Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 331 through 345 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ከማሳቹሴትስ ኢንስቲትዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ (MIT) በትብብር ለመሥራት ስምምነት አደረገ

    ወልቂጤ (ሰሞነኛ) – ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ አሜሪካን ሀገር ካምብሪጅ ከተማ ከሚገኘው ማሳቹሴትስ ኢንስቲትዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ (MIT) ከተሰኘው ዕውቅ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ጋር በትብብር ለመሥራት የሚያስችል የውል ስምምነት ተፈራረመ።

    ሁለቱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የገቡትን ውል በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ተግባር ለማሸጋገር የሚያስችላቸውን የቅድመ-ዝግጅት ሥራዎች ማከናወንም ጀምረዋል።

    በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚደንት ዶ/ር ሐብቴ ዱላ እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው ከማሳቹሴትስ ኢንስቲትዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ ጋር የሚኖረው የትብብር ሥራ በዋናነት በኮምፒዩቲንግና ኢንፎርማቲክስ ኮሌጅ የሚሰጡትን የትምህርት ፕሮግራሞች በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በታገዘ የቤተ-ሙከራ ትምህርት ለማስደገፍ የሚያስችልና በመምህራንና በተማሪዎች የሚሠሩትን የምርምር ሥራዎች እና ፕሮጀክቶች ውጤታማነት ለማሻሻል ወሳኝ ሚና ይኖረዋል።

    እንዲሁም የትብብር ሥራው የኮሌጁን የመማር-ማስተማር ሥራ ለማዘመንና ዓለም ዓቀፍ ደረጃውን ለማስጠበቅ የሚያግዘው ከመሆኑም ባሻገር በምርምርና የማኅበረሰብ አገልግሎት፣ በዕውቀት እና በቴክኖሎጂ ሽግግር መስኮች ለሚከናወኑ ሥራዎች ስኬታማነት የላቀ ፋይዳ እንደሚኖረው ዶ/ር ሐብቴ አስረድተዋል።

    በዩኒቨርሲቲው የኮምፒዩቲንግና ኢንፎርማቲክስ ኮሌጅ ዲን አቶ ኮርአብዛ ሸዋረጋ በበኩላቸው እንደተናገሩት፥ ኢንስቲትዩቱ ከዩኒቨርሲቲው ጋር በገባው ውል መሠረት በያዝነው የ2012 የትምህርት ዘመን ከሁለተኛው መንፈቀ-ዓመት /ሴሚስተር/ ጀምሮ ዓመታዊ ክፍያው ከ160 ሺህ በላይ የሆነውን የኦንላይን ትምህርት በነጻ በመስጠት የኮምፒዩቲንግና ኢንፎርማቲክስ ኮሌጅን ተጠቃሚ ማድረግ ይጀምራል። ለዚህም ዕቅድ ተግባራዊነት ኢንሰቲትዩቱ ድጋፍ ሰጪ ቡድን ወደ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በመላክ ተግባራዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ይገኛል።

    በዚህም መሠረት ድጋፍ ሰጪው ቡድን የኦንላይን ትምህርቱን ለመስጠት ወሳኝ የሆኑት የቤተ-ሙከራ ዕቃዎችን ይዞ በመምጣት ለዩኒቨርሲቲው በእርዳታ አበርክቷል። የተበረከቱት ዕቃዎች እስካሁን ድረስ በንድፈ-ሐሳብ /theory/ ብቻ ሲሰጡ የነበሩትን የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ /artificial intelligence/፣ ሮቦቲክስ /robotics/ እና ተዛማጅ የትምህርት ዓይነቶች የማስተማር ዘዴ በተግባር የታገዘ አንዲሆን ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖራቸው አቶ ኮርአብዛ ገልጸዋል።

    ድጋፍ ሰጪ ቡድኑ ለዩኒቨርሲቲው ያበረከታቸውን የቤተ-ሙከራ መሣሪያዎችን በአግባቡ ሥራ ላይ ለማዋል ከኮምፒዩቲንግና ኢንፎርማቲክስ ኮሌጅና ከኢንጅነሪንግና ቴክኖሎጂ ኮሌጅ ለተውጣጡ 10 መምህራን ከጥር 4 ቀን 2012 ዓ.ም. እስከ ጥር 8 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ ለአምስት ተከታታይ ቀናት ያዘጋጀውን በኮምፒዩተር ፕሮግራም ቋንቋ አጠቃቀም ላይ ያተኮረ የአሰልጣኞች ሥልጠና በመስጠት ላይ ይገኛል።

    በመጨረሻም ዶ/ር ሐብቴ አክለውም፥ ሁለቱ ተቋማት በጋራ ለመሥራት እንዲችሉ በማገናኘቱ ሥራ በአሜሪካ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልድ ኢትዮጵያውያን ሚና ከፍተኛ እንደነበረ በመግለፅ ይህንን የዜግነት ግዴታቸውን ለተወጡት የዲያስፖራ አባላት በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ እና በራሳቸው ስም አመስግነዋል።

    ምንጭ፦ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive
    • በሥራ ላይ ያለው ሥርዓተ-ትምህርት በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት በአዲስ ሥርዓተ-ትምህርት ይቀየራል።
    • በከፍተኛ ትምህርት ዘርፍ የተጀመሩ የለውጥ ሥራዎችን አጠናክሮ ለማስቀጠል ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር ይበልጥ ተቀናጅቶ መሥራት አስፈላጊ ነው።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በሥራ ላይ ያለውን ሥርዓተ-ትምህርት በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት በአዲስ ሥርዓተ-ትምህርት ለመቀየር የሚያስችሉ ሥራዎችን በማከናወን ላይ መሆኑን የትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።

    በትምህርት ሚኒስቴር የሥርዓተ-ትምህርት ዝግጅትና ትግበራ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ እሸቱ አስፋው በጉዳዩ ዙሪያ በተዘጋጀ የባለሙያዎች ምክክር መድረክ ላይ እንደገለፁት ከ2012-2014 የትምህርት ዘመን በሥራ ላይ ያለውን ሥርዓተ-ትምህርት ለመቀየር የአስር ዓመታት ፍኖተ-ካርታ ተዘጋጅቷል።

    በሥራ ላይ ያለውን ሥርዓተ-ትምህርት መቀየር ያስፈለገው በፍኖተ ካርታው ምክረ-ሃሳቦች መሠረት ችግሮች ስላሉበት ነው። በመሆኑም በመጭዎቹ ዓመታት በአዲስ የሚተካው ሥርዓተ-ትምህርት የተማሪዎችን ሥነ-ምግባር ጨምሮ በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን የሚፈታ መሆኑን ዳይሬክተሩ አስታውቃዋል።

    በአውደ-ጥናቱም ከሀገሪቱ ሁሉም ክልሎችና የከተማ መስተዳድሮች የተውጣጡ የትምህርት ቢሮ ባለሙያዎች፣ የሥርዓተ-ትምህርት ዝግጅት ሃላፊዎች፣ ከሁለተኛና ከአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ መምህራን፣ የመምህራን ኮሌጆችና ከአምስቱ የመምህራን ማሰልጠኛ ዩኒቨርስቲዎችና ሌሎችም ባለድርሻዎች ተሳታፊ መሆናቸውን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።

    በትምህርት ሚኒስቴር የሥርዓተ-ትምህርት ዝግጅትና ትግበራ ዳይሬክቶሬት የእንግሊዝኛ ቋንቋ ሥርዓተ-ትምህርት ዝግጅት ባለሙያ የሆኑት አቶ ሰለሞን ወርቁ በበኩላቸው ሥርዓተ-ትምህርቱ እየተዘጋጀ ያለው ከፍኖተ ካርታው በተገኙ ምክረ ሃሳቦችና ጥቆማዎች (recommendations an suggestions) እንዲሁም የካንብሪጅ ኢንተርናሽናል አሰስመንትን (Cambridge Assessment International Education) ጨምሮ በየደረጃው ከሚገኙ ባለድርሻዎች በተገኙ ምክረ ሃሳቦችና ተጨማሪ አስተያየት መሠረት ነው።

    በምክክር መድረኩም የሥርዓተ-ትምህርት ማዕቀፍ፣ የእያንዳንዱ የትምህርት ዓይነት መርህ አቅጣጫ (position papers) እና ሌሎችም ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አቶ ሰለሞን መግለፃቸውን የትምህርት ሚኒስቴር የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዘግቧል።

    ከሀገራችን የከፍተኛ ትምህርት ሁኔታ ጋር በተያያዘ ደግሞ፥ በከፍተኛ ትምህርት ዘርፍ የተጀመሩ የለውጥ ሥራዎችን አጠናክሮ ለማስቀጠል ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር ይበልጥ ተቀናጅቶ መሥራት እንደሚገባ ተገለጸ።

    የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ከሰው ሃብት ልማትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አመራርና አባላት፣ ከሌሎች ቋሚ ኮሚቴ አመራሮች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት ጋር በዘርፉ የተከናወኑ የለውጥ ሥራዎች ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በአዳማ ከተማ ተካሒዷል።

    በመድረኩ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ፕሮፌሰር ሂሩት ወልደማርያም “በዘርፉ የተጀመሩ የለውጥ ሥራዎችን በተሟላ ሁኔታ ተተገብረው ብቁና ተወዳዳሪ እንዲሁም መልካም ሥነ ምግባር የተላበሱ ምሩቃን አፍርተን ዘርፈ ብዙ ፈተናዎችን እያለፍን የሀገራችንን የማስፈጸም አቅም በመገንባት በብልጽግና ከፍታ ላይ ለማድረስ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር ተቀናጅተን እንሠራለን” ብለዋል።

    ሚኒስቴሩ በትምህርትና ስልጠና ፍኖተ ካርታ ጥናት ላይ የተቀመጡ ምክረ ሐሳቦችን መነሻ በማድረግ በነባሩ የትምህርት ሥርዓት ላይ ያለውን ጉድለት ለመሙላት እና ለማሻሻል አዳዲስ የለውጥ ኃሳቦችን በማካተት ከ2012 የትምህርት ዘመን ጀምሮ ትግበራ ላይ መሆኑን የጠቆሙት ሚኒስትሯ፥ ከነዚህም መካከል የከፍተኛ ትምህርትን ሥርዓተ ትምህርት የማሻሻል፣ የትምህርት አሠጣጥ ሥነ-ዘዴዎቹንና የትምህርቶቹንም ይዘት የመከለስና የኮርስ ካታሎግ (course catalog) የማዘጋጀት፣ ከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችንን በተልዕኮና በልህቀት ለይቶ የማደራጀት እንዲሁም አዳዲስ የሕግና የአሠራር ማዕቀፎችን የማውጣትና ነባሮቹንም የመከለስ ሥራዎች ይገኙበታል ብለዋል።

