Search Results for 'አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ'

Home Forums Search Search Results for 'አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 35 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    የጫሞ ሐይቅ ተፋሰስን ወደነበረበት ለመመለስ ለሚሠራው ፕሮጀክት የአመራሮች የጋራ መድረክ ተመሠረተ

    አርባ ምንጭ (አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ) – ከጀርመን ልማት ባንክ በተገኘ 25 ሚሊዮን ዩሮ የገንዘብ ድጋፍ የጫሞ ሐይቅ ተፋሰስን ወደነበረበት ለመመለስ በቅርቡ ሥራ የሚጀምረው ፕሮጀክት ስኬታማ እንዲሆን ከጋሞና ኮንሶ ዞኖች እንዲሁም ከደራሼ፣ ቡርጂና አማሮ ልዩ ወረዳዎች የተወጣጡ አስተዳዳሪዎችን እና የግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ኃላፊዎችን ያካተተ የአመራሮች የጋራ መድረክ ጥር 10 ቀን፥ 2015 ዓ.ም በይፋ ተመሥርቷል። በዕለቱ የጋሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ብርሃኑ ዘውዴም የአመራር መድረኩ ሰብሳቢ ሆነው ተመርጠዋል።

    የዕለቱን መርሃ-ግብር በመክፈቻ ንግግር ያስጀመሩት የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የኃይለማርያምና ሮማን ፋውንዴሽን ሰብሳቢ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በጫሞ ሐይቅ ተፋሰስ በሁለት ዞኖችና ሦስት ልዩ ወረዳዎች ባሉ 10 ወረዳዎች የሐይቁን ህልውና ለመታደግ በቅርቡ ከጀርመን ልማት ባንክ በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ከሌሎች አጋር አካላት ጋር በመሆን አሳታፊና ዘላቂ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እንደሚጀመር ተናግረዋል። ለ5 ዓመታት በሥራ ላይ የሚቆየው ፕሮጀክቱ ሕብረተሰቡን ማዕከል አድርጎ የሚሠራ ሲሆን፥ ሕብረተሰቡን በማስተባበርና በማንቀሳቀስ ሂደት ውስጥ የአካባቢው አመራሮች የሚኖራቸው ሚና የጎላ በመሆኑ፥ ይህንን የአመራሮች መድረክ መፍጠር አስፈልጓል ብለዋል። የአካባቢው አመራሮችም ፕሮጀክቱ የተፈጥሮ ሀብቶቻችንን ወደነበሩበት ከመመለስ ባሻገር ከሥራ ዕድል ፈጠራና የማኅበረሰቡን የአኗኗር ሁኔታ ከመቀየር አንፃር ያለውን ፋይዳ በመገንዘብ ለፕሮጀክቱ ስኬታማነት በታማኝነትና በቁርጠኝነት ሊሠሩ እንደሚገባም አጽንዖት ሰጥተው አሳስበዋል።

    እንደ አቶ ኃይለማርያም ለፕሮጀክቱ እውን መሆን በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በዘርፉ የተደረጉ ሳይንሳዊ የምርምር ሥራዎች ሚናቸው የጎላ ሲሆን፥ በቀጣይም ዩኒቨርሲቲው በፕሮጀክቱ አፈፃፃም ወቅት የተጣለበትን በዕውቀትና ሳይንስ ላይ የተመሠረተ የቁጥጥርና ክትትል ሥራዎች በአግባቡ እንደሚወጣ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።

    በግብርና ሚኒስቴር የግብርና ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ፕ/ር እያሱ ኤሊያስ በበኩላቸው በተፋሰሱ ላይ የሚጀመረው ፕሮጀክት የሐይቁን ህልውና ከመጠበቅ ባሻገር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንዲሁም የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ መሆኑን ተናግረዋል። በጫሞ ተፋሰስ ላይ የሚሠራው ዘላቂ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እንደሀገር ትኩረት የተሰጠው ሲሆን ለውጤታማነቱ የአካባቢው አመራሮች ማኅበረሰቡን በተለይ ወጣቶችን በስፋት በማሳተፍ የበኩላቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። እንደ ግብርና ሚኒስቴርም ጽ/ቤታቸው በፕሮጀክቱ የተጣለበትን ኃላፊነት ሙሉ በሙሉ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል።

    የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ ዩኒቨርሲቲው ለተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ሲገልጹ፥ ከዚህ ቀደም በወዜ ሻራ ተፋሰስ፣ አሁን ላይ ደግሞ በቤራ ተራራ ላይ እየሠራ ያለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ተጠቃሽ ነው ብለዋል። ፕሮጀክቱ የጫሞ ሐይቅ ተፋሰስን ሙሉ በሙሉ በሸፈነ መልኩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ለማከናወን የታቀደ መሆኑ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የሚኖረው ጠቀሜታ ጉልህ መሆኑን ያወሱት ፕሬዝደንቱ የአካባቢው አመራሮችም ይህን በብዙ ጥረት የተገኘ ዕድል በአግባቡ መጠቀም አለባቸው ብለዋል። ዩኒቨርሲቲውም ሆነ የዘርፉ ተመራማሪዎች ለፕሮጀክቱ እውን መሆን እንዳደረጉት ጥረት ሁሉ ለአፈፃፀሙም የበኩላቸውን ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውንም ዶ/ር ዳምጠው ተናግረዋል።

    የጋሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ በበኩላቸው የዚህ ፕሮጀክት እውን መሆን ችግር ከማውራት ወጥተን ወደመፍትሄው እንድንገባ በር የከፈተ መሆኑን ጠቅሰው በዕለቱ የተመሠረተው የአመራሮች መድረክም አመራሩ ሥራውን በባለቤትነት ወስዶት እንዲሠራ ያስችላል ብለዋል። የችግሩን አንገብጋቢነት በመገንዘብ አመራሩ ማኅበረሰቡን የማንቃትና የማስተባበር እንዲሁም ለፕሮጀክቱ ስኬታማነት የሚውሉ አስተዳደራዊና ፖለቲካዊ ውሳኔዎችን በመወሰን ኃላፊነቱን እንዲወጣ አሳስበው እንደመድረኩ ሰብሳቢነታቸውም የበኩላቸውን ሚና በቁርጠኝነት ለመወጣት ቃል ገብተዋል።

    በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የ”AMU-IUC” ፕሮግራም ማኔጀርና የውሃ ሥነ-ምኅዳር ተመራማሪው ዶ/ር ፋሲል እሸቱ ብዙ ጊዜ መሰል ፕሮጀክቶች በፖለቲካ አመራሩ ዘንድ የባለቤትነት ስሜት መፈጠር ባለመቻሉ ስኬታማ ሳይሆኑ እንደሚቀሩ አውስተዋል። አሁን ላይ የተመሠረተው የአመራሮች የጋራ መድረክ ማኅበረሰቡን ከማስተባበር አንፃርና ለፕሮጀክቱ ውጤታማነት የተለያዩ ውሳኔዎችንና እርምጃዎችን መውሰድ የሚችሉ አመራሮችን በሥራው ሂደት ላይ በኃላፊነት ስሜት ማሳተፍ የሚያስችል በመሆኑ ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል። እንደዘርፉ ተመራማሪ በግላቸውም ሆነ በሚመሩት ፕሮግራም አማካኝነትና በፕሮጀክቱ ለዩኒቨርሲቲው በተሰጠው ኃላፊነት መሠረት ለፕሮጀክቱ ስኬት አስፈላጊውን ሙያዊ ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን የገለጹት ዶ/ር ፋሲል የሚመለከታቸው አካላት እንዲሁም የአካባቢው ማኅበረሰብ ሥራው የጫሞ ሐይቅ የህልውና ጉዳይ መሆኑን በመገንዘብ ለፕሮጀክቱ ስኬት የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

    የአመራሮች መድረኩ በፕሮጀክቱ አፈፃፀም ሂደት ውስጥ ፈጣን ፖለቲካዊና አስተዳደራዊ ውሳኔዎችንና እርምጃዎችን የሚወስድ የአስተዳደር መዋቅር ለመፍጠር የተዘጋጀ መሆኑ በዕለቱ በቀረበው መመሪያ ላይ ተመላክቷል። በመመሪያው እንደተመላከተው መድረኩ በፕሮጀክቱ የተያዙ የሥራ ዕቅድና ሀብት በአግባቡ ሥራ ላይ እንዲውሉ የመሥራትና ቁጥጥር የማድረግ፣ የፕሮጀክቱ አፈፃፀምን በየጊዜው የመገምገም፣ በፕሮጀክቱ አፈፃፀም ሂደት ውስጥ የሚገጥሙ ተግዳሮቶችንና ማነቆዎችን ለይቶ በፍጥነት የመፍታት፣ የአካባቢው ማኅበረሰብ በፕሮጀክቱ ላይ በስፋት መሳተፉንና ተጠቃሚ መሆኑን የማረጋገጥና ሌሎች ኃላፊነቶች ተሰጥቶታል።

    ምንጭ፦ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት

    የጫሞ ሐይቅ ተፋሰስን ወደነበረበት የመመለስ ፕሮጀክት

    Semonegna
    Keymaster

    አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በቅድመና ድኅረ ምረቃ መርሃ ግብሮች ያሠለጠናቸውን ተማሪዎች ለ35ኛ ጊዜ አስመረቀ

    አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያና በ2ኛ ዲግሪ መርሃ ግብሮች በመደበኛ፣ በማታ፣ በክረምት፣ በሳምንት መጨረሻ እና በተከታታይና ርቀት፣ እንዲሁም በ3ኛ ዲግሪ በመደበኛ መርሃ ግብር ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ 2,561 ተማሪዎችን ሰኔ 25 ቀን፥ 2014 ዓ.ም አስመርቋል፡፡ ከተመራቂዎቹ መካከል 662ቱ ሴቶች ናቸው፡፡

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ የኢትዮጵያን እድገትና ክብር ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ በሀገሪቱ የሚገኙ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ማኅበረሰብና ምሩቃን ድርሻቸው የጎላ መሆኑን ጠቅሰው ተመራቂዎች በዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው የሀገር ሰላምን ለማደፍረስ የሚሰራጩ እኩይ ተልዕኮዎችን ሳያስተናግዱ በስኬት አጠናቀው ለምረቃ በመብቃታቸው አድናቆትና ምስጋና አቅርበዋል፡፡ ይህን መልካም ሥነ ምግባር በማስቀጠል በሚሄዱበት የሀገራችን አካባቢዎች ሁሉ ለሰላም፣ ልማትና ዲሞክራሲ ቅድሚያ ሰጥተው የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉም አደራ ብለዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው በ6 ካምፓሶች በ75 የመጀመሪያ፣ በ114 የ2ኛ እና በ26 የ3ኛ ዲግሪ በአጠቃላይ ከ25 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በመደበኛና መደበኛ ባልሆኑ መርሃ ግብሮች በማስተማር ላይ ሲሆን የዛሬዎቹን ተመራቂዎች ጨምሮ ዩኒቨርሲቲው ከ72 ሺህ በላይ ምሩቃንን ማፍራቱን ፕሬዝደንቱ ገልጸዋል፡፡

    የብሔራዊ ሚቲዎሮሎጂ ኤጀንሲ ዳይሬክተር ጄኔራል፣ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ አባልና የእለቱ የክብር እንግዳ አቶ ፈጠነ ተሾመ ለተመራቂዎች ባስተላለፉት መልዕክት ትምህርት ለአንድ ሀገር ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ እድገት ቁልፍ መሣሪያ እንዲሁም የማይከስር ሀብት መሆኑን በመገንዘብ እንዲሁም የሀገራችንን ሁለንተናዊ ለውጥ ለማረጋገጥ ከፍተኛ ኃላፊነት እንዳለባቸው በመረዳት ተመራቂዎች በትምህርት ቆይታቸው በንድፈ ሃሳብና በተግባር ያገኙትን ዕውቀት በሚሰማሩበት ዘርፍ ሁሉ ለዘላቂ እድገትና ሽግግር እንዲጠቀሙበት አሳስበዋል፡፡

    የዩኒቨርሲቲው የቀድሞ ምሩቃን /አልሙናይ/ ማኅበር ፕሬዝደንት አቶ ኤርሚያስ ዓለሙ ተመራቂዎች በትምህርት ያገኙትን ዕውቀት በተግባር ውጤታማ ለማድረግ ብዙ የሚጠበቅባቸው መሆኑን ተናግረው በቀጣይ ራሳቸውን ለማሻሻል እንዲሁም ያስተማራቸውን ቤተሰብ፣ ማኅበረሰብና ሀገር ለማገልገል በታማኝነትና በትጋት እንዲሠሩ እንዲሁም የዩኒቨርሲቲው የቀድሞ ምሩቃን አባል በመሆን ለአካባቢው ማኅበረሰብና ለዓለም መልካም አስተዋጽኦዎችን እንዲያበረክቱ ጠይቀዋል፡፡

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የብሔራዊ ሚቲዎሮሎጂ ኤጀንሲ ዳይሬክተር ጄኔራልና የዩኒቨርሲቲው ሥራ አመራር ቦርድ አባል፣ የጋሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ፣ የሃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ከፍተኛ አመራሮችና ተጋባዥ እንግዶች የተገኙ ሲሆን የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ጉዳዮች ም/ፕሬዝደንት ዶ/ር ዓለማየሁ ጩፋሞ እጩ ምሩቃንን ለምረቃ በማቅረብ አስመርቀዋል፡፡

    ምንጭ፦ የዩኒቨርሲቲው የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት

    አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive

    5ኛው “ሀገረሰባዊ ዕውቀት ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት” ሀገራዊ ዓውደ ጥናት በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተካሄደ

    አርባ ምንጭ (አምዩ) –  የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ (አምዩ) የባህልና ቋንቋ ጥናት ኢንስቲትዩት ከኢፌዴሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 5ኛው “ሀገረሰባዊ ዕውቀት ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት” ሀገራዊ ዓውደ ጥናት ግንቦት 26 ቀን 2013 ዓ.ም. በዩኒቨርሲቲው ተካሂዷል።

    በዓውደ ጥናቱ “የአሪ ብሔረሰብ ባህላዊ የተፈጥሮ ሀብት ዕውቀት፣ እሳቤዎችና ክዋኔዎች፣” “ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴ በጋሞ ዞን ካምባ ወረዳ፣” “ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎች በጋሞ ሕዝብ፡- የኦቾሎ ደሬ ተሞክሮ” እና “ሀገር በቀል ዕውቀት ለብዝሃ ሕይወት ጥበቃ፡- የጋሞ እና ኮንሶ ጥብቅ ደኖች” የሚሉ ሀገር በቀል ዕውቀት፣ ክዋኔና እሳቤዎች ለአካባቢ ጥበቃና ለግጭት አፈታት ያላቸውን ሚና የሚዳስሱ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል። ጥናታዊ ጽሑፎቹ በዩኒቨርሲቲው የባህልና ቋንቋ ጥናት ኢንስቲትዩትና በሶሲዮሎጂና ሶሻል አንትሮፖሎጂ ትምህርት ክፍል መምህራንና ተመራማሪዎች የተሠሩ ናቸው።

    በጽሑፎቹ እንደተመለከተው ሀገር በቀል ዕውቀት፣ እሳቤዎችና ክዋኔዎች የተፈጥሮ ሀብትን በመጠበቅና በመንከባከብ እንዲሁም ግጭቶችን በመከላከልና በመፍታት ረገድ ለበርካታ ዘመናት አዎንታዊ ሚና ሲጫወቱ ቆይተዋል። ይሁን እንጂ ዘመናዊነትና ዘመናዊ የመንግሥት አስተዳደር፣ ማኅበራዊና ባህላዊ ለውጦች፣ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች፣ በፌዴራልና በአካባቢ አስተዳደር በቂ ትኩረት አለማግኘትና ሌሎችም ምክንያቶች ለሀገር በቀል እሴቶቹ አደጋ የጋረጡ ሆነዋል። ተመራማሪዎቹ በጥቆማቸው ከመንግሥት አካላት ተገቢው ትኩረትና ዕውቅና እንዲሰጠው፣ ማኅበረሰብ መር የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ እንዲጠናከር እንዲሁም የምርምር፣ የካርታና ዶኪዩሜንቴሽን ሥራዎች እንዲሠሩ ሃሣብ አቅርበዋል።

    የኢፌዴሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚንስትር ዴኤታና የዕለቱ የክብር እንግዳ ወ/ሮ ብዙነሽ መሠረት እንደገለጹት ሀገራችን ኢትዮጵያ በሕክምና፣ በግብርና፣ በግጭት አፈታት፣ በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ እና በሌሎችም በርካታ መስኮች የእምቅ ባህልና ዕውቀት ባለቤት መሆኗ ለማኅበረሰቡ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ሀገር በቀል መፍትሔዎችን ለመስጠት የሚያስችል ነው። በመሆኑም ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በመቅረጽ እንዲሁም ምርምሮች እንዲካሄዱ ድጋፍ በማድረግ ሀገር በቀል ዕውቀትና ክዋኔዎች ለሀገር ጥቅም እንዲውሉ በትኩረት ይሠራል።

    ዓውደ ጥናቱ የኢፌዴሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ የክልሉና የዞኑ ባህልና ቱሪዝም ቢሮዎች እንዲሁም አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በጋራ ለመሥራት ያቀዷቸውን ሥራዎች የሚያጠናክር መሆኑን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው የሚገኝበት አርባ ምንጭ እና አካባቢው በርካታ ባህላዊ እሴቶችን ያቀፈ በመሆኑ ለዩኒቨርሲቲው የባህልና ቋንቋ ጥናት ኢንስቲትዩት ውጤታማነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት መሆኑንም ተናግረዋል።

    የዩኒቨርሲቲው የምርምርና ማኅበረሰብ አገልግሎት ም/ፕሬዝደንት ተ/ፕ በኃይሉ መርደኪዮስ በበኩላቸው ሀገር በቀል ዕውቀት ከዘመናዊ ዕውቀት ጋር ተጣምሮ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲሻገርና ለሀገር ልማት እንዲውል ለሀገር በቀል ዕውቀት ያለንን የተሳሳተ ግንዛቤ ማረም ብሎም በምርምር ማገዝ ያስፈልጋል ብለዋል።

    የዩኒቨርሲቲው የባህልና ቋንቋ ጥናት ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር ዶ/ር ሰኢድ አህመድ ኢንስቲትዩቱ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ምርምሮችን ከማካሄድ ባሻገር የሥነ-ጥበብ ዘርፍን ለማሳደግ አበረታች ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ኢንስቲትዩቱ ከዚህ ቀደም ሀገራዊ የትርጉምና የተርጓሚነት ሙያ ጉባዔ ማዘጋጀቱን አስታውሰው መሰል መድረኮች ልምድና ተሞክሮዎችን ለመቅሰም፣ ሀገራዊ መግባባትን ለመፍጠርና ሙያዊ አቅምን ለመገንባት ፋይዳ እንዳላቸውም ተናግረዋል።

    የኢፌዴሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች፣ የክልልና የዞን የሥራ ኃላፊዎች፣ የዩኒቨርሲቲው አመራሮች፣ መምህራን፣ ተመራማሪዎችና የሀገር ሽማግሌዎች በዓውደ ጥናቱ ተሳትፈዋል።

    ምንጭ፦ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት

    ሀገረሰባዊ ዕውቀት ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት ዓውደ ጥናት

    Semonegna
    Keymaster

    በኢትዮጵያ ስምንት ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል ተብለው ተለዩ

    ጎንደር (ኢዜአ) – በኢትዮጵያ ስምንት የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል (Center of Excellence) በመባል መለየታቸውን የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።

    የጎንደር ዩኒቨርሲቲ በተመረጡ ትምህርት ቤቶች በትምህርት ጥራት ዙሪያ ያካሄደውን የምርምር ግኝቶች ላይ መስከረም 29 ቀን 2013 ዓም ከባለድርሻዎች ጋር ተወያይቷል።

    የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከፍተኛ አማካሪ ዶ/ር ወርቁ ነጋሽ በወቅቱ እንደገለጹት፥ በሀገሪቱ የሚገኙ 46 ዩኒቨርሲቲዎች በምርምር፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ እንዲሁም በአጠቃላይ ትምህርት በሚል በሦስት ደረጃዎች ተለይተዋል።

    ባለፉት ዓመታት በርካታ ችግር ፈቺ የምርምር ውጤቶችን ሲያበረክቱ የቆዩና ወደፊትም አስተዋጽዖ ይኖራቸዋል የተባሉ ስምንት ዩኒቨርሲቲዎች በምርምር ዘርፍ የልህቀት ማዕከል እንዲሆኑ መለየታቸውን ተናግረዋል።

