣ እንደ ህወሓቶች ሁሉ፣ “ኦሮሞ መሪ ካልሆነ ወይም በእጅ አዙር ካልገዛ ስልጣን አንለቅም” የሚሉ መሆናቸው ነው። ስልጣንን በብሔር መንጽር ማየት ኢትዮጵያዊነትን ማዳከም ብቻ ሳይሆን፣ የብሔር አምባገነንነትም ይፈጥራል። ዋ!

    የታዬ አስተሳሰብ ያላቸው ብዙ የኦሮሞ ብሔርተኞች መንግሥት ውስጥ እንዳሉ ይታወቃል። ዶ/ር አብይ አህመድ ከእነዚህ በብሔር ከሚያስቡ ሰዎች በላይ ከፍ ብሎ የሚበር ስልጡን ሰው እንደሆነ በግሌ አስባለሁ። ስለኢትዮጵያ ታሪክ ያለው አመለካከትም ከብዙዎቹ የተለየና በእውቀት ላይ የተመሠረተ ነው። አብይ እንደነ ታዬ ደንደዓ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ አያላግጥም። በአላዋቂነት ድፍረትም ሆነ በስልጣን ግብዝነት የማያውቀውን ታሪክ ሲዘባርቅ ሰምቼው አላውቅም። አብይ ንባብ ከአላዋቂነት ድፍረት ነጻ ያወጣው ሰው ነው።

    የኦሮሞ ብልፅግና ውስጥ እንደ አብይ አህመድ ንባብ ነጻ ያወጣቸው አርቀው የሚያዩ ስንት ሰዎች አሉ? ስለአንድ አብይ ብለን የኦሮሞ ብልፅግናን ሁሉ ይቅር እንበለው ወይስ ስለኦሮሞ ብልፅግና ብለን አንድ አብይ አህመድን እንርገመው የሚለውን ጥያቄ መመለሱ ከባድ እየሆነ ነው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የብልፅግናው ታዬ ደንደዓ

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ለምርጫ አስፈፃሚነት ከተመለመሉት ሰዎች መሀከል ጥያቄ ያነሳባቸውን ለምርጫ ቦርድ አመለከተ

    ‘የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለምርጫ አስፈፃሚነት የመለመላቸው የምርጫ አስፈፃሚዎች ገለልተኛ ናቸው ወይስ አይደሉም?’ የሚለውን ለማጣራት ለሁሉም ፖለቲካ ፓርቲዎች የአስፈፃሚዎቹን ስም ዝርዝር በመላክ ማጣራት እያካሄደ ነው። ቦርዱ አስፈጻሚዎችን ከመለመለ በኋላ የተመለመሉትን አስፈጻሚዎች ስም ዝርዝር ለፖለቲካ ፓርቲዎች በመላክ ፓርቲዎች ገለልተኝነታቸው ላይ አስተያየታቸውን እንዲሰጡ እንደሚያደርግ መናገሩ የሚታወስ ነው። በዚህም መሠረት በመጀመሪያው ዙር ወደ 750 ምርጫ አስፈጻሚዎች ስም ዝርዝር የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ደርሶታል።

    የተላኩላቸውን ምርጫ አስፈጻሚዎች የፓርቲውን መዋቅር በመጠቀም ገለልተኝነታቸውን ለማጣራት ሙከራ እንዳደረጉ ለዜጎች መድረክ የገለፁት የኢዜማ ድርጅት ጉዳይ ኃላፊ አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ፥ ዜጎች መድረክ ከዚህ ቀደም የምርጫ አስፈፃሚዎቹን ስም ዝርዝር ይዞ ለማጣራት አቅም አላችሁ ወይ ብላ ጥያቄ አንስታላቸው እንደነበር አስታውሰው፤ የፓርቲውን መዋቅር በመጠቀም ምርጫ ቦርድ የመለመላቸውን ምርጫ አስፈጻሚዎች ገለልተኝነት ማጣራት መቻላቸውን ተናግረዋል። በማጣራት ሂደቱም አንዳንዶቹ የምርጫ አስፈፃሚዎች ከዚህ ቀደም የኢሕአዴግ አባል የነበሩ አሁን ደግሞ የብልፅግና አባል መሆኑን እንደደረሱበትና ይህንንም በማስረጃ በማስደገፍ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መላካቸውን ለዜጎች መድረክ አስታውቀዋል።

    “የእኛ መዋቅሮችም የብልፅግና አባል የሆኑትን ሰዎች አጣርተው ከእነ ስም ዝርዝራቸውና ከመቼ ጀምሮ የብልፅግና አባል እንደሆነ ጠቅሰው ስማቸውን ልከውልናል። አንዳንዶቹ ሰዎች ለብልፅግና ፓርቲ የአባልነት መዋጮ የከፈሉበትን ደረሰኝ ጭምር አያይዘው ልከውልናል። ይህንንም ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ገቢ አድርገናል” ብለዋል።

    ምርጫ ቦርድ በሁለተኛ ዙር የሌሎች ሰዎችን ስም ዝርዝር የላከላቸው መሆኑን የጠቀሱት ድርጅት ጉዳይ ኃላፊው፥ ይህንንም የሚያጣሩ መሆናቸውንና ተገቢውን ማጣራት ካደረጉ በኋላ ለቦርዱ ምላሻቸውን እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።

    አንዳንድ ቦታዎች ላይ በምርጫ አስፈጻሚነት እየተሳተፉ ያሉ ሰዎች በግልፅ ወገንተኝነት የታየባቸው ናቸው ያሉት ዋሲሁን ተስፋዬ፣ ዋናው የአስፈጻሚነት ሚና ገለልተኝነት መሆኑን ጠቅሰው፥ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምርጫ አስፈፃሚዎችን ገለልተኝነትን በጥንቃቄ ሊመረምረው ይገባል ብለዋል። ቦርዱ፣ ፓርቲያቸው የገለልተኝነት ጥያቄ ያነሳባቸውን ሰዎች ዝርዝር በመመልከት ሌሎቹ አስፈጻሚዎች እንዴት ነው የተመለመሉት የሚለውን ያጣራል ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ ገልፀዋል።

    ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፥ ለምርጫ አስፈጻሚነት የመለመላቸውንና ገለልተኝነታቸው ላይ ጥያቄ ያነሳንባቸውን እነዚህን ሰዎች በሌሎች ሰዎች ይቀይራል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፤ መቀየርም ይኖርበታል ብለዋል አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ።

    ኢዜማ በገለልተኝነታቸው ላይ ጥያቄ ያነሳባቸውና ስም ዝርዝራቸው ለምርጫ ቦርድ የተላከው የምርጫ አስፈፃሚዎች፣ ሲፈርሙባቸው የነበሩ የደሞዝ መክፈያ ሰነድና የብልፅግና አባል መሆናቸውን የሚያሳይ የአባልነት መዋጮ የከፈሉበት ደረሰኝ በማያያዝ ለምርጫ ቦርድ ገቢ ማድረጉን ለማወቅ ተችሏል።

    ሰነድ ማስረጃ ያልተገኘባቸው ደግሞ የሰው ማስረጃ በማቅረብ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ጥር 19 ቀን 2013 ዓ.ም. በደብዳቤ እንዲደርሰው መደረጉን የፓርቲው መጽሔት “የዜጎች መድረክ” መረዳት ችላለች።

    ኢዜማ፥ በመንግሥት ሥር ያሉ እንደ ሥራ ፈጠራ ኮሚሽን ዓይነት ተቋማት፣ ምርጫ አስፈጻሚ መሆን የምትፈልጉ ሰዎች መመዝገብ ትችላላችሁ የሚል ማስታወቂያ ለጥፎ ምልመላ ሲያካሄዱ ደርሶበት ይህንን ከእነ ሰነድ ማስረጃው ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በማቅረብ፣ ከቦርዱ ውጪ የትኛውም አካል ምርጫ አስፈፃሚዎችን የመመልመል ስልጣን እንደሌለው ማስታወቁ አይዘነጋም።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)

    ኢዜማ ለምርጫ ቦርድ ያመለከተው

    Anonymous
    Inactive

    ከባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) የአዲስ አበባ እና ድሬድዋ ከተማ አስተዳድሮች ድምጽ መስጫ ቀንን በተመለከተ የተሰጠ መግለጫ

    ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የ6ኛው ሀገር አቀፍ የመጨረሻ የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ በአዲስ አበባ እና ድሬድዋ ከተማ አስተዳድሮች ምክር ቤቶች እና ለፌደራል የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ድምጽ መስጫ ቀን በሳምንት ወደፊት መገፋቱን በተመለከተ የፓርቲያችንን ቅሬታ በጽሁፍ ለቦርዱ አስገብተናል።

    ቦርዱ በደብዳቤ ላስገባነው ቅሬታ ተገቢውን ምላሽ ሳይሰጥ፥ የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ ማጽደቁን በማኅበራዊ ሚዲያ ገፁ ታኅሣሥ 30 ቀን፥ 2013 ዓ.ም.  (January 8, 2021 G.C.) አሳውቋል። ፓርቲያችን ቦርዱ የድምጽ መስጫውን ቀን በአዲስ አበባ እና ድሬድዋ ብቻ ከሀገሪቱ የምርጫ ቀን በሳምንት ዘግይቶ እንዲደረግ ስለመወሰኑ የሰጣቸውን አስተዳደራዊ ምክንያቶች ፓርቲያችን መርምሯል። ቦርዱ ያቀረባቸውን የሚከተሉትን ምክንያቶች ፓርቲያችን ባልደራስ አሳማኝ ሁነው አላገኛቸውም።

