Search Results for 'የጤና ሚኒስቴር'

Home Forums Search Search Results for 'የጤና ሚኒስቴር'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 58 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    በዲላ ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ሆስፒታል በመጀመሪያ ዙር መልሶ ግንባታ የተጠናቀቁ ህንፃዎች ተመረቁ
    የዲላ ዩኒቨርሲቲ ማስተማሪያ ጠቅላላ ሆስፒታል ደረጃን ለማሻሻል በተሠሩ ሁለተናዊ የለውጥ ሥራዎች በአጭር ጊዜ አበረታች ውጤት እያስመዘገበ መሆኑ ተገለፀ

    ዲላ (ዲላ ዩኒቨርሲቲ እና የጤና ሚኒስቴር) – የዲላ ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ሆስፒታል ደረጃን ለማሻሻል የሚደረግ የመልሶ ግንባታ አካል የሆኑና በመጀመሪያው ዙር ታድሰው የተጠናቀቁ ህንፃዎች የምረቃ በሥነ ሥርዓት ታኅሣሥ 27 ቀን፥ 2015 ዓ.ምተካሂዷል።

    በዲላ ዩኒቨርሲቲ የሕክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ማስተማሪያ ጠቅላላ ሆስፒታል የእድሳት ግንባታ ሥራ በከፊል ርክክብ ሥነ ሥርዓት ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናት በተገኙበት ታህሳስ 27/2015 ዓ.ም ተካሂዷል።

    ከስድስት ወራት በፊት በአገልግሎት አሰጣጥ እንዲሁም በመልካም አስተዳደር እጦት ከፍተኛ የሕብረተሰብ እሮሮ የተነሳበት የዲላ ዩኒቨርስቲ ማስተማሪያ ጠቅላላ ሆስፒታል ከፌደራል እና ክልል ከፍተኛ አመራሮች በተሰጠው አቅጣጫ መሠረት ሁሉን አቀፍ የሥርዓት ማሻሻያ የሪፎረም ሥራዎችና ምቹና ደህንነቱን የጠበቀ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል የሥራ ቦታ ለመፍጠር የግንባታ እድሳት ሥራ በተቀላጠፈ መልኩ እየተከናወነ እንደሆነ በመልስ ምልከታ ማየት ተችሏል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት እንደገለጹት የዩኒቨርስቲ ማኔጅመንት ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት ከሐምሌ ወር መጨረሻ 2014 ዓ.ም ጀምሮ 112 ሚሊዮን ብር በሆነ ወጪ የመማር ማስተማር እና የሕክምና አገልግሎት ሳይቋረጥ በሦስት ዙር እድሳቱ እንዲካሄድ ወደ ሥራ መገባቱን ገልጸዋል።

    በሥነ ሥርዓቱ የዲላ ዩኒቨርሲቲ የሕክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ጠቅላላ ሆስፒታል ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ምፅዋ ሩፎ እንደገለፁት፥ አዲሱ የሆስፒታል አመራር ወደ ሥራ ሲገባ የአሠራር ሥርዓት ክፍተት ስለነበር ክፍተቶችን ለመቅረፍ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ሰፋፊ ሥራዎች እንደተሠሩ እድሳቱንም በቅርብ ክትትል እየተሠራ መሆኑን አብራርተዋል።

    ክብርት ወ/ሮ ጫልቱ ሳኒ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር ሚንስትር እና የዲላ ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ እንደተናገሩት፥ የሆስፒታሉን አገልግሎት ለማጠናከር በየደረጃው ያለው አመራር ቁርጠኝነት እንደሚፈልግ ገልፀው፤ ለዚህም አስፈላጊ ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ ገልጸዋል።

    በጤና ሚኒስቴር ሚንስትር ዴኤታ ዶ/ር አየለ ተሾመ የተጀመረው ሪፎርም፣ የ”SBFR” ትግበራ እና የህንፃዎች እድሳት የሆስፒታሉን ደረጃ ከፍ ከማድረግ ባሻገር የጤና አገልግሎት አሰጣጥ መሻሻል እና የጤና ባለሙያው ላይ ከፍተኛ መነቃቃት እንዲሁም የተገልጋይ እርካታን መጨመር መቻሉን ገልፀው ለዚህ ውጤት መምጣት በቁርጠኝነት ለሠሩት የዪኒቨርስቲው፣ የጌዲዮ ዞን፣ የዲላ ከተማና የሆስፒታሉ አመራር አካላት እንዲሁም መላው የሆስፒታል ማኅበረሰብ በተለይም በሥራ አንጋፋ (senior) ሐኪሞችና ነርሶች ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

    በምርቃት ሥነ ሥርዓቱ ላይ አባገዳዎች፣ የጤና ሚኒስቴር፣ የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት ጤና ቢሮ፣ የጌዲዮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ፣ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች፣ የሆስፒታሉ የበላይ አመራሮች፣ የሕክምና ባለሙያዎች፣ የአከባቢው ማኅበረሰብ ተወካዮች፣ ሠራተኞች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት ታድመዋል።

    ምንጮች፦ ዲላ ዩኒቨርሲቲ እና የጤና ሚኒስቴር

    ዲላ ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ሆስፒታል

    Semonegna
    Keymaster

    በሀገር አቀፍ ደረጃ የተቀናጀ የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ዘመቻ ተጀመረ 

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ከታኅሳስ 13 ቀን እስከ ታኅሳስ 22 ቀን፥ 2015 ዓ.ም በሀገር አቀፍ ደረጀ የሚካሄደው የተቀናጀ የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ዘመቻ የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት፣ የኮቪድ-med19 መከላከያ ክትባት፣ የአጣዳፊ የምግብ እጥረት ልየታ፣ የቫይታሚን ኤ ጠብታ እደላ፣ የሆድ ጥገኛ ትላትል መድኃኒት እደላ፣ የሕፃናት የዞረ እግር ልየታ እንዲሁም በወሊድ ምክንያት የሚከሰት ፊስቱላ ልየታ በቅንጅት የሚሠራበት ዘመቻ ነው።

    በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ሰርጢ ጤና ጣቢያ የማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ላይ የተገኙት የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ እንደገለጹት፥ ለእናቶች እና ለሕፃናት ትኩረት ያደረገው የጤና ፖሊሲ ውስጥ አንዱ እና ባለፉት አራት አስርት ዓመታት በትግበራ ላይ የቆየው የክትባት ፕሮግራም መሆኑን ገልፀው፤ እንደሀገር ከ14 በላይ የሚሆኑ የክትባት ዓይነቶችን በመስጠት ዜጎችን ከህመምና ከሞት መታደግ እንደተቻለ ገልጸዋል።

    በሀገራችን በተወሰኑ አካባቢዎች ተከስተው በነበሩ ሰው ሠራሽና ተፈጥራዊ ችግሮች ምክንያት በሥርዓተ ምግብ እጥረት እና በኩፍኝ በሽታ የሚያዙ ሕፃናት ከፍ ብሎ መታየቱን የገለፁት ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ፥ በዚህ ዘመቻ ዕድሜያቸው ከዘጠኝ ወር እስከ አምስት ዓመት የሆኑ ሕፃናትን የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት፣ የአጣፊ የምግብ እጥረት፣ የዞረ እግር ልየታ እንደሚከናወን እና በወሊድ ምክንያት የሚከሰት ፊስቱላ ልየታም ይካሄዳል።

    ሕፃናት በመደበኛ ክትባት መርሃ-ግብር የሚሰጠውን የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት ካልወሰዱ በቀላሉ በኩፍኝ በሽታ የመያዝና ለከፋ የጤና ችግር የመጋለጥ ዕድላቸው ከፍተኛ  ነው ያሉት የእናቶች እና ሕፃናት ጤና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር መሠረት ዘላለም፥ በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን  ባለፉት 3 ወራት ብቻ የኩፍኝ በሽታ ወረርሽኝ በ6 ክልሎች የታየ ሲሆን፤ በወረርሽኙም ከተያዙ ውስጥ 47 በመቶ  የሚሆኑት ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች የሆኑ ሕፃናት ሲሆኑ፥ ከእነዚህም መካከል 46 በመቶ የሚሆኑት ምንም ዓይነት የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት ያልወሰዱ ናቸው ብለዋል። ለዘመቻው እንቅስቃሴ መሳካት አጋርና ለጋስ አካላት ላደረጉት የተቀናጀ አስተዋጽኦ አመስግነዋል።

    በአዲስ አበባ ከተማ ከ5 ዓመት በታች ለሆናቸው ለ520 ሺህ ሕፃናት ክትባቱ እንደሚሰጥም እና በስድስት የመንግሥት ሆስፒታሎች በ101 የመንግሥት ጤና ጣቢያዎች ከሰኞ አስከ አርብ በሥራ ሰዓት እንደሚሰጥ የገለጹት ደግሞ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ዮሐንስ ጫላ ናቸው።

    ሀገር አቀፍ የተቀናጀ  የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ዘመቻ  የማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ የጤና ሚኒስቴር እና የአዲስ አበባ ከፍተኛ አመራሮች፣ የሀይማኖት አባቶችና የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ተካሂዷል።

    ዘመቻው ለአስር ቀን የሚቆይ ሲሆን ከ15 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ሕፃናት የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ተደራሽ የሚሆን ሲሆን፤ የኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት መርሃ-ግብርም በተያያዘ የሚከናወን ይሆናል። ለዘመቻው ስኬታማነት በየተዋረድ ያሉ የጤናው ዘርፍ ባለሙያዎችና አመራሮች፣ አጋር ድርጅቶችና የየመገናኛ ብዙኃን አካላት ትብብር እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል።

    ምንጭ፦ የጤና ሚኒስቴር

    የኩፍኝ መከላከያ ክትባት

    Semonegna
    Keymaster

    ሳንቴ የሕክምና ኮሌጅ ለ5ኛ ጊዜ ያሰለጠናቸውን የጤና ባለሙያዎች አስመረቀ

    አዲስ አበባ (የጤና ሚኒስቴር) – ሳንቴ የሕክምና ኮሌጅ በአጠቃላይ ሕክምና ዶክትሬት ዲግሪ፣ በጥርስ ሕክምና ዶክትሬት ዲግሪ፣ በሕብረተሰብ ጤና አጠባበቅ በBSc እና MPH ዲግሪ፣ በሕብረተሰብ ጤና አጠባበቅ፣ ኒውትሪሽን በMPH ዲግሪ እና በሥነ-ተዋልዶ ጤና በMPH ዲግሪ ያሰለጠናቸውን የጤና ባለሙያዎች አስመረቀ።

    በምርቃት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት ተግንኝተዉ መልዕክታቸውን ያስተላለፉት የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር አየለ ተሾመ እንዳሉት፥ ተመራቂዎች በኮሌጁ ቆይታችሁ ፈታኙን የሕክምናና የጤና ሳይንስ ትምህርት እንዲሁም ሌሎች ተግዳሮቶችን አልፉችሁ ነውና የእናንተን የአካልና የመንፈስ ጥንካሬ ያረጋገጣችሁበት ስለሆነ ላደረጋችሁት ጥረት፣ ውጤታማነት ምስጋናና አድናቆት እንደሚገባቸው ተናግረዋል።

    ዶ/ር አየለ አያይዘውም የተመራቂ ቤተሰቦችንና የኮሌጁ መምህራን እንዲሁም አመራር/አስተዳደር አባላት ተማሪዎች በስኬት መንገድ እንዲጓዙና ውጤታማ እንዲሆኑ ለከፈላችሁት ዋጋ የሚያስመሰግናቸውና የሚያኮራ ተግባር መሆኑን ገልፀው፤ በዛሬው ጊዜ ልጆችን በኃላፊነት አንፆ ለፍሬ ማብቃትና ሀገር ተረካቢ ትውልድ እንዲሆኑ የወላጅ፣ መምህራን እንዲሁም የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ጥረት እንደሚያስፈልግ አንስተው፣ ለትውልድ ቅብብሎሹ ላደረጉት መስዋዕትነት ሀገርም እንደምታመሰግናቸው ተናግረው እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።