    እንደ ፕሮፌሰር ሂሩት ገለፃ፥ የምክክር መድረኩ ያስፈለገበት ዋነኛ ምክንያት ሚኒስቴሩ በሚያከናውናቸው የለውጥ ሥራዎች ላይ የባለድርሻ አካላት ሚና ከፍተኛ መሆኑን ስለሚያምንና በተለይም በቂ ግንዛቤ ያለውና የተቀናጀ የባለድርሻ አካላት ንቁ ተሳትፎ ለለውጥ ሥራዎቻችን ስኬት ቁልፍ ስለሆነ ነው ሲሉ አስቀምጠዋል።

    ለሁለት ቀናት በቆየው የምክክር መድረክ የትምህርትና ስልጠና ፍኖተ ካርታ ጉዳዮች፣ በፍኖተ ካርታ ምክረ-ሃሳብ መሠረት በከፍተኛ ትምህርትና በቴክኒክና ሙያ ዘርፍ የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት፣ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሴክተር የ10 ዓመት መሪ ዕቅድ እንዲሁም በሰላማዊ መማር ማስተማር ዙሪያ የተሠሩ አንኳር ሥራዎች፣ ተግዳሮቶችና ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ቀርበው ውይይት ይካሄዳል።

    በመጨረሻም የሚኒስቴሩ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የሰው ሃብት ልማትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አመራርና አባላት የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ የልህቀት ማዕከል የሥራ እንቅስቃሴን የሚጎበኙ ይሆናል።

    ምንጮች፦ የትምህርት ሚኒስቴር/ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    ሥርዓተ-ትምህርት

    Anonymous
    Inactive

    በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ በተፈጠረው የሰላም እጦት ጋር በተያያዘ ከ640 በላይ ተማሪዎች፣ 40 መምህራን እና ከ240 በላይ የአስተዳደር ራተኞች ላይ የተለያዩ እርምጃዎች መወሰዳቸው ተገለጸ

    አዲስ አበባ (ኢብኮ) – ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ተፈጥሮ የነበረው የጸጥታ ችግር ለማረጋጋት በ22 ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ በነበሩ ከ640 በላይ ተማሪዎች፣ 40 መምህራን እና ከ240 በላይ የአስተዳደር ሠራተኞች ላይ የተለያዩ እርምጃዎች እንደተወሰደ የሳይንስና የከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ገልጿል።

    በዩኒቨርሲቲዎች በተፈጠረ የሰላም እጦት 35 ሺህ ተማሪዎች ትምህርት ጥለው መውጣታቸውን የገለጸው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ፥ እነዚህን ተማሪዎች ወደ ትምህርት ገበታቸው ለመመለስ እየተሠራ መሆኑን አስታውቋል። የተማሪዎችን አደረጃጀት በኅብረ ብሔር ለማሰባጠር መታሰቡንም ሚኒስቴሩ ገልጿል።

    የሳይንስ እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ዩኒቨርሲቲዎች ሰላም ባጡባቸው ጉዳዮች ላይ ከተለያዩ አካላት ጋር ግምገማ እና ምክክር እያደረገ ይገኛል።

    በ22 ዩኒቨርሲቲዎች ተፈጥሮ የነበረውን የጸጥታ ችግር ለማጣራት የተዋቀረው ኮሚቴ ባደረገው የመስክ ምልከታ ያዘጋጀው ሪፖርት በመድረኩ ላይ ቀርቧል። በቀረበው ሪፖርትም የዩኒቨርሲቲዎች የሰላም መታወክ የፖለቲካ አመራሮች ትልቅ ሚና እየተጫወቱ እንዳለ ተገልጿል።

    በተለያዩ ክልሎች ባሉ የተለያዩ የፖለቲካ አመራሮች የሚወጡ መግለጫዎች እና ከግቢ ውጭ ተማሪዎችን ሰብስቦ ተልእኮ የመስጠት ሥራዎች ለመማር ማስተማሩ መታወክ እንደ አንድ ምክንያት ተጠቁሟል። ተልእኮ የተቀበሉ ተማሪዎች መማር የሚፈልጉ ተማሪዎች ላይ የሥነ ልቦና፣ አካላዊ፣ የሕይወት እና ንብረት ጉዳት በማድረስ ግጭት እንደሚያነሳሱም ተጠቁሟል። በሚዲያዎች፣ በሶሻል ሚዲያዎች እና በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን የተጋነኑ እና የተዛቡ መረጃዎች መሰራጨት፣ የዩኒቨርሲቲ አመራሮች ችግሮችን ውጫዊ ማድረግ ወይም ቸልተኝነትም ሌላው ለዩኒቨርሲቲዎች የሰላም እጦት የተነሣ ተግዳሮት ነው። በዩኒቨርሲቲዎች ያለው በቤተ ዘመድ የተሳሳበ የሠራተኛ አደረጃጀት እንዲሁ እንደ አንድ ችግር ተጠቅሷል።

    ችግር የፈጠሩ እና ምንም ዓይነት የሕግ እርምጃ ሳይወሰድባቸው በነፃ የሚለቀቁ እና እንዲማሩ የሚፈቀድላቸው ተማሪዎችም በዩኒቨርሲቲዎች ለሚታየው የሰላም እጦት ሌላው ምክንያት መሆናቸው ተጠቁሟል።

    በዩኒቨርሲቲ አመራሩ በኩል ውጫዊ ማስፈራሪያዎችን በመፍራት ውሳኔ ሰጭነት ላይ የሚታየውን ማፈግፈግ እንዲሻሻል እና ጠንካራ አስተዳደራዊ እርምጃ እንደሚወሰድም ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢብኮ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የሳይንስና የከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር በዩኒቨርሲቲዎች የሰላም እጦት

    Semonegna
    Keymaster

    ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ መቀመጫውን አሜሪካን ሀገር፣ ሚኖሶታ ግዛት ካደረገው ቡክስ ፎር አፍሪካ (Books for Africa) ከተሰኘው ግብረ-ሰናይ ድርጅት ጋር ባደረገው ግንኙነት፥ በዕርዳታ ያስመጣቸውን የሳይንስ፣ የሂሳብ፣ የቋንቋ እና ስነ-ፅሁፍ መጽሐፎችን በይልማና ዴንሳ ወረዳ ለሚገኙ ትምህርት ቤቶች አከፋፍሏል።

    የዚህ ድጋፍ ተጠቃሚ የሆኑት አዴት ከተማ የሚገኙ ትምህርት ቤቶችና ብርአዳማ ከተማ አካባቢ ደግሞ በሰከላል ጃንባራ መድኃኔዓለም ቀበሌ የሚገኘው ገብረን አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት፣ በስማርጋ ቀበሌ የሚገኘው ቼመን አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤትና በአይቫር ቀበሌ የሚገኘው መጣቅር አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ሲሆኑ እርዳታው ለሌሎችንም የመንግስት ትምህርት ቤቶች ያካተተ እንደነበር ታውቋል። መጽሐፎቹ ለመምህራን እና ለተማሪዎች ማጣቀሻነት የሚሆኑ ከ1ኛ እስከ 4ኛ ክፍል እና ከ5ኛ እስከ 8ኛ ክፍል እንዲሁም ለጎልማሶች ትምህርት የሚያገለግሉ እንደሆኑ ማወቅ ተችሏል። በዕለቱም ከ10 ካርቶን በላይ የሚሆኑ የሳይንስ፣ የሂሳብ፣ የቋንቋ፣ የሥነ-ፅሑፍ እና የማኅበራዊ ሳይንስ ይዘት ያለቸው መጽሐፎች ለእያንዳንዱ ትምህርት ቤት ቦታው ድረስ በመሄድ ለርዕሳነ መምህራን ርክክብ ተፈፅሟል።

    በርክክቡ ወቅት በሰከላል ጃንባራ መድኃኔዓለም ቀበሌ የሚገኘው ገብረን አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር የሆኑት አቶ አዱኛ አጥናፉ እንዳሉት፥ የተደረገላቸው የመጽሐፍ እርዳታ በገንዘብ ሊተመን የማይችልና የተማሪዎችን ብሎም የመምህራንን የዕውቀት ክፍተት ለመሙላት የሚያግዝ ነው ብለዋል። ይህም የተማሪዎቻቸውን በሀገር ደረጃ የመወዳደር አቅም የሚያጎለብት በመሆኑ የመጽሐፍ እርዳታው ለትምህርት ቤቱ ትልቅ ትርጉም እንዳለው ተናግረዋል። ርዕሰ መምህሩ አክለውም በትምህርት ቤታቸው ያሉባቸውን፦ (1ኛ) ለሳይንስ ትምህርቶች የሚያገለግሉ ኬሚካሎች፣ (2ኛ) በፀሀይ የሚሰራ የኃይል ማመንጫ ችግር ለመቅረፍ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የበኩሉን አስተዋፅዖ እንዲያደረግላቸው ጠይቀዋል።

    የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማኅበረሰብ አገልግሎት ካደረገው የመጽሐፍ እርዳታ በተጨማሪ በይልማና ዴንሳ ወረዳ ውስጥ ለሚገኙ ከስድስት በላይ የችግኝ ጣቢያዎች ግብዓት የሚሆኑ የተለያዩ በሰው የሚገፉ ጋሪዎች፣ አካፋዎች ፣የመጎንደያ መቀሶች፣ የአሸዋ መንፊያ ወንፊቶችና መጋዞችን ለጣቢያዎቹ አበርክቷል። የይልማና ዴንሳ ወረዳ የስማርጋ ችግኝ ጣቢያ ሠራተኛና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ተወካይ የሆኑት ወ/ሮ ዳሳሽ ላቃቸው እንዳሉት፥ ችግኝ ጣቢያው በዓመት ከ80 ሺህ በላይ የተለያዩ አገር በቀል ችግኞችን በማፍላት ለአካባቢው ማኅበረሰብ በነፃ እንደሚያቀርብ ገልፀው፥ እስካሁን ባለው የሥራ ሂደት ምንም ዓይነት የቁሳቁስም ሆነ የግብዓት ችግር እንዳላጋጠማቸው ተናግረዋል።