    ቦርዱ የሰጣቸው ምክንያቶች የሚከተሉት ናቸው፡-

    1. የምርጫ አስፈፃሚዎች በአንድ ጊዜ የአንድ ምርጫ አካባቢ የምርጫ ውጤትን ወደ ማዕከሉ መላክ ይችላሉ፤ ከዚህ በላይ ከሆነ ግን ስህተት ሊፈፀም ይችላል፤
    2. መራጮች ካለምርጫ ካርድ ሊመርጡ ይችላሉ፤
    3. ወደ ሌሎች አካባቢዎች የተሰማሩ የምርጫ ቦርድ አስፈፃሚዎች እና የፓርቲዎች የምርጫ ታዛቢዎች ውጤቱን አጠናቅረው ወደ አዲስ አበባ እና ድሬድዋ አስኪመለሱ ድረስ ጊዜ ይፈጅባቸዋል።

    [1ኛ] የምርጫ አስፈፃሚዎች በሁሉም የምርጫ አካባቢዎች በበቂ መጠን እንዲሰማሩ ማድረግ የምርጫ ቦርድ ተግባር ነው። የምርጫ የአስፈፃሚዎች ቁጥር ከምርጫ አካባቢዎች ጋር ተመጣጣኝ እንዲሆን ማድረግ እየተቻለ፥ በአንድ ጊዜ ከአንድ በላይ የምርጫ አካባቢ ውጤትን ወደ ማዕከል መላክ አይቻልም የሚል ምክንያት ውሃ አይቋጥርም።

    [2ኛ] ‘መራጮች ካለምርጫ ካርድ ሊመርጡ ይችላሉ’ የሚለው የቦርዱ አባባል ምንም ስሜት የማይሰጥ እና አሳፋሪ ነው። የምርጫ ቦርድ አስፈፃሚዎች እና የምርጫ ታዛቢዎች የምርጫ ድንጋጌዎች ተግባራዊ መሆናቸውን መከታተል ካልሆነ ሌላ ምን ሊሠሩ ነው?

    [3ኛ] ሌሎች አካባቢዎች የተሰማሩ የቦርድ የምርጫ አስፈፃሚዎች እና የፓርቲዎች የምርጫ ታዛቢዎች ወደ አዲስ አበባ እስኪመለሱ ጊዜ ይወስድባቸዋል በሚል የቀረበው ምክንያትም በኢትዮጵያ ውስጥ የሰው ኃይል እጥረት ያለ የሚያስመስል ነው። ሲጀመር ለሁሉም አካባቢ በቂ ቁጥር ያላቸው የምርጫ አስፈፃሚዎችን እና የምርጫ ታዛቢዎችን ለማሰማራት ምን የሚያስቸግር ነገር አለ?

    አሁንም ፓርቲያችን በተለይ በሁለት ዋነኛ ምክንያቶች የአዲስ አበባ እና የድሬደዋ አስተዳደሮች ድምጽ መስጫ ቀን ከፌደራል ድምጽ መስጫ ቀን የተለየ እንዲሆን መደረጉ (ማለትም ከግንቦት 28 ቀን 2013 ወደ ሰኔ 5/2013 እንዲዛወር መደረጉ) የገዥውን ፓርቲ ፍላጎት ብቻ ከግምት ውስጥ ያስገባ ነው። ሕዝቡ ነፃ ፍላጎቱን ያለ ተፅዕኖ እንዲገልፅ የሚያደርግ አይደለም።

    በባልደራስ በኩል የአዲስ አበባ እና የድሬዳዋ ከተሞች ምርጫ ከሌላው ሀገራዊ ምርጫ በአንድ ሳምንት መገፋቱ፣

    1ኛ. በሕገ ወጥ መንገድ ኦህዴድ/ብልፅግና ከከተማው ነዋሪ ውጪ መታወቂያ ካርድ የሰጣቸው ግለሰቦች ግንቦት 28 ባሉበት አካባቢ ከመረጡ በኋላ በሳምንቱ ሰኔ 5/2013 ካሉበት ቦታ ወደ አዲስ አበባ ተመልሰው በአዲስ አበባ መታወቂያቸው ዳግም ምርጫ ማድረግ እንዲችሉ የታቀደ እንደሆነ፣

    2ኛ. ከሳምንት በኋላ በሚደረገው ምርጫ ተቃዋሚዎችን ሊመርጥ የሚችለውን መራጭ ሕዝብ በብሔራዊ ምርጫው ውጤት ተስፋ ቆርጦ በሳምንቱ በሚካሄደው የከተሞች ምርጫ እንዳይሳተፍ የሥነ ልቦና ተፅዕኖ ውስጥ እንዲገባ እና ለመምረጥ እንዳይተጋ ለማድረግ የተመረጠ ዘዴ እንደሆነ እናምናለን።

    ቦርዱ ባልደራስ ብቻ ሳይሆን ሌሎች ፓርቲዎች ላስገቡት ቅሬታ መልስ ሳይሰጥ ታኅሣሥ 30 ቀን፥ 2013 ዓ.ም.  (January 8, 2021 G.C.) የምርጫ ሰሌዳው የመጨረሻ ተብሎ ለሕዝብ ይፋ ማድረጉ ፓርቲያችንን በእጅጉ ያሳዘነ ጉዳይ ነው። ቦርዱ የፓርቲያችንን ፍትሃዊ ስጋት ወደ ጎን በማለት በምርጫው ላይ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ በሀገራችን የዴሞክራሲ ሥርዓትን ለማዋለድ ለሚደረገው ትግል የማይጠቅም መሆኑን ፓርቲያችን ከልብ ያምናል። ስለሆነም በዚህ ጉዳይ ላይ ያቀረብነው ፍትሃዊ ጥያቄ ምላሽ አግኝቶ አዲስ አበባ እና ድሬድዋ ከተሞች የድምጽ መስጫ ቀን በተመሳሳይ ቀን፥ ማለትም ግንቦት 28 ቀን 2013 ዓ.ም. እንዲሆን በድጋሚ እንጠይቃለን። ቦርዱ አሳማኝ ባልሆኑ ምክንያቶች የደረሰበትን ውሳኔ እንደ ገና በማጤን እንዲያሻሽለው ፓርቲያችን ጥሪውን ያቀርባል። ቦርዱ ይህን የፓርቲያችንን ፍትሃዊ ጥያቄ ገፍቶ ቢያልፈው ግን ቀጣዩ ምርጫ እና እሱን ተከትሎ ሊፈጠር ለሚችለው የተቀባይነት ችግር ቦርዱ ከወዲሁ ኃላፊነቱን የሚወስድ መሆኑን ያሳውቃል።

    እንዲሁም፥ ከምርጫው ጋር በተያያዘ አዲስ አበባ ላይ ለምርጫ አስፈፃሚነት ቦርዱ ካቀረባቸው 64 ግለሰቦች ውስጥ 47ቱ የሕዝብ አመኔታ ከሌላው ብቻ ሳይሆን ባለፉት 27 ዓመታት ከህወሓት ትዕዛዝ እየተቀበለ የአማራውን ሕዝብ ቁጥር በመቀነስ ለፅንፈኛ ሥርዓቱ በታማኝነት ሲያገለግል ከነበረው የ“ማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጄንሲ” እና 15ቱ ደግሞ “ሥራ ፈላጊ ኮሚሽን” ተብሎ ከሚታወቀው የካድሬዎች መጠራቀሚያ ተቋም መሆናቸውን በተመለከተ ለቦርዱ በፅሁፍ ቅሬታችንን ያስገባን መሆኑን እየገለፅን፤ ይህን ጉዳይ በተመለከተ ፓርቲያችን በተከታታይ በሚያወጣው መግለጫ የተቃውሞውን ዝርዝር ይፋ የሚያደርግ መሆኑን ይገልፃል።

    የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ

    አዲስ አበባ እና ድሬድዋ

    Anonymous
    Inactive

    ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተሰጠ መግለጫ

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለ6ተኛው ሀገራዊ ምርጫ የሚያደርገውን ዝግጅት አስመልክቶ የጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱ፥ እንዲሁም የተለያዩ ተግባራትን ለማከናውን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በጋራ እየሠራ እንደሚገኝ ይታወቃል። ከዚህም መካከል የምርጫ ጸጥታን ማረጋገጥ እንዲሁም የምርጫ ክልል እና የዞን ቢሮዎችን ለመክፈት መሥራት ይገኙበታል። በዚህም መሠረት ቦርዱ በተለያዩ ወቅቶች ከክልል መስተዳድር ኃላፊዎች ጋር ውይይቶችን ያከናወነ ሲሆን፥ በእነዚህ ውይይቶች ላይ የምርጫ ኦፕሬሽን መዋቅር እና የክልል መስተዳድሮች የሚጠበቁ ሚናዎችን በዝርዝር አቅርቧል። በውይይቶቹ በተደረሰው ስምምነት መሠረት ቦርዱ የሚከተሉትን ዋና ዋና ትብብሮች ከክልል መንግሥታት የጠየቀ ሲሆን እነሱም በዋናነት፦