    የጤና ሚኒስቴር ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በዘርፉ የሚስተዋለውን የጤና ባለሙያዎች እጥረት ለመቅረፍ ከትምህርት ሚኒስቴር፣ ከከፍተንኛ ትምህርት ተቋማት፣ እንዲሁም ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ዘርፈ ብዙ ሥራዎች እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፥ የጤናና የሕክምና ትምህርት የሚሰጡ በርካታ የመንግሥትና የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን ሚኒስትር ዴኤታው አክለዋል።

    የኮሌጁ ተጠባባቂ ዲን ዶ/ር አህመዲን ኑርሁሴን በበኩላቸው፥ የኮሌጁ ዓላማ ከኮሌጁ ተመርቀው የሚወጡ ባለሙያዎች ሰውን ወዳድ እና አክባሪ፣ አዋቂ፣ በተለያዩ ክህሎቶች የታነፁ፣ ብቁ ለህሙማንና ለማኅበረሰቡ ተቆርቋሪና በጎ አመለካከት ያላቸው ጠቅላላ ሀኪሞች፣ የጥርስ ሀኪሞች፣ ጤና መኮንኖች፣ የሜዲካል ላብራቶሪ ሳይንስ ባለሙያዎች፣ የሕብረተሰብ ጤና አጠባበቅ (ፐብሊክ ሔልዝ)፣ ሥነ ምግብ (ኒውትሪሽን) እና የሥነ-ተዋልዶ ጤና ባለሙያዎችን ማፍራት እንደሆነ ገልፀው፥ ተመራቂዎች ለሀገርና ለወገን ጠቃሚ ትውልድ እንዲሆኑ ትኩረት ተደርጎ እየተሠራ እንደሆነ ጠቁመው ለ5ኛው ዙር ተመራቂዎችና ቤተሰቦቻቸው እንኳን ደስ አላችሁ ብለው መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

    ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ የኮሌጁ የቦርድ አባል በተጨማሪ ባስተላለፉት መልዕክት፥ ተመራቂዎች የተማራችሁት የትምህርት ዓይነት ስለ ሰው ነው፤ ሰው ደግሞ ክቡር የሆነ ህይወትን የተላበሰ ልዩ የሆነ የእርሱ ፍጡር እንደሆነ አንስተው፤ ተመራቂዎች በተማራችሁበት ትምህርት ማኅበረሰቡን ለመርዳትና ሀገራችንን በሕክምናው ዘርፍ የላቀ ደረጃ ለማድረስ ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ የበኩላችሁን አስተዋፅኦ እንድትወጡ በማለት ለተመራቂዎችና ቤተሰቦቻቸው መልካም የምርቃ ጊዜ እንዲሆንላቸው ተመኝተዋል።

    ምንጭ፦ የጤና ሚኒስቴር

    Semonegna
    Keymaster

    ከ350 በሚበልጡ የግል የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ላይ እርምጃ መውሰዱን
    የትምህርትና ስልጠና ባለስልጣን አስታወቀ

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – የትምህርትና ስልጠና ባለስልጣን በ2014 በጀት ዓመት የሥነ-ሥርዓት ጥሰት በፈጸሙ ከ350 በላይ የግል የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ላይ እርምጃ መውሰዱን አስታወቀ። ባለስልጣኑ በበጀት ዓመቱ ከአረጋገጣቸው 10 ሺህ የትምህርት ማስረጃዎች 505 ቱ ሀሰተኛ ናቸው ብሏል።

    የባለስልጣኑ ዋና ዳሬክተር ዶ/ር አንዷለም አድማሴ ከኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ በ2014 በጀት ዓመት ከየትኛውም በጀት ዓመት የበለጠ የትምህርት ጥራትን ሊጎዱ የሚችሉ ነገሮችን የማጽዳት ሥራ ተከናውኗል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተቋሙን የሥራ እንቅስቃሴ ገምግሞ አቅጣጫ ካስቀመጠ ጊዜ ጀምሮ ከ350 በላይ በሚሆኑ የግል የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ላይ እርምጃ ወስዷል።

    መንግሥት የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ እየወሰዳቸው ካሉ ተጨባጭ እርምጃዎች ውስጥ ሕገ-ወጥ የትምህርት ተቋማትን መቆጣጠር አንዱ ተግባር ነው ያሉት ዶክተር አንዷለም፤ አሁን ላይ የትምህርት ጥራት በኢትዮጵያ ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ ካደረጉት ምክንያቶች አንዱ ኃላፊነት የማይሰማቸውና ትርፍን ብቻ አላማ ያደረጉ ሕገ ወጥ የግል የትምህርት ተቋማት መስፋፋት መሆናቸውን ገልጸዋል።

    ተቋምና ፕሮግራም መዝጋት አማራጭ አይደለም ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ነገር ግን የእውቅና ፈቃድ ሳይሰጣቸው በትውልድ ህይወት የሚነግዱ አካላት ላይ ጥብቅ እርምጃ ይወሰዳል ነው ያሉት።

    እንደ ዶ/ር አንዷለም ገለጻ፥ በርካታ ዜጎች እውቅና በሌለው የግል የከፍተኛ የትምህርት ተቋም ገንዘባቸውን ከፍለው ከተማሩ በኋላ ባለስልጣኑ ማረጋገጫ ሲሠራላቸው ሀሰተኛ የትምህርት ማስረጃ ሲሆንባቸው ለተመሰቃቀለ ህይወት እየተዳረጉ ነው። በተቋማት ላይ ድንገተኛ ፍተሻ በማድረግ በ355 የግል የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ላይ ከፕሮግራም መዝጋት እስከ ተቋሙን ሙሉ በሙሉ እስከ መዝጋት የደረሰ የማስተካከያ እርምጃ ተወስዷል። ለዚህም መገናኛ ብዙኃን የነበራቸው ሚና ከፍተኛ ነው።

    የትምህርት ማስረጃ ማረጋገጥ ሥራ በበጀት ዓመቱ በትኩረት ከተሠራባቸው መካከል መሆኑን ያስታወሱት ዶክተር አንዷለም፤ በዘርፉ የጤና ሚኒስቴርና ጉምሩክ ኮሚሽን ለሚቀጥሯቸው ሠራተኞች ቅጥር ከመፈጸማቸው በፊት የትምህርት ማስረጃቸው በባለስልጣኑ እንዲረጋገጥ የሚያደርጉበት አግባብ ለሕገ-ወጥ የትምህርት ማስረጃ ቁጥጥር ጉልህ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። ዕድገትና ቅጥር ሲያከናውኑም በሙሉ ሳያስፈትሹ እንደማያከናውኑ ተናግረዋል።

    ዋና ዳይሬክተሩ የትምህርት ማስረጃ ሲረጋገጥ በቀጣሪ መሥሪያ ቤቶች ተገደው የሚመጡ አካላትን የትምህርት ማስረጃ ማረጋገጥና ከውጭ ሀገር የተገኘ የትምህርት ማስረጃን አቻ ግምት በመስጠት በሁለት መልኩ የሚረጋገጥ ነው ብለዋል። የማረጋገጥ ሥራ የሚጀምረው ከሀገር አቀፍ ፈተናዎች እንደሆነና በወቅቱ ከነበረው የመቁረጫ ነጥብ በመጀመር እያንዳንዱ የትምህርት ማስረጃ ተፈትሾ እስከ ዲፕሎማና ዲግሪ እንደሚረጋገጥም ጠቁመዋል።

    በ2014 በጀት ዓመት የጤና ሚኒስቴርና የጉምሩክ ኮሚሽንን ሳያካትት ተገደው ከመጡ ከ10 ሺ በላይ የትምህርት ማስረጃዎችን ማረጋገጥ ተችሏል ያሉት ዶክተር አንዷለም፤ ከተረጋገጡት የትምህርት ማስረጃዎች 505 የሚሆኑት ትክክለኛ ያልሆኑ የትምህርት ማስረጃዎች እንደሆኑም ተናግረዋል።

    ፈቃድ ሳያገኙ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ክፉኛ እየጎዱ ያሉ ትውልድን እያቀጨጩ የሚገኙ ሕገ-ወጥ የግል ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ለመቆጣጠር በሚደረገው ሂደት ሕብረተሰቡ ጥቆማ በመስጠት ድጋፍ እንዲያደርግም ዶ/ር አንዷለም ጥሪ አቅርበዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

    የትምህርትና ስልጠና ባለስልጣን

    Anonymous
    Inactive

    የጅማ እና ዲላ ዩኒቨርሲቲዎች ከ7,390 በላይ ተማሪዎችን አስመረቁ

    ጅማ ዩኒቨርሲቲ በመደበኛ፣ በማታውና በተከታታይ የትምህርት መርሀግብሮች ያሰለጠናቸውን 3,926 ተማሪዎች በደማቅ ሥነ-ሥርዓት ነሐሴ 1 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. አስመርቋል።

    በምርቃ ሥነ-ሥርዓቱ የተገኙት የዕለቱ የክብር እንግዳ የኢፌዲሪ የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል ባስተላለፉት መልዕክት፥ ከሀይማኖትና ብሔር ልዩነት ባለፈ ተዋድደንና ተፈቃቅረን እንደኖርነው ሁሉ፣ አሁንም በአንድነት እጅ ለእጅ ተያይዘን የሀገራችንን ብልጽግና እናረጋግጣለን ብለዋል።

    የኢፌዲሪ የጤና ሚኒስትር ዴኤታና የጅማ ዩኒቨርሲቲ ቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ በበኩላቸው፥ በቀጣይ ዩኒቨርሲቲውን የላቀ የምርምር ማዕከል ለማድረግ የሥራ አመራር ቦርዱ ተግቶ ይሠራል ብለዋል።

    የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት ዶ/ር ጀማል አባፊጣ ባደረጉት ንግግር፥ ከከፍተኛ ትምህርት ተልዕኮዎች መካከል የመጀመሪያው ጥራት ያለው ትምህርት በመስጠት በእውቀት፣ በክህሎት እና በሥነ-ምግባር የዳበረና ሀገር ተረካቢ ዜጋ ማፍራት ነው። ግቡም ተመራቂው ባካበተው የቴክኖሎጂ አቅም ራሱን አብቅቶ ሀገርንና ወገንን መቀየር ሲሆን፥ ጅማ ዩኒቨርሲቲም ይህንኑ ዓላማ እውን ለማድረግ ተግቶ በመሥራት ላይ ይገኛል ብለዋል። ለዚህም ምስክሩ በምርምርና ተቋማዊ አመራር የላቀ ውጤት ማስመዝገቡ ነው በማለት አክልዋል።

    በዕለቱ ከተመረቁት ተማሪዎች መካከል በቅድመ ምረቃ 2,260 ወንድ ሲሆኑ፣ 1234 ሴቶች ተመራቂዎች ናቸው።

    በድኅረ ምረቃ መርሀ ግብር ከተመረቁት 402 ተማሪዎች ውስጥ 318 ወንዶች ሲሆኑ፣ 85 ሴቶች ናቸው፡፡ ከድኅረ ምረቃ መርሀ ግበሩ 18 የሦስተኛ ዲግሪ (ፒ ኤችዲ) ምሩቃን ሲሆኑ፣ በጅማ ዩኒቨርሲቲ ታሪክ ከፍተኛው የሦስተኛ ዲግሪ መርሀግብር ተማሪዎች የተመረቁበት ነው። የሦስተኛ ዲግሪ ተማራቂዎቹ ከሒሳብ፣ ከጤና ግንኙነት (health communication)፣ እና ከኢንፎርሜሽን ሳይንስ ትምህርት ክፍሎች ናቸው።