    የመጽሐፍ ድጋፉ በጎንደር አካባቢ ለሚገኙ የወረዳ የመንግስት ትምህርት ቤቶችም የተደረገ ሲሆን መጽሐፎች ተመሳሳይ ይዘት ያለቸው መሆኑንም ለማወቅ ተችሏል።

    ምንጭ፦ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ

    Anonymous
    Inactive

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – የውጭ ጉዲፈቻ በመታገዱ የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻ መጨመሩን የአዲስ አበባ ሴቶችና ሕፃናት ጉዳይ ቢሮ አስታወቀ።

    በቢሮው የሕፃናት ድጋፍ ክብካቤ ቡድን መሪ አቶ ኢያሱ ሳሙኤል በተለይ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደተናገሩት፤ ብሔራዊ የሕፃናት ፖሊሲ ተቀርጾ ከወጣበት ከ2009 ዓ.ም. ጀምሮ የውጭ ሀገር ጉዲፈቻ በመታገዱ የሀገር ውስጡ እየጨመረ መጥቷል።

    ከእገዳው በፊት በተለያየ መንገድ ከሀገር ይወጡ የነበሩት ሕፃናት ቁጥር ከፍተኛ ነበር የሚሉት አቶ ኢያሱ፥ የሀገር ውስጡ ግን በአዲስ አበባ በ2007 ዓ.ም. ስድስት በአደራ ሶስት በጉዲፈቻ እንዲሁም በ2008 ዓ.ም. አምስት በአደራ ብቻ ነበር።

    ከአዋጁ በኋላ ግን በየአመቱ ቁጥሩን በመጨመር በ2009 ዓ.ም. በአደራ 160 በጉዲፈቻ 150፤ በ2010 ዓ.ም. በጉዲፈቻ 148 በአደራ 138 እንዲሁም በ2011 ዓ.ም. በጉዲፈቻ 172 በአደራ 156 ማስተላለፍ መቻሉን ተናግረዋል።

    እንደ አቶ ኢያሱ ገለጻ፥ እገዳው የተደረገው ሕፃናቱ በማያውቁት ባህል፣ ቋንቋና ማኅበረሰብ ውስጥ ማደጋቸው ከማንነት ጋር ተያይዞ የሚነሱባቸው ማኅበራዊና ሥነ ልቦናዊ ቀውሶች ስለሚያጋጥማቸው ነው። ለክትትልና ለቁጥጥር አመቺ ስለማይሆን፣ ብሎም በሀገር ውስጥ መሥራት እየተቻለ ለውጭ መደረጉ በሀገር ገጽታ ላይ የሚያመጣውም ተጽዕኖ በመኖሩ መሆኑን ጠቁመዋል።

    እስካሁንም የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻ ዝቅተኛ ሊሆን የቻለው በአግባቡ ባለመሠራቱና የግንዛቤ ክፍተት ስለነበር ሲሆን፥ በአሁኑ ወቅት ግን ቁጥሩ ከመጨመሩም ባለፈ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እና ባለቤታቸው ወ/ሮ ዝናሽ ታያቸውን ጨምሮ ሌሎች ታዋቂ ሰዎችም በጉዲፈቻ ልጆች ከወሰዱ በኋላ ወሳጅ ቤተሰቦች ወረፋ እስከመጠበቅ መድረሳቸውን ጠቁመዋል።

    አቶ እያሱ ጨምረው እንደተናገሩት፥ ቢሮው አምስቱን የጉዲፈቻ የአደራ፣ የማዋሀድ፣ የማኅበረሰብ አቀፍ ድጋፍና አማራጭ የድጋፍ አገልግሎቶች በመጠቀም ሕፃናትን ከችግር የመታደግና ተጠቃሚ የማድረግ ሥራ ይሠራል።

    ለዚህም በስሩ ያሉትን ቀጨኔ የሴቶች፣ ኮልፌ የወንዶች፣ ክበበ ጸሐይ የጨቅላ ሕፃናት ማቆያና ክብካቤ ማዕከል እንዲሁም በወንጀል ውስጥ ገብተው የተገኙ ታዳጊዎች ተሀድሶ ማዕከላትን ይጠቀማል። በተጨማሪም ሰላሳ የሚደርሱ ከቢሮው ጋር በስምምነት የሚሠሩ እንደ አበበች ጎበና እና ሰላም የሕፃናት መንደር ያሉ በተመሳሳይ ተግባር የተሰማሩ የሕፃናት ማሳደጊያ ተቋማት ጋርም በትብበር የሚሠራ ሲሆን ክትትልና ቁጥጥርም ያደርጋል።

    የሕፃናቱን ደኅንነትና ሥነ ልቦና ለማስጠበቅና ለክትትል እንዲያመች ለወሳጅ ቤተሰቦች መስፈርቶች ተቀምጠዋል የሚሉት አቶ እያሱ፥ ከነዚህም መካከል አዲስ አበባ ነዋሪ መሆን፣ ሙሉ የጤና ምርምራ ማድረግ፣ ገቢው ከአምስት ሺ ብር በላይ የሆነና ቢቻል ሌላ የገቢ አማራጭ ያለው፣ የራሳቸው ቤት ያላቸው ቢሆን ይመረጣል፥ ከወንጀል ነጻ አሻራ የሚያቀርብ፣ የጋብቻ የምስክር ወረቀት (marriage certificate) እና የተጋቢዎች ስምምነት፣ አካባቢው ለሕፃናቱ ምቹ መሆን እንዲሁም ወሳጆቹ ቤተሰቦች ከማኅበረሰቡ ጋር ያላቸው ግንኙነት ሰላማዊ መሆኑ፣ ከእድር፣ ከሃይማኖት ተቋማት፣ ወይንም ከወረዳ ሴቶችና ሕፃናት ቢሮ እንዲያቀርቡ እንደሚደረግም ጠቁመዋል።

    አቶ እያሱ እንዳሉት፤ የሕፃናት ቤተሰብ መገኘት አለመገኘቱን ለማረጋገጥ የፖሊስ ሪፖርት ይዘገያል፤ የጤና ምርመራን በተመለከተም አጠቃላይ ምርመራ ውጤት በጽሁፍ እንዲሰጥ ሲጠየቅ በከተማው ካሉ ጤና ጣቢያዎች ፈቃደኛ ሆኖ የተገኘው አንድ ብቻ ነው። ከሆስፒታሎችም ፈቃደኛ የሚሆኑት ሦስት ብቻ ናቸው፤የምርመራ ውጤት እየሰጡ ያሉት በቃል ብቻ ነው። ይሄ ቢሮውን ብቻ ሳይሆን ቤተሰብንም ለእንግልት እየዳረገ በመሆኑ ከጤና ሚኒስቴር ጋር የመግባቢያ ሰነድ በመፈራረም በየክፍለ ከተሞቹ ለማስቀመጥ በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛሉ።

    በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት አብዛኛው የመራጮች ፍላጎት ሴት በመሆኑ ወንዶች ሳይመረጡ የሚቆይበት ሁኔታ አለ። ይህንንም ለማስተካከል የማግባባት ሥራ እየተሠራ ይገኛል ሲሉ ተናግረዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የሀገር ውስጥ ጉዲፈቻ

    Semonegna
    Keymaster

    በጋሞ ዞን ገረሴ ወረዳ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውሉ የከበሩ ማዕድናት መገኘታቸውን አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ

    አርባ ምንጭ (አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ) – የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል መንግሥት ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ከኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ሰርቬይ ኤጀንሲ ጋር በ2010/11 በጀት ዓመት በጋሞ፣ በወላይታና በኮንሶ ዞኖች ያካሄደውን የማዕድን አለኝታ ጥናት ውጤት ታህሳስ 2 ቀን 2012 ዓ.ም. ለባለድርሻ አካላት ይፋ አድርጓል። በመርሀግብሩ ላይ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በጋሞ ዞን ገረሴ ወረዳ ከተሌ ቀበሌ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውሉ የከበሩ ድንጋዮችና ማዕድናት መገኘታቸውን አስታውቋል።

    በክልሉ የሚገኘውን ማዕድን በዓይነት፣ በመጠንና በቦታ ለይቶ ለክልሉ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ለማሳወቅ ጥናቱ መከናወኑን የዩኒቨርሲቲ ኢንዱስትሪ ትስስርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ቶሌራ ሴዳ ተናግረዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ጂኦሎጂ ትምህርት ክፍል መምህርና የጥናት ቡድኑ አባል ረዳት ፕሮፈሰር ጎሳዬ ብርሃኑ እንደገለጹት፥ ጥናቱ በዋናነት ለሴራሚክ ኢንዱስትሪ የሚውሉ የከበሩ ድንጋዮች ላይ ትኩረት በማድረግ የተለያዩ ባለሙያዎችን ባካተቱ 5 ቡድኖች ለ1 ዓመት ያህል የተከናወነ ሲሆን በጥናቱም ከፍተኛ ጥራት ያላቸው “aquamarine”፣ “tourmaline” እና “garnet” የተሰኙ የከበሩ የድንጋይ ናሙናዎች እንዲሁም “feldspar” ማዕድን ውጤታማ ግኝት ተመዝግቧል። “Feldspar” ማዕድን ለሴራሚክ እና ብርጭቆ ኢንዱስትሪዎች ግብዓት የሚሆን ማዕድን ሲሆን በአካባቢው ከ101 ሚሊየን ቶን በላይ ክምችት እንዳለ በጥናቱ ታውቋል።

    የአካባቢው ወጣቶች በመደራጀት አካፋ፣ ዶማና የመሳሰሉትን ባህላዊ መሣሪያዎች ተጠቅመው በተለይም “aquamarine” የተባለውን ማዕድን እያወጡ መሆኑን የጠቀሱት ረዳት ፕሮፈሰር ጎሳዬ፥ ይህም የማዕድኑን ጥራት በከፍተኛ ሁኔታ እየጎዳው ነው ብለዋል። ማዕድናቱ ጥራታቸውን እንደጠበቁ እንዲወጡ የሚመለከተው አካል ለወጣቶቹ ሥልጠና ቢሰጥ መልካም መሆኑን ተናግረዋል።

