Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 151 through 165 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    የሞኝ ለቅሶ መልሶ መላልሶ! ኦሪት ዘህወሓት!
    (ታዬ ዳንደአ)

    የግራ አስተሳሰብ ሁሌ ግራ ተጋብቶ ግራ ያጋባል። ህወሓት የግራ ጁንታ መሆኑ ይታወቃል። የግራ ፖለቲካ ደግሞ ውሸት ሲደጋገም እውነት እንደሚሆን ያምናል። “መስከረም 25/30” የሚደጋገመዉ ለዚህ ይመስላል። ህወሓት ከፈረሶቹ ጋር ብቅ ጥልቅ እያለ ይፎክራል። በሕገ-መንግሥት እና በፌዴራሊዝም ስም ያለቃቅሳል። ከመስከረም 25/30 በኋላ መንግሥት ስለማይኖር “ባለአደራ መንግሥት ከሰማይ ይዉረድልኝ” ይላል። ኢትዮጵያን ወደ ሊቢያ ለመቀየር አቅዶ በሙሉ ኃይሉ ይንደፋደፋል! በእርግጥ ዋነኛ እቅዱ ሰኔ 2012 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ ተሞክሮ በኢትዮጵያዊያን የተባበረ ክንድ ከሽፏል! አሁን ቅዠትን እዉነት ለማድረግ በህወሓት አሻንጉሊቶች በከንቱ ዳንኪራ ይመታል። ይህ በአማርኛ ‘የሞኝ ለቅሶ መልሶ መላልሶ’ ይባላል!

    የህወሓት ህልም ሩቅ ኖሯል። ኢትዮጵያዊያንን ከፋፍሎ እየገዛ ለመቶ ዓመታት ኢትዮጵያን የመጋጥ ግልፅ ዕቅድ እንደነበረዉ ይታወቃል። በዚሁ አግባብ ለ27 ዓመታት በኢትዮጵያዊያን ሰቆቃ ውስኪ እየተራጬ ሲንደላቀቅ ኖሯል። ያ ሁኔታ መጋቢት 2010 ዓ.ም. ላይ አክትሟል። በኢትዮጵያ ሕዝብ የዘመናት ትግልና በለውጥ አመራሩ ቆራጥ ውሳኔ የህወሓት ጉልበት ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ተንኮታኩቷል፤ ነገር ግን እዉነታዉ አልዋጥ ብሎታል። የቀን ቅዠት እዉን እየመሰለዉ አስቸግሮታል! ሁሌ ድምፂ ወያኔ ላይ ወጥቶ “ከመስከረም በኋላ ከኔ ውጭ ሌላ የለም” ይላል። “የለም! የለም!” እያለ ግልፅና ተጨባጭ እዉነታን መሰረዝ ይፈልጋል። መቼስ ከዚህ በላይ የሚገርም በዓለም ላይ ምን ይኖራል? ህወሓት ከነሙሉ ጥርሱና ጥፍሩ በነበረበት ወቅት ታግሎት ያቃተዉን ለዉጥ ከሬሳ ሳጥን ደጃፍ ሆኖ “የለም!” በማለት ብቻ ለመቀልበስ ይሞክራል!

    ዘንድሮ ‘ሰይጣን ለተንኮሉ ቅዱሳን መጽሐፍትን ይጠቅሳል’ የሚባለዉ በግልፅ መታየት ጀምሯል። ህወሓት በምክንያት የኢሬቻ 2013 ዋነኛ አቀንቃኝ ሆኖ ብቅ ብሏል። በኢሬቻ አስታኮ አዲስ አበባ ላይ ተጀምሮ አዲስ አበባ ላይ እንዲያልቅ ታቅዶ የከሸፈዉን ጦርነት ዳግም ለማወጅ ፈልጓል! ፍላጎቱን ለማሳካት ደግሞ በኦሮሞ ስም የሚነግዱ አሉላ የሚቀልባቸዉን ፈረሶች አዘጋጅቷል! በፈረሶቹ በኩል የኦሮሞ ወጣት ኢሬቻን አሳቦ በነቂስ በመዉጣት ሸገር ላይ እንዲረብሽ ይቀሰቅሳል። በዲጂታል ወያኔ ደግሞ “ኢሬቻ የሰይጠን አምልኮ ነዉ” እያለ በአማራ ስም ያሰራጫል። የኦሮሞን ሕዝብ ‘ጋኔን’ ያለዉ ህወሓት መሆኑ ግን ይታወቃል። በተጨማሪም “ኢሬቻ አዲስ አበባ ላይ መከበር የለበትም!” እያለ በሌላዉ አሻንጉሊቱ በኩል የሸገር ወጣቶችን ይቀሰቅሳል። ኢሬቻ 2009ን የዘነጋነዉ መስሎታል። ያኔ ቢሾፍቱ ላይ በአንድ ቀን ብቻ ከ700 በላይ የኢሬቻ ታዳሚ ኦሮሞዎች በወያኔ አግዓዚ ገደል ውስጥ ተጥለዉ ሞቷል። በዚያ ወሳኝ ወቅት “የኦሮሞ ደም ደሜ ነዉ” ያሉትን የጎንደር ወጣቶች ታሪክ መዝግቧል። ኢሬቻን መደገፍ እና ማሞገስ ከቁርጥ ቀን ወገኖች ያምራል! ዛሬ ወያኔ በግራና በቀኝ የሚያጫውታቸዉን አሻንጉሊቶች ማን ይሰማል?