    በተጨማሪም ጅማ ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያ ዲግሪ መርሀግብር በሶፍትዌር ኢንጅነሪንግና በቪዥዋል አርት (ሥነ-ስዕል) የሰለጠኑ ተማሪዎችን ለመጀመሪያ ግዜ አስመርቋል።

    ከተማሪዎች ምርቃት ጋር በተያያዘ ዜና፥፥ ዲላ ዩኒቨርሲቲ በመደበኛና በሁለተኛ ዲግር እንዲሁም በተከታታይ መርሀግብር ያሰለጠናቸውን ከ3,450 በላይ ተማሪዎችን እሁድ ነሐሴ 2 ቀን፥ 2013 ዓ.ም. አስመርቋል።

    ዩኒቨርሲቲው ያስመረቃቸው ተማሪዎች 2,101 ወንድና 983 ሴት በድምሩ 3,084 ተማሪዎችን በመጀመሪያ ዲግሪ፤ 317 ወንድና 72 ሴት በድምሩ 384 ተማሪዎችን በሁለተኛ ዲግሪ፤ በአጠቃላይ 3,468 ተማሪዎችን በዕለቱ አስመርቋል።

    የዘንድሮው የዲላ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ምርቃት ለ23ተኛ ጊዜ የተከናወነ ሲሆን፥ ከተመሠረተበት ከ1989 ዓ.ም. ጀምሮ እስካሁን ድረስ ከ71,475 በላይ ተማሪዎችን አሰልጥኖ ለሀገር ኢኮኖሚ የበኩሉን አስተዋጽኦ አበርክቷል። በአሁኑ ወቃትም ከ26ሺህ በላይ የሚሆኑ ተማሪዎችን በመደበኛ እና በተከታታይ የትምህርት መርሀግብሮች እያሰለጠነ  ይገኛል።

    ዩኒቨርሲቲው በዋናው ግቢው ያከናወነው የተማሪዎች ምርቃት ሥነ-ሥርዓት በፋና ቴሌቪዥን በቀጥታ እንደተተላለፈ የዩኒቨርሲቲው የሕዝብ ግንኙነትና ሚዲያ ዘርፍ ዘግቧል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የጅማ እና ዲላ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎችን አስመረቁ

    Anonymous
    Inactive

    ይድረስ ለትግራይ ወገኖቼ!
    በአቶ ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ

    የትግራይ ሕዝብ ከባለጌ ልጆቹ በላይ ሀገሩን የሚመርጥበት ጊዜ ደርሷል። በተለይም የትግራይ እናቶች እና አባቶች በራሳቸው ልጆች እኩይ ስምሪት ቀደምቶቻቸው ለአንድነቷ ሰማዕትነትን የተቀበሉላት ኢትዮጵያችን ክብሯ እንዲጎድፍ በዝምታ መተባበራቸውን ይበቃል ለማለት ትክክለኛው ወቅት አሁን መሆኑን ልብ ሊሉ ይገባል።

    የዘመን ተጋሪዬ ለሆናችሁ የትግራይ ወጣቶችም “ጅብም ብሆን የወንዝህ ጅብ ስለሆንሁ፤ ልበላህ መብት አለኝ” የሚሉ ሀገር አጥፊዎችን በመተው ከሀገራችን ኢትዮጵያ እና ወንድሞቻችሁ ጎን እንድትቆሙ ወንድማዊ ጥሪዬን አቀርብላችኋለሁ።

    የሀይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች ጨዋው የትግራይ ሕዝብ በሀገር አፍራሽ፣ ዘር አጥፊና ዘራፊ ብኩኖች በኩል ዘላቂ መብቶቹ፣ ጥቅሞቹና ፍላጎቶቹ እንደማይከበሩለት አውቃችሁ፤ ሁለንተናው ከኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ጋር የተሸመነውን የትግራይ ሕዝብ ታሪክ፣ ክብርና የወደፊት በጎ ተስፋ በሚመጥን ስምሪት እንድትገኙ ዝቅ ብዬ እለምናችኋለሁ።

    ታላቁ የትግራይ ሕዝብ በሌባ አይወከልም! ከዘፍጥረት ጀምሮ እስካሁን ድረስም እናት ኢትዮጵያም ሆነች ወንድሙ የአማራ ሕዝብ ለትግራይ ሕዝብ የክብሩ ምንጭ የደኅንነቱ ደጀኖች እንጂ የስጋቱ ምንጮቹኘች ሆነው አያውቁም፤ አይሆኑምም። እንዴት ሀገር ገንቢው ትግራይ በሀገር አፍራሽ ይወከላል?

    ትግራይ የምታሸንፈው ኢትዮጵያ ስታሸንፍ ብቻ ነው፤ ትግራይ አንገት ደፍታ ኢትዮጵያ አትቃናም። በትግራይ ለቅሶ ፈገግታው የሚደምቅ አንድም ኢትዮጵያዊ አይኖርምም። ሌባና ዘራፊ፤ ባንዳና ሀገር አጥፊ ግን ከየትም ይሁን የትም የጋራ ጠላታችን ነውና በጋራ ልንደመስሰው ይገባናል። በባንዳ ሞት ደረት የሚደቃና ፊት የሚነጭ ሊኖር አይገባም።

    እናም ለተከበራችሁ የትግራይ አባቶቼና እናቶቼ፣ ወንድሞቼና እህቶቼ፥ ስለደማቁ የትናንት ትናንታችን ብቻ ሳይሆን ስለብሩህ ነጋችንም ብላችሁ ለኢትዮጵያችን ኅልውና እንዲሁም ለሕዝባችን ፍትሕ፣ እኩልነትና ነፃነት መረጋገጥ በአንድነት እንድንቆም ስል ጥሪዬን ደግሜ ላቀርብላችሁ እወዳለሁ።

    ሁሉም ችግሮች ከጋራ አቅማችን በታች ናቸው። ስንደማመጥ፣ ስንከባበርና ስንተማመን ከባዱ ቀላል ይሆናል። ኢትዮጵያ ስታሸንፍ ሁላችንም እናሸንፋለን!

    አቶ ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ

    አቶ ክርስቲያን ታደለ ጸጋዬ በፌደራል የጤና ሚኒስቴር፥ የማኅበረሰብ ጤና ኤክስፐርት (public health expert) ሲሆኑ፤ በፖለቲካ እንቅስቃሴአቸው ደግሞ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ናቸው። እርሳቸውን በፌስቡክ ገጻቸው ወይንም በትዊተር ሃንድላቸው ሊያገኟቸው ይችላሉ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    አቶ ክርስቲያን ታደለ

    Semonegna
    Keymaster

    በኢትዮጵያ ስምንት ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል ተብለው ተለዩ

    ጎንደር (ኢዜአ) – በኢትዮጵያ ስምንት የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል (Center of Excellence) በመባል መለየታቸውን የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የጎንደር ዩኒቨርሲቲ በተመረጡ ትምህርት ቤቶች በትምህርት ጥራት ዙሪያ ያካሄደውን የምርምር ግኝቶች ላይ መስከረም 29 ቀን 2013 ዓም ከባለድርሻዎች ጋር ተወያይቷል።

    የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከፍተኛ አማካሪ ዶ/ር ወርቁ ነጋሽ በወቅቱ እንደገለጹት፥ በሀገሪቱ የሚገኙ 46 ዩኒቨርሲቲዎች በምርምር፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ እንዲሁም በአጠቃላይ ትምህርት በሚል በሦስት ደረጃዎች ተለይተዋል።

    ባለፉት ዓመታት በርካታ ችግር ፈቺ የምርምር ውጤቶችን ሲያበረክቱ የቆዩና ወደፊትም አስተዋጽዖ ይኖራቸዋል የተባሉ ስምንት ዩኒቨርሲቲዎች በምርምር ዘርፍ የልህቀት ማዕከል እንዲሆኑ መለየታቸውን ተናግረዋል።

    ጎንደርአዲስ አበባባህር ዳርመቀሌጅማሀዋሳአርባ ምንጭ እና ሐረማያ ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል እንዲሆኑ ተለይተዋል” ብለዋል ዶ/ር ወርቁ።

    ለአንድ ሀገር ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ችግር ፈቺ ምርምር ቁልፍ ሚና እንዳለው የገለጹት ዶ/ር ወርቁ፥ “ያደጉ ሀገሮች የእድገት ምስጢርም ከዚህ የመነጨ ነው” ብለዋል። የምርምር (Research) ዩኒቨርሲቲዎቹ በዓለምአቀፍ ደረጃ ከሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር አቻ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ አቅማቸውን ለመገንባት በትኩረት እንደሚሠራ አመላክተዋል።

    ሌሎች 15 የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ በሳይንስና ቴክኖሎጂ (Science and Technology) ዘርፍ ትምህርትና ስልጠና እንዲሰጡ መለየታቸውን ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ በቂ እውቀትና ክህሎት ያዳበረ ዜጋ ማፍራት እንዲችሉ ተከታታይ ድጋፍ እንደሚደረግላቸው አመላክተዋል።

    ቀሪዎቹ 23 ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ አጠቃላይ ትምህርትና ስልጠና እንዲሰጡ የተለዩ መሆኑን ዶ/ር ወርቁ አስታውቀዋል።

    የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር መርሻ ጫኔ ዩኒቨርሲቲው በርካታ ችግር ፈቺ ጥናትና ምርምር በማካሄድ ለማህበረሰቡ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረጉን ተናግረዋል።

    ላለፉት ሶስት አመታት ጎንደር ከተማን ጨምሮ በሰሜን፣ በማእከላዊና በምዕራብ ጎንደር ዞኖች በተመረጡ 1,343 የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ላይ በትምህርት ጥራት ዙሪያ ጥናትና ምርምር መካሄዱን ገልጸዋል። በምርምር ውጤቶቹ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይትና ምክክር እየተካሄደ መሆኑን አስታውቀዋል።

    “በዩኒቨርሲቲው የሥነ-ትምህርት ኮሌጅ መምህራን የተዘጋጀው የምርምር ውጤት ለፖሊሲ አውጪዎች ጠቃሚ ግብዓት ሆኖ የሚያገለግል ነው” ያሉት ደግሞ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አሥራት አጸደወይን ናቸው።

    ባለፈው ዓመት ዩኒቨርሲቲው ከ200 በላይ የምርምር ሥራዎችን ማካሄዱን ዶ/ር አሥራት አስታውሰዋል፤ ዘንድሮም በተለያዩ ዘርፎች ምርምር ለማካሄድ የሚያስችል ቅድመ ዝግጅት እያካሄደ እንደሚገኝ ፕሬዝዳንቱ ማሳወቃቸውን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዘግቧል።

    ለአንድ ቀን በተካሄደው ውይይት የዩኒቨርሲቲው መምህራንና የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም ከጎንደር ከተማ አስተዳደር የተውጣጡ መምህራንና የትምህርት አመራሮች ተሳትፈዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    የምርምር ልህቀት ማዕከል

    Anonymous
    Inactive

    ሰላማችንን በማስጠበቅ እና ቀጣዩ ሀገራዊ ምርጫ ላይ በንቃት በመሳተፍ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መሠረት እንጣል!
    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ መግለጫ

    ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ሊካሄድ የግዜ ሰሌዳ ወጥቶለት ሁሉም ባለድርሻ አካላት እንቅስቃሴ ከጀመሩ በኋላ በዓለም አቀፍ ደረጃ በተከሰተው የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምክንያት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በመታወጁ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያወጣውን የምርጫ ጊዜ ሰሌዳ እንዲሰርዝ መገደዱ ይታወሳል። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በታወጀበት እና የምርጫ ሰሌዳው በተሰረዘበት ወቅት ወረርሽኙ በሌሎች የዓለማችን ሀገራት የጤና ሥርዓት ላይ ያስከተለውን ከፍተኛ ጫና እና በሰው ሕይወት ላይ ሲያደርስ የነበረውን ጉዳት በተጨባጭ በማየት የተለያዩ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች ላይ ገደብ መደረጉ እና በዚህ ምክንያት ምርጫው መራዘሙ ተገቢ ነበር ብለን አምነናል።