    በጥናቱ የማዕድናቱ መገኛ፣ ጥራትና ክምችት በሚገባ የተዳሰሰ በመሆኑ የሚመለከተው የመንግሥት አካል አዋጭ የማውጫ ዘዴ በመለየት ማዕድናቱ የሚወጡበትን ሁኔታ ቢያመቻች ኢንዱስትሪውን በከፍተኛ ሁኔታ የሚጠቅምና ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል የሚፈጥር መሆኑን ረዳት ፕሮፈሰር ጎሳዬ ገልጸዋል።

    የምርምር ውጤቱን የማኀበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ተክሉ ወጋየሁ እና የዩኒቨርሲቲ ኢንዱስትሪ ትስስርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ቶሌራ ሴዳ ዩኒቨርሲቲውን ወክለው ለኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ሰርቬይ ኤጀንሲ ተወካይና ለደቡብ ክልል ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አስረክበዋል።

    ምንጭ፦ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ጥፋት ፈፅመው በተገኙ 77 ተማሪዎች ተማሪዎች ላይ ዛሬ እርምጃ ወሰደ

    ሐረማያ (ሰሞነኛ) – ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተወሰኑት የአገራችን ዩኒቨርሲቲዎች ሰላማዊ መማር ማስተማርን ለማረጋገጥ አስቸጋሪ ችግሮች እንደጋጠማቸው ይታወቃል። በተለይ በአንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ ያለምንም ምክንያት ውድ የሆነው የሰው ሕይወት በሚያሳዝን ሁኔታ ጠፍቷል።

    ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ይህ እንዳይሆን ጠንካራ እና ሁሉን አቀፍ ቅንጅት በማድረግ ሲሠራ በመቆየቱ የሰው ሕይወት ባያልፍም የጥፋት አላማን አንግበው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ጥቂት ተማሪዎች ግን ሰላማዊ መማር ማስተማር እንዲታወክ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ የዩኒቨርሲቲውን አጠቃላይ ህልውናን ጭምር አደጋ ውስጥ በመክተት የጥፋት ተልዕኮአቸውን ሲያከናውኑ ቆይተዋል። እነዚህ ለጥፋት የተሰማሩ ተማሪዎች ከጥፋታቸው እንዲመለሱና እንዲታረሙ ተደጋጋሚ ምክርና ጊዜ የተሰጣቸው ቢሆንም ከጥፋታቸው ሊታረሙ አልቻሉም።

    በመሆኑም የዩኒቨርሲቲውን ሰላማዊ መማር ማስተማርን ለማስቀጠል እንዲቻል በተለያዩ ጊዜያት በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የመማር ማስተማር ሥራው እንዲስተጓጎል ምክንያት በሆኑ 77 ተማሪዎች ላይ እርምጃ የተወሰደባቸው ሲሆን ለእርምጃው መወሰድ ምክንያቶች በዋናነት የሚከተሉትን ያካትታል፦

    • በዩኒቨርሲቲው ሰላማዊ መማር ማስተማር እንዳይኖር በተደራጀ ሁኔታ ሰላማዊ ተማሪ ላይ ጥቃት በማድረስ፣ ሕገ-ወጥ ሰልፍ በማደራጀት እና መማር ማስተማር እንዳይካሄድ የተለያዩ እንቅፋቶችን በመፍጠር፣
    • በቡድን ተደራጅተው በማንነት ላይ የተመሠረተ ጥቃት ማድረስ ፣ የማሸማቀቅ እና የማስፈራራት ተግባርን በመፈፀም፣
    • በሕገ-ወጥ ሰልፍ በዩኒቨርሲቲው ንብረት ላይ ውድመት ማድረስ፥ ለምሳሌ፡- ታህሳስ 30 ቀን 2012 ዓ.ም. ከሰዓት በኋላ በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ተቋም 3 (ሦስት) ተሸከርካሪዎችን አውድመዋል፤ የባንክ ኤቲኤም (ATM) ማሽን ሙሉ በሙሉ ከጥቅም ውጪ አድርገዋል፤ ዩኒቨርሲቲው ላይም ከፍተኛ ውድመት እንዲከሰት እሳት አቀጣጥለዋል።
    • የብሔር ግጭት የሚቀሠቅሱ ፖለቲካዊ ይዘት ያላቸውን ንግግሮችን በማጉላት በተማሪዎች መሀከል የስጋት ድባብ እንዲነግስ ማድረግ እና ብሔርን መሠረት አድርጎ ተማሪን በመከፋፈል ትምህርት አቋርጠው እንዲበተኑ ማድረግ ይጠቀሳል።

    በዚሁ መሠረት ሰላማዊ ተማሪዎችን ሕይወት ለመጠበቅና ሰላማዊ የመማር ማስተማሩን ሥራ ለማስቀጠል ሲባል እርምጃ ከተወሰደባቸው አጥፊ ተማሪዎች መካከል 2 (ሁለቱ) ሙሉ ለሙሉ እንዲሰናበቱ የተደረገ ሲሆን 75 ተማሪዎች ደግሞ ለ2 (ሁለት) ዓመት ከትምህርት ገበታቸው እንዲታገዱ ተወስኗል።

    በተጨማሪም ሁለት መምህራን ተማሪዎችን በማስኮብለል ድርጊት ላይ ተሳትፈው በመገኘታቸው በደመወዝ ቅጣትና የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ እንዲደርሳቸው ተደርጓል።

    ዩኒቨርሲቲው ድብቅ ዓላማን አንግበው በተለያዩ ማደነጋገሪያ ሽፋኖች የሚንቀሣቀሱ እና ተቋሙ የጥፋት ዓላማዎች ማራመጃ ሜዳ እንዲሆን ሁኔታዎችን ለማመቻቸት የሚሠሩ ተማሪዎች፣ መምህራን እና የአስተዳደር ሠራተኞች ላይ በቀጣይ የማጣራት ሥራ የሚሠራ ሲሆን፥ እንደጥፋታቸው ደረጃ እና ጥልቀት ሕጋዊ እና ተቋሟዊ እርምጃ ለመውሰድ በቁርጠኝነት እንደሚሠራ እያሳወቅን፥ ዩኒቨርሲቲው የሚያደርገው ጥረት ስኬታማ እንዲሆን ሁሉም ጉዳዩ የሚመለከታቸው እና የሀገራቸው እና የዩኒቨርሲቲያቸው ሰላም የሚያሳስባቸው የአስተዳደር፣ ፀጥታ እና ማኅበረሰብ አካላት እንደተለመደው ከዩኒቨርሲቲው ጐን እንዲቆሙ በአክብሮት እንጠይቃለን። በተጨማሪም የተማሪ ቤተሰቦች ልጆቻችሁን በመምከር እንድታግዙን ዩኒቨርሲቲው ጠይቋል።

    ምንጭ፦ ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ


    Anonymous
    Inactive

    አዲስ አበባ (ኢቢሲ) በሕዳሴው ግድብ ዙሪያ እየተካሄደ በነበረው ድርድር ግብጽ አዳዲስ ሀሳቦችን በማምጣቷ ኢትዮጵያ ሳትቀበል ቀርታለች። ድርድሩ ለአራተኛ እና ለመጨረሻ ጊዜ የተካሄደ በመሆኑ ስምምነት ላይ ይደረሳል ተብሎ ተጠብቆ ነበር።

    ግብፅ ያቀረበችው ዋነኛው የማያግባባ ሀሳብ የሙሌት ሰንጠረዡ ከ12 ዓመት እስከ 21 ዓመት ይሁን ብላ እንደ አዲስ ማቅረቧ ነው። ግብፅ እስካሁን ወደ መስማማቱ ስትቃረብ ቆይቷ ነው በዛሬው ዕለት (ታህሳስ 30 ቀን 2012 ዓ.ም.) በተደረገው ድርድር አዲሱን ሀሳብ ያነሳችው። ኢትዮጵያ በበኩሏ የሙሌት ጊዜው ከ4 ዓመት እስከ 7 ዓመት የሚል ሀሳብ አቅርባ ስትደራደር ቆይታለች።

    በድርቅ ጊዜ የውሃ አለቃቀቅ እና አሞላል ሂደቱ ምን ይምሰል የሚለው ጉዳይም ኢትዮጵያን እና ግብፅን ያላግባባ ሆኗል። የድርቅ ብያኔ /definition/ ላይም ስምምነት ላይ አልተደረሰም። ግብፅ “የውሃ መጠኑ ከ40 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ በታች ሲሆን ‘ድርቅ ነው’ ተብሎ የተሻለ ውሃ ይለቀቅልኝ” የሚል ሀሳብ ያቀረበች ሲሆን፥ ኢትዮጵያ በበኩሏ “‘ድርቅ’ የሚለው ብያኔ መሰጠት ያለበት የውሃ መጠኑ ከ35 ቢሊዮን ሜትሪክ ኪዩብ በታች ሲሆን ነው” በሚል መከራከሪያ ሀሳብ አቅርባለች። በድርድሩ ላይ እነዚህ ሀሳቦች የማይታረቁ ሆነው ቀርተዋል።

    የኢትዮጵያ ውሃ፣ መስኖ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ በጉዳዩ ላይ በሰጡት አስተያየት “የግብፅ ተደራዳሪዎች ካቀረቡት ሀሳብ አንፃር በአዲስ አበባው ድርድር ላለመስማማት የመጡ ይመስላል” ብለዋል። ከዚህ በፊት የነበረውን መቀራረብ በዚህ ድርድር እንደገና እንዲራራቅ ማድረጋቸውንም ነው ያከሉት ሚኒስትሩ።

    በድርቅ ጊዜ የውሃ አሞላል ሂደት ምን ይምሰል የሚለውም በኢትዮጵያ በኩል ግድቡ ከፍተኛ የውሃ መጠን ከያዘ በኋላ ወደ ግድቡ የሚገባው ውሃ በቀጥታ የማመንጫ ተርባይኑን እየመታ እንዲሄድ እና እንዲለቀቅ እንደሚደረግ ኢትዮጵያ አቋሟን ገልጻለች። ግብፅ ግን ይህ ተቀባይነት የለውም ብላለች። በከፍተኛ ድርቅ ወቅት ደግሞ እስከ 13 ነጥብ 5 ቢሊዮን ሜትሪክ ኪዩብ ውሃ ይለቀቃል የሚል ሀሳብም ከኢትዮጵያ በኩል ቀርቧል። ግብፅ በበኩሏ ወደ 14 ነጥብ 5 ቢሊዮን ሜትሪክ ኪዩብ ከፍ ሊል ይገባል ስትል ተከራክራለች።