    ጎንደርአዲስ አበባባህር ዳርመቀሌጅማሀዋሳአርባ ምንጭ እና ሐረማያ ዩኒቨርሲቲዎች የምርምር ልህቀት ማዕከል እንዲሆኑ ተለይተዋል” ብለዋል ዶ/ር ወርቁ።

    ለአንድ ሀገር ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ችግር ፈቺ ምርምር ቁልፍ ሚና እንዳለው የገለጹት ዶ/ር ወርቁ፥ “ያደጉ ሀገሮች የእድገት ምስጢርም ከዚህ የመነጨ ነው” ብለዋል። የምርምር (Research) ዩኒቨርሲቲዎቹ በዓለምአቀፍ ደረጃ ከሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር አቻ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ አቅማቸውን ለመገንባት በትኩረት እንደሚሠራ አመላክተዋል።

    ሌሎች 15 የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ በሳይንስና ቴክኖሎጂ (Science and Technology) ዘርፍ ትምህርትና ስልጠና እንዲሰጡ መለየታቸውን ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ በቂ እውቀትና ክህሎት ያዳበረ ዜጋ ማፍራት እንዲችሉ ተከታታይ ድጋፍ እንደሚደረግላቸው አመላክተዋል።

    ቀሪዎቹ 23 ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ አጠቃላይ ትምህርትና ስልጠና እንዲሰጡ የተለዩ መሆኑን ዶ/ር ወርቁ አስታውቀዋል።

    የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር መርሻ ጫኔ ዩኒቨርሲቲው በርካታ ችግር ፈቺ ጥናትና ምርምር በማካሄድ ለማህበረሰቡ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረጉን ተናግረዋል።

    ላለፉት ሶስት አመታት ጎንደር ከተማን ጨምሮ በሰሜን፣ በማእከላዊና በምዕራብ ጎንደር ዞኖች በተመረጡ 1,343 የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ላይ በትምህርት ጥራት ዙሪያ ጥናትና ምርምር መካሄዱን ገልጸዋል። በምርምር ውጤቶቹ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይትና ምክክር እየተካሄደ መሆኑን አስታውቀዋል።

    “በዩኒቨርሲቲው የሥነ-ትምህርት ኮሌጅ መምህራን የተዘጋጀው የምርምር ውጤት ለፖሊሲ አውጪዎች ጠቃሚ ግብዓት ሆኖ የሚያገለግል ነው” ያሉት ደግሞ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አሥራት አጸደወይን ናቸው።

    ባለፈው ዓመት ዩኒቨርሲቲው ከ200 በላይ የምርምር ሥራዎችን ማካሄዱን ዶ/ር አሥራት አስታውሰዋል፤ ዘንድሮም በተለያዩ ዘርፎች ምርምር ለማካሄድ የሚያስችል ቅድመ ዝግጅት እያካሄደ እንደሚገኝ ፕሬዝዳንቱ ማሳወቃቸውን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዘግቧል።

    ለአንድ ቀን በተካሄደው ውይይት የዩኒቨርሲቲው መምህራንና የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም ከጎንደር ከተማ አስተዳደር የተውጣጡ መምህራንና የትምህርት አመራሮች ተሳትፈዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    የምርምር ልህቀት ማዕከል

    Semonegna
    Keymaster

    ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ 70 አዳዲስ የድኅረ-ምረቃ ትምህርት ክፍሎችን ሊከፍት ነው

    ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በአዲሱ የትምህርት ዘመን በሁለተኛ እና ሦስተኛ ድግሪ 70 አዳዲስ ትምህርት ዓይነቶችን ለመክፈት መዘጋጀቱን አስታወቀ። ይህም ዩኒቨርሲቲው በሁለተኛ እና ሦስተኛ ዲግሪ የሚሰጣቸውን የትምህርት ዓይነቶች 101 እንደሚያደርሰው ተጠቁሟል።

    የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ታምሩ አኖሌ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንዳሉት በ2013 የትምህርት ዘመን በዩኒቨርሲቲው አዲስ ከሚከፈቱት 19 የሦስተኛ ዲግሪ መርሀግብሮች ውስጥ የገዳ እና የአስተዳደር ጥናት አንዱ ነው።

    ቀሪዎቹ የተለያዩ የሁለተኛ ዲግሪ መርሀግብሮች መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ይህም ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በሦስተኛ ዲግሪ ይሰጥ የነበረውን አንድ መርሀግብር ወደ 20 ከፍ ሲያደርገው የሁለተኛ ዲግሪውን ደግሞ ከ30 ወደ 81 የትምህርት ክፍሎች እንደሚያሳድገው ዶ/ር ታምሩ አመላክተዋል። የትምህርት ክፍሎችን ፍላጎት ከመለየት አንስቶ የየሥርዓተ ትምህርት (curriculum) ቀረጻና ትችት እንዲሁም የሰው ኃይልና ግብዓት የማሟላት ሥራዎች በጥንቃቄ መከናወናቸውንም በማከል አስረድተዋል።

    የመማር ማስተማር ሂደቱን ውጤታማ ለማድረግ የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ከሀገር ውስጥና ከውጭ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር የእውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግር ስምምነት ሰነድ መፈራረሙንም ዶ/ር ታምሩ ገልጸዋል። የመምህራን እጥረት እንዳይከሰት ረዳት ፕሮፈሰርና ከዚያ በላይ የትምህርት ደረጃ ያላቸው 73 የውጭና 43 የሀገር ውስጥ መምህራን ቅጥር መፈጸሙንም አስታውቀዋል።

    ለመማር ማስተማር ሂደት አጋዥ የሆኑ በተለይ ለኢንጅነሪግና ለተፈጥሮ ሳይንስ ቤተ-ሙከራና ቤተ-መጽሐፍት ከ100 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ በማድረግ መደራጀቱን ገልጸዋል። ይህም ጥራቱን የጠበቀ ትምህርት ለማድረስ እገዛ ከማድረግ ባለፈ ከዚህ ቀደም ዩኒቨርሲቲው ለተለያዩ የተግባር ትምህርቶች ወደ ሌሎች አካባቢዎች ተማሪዎችን በመውሰድ የሚያወጣውን ውጭ እንደሚያስቀር አስረድተዋል።

    ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ የልህቀት ማዕከል (Center of Excellence) አቋቁሞ ከኢትዮጵያ ምርጥ አምስት እንዲሁም ከአፍሪካ ምርጥ 10 ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ አንዱ ለመሆን እየሠራ እንደሚገኝ የተናገሩት ደግሞ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር ጫላ ዋታ ናቸው።

    በትምህርት ሥርዓቱ ውስጥ የገዳ ሥርዓት እንዲካተት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ግንባር ቀደሚ ሚናውን ከመወጣት ባለፈ በዩኒቨርሲቲው ከኮመን ኮርስ (common course) እስከ ሦስተኛ ዲግሪ ድረስ የገዳ ሥርዓት ትምህርት እየተሰጠ እንደሚገኝ አብራርተዋል።

    “ዩኒቨርሲቲው በስሩ ባሉት ስምንት ኮሌጆችና በአንድ ኢንስትቲዩት ከ17 ሺህ በላይ ተማሪዎችን እያስተማረ ይገኛል” ብለዋል ዶ/ር ጫላ።

    ምንም እንኳን በኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ስርጭት ምክንያት መደበኛ የመማር ማስተማር ሂደቱ ለጊዜው ቢቆምም በቀጣይ ዓመታት የተማሪዎችን ቁጥር በእጥፍ ለማሳደግ እየተሠራ እንደሚገኝ ከፕሬዝዳንቱ ገለፃ ለማወቅ ተችሏል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን

    ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ እና አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በአጠቃላይ ከ3 ሺህ በላይ ተማሪዎችን አስመረቁ

    ዲላ/አርባ ምንጭ (ኢዜአ/አ.ም.ዩ) – ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት መረሃ ግብሮች ያሰለጠናቸውን 1,043 ተማሪዎችን ነሐሴ 30 ቀን 2012 ዓ.ም. አስመረቀ።

    በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጫላ ዋታ እንደገለጹት ከተመራቂዎቹ መካከል 283 በመጀመሪያና ሁለተኛ ዲግሪ ትምህርታቸውን የተከታተሉ ናቸው። ቀሪዎቹ በምስክር ወረቀት የተመረቁ መሆኑን አስረድተዋል።

    ተመራቂዎቹ ትምህርታቸውን በበይነ መረብ ቴክኖሎጂ አማካኝነት ሲከታተሉ እንደቆዩ አመልክተው፥ በተለይ የሁለተኛ ዲግሪ ተመራቂዎች የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ከመከሰቱ በፊት የክፍል ትምህርታቸውን ማጠናቀቃቸውን አስታውቀዋል።

    ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ሥራው በተጓዳኝ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን መከላከልን ጨምሮ በተለያዩ የማኅበረሰብ አገልግሎቶች ውጤታማ ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝም ዶ/ር ጫላ ገልጸዋል።

    የዩኒቨርሲቲው የቦርድ አባል አቶ ኡዴሳ ክዮላ በበኩላቸው፥ ተመራቂዎቹ በቀጣይ በሚሰማሩበተ የሥራ መስክ ሀገርና ሕዝብ የሚጠብቅባቸውን ኃላፊነት በታማኝነትና ታታሪነት እንዲወጡ አሳስበዋል።

    ከተመራቂዎቹ መካከል በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ትምህርቱን የተከታተለው ቅዱስ ይገረሙ በሰጠው አስተያየት የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ያሳደረውን ተጽዕኖ ተቋቁሞ ትምህርቱን በማጠናቀቅ ለምረቃ በመብቃቱ መደሰቱን ገልጿል። በሰለጠነበት በ“ሶፍትዌር ዲዛይን” ዘርፍ በመሰማራት እራሱንና ሀገሩን ለመጥቀም እንደሚሠራ ተናግሯል።

    በሁለተኛ ዲግሪ ማኔጅመንት የትምህርት ዘርፍ የተመረቀው ዋቆ ጥላሁን በበኩሉ በትምህርት ቆይታው ያገኘውን እውቀት በመጠቀም ውጤታማ ሥራ ለማከናወን እንደሚጥር ገልጿል።

    የሦስተኛ ትውልድ ዩኒቨርሲቲ የሆነው ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የትምህርት መረሃ ግብሮች የሚያስተምራቸው ከ17 ሺህ በላይ ተማሪዎች እንዳሉት በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ወቅት ተገልጿል።

    ከተማሪዎች ምርቃት ጋር በተያያዘ፥ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ መርሃ ግብር ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ለ33ኛ ጊዜ አስመርቋል።

    ዩኒቨርሲቲው በ2012 ዓ.ም በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ መርሃ ግብር በመደበኛ፣ በክረምት፣ በሳምንት መጨረሻ እና በተከታታይና ርቀት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ 2,326 ተማሪዎች ቅዳሜ ነሐሴ 30/2012 ዓ/ም በተመሳሳይ ዕለት አስመርቋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደገለጹት፥ ዩኒቨርሲቲው በስድስት የተለያዩ ካምፓሶች በ76 የመጀመሪያ ዲግሪ፣ በ99 የ2ኛ ዲግሪ እና በ21 የ3ኛ ዲግሪ መርሀግብሮች በአጠቃላይ ከ36 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በመደበኛና መደበኛ ባልሆኑ መርሀግብሮች በማስተማር ላይ ይገኛል። ተቋሙ ባለፉት 33 ዓመታት በልዩ ልዩ የምህንድስና፣ የሕክምናና የጤና፣ የግብርና፣ የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ፣ የማኅበራዊ እንዲሁም የተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ ዘርፎች 56,958 ምሩቃንን በማፍራት ለሀገሪቱ የሰው ሀብት ልማት ጉልህ አስተዋፅዖ በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

    አክለውም በ2012 የትምህርት ዘመን በ2ኛው አጋማሽ ላይ በዓለም ላይ በተከሰተው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በሁሉም ደረጃዎች በመማሪያ ክፍል ሆኖ የመማር ማስተማር ሂደት የተቋረጠ ቢሆንም፥ ዩኒቨርሲቲዎች ከሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመሆን ባደረጉት ከፍተኛ ጥረት ቴክኖሎጂን በመጠቀም የጥናትና ምርምር ሥራቸውን ሲሠሩ የቆዩ ተማሪዎች አስፈላጊውን የምረቃ መስፈርት በማጠናቀቅ ለምረቃ መብቃታቸውን ተናግረዋል። በቀጣይ ዓመታት በተከፈቱ የ2ኛ እና የ3ኛ ዲግሪ መርሀግብሮች ላይ የማጠናከር ሥራ የሚሠራ ሲሆን፥ ዩኒቨርሲቲው በ2013 የትምህርት ዘመን በዩኒቨርሲቲው ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በ3ኛ ዲግሪ የሚያስመርቅ መሆኑን ባቀረቡት ሪፖርት ጠቁመዋል።

    የዕለቱ የክብር እንግዳ የጋሞ ዞን አስተዳዳሪና የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ እንደተናገሩት፥ የመማር ግቡ ከግለሰብ ህይወት እስከ ሀገር ድረስ ያሉ የተለያዩ ችግሮችን በመፍታት ምቹና ተስማሚ አኗኗርን ለመፍጠር የለውጥና የዕድገት ጎዳናን መከተል ነው። በመሆኑም የዕለቱ ተመራቂዎች ሀገራችን ኢትዮጵያ ወደ ብልፅግና ማማ እንድትደርስ የበኩላችሁን ድርሻ እንድትወጡ ሲሉ አሳስበዋል። በተጨማሪም ወደ ሥራ ዓለም ሲቀላቀሉ በተሰማሩበት መስክ ሁሉ ሀገራቸውንና ሕዝባቸውን በታማኝነት እንዲያገለግሉ ጠይቀዋል። ሀገሪቱ በበርካታ ፈተናዎች ውስጥ እየተሻገረች የምትገኝ እንደመሆኗ መጠን ፈተናዎቹን በብቃት መክተን ወደ መልካም ዕድል መቀየር ይጠበቅብናል ብለዋል።

    በመጨረሻም የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝደንት ዶ/ር የቻለ ከበደ እና የሬጂስትራርና አልሙናይ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር በለጠ ይልማ የእጩ ምሩቃን መግለጫ በመስጠት አስመርቀዋል።

    በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የጋሞ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የዩኒቨርሲቲው ሥራ አመራር ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ በክብር እንግድነት፣ የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝደንት እንዲሁም የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ከፍተኛ አመራሮችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እና አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ (አ.ም.ዩ)

    ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ እና አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን አስመረቁ

    Anonymous
    Inactive

    በኢትዮጵያ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ የታሪክ ዳራ፥ በእኩልነት ላይ የተመሠረተች ሀገር ለመፍጠር የተደረጉ ሙከራዎች፣
    ያጋጠሙን የታሪክ ፈተናዎችና ያመለጡን ዕድሎች በብሔራዊ መግባባት መነፅር ሲታይ

    መረራ ጉዲና (ፕሮፌሰር)
    ለብሔራዊ መግባባት ውይይት የቀረበ ጥናት
    ነሐሴ 2012

    አብዛኛዎቹ የሀገራችን የታሪክ ምሁራን የኢትዮጵያ ታሪክ ከክርስቶስ ልደት በፊት፣ በአስረኛው ምዕተ ዓመት የንግስት ሳባ እና የንጉሥ ሰለሞን ግንኙነት በሚባለው ጊዜ ይጀምራል ይላሉ። ይህ ለአንዳንዶቹ የሚታመን ታሪክ ተደርጎ የሚወሰደው፤ ለሌሎች ደግሞ ተረት እንደነበረ የሚነገረው ክስተት የማስመሰያ ትርክቱ የእስራኤል አምላክ የቀባቸው ገዥዎች ተብሎ በሺዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት ንጉሦቹ ቅቡልነትን አግኝተውበታል። በትርክቱም ሀገሪቷን እስከ 1966 ሕዝባዊ አብዮት ድረስ ያለ ብዙ ጭንቀት ገዝተውበታል።

    የዛሬይቱ ሰፊዋ ኢትዮጵያ እንደ ሕብረ ብሔራዊ የነገሥታት መንግሥት (multi-ethnic empire state) የተፈጠረችው በ2ኛው የ19ኛው ክፍለ ዘመን ግማሽ፤ የዘመነ መሳፍንት ከሚባለው ዘመን በኋላ ስለሆነና ዛሬም በጣም ሰፊ ቀውስ ውስጥ የከተተን ታሪካዊ ዳራም ከዚሁ ጊዜ ጀምሮ ስለሆነ፥ ጽሑፌም ከዘመናዊ ኢትዮጵያ መፈጠር ጋር በተፈጠሩ ችግሮች ላይ ያተኩራል።

    የዘመነ መሳፍንትን ክስተት በመለወጥ የተጀመረው የዛሬዋን ሰሜናዊ ኢትዮጵያን አንድ የማድረግ ሕልም በግማሽ ምዕተ ዓመት ውስጥ ከሦስት እጥፍ በላይ የሰፋች ኢትዮጵያን መፍጠር ችሎዋል። ይህ የታሪክ ክስተት የሦስት ምኞቶች ዉጤት ነበር። እነዚህም፡-

    1ኛ/ ተበታትና የነበረችውን የዛሬዋን ሰሜናዊ ኢትዮጵያ ሕዝቦችን ለማሰባሰብ የታለመ ምኞት፣
    2ኛ/ የኦሮሞና የሶማሌ ሕዝቦችን ጨምሮ ሰፊውን የደቡብ ክፍል የማስገበር ምኞት፣
    3ኛ/ አፍሪካን ለመቀራመት የመጡትን የአውሮፓ ሀገሮች ጋር የመፎካከር ምኞት ነበሩ።

    እነዚህን ሦስት ምኞቶች ለማሳካት የመጀመሪያ የሆነውን ሙከራ የጀመሩት እንደምታውቁት አፄ ቴዎድሮስ ነበሩ። ቴዎድሮስ ሕልሞቹን ለማሳካት ጠንካራና ሰፊ ሠራዊት ማደራጀት ነበረባቸው፤ ለዚህም ሰፊ መሬት የያዙትን ቄሶች መሬት መቀማትና ዘመናዊ መሣሪያን ከክርስቲያን አውሮፓ ለማግኘት ጥረት ማድረግ ነበር። የአዉሮፓ መሪዎችን ማሳመን ሲያቅታቸው ደግሞ ሙያው የሌላቸውን አውሮፓዊያንን ሳይቀር በቤተ መንግሥታቸው ሰብስበው ከባድ የጦር መሣሪያ ውለዱ እስከማለት ደርሰዋል። ይህም ምኞታቸዉ ይሳካ ዘንድ በነበራቸዉ የጦር መሣሪያ የአካባቢ ገዥዎችንም ለማንበርከክ ተንቀሳቅሰዋል።

    ቄሶችን ለመግፋት ያደረጉት ሙከራ እግዚአብሔርን የካዱ ንጉሥ ተብሎ ተሰባከባቸዉ። የአውሮፓውያንን ዘመናዊ መሣሪያ ለማግኘት ገደብ ያለፈ ጉጉታቸው ከእንግሊዘኞች ጋር ያለጊዜ አላተማቸው። የየአከባቢውን ገዥዎች በጉልበት ለማንበርከክ እጅና አንገት በመቁረጥ የገፉበት ሙከራ ከእንግሊዞች ጋር ለመዋጋት የቁርጥ ቀን ሲመጣ፥ የትግራይ፣ የወሎ፤ የጎጃም፣ የሸዋ፣ የጎንደር ገዥዎች ሁሉም በሚባልበት ደረጃ ካዷቸው። በአጭሩ የየአከባቢዉ ገዥዎች በእንግሊዞች እጅ መሞታቸውን ሲሰሙ ከማዘን ይልቅ ተገላገልን ያሉ ይመስላል። ለዚህም ይመስለኛል ዕውቁ የታሪክ ምሁር ፕሮፌሴር ባህሩ ዘውዴ የቴዎድሮስን ሚና በተሻለ የታሪክ ሚዛን ላይ ለማስቀመጥ ሲሞክር፥ “የተወናበዱ የለዉጥ ነቢይ” (“confused prophet of change”) ያላቸዉ።

    በዚህ የቴዎድሮስ የታሪክ ሚና ላይ ብዙ ሰው ልብ የማያደርገውን የታሪክ ማስታወሻ አስቀምጬ ልለፍ። ይኼውም ቴዎድሮስ በጊዜው ለነበሩ የአውሮፓ ኃያላን መንግሥታት በፃፉት ደብዳቤ ውስጥ፥ “አባቶቼ በሠሩት ኃጢአት ምክንያት እግዚአብሔር “ጋሎችን” በሀገሬ ላይ ለቆ፣ እነሱ ጌቶች ሆነው፣ እኛ የእስራኤል ልጆች የነሱ አሽከሮች ሆነን እንኖር ነበር። አሁን እግዚአብሔር ከትቢያ አንስቶኝ የኢትዮጵያ ንጉሥ አድርጎኛል። እናንተ ከረዳችሁኝ በጋራ እየሩሳሌምንም ነፃ ልናወጣ እንችላለን” ማለታቸዉ ነዉ (ትርጉም የኔ ነው)። እዚህ ላይ ሁለት ነገሮችን ልበል፦