    ምርጫው አለመካሄዱን ተከትሎ የመንግሥት ቀጣይነትን ለማረጋገጥ በተለያዩ ወገኖች የተለያዩ አማራጮች መቅረባቸው የሚታወስ ነው። የተለያዩ ፖለቲካ ፖርቲዎችም ከሕገ-መንግሥት ውጪ ያሉ አማራጮችን አቅርበው ነበር። ኢዜማ የመንግሥት ቀጣይነትን በሕጋዊ ማዕቀፍ ውስጥ መፍታት እንደሚቻል ጠቅሶ፥ አሁን በሥራ ላይ ያለው ሕገ-መንግሥት ከሚሰጣቸው የመፍትሄ አማራጮች ውስጥ ደግሞ የመንግሥትን የሥልጣን ጊዜ እና ምርጫ የሚደረግበትን ጊዜ የሚደነግገውን የሕገ-መንግሥት አንቀጽ ከአቅም በላይ እና በድንገተኛ ምክንያት ምርጫ ማድረግ የማይቻልበት ሁኔታ ሲፈጠር የመንግሥትን ሥልጣን ከአንድ ዓመት ላልበለጠ ጊዜ ማራዘም እንዲያስችል አድርጎ ማሻሻል የተሻለ አማራጭ እንደሆነ ማቅረቡ ይታወሳል። ማሻሻያው ሥልጣን ላይ የሚቆየው መንግሥት የሥልጣን ጊዜ ገደብ ያስቀመጠ እና ውሳኔ የሚሰጥባቸው ጉዳዮች በቀጣይ ምርጫ አሸንፎ ሥልጣን የሚይዘው መንግሥት ላይ ግዴታ የማይጥሉ መሆናቸውን ባረጋገጠ መልኩ መሆን እንዳለበትም ምክረ-ሀሳብ አቅርበን ነበር።

    የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ክፍተቱን በሕገ-መንግሥት ትርጉም ለመሙላት ወስኖ የሕገ-መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ ባቀረበው የውሳኔ ሀሳብ እና በፌደሬሽን ምክር ቤት ውሳኔ ምርጫውን የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ስጋት አለመሆኑ በጤና ሚኒስቴር እና የኅብረተሰብ ጤና ተቋም እስኪረጋገጥ ድረስ አራዝሞ የፌደራል እና የክልል መንግሥታት እና ምክር ቤቶችን የሥራ ጊዜ ያለገደብ እንዲቀጥል መወሰኑ ይታወሳል።

    ይህን ውሳኔ ተከትሎ ኢዜማ የጊዜ እና ውሳኔ የሚያሳልፍባቸው ጉዳዮች ላይ ወሰን ሳይደረግ ሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት የሥራ ዘመን መራዘሙ ላይ ያለውን ተቃውሞ ገልፆ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለሕገ-መንግሥት አጣሪ ጉባዔ በገለጸው መሠረት አስፈላጊው ጥንቃቄ ተደርጎ ምርጫው መደረግ በሚችልበት ቅርብ ጊዜ እንዲደረግ ጠይቋል።

    በቅርቡ የጤና ሚኒስትር አስፈላጊው ጥንቃቄ እየተደረገ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎችን ማድረግ እንደሚቻል ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባሳወቀው መሠረት ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ በያዝነው ዓመት እንዲካሄድ ውሳኔ ተላልፏል።

    ይህ በእንዲህ እያለ፥ “ሥልጣን ለማራዘም የተሄደበት መንገድ ሕገ-መንግሥታዊ አይደለም፤ በዚህም ምክንያት ከመስከረም 25 ቀን 2013 ዓ.ም በኋላ መንግሥት የለም፤ ሕዝብ እና የመንግሥት መዋቅር ለፌደራል እና የክልል መንግሥታት ሊታዘዙ አይገባም» በሚል ቅስቀሳ ሲደረግ መቆየቱን እና አሁንም እየተደረገ እንደሚገኝ ለማስተዋል ችለናል

    ይህ ቅስቀሳ የሀገራችንን ሰላም እና መረጋጋት ከማወክ እና የዜጎችን ሕይወት አደጋ ላይ ከመጣል በዘለለ ፋይዳ እንደሌለው የኢትዮጵያ ሕዝብ በደንብ እንደሚገነዘብ እናውቃለን። ይህንን ቅስቀሳ እያደረጉ ያሉ አካላትም ከዚህ ተግባራቸው ተቆጥበው የጋራ ሀገራችን ሰላም እና የዜጎች ደህንነት ተጠብቆ በሰላማዊ መንገድ ችግሮቻችንን መፍታት ወደምንችልበት የውይይት መድረክ ከመምጣት ውጪ በሁከት እና በጉልበት ወደሥልጣን ለመውጣት የሚደረግ ማንኛውም እንቅስቃሴ ለራሳቸውም ቢሆን የማይጠቅም አደገኛ መንገድ መሆኑን ሊረዱ ይገባል። መንግሥትም እነዚህን ቅስቀሳዎች በንቃት እየተከታተለ አደጋ ከመድረሱ በፊት የመከላከል እና አደጋ ለማድረስ የሚንቀሳቀሱ አካላት ላይ ሕጋዊ እርምጃ በመውሰድ የሀገር ሰላምን እና የዜጎችን ደህንነት የማስከበር ኃላፊነቱን እንዲወጣ እናሳስባለን።

    ሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ዘንድሮ እንዲካሄድ የተወሰነውን ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ፣ ነፃ እና ፍትሃዊ ማድረግን ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንደሚገባው እና ምርጫው እስከሚካሄድ እና የሕዝብ ድምፅ ያገኘው ተለይቶ እስከሚታወቅ ድረስ የዜጎችን ደህንነት ማስጠበቅ፣ የሀገር ሉዓላዊነትን ማስከበር እና ምርጫውን ነፃ እና ፍትሃዊ ከማድረግ ጋር በቀጥታ ግንኙነት የሌላቸውን በተለይም በምርጫው የሚወዳደሩ ፓርቲዎች የተለያየ ፖሊሲ አቅርበው የሕዝብን ቅቡልነት ለማግኘት በሚወዳደሩባቸው ጉዳዮች ላይ ውሳኔ ከማሳለፍ እና ከመተግበር እንዲቆጠብ እናሳስባለን።

    እኛንም ጨምሮ በሀገራችን የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሙሉ በነፃነት ተንቀሳቅሰው ሃሳባቸውን መግለፅ እንዲችሉ ከዚህ ቀደም በተስማማንበት የፖለቲካ ፓርቲዎች የቃል ኪዳን ሰነድ መሠረት የምናደርጋቸው እንቅስቃሴዎች ሰላማዊ፣ ሕጋዊ እና የሌሎችን መብት ያከበረ መሆኑን እያረጋገጥን ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ፣ ነፃ እና ፍትሃዊ እንዲሆን የሚጠበቅብንን ሁሉ እንድናደርግ እንጠይቃለን። በሀገራችን የምትንቀሳቀሱ የሲቪክ ተቋማትም የፖለቲካ ፓርቲዎች የተስማሙበትን የቃልኪዳን ሰነድ እንዲያከብሩ ግፊት እንድታደርጉ እና በጋራ ሊሠሯቸው እና ሊስማሙባቸው በሚገቡ ተጨማሪ ጉዳዮች ላይ ውይይት ማድረግ የሚችሉበት መድረክ እንድታዘጋጁ የአደራ ጥሪያችንን እያስተላለፍን፥ በመድረኮቹ ላይ በንቃት ለመሳተፍ ያለንን ፍላጎት ከወዲሁ ለመግለጽ እንወዳለን።

    መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ በሀገራችን ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ለምንገነባው ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መደላድል የምንጥልበት ወሳኝ ምዕራፍ መሆኑን በመገንዘብ የምርጫውን ሂደት ከአሁን ጀምሮ በንቃት እንዲከታተል እና ምርጫው ሰላማዊ፣ ነፃ እና ፍትሃዊ መሆኑን ለማረጋገጥ የሚጠበቅባችሁን ሁሉ እንድታደርጉ የአደራ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
    መስከረም 26 ቀን 2013 ዓ.ም

    ሀገራዊ ምርጫ

    Semonegna
    Keymaster

    ትምህርት እንደሚጀመር ከሁለቱ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች የተሰጡ ማብራሪያዎች

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ትምህርት ሚኒስቴር በሦስት ሳምንት ጊዜ ውስጥ ትምህርት እንደሚጀመር ሲያሳውቅ፤ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ደግሞ ዩኒቨርሲቲዎች እና የቴክኒክና ሙያ ተቋማት የተቋረጠውን ትምህርት የሚያስቀጥሉበት አቅጣጫን አስቀምጧል።

    ከሁለቱም የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች መቼ እና እንዴት ትምህርት እንደሚጀመር የተሰጡት መረጃዎች የሚከተሉት ናቸው።

    ትምህርት ሚኒስቴር

    የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመከላከል የተቀመጡ ቅድመ ሁኔታዎችን በሦስት ሳምንታት ውስጥ ያሟሉ ትምህርት ቤቶች ትምህርት እንዲጀምሩ ተወስኗል።

    የዓለም የጤና ድርጅትና የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ጤና ሚኒስቴር ወረርሽኙን ለመከላከል ባስቀመጡት ቅድመ ሁኔታ መሠረት ትምህርት ቤቶች ከመከፈታቸው በፊት በመድኃኒት ማጽዳት፣ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭንብልና የእጅ ማጽጃ ማሟላት እንዲሁም አካላዊ ርቀትን ማስተግበር ይጠበቅባቸዋል፡፡

    ለሌላ አገልግሎት (ለምሳሌ፥ ለለይቶ ማቆያነት) ውለው የነበሩ ትምህርት ቤቶችም አስፈላጊውን የማስተካከያ ሥራ ሊሠራላቸው እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡

    እንደየ ትምህርት ቤቶቹ ነባራዊ ሁኔታ ትምህርት በፈረቃ እና አንድ ቀን በመዝለል ተራ ሊያስተምሩም ይችላሉ፡፡

    ትምህርት ሚኒስቴር ባስቀመጠው መስፈርት መሠረት በአንድ ክፍል ውስጥ ከ20 እስከ 25 ተማሪ ማስተማር የሚችሉ መሆንም ይጠበቅባቸዋል ተብሏል፡፡

    የተቀመጠው መስፈርት እንዳለ ሆኖ፡-

    • በገጠር ወረዳና ቀበሌ ከተሞች የሚገኙ ትምህርት ቤቶች በመጀመሪያው ዙር ጥቅምት 9 ቀን 2013 ዓ.ም፤
    • በሁሉም የዞንና የክልል ከተሞች የሚገኙ ትምህርት ቤቶች በ2ኛ ዙር ጥቅምት 16 ቀን 2013 ዓ.ም፤
    • በአዲስ አበባና አዲስ አበባ ዙሪያ ኦሮሚያ ልዩ ዞን የሚገኙ ትምህርት ቤቶች ደግሞ በሦስተኛ ዙር ጥቅምት 30 ቀን 2013 ዓ.ም

    ትምህርት እንዲጀምሩ የውሳኔ ምክረ ሀሳብ መቅረቡ ይታዋሳል፡፡

    በዚህ መሠረት የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመከላከል በሦስት ሳምንታት ውስጥ አስፈላጊውን ቅድመ ሁኔታ ያሟሉ ትምህርት ቤቶች በተቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ትምህርት መጀመር ይችላሉ ተብሏል፡፡