    1. የአዲስ አበባ ከተማ መስተዳድር – 33 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 3 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
    2. የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ብሔራዊ ክልል መንግሥት – 22 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 3 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
    3. ድሬደዋ ከተማ መስተዳድር – 47 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 1 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
    4. ሶማሌ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት –72 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 11 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
    5. ጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት – 14 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 3 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
    6. ደ/ብ/ብ/ህ ክልላዊ መንግሥት – 113 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 16 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
    7. ሃረሪ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት – 3 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 1 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
    8. አፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት –32 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 5 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
    9. አማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት – 138 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 12 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች
    10. ሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት –19 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 1 ዞን ማስተባበሪያ ቢሮ እና የስልጠና ቦታዎች
    11. ኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት – 179 የምርጫ ክልል ቢሮዎች እና 20 የዞን ማስተባበሪያ ቢሮዎች እና የስልጠና ቦታዎች

    ናቸው። ቦርዱም በጥያቄው ለክልሎች ለዕቅድ እና ለአፈፃፀም ያመቻቸው ዘንድ የምርጫ ክልሎች ዝርዝር እና ቢሯቸው የሚቋቋምባቸው ከተሞች ዝርዝር፣ የዞን ማስተባበሪዎች ዝርዝር እና ቢሯቸው የሚቋቋምባቸው ከተሞች ዝርዝር እንዲሁም ቦርዱ ያወጣውን ረቂቅ የምርጫ ሰሌዳ ቅጂ (copy) አብሮ አቅርቧል።

    ይሁንና ለክልሎች ይህንኑ ለቢሮ መከፈት የሚያስፈልግ ዝግጅት በደብዳቤ በመጠየቅ ለጥር 10 ቀን 2013 ዓ.ም. እንዲያሳውቁ ጥያቄ ያቀረበ ቢሆንም፥ እስከአሁን ድረስ ይህንን ዝግጅት አስመልክቶ ምላሽ ያቀረበ የክልል መስተዳድር የለም። በመሆኑም በደብዳቤ የተገለጹት አስፈላጊ የምርጫ ክልል ቢሮዎችን ለመክፈት የሚያስፈልጉ ትብብሮች ለምርጫው ሂደት አስፈላጊነታቸውን በመገንዘብ ክልሎች ትብብራቸውን እንዲፋጥኑ እንዲሁም በኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ ምግባር አዋጅ 1162/2011 አንቀጽ 161 የተቀመጠውን የመተባበር ግዴታቸውን እንዲወጡ እናሳስባለን።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ
    ጥር 10 ቀን 2013 ዓ.ም.

    ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተሰጠ መግለጫ

    Anonymous
    Inactive

    ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ― አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለ

    ትኩረት ለትግራይ!!!
    ትኩረት ለአስቸኳይ ሰብዓዊ እርዳታ!
    ትኩረት ለሰብዓዊ መብቶች መከበር!

    ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ፥ መንግሥት በትግራይ ክልል ሲያካሄድ የቆየውን ሕግን የማስከበር እርምጃ ተከትሎ በተለያዩ አካባቢዎች ያለው የዜጎች መሠረታዊ ፍላጎቶች ማለትም የምግብ፣ የመጠጥ ውሃ፣ የሕክምና እና የመድኃኒት፣ የደህንነት፣ ባንክ፣ ትራንስፖርት የመሳሰሉት አገልግሎቶች አሁንም ያለመሟላት እና ከፍተኛ የሆነ የሕግና ሥርዓት ያለመከበር ስጋት እንዲሁም ጥቃት ያለባቸው አካባቢዎች እንዳሉ ከታማኝ ምንጮች አረጋግጧል። ጊዜያዊው የክልሉ አስተዳደር ሁኔታዎችን ለማስተካከል እየጣረ ያለበትን ጥረት ብንረዳም፥ ችግሩ ዘርፈ ብዙ ነውና የሁላችንንም ኢትዮጵያውያን ርብርብ እና እገዛ እንደሚጠይቅ ተረድተናል። ሁኔታዎች ከእስከአሁኑም በላይ ተባብሰው ከቁጥጥር ውጭ ሳይሆኑ በፊት አስቸኳይ እርምጃ ሊወሰድ ይገባል።

    በመሆኑም፦

    1. በክልሉ ባለፈው ክረምት ወቅት በአዝርዕት ላይ በደረሰው የበረዶ፣ የመሬት መንሸራተት፣ የጎርፍ አደጋ እና የበረሀ አንበጣ ወረርሽኝ የተነሳ ጉዳት የደረሰ እንደነበርና ከዚህም የተረፈውን በነበረው ጦርነት ምክንያት በበቂ ሁኔታ መሰብሰብ ባለመቻሉ እና በተያያዥ ምክንያቶች ከ3.5 ሚሊዮን በላይ ዜጎቻችን አስቸኳይ የህይወት አድን እርዳታ እንደሚያስፈልጋቸው በመረዳታችን፥ ነገ ዛሬ ሳይባል በአስቸኳይ የምግብና የመጠጥ እርዳታ የሚደርስበትን መንገድ እንዲመቻች፥ ለዚህም ለሚመለከታቸው አካላትና መላው የኢትዮጵያ ዜጎችን ጥሪ እናቀርባለን።
    2. ለሕክምና ተቋማት የመድኃኒት፣ የሕክምና መሳሪያዎች፣ ባለሙያ እና ጥበቃ በማሟላት ማስቀረት የሚቻሉ የጤንነት ችግሮች እንዲቀረፉ እና በተለይ ሕጻናት፣ ሴቶችና አቅመ ደካሞች እንዲረዱ እንጠይቃለን።
    3. ጊዜያዊው የክልሉ መንግሥት እስከታችኛው የፀጥታና የአስተዳደር መዋቅር መልሶ ለማዋቀር እየሠራ እንደሆነ ብንገነዘብም፥ በዘላቂነት ሥራው እስኪሳካ ከነዋሪው እና ከሌሎች እትዮጵያውያን የሕብረተሰብ ክፍሎች የተውጣጣ ሰላምና ማረጋጋቱን ለማገዝ የሚችል ግብረ-ኃይል በማሰማራትም ጭምር ሕግና ሥርዓትን በማስከበር ዜጎቻችን ላይ ያለውን የደህንነት፣ የዝርፊያና የመደፈር… ስጋት በአፋጣኝ እንዲያስቆም እንጠይቃለን።
    4. በክልሉ እርዳታ ወደሚያስፈልጋቸው አካባቢዎች የእርዳታ ቁሳቁሶችና በማከፋፈል ሊያግዙ የሚችሉ በጎ ፈቃደኞች መሰማራት እንዲችሉ ሁኔታዎች እንዲመቻቹ እናሳስባለን።
    5. የምግብ እና ሕክምና አገልግሎት ማድረስ የማይቻልባቸው ቦታዎች ካሉም ሰላማዊ ዜጎች በተለይ ሴቶች፣ ሕፃናት እና አቅመ ደካሞች ከአካባቢው ተጓጉዘው ወደሌሎች አቅርቦት ሊደርስላቸው ወደሚችሉበት የትግራይ ክልል ከተሞች ወይም ወደ አቅራቢያ የሀገራቸው ክልሎች በማድረስ የህይወት አድን ሥራዎች እንዲሠሩ አበክረን እንጠይቃለን።
    6. በሰላማዊ ሰዎች እና ባልታጠቁ ዜጎች ላይ የደረሰው አካላዊ ጥቃት፣ ዘረፋ እና የሞራል ድቀት በገለልተኛ አካላት ተጣርቶ ፍትህ እንዲሰጥ አበክረን እንጠይቃለን።
    7. በቀጥታ ከሕግ ማስከበር እርምጃው ጋር ባልተያያዘ ሁኔታ በተለያዩ ተቋማት ላይ የደረሰውን ዝርፍያ እና የንብረት ውድመት በገለልተኛ ወገን ተጣርቶ ፍትህ እንዲሰጥ አበክረን እንጠይቃለን።
    8. በሀገርም ውስጥ በውጭም ያላችሁ ኢትዮጵያውያን ልዩነቶችን ወደ ጎን በመተው እየተጎዱ ያሉት ንጹኃን ዜጎቻችን ናቸውና ይህ ስቃይ እና ስጋት አብቅቶ ወደ ማቋቋም ለመሸጋገር ይቻል ዘንድ በሁሉም ዘርፍ የበኩላችሁን አስተዋፅኦ ታደርጉ ዘንድ እንጠይቃለን።
    9. የመንግሥት የሚመለከታችሁ አካላት፣ የሀይማኖት ተቋማት፣ ሲቪል ማኅበረሰብ፣ የሚድያ፣ የበጎ አድራጎት ማኅበራት ያላችሁን መዋቅር በመጠቀም ቅድምያ ህይወት ለማዳን እና ሰብዓዊነትን በማስቀደም በአንድነት እንድንቆም እንለምናችኋለን።

    ኦባንግ ሜቶ
    ዋና ዳይሬክተር፥ ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ
    ጥር 10 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ

    Anonymous
    Inactive

    መቆሚያ ያጣው በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል ዞን) ያሉ ሰዎች እልቂት!
    አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ (ኢሰመጉ)

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ) በቤንሻንጉል ጉሙዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ መተከል ዞን፣ በቡለን፣ ድባጤ፣ እና ዳንጉር ወረዳዎች ላይ በንጹኃን ሰዎች ላይ የሚፈጸመው ጥቃት አሁንም ተባብሶ መቀጠሉ እጅግ አሳስቦታል።