    1) “ጋሎቹ” የሚባሉት በዘመነ መሳፍንት የጎንደርን ቤተ መንግሥት በበላይነት ሲቆጣጠሩ የነበሩ የየጁ ኦሮሞዎች መሆናቸውና እየሩሳሌም በጊዜው በእስላሞች እጅ የነበረች መሆንዋን ነው።
    2) ከዚህ አንጻር ማስታወስ የሚያስፈልገው ትልቁ ጉዳይ አፄ ቴዎድሮስ የብሔረሰብ (የዘር) ፖለቲካን በግልፅ የተናገሩ የመጀመሪያዉ የኢትዮጵያ መሪ መሆናቸው ነው።

    ከቴዎድሮስ ሞት በኋላ ለሦስት ዓመታት በተክለጊዮርጊስ እና ካሣ (አማቾች የነበሩ ይመስለኛል) ከተካሄደው የሥልጣን ትግል በኋላ በአሸናፊነት የወጡት አፄ ዮሐንስ (ካሣ ምርጫ) ነበሩ። አፄ ዮሐንስ ከሀገር ውስጥ ከወሎ፣ ከጎጃም፣ ከጎንደር፣ ከሸዋ ገዢዎች ጋር እየተጋጩ፥ ከውጭ ደግሞ ከጣሊያኖች፣ ከግብፆችና ከሱዳን መሐዲስቶች (ደርቡሾች ) ጋር ሲዋጉ በመጨረሻ በመሐዲስቶች እጅ ወድቋዋል።

    በአጭሩ ዮሐንስ ለትግራይ ሊሂቃን የኢትዮጵያ ማዕከል ነበርን፤ የአክሱም ሀቀኛ ወራሾች እኛ ነን የሚለውን የፖለቲካ ስሜት መፍጠር ቢችሉም፥ በኢትዮጵያ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ታሪክ ውስጥ የተለየ ሚና መጫወት አልቻሉም።

    በማያሻማ ቋንቋ፥ የዛሬዋ ኢትዮጵያ በዋናነት የተፈጠረችውና የዛሬው የታሪክ ጣጣችንም በዋናነት የተፈጠረው በአፄ ምኒልክ ነው። ምኒልክ ንጉሠ ነገሥት ዮሐንስን የሱዳን መሐዲስቶች እስኪገድሉላቸው ድረስ ከአውሮፓ መንግሥታት፥ በተለይም ከጣሊያን በገፍ ባገኙት የጦር መሣሪያ እነራስ ጎበና የመሳሰሉ የኦሮሞ የጦር መሪዎችን በመጠቀም በጊዜው ጠንካራ የሚባል ግዙፍ ሠራዊት መገንበት ችለዋል። ይህንን ግዙፍ ሠራዊትን ከዮሐንስ ጋር በመዋጋት ከማድከም ይልቅ፥ በአንድ በኩል ዮሐንስን እየገበሩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ያኔ የነበረችውን ኢትዮጵያ ሦስት እጅ እጥፍ የሆነ ሰፊ ግዛት መፍጠር ችሎዋል። በዚህም መጀመሪያ ሳይጠቀለሉ የቀሩትን የሸዋ ኦሮሞዎችን ጠቅልለው ያዙ። ከዚያ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር (እ.አ.አ) በ1876 ጉራጌን ብዙ ሕይወት ከጠየቀ ጦርነት በኋላ አስገበሩ። ብዙ ዝርዝር ውስጥ ሳይገባ የምኒልክን የመስፋፋት ጦርነቶች እንደሚከተለው ማጠቃለል ይቻላል። ይኸውም በምኒልክና ጀኔራሎቹ ብዙ የግዛት መስፋፋት ጦርነቶችን ቢወጉም ሦስቱ ወሳኝ ጦርነቶች ነበሩ።

    አንደኛው በምዕራብ በኩል በእማባቦ (ዛሬ ሆሮ ጉዱሩ በሚባለው ላይ በጎበና መሪነት እ.አ.አ በ1882 የተዋጉት ጦርነት ነበር። ይህ ጦርነት ኦሮሞን ጨምሮ የምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦችን ዕድልና የጎጃም መሪዎች ከሸዋ ጋር የነበራቸውን ፉክክር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የወሰነና የሸዋንም የበላይነት ያረጋገጠ ነበር።

    ሌላው የምኒልክ ጦርነት በአርሲ ላይ እ.አ.አ በ1886 የተደመደመዉ ነው። አርሲዎች ከሌሎች የኦሮሞ አካባቢዎች በተለየ መንገድ ለአምስት ዓመታት በጀግንነት ተዋግተዋል። በመጨረሻም በራሳቸው በምኒልክ በተመራ ጦር የአውሮፓ መሣሪያ በፈጠረው ልዩነት ሊሸንፉ ችለዋል። ተመሳሳይ የመከላከል ጦርነት እንዳይገጥማቸው ይመስላል ምኒልክ ዛሬ አለ፣ የለም የሚባለውን የአኖሌ ዓይነት የጭካኔ በትር በአርሲዎች ላይ አሳርፈዋል። እዚህ ላይ ዛሬ እየተነጋገርንበት ላለው የብሔራዊ መግባባት መሳካት፥ የለም ከሚለው አጉል ክርክር ወጥተን የትናንትናውን የታሪክ ቁስላችንን በሚያክም መልኩ እንድናስተካክል መምከርን እወዳለሁ።

    ሦስተኛው የምኒልክ ትልቁ ጦርነት አሁንም በእሳቸው የተመራውና እ.አ.አ በ1887 የተካሄደው የጨለንቆ ጦርነት ነበር። የዚህ ጦርነት ውጤት በጊዜው የሀብታሟ የሐረር ከተማ መንግሥት (the Harari city-state) ጨምሮ ምስራቅ ኢትዮጵያ ያለ ደረሰኝ ምኒልክ እጅ የገባበት ሁኔታን ፈጥሯል። ከዚህም በኋላ ከፋን፣ ወላይታን፣ ወዘተ ለመያዝ ብዙ ደም የፈሰሰባቸው ጦርነቶች ነበሩ። እንደሚባለው በእንግሊዝ ተስፋፊዎችና በምኒልክ ኢትዮጵያ መካከል የመምረጥ ዕድል የገጠማቸው የቦረና ኦሮሞዎች፥ ‘ማንን ትመርጣላችሁ?’ ሲባሉ፥ የፊታወራሪ ሀብተጊዮርጊስ ፊትን አይተው፥ የእኛኑ ፊት የሚመስለው ይሻላል ብለው በሪፈረንደም (referendum) እየሰፋ በመጣው የኢትዮጵያ መንግሥታዊ ግዛት ውስጥ የተቀላቀሉበት ሁኔታም እንዳለ ይነገራል።

    እ.አ.አ በ1889 አፄ ዮሐንስ በመሐዲስቶች ሲገደሉ፥ ኦሮሞን ጨምሮ አብዛኛው ደቡብን የተቆጣጠሩት ምኒልክ ለሰሜኑ ወንድም መሪዎች ፈረንጆች እንደሚሉት “ካሮትና ዱላን ማስመረጥ” (carrot-and-stick approach) ብቻ በቂ ነበር። የሰሜኑ መሪዎች ምርጫም በማያሻማ መንገድ ካሮት ነበር። ስለካሮቱም በግልፅ ቋንቋ ለማስቀመጥ፥ የኦሮሞ አከባቢዎችን ጨምሮ በደቡብ የተገኘውን እጅግ በጣም ሰፊ ግዛት ዉስጥ በታናሽ ወንድምነት ሹማቶችን መቀራመት ነበር።

    በብሔራዊ መግባባታችን ውይይት አንፃር በምኒልክ በተፈጠረው ሰፊ አፄያዊ ግዛት ጋር የተፈጠሩ ችግሮችን ወደ ማንሳቱ ልለፍ። አንደኛው ችግር ከላይ እንዳነሳሁት፥ በጉልበት የግዛት ፈጠራ ላይ አኖሌን የመሳሰሉ የታሪክ ጠባሳዎች መፈጠራቸው። ሁለተኛውና ዋናው ነገር ግን ከማቅናቱ ጋር የተፈጠረው የፖለቲካል ኤኮኖሚው ነው። ይህም በነፍጥ ላይ የተመሠረተዉ የፖለቲካ ኤኮኖሚ ዛሬም እያወዛገበን ያለው የነፍጠኛ ሥርዓት በሚባለው ላይ የተመሠረተዉ ነዉ። ለማቅናት የተሰማራው የፊውዳሉ ሥርዓት ሠራዊት የገባር ሕዝቦችን ነፃነት ቀምተዋል፤ መሬታቸዉን ዘርፈዋል፤ ሕዝቦችን በገዛ መሬታቸው ላይ ጭሰኛና አሽከር አድርገዋል፤ ቋንቋቸውን አፍነው በ’ስማ በለው’ ገዝቷቸዋል። በአጭሩ፥ እጅግ በጣም ዘግናኝና ጨካኝ የሆነ የፖለቲካ ሥርዓት ጭነውባቸዋል። አንዳንዱ ነፍጠኛ በሃያ ሺዎች የሚቆጠር ጋሻ መሬትም ነበረው። ወረ-ገኑ የመሳሰሉ የቤተ መንግሥት መሬቶች እጅግ በጣም ብዙ ነበሩ። እዚህ ላይ ማስታወስ የሚያስፈልገው የሰሜንና የደቡብ ኢትዮጵያ የመሬት ይዞታም በፍጹም የተለያዩ መሆናቸው ነው። አነሰም በዛ የሰሜኑ ገበሬ የዘር ግንዱን ቆጥሮ መሬት ያገኛል። መሬት አያያዙም የወል ነበር። ሌላው ቢቀር የሚገዛውም በራሱ ቋንቋ ነበር። በደቡቡ ያለው ግን የመሬት ሥርዓቱ የግል ሆኖ፥ ጭሰኝነት እጅግ የተንሠራፋበት ነበር። ሲሶ ለነጋሽ፣ ሲሶ ለቀዳሽ፣ ሲሶ ለአራሽ የሚባለው የኢትዮጵያ ነገሥታት የመሬት ፖሊሲ እጅግ በጣም ዘግናኝ በሆነ ሁኔታ ሥራ ላይ የዋለው በደቡቡ የሀገራችን ክፍል ላይ ነው።

    በ1960ዎቹ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ዘመን “መሬት ላራሹ” እና “የብሔረሰቦች እኩልነት” የተባሉ ሕዝባዊ መፈክሮች የተወለዱት ከዚሁ ጨቋኝ ሥርዓት ነበር። ዛሬ የታሪክ ክለሳ ውስጥ ብንገባም፥ በእውነቱ ከሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብራክ የወጡ ወጣቶች፥ እንዲያውም በወቅቱ ‘አማራ’ ከሚባለው ክፍል የሚበዙ ይመስለኛል፤ መፈክሮቹን በጋራ አስተጋብተዋል።

    ለማንኛውም ከብሔራዊ መግባባታችን አንፃር አንድ ነገር ግልፅ ላድርግ። ‘ነፍጠኛ’ የሚባለው ሥርዓት ገዝፎ የነበረ ሥርዓት መሆኑና፥ ይህም ሥርዓት ከደቡቡ አርሶ አደር የተሻለ ኑሮ የማይኖሩትን፥ ቢፈልጉ እንኳን የደቡቡን ገበሬ ለመዝረፍ አቅሙም ሆነ ዕድሉን ያልነበራቸውን የአማራ አርሶ አደርን አይጨምርም፤ መጨመሩም ጩቡ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ዛሬ አንዳንድ የአማራ ሊሂቃን “እኔም ነፍጠኛ ነኝ” የሚለውን መፈክር ሲያሰሙ፥ ጥቅሙ ኦሮሞን ጨምሮ የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦችን ከአማራ ሕዝብ ጋር ከማጋጨት የዘለለ የፖለቲካ ትርፍ የሚኖረው አይመስለኝም። ስለሆነም የምንችለውን ያክል ሁላችንም ከሁለቱም ጩቡዎች እንጠንቀቅ ዘንድ አደራ እላለሁ።

    ወደ ሌሎች ነጥቦች ከማለፌ በፊት በዋናናት በምኒልክ የተፈጠረችዉ ኢትዮጵያን ለማስተካከል ያቃታቸዉና መሪዎች ማለፍ ያልቻሉት የታሪክ ፈተና ምንድን ነው? የሚለውን ጥያቄ በንጽጽር እንደ ታሪክ ቁጭት ማንሳትን እወዳለሁ። አፄ ቴዎድሮስ የሞቱት እ.አ.አ በ1868 ነበር። ጃፓንን ከታላላቅ የዓለም መንግሥታት ተርታ ያሰለፏት መጅ (Meiji) የሚባሉ የንጉሣውያን ቤተሰብ ወደ ሥልጣን የተመለሱት (The Meiji Restoration) በዚሁ ዓመተ ምኅረት ነበር። የጃፓን ንጉሣዊ ቤተሰቦች በሰላሳ ዓመታት ውስጥ በኢኮኖሚ የበለፀገች ታላቋ ጃፓንን ፈጠሩ። የጃፓኖች የሀገር ፍቅር ግንባታቻውም ባዶ አልነበረም። ትዝ እስከሚለኝ ድረስ አንድ የጃፓን ወታደር ንጉሤ የጃፓንን በሁለተኛው የዓለም ጦርነት መሸነፍ አልነገሩኝም ብሎ ከሃምሳ ዓመታት በኋላ በፊሊፕንስ ይሁን፤ በኢንዲኔዢያ ጫካ ውስጥ ተገኝቷል። ለሀገር ፍቅር ሲባል እራስን በራስ ማጥፋት በሁለተኛው የዓለም ጦርነት በትናንሽ አይሮፕላኖችን የአሜሪካን መርከቦች ውሰጥ እየጠለቁ አጥፍቶ መጥፋትን የጀመሩት የጃፓን ካሚከዞች (Kamikaze) የሚበሉ ነበሩ። የኢትዮጵያ መሪዎች ግን በተመሳሳይ ጊዜ (እ.አ.አ 1868-1900) ድረስ ሀገሪቷን ከዓለም ጭራነት አላላቀቋትም። በነገራችን ላይ ጃፓንና ኢትዮጵያ በ1868 ላይ ተመሳሳይ የዕድገት ደረጃ ላይ ነበሩ።

    ሌላው ንጽጽሬና የታሪክ ቁጭታችን መሆን ያለበት፥ ታላቋ ጀርመንን የፈጠሩት ቢስማርክ (Otto von Bismarck) እና ምኒልክ የአንድ ዘመን ሰዎች ነበሩ። ምንም ይሁን ምን እነ ቢስማርክ ዓለምን ሁለት ጊዜ ጦርነት ውስጥ መክተት የቻለች ኃያሏን ጀርመን ሲፈጥሩ፥ የኢትዮጵያ ገዥዎች ግን ኋላቀር ኢትዮጵያን ትተውልን ሄደዋል። በነገራችን ላይ ሀገር ትፈርሳለች ተብሎ ስለተሰጋ፥ የምኒልክ ሞት ለሕዝብ ይፋ የሆነው ከዓመታት በኋላ ነበር ይበላል።

    በአጠቃላይ ከብሔራዊ መግባባት ፈጠራችን አንፃር መረሳት የሌለበት ቁመነገር፥ በምኒልክና ጣይቱ የተመራው የአድዋው የጋራ ድል እንኳ ያልፈቱት የሚጋጩ ሦስት አመለካከቶች ዛሬም ከእኛ ጋር መኖራቸዉ ነዉ።

    አንደኛው፥ የሀገራችን ሀገረ-መንግሥት ግንባታ አንድ የነበሩና የተበታተኑ ሕዝቦችን አንድ ላይ መልሶ ያመጣ ነዉ የሚላዉ አመላካከት (reunification)፤
    ሁለተኛው፥ በአንድ ላይ ያልነበሩ ሕዝቦችን ወደ አንድ ማምጣት ነዉ የሚለዉ አመላካከት (unification and/or expansion)፤
    ሦስተኛው፥ ነፃ ሕዝቦችን ጨፍልቆ በኃይል ማቅናት ነዉ የሚላዉ አመላካከት (colonial thesis) ናቸው። የበለጠ ግልፅ ለማድረግ፥ የኢትዮጵያ አንድነት አጥባቂዎች ነን የሚሉ በዋናነት የምኒልክን ኃጢአቶች አይቀበሉም። እንደሚሉት እምዬ ምኒልክ በዓለም ከተደረጉት የሀገር ግንባታዎች ምን የተለየ ነገር ሠራ የሚለውን ሐሳብ ያራምዳሉ። ከዚያም አልፈዉ ምኒልክ የሠራዉ ሥራ ተለያይተዉ የነበሩትን የኢትዮጵያ ግዛቶችን መመለሰ ነበር ይላሉ። በአንፃሩ የኢትዮጵያ አንድነትን የማያጠብቁ ብሔረተኞች ደግሞ የአቶ ሌንጮ ለታን አባባል ለመጠቀም (አሁን አቋማቸዉ ያ መሆኑን አላዉቅም)፥ ሲያንስ “ኢትዮጵያዊ ለመሆን እንደራደራለን ሲበዛ ደግሞ ነፃ መንግሥታትን እስከ መፍጠር ድረስ እንሄደለን” የሚሉ ናቸው። በጥቅሉ እነዚህ አመለካከቶች በፖለቲካችን ለሚጋጩ ሕልሞቻችን መሠረት የሆኑና ካልተገደቡ የሥልጣን ሕልሞች ጋር ተደምሮ የብሔራዊ መግባባት ጥረታችንን የሚያወሳስቡ አመለካከቶች መሆናቸውን በውል መገንዘብ ያስፈልጋል።

    በእነምኒልክ የተፈጠረችዉን ኢትዮጵያን ለማስተካከል የተደረጉ ሙከራዎችና ያመለጡን ዕድሎች፡-

    1) የልጅ ኢያሱ ሙከራ

    ልጅ ኢያሱ የምኒልክ ልጅ ልጅ ሲሆን፥ በእኩልነት ላይ የተመሠረተች ኢትዮጵያን ለመፍጠር ልዩ ዕድል የነበረውና ያንንም ልዩ ዕድል አውቆ ለመጠቀም ሲሞክር በወጣትነት ዕድሜው ላይ የተቀጨ መሪ ነበር። በብሔር ግንዱ ኦሮሞና አማራ የነበረ፣ በሃይማኖት ጀርባዉ ክርስቲያንና ሙስሊም የነበረ ሰዉ ነዉ። ከወሎም በመወለዱ፣ ትግራይንና ሸዋን ለማገናኘት የተሻለ ድልድይ ለመሆን ይችል ነበር። የሚገርመው ግን፥ የልጅ ኢያሱ ወንጀሎች የሚመነጩት እነዚህኑ አዎንታዊ እሴቶችን ለሀገረ-መንግሥት ግንባታ ለመጠቀም መሞከሩ ነበር። ለምሳሌ አንዳንድ የታሪክ ማስታወሻዎች እንደሚያስረዱት፥ አርሲዎች እንደልጃቸው ይመለከቱት ነበር ይባላል። ከሱማሌዎችና ከአፋሮች ጋር ጥብቅ ግንኙነት እንደነበረው በቂ የሆነ የታሪክ ማስረጃ አለ። ከጎጃሙ ራስ ኃይሉና ከወለጋው ደጃዝማች ጆቴ ቱሉ ጋር የጋብቻ ዝምድና እንደነበረው ይታወቃል። ቤተ ክርስቲያንን ለማሠራት የሚጥረውን ያክል (ለምሳሌ የቀጨኔውን መድሃኔዓለምን እሱ ነው ያሠራው ይባላል) መስግዶችን ያሠራ ነበር። ከሥልጣን ላወረዱት የሸዋ ሊሂቃን ግን፤ አንዱና ትልቁ የልጅ ኢያሱ ወንጀል መስጊዶችን ማሠራቱ ነበር። የመጨረሻው ትልቁ ወንጀል ደግሞ ኢትዮጵያን ለመቀራመት ያንዣበቡ የቅኝ ገዥ ኃይሎች ከሰሜንና ምስራቅ ጣሊያን፣ በምዕራብ፣ በደቡብና በምስራቅ እንግሊዝ፣ በምስራቅ ፈረንሳይ የሦስትዮሽ ስምምነት (tripartite treaty) የሚባለውን እ.አ.አ በ1903 ፈርሞ የምኒልክን ሞት ይጠብቁ ከነበሩት መራቅና በአንደኛው የዓለም ጦርነት በአከባቢያችን ግዛት ካልነበራቸው ከነጀርመንና ቱርክ ጋር ለመደጋገፍ መሞከሩ ነበር።