    የሳይንስ እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    መስከረም 14 ቀን 2013 ዓ.ም የኮቪድ-19 ወረርሽኝን እየተከላከልን የዩኒቨርሲቲዎችን እና የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠናን ከተቋረጠበት ለማስቀጠል በመሪዎች ደረጃ በተካሄደው ስብሰባ አቅጣጫ ተቀምጧል።

    በዚህም መሠረት፥ በዓለም የጤና ድርጅት መስፈርትና በኢ.ፌ.ዴ.ሪ ጤና ሚኒስቴር የየኮቪድ-19 መከላከያ መመሪያ መነሻ፣ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር የትምህርትና ሥልጠና ዘርፍ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅት የማስተማርና የማሰልጠን ተግባራት ዝርዝር መመሪያ እንዲያዘጋጅና ተገቢውን ውይይት ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር በማድረግና ግንዛቤ በማሳደግ፣ የተቋማትን ዝግጁነት በማረጋገጥ፣ አግባብነት ያለውን የትምህርትና ሥልጠና መርሀግብር በማዘጋጀት ተማሪና ሰልጣኝ መቀበል የሚችሉ መሆኑን፤ ለዚህም ተቋማት ቀሪ የመስከረም ወር ቀናትንና የጥቅምት ወር የመጀመሪያ ሳምንትን የዝግጅት ምዕራፍ ሥራዎችን ለማከናወን እንዲጠቀሙ ስምምነት ላይ ተደርሷል።

    ስለሆነም፥ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ እስከ ጥቅምት ወር የመጀመሪያ ሳምንት መጨረሻ የተቋማትን የዝግጅት ምዕራፍ አፈፃፀም በአካል እየተገኘ ገምግሞ በቂ የኮቪድ-19 መከላከያ ዝግጅት ላደረጉት የመንግሥትና የግል ዪኒቨርሲቲዎች እንዲሁም የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ተቋማት ተማሪና ሰልጣኝ እንዲቀበሉ የሚፈቅድ ይሆናል። በቂ ዝግጅት ያላደረጉ ተቋማት፣ ዝግጅታቸውን እስከሚያጠናቅቁ ድረስ ክትትል ይደረጋል። ያለ በቂ ዝግጅትና ያለሚኒስቴሩ የመስክ ምልከታና ፈቃድ ተማሪዎችን ወይም ሰልጣኞችን ተቀብሎ መገኘት አግባብነት አይኖረውም።

    ስለሆነም፥ የ2012 ዓ.ም ተመራቂ ተማሪዎችና የስልጠና አጠናቃቂዎች እንዲሁም በሌሎች የትምህርትና ሥልጠና እርከን የሚገኙ የሕብረተሰብ ክፍሎች በቀጣይ በሚዲያ በሚታወጀው የተማሪና ሰልጣኝ ቅበላ መርሀግብር መሠረት በየተቋሞቻቸው ጥሪ የሚደርግላቸው መሆኑን፤ እስከዚያው ድረስ አስፈላጊውን ዝግጅት እያደረጉ እንዲቆዩ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ ገልጸዋል። አያይዘውም ትምህርት/ስልጠና በሚጀመርበት ጊዜ የተጣበበ የትምህርትና ስልጠና ጊዜ የሚኖር በመሆኑ፥ ተማሪዎች/ሰልጣኞች ቀጣይ ጊዜያቸውን ለንባብና ለተያያዥ ዝግጅቶች እንዲጠቀሙበት አሳስበዋል።

    ወቅቱ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በመሆኑ፥ ሁሉን አቀፍ ጥንቃቄ እየተደረገ የትምህርትና ስልጠና ተግባራትን በጋራ ሆነን እንወጣዋለን በማለት ዶ/ር ሳሙኤል መግለጫቸውን ቋጭተዋል።

    ትምህርት እንደሚጀመር

    Anonymous
    Inactive

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን መቀበል ከመጀመራቸው በፊት የተቋማቱ ዝግጁነት እንደሚረጋገጥ ተገለጸ

    አዲስ አበባ (የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር) – የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን መልሶ ለመክፈት የሚያስችሉ ሁኔታዎች ላይ መስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም በጅማ ዩኒቨርሲቲ መሰብሰቢያ አዳራሽ ውይይት ተካሂዷል።

    በውይይቱ መጀመሪያ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሙሉ ነጋ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በመከላከል የትምህርትና ስልጠና ተቋማት መልሶ የመክፈት ሂደትና ዝግጅት በሚል ርዕስ ምክረ-ሃሳብ አቅርበዋል።

    በ2012 ዓ.ም የተቋረጠዉን ትምህርት በልዩ ዕቅድ ለማጠናቀቅ በሚሠሩ ሥራዎችና ትምህርት ሲጀመር ሊደረጉ ስለሚገባቸው ጥንቃቄዎች እንዲሁም ቀደም ተብለው በከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ የሚደረጉ ጥንቃቄዎች ምን መምሰል እንዳለባቸው በምክረ-ሃሳባቸው ቀርቦ ውይይት ተካሂዶባቸዋል።

    በጉባኤው የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ በበኩላቸው ‘መቼ እንክፈት?’ ለሚለው ትክክለኛ መልስ እያንዳንዱ ዩኒቨርሲቲ በዓለም የጤና ድርጅት መለኪያ መስፈርት መሠረት ደረጃውን ጠብቆ በተዘጋጀ ዝርዝር በጥልቀት የዝግጅት መጠኑ ተፈትሾ ዝግጁ ሲሆን ብቻ ነው ብለዋል። በዚያ መሠረት የተቋማት ዝግጅት ይፈተሻል፤ በዳሰሳውም መሠረት መቀበል እንደሚችሉ ፍቃድ ይሰጣል ሲሉ አብራርተዋል።

    ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ እንደገለፁት፥ ቅድሚያ ለተመራቂዎች [ቅድሚያ] በመስጠት፣ ተማሪዎችን በመከፋፈል በትንሽ ቁጥር ይጀመራል። ይህም ከሚታዩ ነገሮች እየተማርን የተማሪ ቁጥር ለመጨመር ዕድል ይሰጠናል ብለዋል። ዝርዝር አፈጻጸሙ በምን እንደሚመራ ከጤና ሚኒስቴር ጋር በመሆን ፕሮቶኮል ይዘጋጃልም ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲዎች የለይቶ ማቆያ ማዕከላት እንደመሆናቸው የክልል መንግሥታት ሥራ ይጠበቅባቸዋል። አማራጭ የለይቶ ማቆያ (quarantine) ቦታዎችን ማዘጋጀትም ግድ ስለሚላቸው እዚያ ላይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ይሠራል ብለዋል። ተማሪዎችን በማጓጓዝ ሂደት ችግር እንዳያጋጥም ከትራንስፖርት ሚኒስቴር እና ጤና ሚኒስቴር ጋር በትብብር እንሠራበታለን ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎችን መልሶ ለመቀበል የሚያስችል እቅድ ካሁኑ አዘጋጅተው ከአስተዳደር ሠራተኞችና መምህራን ጋር በመወያየት የጋራ ሊያደርጉ እንደሚገባም አሳስበዋል። የበፊቱን አሠራር ይዘን መቀጠል አንችልም፤ ዝግጅታችንን፣ ተጋላጭነታችንን አውቀን ተማሪ እንቀበላለን። አንድ ብሎክ ወይም አንድ ካምፓስ ኮቪድ-19 ቢያጋጥም ምን እናደርጋለን ከሚለው ጀምሮ በዝርዝር መሥራት እና እያንዳንዱ እቅድ ያለተማሪዎች እገዛ ተፈፃሚ ስለማይሆን ወደእነሱ ለማስረፅ መሥራት የግድ ይለናል ብለዋል።

    ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ እንዳሉት፥ ጊዜው የተማሪዎች ሕብረት ኃላፊነት የሚፈተንበት ነው። የተማሪዎች ሕብረት አባላት የመፍትሄ ሃሳብ ሆናችሁ ለተፈፃሚነቱ ከዩኒቨርሲቲያችሁ ጋር በትብብር እንድትሠሩ ከእናንተ ይጠበቃል። ሰላማችሁን ማስጠበቅና ለደህንነታችሁ ዘብ መቆም ለትምህርታችሁ ቀጣይነት ዋስትና ነው ሲሉ አብራርተዋል። ዩኒቨርሲቲዎች መከፈታቸው ላይ ብቻ ሳይሆን ተመልሰው እንዳይዘጉም ጭምር የተማሪዎች ድርሻ ከፍተኛ እንደሆነም ጠቁመዋል።

    የጥንቃቄ ቁሳቁሶችን አስመልክቶም የትኞቹ በዩኒቨርሲቲዎች ይቅረቡ የትኞቹ በተማሪዎች ይሟሉ የሚለውን ከተጨባጭ ሁኔታ አንፃር ለይቶ መወሰን አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል።

    በውይይቱ ማጠቃለያ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ ውይይቱ ተቋማት የት ላይ እንደሆኑ ለይተን ድጋፍ ለማድረግ የሚያስችል ግንዛቤ ለመያዝ ታስቦ የተካሄደ ነው ብለዋል። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መሪዎች በአሁኑ ጊዜ ቁርጠኝነት የሚፈልግ የለውጥ ሥራ እየሠራን እንደሆነ መገንዘብ እና በዚያው መጠን መፍጠን ያስፈልጋቸዋል ብለዋል። ተማሪዎችን ወደ ትምህርት የመመለስ ሂደት ባለድርሻ አካላትን በተገቢው መንገድ የማቀናጀት ኃላፊነት ተወስዶ መሠራት ያለበት ጉዳይ ነውም ብለዋል።

    ተማሪዎችን ከመመለስና የኮቪድ-19 ለይቶ ማቆያ ቦታዎችን ከማዘጋጀት አንፃር የፌደራልም ሆነ የክልል መንግሥታት እያንዳንዱ የራሱን ኃላፊነት ወስዶ እንዲሠራ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሥራት ያስፈልጋል ሲሉ ገልፀዋል። እንደከፍተኛ ትምህርት ዓለም-አቀፋዊና ሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ ትኩረት እናደርጋለን። ምርምር ላይ የተገኘውን እውቀት ተጠቅመን ለሀገር የሚውል አድርገን መጠቀምም ይገባናል ብለዋል።

    ዶ/ር ሳሙኤል ኡርቃቶ ሥራውን በማስፈፀም ሂደት ኃላፊዎች የግንኙነት (communication) ክፍተት እንዳይኖር በመነጋገር ሊሠሩ እንደሚገባ ጠቁመው አመራር የሁሉ ነገር ቁልፍ እንደመሆኑ በጋራ መሥራት ያስፈልጋል ብለዋል።

    ነገ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በጉዳዩ ላይ እንደሚወያይና ውሳኔ እንደሚያሳልፍ ይጠበቃል የተባለ ሲሆን፤ ከዚያም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ተቋማቱን ለመክፈት ያበቃሉ ተብለው የተቀመጡ ዝርዝሮችን በመያዝ በዩቨርሲቲዎች በመገኘት ብቁ መሆን አለመሆናቸው ታይቶ አስፈላጊውን መስፈርት ካሟሉ ብቻ እንዲከፍቱ ይደረጋል ብለዋል – ዶ/ር ሳሙኤል።

    ተማሪዎችን መልሶ ለመቀበል በሚደረግ ቅድመ ዝግጅት ወደኋላ የቀራችሁ ዩኒቨርሲቲዎች ካላችሁ ፈጥናችሁ ዝግጅታችሁን አጠናቅቁ ብለው መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን፤ ጉዳዩንም እንደፕሮጀክት ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንዳለባቸው አስበዋል።

    ከተሳታፊዎች የተለያዩ ስጋት ናቸው ተብለው የተነሱ ጉዳዮች ተነስተው ውይይት የተደረገባቸው ሲሆን በሂደት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሆኖ ለመፍታት እንደሚሠራ ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን መቀበል