    የቴክኒክ ኮሚቴው ውጤት ሪፖርት በሚቀጥለው ሰኞ (ጥር 4 ቀን 2012 ዓ.ም.) ዋሽንግተን ዲሲ ውስጥ በሚካሄድ ስብሰባ ላይ ይፋ ይደረጋል። ይህንን ተከትለሎም የየሀገራቱ መሪዎች የሚወስኑት ውሳኔ በሀገራቱ መካከል ቀጣይ ምን ዓይነት ድርድር ሊካሄድ ይችላል የሚለውን የሚወስን ይሆናል።

    ኢትዮጵያ በዚህ የቴክኒክ ኮሚቴ ላይ በመመሥረት ቀጣይ ድርድሮችን ለማድረግ እንደምትፈልግ ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ ተናግረዋል። በአዲስ አበባው ድርድር መግባባት ላይ ይደረሳል የሚል እሳቤ የነበረ ቢሆንም ተፈላጊው ውጤት አለመገኘቱን ነው ሚኒስትሩ የገለጹት።

    የሆነው ሆኖ የግድቡ ሂደት የማይቋረጥ መሆኑን እና ኢትዮጵያ ከሚቀጥለው ሐምሌ ወር ጀምሮ ግድቡን ውሃ የመሙላት ሂደት እንደምትጀምር ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ)/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    የሕዳሴ ግድብ ድርድር ስምምነት ላይ ሳይደረስ ተጠናቀቀ

    Anonymous
    Inactive
    • ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ በዩኒቨርሲቲው የጸጥታ ችግር የተሳተፉ ተማሪዎች ላይ እርምጃ ወሰደ
    • ወሎ ዩኒቨርሲቲ በ335 ተማሪዎች፣ ሁለት የአስተዳደር ሠራተኞች እና አንድ መምህር ላይ እርምጃ ወሰደ
    • የጋምቤላ፣ ቦንጋ እና አርባምንጭ ዩኒቨርሲቲዎች የተማሪዎች ጥያቄዎች በተለያዩ ሀይሎች ሴራ እንዳይጠመዘዝ አስቀድመው በመሥራታቸው የመማር ማስተማር ሂደቱ በሰላማዊ ሁኔታ መቀጠሉን አስታወቁ

    የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ሴኔት ታህሳስ 27 ቀን 2012 ዓ.ም. ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በ2012 ዓ.ም. በተደጋጋሚ በተፈጠረው የጸጥታ ችግር የተለያየ ተሳትፎ በነበራቸው ተማሪዎች ላይ የሚከተሉትን ውሳኔዎች ወስኗል።

    1. ሁለት (2) ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ ከትምህርት ገበታቸው እንዲሰናበቱ፣
    2. ሰባት (7) ተማሪዎች እያንዳንዳቸው ለሦስት (3) ዓመት ከትምህርት ገበታቸው እንዲታገዱ፣
    3. ስምንት (8) ተማሪዎች እያንዳንዳቸው ለሁለት (2) ዓመት ከትምህርት ገበታቸው እንዲታገዱ፣
    4. አንድ (1) ተባሮ የነበረ (በወቅቱ የዩኒቨርሲቲው ተማሪ ያልነበረ) ነገር ግን በተፈጠረው የጸጥታ ችግር ውስጥ ተሳታፊ የነበረ ዩኒቨርሲቲው ክስ መስርቶ ግለሰቡን በሕግ ተጠያቂ እንዲያደርግ፤

    በመጨረሻም በወቅቱ ለሴኔቱ ውሳኔ ለቀረበ ተጨማሪ ስልሳ ዘጠኝ (69) ተማሪዎች ዲሲፕሊን ጉዳይ ላይ ተወያይቶ ጥፋታቸው በሂደት ተጣርቶ ወደ ፊት እርምጃ እንደሚወሰድባቸው እንዲሁም በቀጣይ በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በተፈጠረው የጸጥታ ችግር በተለያየ መልኩ ተሳታፊ የነበሩ የዩኒቨርሲቲው ሠራተኞች ላይ እንደየጥፋታቸው እርምጃ እንደሚወሰድ አቅጣጫ ተቀምጧል።

    በተያያዘ ዜና የጋምቤላ፣ ቦንጋ እና አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲዎች የተማሪዎች ጥያቄዎች በተለያዩ ሀይሎች ሴራ እንዳይጠመዘዝ አስቀድመው በመሥራታቸው የመማር ማስተማር ሂደቱ በሰላማዊ ሁኔታ መቀጠሉን አስታወቁ።

    ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሃይማኖትና የብሄር ተኮር ግጭቶች ማዕከል ሆነው እና የጸጥታ ችግር ተጋርጦባቸው ጥቂት የማይባሉ ዩኒቨርሲቲዎችም በተደጋጋሚ ትምህርት ለማቆም ተገደዋል፤ በተማሪዎች ላይም ጉዳት አጋጥሟል። የግጭት መንስኤዎች የተለያዩ ሲሆን አንዳንዶቹ ከአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮች ጋር የተያያዙ ናቸው።

    ወሎ ዩኒቨርሲቲ የመማር ማስተማር ሥራውን አውከዋል ያላቸውን 332 ተማሪዎች፣ ሁለት የአስተዳደር ሠራተኞች እና አንድ መምህር ላይ እርምጃ መውሰዱን አስታወቋል።

    ከፀጥታ መዋቅሩ ጋር በመሆን ባለፉት ሁለት ወራት ችግር ፈጣሪዎችን ለመለየት በተከናወነው ጠንካራ የሕግ ማስከበር ሥራ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሥራው እንዳይቀጥል ፍላጎት ባላቸው 332 ተማሪዎች፣ ሁለት የአስተዳደር ሠራተኞች እና አንድ መምህር ላይ እርምጃ መወሰዱን ዩኒቨርስቲው አስታውቋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር አባተ ጌታሁን ለ ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደገለጹት፥ ዩኒቨርሲቲው በሰላማዊ የመማር ማስተማር ሥራ ተመራጭ እና ተምሳሌት ሆኖ ቆይቷል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በብሔር እና በሀይማኖት ሽፋን በተፈጠረ አለመረጋጋት የመማር ማስተማር ሥራው ባለፉት ወራት ውስጥ ለሦስት ጊዜ መቋረጡን አውስተዋል።

    በዚህም የሁለት ተማሪዎች ሕይወት ማለፉንና በተወሰኑት ላይ ደግሞ የአካል ጉዳት መድረሱን ጠቅሰው፣ ይህም ከአንድ የእውቀት ምንጭ ተቋም የማይጠበቅ አሳፋሪ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል።

    የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ጴጥሮስ ወልደጊዮርጊስ ግን በከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ የሚታዩት የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮች ለግድያ የሚያደርሱ እንዳልሆኑ ይናገራሉ። አብዛኛዎቹ ተማሪዎች ሰላም ወዳድ መሆናቸውን የሚገልጸው ዩኒቨርሲቲው የመማር ማስተማሩን ለማወክ የሞከሩ ጥቂት ተማሪዎች እንዳልተሳካላቸው የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ገልፀዋል።

    ከ4 ሺህ በላይ ተማሪዎችን እያስተናገደ የሚገኘው ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲም ሁነኛ የጸጥታ ችግር ሳያጋጥመው የመማር ማስተማሩ ሂደት በሰላማዊ ሁኔታ ከቀጠለባቸው ዩኒቨርሲቲዎች መካከል ተጠቃሹ ነው። ዩኒቨርሲቲው ባወጣው መርሃ ግብር መሠረት የአንደኛ መንፈቅ ዓመት ትምህርትን ወደማገባደድ መቃረቡን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ኡጁሉ ኦካክ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተናግረዋል።

    የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛም የመማር ማስተማር ሂደቱ በሰላማዊ ሁኔታ መቀጠሉን አንስተዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ በተለይም ተማሪዎች በተደጋጋሚ የሚያነሷቸውን የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመቅረፍ ካልተቻለም ለማሻሻል ጥረት ማድረጋቸውን አስታውቀዋል።

    ተማሪዎችን ተቀብለው ማስተናገድ ከጀመሩ በኋላ የሚነሱ ቅሬታዎችን በአጭሩ ለመፍታትም ከተማሪዎች ጋር የሰከነ እና የሰለጠነ ውይይት ማድረጋቸውን የአርባምንጭ እና ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንቶች ገልፀዋል። ለዚህም ተማሪዎች እያንዳንዱ ጥያቄ በሂደት እንደሚፈታ ማመናቸውና አርቆ ተመልካችነታቸው ሰላማዊ ሁኔታው እንዲቀጥል ትልቁን ድርሻ እንደተወጣም ተጠቁሟል።

    የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገኙባቸው አካባቢዎች የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሀይማኖት መሪዎች እና ወጣቶች በሰላማዊ የመማር ማስተማሩ ሂደት ላይ የራሳቸውን ሚና እንዲወጡ መደረጉንም ዩኒቨርሲቲዎቹ የገለጹት።

    የዩኒቨርሲቲዎቹ ባለቤት የሆነው ማኅበረሰብ ተማሪዎቹን እንደ ራሱ ልጆች ተመልክቶ እንዲጠብቃቸው የተሰራው ሥራም ውጤታማ እንደነበር ነው ፕሬዚዳንቶቹ የገለጹት።

    ተማሪዎችም በሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች የታዩ አሰቃቂ ተግባራት እንዳይደገሙ በጋራ መሥራት አለባቸው፤ ከስሜታዊ ድርጊትም ሊታቀቡ ይገባልም ነው ያሉት። የብዙሃኑን ሰላም ለመጠበቅ ጥቂት በጥባጮችን አደብ ማስገዛት ይገባል ብለዋል በመልዕክታቸው።

    ምንጮች፦ ድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ / የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    በዩኒቨርሲቲዎች የጸጥታ ችግር

    Semonegna
    Keymaster

    ባሕር ዳር (ሰሞነኛ) – ዶክተር መሐሪ ታደሰ ወልደጊዮርጊስ አቶ አየነው በላይን በመተካት የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ሆነው ተሾሙ።