    በጥቅሉ ከሁሉም በላይ ወንጀሎቹ ሰፊዋን ኢትዮጵያን የፈጠርን እኛ ነን የሚሉትን የሸዋ ልሂቃንን መጋፋቱ ነበር። በግልፅ ቋንቋ ለማስቀመጥ፥ የኢያሱ ወንጀሎች የሸዋ ልጅ አለመሆኑ (የኢያሱ አባት ወሎ ነው)፣ ሐቀኛ የክርስቲያን ልጅ አለመሆኑ (አባቱ የግድ ክርስቲያን ከመሆናቸው በፊት መሐመድ ዓሊ ነበሩና) እንዲሁም የአውሮፓ የቅኝ ገዥ ኃይሎችን ማስቀየሙ ናቸው።

    እ.አ.አ በ1916 በመስቀል ቀን ኢያሱን ለማውረድ ሁሉም መሣሪያዎቻቸውን ይዘው ተሰለፉ። ቄሶቹ ኢያሱ ሐቀኛ የክርስቲያን ልጅ አይደለም በማለት በማውገዝ፣ የሸዋ ሊሂቃን ሠራዊታቸውን በመሳለፍ፣ የአውሮፓዊያኑ መንግሥታት ምክርና ጥበባቸውን ይዘው ተሰለፉ። የአውሮፓዊያኑ ጥበብ የሚገርም ነበር፤ ኢያሱ በኢትዮጵያ ባንዲራ ላይ የእስልምና ምልክት የሆነውን ግማሽ ጨረቃ ለጥፎ ለቱርኮች ዲፕሎማት ሲሰጥ የሚያሳይ ፎቶ ሾፕ የሆነ ሥዕል (ፎቶ ሾፕም፣ የባንድራ ፖለቲካም በልጅ ኢያሱ ዘመንም ነበር) መፈንቅለ መንግሥት እንድያከሄዱ የሸዋ ሊሂቃንን መርዳት ነበር። እዚህ ላይ ለታሪክ ትዝብት አንድ ነገር ልብ በሉልኝ። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያን ፖለቲካ ሳስተምር፥ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ችግሮቻችንን በሚመለከት ፈተናም ፈትኜበታለሁ፤ የሸዋው ጦር መሪ የነበሩት ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴ የመፈንቅለ መንግሥቱም መሪ ነበሩ፤ ልጅ ኢያሱን ሲያወርዱ ባስተላለፉት መልዕክት ውስጥ የሚከተለው ይገኝበታል።

    “He claims that he eats flesh of cattle slain by Muslims in order to extend frontiers and to win hearts. But these Somali and Muslims have already been brought to heel [and do not need such diplomacy]”

    በጥሬው ሲተረጎም፥ ግዛትን ለማስፋፋትና ልቦችን ለመሳብ ብዬ በሙስሊም የታረደውን የከብት ሥጋ እባላለሁ ይላል። ነገር ግን እነዚህን ሱማሌዎችና ሙስሊሞችን ቀድሞውኑ ስላንበረከክን እንዲህ ዓይነቱ ዲፕሎማሲ አያስፈልጋቸውም።

    ይህንን የሀብተጊዮርጊስን ንግግር በሚመለከት ሰፊውን ትንተና ለናንተ ትቼ፥ በዚህ ዓይነት የተዛባ አመለካከት ላይ የተገነባችውን ኢትዮጵያን አስተካክሎ በሰፊ መሠረት ላይ የተገነባችውን ኢትዮጵያን ለመፍጠር የተደረገው የመጀመሪያ ሙከራ፥ ልጅ ኢያሱን ለሥልጣን ተብሎ በተጠነሰሰው ሤራ መውረዱን እንዳትረሱት አደራ ማለት እፈልጋለሁ። ያመለጠንን ዕድል ትርጉም ግን ለታሪክ መተውን አመርጣለሁ።

    2) ኢያሱን በወሳኝነት የተኩት ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ

    የሀገራችንን ሀገረ-መንግሥት ግንባታን በተሻለ መሠረት ላይ ለመገንባት ረጅም ጊዜ (ለ60 ዓመታት ገደማ አገሪቷን መርተዋል) በልጅነታቸው የተሻለ የፈረንጅ ዕውቀት የቀመሱና ከማንም የበለጠ ተደጋጋሚ ዕድል ያገኙ ነበሩ። ነገር ግን በእኔ ግምት ታሪክ የሰጣቸዉን ዕድል አልተጠቃሙበትም። ንጉሥ ኃይለ ሥላሴን የተለያዩ ሰዎች በተለያዩ የታሪክ ሚዛን ላይ ቢያስቀጣቸውምና እኔም ቢሆን በዘመናዊ ትምህርትና በመሳሰሉት ላይ የነበራቸውን አሻራ ቀላል ነው ብዬ ባላስብም፥ ንጉሡ ሕይወት ዘመናቸውን በሙሉ የግል ዝናንና ሥልጣንን ማዕከል ማድረጋቸው ኢትዮጵያዉያንን የ20ኛው ክፍለ ዘመን ሕዝቦች ማድረግ አልተቻላቸውም። ስለዘር ግንዳቸው ሀሜቱ እንዳለ ሆኖ፥ ከኢያሱ በተሻለ ደረጃ ኦሮሞም፣ ጉራጌም አማራም ነበሩ። ይህንን ስረ ግንድ አልተጠቀሙም። በተለይ ኦሮሞ ከሚባል ሕዝብ ሲሸሹ እንደኖሩ ብዙ ማስረጃዎች አሉ። ለማንኛዉም፤ አንድንድ ወሳኝ ነገሮችን እንመልከት።

    አምቦ 2ኛ ደረጃ ተማሪ በነበርኩበት ጊዜ የሰማሁት ይመስለኛል፤ አንድ ጋዜጠኛ ካነበቡት መጽሐፍት ዉስጥ የትኛውን እንደሚያደንቁ ሲጠይቃቸው፥ ቀልባቸውን በጣም የሳበውና ብዙ ጊዜ ደጋግመው ያነበቡት በኒኮሎ ማኪያቬሊ (Niccolò Machiavelli) የተፃፈውን “The Prince” የተባለውን እንደነበረ ትዝ ይለኛል። ንጉሡ አብዘኛዉን የሕይወት ዘመናቸዉን የተመሩት በማኪያቬሊ ምክር ነበር ብዬ እጠረጥራለሁ። በማክያቬሊ ትምህርት በመመራትም የሥልጣን ተቀናቃኞቻቸውን አንድ በአንድ አስወግደው ከአስራ አራት ዓመታት በኋላ እ.አ.አ በ1930 ጥቁር ማክያቬሊ ፈላጭ ቆራጭ ንጉሥ ሆነው ወጡ።

    እንደ ሀብተጊዮርጊስ ዓይነቱን እግዚአብሔር በጊዜ ሲገላገልላቸው፣ እንደ ጎንደሩ ራስ ጉግሳና ባለቤታቸው ንግስት ዘዉድቱን ያስወገዱበት የፖለቲካ ጥበብ፣ በጊዜው በርግጥም አስደናቂ ነበር። ይህ የንጉሡ ጥበብ፤ አርባ ዓመታትን ቆጥራ የአድዋን ሽንፈት ለመበቀል የመጣቸውን ጣሊያንን ለመከላከል አልረዳም። መንግሥታቸዉንም፤ ሀገሪቷንም ለክፉ ቀን አላዘጋጁም።

    አድዋ ላይ ታሪካዊ ድል ያስገኙ ጀግኖችም የሉም። አንድ ለታሪክ የተረፉት ደጀዝማች ባልቻ ሣፎም በንጉሡ ዉሰኔ እስር ቤት ነበሩ። እዚህም ላይ አንድ የታሪክ ትዝብት አስቀምጬ ማለፍ እፈልጋለሁ። ኃይለ ሥላሴ ለሥልጣናቸዉ ብሎ የገፏቸው ብዙ የአከባቢ መሪዎች፥ ከትግራዩ ደጃዝማች ኃይለሥላሴ ጉግሳ ጀምሮ የጎንደር፣ የጎጃም፣ የሸዋ፣ የጅማ፣ የወለጋ ገዥዎች የጣሊያን ባንዳ ሆኑ። ከሚታወቁት ውስጥ ለታሪክ ‘ተፈሪ ሌላ፣ ሀገር ሌላ’ ብለው ሲዋጉ የሞቱት ደጃዝማች ባልቻ ብቻ ነበሩ። በንጉሡ ስህተት ሀገሪቷ ውድ ዋጋ ከፍላለች። ለዚህ ነው ጠቅላይ ሚኒስቴሩን ጨምሮ የብልጽግና ፓርቲ ባለሥልጣናት ጠዋትና ማታ ባንዳ፣ ባንዳ ሲሉ፥ ግብፅ ሱዳንን ይዛ የምር ከመጣች ሰው ያላሰበውን አሳስበው ለኪሳራ እንዳይዳርጉን የሚፈራው።

    ያም ሆነ ይህ፥ ኃይለ ሥላሴ ለጦርነት ያላዘጋጇትን ሀገር በክፉ ቀን ጥለው ሸሹ። ሐረርጌ ላይም የጂቡቲን ባቡር ሲሳፈሩ ከጦር ሜዳ መሸሻቸውን ለመሸፈን፥ ‘የት ይሄደሉ?’ ብሎ ለጠያቀቸዉ የፈንሳይ ጋዜጠኛ፡ “Je ne suis pas né soldat” (“ወታደር አይደለሁም”) ብለው ያለፉት። ለሳቸዉም ፍትሃዊ ለመሆን፥ የአውሮፓ ዲፕሎማቶች ቢክዷቸውም በዓለም መንግሥታት ማኅበር ላይ የሚያስመካ ሥራ ሠርተዋል። ሆኖም ከጦር ሜዳ የመሸሻቸው ጉዳይ እስከ መንግሥታቸው ፍፃሜ ድረስ እንደ ጥቁር ነጥብ ስትከታላቸዉ ኖራለች። የአርበኞችም ሆነ የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ዋናው የተቃውሞ መፈክርም ይህች የሽሸት ጉዳይ ነበረች። ከጣሊያን ወረራ በኋላም ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ በሁለት መሠረታዊ ነገሮች ምክንያት፥ ጋዜጣቸውን “አዲስ ዘመን” ብለው እንደሰየሙ፥ በእርግጥም አዲስ ዘመን፤ ለአዲስቷ ኢትዮጵያ ይፈጠራሉ ብሎ የጠበቁ ብዙ መሆናቸውን ብሎ መገመት አስቸጋሪ አይመስለኝም።

    ለአምስት ዓመታት በእንግሊዝ ሀገር በስደት ሲኖሩ ስለራሳቸው ስህተትም ሆነ የሰለጠነው ዓለም ንጉሦች እንዴት ሕዝቦቻቸውን እንደሚመሩና በዚያም ምክንያት በሕዝቦቻቸው ዘንድ ተከብረው እንዴት እንደሚኖሩ ተምረዋል ብሎ መጠበቅ ይቻል ነበር። ከሁሉም በላይ በጣሊያን ወረራ ምክንያት እሳቸውንም ሆነ ሀገራቸውን ከገጠመው ውርደትና ኪሳራ ይማራሉ ተብሎ ይጠበቅም ነበር። ከሁሉም አልተማሩም። በባሰ ሁኔታና ፍጥነት ወደ ድሮአቸው ተመለሱ። ለዓቢይነት፥ አስተዳደራቸውን የተቃወሙ የራያ ገበሬዎችን (ቀዳማይ ወያኔ የሚባለዉ ነዉ) ከየመን በመጡ የእንግሊዝ አይሮፕላኖች አስደበደቡ። የሪፐብሊካን አስተሳሰብ ነበራቸው የሚባሉትን አርበኛ ደጃዝማች ታከለን (ደጃዝማች ታከለ ወልደሀዋርያት) አሰሩ። እኚህ ሰው ከተደጋጋሚ እስር በኋላ በመጨረሻም ሊይዟቸው ከተላኩ የንጉሡ ወታደሮች ጋር ሲዋጉ ሞቱ። ሌላው ስመጥር አርበኛ የነበሩ በላይ ዘለቀንም ያለርህራሄ ሰቀሉ።

    የአምባሳደር ብርሃኑ ድንቄ ግልፅ ደብዳቤ እንኳን (አምባሳደር ብርሃኑ፤ በአሜሪካ አምባሳደር የነበሩና ንጉሡ የገፉበት መንገድ ዉሎ አድሮ ንጉሡንም ሆነ ሀገሪቷን ለዉርደት እንደሚያበቃ የመጀመሪያ የማስጠንቃቂያ ደወል በአደባባይ የሰጡ ባለስልጣን ነበሩ) አሠራራቸውን አላስለወጧቸውም።

    በፖለቲካ ሥርዓታቸው ላይ በተከታታይ ቦንቦች ፈነዱ። የመጀመሪያዉ ትልቁ ቦንብ በራሳቸው ቤተ መንግሥት ውስጥ የፈነዳው የነመንግሥቱ ንዋይ ያውም የእሳቸውን ክብርና ሞገስ ለመጠበቅ ከፈጠሩት የክብር ዘበኛ ጦር ነበር። ንጉሡ ከክስተቱ ከመማር ይልቅ ጀኔራል መንግሥቱ ንዋይን በሞት ቀጡ፤ የታናሽ ወንድማቸውን ሬሳ እኔን ያየህ ተቀጣ በሚመስል መንገድ በስቅላት ቀጡ። የበሉበትን [ወጭት] ሰባሪዎች ናቸው ብለውም በአዝማሪ አዘለፏቸው።

    ማን እንደመከራቸው ባይታወቅም ትልቁን የመንግሥታቸውን የዲፕሎማሲ ውጤትን ያበላሸውና ለትልቅ ኪሳራ ያበቃንን የኤርትራን ፌዴሬሽንን አፈረሱ። ውጤቱም ሁላችንም እንደምናውቀው የኤርትራ ነፃ አውጪ ግንባር መፈጠር ሆነ። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ኦሮሞዎች የሜጫና ቱለማ ልማት ማኅበር በመፍጠራቸው ጠገቡ ተብሎ መሪዎቹ እነ መቶ አለቃ ማሞ መዘምር ተሰቀሉ፤ ኃይለማርያም ገመዳ እስር ቤት ውስጥ በተፈፀመበት ድብዳባ ሞተ። ጀኔራል ታደሰ ብሩ ሞት ተፈርዶባቸው በአማላጅ ወደ ሐረርጌ በግዞት ተላኩ። እኔ እስከ ማውቀው ድረስ ሁሉም በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ጥያቄ አልነበራቸውም። ውጤቱ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)ን መፍጠር ሆነ። በነገራችን ላይ በእነ ኤሌሞ ቅልጡ በኦነግ ስም የመጀመሪያዋ ጥይት የተተኮሰችው ጀኔራል ታደሰ ብሩ የታሰሩበት ሥፍራ ሐራርጌ ዉስጥ ነበር። በዚሁ ጊዜ ሰፋፊ ማኅበራዊ ፍትህን የሚጠይቁ ተከታታይ ጥያቄዎችም መቅረብ ጀመሩ። እ.አ.አ በ1965 የንጉሡ ፊውዳላዊ ሥርዓት የተመሠረተበት ላይ በመሬት ላራሹ ሰልፍ ድንገተኛ የፖለቲካ ቦንብ ፈነዳ። ከአራት ዓመት በኋላ ደግሞ እስከዛሬ ኢትዮጵያን እያመሰ ያለው በእነ ዋለልኝ መኮንን የብሔረሰቦች ጥያቄ ታወጀ። ይህችኛውን ንጉሡና ሥርዓቱ በቀላሉ የተመለከቷት አይመስልም። ንጉሡ የቀ.ኃ.ሥ ዩኒቨርሲቲ፥ የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ማኅበር ፕሬዝደንት የነበረውን ጥላሁን ግዛዉን በማሰገደል “ልጆቼ” ከሚሏቸው ተማሪዎች ጋር ደም መቃባት ዉስጥ ገቡ። በዚህም የታሪክ ጎማው ወደፊት እንዳይሽከረከር ጣሩ።

    አሳዛኙ ጉዳይ መካሪዎቻቸውም ሆኑ እሳቸው አስተዳደራቸው ለሃያኛዉ ክፍለ ዘመን የማይመጥን መሆኑን፣ በጣም እወዳታለሁ የሚሏትም ኢትዮጵያ በታሪክ ፍራሽ ላይ ተኝታ የምትሸሞነሞን ሀገር መሆኗን አልተረዱም። የኤርትራ ግንባሮች ጥይትም ከረጅም ዘመን እንቅልፋቸው አላነቋቸውም። የባሌና የጎጃም ሕዝብ አመፅም አልቀሰቀሳቸውም። ለዓመታት የቆየው የተማሪዎች ንቅናቄ ጩኸትም አላነቃቸውም። ከኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ በቀጥታ የወጡ የመኢሶንና የኢህአፓ የሶሻሊስት አብዮት ደወልም አላነቃቸውም። በመጨረሻም በመቶ ሺዎች የሚቆጠረው የወሎ ሕዝብ እልቂት እንኳን ከእንቅልፋቸዉ አላበነናቸውም።

    በነገራችን ላይ፥ ብልጡ ደርግ በጠዋቱ ሊያወርዳቸው፣ ማታ ያሳየው የወሎ ሕዝብ እልቂት፥ በአንድ በኩል የንጉሡ ውሻ በጮማ ሥጋ ሲጫወት፣ በሌላ በኩል ደግሞ በረሃብ በተረፈረፈ ሕዝብ ውስጥ ሕፃን ልጅ የሞተች እናቷን ጡት ስታጠባ የሚያሳየዉን የጆናታን ዲምበልቢ (Jonathan Dimbleby, “The Unknown Famine”) ፊልም ነበር። ያንን ፊልም ደርግ በቅድሚያ ንጉሡና የኢትዮጵያ ሕዝብን እንዲያዩ ስለጋበዘ ቴሌቪዥን ያልነበረን የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በስድስት ኪሎና አራት ኪሎ አካባቢዎች ያሉትን ቡና ቤቶችን አጣብበን ስንመለከት ነበር። የንጉሡ ደጋፊዎች እንኳ ጃኖሆይ እንዲህ ጨካኝ ነበሩ እንዴ? የሚሉትን ይዘን ወደ ዶርማችን እንደገባን ትዝ ይለኛል። ምናልባት ከእንቅልፋቸው የነቁት በማግስቱ የደርግ አባላቱ በኩምቢ ቮልስዋገን ከቤተ መንግሥታቸው ወደ አራተኛ ክፍለ ጦር ሲወስዷቸው በሠሩባቸው ድራማ ይመስለኛል። ብልጣብልጦቹ ደርጎች የተጠቀሙት ቮልስ መጀመሪያ መስኮቷ ዝግ ነበር ይባላል።

    ንጉሡ ከውጭ ብዙ ሰው ሲጮህ ተመልክተው፥ “እናንተ ልጆች የሚወደን ሕዝባችን ንጉሤን የት እየወሰዳችሁ ነው እያለ ነዉ” ሲሉ፥ ብልጦቹ ደርጎችም መስኮቱን ከፍተው የሕዝቡን ድምፅ ሲያሰሟቸው ጩኼቱ “ተፈሪ ሌባ፤ ተፈሪ ሌባ” የሚለውን ሰምተው፥ “አይ ኢትዮጵያ ይኼን ያክል በድዬሻለሁ እንዴ?” አሉ ይባላል። በዚህ ሽኝታቸው ድሮ ቤተ ክርስቲያን ሲሄዱ ዳቦ የሚጥሉላት ለማኝ ዳቦዋን ስትጠብቅ፥ ‘ንጉሡ ወረዱ፤ ንጉሡ ወረዱ’ ሲባል ሰምታ፥ ‘ለዚህ ያበቃኸኝ አንተ ነህ!’ ብላ በቮልሷ አቅጣጫ የወረወረችው ዳቦ ብቻ ነበር ይባላል። የንጉሡ ሬሳም ከ17 ዓመታት በኋላ ከመንግሥቱ ኃይለማርያም ሽንት ቤት ሥር ተቆፍሮ እንደተገኘ ይታወቃል። እዚህ ላይ ልብ አድርገን ማለፍ ያለብን የፖለቲካ ቁም ነገር ለ60 ዓመታት ገደማ (የአምስት ዓመቱ የጣሊያን ወረራ እንዳለ ሆኖ) በፈላጭ ቆራጭነት ኢትዮጵያን ሲገዙ የሀገረ መንግሥታቸው ግንባታ ፕሮጀክት በአጉል ምክርም ይሁን በራሳቸው ገታራ አቋም ከሽፎ ሽኝታቸው በለማኟ ዳቦ፣ ቀብራቸው ደግሞ በአሳደጓቸው ወታደሮች ሽንት ቤት ሥር መሆኑ ነው።