    ታዲያ በመጨረሻ ምን ይሆናል? ውሾቹ እየጮሁ ግመሉ ይጓዛል! ባቡሩ ፍጥነቱን እና አቅጣጫዉን ጠብቆ ወደፊት ይገሰግሳል። ኢትዮጵያዊያን ለዘመናት በከፈሉት ውድ ዋጋ የመጣዉ ለውጥ ከመስከረም 25/30 በኋላም ተጠናክሮ ይቀጥላል! የተቋማት ግንባታ እና ብሔራዊ ውይይት መሠረት ይይዛል። በዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት ይፈጠራል። ህወሓት ሲያበላሸዉ የነበረዉ ብሔራዊ ምርጫም በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ግልፅ፣ አሳታፊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ ይከወናል። የማይኖረዉ ህወሓት እና ተፅዕኖዉ ብቻ ይሆናል። ጓድ ህወሓት ቀስ እያለ ወደ መቃብሩ ጠጋ ጠጋ ይላል! በትግራይ ላይ ጠባሳ ሳይጥል፤ ማንም ሳይነካዉ ራሱን ችሎ ይሞታታል! የትግራይ ሕዝብም እንደወገኖች የነፃነትን አየር ይተነፍሳል! አሉላ ፈረሶቹን የሚቀልብበት መኖ ያጣል። በዚያዉ ጋብቻዉ ለአንዴና ለመጨረሻ ግዜ ይፈርሳል። አሻንጉሊትም አስታዋሽና አጫዋች ያጣል! የሴራና የሸር ሥራ ብኩን ይሆናል። የሌብነት፣ የውሸት፣ የፅንፈኝነት እና የክፋት ዘመን ያበቃል! እዉነት እና ዕዉቀት መርህና መመሪያ ይሆናል! የኢትዮጵያ ኅብረ-ብሔራዊ አንድነት እና ብልጽግና ደግሞ እየጎለበተ ይሄዳል! የኢትዮጵያ ሕዝብ ወንድማማችነትን መሠረታዊ መርሁ አድርጎ በድል ላይ ድል ይጎናጸፋል! ይህ ቃል ነዉ! ቃል ይነቅላል! ቃል ይተክላል! አሜን!!

    ታዬ ዳንደአ

    አቶ ታዬ ዳንደአ የኦሮሚያ ብልፅግና ፓርቲ ቃል አቀባይ ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    አቶ ታዬ ዳንደአ

    Semonegna
    Keymaster

    ኢዜማ በአባላቱ ላይ እየደረሰ ስላለው እስር እና እንግልት ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በደብዳቤ አቤቱታውን አቀረበ

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ብሔራዊ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ማክሰኞ፥ መስከረም 19 ቀን 2013 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ በተለያዩ ክልሎች በአባላቱና በደጋፊዎቹ ላይ እየተፈፀሙ ስላሉ እስር እና እንግልቶች ውይይት ካደረገ በኋላ የጉዳዩን አሳሳቢነት በመረዳት ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ድብዳቤ እንዲፃፍ ውሳኔ ማስተላለፉን ተከትሎ ደብዳቤው እንደተፃፈና ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እንደተላከ የኢዜማ ድርጅት ጉዳይ ኃላፊ አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ ለዜጎች መድረክ ገለፁ።