    ዶክተር መሐሪ ታደሰ ወልደጊዮርጊስ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪያቸውን ደግሞ በአሜሪካው ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኖርዝ ቴክሳስ (The University of North Texas) ተከታትለዋል። በዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቴክሳስ አት ኦስተን (The University of Texas at Austin) እና በሌሎችም በተመራማሪነት ማገልገላቸውም ታውቋል። የተለያዩ የምርምር ሥራዎችን በአሜሪካና ካናዳ ማቅረባቸውም በግለ ታሪካቸው ተብራርቷል።

    ዶክተር መሐሪ የተለያዩ ዓለማቀፍ የሙያ ማኅበራት አባል መሆናቸውም ነው የተገለጸው። የአሜሪካ የስታትስቲክስ ማኅበር (American Statistical Association)፣ የአሜሪካ የትምህርት ጥናት ማኅበር (American Educational Studies Association)፣ የተቋማዊ ጥናት ማኅበር፣ የከፍተኛ ትምህርት ጥናት ማኅበር፣ የደቡብ ምዕራብ የትምህርት ጥናት ማኅበርና የቴክሳስ የትምህር ጥናት ማኅበር አባል እንደሆኑም ነው የተገለጸው።

    ከ13 ዓመታት የአሜሪካ ቆይታ በኋላ ባለፉት አምስት ዓመታት በኢትዮጵያ በተለያዩ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በምርምርና የተለያዩ ትምህርቶችን በማስተማር እንደቆዩም ተገልጿል፤ በተለያዩ የመንግሥት ተቋማት በኃላፊነት ደረጃ ማገልገላቸውም ነው የተነገረው።

    ዶክተር መሐሪ ታደሰ ወልደጊዮርጊስን ልምዳቸውንና የአመራር ብቃታቸውን ግምት ውስጥ በማስገባት የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ታኅሳስ 25 ቀን 2012 ዓ.ም. ማካሄድ በጀመረው መደበኛ ጉባኤው የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አድርጎ ሾሟቸዋል።■

    ከአማራ ክልል ሳንወጣ፥ በደብረ ብርሃን ከተማ የሚገነባው የበላይ ባለ ኮኮብ 5 ሆቴልና ቢዝነስ ሴንተር ፕላን በዘርፉ ባለሙያዎች ተገመገመ። የፕሮጀክቱ ዲዛይንና አማካሪ የሆኑት አቶ ነቢዩ ሰለሞን እንዳብራሩት፥ ሆቴሉ በ3,690 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ እንደሚያርፍ፣ 3 ደረጃቸውን የጠበቁ የመሰብሰቢያ አዳራሾች፣ 120 የመኝታ ክፍሎች፣ 2 ሬስቶራንቶች፣ ባር፣ ጂም እና ሌሎች አገልግሎቶችን የሚሰጡ ክፍሎች እንደሚኖሩት፣ ዲዛይኑ አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ ያደረገ እንደሆነ ገልጸዋል።

    የደብረ ብርሃን ከተማ ህንጻ ሹም ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አምሳሉ መኮንን በበኩላቸው በቀረበው ዲዛይን መሠረት ገንቢ አስያየት በመስጠት ሆቴሉ ከታሰበው በላይ ተሻሽሎና ዳብሮ እንዲሠራ ባለሙያዎች የድርሻቸውን አንዲወጡ አሳስበዋል።

    የውይይቱ ተሳታፊዎችም የቡና ስኒ በዲዛይኑ ላይ መካተቱ ከደብረብርሃን ጋር ምን ያገናኘዋል? የሠራተኞች ማረፊያ ክፈል፣ ሕፃናት መዝናኛ፣የመዋኛ ገንዳ መካተት አለበት የሚሉና እና ሌሎችም በርካታ ሀሳብ አስተያየቶች ተሰጥተዋል። በመድረኩ ከደብረብርሃን ዩኒቨርስቲ፣ ከኢንቨስትመንት፣ ከህንጻ ሹም፣ ከህንጻ ዲዛይን አማካሪዎች፣ ከባህል ቱሪዝም ጽሕፈት ቤቶች የመጡ የሥራ ኃላፊዎችና የዘርፉ ባለሙያዎች ተሳታፊ ሆነዋል።

    የበላይ ባለ 5 ኮኮብ ሆቴልና ቢዝነስ ሴንተር ከ2 መቶ ሚሊየን ብር በላይ በጀት እንደተያዘለት የመሠረት ድንጋው ሲጣል መገለጹ የሚታወስ ነው።

    ምንጮች፦ የአማራ ብዙኃን መገናኛ ድርጅት እና የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዶክተር መሐሪ ታደሰ

    Anonymous
    Inactive

    ጎንደር (ሰሞነኛ) – ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በተከሰተው አለመርጋጋት በተለያየ ደረጃ ተሳታፊ ሆነው በተገኙ ተማሪዎች፣ መምህራን፣ የአስተዳደር ሠራተኞች እና የጤና ባለሙያ ከቀላል እስከ ከባድ እርምጃ ወሰደ።

    ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በተከሰተው አለመረጋጋት የመማር ማስተማር ሂደቱ ሲቆራረጥ መቆየቱ ይታወቃል። በዚህም መሠረት በዩኒቨርሲቲው ሰላም እንዲሰፍን፣ ዩኒቨርሲቲው ሲሠራቸው ከቆየው ሰፊ ተግባራት በተጨማሪ ከፌደራል መንግሥት የተላኩ ልዑካን በዩኒቨርሲቲያችን ውስጥ ከሚገኙ ተማሪዎች፣ መምህራን፣ የጤና ባለሙያዎች፣ የአስተዳደር ሠራተኞች፣ የፀጥታ አካላት እንዲሁም ከከተማው ማኅበረሰብ ተወካዮች ጋር ሰፊ ውይይት ሲያደርጉ ቆይተዋል።

    በእነዚህ ውይይቶችም አንዳንድ መምህራን፣ ተማሪዎች፣ የአስተዳደር ሠራተኞች እና የጤና ባለሙያ የተከሰተውን ሁከት በማነሳሳት፣ የሕይወት እና የአካል ጉዳት እንዲደርስ በተለያዩ ደረጃዎች አሉታዊ አስተዋፅኦ በማድረግ በተደጋጋሚ ምክር ቢሰጣቸውም ችላ በማለት ተማሪዎች ክፍል እንዳይገቡ ክልከላ በማድረግ እና ትምህርት እንዳይጀመር ተማሪዎችን እና መምህራንን በማስፈራራት፣ ስለት ነገሮችን ግቢ ውስጥ ይዘው በመገኘት፣ አደንዛዥ እፆችን በመጠቀም እና ይዘው በመገኘት፣ ኃላፊነትን ባለመወጣት በሥራ ቦታቸው ላይ ባለመገኘት እና ችግሩ ሲከሰት ሪፖርት ባለማድረግ ሁከት እንዲስፋፋ በማሰብ ሠራተኞችን በማነሳሳት እና ቀስቃሽ መልእክቶችን በመበተን ተሳታፊ ሲሆኑ መቆየታቸውን መረዳት ተችሏል።

    በመሆኑም ታህሳስ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. የዩኒቨርሲቲው ሴኔት ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ በተለያየ ደረጃ ተሳታፊ ሆነው በተገኙ ተማሪዎች፣ መምህራን፣ የአስተዳደር ሠራተኞች እና የጤና ባለሙያ ከቀላል የፅሁፍ ማሰጠንቀቂያ እስከ ሙሉ በሙሉ ከሥራ እና ከትምህርት የማሰናበት እርምጃ ወስዷል።

    በዚህም 2 የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች አንድ ዓመት ከትምህትር ገበታቸው እንዲታገዱ፣ 39 ተማሪዎች ለሁለት ዓመት ከትምህርት ገበታቸው እንዲታገዱ እንዲሁም 11 ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ ከትምህርት ገበታቸው (ከዩኒቨርሲቲው) እንዲሰናበቱ ሴኔቱ ወስኗል።

    ከዚህም በተጨማሪ ለ7 የዩኒቨርሲቲው መምህራን ቀላል የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ፣ ለ3 መምህራን የመጨረሻ የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ፣ ለ3 መምህራን እና ለ8 የአስተዳደር ሠራተኞች እንዲሁም የጤና ባለሙያ ሙሉ በሙሉ ከሥራ እንዲሰናበቱ ሴኔቱ ወስኗል።

    ወደፊትም ትምህርት የመማር ፍላጎት ያላቸው ተማሪዎች መብት ለማስጠበቅ እንዲሁም የዩኒቨርሲቲውንም ሆነ የጎንደር ከተማን ማኅበረሰብ ሰላም ለማስከበር በመሰል ድርጊቶች ሲሳተፉ በሚገኙ ተማሪዎች፤ የአስተዳደር ሠራተኞች፣ መምህራን እና የጤና ባለሙያዎች ላይ ተመሳሳይ እርምጃ እንደሚወስድ ሴኔቱ በጥብቅ አሳስቧል።

    ጎንደር ዩኒቨርሲቲ

    ምንጭ፦ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    Semonegna
    Keymaster

    ደብረ ታቦር (ሰሞነኛ) – “የኪነጥበብ (የአዝማሪ) ሚና ትናንት፣ ዛሬና ነገ” በሚል ርዕስ የሰላም እና የኪነጥበብ መድረክ በርከት ያሉ ታዳሚዎች በተገኙበት በደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ተካሄደ።

    በአዝማሪ ላይ የተሠሩ ጥናቶች እንደሚሉት የአዝማሪዎች አገልግሎት በማኅበራዊ ሕይወት ላይ ብቻ የተወሰነ አልነበረም፡፡ አዝማሪዎች ዘፈንን ከሚከውኑበት ሰውን የማዝናናት ተለምዷዊ ተግባር ባሻገር በኢትዮጵያ ባህላዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ታሪክ ውስጥ ጉልህ ስፍራ ነበራቸው፡፡ ለዚህም ምክንያቱ Kimberlin (1983) እንደሚገልፁት፥ ዘፈን ከኢትዮጵያ ሕዝብ አኗኗር፣ ይትብሃልና ሕይወት ጋር ከፍተኛ ቁርኝት ያለው በመሆኑ ነው፡፡ እንደ Ashenafi (1971) እና Teclehaimanot (1986) ትንታኔ አዝማሪዎች ዋና ሥራቸው ማዝናናት ቢሆንም በተጨማሪ ግን ዜናና ታሪክ ነጋሪዎች፣ ሃያሲዎች፣ የፖለቲካ ተንታኞች፣ መዝጋቢዎች፣ አዝማቾች፣ ሆነው አገልግለዋል፡፡ ይህንን ታሳቢ ያደረገው የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ከሰላም ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር “የኪነጥበብ (አዝማሪ) ሚና ትናንት፣ ዛሬና ነገ” በሚል ርዕስ ታህሳስ 20 ቀን 2012 ዓ.ም. የግማሽ ቀን መርሐ-ግብር አካሂዷል።