    3) አብዮቱ እና የደርግ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ሙከራ

    አዲስቷን ኢትዮጵያን ለመፍጠር ሕዝባዊ አብዮቱ ልዩ ዕድል ፈጥሮ ነበር። አብዮቱ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ማኅበረሰቦች የመጡ የአዲሱ ትዉልድ ምሁራን ድጋፍና ተሳትፎ ነበረው። እንደ አብዮቱ መሪ ወደፊት የመጣውን መንግሥቱ ኃይለማርያምም ‘ቪቫ መንግሥቱ፣ ቪቫ መንግሥቱ!’ ብለን ተቀብለን ነበር።

    የኢትዮጵያ አብዮትን አብዮት ያደረገው የጭሰኝነት ሥርዓትን ያስወገደውና የደርግ እርምጃ (ውለታው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ንቅናቄ ቢሆንም) እስከዛሬ በኢትዮጵያ የሕዝቦች የትግል ታሪክ ውስጥ ልዩ ሥፍራ አለው ብዬ ባምንም፥ ነገሮችን በቶሎ የሚያዩ ወጣቶች “ተፈሪ ማረኝ፤ የደርጉ ነገር አላማረኝ ” ማለት የጀመሩት ብዙዉም ሳይቆዩ ነበር። በአጭሩ ለማስቀመጥ፥ የደርግ የሥልጣን ፍቅር፣ የመኢሶንና የኢህአፓ አሳዛኝ ክፍፍል፣ የኤርትራ ግንባሮችና የህወሓት የተናጠል የፖለቲካ ፕሮጀክቶች በአብዮቱ መፈንዳት የተፈጠረውን ልዩ ታሪካዊ ዕድል አምክኖታል።

    ደርግ መሃይምነትና የሥልጣን ፍቅር ስለተደባለቀበት፥ የሶሻሊስት አብዮቱን እንደሰው ማሰርና መግደል ወሰደው። በዚህ ሶቭዬት ህብረት ድረስ ሄዶ የሌኒን ሐውልት አይተው የመጡት ባለሥልጣኖቹ ስለሶሻሊዝም የተማርነው ከበሰበሰ ከቡርዧ ቤተ መፃሕፍት ሳይሆን ከምንጩ ከሌኒን ሀገር ነው እያሉ ተዘባበቱ። ካደሬዎቻቸው ድንቅ የሶሻሊስት ዕውቀታቸውን ከፍተኛነት ለማሰየት በሚመስል መንገድ የስታሊን ቀይ በትር ሥራ ላይ ይዋል አሉ። ደርግ የሱማሌ ወረራን፣ የኤርትራ ግንባሮችና የህወሓት እንቅስቃሴዎች በኢትዮጵያ አንድነት እንዲነግድ ልዩ ሁኔታ ስለፈጠሩለት “አብዮታዊት እናት ሀገር፥ ወይም ሞት!” አለ።

    ከኤርትራ ግንባሮች እስከ ኢህአፓ እና መኢሶን (ኢጭአት/ ኦነግን ጨምሮ ሌሎች ድርጅቶች እዚህ መሃል ናቸው) የኢትዮጵያ ሕዝቦች የአንድነትና የአብዮት ጠላቶች ሆነው ልዩ ልዩ ስሞች ተለጣፈበቸው። በአጭሩ የኢህአፓና መኢሶን መከፋፈልም ደርግን ብቻኛ የሀገር አንድነትና የአብዮት ተወካይ አደረገው። ሌሎች ዝርዝሮችን ትቼ ለኢትዮጵያ አንድነትና አብዮት ግንባታ ወሳኝ የሆኑ እርምጃዎችን ላንሳ።

    የደርግ የመጀመሪያው ሊቀ መንበር አማን አንዶም የሚባሉ ኤርትራዊ ጀኔራል ነበሩ። የደርግ ሊቀ መንበር ተብሎ ከደርግ ውጭ የተመረጠትም ለኢትዮጵያ አንድነት ብሎ እስከ ሞቃዲሾ ድረስ ሄዶ ካልተዋጋሁ ብሎ ንጉሡን ያስቸገሩ መኮንን ስለነበሩ ነዉ። በወታደሮቹ ዘንድም ተወዳጅ ስለነበረ በራሳቸው በደርግ አባሎቹ ጥያቄ መጀመሪያ መከላከያ ሚኒስቴር፣ ከዚያም ከደርግ ውጭ የደርግ ሊቀ መንበር የሆነው የተመረጡትና በአደባባይ እስከሚታወቀውም በኢትዮጵያ አንደነት ላይም (መቼም በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ልዩ ፍቅር አለን የሚሉ ብዙ ቢኖሩም፥ ፍቅራቸውን የሚለካልን መሣሪያ በሜዲካል ሳይንስ እስካሁን አልተፈጠረልንም) ምንም ዓይነት ጥያቄ ያልነበራቸውና የኤርትራን ችግር በሰላም ለመፍታት አሥመራ ድረስ ሄዶ ሕዝቡን ያወያዩ ነበሩ። ለኢትዮጵያ ልዩ ፍቅር አለኝ የሚሉ እነሻለቃ መንግሥቱ ኃይለማርያም ግን ጠረጠሯቸዉ፤ በታንክ እቤታቸው ውስጥ ገደሉት። በእኔ ግምት ውጤቱ የኤርትራና የኢትዮጵያን አንድነት መግደል ነበር። በዚህም ኤርትራ የደም ምድር ሆነች። ዛሬ እንዲህ ልንሆን የፈሰሰው የሰው ደም ዋጋም ሆነ ለጠፋው ሀብትና ንብረት ሂሳብ ለፈረደበት ታሪክ መተው ይመረጣል።

    የብሔራዊ አንድነት መንግሥትን ልታመጡብኝ ብሎ መንግሥቱ ኃይለማርያም ሁለተኛውን የደርግ ሊቀ መንበር የነበሩትን ጀኔራል ተፈሪ በንቲን ከደጋፊዎቻቸው የደርግ አባላት ጋር ረሸናቸው።

    ኮሎኔል አጥናፉ አባተንም ቅይጥ ኢኮኖሚ ልታመጣብን ነው ብሎ መንግሥቱ ኃይለማርያም በፀረ-አብዮታዊነት ረሸነዉ። በነገራችን ላይ የመጨረሻ ጭንቅ ሲመጣ መንግሥቱ ኃይለማርያም የአጥናፉን ቅይጥ ኢኮኖሚ ላይ ለመንጠላጠል ሞክሮ ነበር።

    በዛሬው የኦሮሞ ፖለቲካ ውስጥ ልዩ ሥፍራ ያላቸው ጀኔራል ታደሰ ብሩ ለሁለተኛ ጊዜ ሞት ተፈርዶባቸው ተረሸኑ። እኔ መከታተል እስከቻልኩ ድረስ ታደሰ ብሩ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ፍጹም ጥያቄ ያልነበራቸው፤ ለኢትዮጵያ ብሎ ከሰላሌ ጫካ እሰካ ሞቃዲሾ ድረስ ተወስደው የታሰሩ እንግሊዞች ኢትዮጵያን ነፃ እናወጣለን ብለው ሲመጡ ከነሱ ጋር እየተዋጉ የመጡ አርበኛ ነበሩ። ከተራ ወታደርነት እስከ ጀኔራል ማዕረግ ድረስ ሀገራቸውን ያገለገሉም ነበሩ። እግር ጥሏቸው አብዮቱ ውስጥ የገቡት መንግሥቱ ኃይለማርያም ያላርህራሄ ገደሏቸዉ። በነገራችን ላይ ከጀኔራል ታደሰ ብሩ ጋር በፀረ አንድነት ክስ የተገደለ፣ ብዙ ሰው የማያስታውሰው መለስ ተክሌ የሚባል በቀ.ኃ.ሥ ዩኒቨርሲቲ ከተማሪ መሪዎች አንዱ የሆነ የትግራይ ተወላጅ ነበር (በጊዜዉ ከነበረዉ አቋም ተነስቼ፥ ይህ ሰው ቢቆይ ኖሮ የትኛው ድርጅት ውስጥ ሊገባ እንደሚችል ዶክተር አረጋዊን ደግሜ መጠየቄን አስታውሳለሁ)። ይህ ሰዉ ሌላ ተከታይ ቢያጣ ለሩብ ምዕተ ዓመት አከባቢ የምኒልክ ቤተ መንግሥትን ተቆጣጥሮ በፈላጭ ቆራጭነት ሀገሪቷን የገዛው ለገሠ ዜናዊ ስሙን አንስቶ ትግራይ በረሃ ገብቷል። ይህም ደርግ በኢትዮጵያ አንድነት ስም ያመጣብን የታሪክ ዕዳ ነው።

    በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ምንም ዓይነት ጥያቄ እንዳልነበራቸው በተሻለ የማውቃቸውን የመኢሶን መሪዎችን ላንሳ። ለሥልጣን ተብሎ በደርግና ብዙ የፖለቲካ ተቀናቃኞቹ ዘንድ እንደ ኦሮሞ ድርጅት፥ በኦሮሞ ደግሞ እንደነፍጠኛ ድርጅት የሚታየው መኢሶን በዘመኑ በየትኛውም ሚዛን የተሻለ ትምህርት የነበራቸው መሪዎች ነበሩት፤ በስብጥራቸውም ኤርትራዊ የዘር ግንድ አላቸው ከሚባሉት ኅሩይ ተድላ እና አበራ የማነአብ እስከ ሲዳማው እሼቱ አራርሶ የነበሩበት ነው። ሽኩሪ የሚባል አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አብረን የነበርነው ልጅ በስተቀር ሰፊ ተሳትፎ እንደልነበራቸዉ የማዉቀዉ የሱማሌ ምሁራንን ብቻ ነበር።

    የመጀመሪያዉ የመኢሶን ሊቀ መንበር የሰሜን ሸዋ አማራ ከሚባለው የተወለዱ፥ ዶ/ር ወርቁ ፈረደ፣ ሁለተኛው ኃይሌ ፊዳ፣ ሦስተኛው የወሎ አማራ ከሚባለው የመጡ ዶ/ር ከበደ መንገሻ ነበሩ። ሕብረ ብሔር ነን፤ ለሀገረ- መንግሥት ግንባታው የተሻለ ግንዛቤም እዉቀትም አለን ለሚሉ የመኢሶን ምሁራንም ደርጎች ርህራሄ አላደረጉም። በተለይ የመጀመሪያው የኦሮሞ የምሁር ትዉልድ የሚባሉት ኃይሌ ፊዳን ጨምሮ አብዱላህ ዩሱፍ፣ ዶ/ር ከድር መሀመድ፣ ዶ/ር ተረፈ ወልደፃዲቅ፣ ዶ/ር መኮንን ጆቴ የመሳሰሉት ሕበረ ብሔር በሚባለው መኢሶን ውስጥ አልቀዋል። በእኔ እምነት ብዙዎች ሊቀየሙኝ ቢችሉም፥ እንደስማቸው በኢትዮጵያ ምድር ሕብረ ብሔር የነበሩ ድርጅቶች መኢሶንና ኢህአፓ ብቻ ነበሩ። አላስፈላጊ ክርክር ዉስጥ ሳልገባ፥ እኔ እስከ ማምነው ድረስ ኢሠፓ የወታደሮች ፓርቲ ነበር። የኢህአዴግን ምንነት ለብልጽግና አበላት እተዋለሁ። የብልጽግናን ምንነት ደግሞ የታሪክ ፈተናዉን ሲያልፍ ብንነጋገርበት የተሻለ ይመስለኛል።

    ደርግ ሕበረ ብሔር ድርጅቶችን በቀላሉ አንድ በአንድ ቀርጥፎ በላቸው። ኢህአፓን ቁርስ አደረገ፤ መኢሶንን ምሳ አደረገ:: ብሔር ሆኖ ለመውጣት ገና ዳዴ የሚሉትን ወዝሊግንና ማሌሪድን እራት አደረጋቸው። ከደርግ ዱላ የተረፉት በደርግ አስተዋጽኦ ጭምር በተሸለ ሁኔታ ኃይል ሆነዉ የወጡት የብሔር ንቅናቄዎች ናቸው። ኢጭአት (የኢትዮጵያ ጭቁኖች አብዮታዊ ትግል) ወደ ኦነግ ተጠቃልሎ ገብቶ ዛሬ የምናውቀው ኦነግን ፈጠረ። የሱማሌ ድርጅቶች ኦብነግ ዓይነትን ፈጠሩ። የሲዳማ አርነት ንቅናቄ ቢያንስ ዋናው ክንፍ ዛሬ ሲአን (የሲዳማ አርነት ንቅናቄ) የሚለው ሆነ። አፋሮችም የአፋር ግራ ክንፍ አርዱፍ እያሉ በሕይወት ያሉ ድርጅቶች አሏቸው። በጣም የተሳካላቸው የብሔር ንቅናቄዎች በኢትዮጵያና ኤርትራ ላይ ደርግን ለሁለት ቀብረው መንግሥታት ሆኑ።

    የደረግ ዘመንን ስናጠቃልል መረሳት የሌለባቸው ሦስት ዋና ዋና ጉዳዮች፥ ለሥልጣን ብሎ ደረግ ባካሄዳቸው ጦርነቶች፡-

    የሀገረ-መንግሥት ግንባታውን የበለጠ አወሳስቦ መሄዱን፣
    ሻለቃ ዳዊት ወልደጊዮርጊስ በፃፉት መጽሐፍ በትክክል እንዳስቀመጡት፥ ደርግ ትቶት የሄደው በደም እምባ የታጠበች ሀገር መሆንዋን፣
    በሀገር አንድነት ስም ባካሄደው ትርጉም-የለሽ ጦርነት የባከነው የሀገር ሀብት ብቻ ሳይሆን በዓለም ትልቋ ወደብ-አልባ ሀገር ኢትዮጵያን ትቶ መሄዱን ነዉ።

    ደርግ ለ17 ዓመታት የተጫወተዉ የአጥፍቶ መጥፋት ፖለቲካን እንደ ኑዛዜም፣ እንደ ቁጭትም የደርግ ከፍተኛ ባለሥልጣን የነበሩት ኮሎኔል ፍስሃ ደስታ (ኮ/ል መንግሥቱ ኃይለማርምም ሆነ ሻምበል ፍቅረ ሥላሴ ወግደረስ እድፋቸውን ከታጠቡበት በጣም ይሻላል) በፃፉት መጽሐፍ ልዝጋ።

    የኢህአፓ ወጣቶችን የትግል ስሜት፣ የመኢሶን መሪዎች ዕውቀትና የእኛን የወታደሮቹን የሀገር ወዳድነት ብንጠቀምበት ኖሮ ሀገራችን እንዲህ አትሆንም ማለታቸውን እስር ቤት ሆኜ ማንበቤ ትዝ ይለኛል። ምክራቸው ለጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይም የሚሆን ይመስለኛል። በነገራችን ላይ በታሪክ አጋጣሚ ወደ አስር ወሮች ገደማ በኢህአዴግ እስር ቤት የተኛሁበት አልጋ ኮ/ል ፍስሃ ደስታ ይተኙበት እንደነበረ ሰምቻለሁ።

    4) የኢህአዴግ ዘመን የሀገረ-መንግሥት ግንባታ

    ለአራተኛ ጊዜ የሀገራችን ፖለቲካን ማሰልጠንና የተሻለ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ዕድል ያመለጠን የኢህአዴጉ ዘመን ነው (ይህ የመለስ እና የኃይለማርያም ዘመንን ይጨምራል)። የኢህአዴግ ዘመን ሌላው ቢቀር የብሔረሰቦች ጥያቄን ለሁሉም ሕዝቦች ተቀባይነት ባለው መንገድ ይመልሳል ብሎ (እኔን ጨምሮ) የጠበቁ ብዙ ናቸው። ይህም ለሀገረ-መንግሥት ግንባታ የተሻለ ዕድል ይፈጠራል ተብሎም ተገምቶ ነበር።

    ገና የሽግግር መንግሥቱ ሲመሠረት፥ የኢህአዴግ ባለሥልጣናት እንደግል ሠርጋቸው የፈለጉትን ጠርተው፣ ያልፈለጉትን በመተው የሠሩት የፖለቲካ ቲያትር ጫካ ሆነው ስደግፋቸው ከነበሩት የኢህአዴግ መሪዎች ተለየሁ። እኔም ብቻ ሳልሆን ብዙ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ጓደኞቼ በዚህ ጊዜ የተለዩዋቸዉ ይመስለኛል። ኢህአዴግ መጀመሪያ በጦርኛነት፤ ቀጥሎ ደግሞ በዘመኑ ቋንቋ የሽብርተኝነት ታርጋ እየለጠፈ ለ27 ዓመታት ሕዝብና ሀገርን አመሰ። ዝርዝር ነገሮች ውስጥ ሳልገባ፥ በኦሮሚያ እና በሱማሌ ክልሎች፤ በሲዳማ፣ በሀዲያ፤ በወላይታ፣ በጋምቤላ፣ በአፋር፣ ቁጥራቸውን የኢህአዴግ ባለሥልጣናት እንኳ የማያውቁት ሕይወት ጠፋ። የአፍሪካ መዲና የምትባለው አዲስ አበባ/ፊንፊኔም ሆነች የኢህአፓን ጠበል በቀመሱ ብአዴኖች የሚመራው የአማራ ክልልም ውሎ አድሮ ከኢህአዴግ ዱላ አልተረፉም።

    በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ርዕዮተ ዓለም (ነገርየው መሬት ላይ ሲፈተሽ፥ የአብዮታዊነትም የዴሞክራሲያዊነትም ባህርይ አልነበረውም) የተተበተበው የሞግዚት አስተዳደር እውነተኛ የፌዴራል ሥርዓት ሊሆን አልቻለም። የሕዝቦችን እራስን በራስ ማስተዳደር ጋር ምንም ግንኙነት ያልነበረው፥ ጆርጅ ኦርዌል የእንስሳት እርሻ (George Orwell, “Animal Farm”) በሚለዉ መጽሐፉ ላይ፥ ሁሉም እንስሶች እኩል ናቸው፤ አንዳንድ እንስሶች የበለጠ እኩል ናቸው “All animals are equal, but some are more equal than others” ከሚለው ያለፈ የፖለቲካ ፋይዳ አልነበረውም። ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ተብዬዎቹም ከ97ቱ በስተቀር ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መፍጠር ይቅርና ቅርጫ እንኳ ሊ ሆኑ አልቻሉም። ዉጤቱም ዴሞክራሲያዊ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ዕድል መጨናገፉ ብቻም ሳይሆን ለ27 ዓመታት ውድ የሕይወት ዋጋ ጭምር ሲያስከፍለን ኖሯል። በዚህም ምክንያት የታሪክ ጣጣችንን አስተካክለን በእኩልነት ላይ የተመሠረተ ዴሞክራሲያዊ ፌዴራሊዝም የመፍጠር ተስፋችን ሕልም ሆኖ ቀርቷል።

    5) በማምለጥ ላይ ያለ አዲስ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ ሙከራ

    አሁን እየገጠመን ያለውን የታሪክ ፈተናን ለማለፍ፥ ጨክነን በቁርጠኝኘት ብሔራዊ መግባባት ውስጥ መግባት ወይም ኢትዮጵያን እንደ ሀገረ-መንግሥት የምታበቃበት የሚጨምር ቀውስ ውስጥ መግባት ይመስለኛል። እዚህ ላይ የሌሎች ሀገሮችን ፖለቲካ በድኅረ ቅኝ ግዛት ዘመን ብቻ እንኳን በመቀኛት ብጀምር፥ ችግሮቻቸውን ለመፍታት በቁርጠኝነት የሠሩት ተሳክቶላቸዋል። ያንን ያልቻሉት ወይ ፈርሰዋል ወይም አሁንም በቀውስ ውስጥ እየዳከሩ ነዉ። ቅኝታችንን በላቲን አሜሪካ ብንጀምር፥ ቀዉስ ገጥሟቸዉ አነ አርጀንቲና፣ ቺሌ፣ ፔሩ፣ ኒካራጓ፣ ኮሎምቢያ የመሰሰሉ ሀገሮች በተለያየ ደረጃ ፖለቲካቸውን ያስተካከሉ ሀገሮች ናቸው። ከ60 ዓመታት በላይ ለልዕለ ኃያሏ አሜሪካ ሳትበገር በአሜሪካ አፍንጫ ሥር የኖረችው አስደናቂዋ ሶሻሊስት ኩባና በአሜሪካ ጣልቃ ገብነት ምክንያት አሁን በሁለት ፕሬዝዳንቶች የምትገዛዋ ሶሻሊስት ቬኔዙዌላም በዚሁ ክፍለ ዓለም ይገኛሉ። በአውሮፓ ፖርቹጋል፣ ስፓኝ፣ ግሪክ፣ ፖለቲካቸዉን ማስተካከል ችለዋል። ዩጎዚላቪያ ውድ ዋጋ ብትከፍልም ከመፍረስ አልደነችም። ሶቭዬት ህበረትና (ግማሽ አውሮፓ ነች) ቼኮዝላቫኪያ በሰላማዊ መንገድ ፈርሰዋል። በኤዥያ፥ ኔፓል የፓለቲካ ችግርዋን በብሔራዊ መግባባት ስትፈታ፥ፓኪስታን፣ ቬየትናም፣ ካምቦዲያና ላኦስ ደግሞ ችግሮቻቸውን በጦርነት ፈተዋል። አፍጋኒስታን፣ ኢራቅ፣ ሶሪያና የመን አሁንም እየቀወሱ ነው። ወደ አፍሪካችን ስንመጣ፥ ደቡብ አፍሪካና ጋና ከመሳሰሉት በስተቀር አብዘኛዎቹ በይስሙላ ምርጫ ላይ የተመሠረቱ አምባገነን መንግሥታት ሲሆኑ፥ የአፍሪካ ሕብረትም የዲክታተሮች ማኅበር (trade union of dictators) ከመሆን አላለፈም (በኢህአዴግ ጊዜ የተከሰስኩበት አንዱ ወንጀሌ የአፍሪካ መሪዎችን ተሰደብክ የሚል ነበር)። ሱማሊያና ሊቢያ ፈረንጆች የወደቁ መንግሥታት (failed states) የሚሏቸው ሲሆኑ፤ ሩዋንዳ ጊዜውን ጠብቆ የሚፈነዳ ሌላ ቦንብ የምትጠብቅ ይመስለኛል።