    ኢሰመጉ ታህሳስ 15 ቀን 2013 ዓ.ም ባወጣው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል ዞን)፣ ቡለን ወረዳ፣ በኩጂ ቀበሌ ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት ከ100 በላይ ንጹኃን ሰዎች መገደላቸውን፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መፈናቀላቸውን እና ለከፍተኛ ችግር የተጋለጡ መሆናቸውን አውግዞ፤ መንግሥት በአካባቢው በተደጋጋሚ ጊዜ የሚከሰተውን የንጹኃን ሰዎች ሰቆቃ ለማስቆም የሚያስችል ፈጣን፣ ተጨባጭ እና ዘላቂ መፍትሔ እንዲያበጅ ማሳሰቡ አይዘነጋም።

    ሆኖም፤ ከሰሞኑ ይኸው ችግር ዳግም ተከስቶ ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውን ተጎጂዎች እና የተጎጂ ቤተሰቦች ለኢሰመጉ ተናግራዋል። ታህሳስ 25 ቀን 2013 ዓ.ም ከቻግኒ ወደ ግልገል በለስ የሚሄድ መኪና ውስጥ የነበሩ ተጓዦች ማንዱራ ከተማ ላይ በታጣቂዎች እንዲወርዱ ተደርጎ አንድ ሰው መገደሉን እና ሁለት ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን ለማወቅ ተችሏል።

    ከጥር 2 እስከ ጥር 3 ቀን 2013 ዓ.ም. በቡለን እና ጉባ ወረዳዎች፣ ኦሜድላ እና አይነሸምስ በተባሉ ቀበሌዎች ላይ ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት ከ50 በላይ ሰዎች መገደላቸውን እና መኖሪያ ቤቶችም መቃጠላቸውን ኢሰመጉ መረጃዎች ደርሰውታል።

    በሌላ በኩል፤ ‹‹በድባጤ ወረዳ፣ ቆርቃ ቀበሌ፣ ዳሌቲ በተባለች መንደር ትላንት ጥር 4 ቀን 2013 ዓ.ም ከሌሊቱ 11፡30 ጀምሮ የኦነግ ሸኔ እና የቤኒን ታጣቂዎች በፈጸሙት ጥቃት ሰዎች መገደላቸውን፣ እስከአሁን ድረስ እኔ ራሴ ባለሁበት የ82 ሰዎች አስከሬን በፍለጋ መገኘቱን እና የቀብር ቦታዎች እየተዘጋጁ መሆኑን አይቻለሁ›› ሲሉ አንድ የዓይን እማኝ ለኢሰመጉ ተናግረዋል።

    ኢሰመጉ በትላንትናው (ጥር 4 ቀን) ጥቃት ሰለባ የሆኑ ሰዎች ቁጥር ከ100 ሊበለጥ እንደሚችል፣ በአብዛኛው ሴቶችና ህጻናት መሆናቸውን እና ከ24 በላይ የሚሆኑ ሰዎች ቆስለው በጋሊሳ ጤና ጣቢያ እና ቡለን ሆስፒታል ውስጥ ህክምና እየተደረገላቸው መሆኑን ከአካባቢው ካሰባሰባቸው መረጃዎች ለማወቅ ችሏል።

    በመሆኑም፥ መንግሥት ድርጊቱን የሚፈጽሙ አካላትን በአግባቡ አጣርቶ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወስድ፤ ለዚህ ተደጋጋሚ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ፈጣን፣ ተጨባጭ እና ዘላቂ መፍትሔ ማፈላለጉ ላይ በብርቱ እንዲሠራ ኢሰመጉ ያሳስባል። ኢሰመጉ ይህ ጉዳይ እልባት እንዲያገኝ ሁሉም ግለሰቦች፣ የማኅበረሰብ አንቂዎች፣ መገናኛ ብዙኃን፣ የሲቪል ማኅበራት፣ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ የሀይማኖት ተቋማት እና የሀገር ሽማግሌዎች በመንግሥት ላይ ውትወታ እንዲያደርጉ ጥሪውን ያቀርባል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ (ኢሰመጉ)
    ጥር 5 ቀን፥ 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    መቆሚያ ያጣው በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል (መተከል ዞን) ያሉ ሰዎች እልቂት

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) መግለጫ
    ኦሮሚያ ክልል ― የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ተከስቷል፤ አጥፊዎቹ ሕግ ፊት መቅረብ አለባቸው

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል ልዩ ልዩ አካባቢዎች በተከሰተ የፀጥታ መደፍረስ የተሳተፉ ሰዎችና ቡድኖች በሲቪል ሰዎች ላይ ያደረሷቸው ጥቃቶች በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ባህርያትን የሚያሟሉ መሆናቸውን በምርመራ ሪፖርቱ አመለከተ።

    ኢሰመኮ ከሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ በነበሩ ሦስት ተከታታይ ቀናት በኦሮሚያ ክልል የተከሰተውን የፀጥታ መደፍረስና የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት የባለሙያ ቡድኖቹን ወደ 40 የክልሉ አካባቢዎች የላከ ሲሆን፥ የምርመራውን ግኝቶች ታኅሣሥ 23 ቀን 2013 ዓ.ም. ይፋ አድርጓል።

    በ59 ገጽ ሪፖርቱ እንደተመለከተው፥ በዚህ መጠነ ሰፊ ጥቃት የተሳተፉት ብዙ ቁጥር ያላቸው እና ከቦታ ቦታ በቡድን ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሰዎች ሲሆኑ፤ በጩቤ፣ በድንጋይ፣ በእሳት፣ በኤሌክትሪክ ገመድ፣ በዱላ፣ በዶማ፣ በገጀራ እና በመጥረቢያ ተጠቅመው ሰዎችን ደብድበዋል፤ የአካል ጉዳት አድርሰዋል፤ ፍጹም ግፍና ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ በማሰቃየት እና በማረድ ጭምር ሰዎችን ገድለዋል። በጥቃቶቹ የ123 ሰዎች ሕይወት አልፏል፤ 500 ሰዎች የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፤ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተፈናቅለዋል።

    በአብዛኛው በቡድን የተደራጁ ሰዎች ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሱ፣ በብሔርና በሀይማኖታቸው ተለይተው የተመረጡ ሲቪል ሰዎችን፣ ቢያንስ በ40 የተለያዩ ቦታዎች በተስፋፋና ለሦስት ቀናት በቆየ ሁከት ማጥቃታቸው፣ በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል እንደሚያደርገው የኮሚሽኑ ግኝቶች ያመላክታሉ።

    ምንም እንኳን የፀጥታ ኃይሉ በየቦታው የገጠመውን መጠነ ሰፊ የፀጥታ መደፍረስ ችግር እና የፀጥታ አባሎቹንም የሕይወት መስዋዕትነት በሚጠይቅ ሁኔታ በመሰማራታቸው ኃላፊነታቸው እጅግ ፈታኝ የነበረ መሆኑን መገንዘብ ቢቻልም፤ በተወሰኑ ቦታዎች የኃይል አጠቃቀም ተመጣጣኝነት ከፍተኛ ጥያቄ የሚያስነሳ መሆኑን ሪፖርቱ አክሎ ገልጿል። በአንዳንድ አካባቢዎች የፀጥታ ኃይሉ በወሰደው ያልተመጣጠነ እርምጃ፥ ሰልፍ ውስጥ ያልነበሩ፥ በመንገድ ወይም በቤታቸው በር ላይ የተገደሉ፣ ለማሸማገል ጣልቃ የገቡ የአገር ሽማግሌዎችን እና የአዕምሮ ህመምተኛ ጭምር እንዲሞቱ ምክንያት ሆኗል።

    የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ ‘በኢትዮጵያ የሚታየው የግፍና የጭካኔ ወንጀሎች መደጋገም፣ የችግሩን ስር መሠረት ለመፍታት የሚያስችል የተሟላ ብሔራዊ የግፍና ጭካኔ ወንጀል መከላከያ ስትራቴጂ ነድፎ በአፋጣኝ በሥራ ላይ ማዋል እንደሚገባ የሚያሳይ መሆኑን’ ገልጸዋል።

    ሙሉ ሪፖርቱ “መንግስት ያለ አይመስልም ነበር፡ የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በተከሰተው የፀጥታ መደፍረስ ምክንያት የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ምርመራ ሪፖርት” በሚል ርዕስ እዚህ ጋር በመጫን ያገኙታል።

    የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በሰብዓዊነት ላይ የተፈጸመ ወንጀል ተከስቷል

    Anonymous
    Inactive

    የብሔር ልዩነታችን ላይ መሠረት ባደረገ ፖለቲካዊ የአስተዳደር ሥርዓት የዜጎችን መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቶች ማረጋገጥ አይቻልም
    ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ
    ጋዜጣዊ መግለጫ

    በሀገራችን ኢትዮጵያ በንጹሃን ዜጎች ላይ እየደረሰ ያለ አሰቃቂ ግድያ፣ የአካል መጉደል፣ ለዘመናት ከኖሩበት ስፍራ መፈናቀል፣ እንዲሁም ያፈሩትን ሀብትና ጥሪት በአንድ ጀንበር አጥተው ለተረጅነት መዳረግ በየጊዜው የሚያጋጥም የተለመደ አሳዛኝ ክስተት ሆኗል።

    ይህንን በዜጎች እየደረሰ ያለውን አሰቃቂ ግድያ፣ የአካል መጉደል፣ መፈናቀልና  ሀብትና ንብረታቸውን ማጣት እንዲቆም ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄን ጨምሮ የተለያዩ ተቋማትና ግለሰቦች ደግመው ደጋግመው ቢያወግዙም በተቃራኒው ችግሩ ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሰ ይገኛል።