    Anonymous
    Inactive

    8ኛው የበጎ ሰው ሽልማት ስምንት ግለሰቦችንና ተቋማትን የዓመቱ በጎ በማለት ሸልሟቸዋል

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በልዩ ሁኔታና መስፈርት ጳጉሜን 1 ቀን 2012 ዓ.ም በኢንተርኮንቲነንታል አዲስ ሆቴል የተከናወነው 8ኛው የበጎ ሰው ሽልማት ስምንት የተለያዩ ግለሰቦችን፣ ድርጅቶችንና ማኅበራትን በጎ ተሸላሚዎች በማለት ዕውቅና ተሰጥቷቸዋል።

    የዘንድሮውን የስምንተኛውን ዙር የበጎ ሰው ሽልማት እንደቀደሙት ዓመታት ሁሉ በተለመዱት በአስሩ ዘርፎች እና በተለየ ድምቀት እንዳይካሄድ በዓለምአቀፍ ደረጃ የተከሰተው የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ (ኮቪድ-19) የሽልማቱ አዘጋጆችን እንደገታቸው ጋዜጠኛና የሥራ አመራ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ ወ/ሮ ሕሊና አዘዘ በመግቢያ ንግግሯ ላይ ገልጻለች።

    የዚህን ዓመት ሽልማት ለማከናወን ከየካቲት 1 እስከ መጋቢት 15 ቀን 2012 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ከ200 በላይ የዕጩዎች ጥቆማ ከሕዝብ መቀበላቸውን እና የሽልማት ድርጅቱ የሥራ አመራር ቦርድ የዕጩዎቹን ታሪካቸውንና አብርክቷቸውን በማጥናት ላይ እያለ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ በመከሰቱ ምክንያት የተሟላ ዝግጅት ሊያደርጉ አለመቻላቸውን ጋዜጠኛ ሕሊና ጠቅሳለች።

    የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢ.ፌ.ዲ.ሪ) ፕሬዝደንት ክብርት ወ/ሮ ሳህለወርቅ ዘውዴ፣ የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ ካርዲናል ብርሃነኢየሱስ፣ እንዲሁም የበጎ ሰው ሽልማት የበጎ አድራጎት ድርጅት መሥራችና የቦርድ ሰብሳቢ እንዲሁም የአግዮስ መጻሕፍት ሥራ አስኪያጅ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት ተገኘተዋል።

    የ8ኛው የበጎ ሰው ሽልማት ተሸላሚዎች የሚከተሉት ናቸው፡-

    1. አቶ ካሊድ ናስር

    የመጀመሪያ ልዩ ተሸላሚ ባለፉት አምስት ወራት በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት የገዛ መኖሪያ ግቢያቸውን ሳይቀር በመስጠት፣ መጠለያ የሌላቸውን (የጎዳና ተዳዳሪዎችን) በመደገፍ የበጎ አድራጎት ሥራ የሠሩት አቶ ካሊድ ናስር ናቸው።

    1. አቶ ኪሮስ አስፋው

    አቶ ኪሮስ አስፋው ላለፉት ዘጠኝ ዓመታት ያለማቋረጥ መቶ ጊዜ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ቦንድ የገዙ እና በደም መፍሰስ የሚሞቱ እናቶችን ለመታደግ ለ21 ጊዜ ደም የለገሱ ግለሰብ ናቸው።

    1. አቶ ብንያም ከበደ

    የኢትዮጵያ ልጆች ቴሌቪዥን መሥራች ጋዜጠኛ ብንያም ከበደ የ8ኛው የበጎ ሰው ሽልማት 3ኛ ልዩ ተሸላሚ ሆኗል። ጋዜጠኛ ብንያም ከበደ በኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ ወቅት ልጆች በየቤታቸው ሲሆኑ የሚመለከቱት የሚመጥናቸውና በተለያየ ቋንቋ መሰናዶዎች የሚቀርብበት የኢትዮጵያ ልጆች ቴሌቭዥንን ከመክፈት ጀምሮ ያደረጉት አስተዋጽዖም የበጎ ሰው ሽልማት ተሸላሚ አድርጓቸዋል።

    1. ጋዜጠኛ መሀመድ አል-አሩሲ (محمد العروسي / Mohammed Al-Arousi)

    በአረብኛ ቋንቋ የኢትዮጵያን ሀሳብና እውነት (በተለይም በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ዙሪያ) በዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ሲያስረዳና ሲከራከር የቆየው አቶ መሐመድ አል-አሩሲ (محمد العروسي / Mohammed Al-Arousi) የዘንድሮ የበጎ ሰው ልዩ ተሸላሚ ሆኗል። ከኢትዮጵያዊ ቤተሰቦች በሳዑዲ አረቢያ የተወለደው መሐመድ አል አሩሲ፥ የሕዳሴ ግድብን በሚመለከት ስለኢትዮጵያ በተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን ሙግት በማድረግ ይታወቃል።

    1. ዶ/ር ያዕቆብ አርሳኖ

    በሕዳሴ ግድብ ላይ እንዲሁም በአባይ ወንዝ ላይ ኢትዮጵያ ባላት የልማት ተጠቃሚነት ዙሪያ የተለያዩ ጥናቶችን ያደረጉትና በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ ስለሕዳሴ ግድብ ተግተው በመሞገት የሚታወቁት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ ዶ/ር ያዕቆብ አርሳኖ የዘንድሮው የበጎ ሰው ተሸላሚ ሆነዋል።

    1. ኢትዮ ቴሌኮም

    ኢትዮ-ቴሌኮም በዓመቱ ውስጥ በተለይ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል መልዕክት በማስተላለፍ፣ ማዕድ በማጋራት፣ እንዲሁም የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል በሠራቸው የበጎ አድራጎት ሥራዎቹ የ2012 ዓ.ም የበጎ ሰው ሽልማት ተሸላሚ ሆኗል። ድርጅቱን በመወከል የተገኙት ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ ወ/ት ፍሬሕይወት ታምሩ ሽልማቱን ተረክበዋል።

    1. የሕክምና ባለሙያዎችና ድጋፍ ሰጪ ሠራተኞች

    የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በሀገራችን ከተከሰተ ጀምሮ ራሳቸውን አደጋ ላይ ጥለው የዜጎችን ደኅንነት ለመጠበቅ ከፊት የተሰለፉ የጤና ባለሞያዎችና ድጋፍ ሰጪ ሠራተኞች የ2012 ዓ.ም የዓመቱ የበጎ ሰው ልዩ ተሸላሚ ሆነዋል። የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ሊያ ታደሰ በመድረኩ የጤና ባለሞያዎችንና የድጋፍ ሰጪ ሠራተኞችን በመወከልም ሽልማቱን ተቀብለዋል።

    1. የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሠራተኞች በሙሉ

    የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ጸጥታውን የሚቆጣጠሩ የመከላከያ ሠራዊት እና የፌዴራል ፓሊስ አባላት፣ እንዲሁም የሕዳሴው ግድብ የመሠረት ድንጋይ ከተጣለበት ከመጋቢት 24 ቀን 2004 ዓ.ም ጀምሮ በጉባ በሥራ ላይ የሚገኙ የግድቡ ሠራተኞች የ2012 ዓ.ም የበጎ ሰው ሽልማት ልዩ ተሸላሚ ሆነዋል። በጉባ የሚገኙ ሠራተኞችን ወክለው የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሥራ አስኪያጅ ኢ/ር ክፍሌ ሆሮ ሽልማቱን ተረክበዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    8ኛው የበጎ ሰው ሽልማት

    Semonegna
    Keymaster

    ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ እና አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በአጠቃላይ ከ3 ሺህ በላይ ተማሪዎችን አስመረቁ

    ዲላ/አርባ ምንጭ (ኢዜአ/አ.ም.ዩ) – ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት መረሃ ግብሮች ያሰለጠናቸውን 1,043 ተማሪዎችን ነሐሴ 30 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመረቀ።

    በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫላ ዋታ እንደገለጹት ከተመራቂዎቹ መካከል 283 በመጀመሪያና ሁለተኛ ዲግሪ ትምህርታቸውን የተከታተሉ ናቸው። ቀሪዎቹ በምስክር ወረቀት የተመረቁ መሆኑን አስረድተዋል።

    ተመራቂዎቹ ትምህርታቸውን በበይነ መረብ ቴክኖሎጂ አማካኝነት ሲከታተሉ እንደቆዩ አመልክተው፥ በተለይ የሁለተኛ ዲግሪ ተመራቂዎች የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ከመከሰቱ በፊት የክፍል ትምህርታቸውን ማጠናቀቃቸውን አስታውቀዋል።

    ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ሥራው በተጓዳኝ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን መከላከልን ጨምሮ በተለያዩ የማኅበረሰብ አገልግሎቶች ውጤታማ ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝም ዶ/ር ጫላ ገልጸዋል።

    የዩኒቨርሲቲው የቦርድ አባል አቶ ኡዴሳ ክዮላ በበኩላቸው፥ ተመራቂዎቹ በቀጣይ በሚሰማሩበተ የሥራ መስክ ሀገርና ሕዝብ የሚጠብቅባቸውን ኃላፊነት በታማኝነትና ታታሪነት እንዲወጡ አሳስበዋል።

    ከተመራቂዎቹ መካከል በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ትምህርቱን የተከታተለው ቅዱስ ይገረሙ በሰጠው አስተያየት የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ያሳደረውን ተጽዕኖ ተቋቁሞ ትምህርቱን በማጠናቀቅ ለምረቃ በመብቃቱ መደሰቱን ገልጿል። በሰለጠነበት በ“ሶፍትዌር ዲዛይን” ዘርፍ በመሰማራት እራሱንና ሀገሩን ለመጥቀም እንደሚሠራ ተናግሯል።

    በሁለተኛ ዲግሪ ማኔጅመንት የትምህርት ዘርፍ የተመረቀው ዋቆ ጥላሁን በበኩሉ በትምህርት ቆይታው ያገኘውን እውቀት በመጠቀም ውጤታማ ሥራ ለማከናወን እንደሚጥር ገልጿል።

    የሦስተኛ ትውልድ ዩኒቨርሲቲ የሆነው ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት መረሃ ግብሮች የሚያስተምራቸው ከ17 ሺህ በላይ ተማሪዎች እንዳሉት በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ወቅት ተገልጿል።

    ከተማሪዎች ምርቃት ጋር በተያያዘ፥ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ መርሃ ግብር ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ለ33ኛ ጊዜ አስመርቋል።

    ዩኒቨርሲቲው በ2012 ዓ.ም በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ መርሃ ግብር በመደበኛ፣ በክረምት፣ በሳምንት መጨረሻ እና በተከታታይና ርቀት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ 2,326 ተማሪዎች ቅዳሜ ነሐሴ 30/2012 ዓ/ም በተመሳሳይ ዕለት አስመርቋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደገለጹት፥ ዩኒቨርሲቲው በስድስት የተለያዩ ካምፓሶች በ76 የመጀመሪያ ዲግሪ፣ በ99 የ2ኛ ዲግሪ እና በ21 የ3ኛ ዲግሪ መርሀግብሮች በአጠቃላይ ከ36 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በመደበኛና መደበኛ ባልሆኑ መርሀግብሮች በማስተማር ላይ ይገኛል። ተቋሙ ባለፉት 33 ዓመታት በልዩ ልዩ የምህንድስና፣ የሕክምናና የጤና፣ የግብርና፣ የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ፣ የማኅበራዊ እንዲሁም የተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ ዘርፎች 56,958 ምሩቃንን በማፍራት ለሀገሪቱ የሰው ሀብት ልማት ጉልህ አስተዋፅዖ በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