    ሰላም ኢትዮጵያ፣ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ እና ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ በመተባበር ባዘጋጁት መድረክ የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር አነጋግረኝ ጋሻው የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን፥ በንግግራቸውም እንደገለፁት ኪነጥበብ ለዕድገት ወሳኝ መሆኑንና፣ ኪነጥበብንና ባህልን ያላካተተ ዕድገት ሙሉ ሊሆን እንደማይችል እና ይህ ሰላምና ባህልን አጣምሮ የያዘ መድረክ የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚከታተለው ገልጸዋል።

    በመርሐ-ግብሩ “የኪነጥበብ (አዝማሪ) ሚና ትናንት፣ ዛሬና ነገ” በሚል ርዕስ የተካሄደ ሲሆን ከውይይቱ በተጨማሪ በመድረኩ የቀረቡት ልዩ ልዩ የኪነጥበብ ሥራዎች ድምቀት ሰጥተውታል።

    በመርሐ-ግብሩ መጨረሻ የመዝጊያ ንግግር ያደረጉት የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ የም/ማ/አ/ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር መንበሩ ተሾመ ባህሉንና ትውፊቱን የማያውቅና እነዚህን ሀብቶቹን የማያለማ ማኅበረሰብ ሁልግዜም አያድግም፤ በመጤ ባህሎች የራሱን ወርቃማ የሆኑ ሀብቶቻችንን እያጣንሁልግዜ የውጭ ናፋቂ እየሆንን፤ ስልጣኔ የሚመስለን የሌሎቹ ነው። ግን እኛ ወርቃማ የሆነ ጥበብ አለን፤ እናም ይኸ ለማኅበራዊ፣ ለኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ፋይዳው ከፍተኛ ለሆነው ባህል ሁላችንም የበኩላችንን ድጋፍ ማድረግ፣ መስመር ማሳየት፣ ስልጠናዎችን ማዘጋጀት ባለሙያዎችን አይዟቹህ ማለት አለብን ሲሉ ገልጸዋል። ባለሙያዎችን ለወደፊቱ እንዴት እንደግፋቸው? እንዴት እናበረታታቸው? የውጭና የውስጥ ሀይሎችን እንዴት እናስተሳስራቸው የሚለውን ለቀጣይ የሁላችንም የቤት ሥራ መሆን አለበት ያሉ ሲሆን በመጨረሻም ለመርሐግብሩ መሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱትን አካላት በሙሉ አመስግነዋል – ዶ/ር መንበሩ ።

    ማጣቀሻዎች፦

    • Ashenafi Kebede: The music of Ethiopia: its development and cultural setting. Dissertation, Wesleyan University. (1971)
    • Cynthia Tse Kimberlin: “The Music of Ethiopia“, in Music of Many Cultures, E. May, ed., Berkeley, Los Angeles: University of California Press. (1983).
    • Teclehaimanot G. Selassie: A brief survey study of the Azmaris in Addis Ababa. Proc. of the International Symposium on the Centenary of Addis Ababa. (1986).

    ምንጭ፦ ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኪነጥበብ

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ኢትዮ ቴሌኮም በዩኒቨርሲቲ የሚገኙ ተማሪዎች የድጋፍ መርሐ ግብርን በ2006 ዓ.ም. የጀመረ ሲሆን የተጠቃሚዎችም ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በ2011 በጀት ዓመት መጨረሻ በ13 ዩኒቨርስቲዎች ለ840 ተማሪዎች ድጋፍ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን ይህ ድጋፍ የሚኖረውን ጠቀሜታ ታሳቢ በማድረግ  በመላው ሀገሪቱ በሚገኙ 45 ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የሚማሩ አራት ሺህ (4000) ተማሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የድጋፍ መርሐ ግብር አዘጋጅቶ ጥሪ የተደረገላቸው የመንግሥት ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንቶች፣ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎችና ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት በተገኙበት ታኅሣሥ 21 ቀን 2012 ዓ.ም.  ይፋ አድርጓል። ለዚህም ፕሮጀክት የሚውል በዓመት ብር 16 ሚሊዮን ብር መድቧል።

    ­­­­­­­­­ኢትዮ ቴሌኮም ማኅበራዊ ኃላፊነቱን (corporate social responsibility) ለመወጣት ትኩረት ሰጥቶ እየሠራባቸው ከሚገኙ ጉዳዮች መካከል የትምህርት ዘርፍ አንዱ ሲሆን ከዚህም ውስጥ በመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ለሚገኙና ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ተማሪዎች ወርኃዊ የገንዘብ ድጋፍ ያደርጋል።

    ኩባንያው በትምህርት ዘርፍ በተለያዩ አካባቢዎች ድጋፍ ለሚሹ ከአሥራ አራት ሺህ በላይ ተማሪዎች የምገባ፣ የትምህርት ቁሳቁስና የኪስ ገንዘብ ድጋፍ እንዲሁም በያዝነው 2012 በጀት ዓመት በመላው ሀገሪቱ በሚገኙ 93 ትምህርት ቤቶች ለሚማሩ 32,974 ተማሪዎች ለእያንዳንዳቸው የአንድ ደርዘን ደብተር ድጋፍ እንዲሁም ከአምስት ሺህ በላይ ለሚሆኑ ተማሪዎች የዩኒፎርምና ቦርሳ ድጋፍ አድርጓል።

    ከዚሁ በተጨማሪ ኢትዮ ቴሌኮም ሴቶች በኢኮኖሚው መስክ ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ ከአዲስ አበባ ክፍለ ከተሞች ለተውጣጡ አንድ መቶ ሴቶች የፋሽን ዲዛይን ሥልጠና እንዲወስዱ ሙሉ ወጪውን በመሸፈን ድጋፍ አድርጓል። የሥልጠና ዕድሉ የተመቻቸው ሴቶች በትምህርት፣ በሥራ እንዲሁም በአጠቃላይ የምጣኔ ሀብት (የኢኮኖሚ) መስኮች ያለባቸውን ተጽእኖ ከግምት በማስገባት ሴቶችን ማስተማር እና በኢኮኖሚ በማብቃት ራሳቸውን እንዲችሉና ልጆቻቸውን ማስተማር እንዲችሉ እገዛ ለማድረግ ነው።

    ኩባንያው በተለይ ከ2011 በጀት ዓመት ጀምሮ በተደራጀ መልኩ ማኅበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት ለዋና ሥራ አስፈጻሚ ተጠሪ የሆነ የሥራ ክፍል በማደራጀት ማኅበረሰባችን ድጋፍ የሚሻባቸውን የትኩረት መስኮች በመለየት የማኅበራዊ ኃላፊነት ሥራዎችን አጠናክሮ በመሥራት ላይ ይገኛል። በዚህም ረገድ:-

    • በሰብዓዊ እና ማኅበረሰብ አቀፍ ድጋፎች ለሴቶች፣ ለአረጋውያን፣ ለሕፃናት፣ ለአካል ጉዳተኞች፣ ለጎዳና ተዳዳሪዎች እና ለመሳሰሉት የማኅበረሰብ ክፍሎች ድጋፍ አድርጓል፤
    • በአረንጓዴ ልማትና በአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ “በአረንጓዴ ኢትዮጵያ ፕሮጀክት” አማካኝነት በመላ ሀገሪቱ ከ17 ሺ በላይ ሠራተኞችን በማሳተፍ ከ1.5 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ተክሎ እንክብካቤ በማድረግ ላይ ይገኛል፤
    • ኢትዮ ቴሌኮም ሸገርን ለማስዋብ ፕሮጀክት ካደረገው የገንዘብ ድጋፍ በተጨማሪ ከቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ እስከ ብሔራዊ ቤተመንግሥት የመንገድ ላይ መብራቶች ድጋፍ በማድረግ አዲስ አበባ ከተማ ውብና ጽዱ ለማድረግ የበኩሉን አስተዋፅኦ በማድረግ ላይ ይገኛል። ከዚህም ጋር በተያያዘ ኩባንያው ሌሎች የሀገራችን ከተሞች ጽዱና አረንጓዴ አካባቢን ለመፍጠር የሚያደርጉትን ጥረት በመደገፍ ላይ ይገኛል፤ ለወደፊትም ይህንኑ አጠናክሮ ይቀጥላል፤
    • በተጨማሪም ኩባንያው ለሌሎች የመንግሥት ፕሮጀክቶችም በሄልዝ ኔት (Health Net)፣ በወረዳ ኔትና (Woreda Net) በስኩል ኔት (School Net) ፕሮጀክቶች አማካኝነት ድጋፉን እያደረገ ይገኛል፡

    ማኅበራዊ ኃላፊነትን የመወጣት ባህል ኩባንያው ብቻ ሳይወሰን በሠራተኞቻችንም በበጎ ፈቃደኝነት የሚሠራ ሲሆን፥ በዚህም ረገድ በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ ሠራተኞቻችን በየአካባቢያቸው በጤና፣ በሰብዓዊነት፣ በትምህርት፣ በአካባቢ ጥበቃ እና በመሳሰሉት ዘርፎች ከፍተኛ አስተዋፅኦ በማድረግ ላይ ይገኛሉ።

    በዩኒቨርሲቲ እንዱስትሪ ትስስር፣ በተመራቂ ተማሪዎች የኤክስተርንሺፕ (externship) እና በተለያዩ ዩኒቨርሲቲ መምህራን የጥናት ፕሮጀክቶች ላይ ኢትዮ ቴሌኮም በሀገራችን ከሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በመተባበር እንደሚሠራ ይታወቃል። በቀጠይም ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በቅንጅት ማኅበረሰቡን የሚጠቅሙ ፕሮጀክቶች ላይ በመሳተፍ የሀገራችን ዜጎች ከሁለቱ ተቋማት የሚጠቀሙበትን ሁኔታዎች በጋራ እንደሚያመቻች ኩባንያው በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቋል።