    እኛ ኢትዮጵያውያን እምነት፤ ባህል፣ ሥነ ልቦና፣ ጋብቻ፣ ሥራ፣ ጉርብትና ሌሎችም መስተጋብሮች ላንለያይ አስተሳስረውን ጠንካራ የአብሮነት ባህል የነበረን ሕዝቦች ነን። ይህ የአብሮነት መስተጋብር በብዙ አጋጣሚዎች ፈተና ላይ የወደቀ ቢሆንም እስከዛሬዋ ቀን ድረስ አብረን እንድንጓዝ አድርጎናል።

    መሠረታዊ የዜጎችን ሰብዓዊ መብቶች ሳይሸራረፉ በማክበር የሁላችንም መኖሪያ የሆነችውን ሀገር አንድነት በማስጠበቅ፣ በመንግሥት አስተዳደር ሥርዓት ውስጥ ብዝኃነታችንን የሚያስተናግዱ የተለያዩ ፖሊሲዎችንና የሕግ ማእቀፎችን በማዘጋጀት ለጋራ ጥቅም በማዋል፣ እስከዛሬ የነበሩንን ጠንካራ ልምዶች ይበልጥ በማጠናከር ከድክመቶቻችን እና ስህተቶቻችን በመማር ብሎም በማሻሻል በአብሮነት ሁሉም አሸናፊና ተጠቃሚ የሚሆንበት ሥርዓት መዘርጋት ይቻላል ብለን እናምናለን።

    በእኛም ሀገር ይሁን በሌሎች ሀገራት ላይ ለሚከሰቱ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የተለያዩ ምክንያቶች ቢኖሩም በአሁኑ ጊዜ የቆየ አብሮ የመኖር እሴቶቻችንን በመፈታተን በሀገራችን እየተከሰቱ ለምንመለከታቸው ከፍተኛ የንጹሃን ህይወት መቀጠፍ፣ መፈናቀልና የንብረት ውድመት የመብት ጥሰቶች ዋነኛው መንስዔ የሀሰት ትርክት (false narrative) የወለደው ብሔር ተኮር የጥላቻ ፖለቲካ መሆኑ ጥርጥር የሌለው አሳዛኝ ሐቅ ነው።

    አሁንም መንግሥትም ሆነ ሌሎች የሚመለከታቸው የፖለቲካ ባለድርሻ አካላት በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት፣ ሀገራዊ ፍቅርና ቁርጠኝነት የዓለም አቀፍ ሕግጋትን መሠረት ባደረገ መልኩ፥ ያለንበትን 21ኛውን ክ/ዘመን በሚመጥን፣ በሰከነ ስሜት በቅንነት በመነጋገር፥ መሬት ላይ ያለውን ብዙኃኑን ምስኪን የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚመስል የፖለቲካ አስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት እስካልወሰኑ ድረስ በሁሉም የሀገራችን ወሰን ውስጥ ያሉ ዜጎቻችንን መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች በዘላቂነት ማስከበር ከቶውንም አይቻልም።

    ሰብዓዊ መብቶች ባልተከበሩበት፣ የሕግ የበላይነት ባልተረጋገጠበት፣ ሰላም ባልሰፈነበት ሁኔታ የሀገርን እድገትና ለውጥ እውን ለማድረግ ማሰብ እጅግ አዳጋች ነው።

    በአሁኑ ጊዜ እየተስተዋለ ያለው የጥላቻ፣ የመናናቅ፣ ልዩነትን መሠረት ያደረገ የብሔር ፖለቲካ፣ የጨቋኝ ተጨቋኝና የመጤ ሰፋሪ ትርክት ምንአልባትም ከእስካሁኑም ወደከፋ የግጭት አረንቋ ቢከተን ነው እንጂ የዜጎችን ሰው በመሆናቸው ብቻ እና በዜግነታቸው ማግኘት ያለባቸውን መብቶች ማስከበር ፈጽሞ አይቻልም። ችግሩን በፈጠርንበት አስተሳሰብ፣ ችግሩን በፈጠሩት የፓለቲካና የታሪክ ስሁት ትርክቶችን ሳናስተካከል መፍትሔ ማምጣትም ከባድ ነው።

    በሀገራችን በየትኛውም ዘመን እንደሕዝብ ተለይቶ የደላው ወይ ሌላውን የጨቆነ የለም። ይህንንም የተለያዩ የመንግሥት እና የፖለቲካ ድርጅቶች አመራሮች በተደጋጋሚ አስረግጠው የተናገሩት እውነታ ቢሆንም በተቃራኒው በተዛባ የታሪክ አረዳድ ሆን ብለውም ይሁን በስህተት የፖለቲካ አጀንዳ ባደረጉ አካላት ምክንያት የተነሳ ምንም የማያውቁ ንጹሀን ወገኖቻችን ደም እንደጎርፍ እየፈሰሰ ንብረታቸው እየወደመ ይገኛል። ይህም የሀገር ህልውናን አደጋ ላይ በመጣል ወደ ከፍተኛ ግጭት፣ ሞት፣ መፈናቀልና ስደት፣ ብሎም ለውጭ ኃይሎች ወረራና ጥቃት ሊያጋልጠን ይችላል።

    ከአባይ ግድብ ጋር በተገናኘም ሆነ በቀጠናችን ካለ የሽብርተኝነት እንቅስቃሴ ይህ የማይሆንበት ሁኔታ ይኖራል ብለን አንገምትም። ስለሆነም በቅርቡ በእርስ በርስ ግጭት ሕዝባቸውን ለስደትና ሞት ከዳረጉ ሀገራት በመማር ከምን ጊዜውም በላይ ሀገራዊ እና ሕዝባዊ አንድነታችንን ማጠናከር የሚገባን ጊዜ ላይ እንገኛለን።

    መንግሥት ሕግና ሥርዓት እያለ እንኳ በተገቢው መልኩ ማስቀረት ያልቻለውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት በጦርነትና በስደት መካከል ደግሞ ምን ያህል የከፋ ሊሆን እንደሚችልና ለውርደት እንደሚዳርገን ማስተዋል ያስፈልጋል።

    ይህ ፖለቲካው የወለደው የዜጎች ማንነትን መሠረት ያደረገ ጥቃት አይነቱን እየቀያየረ አንድ ጊዜ ሀይማኖትን ሌላም ጊዜ ብሔርን ወይንም አመለካከትንና አቋምን ሰበብ በማድረግ ይብዛም ይነስም ያልደረሰበትና ያልነካው የሕብረተሰብ ክፍል የለም ማለት ይቻላል። የችግሩ ምንጭም የቅርብ ሳይሆን አስርት አመታትን የቆየና አሁን እየባሰ የመጣ ነው።

    በሀገራችን ይህ ሁሉ ቢሆንም እንደ ሕዝብ የሚገድልና እንደሕዝብ የሚያፈናቅል አላየንም። ለዚህም ጥቃት በሚደርስባቸው አካባቢዎች ያሉ ነዋሪዎች ተጠቂዎችን ለማዳን፤ ለማሸሽ እና ለመደበቅ ያደረጉት ወገናዊና ሞራላዊ መልካም ሥራ ማስረጃ ነው።

    የፖለቲካው በቅንነት በመተማመን እና በአንድ ሀገራዊ ስሜት አለመመራት ሁሉንም የሀገሪቱ ዜጎች በየትኛውም ስፍራ በእኩል ዓይን በማየት ለሰብዓዊ እና የዜግነት መብቶቻቸውን በሚያከብር እና በሚያስከብር መልኩ ባለመመራቱ የተነሳ ችግሩን ከማቅለል ይልቅ በማወሳሰብ፡-

    • እጅግ ብዙ ንፁሐን ወገኖቻችን ሕፃናትን፡ ነፍሰጡሮችን፡ አቅመ ደካሞችን ጨምሮ ያለአግባብ በአሰቃቂ ሁኔታ ሕይወታቸው እንዲያልፍ ሆኗል፤
    • የሀገሪቱን የቀድሞ ኤታ ማዦር ሹም ጨምሮ የክልል ከፍተኛ አመራሮችን አጥተናል፤
    • ኢማሞችን እና ቀሳውስትን ጨምሮ የቤተ እምነት አገልጋዮችን ውድ ሕይወት አጥተናል፤
    • በዩንቨርሲቲዎቻችን ለትምህርት የሄዱ ብዙ ወጣቶችን ትርጉም በሌለው ምክንያት ተቀጥፈውብናል፤
    • ለትምህር የሄዱ ሴት ተማሪዎችና የጤና ረዳት ሰራተኞች ታግተው ለስቃይ ተዳርገዋል፤
    • በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች መሠረታዊ አቅርቦቶች ለምሳሌ እንደ ትራንስፖርት፤ መንገድ መዘጋት፤ ምግብ፤ ባንክ፤ ቴሌኮሚኒኬሽን አገልግሎት፣ መድሀኒት ወዘተ አቅርቦት በተደጋጋሚ ረዘም ላሉ ጊዜያት በመቆራረጥ ሰላማዊ ዜጎች ለከፍተኛ ችግር እንዲዳረጉ ሆኗል፤
    • ግምቱ ከፍተኛ የሆነ የሀገር እና የሕዝብ ንብረትና ሀብት እንዲወድም ሆኗል፤
    • ከዚህ ሁሉ በላይ በሰሜን እዝ የመከላከያ ሰራዊት ላይ የደረሰው ጥቃት ችግራችን የደረሰበትን የአሳሳቢነት ደረጃ ፍንትው አድርጎ የሚያሰይ ነው። ለዚህ ጥቃት ዋንኛ መንስኤ ከሀገርና ከሰው ይልቅ ብሔርን ያስቀደመ የማንነት ፖለቲካ ውጤት ሁኖ እናገኘዋለን።