    በዚህ የአፍሪካ ፖለቲካ ምስቅልቅል ጉዞ ውስጥ አንዱ የሚገርመኝ ላለፉት 60 ዓመታት ፖለቲካቸውን ማስተካከል አቅቷቸው በቀውስ ሲናጡ የኖሩ ሁለት ሀገሮች፥ በተፈጥሮ ፀጋ እጅግ ሀብታሟ የኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፑቢሊክና የሦስት ሺህ ዓመታት ዕድሜ አለኝ የምትለዋ ድሃዋ ኢትዮጵያ መሆናቸው ነው።  ከንጉሡ ዘመን ጀምሮ ይህንኑ የሀገራችንን የፖለቲካ እንቆቅልሾችን የተከታተለ፣ ያጠና፣ ያስተማረና ብዙ ጽሑፎችን የፃፈበት ጆን ማርካከስ (John Markakis) የሚባል ፈረንጅ፥ የታሪክና ፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፌሴር “Ethiopia: The Last Two Frontiers” (የኢትዮጵያ፥ የመጨረሻዎቹ ሁለት ድንበሮች) ብሎ ፅፏል። ምሳ ጋብዞኝ መፅሐፉን ለዶ/ር ዓቢይ ስጥልኝ ብሎኝ፥ ዶ/ር ዓቢይ ያንብበው አያንብበው ባላውቅም፥ እሳቸውን ማግኘት ለሚችል ለኦፒድኦ ባለሥልጣን ልኬላቸው እንደነበርም አሰታዉሰለሁ። መፅሐፉ በአጭሩ የኢትዮጵያ መሪዎች የሀገረ-መንግሥት ግንባታ የንጉሦቹ ሞዴል (the Imperial model) ፣ የደርግ የሶሻሊስት ሞዴልና የኢህአዴጉ ፌዴራሊስት ሞዴል በሙሉ ከሽፈዋል ይላል። የከሸፉበትም ዋናዉ ምክንያት የባለጊዜ ገዥዎችን ሥልጣን ለማሳካት የተገፋበት መንገድ የኢትዮጵያ ሕዝቦችን እኩልነት ያላጎናፀፈና የልማት ጥማታቸውንም ያላረካ በመሆኑ ነው ይላል።

    ይህ የፈረንጅ ምሁር እንዳለው፥ ፖለቲካችንን ማሰልጠን ባለመቻላችን ሚሊየኖች ሕይወታቸውን አጥተዋል፤ ሚሊዮኖች ከቀዬያቸው ተፈናቅለዋል፤ ሚሊዮኖችም ተሰደዋል። እኔም ከላይ ባነሳሁት ከዚሁ ምሑር ዕይታ ተነስቼ ሀገራችን ስለገባችበት የፖለቲካ ቅርቃርና በብሔራዊ መግባባት አንፃር ከቅርቃሩ ለማውጣት በሌኒን ቋንቋ ምን መደረግ አለበት (What is to be done?) የሚለውን መሠረታዊ ጥያቄ የሀገራችን ፖለቲካ እስከገባኝ ድረስ ልመልስ።

    1. መሠረታዊ ችግራችን በታሪክ አጋጣሚ ሥልጣን ላይ የወጡ መሪዎቻችን ሀገርን የመምራት ሕልማቸው፤ ሥልጣንን ጨምድዶ ከመቆየት ሕልማቸው ጋር ሁሌ ስለሚጋጭባቸው ነው። ለሕዝብ አለን ከሚሉት ፍቅር የሥልጣን ፍቅራቸው ስለሚበልጥባቸው ነው። ለዚህ ነው ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ የሚወደንና (ሕዝቡ ምን ያከል እንደሚወደቸዉ እንዴት እነዳወቁ ባናዉቅም) የምንወደው ሕዝባችን ሲሉ ኖረው ለ60 ዓመታት ገደማ የገዟትን ኢትዮጵያ ለ20ኛዉ ክፍለ ዘመን ሳያበቁ ከዓለም ሀገሮች ጭራ ደረጃ ትተዋት የሄዱት። የሕዝብ ፍቅራቸውንም ደረጃ በረሃብ በመቶ ሺህዎች ያለቀው የወሎ ሕዝብ ይመሰክራል። ይህን የመሳሰሉ የመሪዎቻችን ባዶ የሕዝብና የሀገር ፍቅር፥ የንጉሡ ሕይወቴና የኢትዮጵያ እርምጃ፣ የመንግሥቱ ኃይለማርያም አብዮታዊት እናት ሀገር ወይም ሞት የመለስ ዜናዊ በቀን ሦስት ጊዜ የሚመገቡ ዜጎችን እፈጠራለሁ ወ.ዘ.ተ መሸፈን አይችልም። ለዚህ አሁን ያሉ መሪዎቻችንም ሆኑ ተስፈኛ መሪዎች ይህንን የታሪክ እውነታ በውል እንዲገነዘቡት እፈልጋለሁ።
    2. የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎችና የተቀሩት ልሂቃን በተለያየ ደረጃ የሚጋጩ ሕልሞቻቸውን ይዘው መጓዛቸው ነው። ከመኢሶንና ኢህአፓ ዘመን እስከዛሬ ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶቻችንና መሪዎቻቸው ይህንን እውነታ በውል መገንዘብ ይኖርባቸዋል። የሕልሟን ጉዳይ በፈንጆቹ አባባል ከዜሮ ድምር ፖለቲካ (zero-sum game politics) የመውጣቱን ጉዳይና የፖለቲካ ፍላጎቶቻቸዉን በገደብ የማድረጉን ነገር በጥብቅ እንዲያስቡበት እመክራለሁ። ዋና ጉዳያችን ሥልጣን ሆኖ ከፊንፊኔ እስከ መቀሌ ባንዳ፣ ባንዳ እየተባባሉ መካሰሱ ሕዝባችንን ከማደናገር በላይ ብዙ የፖለቲካ ትርፍ የለውም። ዛሬ በአሜሪካና በአውሮፓ በሚደረጉ ሰልፎች ላይ በአንድ እጅ እስክንድር ነጋ ይፈታ፣ በሌላ እጅ ጃዋር ሽብርተኛ ነው የሚሉት መፈክር ዓይነቶቹ ለሀገረ-መንግሥት ግንባታችንም ሆነ ለብሔራዊ መግባባት ሥራችን ብዙ የሚጠቅሙ አይመስሉኝም። በእኔ በኩል እንዲህ ዓይነቱ ጉዳይ ስላስቸገረኝ ነበር በ2008 በፃፍኩት መፅሐፍ ላይ ለቡዳ ፖለቲካችን መላ እንፈልግ ብቻ ሳይሆን የሚጋጩ ሕልሞች ሊታረቁ ወይስ ኢትዮጵያን ሊያፈርሱ በሚል ግልፅ ጥያቄ የደመደምኩኝ። ለእኔ መፍትኼው ለአዲስቷ ኢትዮጵያ ፈጠራ የሚሆን አዲስ ማኅበራዊ ውል (new social contract) ከመፈራረም ውጭ የተሻለ የማጂክ ፎርሙላ ያለን አይመስለኝም። ይህንን እውነታ የምኒልክ ቤተ መንግሥት ያሉ የብልጽግና ወንድሞቻችንም ሆኑ ከአዲስ አበባ/ፍንፍኔም እስከ አውሮፓና አሜሪካ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ግፋ በለው የሚሉ ሁሉ እንዲረዱልኝ አደራ እላለሁ። በቅርብ ጊዜ በተፈጠረው ቀውስ በሁሉም በኩል ላለቁትም የተሻለ የሐዘን መግለጫ የሚሆነውና ዕንባቸውን የሚያብሰው የችግሮቻችን ምንጭ አዉቀን ዘለቂ መፍትኼ ስንፈልግ ይመስለኛል።
    1. ከላይ ካነሳኋቸው ሁለት ነጥቦች ጋር ተያይዞ ሺህ ጊዜ ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ እየተባለ በሕዝብ ላይ የሚሠራዉ የፖለቲካ ትያትር መቆም አለበት።
      የንጉሡ ዘመን የምርጫ ትያትሮች፣ የደርግ ዘመን የምርጫ ትያትሮች፣ የኢህአዴግ ዘመን የምርጫ ትያትሮች በግልፅ ቋንቋ ለማስቀመጥ፥ ሲያንሱ በዴሞክራሲ ስም የተቀለዱ  ቀልዶች፣ ሲበዙ ደግሞ በኢትዮጵያ ሕዝቦች ላይ የተሠሩና ታሪክ ይቅር የማይላቸው ወንጀሎች ነበሩ። በሰለጠነው ዓለም የሕዝብን ድምፅ ከመስረቅ በላይ ወንጀል የለም። እዚህ ላይ ሁለት ነገሮችን አስታውሼ ልለፈው። በ“ኢህአዴግ-1” ዘመን አቶ በረከት፥ “ኢህአዴግ ከስድስት ሚሊዮን በላይ አባላት አሉትና በዝረራ ያሸንፋል” ብሎ ሲያስቸግረኝ፤ አቶ በረከት፥ “ኢህአዴግ ሁለት ምርኩዞች አሉት፤ አንደኛው ምርጫ ቦርድ ነው። ሁለተኛው ጠመንጃችሁ ነው። ሁለቱን ምርኩዞቻችሁን አስቀምጣችሁ ተቃዋሚዎችን ካሸነፋችሁ፥ እኔ በግሌ እናንተ የምትሉትን 20 ና 30 ዓመታት ብቻ ሳይሆን ለሃምሳ ዓመታት እንድትገዙን እፈርምልሀለሁ” እንዳልኩት አሰታዉሰለሁ። በ“ኢህአዴግ-2” ጊዜ ደግሞ ዶ/ር ዓቢይ በጠሩት ድንገተኛ ስብሰባ ላይ ገለልተኛ የሆነው ጠቋሚ ኮሚቴ ስምንት ሰዎች አጣርቶ ስላቀረበ አራት ሰዎች መመረጥ ስላለባቸው በተጠቆሙት ሰዎች ላይ አስተያየት ስጡ አሉን። ሌሎች ስብሰባው ላይ የተገኙ የየድርጅት መሪዎች ያሉትን ብለዋል፤ እኔ ጨዋታው ስላላማረኝ፥ “አብዛኛዎቹን ዕጩዎች ብዙዎቻችን አናዉቃቸውምና ከየት እንደመጡ እንኳ ለማወቅ የ24 ሰዓት ጊዜ ስጡኝ” ብዬ አጥብቄ ጠየኩኝ። ዶ/ር አቢይ ‘አይቻልም’ አሉ። ነገ የምናገረው እንዳይጠፋኝና ለታሪክም ቢሆን ተአቅቦ (reservation) መዝግቡልኝ ማለቴ ትዝ ይለኛል። ምስክሮችም አሉኝ። የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መጥቶ የምርጫ ቦርድ ኃላፊዎች የምርጫ ጊዜውን ሰሌዳ ለማስተላለፍ በጠሩት የምክክር ስብሰባ ላይ እንደተናገርኩኝ፥ መለኮታዊ ጣልቃ ገብነት (divine intervention) ነው እንዳልኩኝ ምርጫው ባይተላለፍ ኖሮ የአዲሱ ምርጫ ቦርድ አካሄድ ሌላ ከበድ ቀውስ ሊያስከትል ይችል እንደነበረ ዛሬ ላይ ሆኜ በእርግጠኝነት መናገር እችላለሁ። ይህንኑ ደግም ብዙ ጊዜ በታጋይነቷ ለምናውቃት ክብርት ብርቱካንም ጭምር መናገሬን አስታውሳለሁ።

    ስለሆነም የሚመጣውን ምርጫ አዲስቷን ዴሞክራትክ ኢትዮጵያ እንድትወለድበት ካላደረግን፥ የንጉሥ የማክያቬሊ ምክር፣ የመንግሥቱ ኃይለማርያም፣ የጆሴፍ ስታሊን ቀይ በትር፣ የመለስ ዜናዊ፣ የሊቀ መንበር ማኦ አብዮታዊ ዴሞክራሲ ውሰት፣ ኢትዮጵያን ለመለወጥ የታሪክ ፈተናውን ለማለፍ እንዳላስቻላቸዉ፥ የዶ/ር ዓቢይም የመደመር የፖለቲካ ቀመር አዛውንቱ የፈረንጅ ምሁር የሚለውን የኢትዮጵያ ፖለቲካ የመጨረሻ ሁለት ድንበሮችን የሚያሻግረን አይመስለኝም። እሱን ካልተሻገርን ደግሞ ሁሌም እንደምለው ለሁላችንም የምትሆን ዴሞክራትክ ኢትዮጵያ የምትፈጠር አይመሰልኝም።

    ከማጠቃለሌ በፊት የብሔረታዊ መግባባቱ የፖለቲካ ጥረታችን ይሳካ ዘንድ መፍትሄ የሚሹ ቁልፍ ጉዳዮች ላስቀምጥ፦

    1. ያለ ሀገራዊ ስምምነት በዋናነት በአንድ ቡድን ሕልምና ፍላጎት (በተለይ የአንድ ቡድን ፍኖተ-ካርታ /road map/) የመመረቱ ጉዳይ ለዉጡን አጣብቂኝ ዉስጥ ማስገበቱን የማወቅ ጉዳይ፤
    2. ለውጡን ለማምጣት በዋናነት የላቀ አስተዋጽኦ ያላቸው ኃይሎች (ለምሳሌ እንደ ኦሮሞ ቄሮ ዓይነቶቹ) ወደ ዳር የመገፋታቸው ጉደይ፤
    3. ለውጡን እየመራ ያለው ከራሱ ከኢህአዴግ የወጣ ቡድን ቢሆንም፥ በለውጡ ምንነት፣ ፍጥነት፣ ስፋትና ጥልቀት ላይ የተለያዩ የኢህአዴግ ክንፎች ስምምነት ማጣታቸውና በዚህም ምክንያት እያመጣ ያለው አደገኛ ሁኔታ፤
    4. በሚጋጩ ሕልሞቻችን ምክንያት ላለፉት 50 ዓመታት መፍትሄ ያላገኘንለት የመከፋፈል ፖለቲካችን (political polarization) ጉዳይ፤
    5. ዴሞክራሲያዊ ለውጡ ለአብዛኛዉ የኢትዮጵያ ሕዝቦችና የፓለቲካ ኃይሎች ተቀባይነት ያለዉ፣ ሰላማዊና የተሳካ እንዲሆን የጋራ ፍኖተ-ካርታ (roadmap) የመቀየስ አስፈላጊነት ጉዳይና፤ የተቀየሰዉን በጋራ ሥራ ላይ የማዋል ጉደይ፤
    6. ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ማለት በእርግጥም በሕዝቦች ይሁንታ ላይ የተመሠረተ የፓለቲካ ጨዋታ መሆኑን የመረዳት ጉዳይ፤
    7. ሀገራችን እዉነተኛ ዲሞክራሲያዊ የፈድራል ሥርዓት ያስልጋታል ስንል፥ ከሕልሞቻችን በሻገር በሕዝቦቻችን ፍላጎት ላይ የተመሠረተ የፖሊቲካ ሥርዓት መሆኑን የማረጋገጥ ጉዳይ፤
    8. ብሔራዊ መግባባቱ በተሻለ መንገድ የሚሳካው፥ በደቡብ አፍሪካ እና ኮሎምቢያ በመሰሰሉት ሀገሮች እንዳየነው የፖለቲካ እስረኞችንና የጫካ አማፅያንን መጨመርን የማስፈለጉ ጉዳይ፤
    9. የተሳካ ብሔራዊ እርቅን ለመምጣት ከሥልጣን በሻገር የምር የፖለቲካ ቁረጠኝነት (political will) የማስፈለጉ ጉዳይ፤
    10. ስለኢትዮጵያ አንድነት ያለን ግንዘቤ ከፊታዉራሪ ሀብተጊዮርጊስ እይታ የሰፋና ለሀገሪቷ ያለን ፍቅርም ገደብ የማድረጉ ጉደይ ናቸዉ።

    በመደምደሚያዬም፥ እዚህ ያደረሰንን የሀገራችንን ፖለቲካ ጉዞ ታሪክ ወደኋላ እያየሁ፥ የወደፊቱን የሀገራችንን ዕጣ ፈንታንም እያማተርኩ ለጠቅላይ ሚኒስትሩም፣ ለሁላችንም የታሪክ የግርጌ ማስታወሻ ልተዉ።

    በቅርብ ቀን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‘ኢትዮጵያ አትፈርስም፤ ኢትዮጵያን የሚያፈርሷት እኛን ቀድሞ ሲያፈርሱ ነው፤ ኢትዮጵያን ለማፍረስ አይፈቀድላቸውም’ ሲሉ አዳምጫለሁ። ሀገርን ለመፍረስ የሚፈልጉ ኃይሎች መጀመሪያኑ ፈቃድ ይጠይቃሉ፤ አይጠይቁም የሚለዉን ክርክር ውስጥ ሳልገባ፥ በጨዋ ቋንቋ ንግግራቸውን አልወደድኩላቸውም። ንግግራቸውንም ተከትሎ የኢሳት ቴሌቪዥን የፖለቲካ ተንታኞች የሚታወቁ የአዛውንት ምሁርን በመጥቀስ (ይህኑን ምሁር መንግሥቱ ሀይለማርያምም ያዉቃል ብለን ስለተሠሩ የንጉሡ ባለስልጣኖች ምክር ጠይቀነዉ፥ ጠመንጃዉ በእናንተ እጅ ነዉ፤ የምን ምክር ትጠይቁናላችሁ ብሎኛል ማለቱን አንብቤአለሁ) ዶ/ር ዓቢይ ጥሩ ይዘዋል፤ ሕጉንም ሰይፉንም እየተጠቀሙ ነው ያሉት የበለጠ ሥጋት ፈጥሮብኛል። እዚህ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ሁላችንም ደጋግመን ማሰብ ያለብን ጨዋታው ከተበላሸ አብዛኛው ዓለምን በሰዓታት ውስጥ ወደ አመድነት የሚለወጥ ወይም ሕይወት-አልባ ሊያደርግ የሚችል የኒዩክሊየርር መሣርያ የታጠቀ፣ ነፍሷን ይማርና የሶቭዬት ህብረት ሠራዊት ዓይኑ እያየ ሀገራቸው መበቷን ነው። የሀገራችንን ፖለቲካ በጋራ አስተካክለን ሁላችንንም በእኩልነት የምታስተናግድ ዴሞክራቲክ ኢትዮጵያን ለመፍጠር እግዚአብሔር ይርዳን እላለሁ።

    ዋቢ መፃሕፍት:

    1. Bahiru Zewde (1991) A History of Modern Ethiopia, 1885 -1991.
    2. Gebru Tareke (1996) Ethiopia: Power and Protest, Peasant Revolts in the Twentieth Century.
    3. John Markakis, (2011) Ethiopia: The Last Two Frontiers.
    4. Merera Gudina, (2002) Ethiopia: Competing Ethnic Nationalisms and the Quest for Democracy, 1960-2000.
    5. Teshale Tibebu, (1995), The Making of Modern Ethiopia, 1896-1974.