    ምንጭ፦ ኢትዮ ቴሌኮም/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ኢትዮ ቴሌኮም

    Anonymous
    Inactive

    ዘመን ባንክ ባለፈው የበጀት ዓመት ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች የሰጠው ብድር 7.6 ቢሊዮን ብር የደረሰ ሲሆን፥ ይህም ከቀዳሚው ዓመት የ50.7 በመቶ እድገት የተመዘገበበት እንደሆነ ባንኩ ጨምሮ ገልጿል።

    አዲስ አበባ (አዲስ አድማስ) – ዘመን ባንክ ባለፈው የበጀት ዓመት የትርፍ መጠኑን ወደ 86 በመቶ ማሳደጉን አስታወቀ። ባንኩ በ2011 ዓ.ም. የበጀት ዓመት ከሰጣቸው የአገር ውስጥና የውጭ አገር የባንክ አገልግሎት ዘርፎች ከ1.5 ቢሊዮን ብር በላይ ያገኘ ሲሆን ሊያገኝ ካቀደው የ1 ቢ. 492 ሚሊዮን ብር ገቢ አንጻር፣ የ6 በመቶ ብልጫ እና ከ2010 ዓ.ም. አንፃር የ39 በመቶ ብልጫ ወይም የ447 ሚሊዮን ብር እድገት ማሳየቱን ባንኩ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል።

    ለትርፉ ማደግ እንደ ምክንያት ከተቆጠሩት መካከል የወጪ ቅነሳ፣ የብድር አቅርቦትና በአገልግሎት ዘርፍ የተመዘገበው መልካም አፈፃፀም ዋና ዋናዎቹ እንደሆኑ የጠቀሰው ባንኩ፥ በበጀት ዓመቱ 1 ቢሊዮን 84 ሚሊዮን ብር ወጪ ይኖረዋል ተብሎ የነበረ ቢሆንም በዓመቱ ውስጥ በተሠሩ የወጪ ቅነሳ መርሃ ግብሮች አጠቃላይ ወጪው 947 ሚሊዮን ብር እንዲሆን በማድረግ ትርፋማነቱን ለማሻሻል  እንደረዳውም ተገልጿል።

    ዘመን ባንክ በበጀት ዓመቱ ከታክስ በፊት 635.9 ሚሊዮን ያልተጣራ ትርፍ ያስመዘገበ ሲሆን፥ ይህም ከቀዳሚው 2010 ዓ.ም የ86 በመቶ ወይም የ293.5 ሚሊዮን ብር ብልጫ ማሳየቱንና ከዕቅዱ ደግሞ የ55 በመቶ ብልጫ ያለው አፈፃፀም ሆኖ መመዝገቡን አስታውቋል።

    ባለፈው የበጀት ዓመት ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች የሰጠው ብድር 7.6 ቢሊዮን ብር የደረሰ ሲሆን፥ ይህም ከቀዳሚው ዓመት የ50.7 በመቶ እድገት የተመዘገበበት እንደሆነ ባንኩ ጨምሮ ገልጿል። ባንኩ በበጀት ዓመቱ ካገኘው ከ1.5 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ውስጥ 1 ቢሊዮን  15 ሚሊዮን ከወለድ፣ ከዓለም አቀፍ ባንክና ከሌሎች አገልግሎቶች ያገኘው እንደሆነም አስታውቋል።

    የዘመን ባንክ አጠቃላይ ሀብት እ.ኤ.አ በ2019 ዓ.ም. መጨረሻ 14.7 ቢሊዮን የደረሰ ሲሆን ይህም ከቀዳሚው ዓመት በ18 በመቶ ወይም በ2.2 ቢሊዮን ብር ጭማሪ ማሳየቱ የተገለፀ ሲሆን፥ በ2010 ዓ.ም ከነበረው የ10.2 ቢሊዮን ብር ተቀማጭ ገንዘብ፣ በ2011 ዓ.ም. ወደ 11.6 ቢሊዮን ብር ማደጉም ታውቋል።

    በሌላ በኩል ባንኩ በ2011 ዓ.ም. የበጀት ዓመት የደንበኞቹን የባንክ አገልግሎት ፍላጎት ለማሟላትና በቅርበት ለማገልገል ባደረገው ጥረት፣ የቅርጫፎቹን ብዛት ኪዮስኮችን ጨምሮ ወደ 43 ያሳደገ ሲሆን በተያዘው አዲስ የበጀት ዓመትም ይህንኑ የቅርንጫፍ ቁጥር የማሳደግ ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል።

     SEMONEGNA on Social Media: FacebookTwitterInstagramPinterest | Video | Forum

    ምንጭ፦ አዲስ አድማስ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዘመን ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    ጉራጌ በክልል የመደራጀት ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄ የክልሉ መንግሥት በሰላማዊና በሰለጠነ መንገድ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጠው የብሔሩ ተወላጆች ጠየቁ።

    ኧዣ ወረዳ ፥ጉራጌ ዞን (ሰሞነኛ) – የደቡብ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ርስቱ ይርዳው ከጉራጌ ማኅበረሰብ ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ በጉራጌ ዞን ኧዣ ወረዳ በደሳለኝ ሎጅ ውይይት አካሄዱ። የውይይቱ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት ጉራጌ በክልል የመደራጀት ሕገ መንግሥታዊ መብቱ በሰላማዊና በሰለጠነ መልኩ የክልሉ መንግሥት አፋጣኝ ምላሽ ሊሰጠው እንደሚገባ ጥሪ አቀረቡ።

    በጠንካራ የሥራ ባህሉና ከየትኛውም ብሔር ብሔረሰቦች ጋር ተግባብቶ፣ ተቻችሎና ተከባብሮ የመኖር የቆየ ልማድ ያለው የጉራጌ ብሔር ባለፋት 27 ዓመታት በማኅበራዊ፣ በፓለቲካዊና በኢኮኖሚው ከፍተኛ በደልና ጭቆና ሲደርስበት እንደነበር ያስታወሱት አስተያየት ሰጪዎቹ፥ አሁን በመጣው የሀገሪቱ ለውጥ ፍትሃዊ የኢኮኖሚና የፓለቲካ ተጠቃሚነቱ ሊረጋገጥለት እንደሚገባ ተናግረዋል።

    አክለውም ብዙ ጊዜ በክልል የመደራጀት ጥያቄ ሲነሳ ጉራጌ ክልል አያስፈልገውም የሚል አስተያየት የሚሰጥ መሆኑን የገለጹት ተሳታፊዎቹ፥ ክልል የማያስፈልግ ከሆነ አሁን ያለው የዞን አስተዳደር ለምን ያስፈልጋል፣ ጉራጌ በክልል ቢደራጅ ስጋቱ ምንድን ነው የሚል ጥያቄዎች ተነስተው በመድረክ አወያዮቹ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል።

    የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሀመድ ጀማል እንደገለጹት፥ ዞኑ የብዙ ብሔር ብሔረሰቦች መኖሪያ ስትሆን መንግሥት እንኳ ባይኖር ሕዝቡ ራስ በራሱ መምራት የሚችልበት ቱባ ባህል፣ እሴትና እምነት እንዲሁም ባህላዊ የዳኝነት ሥርዓት ያለው ነው ብለዋል።

    የዞኑ ሰላም ለማስጠበቅ የሀይማኖት አባቶችና ሽማግሌዎች እየሠሩት ያለው ሥራ የሚበረታታ መሆኑን የገለጹት አቶ መሀመድ፥ በቀጣይም የሕዝቦች አንድነት ለማጠናከር በትኩረት ይሠራል ብለዋል። ጉራጌ በክልል የመደራጀት ጥያቄ የሚጠይቀው ለቅንጦት ሳይሆን ሕገ መንግሥታዊ መብቱ ስለሆነ መንግሥት አፈጣኝ ምላሽ እንዲሰጥ አቶ መሀመድ ጠይቀዋል።

    በክብር እግድነት የዞኑ ማኅበረሰብ ለማወያየት የመጡት የደቡብ ክልል የብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ እንደተናገሩት፥ የጉራጌ ብሔር ለሥራ እንጂ ለግጭትና ለንትርክ ጊዜ የሌለው ከየትኛውም ብሔር ብሔረሰብ ጋር ተከባብሮና ተዋዶ በፍቅር የሚኖር ነው ብለዋል። ጉራጌ በክልል እንዲደራጅ ለተጠየቀው ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት አሁን አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ መልስ መስጠት እንደማይችሉና በቀጣይ በመመካከር ለህብረተሰቡ ምላሽ እንደሚሰጠው አቶ ሞገስ ተናግረዋል።

    የደቡብ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ርስቱ ይርዳው ከውይይቱ ተሳታፊዎች ለተነሳላቸው ጥያቄዎች መልስ ሲሰጡ እንደተናገሩት፥ በመስቃን ቤተ ጉራጌና በማረቆ መካከል የተፈጠረው ግጭት ለመፍታት ከሀይማኖት አባቶች፣ ከሀገር ሽማግሌዎች እና ከሌሎችም የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር በመሆን ጥረት እየተደረገ መሆኑንና በአጭር ጊዜ መፍትሄ ያገኛል ብለዋል።

    ክቡር ርዕሰ መስተዳድሩ የሕዝቡ በክልል የመደራጀት ጥያቄ ሲመልሱ እንደተናገሩት፥ ጉራጌ በክልል የመደራጀት መብት እንዳለው ጠቁመው ጥያቄው የሀገሪቱ የለውጥ ጉዞ በማያደናቅፍ መልኩ መሆን አለበት በማለት አቋማቸውን ተናግረዋል።

    በመድረኩ የደቡብ ክልል የካቢኔ አባላት፣ ከአዲስ አበባ የመጡ አመራሮችና ተወላጆች፣ ባለሀብቶች፣ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር አመራሮች ፣ የሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳታፊ ነበሩ ሲል የዘገበው የጉራጌ ዞን አስተዳደር ሕዝብ ግንኙነት ጽህፈት ቤት ነው።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን አስተዳደር ሕዝብ ግንኙነት ጽህፈት ቤት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ጉራጌ በክልል የመደራጀት

Viewing 15 results - 331 through 345 (of 730 total)