    ይህ አሳዛኝ ሁኔታ ዳግም እንደማይፈጠርስ ምን ማስተማመኛ አለን? ከብሔር፤ ከሀይማኖትና ከፖለቲካ ነጻ የሆነውን የመከላከያ ሠራዊት ከውስጡ የወጡ የራሱ ወገኖች ያጠቁት የብሔር ፖለቲካው ውጤት ነው።

    ይህም በቶሎ በታላቅ መስዋዕትነት በቁጥጥር ባይውል ኖሮ የሀገራችንን ሉዓላዊነትን የሚገዳደርና ከዚህ የከፋ ቀውስ የሚያስከትል እንደነበረ መረዳት አያዳግትም።

    ችግሩ ላይ ብቻ ሳይሆን የችግሩ መንስዔ ላይ አተኩረን ለመሥራት እና ለማስተካከል ከዚህ በላይ ምን ምክንያትና ምቹ ጊዜ እየጠበቅን ነው? ምንስ እስኪፈጠር ነው ለውሳኔ የምንዘገየው?

    በየቀኑ ክቡር የሰው ነፍስ በአሰቃቂ ሁኔታ እየተቀጠፈ እያለ የሞተው ወይም ገዳይ ከኛ ነው ከነሱ ነው እያሉ የፖለቲካ ቁማር ከመጫወት ሁላችንንም እንደሀገር ከሰውነት ከፍታ ያወረደንን የጥላቻ ፖለቲካ በመመካከርና በማሻሻል የተሻለ ሥርዓትን ለትውልድ እናቆይ።

    ለፌደራልና ለክልል መንግሥታት አመራሮች፦

    ልዩነታችን ላይ መሠረት ባደረገ የፖለቲካ አስተዳደር ሥርዓት የዜጎችን መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች ማረጋገጥ አይቻልም።

    የፖለቲካ ባለድርሻ አካላት በከፍተኛ ታሪካዊ ሀገራዊ ስሜት በመሞላት በቁርጠኝነት የዓለም አቀፍ ሕግጋትን መሠረት ባደረገ፤ ያለንበትን 21ኛውን ክ/ዘመን በሚመጥን በሰከነ ስሜትና በቅንነት በመነጋገር፤ መሬት ላይ ያለውን በደምና በእምነት ተሳስሮ በሀዘንም በደስታ አብሮ የሚኖረውን ብዙኃኑን ምስኪን የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚመስል የፖለቲካ አስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት እስካልወሰናችሁ ድረስ በሁሉም የሀገራችን ወሰን ውስጥ ያሉ ዜጎቻችንን መሠረታዊ የሰብዓዊ መብቶች በዘላቂነት ማስከበር ከቶውንም አትችሉም።

    ሰብዓዊ መብቶች፤ ሰላምና ሕግ ባልተከበረበት ሁኔታ ደግሞ እድገትንና ለውጥን ማሰብ እጅግ አዳጋች ነው። ይህ አካሔድ ደግሞ ለናንተም አይጠቅምም። ከእስካሁኑ ተግዳሮት በጊዜ ትምህር መውሰድ መልካም ነው።

    ችግሩን ለመፍታት እንደሚታሰበውም ቀላል እንዳልሆነ ብንረዳም እንደሚፈራውም ከባድ እንዳልሆነ እናምናለን።

    ከባድ ቢሆንም ደግሞ የእውነትን የአንድነትን የእኩልነትን ሰብዓዊ መብቶች የሚከበሩበትን፤ ለትውልድ ጥላቻን ሳይሆን ፍቅርን የምናወርስበትን መንገድን መርጠን የሚጠይቀውን መስዋዕትነት መክፈል የተሻለ ነው። ተቋማትም እስኪገነቡም ቢሆን የሰው ልጆች ወጥተው መግባት ዜጎች በህይወት የመኖር መብት አላቸው።

    መንግሥት የዜጎቹን ደህንነት ከማረጋገጥ የቀደመ ምን አይነት አጀንዳ ሊኖረው ፈጽሞ አይገባም።

    በመሆኑም፦

    1. መንግሥት ችግሩን ከምንጩ ለአንዴና ለመጨረሻ ለማድረቅ ቁርጠኛ ውሳኔ በመወሰን ጊዜ ባለመስጠት ውይይትና ምክክር ከላይ እስከታች እንዲጀመር እስከዚያውም በከፍተኛ ርብርብ ሕግ የማስከበር ሥራውን እንዲያስፈፅም እንጠይቃለን፤
    2. እስከዛሬም ድረስ በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች የተፈጠሩትን ዘግናኝ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ገለልተኛ ወገን እንዲያጣራ በማድረግ አጥፊዎችና ተባባሪዎች እንደ ተሳትፎዋቸው መጠን ከፍተኛውን ቅጣት እንዲያገኙ ተጎጂዎችም ተመጣጣኝ ካሳ እንዲያገኙ እንዲደረግ እንጠይቃለን፤
    3. እስከዛሬም ድረስ በተፈጠሩ ችግሮች ምክንያት ከሚኖሩበት አካባቢ የተፈናቀሉ ዜጎች ተገቢው ድጋፍ ተደርጎላቸው ወደነበሩበት እንዲመለሱና መደበኛ ኑሯቸውን እንዲጀምሩ በመንግሥት ያለተገደበ ድጋፍ እንዲደረግላቸው እንጠይቃለን።

    ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፦

    እስከዛሬ ድረስ በፖለቲካው ምክንያት በተፈጠሩ ችግሮች ብዙ ዋጋ እየከፈለ እና መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቱን እየተገፈፈ ያለው ንጹህ የሆነው እና አብሮ በሰላም እየኖረ ያለው በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች የሚኖረው ሕዝባችን እንደሆነ ይታወቃል። ያለንን አብሮነት አሁንም በማጠናከር እንደሕዝብም እንደግለሰብም አብረን በመቆም ለልጆቻችን የተሻለች ሀገር እናቆይ።

    ከጥላቻና ከብሔር ወይም ከማናቸውም የማንነት ልዩነት በመውጣት ለፖለቲካ ቁማር የማንመች እንሁን። ካለበለዚያ ከእስካሁኑ በባሰ የመጨረሻ ተጎጂዎች እኛው ነን።

    ምንም እንኳን የተለያየ አመለካከት ቢኖረንም በሰው ልጆች ሰብዓዊ መብቶች እና በሀገር አንድነት ጉዳይ የማንደራደር እንሁን። ሁላችንንም ስደተኞች ረሀብተኞችና ጠፊዎች ያደርገናል እንጂ ሀገር ለአንድ ብሔር፤ ለአንድ ክልል፤ለአንድ ቡድን ወይ ለአንድ ፓርቲ ብቻ ተለይታ አትፈርስም። ለተወሰነ ባለስልጣን ወይ አክቲቪስት ፈርሳ ለሌሎቻችን አትቆምም።

    ከሰሜን እስከደቡብ ከምሥራቅ እስከምእራብ አብረን ስንቆም ችግሮቻችን ከኛ በታች ይሆናሉ። ጥላቻና መጋደል በሕግም ፊት ወንጀል በሞራልም ነውር በእምነቶቻችንም ኃጥያት ነውና በሰከነ መንፈስ ሰብዓዊነትን በማስቀደም ሀገራችንን በማስከበር በብዝኃነት መኖር እንደለመድነው ቃልኪዳናችንን እናድስ።

    ውስጣዊ አንድነታችን በተዳከመ ቁጥር የውጭ ጠላቶቻችን ይደፍሩናል ያጠቁናል የዚያን ጊዜ ብሔር መርጠው አይወጉንም፤ ሁላችንንም ጨለማ ይወርሰናል። ምርጫው በእጃችን ነውና ሳይዘገይብን በይቅርታ መንፈስ እንነሳ።

    ሰው መሆናችን ትልቁ አንድነታችን መሆኑን እናስተውል።የነበሩንን እና ያሉንን መልካም አብሮ የመኖር እሴቶች በማጠናከር ችግሮቻችንን በእርጋታ እየፈታን እንጓዝ። የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች በማንም ይፈጠሩ፤ ማንም ተጎጂ ይሁን ሰው ነውና ወገን ነውና በአንድነት በማውገዝ በአንድነት ፍትህን በመጠየቅ ለሚለያዩን የማንመች እንሁን። ለልጆቻችን ፍቅርን ተስፋን መከባበርንና የሥራ ባህልንና ማውረስ አለብን።