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forumsላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    በኢትዮጵያ የሀገረ-መንግሥት ግንባታ የታሪክ ዳራ… መረራ ጉዲና (ፕሮፌሰር)

    Anonymous
    Inactive

    በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ሞታ በተገኘችው ተማሪ (ሃይማኖት በዳዳ) የተጠረጠረው ግለሰብ በቁጥጥር መዋሉን ፖሊስ አስታወቀ

    አዲስ አበባ (ኢፕድ) – ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ውስጥ የተገደለችው የወጣት ሃይማኖት በዳዳ ተጠርጣሪ ገዳይ በቁጥጥር ስር መዋሉን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ። የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በቁጥጥር ስር ያዋለው የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪ የሆነውና በ20ዎቹ እድሜ ክልል ውስጥ የሚገኝ ደግነት ወርቁ የተባለ ወጣት ሲሆን፥ ወጣት ደግነት ወርቁን ፖሊስ የ27 ዓመቷን ሃይማኖት በዳዳ ሕይወት በማጥፋት ጠርጥሮት በቁጥጥር ስር አውሎታል።

    ግንቦት 20 ቀን 2012 ዓ.ም. ከምሽቱ አንድ ሰዓት ላይ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ከብሔራዊ መረጃና ደህንነት ባካሄደው ክትትል ነው ተጠርጣሪውን በቁጥጥር ስር የዋለው። ቀን ከሌሊት በተካሄደው በዚህ ክትትል የተያዘው ወጣቱ ደግነት ወርቁ ከሟች ጋር ምንም ዓይነት ትውውቅ እንዳልነበራቸው በቁጥጥር ስር በኋላ ለሰዓታት በተደረገ ምርመራ የወንጀሉን ዝርዝር ለፖሊስ አስርድቷል።

    ግለሰቡ የ12ኛ ክፍል ተማሪ እንደነበርና የኤች አይ ቪ ኤድስ መድኃኒት ለማግኘት ምርምር ላይ ስለሆንኩ የጥቁር አንበሳ ሐኪሞች ይርዱኝ በማለት ወደ ግቢው በተለያዩ ጊዜያት ይመላለስ እንደነበር ዘርዝሯል። ከዚያም በግንቦት 17 ቀን 2012 ዓ.ም. እንደልማዱ ለዚሁ ጉዳይ እንደመጣ ገንዘብ እንደተቸገረና ቢላዋ ይዞ በግቢው ውስጥ ከሚገኙ ቢሮዎች በአንዱ ላፕቶፕ ወይም ሞባይል ካገኘ ሰርቆ ሽጦ ለመጠቀም ሲዟዟር የሟች ክፍል ክፍት በመሆኑ መግባቱን አስረድቷል። ሟች ሃይማኖት በዳዳ ሞባይሏን እንድትሰጠው ጠይቋት እምቢ ስትለው መታገላቸውንና ከዚያም በያዘው ስለት ወግቷት ንብረቱን ይዞ መውጣቱን ተናግሯል።

    ፖሊስ ከሟች ጋር የቅርብ ግንኙነት የነበራቸው 12 ተጠርጣሪዎችን ይዞ ተጨማሪ ምርመራ ማድረጉን የግድያ ወንጀሎች ምርመራ ዳይሬክቶሬት ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን (ኢቲቪ) ገልጿል። ለፖሊስ ምርመራ ትልቅ አቅም የሆነው የሟች ወላጅ አባት ከሳምንት በፊት ለልጃቸው የሰጧት የ5 ሺ ብር ቼክ ነው።

    ገዳዩ በወቅቱ የሟችን ላፕቶፕና ሞባይል ፓስፖርት መታወቂያና ይህንን ቼክ ወስዶ ስለነበር ቼኩን የካ አካባቢ በአንድ ባጃጅ ተሳፍሮ አሽከርካሪውን መታወቂያ ስላልያዝኩ በአንተ መታወቂያ ይህንን ብር አውጣልኝ ብሎት የባጃጁ ሹፌርም (አቶ እንዳለማው ታረቀኝ) መልኩን አስተውሎ ስለነበር ምርመራው ከዚህ እንደጀመረ ፖሊስ ገልጿል፡

    ኮሚሽኑ በወቅቱ የሆስፒታሉ የደኅንነት (security) ካሜራ ከአገልግሎት ውጪ መሆኑን (‘update’ እንዳልተደረገ) እና የጥበቃ ሠራተኞችም ቢላዋ ተይዞ እስከሚገባ ፍተሻቸው አጋላጭ መሆኑንም ጠቁሟል ሲል የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) ዘግቧል።

    ሃይማኖት በዳዳ ማነች?

    ወጣት ሃይማኖት በዳዳ ተወልዳ ያደገችው መተሃራ ከተማ ሲሆን፥ ወላጆች በአሁኑ ወቅት በአዳማ ከተማ ጎሮ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ይኖራሉ። በ2009 ዓ.ም. ከሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ በ’ክሊኒካል ፋርማሲ’ የመጀመሪያ ዲግሪዋን በማዕረግ ያገኘች ሲሆን፥ በዚያው በተማረችበት ዩኒቨርሲቲ በመምህርነት ስታገለግል ነበር። ከዚያም በ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የጤና ሳይንስ ኮሌጅ የሁለተኛ ዲግሪዋን በመከታተል ላይ እንደነበረች አባቷ አቶ በዳዳ ፈይሳ ተናግረዋል።

    የሃይማኖት አባት አቶ በዳዳ ፈይሳ ልጃቸው 2009 ዓ.ም ከሚዛን ቴፒ ዩኒቨርስቲ በ’ክሊኒካል ፋርማሲስት’ በማዕረግ ተመርቃ በዩኒቨርስቲው በመምህርነት ስታገለግል መቆየቷን ያስታውሳሉ። ከዚያም ሁለተኛ ዲግሪዋን ለመማር ወደ ጥቁር አንበሳ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ ተልካ ትምህርቷን በመከታተል ላይ እንደነበረች ይናገራሉ።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት (ኢፕድ) እና ቢቢሲ አማርኛ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    ሃይማኖት በዳዳ

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ከነሐሴ ወር 2010 ዓ.ም. ጀምሮ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሆነው ያገለገሉት ዶ/ር አብርሃም በላይ በጥር ወር 2012 ዓ.ም. የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ሆነው መሾማቸውን ተከትሎ በምትካቸው አቶ አሸብር ባልቻ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው ተሹመዋል።

    በጥር ወር 2012 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሆነው ከነሐሴ ወር 2010 ዓ.ም. ጀምሮ ያገለገሉት ዶ/ር አብርሃም በላይ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ሆነው መሾማቸውን ተከትሎ አቶ አሸብር ባልቻ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው ተሹመዋል።

    በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን አምቦ ከተማ በ1973 ዓ.ም. የተወለዱት አቶ አሸብር የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን በዚያው በአምቦ አዲስ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት፤ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ደግሞ በአምቦ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተከታትለዋል።

    የከፍተኛ ትምህርታቸውን ደግሞ በቀድሞ የአርባ ምንጭ ውሃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት፤ በአሁኑ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተከታትለው 1995 ዓ.ም. ላይ በሜካኒካል ኢንጂነሪንግ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ተቀብለዋል። ከግሪንዊች ዩኒቨርሲቲ (Greenwich University) በዓለምአቀፍ ቢዝነስ የማስተርስ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል። ከስዊዲን ሀገር ኬ. ቲ. ኤች ሮያል ኢንስቲትዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ (KTH Royal Institute of Technology) በዘላቂ ኢነርጂ ምህንድስና ዘርፍ ተጨማሪ ኮርሶችን ወስደዋል።

    አቶ አሸብር በሜካኒካል ምህንድስና ከተመረቁ በኋላ በበደሌ ቢራ ፋብሪካ ጀማሪ ሜካኒካል ኢንጂነር የሥራ መደብ ላይ ለ7 ወራት አገልግለዋል። ከነሐሴ 1996 ዓ.ም. ጀምሮ በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ተቀጥረው በጊምቢ–መንዲ–አሶሳ የኃይል ማስተላለፊያ መስመር ፕሮጀክት ሥራቸውን ጀምረዋል። በተከዜ የውሃ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ከጥር ወር 1997 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ግንቦት ወር 2003 ዓ.ም. ድረስ መሪ መካኒካል ኢንጂነር ሆነው የኤሌክትሮ ሜካኒካል ሥራዎችን በመቆጣጠር ተቋሙን አገልግለዋል።

    ከግንቦት 2003 ዓ.ም. እስከ መስከረም ወር 2012 ዓ.ም. ድረስ የገባ የውሃ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ በመሆን ካገለገሉ በኋላ ከጥቅምት ወር 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ይህን ኃላፊነት እስከተቀበሉበት ቀን ድረስ የኃይል ማመንጫዎች ግንባታ ሥራ አስፈፃሚ ሆነው ሲያገለግሉ ቆይተዋል።

    አቶ አሸብር ባልቻ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይልን በተለያዩ የሥራ መደቦች በባለሙያነትና በኃላፊነት ለ16 ዓመታት አገልግለው ከየካቲት 09 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ ተቋሙን በዋና ሥራ አስፈፃሚነት እንዲመሩ በተቋሙ የሥራ አመራር ቦርድ ተሹመዋል።

    ከዚሁ ጋር በተያያዘ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ሆነው የተሾሙት ዶ/ር አብርሃም በላይ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የሥራ አመራር ቦርድን እንዲመሩ ተጨማሪ ኃላፊነት ተሰጥቷቸዋል።

    ዶ/ር አብርሃም እስካሁን የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ወደትክክለኛው መስመር እንዲመጣና እንዲፋጠን ከፍተኛ ክትትልና ድጋፍ ሲያደርጉ ቆይተዋል። በተለይም በኢፌዲሪ ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ሜቴክ ተይዘው የነበሩ ሥራዎች ልምድ ላላቸው ዓለም አቀፍ ተቋራጮች እንዲሰጥና ተቋራጮቹም በተቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ እንዲሰሩ በማድረግ በኩል ጉልህ የአመራር ሚና ነበራቸው። የገናሌ ዳዋ 3 የውሃ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት የካሳ ጥያቄ እልባት አግኝቶ ለምርቃት እንዲበቃም ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክተዋል።

    ቢተገበሩ ወጪ ከማውጣት ባለፈ ውጤታማ የማይሆኑ ረዥም ዓመታት የወሰዱ ፕሮጀክቶች በህጋዊ መንገድ እንዲቋረጡ በማድረግ ተቋሙንና መንግስትን ከተጨማሪ ወጪ ማዳን ችለዋል። በተጨማሪም የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ጤናማ የፋይናንስ አቅም እንዲኖረው በማድረግና በተቋሙ የአሰራር ስርዓቶችን በማሻሻል ተጨባጭ አምጥተዋል።

    የተቋሙን የዕዳ ጫና በተመለከተ ተቋሙ የሚመለከተውን ብድር ብቻ እንዲሸከምና ሌሎች ብድሮች ግን ወደ ብድሩ ባለቤቶች እንዲተላለፉ የሚያስችል ቁርጠኛ አቋም በመያዝ የብድር ጫናው እንዲቀንስ አድርገዋል።

    በመሆኑም በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የተጀመረው ለውጥ እንዲቀጥል በማሰብ እና በተቋሙ ላከናወኑት ሥራ እውቅና ለመስጠት ተቋሙን በሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢነት እንዲመሩ በጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ተጨማሪ ኃላፊነት ተሰጥቷቸዋል።

    ዶ/ር አብርሃም ባሳዩት ውጤት በተቋሙ አመራር እና ሰራተኞች ዘንድ ተወዳጅ የነበሩና የለውጥ መሪ ተምሳሌት ተደርገው የሚወሰዱ ነበር። የተቋሙ አመራርና ሠራተኞችም ዶ/ር አብርሃም በሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢነት ዳግም ወደተቋሙ በመምጣታቸው ደስታቸውን ገልፀዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል

    Anonymous
    Inactive

    የጋሞ ሽማግሌዎች (የጋሞ አባቶች) መንግሥት ኖረም አልኖረ በአካባቢያቸው ላይ፤ በተለይም በገዛ ልጆቻቸው የማንም ሌላ ኢትዮጵያውን ሕይወትም ሆነ ንብረት እንደማይወድም ተንበርክከው፤ ግን ደግሞ በመንፈስ ልዕልና ከፍ ብለው አሳይተውናል።

    ታላቅ ክብር ለጋሞ ሽማግሌዎች ይሁን!
    (ያሬድ ኃይለማርያም)

    ለእውነት የቆሙ ሽማግሌዎች እጦት፣ በካድሬ እና በመንጋ ፖለቲከኛ ክፉኛ ለተመታችው አገሬ የጋሞ ሽማግሌዎች (የጋሞ አባቶች) ፍቱን መድኃኒት ናቸው። እንደ ጋሞ ሽማግሌዎች ዓይነት ቅን አሳቢ፣ የፍቅር መምህር፣ የተግባር ሰው፣ ደፋር እና ዝቅ ብለው የከፍታን ውሃ ልክ የሚያሳዩ ሽማግሌዎች ከየማህበረሰቡ ቢገኙ ከገባንበት ቅርቃር በቀላሉ ለመውጣት ዕድል ይኖረን ነበረ። በሽማግሌ እና በካድሬ መካከል ያለውን ልዩነት መለየት ያልቻሉ ቀሳውስት፣ ሼኾች፣ አባገዳዎች፣ ፓስተሮች፣ መንፈሳዊ አባቶች ኮሽ ባለ ቁጥር አበል እየተከፈላቸው በየሆቴሉ ሲማማሉ እና በሕዝብ ስም እነሱ ሲታረቁ ቢውሉም መሬት ላይ ጠብ ያለ ነገር የለም።

    የአገራችን ችግር ቅን አሳቢ እና ለእውነት የወገነ፣ ያመነበትን በትክክል የሚናገር፣ ክፉን የሚያወግዝን እና ጥሩውን የሚያበረታታ እውነተኛ ሽማግሌ፣ ደፋር ምሁር፣ ሃቀኛ ፖለቲከኛ፣ ሚዛናዊ ጋዜጠኛ እና መሰሪ ያልሆነ የአገር መሪ ይፈልጋል። ለጋሞ ሽማግሌዎች እና ሽማግሌዎቹንም ለሚያከብሩት የጋሞ ወጣቶች ትልቅ ክብር አለኝ። ጥሩ ምሳሌም ሊሆኑ ይችላሉ።

    የአማራ ሽማግሌዎች ከወዴት አላችሁ? የትግራይ ሽማግሌዎች ከወዴት አላችሁ? የኦሮሞ ሽማግሌዎች እና አባገዳዎች ከወዴት አላችሁ? እነዚህን ክልሎች በተለየ ሁኔታ የምጠራው ሦስቱም ክልል ውስጥ ያለው እሳት አገሪቱን ወደ ከፋ ሁኔታ እየገፋት ያለ ስለመሰለኝ ነው። በማኅበረሰብ ውስጥ ግጭት ሲፈጠር፣ ዜጎች በጠራራ ፀሀይ ሲታረዱ፣ እናት ከነልጆቿ ከቅዮዋ ተፈናቅላ ዱር ስታድር፣ ሕጻናት በነፍሰ በላዎች ታፍነው ገሚሱ ሲገደሉ፣ የዩንቨርሲቲ ሴት ተማሪዎች በወሮበላ ታጣቂዎች ታፍነው ሲወሰዱ የመንግስት ክርን ቢዝል እናንተ የአገር ሽማግሌዎች የት ገባችሁ?

    የጋሞ ሽማግሌዎች (የጋሞ አባቶች) መንግሥት ኖረም አልኖረ በአካባቢያቸው ላይ፤ በተለይም በገዛ ልጆቻቸው የማንም ሌላ ኢትዮጵያውን ሕይወትም ሆነ ንብረት እንደማይወድም ተንበርክከው፤ ግን ደግሞ በመንፈስ ልዕልና ከፍ ብለው አሳይተውናል። ከዛም አልፈው ይህን ትልቅ የሽምግልና እና የፍቅር መንፈስ ይዘው ከአንድ አገሪቱ ጫፍ ወድ ሌላው ጫፍ ተጉዘዋል። መንፈሳችሁ በሌሎች ሽማግሌዎች ይደር!!

    ክብር ለጋሞ ሽማግሌዎች ይሁን!
    (ያሬድ ኃይለማርያም)

    ከጋሞ ኢትዮጵያውያን ጋር በተያያዘ የጋሞ አባቶች እና ወጣቶች ጥር 14 ቀን 2012 ዓ.ም. “የሰላም ጉዞ” በሚል መርህ ከአርባ ምንጭ በመነሳት የተለያዩ ከተሞችን በማቋረጥ መዳረሻቸውን ጎንደር ከታማ እና የጥምቀት በዓልን አድርገው መጓዛቸውንበዚህ ሳምንት ተዘግቧል።

    በጉዞው የጋሞ አባቶች የአካባቢያቸውን ሰላም እንዴት እንዳስጠበቁ ተሞክሮዎቻቸውን ለሌሎች እንዳካፈሉ እና የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሰላም ተምሳሌትነትም ለሌሎች የመንግስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በተሞክሮነት አሳይተዋል። አባቶች በጉዞው የተለያዩ ከተሞችን ያቋረጡ ሲሆን፥ በጉዟቸው መሃል ባረፉባቸው ከተሞችም ስለ ሰላም እና አንድነት ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር ምክክር አድርገዋል። እንዲሁም ተማሪዎችን ስለአቃፊነት፣ ስለ ሰላምና አንድነት እንደመከሩም የጋሞ ዞን ኮሙዩኒኬሽን መምሪያ መረጃ ሰጥቶ ነበር።

    የሰላም ዦቹ የጋሞ አባቶች እና ወጣቶች በአዲስ አበባ በብሔራዊ ቤተ መንግሥት ተገኝተው የአንድነት ፓርክን የጎበኙ ሲሆን፥ የጉዞው መዳረሻ በሆነችው ታሪካዊቷ የጎንደር ከተማም ከከተራ በዓል ጀምረው እስከ ጥር 14 ቀን 2012 ዓ.ም. ለአራት ቀናት እንደሚቆዩ ተዘግቧል።

    የአብሮነትና የሰላም ጉዞውን ኅብረ መንጎል ሚዲያና ኦሞቲክ ጀኔራል ጠቅላላ ንግድ ድርጅት በጋራ ያዘጋጁት ሲሆን፥ የጉዞውን አላማ በመደገፍ የሰላም ሚኒስቴር፣ የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ እንዲሁም የደቡብ ክልል ሰላም እና ፀጥታ ቢሮዎች ለአዘጋጆች የድጋፍ ደብዳቤ ሰጥተዋቸዋል።

    ምንጮች፦ ያሬድ ኃይለማርያም እና ፋና ብሮድካስቲንግ

    የጋሞ አባቶች

    Semonegna
    Keymaster

    በጋሞ ዞን ገረሴ ወረዳ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውሉ የከበሩ ማዕድናት መገኘታቸውን አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ

    አርባ ምንጭ (አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ) – የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል መንግሥት ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ከኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ሰርቬይ ኤጀንሲ ጋር በ2010/11 በጀት ዓመት በጋሞ፣ በወላይታና በኮንሶ ዞኖች ያካሄደውን የማዕድን አለኝታ ጥናት ውጤት ታህሳስ 2 ቀን 2012 ዓ.ም. ለባለድርሻ አካላት ይፋ አድርጓል። በመርሀግብሩ ላይ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በጋሞ ዞን ገረሴ ወረዳ ከተሌ ቀበሌ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውሉ የከበሩ ድንጋዮችና ማዕድናት መገኘታቸውን አስታውቋል።

    በክልሉ የሚገኘውን ማዕድን በዓይነት፣ በመጠንና በቦታ ለይቶ ለክልሉ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ለማሳወቅ ጥናቱ መከናወኑን የዩኒቨርሲቲ ኢንዱስትሪ ትስስርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ቶሌራ ሴዳ ተናግረዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ጂኦሎጂ ትምህርት ክፍል መምህርና የጥናት ቡድኑ አባል ረዳት ፕሮፈሰር ጎሳዬ ብርሃኑ እንደገለጹት፥ ጥናቱ በዋናነት ለሴራሚክ ኢንዱስትሪ የሚውሉ የከበሩ ድንጋዮች ላይ ትኩረት በማድረግ የተለያዩ ባለሙያዎችን ባካተቱ 5 ቡድኖች ለ1 ዓመት ያህል የተከናወነ ሲሆን በጥናቱም ከፍተኛ ጥራት ያላቸው “aquamarine”፣ “tourmaline” እና “garnet” የተሰኙ የከበሩ የድንጋይ ናሙናዎች እንዲሁም “feldspar” ማዕድን ውጤታማ ግኝት ተመዝግቧል። “Feldspar” ማዕድን ለሴራሚክ እና ብርጭቆ ኢንዱስትሪዎች ግብዓት የሚሆን ማዕድን ሲሆን በአካባቢው ከ101 ሚሊየን ቶን በላይ ክምችት እንዳለ በጥናቱ ታውቋል።