    አክለውም በ2012 የትምህርት ዘመን በ2ኛው አጋማሽ ላይ በዓለም ላይ በተከሰተው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በሁሉም ደረጃዎች በመማሪያ ክፍል ሆኖ የመማር ማስተማር ሂደት የተቋረጠ ቢሆንም፥ ዩኒቨርሲቲዎች ከሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመሆን ባደረጉት ከፍተኛ ጥረት ቴክኖሎጂን በመጠቀም የጥናትና ምርምር ሥራቸውን ሲሠሩ የቆዩ ተማሪዎች አስፈላጊውን የምረቃ መስፈርት በማጠናቀቅ ለምረቃ መብቃታቸውን ተናግረዋል። በቀጣይ ዓመታት በተከፈቱ የ2ኛ እና የ3ኛ ዲግሪ መርሀግብሮች ላይ የማጠናከር ሥራ የሚሠራ ሲሆን፥ ዩኒቨርሲቲው በ2013 የትምህርት ዘመን በዩኒቨርሲቲው ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በ3ኛ ዲግሪ የሚያስመርቅ መሆኑን ባቀረቡት ሪፖርት ጠቁመዋል።

    የዕለቱ የክብር እንግዳ የጋሞ ዞን አስተዳዳሪና የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ እንደተናገሩት፥ የመማር ግቡ ከግለሰብ ህይወት እስከ ሀገር ድረስ ያሉ የተለያዩ ችግሮችን በመፍታት ምቹና ተስማሚ አኗኗርን ለመፍጠር የለውጥና የዕድገት ጎዳናን መከተል ነው። በመሆኑም የዕለቱ ተመራቂዎች ሀገራችን ኢትዮጵያ ወደ ብልፅግና ማማ እንድትደርስ የበኩላችሁን ድርሻ እንድትወጡ ሲሉ አሳስበዋል። በተጨማሪም ወደ ሥራ ዓለም ሲቀላቀሉ በተሰማሩበት መስክ ሁሉ ሀገራቸውንና ሕዝባቸውን በታማኝነት እንዲያገለግሉ ጠይቀዋል። ሀገሪቱ በበርካታ ፈተናዎች ውስጥ እየተሻገረች የምትገኝ እንደመሆኗ መጠን ፈተናዎቹን በብቃት መክተን ወደ መልካም ዕድል መቀየር ይጠበቅብናል ብለዋል።

    በመጨረሻም የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝደንት ዶ/ር የቻለ ከበደ እና የሬጂስትራርና አልሙናይ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር በለጠ ይልማ የእጩ ምሩቃን መግለጫ በመስጠት አስመርቀዋል።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የጋሞ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የዩኒቨርሲቲው ሥራ አመራር ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ በክብር እንግድነት፣ የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት እንዲሁም የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ከፍተኛ አመራሮችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እና አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ (አ.ም.ዩ)

    ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ እና አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን አስመረቁ

    Semonegna
    Keymaster

    በሁለቱ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲዎች ያሉ የልህቀት ማዕከላት የሚሹትን ትኩረት ለይቶ ለመደገፍ ያለመ ጉብኝት ተካሄደ

    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ ዳይሬክተር ጄኔራሎች፣ ከፍተኛ አማካሪዎች እና ሌሎች ባለሙያዎችን የያዘ ቡድን በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ እና በአዳማ ሳይንስና ቴክሎጂ ዩኒቨርሲቲዎች የሥራ ጉብኝት አድርጓል።

    በጉብኝቱ በሁለቱም ዩኒቨርሲቲዎች በአካል በመገኘት ዩኒቨርሲቲዎቹ የልህቀት ማዕከላት ሆነው ከተፈጠሩ ጊዜ አንስቶ ‘የመንግሥትን ተልዕኮ ተሸክመው የት ደርሰዋል? ምን ውጤት አስመዝግበዋል? ያጋጠማቸው ማነቆ ካለስ ምንድን ነው?’ የሚሉትን ጉዳዮች ለመለየትና መፍትሄ ለማስቀመጥ እንደተካሄደ ተገልጿል።

    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ፕ/ር አፈወርቅ ካሱ የጉብኝቱ ዓላማ በሀገራችን 16 የተለያዩ የልህቀት ማዕከላትን የያዙት አዲስ አበባ እና አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲዎች ከተቋቋሙለት ዓላማ አንፃር የሚገባቸውን ያህል እየሠሩ ነው ወይ የሚለውን ለማየት፣ ያጋጠሟቸውን ችግሮች ለመለየትና በዚያው መጠን ድጋፍ ለማድረግ መሆኑን ገልፀዋል።

    ሁለቱን ዩኒቨርሲቲዎች ሐምሌ 2006 ዓ.ም መንግሥት የሳይንስና ቴክኖሎጂ ተቋም እንዲሆኑ አድርጎና ተጠሪነታቸውን በወቅቱ ለሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አድርጎ ሲያዋቅራቸው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ስርጸት ዩኒቨርሲቲዎች ተብለው በልዩ ሁኔታ የተመሠረቱ ሲሆን፤ ከመማር-ማስተማር ሥራ ጎን ለጎን በጥናትና ምርምር ልህቀት ማዕከልነት (centers of excellence) በኢንዱስትሪ-ዩኒቨርሲቲ ትስስር (industry-university linkages) እና በኢንኩቤሽን ማዕከልነት (incubation centers) እንዲያገለግሉ ታስበው ነው ብለዋል።

    በልህቀት ማዕከላቱ ተማሪዎች ተምረው ሲወጡ ኢንዱስትሪውን በቀጥታ መቀላቀል የሚችሉበት አቅም እንዲያፈሩ ታልሞ መሠራት እንዳለበት ጠቁመው፥ ይህ እውን እንዲሆን ከመቼውም ጊዜ በተለየ ሁኔታ በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ሥራዎች ጋር አገናዝበን በቋሚነት በዕቅድ እንድናግዛቸው እንሠራለን ብለዋል ፕ/ር አፈወርቅ። የልህቀት ማዕከላት በሀብት መደገፍ እንዳለባቸው ገልጸው፥ ነገር ግን ከመንግሥት ቋት ብቻ ሊሆን ስለማይቻል ሀብቶች ማፈላለግ ላይ በጋራ መሥራት ይጠበቃል ብለዋል።

    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ በበኩላቸው፥ የተደራጀ ተቋማዊ አሠራር በመፍጠርና ተቋማዊ አቅምን በመገንባት ተቋማቱን ወደ ትክክለኛ የልህቀት ማዕከልነት መለወጥ ይቻላል ብለዋል። በአከባቢያቸው ከሚገኙ ኢንዱስትሪዎች ጋር ትስስር በመፍጠር መሥራት እንደሚያስፈልግም ጠቁመዋል። የሀገራችን የቴክኖሎጂ፣ ምህንድስና፣ ሳይንስና ምርምር ተቀባይ ብቻ ሆኖ መቀጠል የለበትም ያሉት ዶ/ር ሳሙኤል፥ መሪ እንዲሆኑ ሀብት አፈላልጎ ዩኒቨርሲቲ-ኢንዱስትሪ ትስስር ፈጥሮ መሥራት ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። ቴክኖሎጂ ላይ ትኩረት ሰጥተው እንዲሠሩ በሁሉም የልዕቀት ማዕከላት የሰው ኃይል ችግር መፍታት እንደሚገባ ጠቁመው፤ ለዚህም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥልና ለሀገር ብልጽግና ካላቸውም ፈይዳ አንጻር በየደረጃው ካሉ ባለድርሻ አካላት ጋር በመነጋገር አስፈላጊው ድጋፍና ክትትል እንዲሚደረግላቸውም ገልፀዋል።

    ቡድኑ በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በነበረው ጉብኝት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ደረጀ እንግዳ በዩኒቨርሲቲው ያለውን ነባራዊ ሁኔታ የገለፁ ሲሆን፤ ዓለምአቀፍ እውቅና ለማግኘት የሚያግዙ የአሠራር ሂደቶችን ተከትለው ለመሥራት እየጣሩ መሆኑን ገልፀው፥ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ቢያግዘን ያሏቸውን ተግዳሮቶች አቅርበው ውይይቶች ተካሂደው የመፍትሄ ኃሳቦችም ተጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው ግቢ ውስጥ ያሉ የልህቀት ማዕከላት፣ ቤተ-ሙከራዎች እና የግንባታ ሥራዎችም ተጎብኝተዋል።

    በተመሳሳይ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ጉብኝት ሲካሄድ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ለሚ ጉታ ዩኒቨርሲቲው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ተብሎ ከተሰየመበት ከ2006 ዓ.ም ጀምሮ የተሰሩ ሥራዎችን እና ያጋጠሙ ችግሮችን፥ እንዲሁም የተፈጠሩ ትስስሮችን (partnerships) እና አጠቃላይ በዩኒቨርሲቲው ያለውን የሰው ሀብትና ተማሪዎች መረጃ አቅርበው ውይይት ተካሂዷል። በዩኒቨርሲቲው ልዩ ነው ያሉትን የደብል ሜጀር እና ፋስት ትራክ የትምህርት አሰጣጥ ሁኔታንም ጨምረው አብራርተዋል። ፕሬዚዳንቱ እንዳሉት፥ በአሁኑ ጊዜ በዩኒቨርሲቲው 161 የሦስተኛ ዲግሪ (doctoral) ተማሪዎች አሉ።

    በሁለቱ ጉብኝቶች ከተነሱት ዋና ዋና ድጋፍ የሚሹ ጉዳዮች ውስጥ የግዥ ሥርዓት ችግሮች፣ የተሽከርካሪዎች እጥረት፣ ብቁ መምህራን ከገበያ ላይ በቀላሉ ያለማግኘት፣ በፋይናንስ ምክንያት የግንባታ ሥራዎች መዘግየት ይገኙበታል።

    በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በነበረው ቆይታ ማጠቃለያ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ሙሉ ነጋ እንዳሉት፥ የልህቀት ማዕከላት ሲባል አንድ ተቋም በአገሪቱ መሪ የሆነ የቴክኖሎጂ ማዕከል መሆን ማለት ነው። ይሄንን ደግሞ ከኢንዱስትሪ ጋር ትስስር በመፍጠር፣ ከቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና (TVET) ማዕከላት ጋር በመቀናጀት ኢንዱስትሪውን የሚመጥን፣ የኢንዱስትሪውን ፍላጎት ያሟላ ሰልጣኝ ለገበያ የሚያቀርብ፣ ተግባራዊ ምርምሮች የሚካሄዱበት መሆን ሲቻል ነው ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲዎቹ ከሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ድጋፍ እንፈልጋለን ብለው ያቀረቧቸውን በመውሰድ እንሠራበታለን ሲሉም ዶ/ር ሙሉ አክለዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ ዘመናዊ የሳይንሳዊ አስተሳሰቦች እና የቴክኖሎጂ ውጤቶች ተገናኝተው ለሀገር ብልጽግና የሚውሉባቸው እንደመሆናቸው አስፈላጊው ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።

    በሁለቱም ዩኒቨርሲቲዎች ያሉ የልህቀት ማዕከላት በቡድኑ የተጎበኙ ሲሆን፤ በጉብኝቱም ዩኒቨርሲቲዎቹ የተለያዩ የሀገር ሀብት የሆኑና ምናልባትም በኢትዮጵያ ውስጥ በሌሎች ተቋማት የሌሉና በተለይ ለምርምር ትልቅ ፋይዳ ያላቸው እንደ ኤሌክትሮማይክሮስኮፕ ያሉ መሣሪያዎች መኖራቸው ተመልክቷል። ይሄንንም ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር ትስስር በመፍጠር በጋራ ለመጠቀም የሚቻልባቸው ሁኔታዎች ማመቻቸት ያስፈልጋል ተብሏል። በቀጣይም ተቋማቱ የተፈጠሩበትን ዓላማ ማሳካት እንዲችሉ እና ውጤታማ ሥራዎችን ለመሥራት እንዲቻላቸው የሚያግዙ የታቀዱ ድጋፍና ክትትሎች ከሌላው ጊዜ በተለየ ይካሄዳሉ ተብሏል።

    አዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሚገኙ የልህቀት ማዕከላት፦

    1. Sustainable Energy
    2. Mineral Exploration, Extraction and Processing
    3. Nano Technology
    4. Bioprocessing and Biotechnology
    5. Construction Quality and Technology
    6. High Performance Computing and Big Data Analysis
    7. Artificial Intelligence and Robotics
    8. Nuclear Reactor and Technology

    አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሚገኙ የልህቀት ማዕከላት፦

    1. Space Technology Institute
    2. Institute Of Pharmaceutical Science
    3. Institute Of Water Resource and Irrigation Engineering
    4. Electrical System and Electronics
    5. Advanced Manufacturing Engineering
    6. Advanced Material Engineering
    7. Urban Housing and Development
    8. Transportation and Vehicle

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር

    ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ መርሀ ግብሮች ያሰለጠናቸውን 7520 ተማሪዎች በበይነ-መረብ አስመረቀ

    (ባሕር ዳር) – ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በድኅረ ምርቃ መርሀ-ግብር በሁለተኛ ዲግሪ በመደበኛውና በተከታታይ መርሀ-ግብር 2254 ተማሪዎች፣ በሦስተኛ ዲግሪ መርሀ-ግብር 40 ተማሪዎች፣ እንዲሁም በስፔሻሊቲ መርሀ-ግብር 41 ተማሪዎች፣ በምስክር ወረቀት መርሀ-ግብር 642 ተማሪዎች በድምሩ 7520 ተማሪዎችን በበይነ-መረብ በመታገዝ ነሐሴ 23 ቀን 2012 ዓ.ም አስመርቋል። ከተመራቂ ተማሪዎቸ መካከል 2345 ሴቶች ሲሆኑ፤ ከእነዚህ ሴት ተመራቂ ተማሪዎች መካከል አምስቱ የሦስተኛ ዲግሪ ተመራቂ ተማሪዎች መሆናቸው ታውቋል።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ድኤታና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ አባል ወ/ሮ ሰሀረላ አብዱላሂ፣ የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ዋና ዳሬክተርና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ አባል ፕ/ር ማስረሻ ፈጠነ፣ እንዲሁም የአማራ መልሶ ማቋቋም ልማት ድርጅት /አመልድ/ ዋና ዳሬክተርና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ አባል ዶ/ር አለማየሁ ዋሴ፣ የዩኒቨርሲቲው የሴኔት አባላት፣ ዲኖችና ዳይሬክተሮች እና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።

    በሥነ-ሥርዓቱ የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ፍሬው ተገኘ ለተመራቂ ተማሪዎችና ለተመራቂ ቤተሰቦች የእንኳን ደስ ያላችሁ መልክዕት አስተላልፈዋል። በመልዕክታቸውም ዓለምን ባስጨነቀው የኮሮና ወረርሽኝ ተግዳሮት ሳይደናቀፉ የሚጠበቅባቸውን አሟልተው ለተመረቁ ተማሪዎች አድናቆታቸውን ገልፀው ወደ ቀደምት ትልቅነታችን እና ጥበብ ለመመለስ እና አሁን የጀመርናቸውን የአባይ ግድብን ጨምሮ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ለማሳካት የጋራ መድኃኒት ስለሚያስፈልገን ሁላችንም ለሀገራችን ሰላም በጋራ መሥራት እንደሚገባን አሳስበዋል።

    የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን (ኮቪድ-19) ለመከላከል እና ለመቆጣጠር እየተደረገ ባለው እንቅስቃሴ ዩኒቨርስቲዎች ሕይወትን ለመታደግ የእውቀት እና የሕዝብ ተቋምነታቸውን ማስመስከራቸውን ጠቅሰው ለዚህም ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል የሚያስችሉ ቁሳቁሶችን በማምረት እና በርካታ የፈጠራ ሥራዎችን በማበርከት ሕበረተሰቡን ከወረርሽኙ እየታደገ መሆኑን ዶ/ር ፍሬው ገልፀዋል። በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት ተማሪዎች በኮቪድ-19 ምክንያት ሙሉ በሙሉ ከትምህርት እንዳይለዩ በዩኒቨርሲቲው የICT ባለሙያዎች የበለፀገ የትምህርት አስተዳደር ሥርዓት (learning management system) ለአማራ ክልለዊ መንግሥት ትምህርት ቢሮ ማበርከቱን አውስተዋል።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚንስትርና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር ኢ/ር ስለሺ በቀለ እንዳሉት መማር ትርጉም የሚኖረው የሕበረሰተቡን ኑሮ ማሻሻልና ለችግሮቹ መፍቻ የሚሆን አዳዲስ አሠራሮችንና ሀሳቦችን መፍጠር ሲቻል መሆኑን ጠቁመው የሀገራችን ችግር የሚፈታው የችግሮችን ስፋትና ጥልቀት በሚረዱ ምሁራን በመሆኑ የምንግዜም ጠላታችን የሆነውን ድህነትን ለማስወገድ ተመራቂ ተማሪዎች በተመረቁበት መስክ ትኩረት ሰጥተው ለመሥራት ትልቅ ኃላፊነት እንዳለባቸው አሳስበዋል።

    አክለውም፥ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የልሕቀት ማዕከል ለመሆን የሚያደርገውን ትጋት አድንቀው፤ በእምቦጭ ዙሪያ ብዙ ሥራ መሥራት የሚያስችል በመሆኑ ዩኒቨርሲቲው ትኩረት ሰጥቶ በስፋት እንዲሠራ ጥሪ አቅርበዋል። ከአባይ ፏፏቴ ጀምሮ እስከ ሰሜን ብሔራዊ ፓርክ ድረስ ትኩረት በመስጠት የቱሪዝም ኮሪደር ለማድረግ የሚቻልበትን ምርምር በመሥራት መሻሻል የሚገባቸውን ጉዳዮች ማሳየትም ከዩኒቨርሲቲው እንደሚጠበቅ ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ ተናግረዋል።

    የምረቃ ሥነ-ሥርዓቱን ጥቂት ተማሪዎች አዳራሽ ውስጥ በአካል በመገኘት፥ አብዛኛዎቹ ተመራቂ ተማሪዎች ደግሞ በየቤታቸው ሆነው በአማራ ቴሌቪዥን ከጥበብ ህንፃ የመሰብሰቢያ አዳራሽ በቀጥታ ስርጭት፣ በፌስቡክ (Facebook) እና ዩቲዩብ (YouTube) የተላለፈውን ታድመዋል።

    ምንጭ፦ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ

    ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ

     

    Anonymous
    Inactive

    ለመጪው የትምህርት ዘመን ትምህርት ቤቶች ከነሐሴ 20 ጀምሮ ምዝገባ እንደሚጀምሩ ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)፦ የ2013 ዓ.ም. የትምህርት ዘመን ምዝገባ ከነሐሴ 20 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ እንደሚጀመር ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ ትምህርት ቤቶች የቀጣይ ዓመት የትምህርት ምዝገባን ከነሐሴ 20 ጀምረው ማካሄድ ይችላሉ ብሏል።

    የትምህርት ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ወ/ሮ ሀረጓ ማሞ፥ ትምህርት ቤቶች ምዝገባውን ሲያካሂዱ ኮሮና ቫይረስን (ኮቪድ 19) ለመከላከል በዓለም የጤና ድርጅት እና በኢፌዲሪ ጤና ሚኒስቴር የተቀመጡ ቅድመ ዝግጅቶችንና መከላከያ መንገዶችን በሚገባ በመተግበር መሆን እንዳለበት አሳስቧል።

    ትምህርት የሚጀመርበት ቀን በቀጣይ እንደሚወሰንና ይፋ እንደሚደረግም የገለፁት ዳይሬክተሯ፥ የቀጣዩ ዓመት የትምህርት ሂደት ስኬታማ እንዲሆንም ተማሪዎች፣ መምህራን፣ ወላጆችና መላው የትምህርት ማኅበረሰብ ይህን አስቸጋሪ ወቅት ለማለፍ የሚተላለፉትን ገዢና አስፈላጊ መልዕክቶች ብቻ በመከታተልና ቫይረሱ ሊተላለፍ የሚችልባቸውን መንገዶች ከውዲሁ በማስወገድ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግም አሳስበዋል።

    አካላዊ ርቀትን ጠብቆ ለማስተማር፣ የንፅህና መጠበቂያዎችን ከማዘጋጀትና መሰል የኮሮና ቫይረስን  የመከላከያ መንገዶችን ተግባራዊ ለማድረግ በሚያስችል መልኩ ቀድመው ዝግጅት የሚደረግባቸው ተግባራትም እንደሆኑ አክለው ገልጸዋል።

    በምን ዓይነት መልኩ ትምህርት መጀመር እንዳለበት የተለያዩ አማራጮችን ለማመላከት ሰፊ ውይይት እየተደረገባቸው ሲሆን፥ ውሳኔዎች ላይ ሲደረሱ በቀጣይ ይፋ ይደረጋሉ።

    የ8ኛና የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ጊዜን በተመለከተ ትምህርት ሚኒስቴር በቅርብ የሚያሳውቅ ሲሆን ተማሪዎች ራሳቸውን እያዘጋጁ እንዲቆዩ ሚኒስቴሩ አሳስቧል።

    በመጪው የትምህርት ዘመን ተማሪዎች ለኮሮና ተጋላጭ እንዳይሆኑ ትምህርት ሚኒስቴር ምን ዓይነት ዝግጅት እያደረገ ነው?

    በ2013 የትምህርት ዘመን ተማሪዎች ለኮሮና ተጋላጭ እንዳይሆኑ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ትምህርት ሚኒስቴር ነሐሴ 19 ቀን 2012 ዓ.ም. አስታወቋል።

    የትምህርት ሚኒስትሩ ዶ/ር ኢ/ር ጌታሁን መኩሪያ እንደገለጹት፥ የቀጣዩ ዓመት ትምህርት ምዝገባ ከነገ ነሐሴ 20 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ በመንግሥት እና በግል ትምህርት ቤቶች እንደሚጀመር እና ትምህርት ቤቶች የኮሮና ቫይረስ መከላከያ ቅደመ ዝግጅቶችንና  ተግባራትን በተገቢው መንገድ በመተግበር ምዝገባ እንዲያከናውኑ አሳስበዋል።

    የበሽታው ሁኔታ እየተስፈፋ ቢሆንም የትምህርት ዝግጅት እና እንቅስቃሴ መጀመር አስፈላጊ ሆኑ መገኘቱን ነው ሚኒስትሩ የተናገሩት።

    ወደ መማር ማስተማር ተግባር በሚገባበት ወቅት ለተማሪዎች ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር እንደሚሠራ ገልጸው፥ የፊት መሸፈኛ ጭንብል (face mask)፣ የእጅ ማፅጃ (sanitizer) እና መሰል አቅርቦቶችን ከባላድርሻ አካላት ጋር በመሆን ለማቅረብ በዝግጅት ላይ መሆናቸውን ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    በግልም ሆነ በመንግሥት ትምህርት ቤቶች የኮሮና ቫይረስ ስርጭት እንዳይከሰት ተማሪዎች የፊት መሸፈኛ ጭንብል በማድረግ፣ አካላዊ ርቀትን በመጠበቅ እና እጅን በተደጋጋሚ በመታጠብ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚኖርባቸው ሚኒስትሩ አሳስበዋል።

    ከቅድመ መደበኛ ጀምሮ እስከ 12ኛ ክፍል ላሉት ተማሪዎች በ2012 የትምህርት ዘመን በ2ኛ ሴሚስተር ያለፋቸውን ትምህርቶች ማካካሻ ለመስጠት መታሰቡንም ዶ/ር ኢ/ር ጌታሁን ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮሮፖሬሽን (EBC) ጋር በነበራቸው ቆይታ ገልጸዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    በመጪው የትምህርት ዘመን ተማሪዎች

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 58 total)