    እናቶች፣ አባቶች፣ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ የሀይማኖት አባቶች፣ ምሁራን፣ የጥበብ ሰዎች፣ የሚድያ አካላት በአጠቃላይ ሁላችሁ ኢትዮጵያውያን በሀገር ውስጥም ይሁን በውጭ ያላችሁ በሙሉ ይህን ከባድ ጊዜ ተያይዘን እንድናልፈው የበኩላችንን አስተዋጽዖ እንድናደርግና የዜጎች ሰብዓዊ መብቶች ሳይሸራረፉ የሚከበሩበት፡ በሕግና በሥርዓት ብቻ ፍትህ የሚጠየቅበትና የሚገኝበት ማንኛውም አካል ከዜጎችና ከሀገር ደህንነት በታች የሚሆንበት መዋቅራዊ የሥርዓት መሻሻል እንዲመጣ በሰላማዊ መንገድ አብረን ጥሪያችንን እንድናሰማ ስንል በታላቅ አክብሮት እንማፀናችኋለን።

    ቅድሚያ ለሰብዓዊነት!
    ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ
    ታህሳስ 22 / 2013
    ​አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    የዜጎችን መሠረታዊ ሰብዓዊ መብቶች ማረጋገጥ

    Anonymous
    Inactive

    በመተከል፣ በወለጋ፣ በሰገን አካባቢ እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት አጥብቀን እናወግዛለን!
    ከባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ እና የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ጥምረት (ባልደራስ-መኢአድ)  የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    በዓለም ላይ ማንነትን መሠረት አድርጎ የሚፈፀም ግፍ እየጠፋ ነው። ይሁን እንጂ በሀገራችን ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ዜጎች በማንነታቸው ምክንያት እየተገደሉ ነው፤ ግልፅ የሆነ የዘር ፍጅት ወንጀል እየተፈፀመ ነው። በታህሳስ 13 ቀን 2013 ዓ.ም ከ207 በላይ የአማራ ተወላጆች በመተከል አካባቢ ተገድለዋል። ባልደራስ-መኢአድ የተሰማውን መሪር ሐዘን ይገልፃል። ከዚህ በፊት በቤንሻንጉል ጉምዝ አካባቢ በተደጋጋሚ አንድን ዘር መሠረት ያደረገ ተመሳሳይ ግድያ መፈፀሙን ዓለም ያውቃል። የአማራ ተወላጆች በወለጋ፣ በጉራፈርዳ፣ በቤንሻንጉልና በሌሎች አካባቢዎች በማንነታቸው ብቻ ለዘር ፍጅት እየተዳረጉ ነው።

    በሀገራችን ኢትዮጵያ ሌላው የዘር ፍጅት የሚካሄድበት አካባቢ ደግሞ በሰገን ሕዝብ አካባቢ ነው። በደቡብ ኢትዮጵያ የጉማይዴ ነዋሪዎችና የኩስሜ ብሔረሰብ አባላት አካባቢ ወገኖቻችንን እያለቁ ነው። የኩስሜ ብሔረሰብ በቁጥሩ አነስተኛ ሲሆን 40‚000 ሺህ የሚሆኑ ዜጎች ያሉት ነው። የኩስሜ ዜጎች በአነሷቸው የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች፣ የንፁህ ውሃ አገልግሎት ጥያቄዎች ለእልቂት ተዳርገዋል።የኩስሜ ብሔረሰብ አስተዳደር ካሉት 9 አስተዳደር ቀጣናዎች መካከል በ7ቱ ቀጣናዎች ከፍተኛ የሰብዓዊና ቁሳዊ ውድመት የደረሰ ሲሆን በተለይ ቀጣና 1 ሙሉ በሙሉ ወድሞ የኩስሜ ብሔር አባላት ተሰደዋል። በተመሳሳይ በአሁን ሰዓት በምስራቅ ወለጋ ጌዳ ወረዳ፣ በምዕራብ ወለጋ ሳምቦ ወረዳ፣ በሆሮ-ጉድሩ ዞን እየተፈፀመ ያለው ታሪክ ይቅር የማይለው የግፍ ጭፍጨፋ ሊቆም አልቻም። ይህ ሁሉ ሲሆንና ማንነትን መሠረት ያደረገ ጥቃት ሲፈፀም ፌደራል መንግሥትም ሆነ የክልሉ መንግሥት ትኩረት አልሰጡትም። ዛሬ በኩስሜ ብሔር አካባቢ የትምህርት ተቋማት፣ ጤና ጥበቃ ተቋማት፣ ግብርና ወዘተ የመሳሰሉት ተቋማት ፈርሰዋል፤ ሕዝቡ በስደትና በስጋት ቁም ስቅሉን እያየ ነው። በዚሁ በሰገን ሕዝቦች አካባቢ የጉማይዴ ሕዝብ የማያባራ የዘር ፍጅት ወንጀል እየተፈፀመበት ነው። ዛሬ ጉማይዴ ውስጥ በሰላም ውሎ በሰላም መግባት የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል። በ100 ሺህ የሚቆጠሩ የጉማይዴ ነዋሪዎች ተሰደዋል። ይህ ሕዝብ በማንነቱ ጥቃት ሲደርስበት የሚከላከልለት ከማጣቱም በላይ በተሰደደባቸው አካባቢዎች የዕለት ደራሽ እርዳታ ማግኘትም አልቻለም። መንግሥት ለዚህ ሕዝብ ሰላምና ፀጥታ መከታ መሆን አለመቻሉም ብቻ ሳይሆን ሕዝቡን የጎዳው በጥቃቱ የመንግሥት ባለሥልጣናት ቀጥተኛ እጅ መኖሩ ነው። ይህ ሕዝብ የሚደርስበት ግፍ የማያባራው ጥቃቱ በመንግሥት የተደራጀ ኃይል እየተፈፀመ በመሆኑ ነው።

    በሀገራችን ውስጥ እየተፈፀመ ያለውን ማንነት ተኮር የሆነ የዘር ፍጅት ሕዝባችን ለእልቂት ከመዳረጉም በላይ በየጊዜው የሚያልቁ ወገኖቻችን አስከሬናቸው እንኳን በወጉ አያርፍም። በታህሳስ 13 ቀን 2013 ዓ.ም በመተከል የተጨፈጨፉት ከ207 በላይ ወገኖቻችንን መንግሥት በግሪደር አንድ ጉድጓድ ውስጥ እንዲቀበሩ አድርጓል። በዓለም አቀፍ የዘር ፍጅት ጥናት ውስጥ የዘር ፍጅት አንዱ መገለጫ በጅምላ መግደልና በጅምላ መቅበር ነው። በጅምላ መቅበር አንዱ የዘር ፍጅት የመደምደሚያው ወንጀል ነው። መንግሥት ይህንን ወንጀል በገሀድ ፈፅሞታል። ይህ ጉዳይ የሀገራችንን ባህል፣ ሀይማኖትና የቀብር ሥርዓት የጣሰ እና ያላገጠ ሲሆን ሥነ-ልቦናቸውንም ጎድቷል። በመሆኑም መንግሥት ሊጠየቅበት ይገባል። በአጠቃላይ በሀገራችን ውስጥ የዘር ፍጅት ወንጀል በየጊዜው እየተፈመ ሲሆን ፌደራል መንግሥትም ሆነ የክልል መንግሥት ይህንን ወንጀል ለመመከት አልቻሉም፤ ተጠያቂም ናቸው። በዓለም አቀፍ የዘር ፍጅት ወንጀል ክስ ወቅት በየትም ሀገር የዘር ፍጅት ሲፈፀም ተጠያቂው ራሱ መንግሥት ነው።

    በመሆኑም ለኢትዮጵያ ሕዝብና ለዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ የሚከተሉትን አስቸኳይ ጥሪዎች እናቀርባለን፡-

    1ኛ. የዘር ፍጅት ምልክቶች የሚታዩባቸው አካባቢዎች በፍጥነት ሠራዊታችን በቂ ኃይል እንዲያሰፍር፤
    2ኛ. መላው የሀገራችን ሕዝብ የዘር ፍጅትን በሰላማዊ መንገድ ብቻ ነቅቶና ተግቶ እንዲቃወም፤
    3ኛ. ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች ይህንን ክፉ ወንጀል በመቃወም በአንድነት እንዲቆም፤
    4ኛ. በሀገር ውስጥና በውጪ ያላችሁ የኢትዮጵያ ምሁራን በኢትዮጵያ ውስጥ እየተፈፀመ ያለውን የዘር ፍጅት ወንጀል ወደ ሕግ እንድታቀርቡ፤
    5ኛ. በኢትዮጵያ ውስጥ የምትገኙ የሀገር ውስጥና የውጪ ሀገር ሰብዓዊ መብት ተቋማት በሙሉ ይህንን ወንጀል እንድትቃወሙ እና ወንጀል የፈፀሙት ኃይሎች ወደ ሕግ እንዲቀርቡ እንድትታገሉ፤
    6ኛ. የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትና ወዳጅ ሀገራት በሙሉ የዘር ፍጅት ወንጀልን እንድታወግዙና በመንግሥት ላይ ተገቢውን የዲፕሎማሲ ተፅዕኖ በማሳደር ወንጀሉ እንዲቆም እና ወንጀለኞች ለፍትህ እንዲቀርቡ እንድታደርጉ፤
    7ኛ. መላው የሀገራችን ሕዝብ በዘር፣ በሀይማኖት፣ በብሔር ሳንከፋፈል ከመቼውም ጊዜ በላይ በአንድነት ፀንተን እንድንቆምና የዘር ፍጅት እንድንከላከልና የተባበረችውን ኢትዮጵያችንን በጋራ እንድንገነባ በትህትና እንጠይቃለን።

    የተባበረችውን ኢትዮጵያን እንገነባለን! “አንዲት ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር”!!