    የአካባቢው ወጣቶች በመደራጀት አካፋ፣ ዶማና የመሳሰሉትን ባህላዊ መሣሪያዎች ተጠቅመው በተለይም “aquamarine” የተባለውን ማዕድን እያወጡ መሆኑን የጠቀሱት ረዳት ፕሮፈሰር ጎሳዬ፥ ይህም የማዕድኑን ጥራት በከፍተኛ ሁኔታ እየጎዳው ነው ብለዋል። ማዕድናቱ ጥራታቸውን እንደጠበቁ እንዲወጡ የሚመለከተው አካል ለወጣቶቹ ሥልጠና ቢሰጥ መልካም መሆኑን ተናግረዋል።

    በጥናቱ የማዕድናቱ መገኛ፣ ጥራትና ክምችት በሚገባ የተዳሰሰ በመሆኑ የሚመለከተው የመንግሥት አካል አዋጭ የማውጫ ዘዴ በመለየት ማዕድናቱ የሚወጡበትን ሁኔታ ቢያመቻች ኢንዱስትሪውን በከፍተኛ ሁኔታ የሚጠቅምና ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል የሚፈጥር መሆኑን ረዳት ፕሮፈሰር ጎሳዬ ገልጸዋል።

    የምርምር ውጤቱን የማኀበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ተክሉ ወጋየሁ እና የዩኒቨርሲቲ ኢንዱስትሪ ትስስርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ቶሌራ ሴዳ ዩኒቨርሲቲውን ወክለው ለኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ሰርቬይ ኤጀንሲ ተወካይና ለደቡብ ክልል ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አስረክበዋል።

    ምንጭ፦ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive
    • ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ በዩኒቨርሲቲው የጸጥታ ችግር የተሳተፉ ተማሪዎች ላይ እርምጃ ወሰደ
    • ወሎ ዩኒቨርሲቲ በ335 ተማሪዎች፣ ሁለት የአስተዳደር ሠራተኞች እና አንድ መምህር ላይ እርምጃ ወሰደ
    • የጋምቤላ፣ ቦንጋ እና አርባምንጭ ዩኒቨርሲቲዎች የተማሪዎች ጥያቄዎች በተለያዩ ሀይሎች ሴራ እንዳይጠመዘዝ አስቀድመው በመሥራታቸው የመማር ማስተማር ሂደቱ በሰላማዊ ሁኔታ መቀጠሉን አስታወቁ

    የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ሴኔት ታህሳስ 27 ቀን 2012 ዓ.ም. ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በ2012 ዓ.ም. በተደጋጋሚ በተፈጠረው የጸጥታ ችግር የተለያየ ተሳትፎ በነበራቸው ተማሪዎች ላይ የሚከተሉትን ውሳኔዎች ወስኗል።

    1. ሁለት (2) ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ ከትምህርት ገበታቸው እንዲሰናበቱ፣
    2. ሰባት (7) ተማሪዎች እያንዳንዳቸው ለሦስት (3) ዓመት ከትምህርት ገበታቸው እንዲታገዱ፣
    3. ስምንት (8) ተማሪዎች እያንዳንዳቸው ለሁለት (2) ዓመት ከትምህርት ገበታቸው እንዲታገዱ፣
    4. አንድ (1) ተባሮ የነበረ (በወቅቱ የዩኒቨርሲቲው ተማሪ ያልነበረ) ነገር ግን በተፈጠረው የጸጥታ ችግር ውስጥ ተሳታፊ የነበረ ዩኒቨርሲቲው ክስ መስርቶ ግለሰቡን በሕግ ተጠያቂ እንዲያደርግ፤

    በመጨረሻም በወቅቱ ለሴኔቱ ውሳኔ ለቀረበ ተጨማሪ ስልሳ ዘጠኝ (69) ተማሪዎች ዲሲፕሊን ጉዳይ ላይ ተወያይቶ ጥፋታቸው በሂደት ተጣርቶ ወደ ፊት እርምጃ እንደሚወሰድባቸው እንዲሁም በቀጣይ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በተፈጠረው የጸጥታ ችግር በተለያየ መልኩ ተሳታፊ የነበሩ የዩኒቨርሲቲው ሠራተኞች ላይ እንደየጥፋታቸው እርምጃ እንደሚወሰድ አቅጣጫ ተቀምጧል።

    በተያያዘ ዜና የጋምቤላ፣ ቦንጋ እና አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲዎች የተማሪዎች ጥያቄዎች በተለያዩ ሀይሎች ሴራ እንዳይጠመዘዝ አስቀድመው በመሥራታቸው የመማር ማስተማር ሂደቱ በሰላማዊ ሁኔታ መቀጠሉን አስታወቁ።

    ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሃይማኖትና የብሄር ተኮር ግጭቶች ማዕከል ሆነው እና የጸጥታ ችግር ተጋርጦባቸው ጥቂት የማይባሉ ዩኒቨርሲቲዎችም በተደጋጋሚ ትምህርት ለማቆም ተገደዋል፤ በተማሪዎች ላይም ጉዳት አጋጥሟል። የግጭት መንስኤዎች የተለያዩ ሲሆን አንዳንዶቹ ከአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮች ጋር የተያያዙ ናቸው።

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ የመማር ማስተማር ሥራውን አውከዋል ያላቸውን 332 ተማሪዎች፣ ሁለት የአስተዳደር ሠራተኞች እና አንድ መምህር ላይ እርምጃ መውሰዱን አስታወቋል።

    ከፀጥታ መዋቅሩ ጋር በመሆን ባለፉት ሁለት ወራት ችግር ፈጣሪዎችን ለመለየት በተከናወነው ጠንካራ የሕግ ማስከበር ሥራ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሥራው እንዳይቀጥል ፍላጎት ባላቸው 332 ተማሪዎች፣ ሁለት የአስተዳደር ሠራተኞች እና አንድ መምህር ላይ እርምጃ መወሰዱን ዩኒቨርስቲው አስታውቋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን ለ ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደገለጹት፥ ዩኒቨርሲቲው በሰላማዊ የመማር ማስተማር ሥራ ተመራጭ እና ተምሳሌት ሆኖ ቆይቷል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በብሔር እና በሀይማኖት ሽፋን በተፈጠረ አለመረጋጋት የመማር ማስተማር ሥራው ባለፉት ወራት ውስጥ ለሦስት ጊዜ መቋረጡን አውስተዋል።

    በዚህም የሁለት ተማሪዎች ሕይወት ማለፉንና በተወሰኑት ላይ ደግሞ የአካል ጉዳት መድረሱን ጠቅሰው፣ ይህም ከአንድ የእውቀት ምንጭ ተቋም የማይጠበቅ አሳፋሪ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል።

    የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጴጥሮስ ወልደጊዮርጊስ ግን በከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ የሚታዩት የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮች ለግድያ የሚያደርሱ እንዳልሆኑ ይናገራሉ። አብዛኛዎቹ ተማሪዎች ሰላም ወዳድ መሆናቸውን የሚገልጸው ዩኒቨርሲቲው የመማር ማስተማሩን ለማወክ የሞከሩ ጥቂት ተማሪዎች እንዳልተሳካላቸው የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ገልፀዋል።

    ከ4 ሺህ በላይ ተማሪዎችን እያስተናገደ የሚገኘው ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲም ሁነኛ የጸጥታ ችግር ሳያጋጥመው የመማር ማስተማሩ ሂደት በሰላማዊ ሁኔታ ከቀጠለባቸው ዩኒቨርሲቲዎች መካከል ተጠቃሹ ነው። ዩኒቨርሲቲው ባወጣው መርሃ ግብር መሠረት የአንደኛ መንፈቅ ዓመት ትምህርትን ወደማገባደድ መቃረቡን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኡጁሉ ኦካክ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተናግረዋል።

    የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛም የመማር ማስተማር ሂደቱ በሰላማዊ ሁኔታ መቀጠሉን አንስተዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ በተለይም ተማሪዎች በተደጋጋሚ የሚያነሷቸውን የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመቅረፍ ካልተቻለም ለማሻሻል ጥረት ማድረጋቸውን አስታውቀዋል።

    ተማሪዎችን ተቀብለው ማስተናገድ ከጀመሩ በኋላ የሚነሱ ቅሬታዎችን በአጭሩ ለመፍታትም ከተማሪዎች ጋር የሰከነ እና የሰለጠነ ውይይት ማድረጋቸውን የአርባምንጭ እና ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች ገልፀዋል። ለዚህም ተማሪዎች እያንዳንዱ ጥያቄ በሂደት እንደሚፈታ ማመናቸውና አርቆ ተመልካችነታቸው ሰላማዊ ሁኔታው እንዲቀጥል ትልቁን ድርሻ እንደተወጣም ተጠቁሟል።

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገኙባቸው አካባቢዎች የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሀይማኖት መሪዎች እና ወጣቶች በሰላማዊ የመማር ማስተማሩ ሂደት ላይ የራሳቸውን ሚና እንዲወጡ መደረጉንም ዩኒቨርሲቲዎቹ የገለጹት።

    የዩኒቨርሲቲዎቹ ባለቤት የሆነው ማኅበረሰብ ተማሪዎቹን እንደ ራሱ ልጆች ተመልክቶ እንዲጠብቃቸው የተሰራው ሥራም ውጤታማ እንደነበር ነው ፕሬዚዳንቶቹ የገለጹት።

    ተማሪዎችም በሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች የታዩ አሰቃቂ ተግባራት እንዳይደገሙ በጋራ መሥራት አለባቸው፤ ከስሜታዊ ድርጊትም ሊታቀቡ ይገባልም ነው ያሉት። የብዙሃኑን ሰላም ለመጠበቅ ጥቂት በጥባጮችን አደብ ማስገዛት ይገባል ብለዋል በመልዕክታቸው።

    ምንጮች፦ ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ / የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    በዩኒቨርሲቲዎች የጸጥታ ችግር

    Semonegna
    Keymaster

    ዲላ፥ ኢትዮጵያ (ዲዩ) – ዲላ ዩኒቨርሲቲ (ዲዩ) ሪፈራል ሆስፒታል ከኦርቢስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ እና ከደቡብ ክልል ጤና ቢሮ ጋር በመተባበር የዓይን ህክምና ማዕከል በመገንባት በዲላ ከተማ እና አካባቢው ለሚገኝ ማኅበረሰብ የተለያዩ የዓይን ችግር (የትራኮማ፣ የዓይን ማየት ችግር፣ የሞራ ግርዶሽ) ያለባቸው ሰዎችን ቀዶ ህክምና አገልግሎት መስጠት ጀምረ።

    የዓይን ህክምና ክፍል አስተባባሪ የሆኑት አቶ ቢንያም እስጢፋኖስ፥ ዲላ ዩኒቨርሲቲ ሪፈራል ሆስፒታል ለአስር ዓመታት በአንድ ክፍል ውስጥ በቂ ባልሆነ የዓይን ህክምና እየሰጠ በመሆኑ ይርጋለም፣ ሀዋሳ እና አዲስ አበባ ሲላኩ (“ሪፈር” ሲደረጉ) በሽተኞች፣ በተለይም ከገጠሩ አከባቢ የሚመጡ ህክምና ፈላጊዎች ለተለያዩ ችግሮች ይጋለጡና ለእንግልት ይዳረጉ ነበር። በዚህ ምክንያት ከኦርቢስ ኢንተርናሽናል ጋር በመተባበር ህንፃውን ለማቋቋም ግንባታው ለአንድ ዓመት ሲገነባ እንደነበረና አሁን የሞራ ግርዶሽ ህክምና (cataract surgery) እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።

    የጌዴኦ ዞን፣ ቡርጅና አማሮ የመስክ አስተባባሪ የሆኑት አቶ ተመስገን ጌታቸው፥ “ከዚህ በፊት ለተለያዩ ነገሮች መጋለጥ ይኖራል፤ አሁን ግን ኦርቢስ ኢንተርናሽናል ስለተቋቋመ እነዚህ ችግሮች ሁሉ ይቀረፍላቸዋል፤ ጊዜያቸውንም ይቆጥባሉ፤ በጊዜም ህክምናውን ያገኛሉ ብለዋል።” ኦርቢስ ዓለምአቀፍ ኘሮጀክት የሥራ ድርሻው አስፈላጊ የህክምና እቃዎችን የማሟላት እገዛና የባለሙያውን ክኅሎት ለመጨመር ድጋፍ ማድረግ ሲሆን ሌሎች ነገሮች ሆስፒታሉ የሚችል መሆኑን አቶ ተመስገን ገልጸዋል።

    ለጊዜው ኦርቢስ ኢንተርናሽናል ለጊዜው የባለሙያዎች አቅም ግንባታ ስልጠና የመስጠት ተግባር እያከናወነ ቢሆንም የተለያዩ የዓይን ችግር ያለባቸው ሰዎችን የትራኮማ፣ የዓይን ማየት ችግር ያለባቸው የሞራ ግርዶሽ ቀዶ ህክምና በተጓዳኝነት መስጠት በመጀመሩ ሥራው ከተጀመረ በ5 ቀናት ውስጥ ከ200 በላይ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ቀዶ ጥገና እንደሚያገኙ ይጠበቃል። ህክምናው ከተጀመረ ጀምሮ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ህመምተኞች ለተለያዩ የዓይን በሽታዎች ምርመራ ተደርገው ከ140 በላይ የሞራ ግርዶሽ ቀዶ ህክምና መሠራቱን ተገልጿል።

    ህክምናው በቅርበት በዲላ ሪፈራል ሆስፒታል መከፈቱ ከዚህ በፊት በዓመት 3 ጊዜ ብቻ የነጻ ህከምና እንደሚሰጥና ሀዋሳ እና ይርጋለም በመመላለስ የህክምና፣ የትራንስፖርት እና የመኝታ ወጪ ብቻ ከ3 ሺህ ብር በላይ ይወጣ የነበረው ከመቅረቱም ባሻገር የነፃ ህክምና ሳይመላለሱ በአንድ ቀን አገልግሎት ማግኘት መቻላቸው ታካሚዎችና አስታማሚዎች እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ ዲላ ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዲላ ዩኒቨርሲቲ የዓይን ህክምና

    Anonymous
    Inactive

    የትግራይ ክልል ትምህርት ቢሮ አዲስ ገቢ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ወደ አማራ ክልል አንደማይልክ አስታወቀ
    —–

    መቐለ (ቢቢሲ አማርኛ) – የትግራይ ክልል አዲስ ገቢ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን አማራ ክልል ወደሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች እንደማይልክ አስታውቋል።

    የትግራይ ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ገብረመስቀል ካሕሳይ ጥቅምት 7 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፥ “ማንነትን መሠረት ያደረጉ ጥቃቶች ወደ ሚሰነዘሩባቸው ዩኒቨርሲቲዎች እና ኃላፊነት ወደማይወስድ ክልል አዲስ ተማሪዎችን ላለመላክ የክልሉ አቋም ነው” ብለዋል።

    “አማራ ክልል የተመደቡት 600 ተማሪዎች እንደማይሄዱ ለሚመለከተው የፌደራል መንግሥት አሳውቀናል። ይህ የክልሉ አቋም ነው” ሲሉ የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል።

    ዘንድሮ፤ በትግራይ ክልል የዩኒቨሲቲ መግብያ ፈተና ወስደው ማለፍ የቻሉ የተማሪዎች ቁጥር ከ9000 በላይ መሆኑን የጠቀሱ ኃላፊው፤ ወደ አማራ ክልል ተመድበው የነበሩ ተማሪዎች ከ2000 በላይ እንደነበረ እና ከሚመለከታቸው የፌደራል መንግስት አካላት ጋር በተደረገው ውይይት ወደ 600 ዝቅ እንዲል መደረጉን ተናግረዋል።

    “ከአንድ ወር ተኩል በላይ የክልሉ መንግሥት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ሲወያይ ቆይቷል። የተቀሩ 600 ተማሪዎችን ሌላ ቦታ እንዲመደቡ ይሠራል። ይህ የማይሆን ከሆነ ግን የትግራይ ክልል ሌላ አማራጭ ይፈልጋል እንጂ ተማሪዎቹን ወደዚያ አይልክም” ብለዋል።

    ከዚህ ቀደም በዩኒቨርሲቲ አመዳደብ ሥርዓት መሠረት ከአንድ ክልል አጠቃላይ ተማሪዎች መካከል 40 በመቶ የሚሆኑት በክልላቸው የተቀሩት 60 በመቶ ደግሞ ሌላ ክልል በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ይመደቡ እንደነበረ የሚያስታውሱት ኃላፊው፤ “ብሔርን መሠረት ያደረጉ ጥቃቶች በበዙበት ወቅት ይህ ተቀይሮ 10 በመቶ በክልላቸው 90 በመቶ ደግሞ ወደ ሌላ ክልል እንዲላኩ መደረጉ አግባብ አይደለም” ብለዋል በሰጡት መግለጫ።

    ይህ እንዲስተካከል ከፌደራል እና ከሌሎች አካላት ጋር ውይይት መደረጉን እና 20 በመቶ በክልላቸው 80 በመቶ ደግሞ ከክልል ውጪ እንዲመደቡ መወሰኑን ጨምረው ተናግረዋል።

    የትምህርት ቢሮው ኃላፊ ገብረመስቀል ካሕሳይ ትግራይ ክልል ወደሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ተመድበው የሚመጡ ተማሪዎች “ምንም አይነት የደህንነት ችግር አይገጥማቸውም” ብለዋል።

    የትምህርት ቢሮ ኃላፊው ሁለተኛ ዓመት እና ከዚያ በላይ በሆኑ ተማሪዎች ዙሪያ ያሉት ነገር የለም።

    ምንጭ፦ ቢቢሲ አማርኛ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    Anonymous
    Inactive

    አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የ2012 የትምህርት ዘመንን ሠላማዊ ለማድረግ የሠላም ጥምር ግብረ ኃይል አቋቁሞ እንደሚሠራ ገለፀ

    አርባ ምንጭ (ሰሞነኛ)– አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የ2012 የትምህርት ዘመንን ሠላማዊ ለማድረግ የሠላም ጥምር ግብረ ኃይል አቋቁሞ እንደሚሠራ ገለፀ። ዩኒቨርሲቲው በ2012 የትምህርት ዘመን ሠላማዊ መማር ማስተማር ለማረጋገጥ በተዘጋጀ የሠላም ጥምር ግብረ ኃይል መሪ ዕቅድ ዙሪያ ከዩኒቨርሲቲው ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች ጋር ጳጉሜ 2/2011 ዓ/ም ውይይት አካሂዷል።

    ጥምር ግብረ ኃይሉ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ በማዕከል እንዲሁም በየካምፓሱ የሚቋቋም ሲሆን ዓላማውም የትምህርት ዘመኑ በተሻለ ሁኔታ ውጤታማና ሠላመዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ማድረግ መሆኑን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ ተናግረዋል። ጥምር ግብረ ኃይሉ ከዩኒቨርሲቲው አመራሮች ባሻገር የተማሪዎች ኅብረት ተወካዮችን፣ የሠላም ፎረም አመራሮችን፣ የዞንና የከተማ የሥራ ኃላፊዎችንና ፀጥታ አካላትን ያካተተ መሆኑንም ፕሬዝደንቱ ገልፀዋል።

    ጥምር ግብረ ኃይሉ በዋናነት ከታች እስከ ላይ ባለው የዩኒቨርሲቲው መዋቅር መማር ማስተማሩን ሊያውኩ የሚችሉ ጉዳዮችን በየጊዜው እየተከታተለና እየገመገመ መፍትሔና ማስተካከያ የሚሰጥ መሆኑን ዶ/ር ዳምጠው ገልፀዋል። ጥምር ግብረ ኃይሉ በውስጥና በውጪ ጭምር የሚዋቀር መሆኑን የተናገሩት ፕሬዝደንቱ መዋቅሩ ከዩኒቨርሲቲው ባሻገር ከማህበረሰቡ ጋር በጋራ ይሠራል ብለዋል።

    በትምህርት ዘመኑ ለተማሪዎች ቅበላ ይረዳ ዘንድ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ የቅድመ ዝግጅት ሥራ እቀድ ተዘጋጅቶ እየተሠራ ሲሆን በቅርቡም አፈፃፀሙን በተመለከተ በዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮች የሚመራ ልዑክ ወደየካምፓሱ በመሄድ ምልከታ እንደሚያደርግና ሥራው ያለበትን ደረጃ በመገምገም አቅጣጫ እንደሚሰጥ ዶ/ር ዳምጠው ተናግረዋል።

    ሠላማዊ የመማር ማስተማሩ ሥራ ካለ ህብረተሰቡ ተሳትፎ ስኬታማ መሆን ስለማይችል መስከረም መጀመሪያ አካባቢ ከሀገር ሽማግሌዎች፣ ከሀይማኖት አባቶችና ከአካባቢው ማህበረሰብ ጋር ውይይት ይደረጋል ብለዋል።

    ምንጭ፦ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 35 total)