    ታኅሣሥ 20 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ
    ባልደራስ-መኢአድ

    ባልደራስ-መኢአድ

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እና ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ የዘላቂ አጋርነት ስምምነት ተፈራረሙ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በባለአክሲዮን ብዛት ከቀዳሚ ባንኮች ተርታ የሚመደበው ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ እና በደጋፊ ቁጥር ቀዳሚ የሆነው የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ የዘላቂ አጋርነት ስምምነት ተፈራረሙ።

    ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ እና የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ በሁሉም ዘርፍ በጋራ ለመሥራት የሚያስችላቸውን የጋራ ስምምነት ተፈራርመው ወደሥራ መግባታቸውን ይፋ ያደረጉት ታኅሣሥ 17 ቀን 2013 ዓ.ም በሃያት ሪጀንሲ አዲስ አበባ ሆቴል በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ነው። ስምምነቱ ይፋ በተደረገበት ወቅት እንደተገለጸው፥ ባንኩም ሆነ ክለቡ የሚጋሩት ስም የሁሉም ኢትዮጲያዊ ከመሆኑ ባሻገር ሕዝባዊ መሠረት ያላቸው መሆናቸው አንድ የሚያደርጋቸው የጋራ መለያቸው ነው ተብሏል።

    ስምምነቱ የተፈረመው በቡና ኢንተርናሽናል ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሙሉጌታ አለማየሁ እና በኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ ሥራ አስኪያጅ አቶ ገዛኸኝ ወልዴ ሲሆን፥ በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የባንኩና የክለቡ የሥራ አመራር አባላት ተገኝተዋል። በስምምነቱ መሠረትም ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ ለኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ የአምስት ሚሊዮን ብር የአንድ ዓመት ስፖንሰርሺፕ ክፍያ የሚከፍል ሲሆን ስምምንቱም በየዓመቱ የሚታደስ ይሆናል።

    በስምምነቱ መሠረት የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ የባንኩን አርማ በተጫዋቾች ቲሸርትና ላይ በማሳየት ባንኩን ያስተዋውቃል። በተጨማሪም በሜዳውም ይሁን ያለሜዳው ጨዋታ በሚኖረው ወቅት የባንኩ ቢልቦርድ ማስታወቂያ በጨዋታው ሜዳ አካባቢ እንዲቀመጥ ያደርጋል። ክለቡ በተቻለው መጠን የባንኩን ብራንድ እና አገልግሎቶች እንዲያስተዋውቅም በስምምነቱ ተካትቷል።

    ስምምነቱ ከዚህ በተጨማሪ የስፖርት ክለቡ የባንክ ሂሳቡን በባንኩ እንዲከፍት ከማድረግ ጀምሮ የክለቡ አባላትና ደጋፊዎች የባንኩ ደንበኛ እንዲሆኑ ማድረግን የመሳሰሉ የባንክ አገልግሎቶችን ከባንኩ እንዲያገኙ የሚያደርግ ነው ተብሏል።

    እንደስምምነቱ ቡና ባንክ በበኩሉ የስፖርት ክለቡ ደጋፊዎች ማኅበር ወርሃዊ የአባልነት መዋጮአቸውን በዘመናዊ የቴክኖሎጂ አሠራር በመታገዝ በባንኩ በኩል እንዲከፍሉ የሚያስችላቸው አሠራር ይዘረጋል፤ በተለያየ የሀገሪቱ ክፍል ለሚገኙ የክለቡ አባላትም የባንክ አገልግሎት እገዛ እንደሚያደርግ ተገልጿል።

    ቡና ባንክ እና የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እንደስማቸው አንድ መሆን የጋራ እድገት ለማስመዝገብ የሚያስችሉ ሌሎች በርካታ ሥራዎችንም በጥምረት ለመሥራት መስማማታቸውን ነው በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ያበሰሩት።

    ከተመሠረተ 11 ዓመታት የሆነውና ከ13 ሺህ በላይ ባለአክሲዮኖች ያሉት ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ የእግር ኳስ ስፖርቱን በመደገፍና በዓለም አደባባይ አርማውን በማስተዋወቅ ከቀዳሚዎቹ ተርታ የተሰለፈ ባንክ ሆኗል። ባንኩ በ2012 የሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት ከ582 ሚሊዮን ብር በላይ ማትረፉንም በዚያው ሳምንት አሳውቋል። የባንኩ ሀብት በሒሳብ ዓመቱ መጨረሻ ላይ የ4.4 ቢሊዮን ብር ዕድገት ያሳየ ሲሆን፣ ጠቅላላ ሀብቱም ወደ 18.9 ቢሊዮን ብር አድጓል፡፡ ከባንኩ ጠቅላላ ሀብት ውስጥ የተጣራ ብድር 60.9 በመቶውን በመሸፈን ከፍተኛውን ድርሻ ይዟል ሲል ባንኩ የ2012 የሒሳብ ዓመት የሥራ አፈጻጸሙን ይፋ ባደረገበት ጠቅላላ ጉባዔ ላይ አሳውቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ

    ኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ እና ቡና ኢንተርናሽናል ባንክ

    Anonymous
    Inactive

    ኦህዴድ/ ብልጽግና አዲስ አበባን የኦሮሞ ንብረት ለማድረግ የጀመረውን ዘመቻ ያቁም!
    ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ

    ኦህዴድ/ ብልጽግና ቤተ-መንግሥት ከገባ ጀምሮ የመላ ኢትዮጵያውያን ብሎም የአፍሪካ መዲና የሆነችውን አዲስ አበባን በኦሮማዊነት መንፈስ ለመቆጣጠር እንቅስቃሴዎችን እያደረገ ይገኛል።

    ከሰሞኑ ከተማዋን የኦሮሞ ብቻ መዲና ለማድረግ እና ኦሮማዊ ሥነ-ልቦናን ለማላበስ ኦሕዴድ/ ብልጽግና የሕንፃዎች ግንባታ ዘመቻን ጀምሯል። የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በ1.8 ቢሊዮን ብር ወጭ የኦሮሚያ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሕንፃን፣ በ1.5 ቢሊዮን ብር ወጭ የኦሮሚያ ብዙኃን መገናኛ ድርጅት ሕንፃን፣ በአንድ ቢሊዮን ብር የኦሮሞ ታጋዮች ፋውንዴሽን ሕንፃን እንዲሁም በሰባት መቶ ሚሊዮን ብር ወጭ የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ሕንፃን በአዲስ አበባ ለመገንባት ሥራዎች ጀምሯል። ይህ እንቅስቃሴ ህወሓት ሲያደርግ እንደ ነበርው የሕዝብ ሀብት እየተዘረፈ ለነገድ የፖለቲካ ድርጅቶች እና ለሚመሯቸው የፖለቲካ ኤሊቶች ጥቅም ማስገኛ እንደሚሆን ሳይታለም የተፈታ እውነታ ነው። በሕገ-መንግሥቱ የኦሮሚያ ክልል ዋና ከተማ አዲስ አበባ እንደሆነች ባልተፈቀደበት ሁኔታ ይህ የተወሰደው እርምጃ አዲስ አበባን በኦሮሞ ሥነ-ልቦና ለመሥራት በሚል ሽፋን የኦሮሞ የነገድ ፓለቲካ ኤሊቶች ጥቅም ማጋበሻ እንዲሆኑ የታለሙ መሆናቸውን ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ያምናል። ይህም በ16 እና በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመናት ተቋርጦ የነበረውን የገዳ ሥርዓት ወረራ ለማስቀጠል እየተደረገ ያለ እንቅስቃሴም አካል ነው።

    አቶ ሽመልስ አብዲሳ እንዳሉት ይህ ወረራ አዲስ አበባን ሙሉ በሙሉ ለመዋጥ ወይም ለማጥፋት ያለመ ነው። ‹በረራ› በመባል ትታወቅ የነበረችው ጥንታዊቷ አዲስ አበባ ዳግማዊ ምኒልክ እንደ ገና የዛሬዋን አዲስ አበባ እስከቆረቆሩበት ጊዜ ድረስ ፈርሳ የቆየችው በገዳ ወረራ እንደሆነ ታሪክ ያስረዳል። በ16ኛው እና በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመናት በተካሄደው የገዳ ሥርዓት ወረራ ከ28 በላይ ነባር የኢትዮጵያ ነገዶች መጥፋታቸው በታሪክ የተመዘገበ ነው።

    በመሆኑም በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ከመላ ኢትዮጵያ የተሰበሰቡ ነዋሪዎች ከሚገብሩት ግብር ለክልሎች ፈሰስ ከሚደረገው ድጎማ የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት ለነገድ የፖለቲካ ማራመጃነት እና ለግል ጥቅም ማካበቻ በማን አለብኝነት የሚያባክኑት የሀገር ሀብት ተጠያቂ የሚሆኑበት ሥርዓት እንዲፈጠር መላው የከተማዋ ነዋሪ በሰላማዊ ትግል አድሏዊ ከሆነ የኪራይ ሰብሳቢ አካሄድ እንቅስቃሴያቸው እንዲታቀቡ ባልደራስ በአፅንኦት ያሳስባል።

    ታኅሣሥ 14 ቀን 2013 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ
    ድል ለዲሞክራሲ!
    ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ

    ኦህዴድ ብልጽግና አዲስ አበባን የኦሮሞ ንብረት ለማድረግ የጀመረውን ዘመቻ ያቁም!

Viewing 15 results - 61 through 75 (of 495 total)