    ኃላፊው፥ ኢዜማ ምሥረታውን ካደረገበት ጊዜ አንስቶ እዚህም፣ እዚያም ግጭቶች ይከሰቱ እንደነበርና አብዛኛዎቹ ቦታዎች ላይም የጸጥታ ችግር እንደነበር አስታውሰዋል። ፓርቲያቸው በእነዚህ ችግሮች ውስጥ በማለፍ አባላቶቹን በማደራጀት መዋቅሮቹን ሲዘረጋ እንደነበር አውስተዋል። “በማደራጀት ሂደት ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች የጸጥታ ችግር ይገጥመን ነበር” ያሉት አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ፥ የተለያዩ ኢ-መደበኛ የሆኑ አደረጃጀቶች መዋቅሮቻችንን እንዳንዘረጋ የተለያየ ጫና ያሳድሩብን ነበር ብለዋል።

    “የተለያዩ ፈተናዎች ነበሩ፤ በእነዚህ ፈተናዎች ውስጥ ታልፎ ነው እዚህ ደረጃ የተደረሰው። ለዚህም በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ አባሎቻችን ብዙ ዋጋ ከፍለዋል›› ያሉት ድርጅት ጉዳይ ኃላፊው፥ በአባላቶቻቸውና በደጋፊዎቻቸው ላይ የሚደርሰው እንግልት፣ እስር እና ጫና ከመቀነስ ይልቅ እየተባባሰ በመምጣቱ የተነሳ ለሚመለከተው አካል ማሳወቅ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ጉዳዩን እንዲመረምርና ችግሩ በአፋጣኝ መፍትሔ እንዲያገኝ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ደብዳቤ መፃፍ አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱን አስረድተዋል።

    “አባላቶቻችሁ ሲታሰሩ አልያም እንግልት ሲደርስባቸው ብዙም ስትሉ አይደመጥም አሁን ምን ተፈጥሮ ነው ደብዳቤ ለመፃፍ የወሰናችሁት?” በሚል ከዜጎች መድረክ (በኢዜማ ሕዝብ ግንኙነት የሚዘጋጅ ሳምንታዊ ጋዜጣ) ለተነሳላቸው ጥያቄ ኃላፊው ሲመልሱ፥ “የተለያዩ ፈተናዎች ሲገጥሙን ችግሩን ወደ አደባባይ በማውጣት ችግሩ ይፈታል የሚል እምነት የለንም። አሁንም ቢሆን ችግሩን ከመፍታት አንጻር ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ቁጭ ብሎ በመነጋገር እንዲፈታ እንፈልጋለን። ከፖለቲካ አተያይ አንጻርም አባሌ ታስሯል እያሉ አባል ለማፍራት አይቻልም። እኛ ሰላማዊ የሆነ ምህዳር ተፈጥሮ ማንኛውም አካል ሳይፈራና ሳይሸማቀቅ በነፃ አባል እንዲሆን ነው የምንሻው። እዚህ ጋር አባሌ እንዲህ ሆኗል፤ እዚህ ጋር አባሌ ታስሯል እያሉ አባል ማፍራት ያሰቸግራል” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    “በብዙ ፈተናዎች ውስጥ አልፈን ነው እዚህ ደረጃ የደረስነው” ያሉት ድርጅት ጉዳይ ኃላፊው፥ ፓርቲያቸው በአሁኑ ሰዓት በመላው ኢትዮጵያ 280 ቢሮዎች እንዳሉትና 435 የምርጫ ወረዳ ላይ አደረጃጀቱን መዘርጋቱን ጠቁመዋል። ፓርቲያቸው ይህንን ሊያሳካ የቻለውም ችግሮች ሲከሰቱ ከመካሰስ ይልቅ በችግሮቹ ውስጥ መውጫን በመፈለግ ላይ በማተኮሩ የተነሳ መሆኑን ተናግረዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በተለያዩ ክልሎች ላይ በሚገኙ አባላትና ደጋፊዎቻቸው ላይ የሚደርሰው እስራትና እንግልት እያየለ በመምጣቱ የተነሳ በደብዳቤ ለሚመለከተው አካል ማሳወቅ አስፈላጊ ሆኖ ስላገኙት ለሚመለከተው አካል አቤቱታቸውን ማስገባታቸውን ኃላፊው አስረድተዋል።

    በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በሚገኙ የኢዜማ አባላትና ደጋፊዎች ላይ እየደረሰ ያለው እስር እና እንግልት እየጨመረ መምጣቱን የሚያነሱት የኢዜማ ድርጅት ጉዳይ ኃላፊ አቶ ዋሲሁን ተስፋዬ፥ በቤንች ማጂ ዞን፣ ቴፒና ጋምቤላ ብቻ ከ30 በላይ አባላቶቻቸው ታስረው እንደሚገኙባቸው ገልፀዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜማ

    ኢዜማ በአባላቱ ላይ እየደረሰ ስላለው እስር እና እንግልት ለምርጫ ቦርድ በደብዳቤ አቤቱታውን አቀረበ

    Semonegna
    Keymaster

    መንግሥት የሰዎችን በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደህነነትና ነጻነት የመጠበቅ እና ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት ይጠብቅ!
    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ – ኢሰመጉ

    • መንግሥት በቤንሻንጉል ክልል የሰዎችን በሕይወት የመኖርና የአካል ደህንነት መብት ይጠብቅ

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 14 ማንኛውም ሰው ሰብዓዊ በመሆኑ የማይደፈርና የማይገሰስ በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደህንነትና ነጻነት መብት እንዳለው በግልጽ ይደግጋል። ይሁንና፥ በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፥ መተከል ዞን፥ ጉባ፣ ዲባጢ፣ ቡለን እና ወንበራ ወረዳዎች ውስጥ ከባለፈው ጳጉሜ ወር ጀምሮ ማንነቸታው ባልታወቁ አካላት ሲደርስ የነበረው ጥቃት፤ መስከረም 14 ቀን 2013 ዓ.ም በዳንጉር ወረዳ፣ በንገዝ ቀበሌ ዳግም ተከስቶ የበርካታ ንጹኃን ሰዎች ሕይወት መጥፋቱን፣ እንዲሁም የአካል ጉዳት መድረሱን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) ከቦታው ካሉ እማኞች ለመረዳት ችሏል። ጥቃቱ እየደረሰባቸው ያሉ ወረዳዎች በኢ.ፌ.ዲ.ሪ መከላከያ ሠራዊት ኮማንድ ፖስት ስር ተይዘው የጸጥታ ማስከበር እርምጃዎች እየተሠሩ ያሉ ቢሆንም፤ አሁንም ግን ተጨባጭ ስጋቶች እንዳሉ ኢሰመጉ ለማወቅ ችሏል።

    በመሆኑም፥ ኢሰመጉ መስከረም 9 ቀን 2013 ዓ.ም ባወጣው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ ይህ መሰሉ ጥቃት ዳግም እንዳይከሰት መንግሥት አስፈላጊና ሕጋዊ የሆኑ የአጭር እና የረዥም ጊዜ እርምጃዎችን በአስቸኳይ እንዲወስድ ማሳሰቡ አይዘነጋም። ስለሆነም፥ በእነዚህ አካባቢዎች ላይ በተደጋጋሚ በንጹኃን ሰዎች ላይ የሚደርሰውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች መንግሥት በከፍተኛ ትኩረት በመመልከት የሰዎችን በሕይወት እና በሰላም የመኖር፣ የአካል ደህነነትና ነጻነት የመጠበቅ ሰብዓዊ መብት በምልዓት እንዲያረጋግጥ ኢሰመጉ ዳግም ጥሪውን ያቀርባል። የችግሩ ስፋት ተባብሶ ከዚህም የባሱ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ከመድረሱ በፊት፥ የፌደራል እና የክልሉ መንግሥት፣ የአዋሳኝ ክልሎች መንግሥታት፣ የሲቪክ ማኅበራት፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና የሀይማኖት አባቶች በአካባቢው ዘላቂ ሰላም ለማስፈን በትኩረት እንዲሠሩ ኢሰመጉ ያሳስባል።

    በተጨማሪም፥ መንግሥት በእስካሁኑ ሕገ-ወጥ ድርጊት የተሳተፉ አጥፊዎችን ለሕግ እንዲያቀርብ፣ ለተጎጂዎች ተገቢውን ካሳ እንዲሰጥ እና የአካባቢውን ሰላም በማስጠበቅ የደረሰውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት መጣራት የሚቻልበት ሁኔታ እንዲያመቻች ኢሰመጉ በጥብቅ ያሳስባል።

    • መንግሥት የዜጎችን ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ ነጻነት ይጠብቅ

    የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ-መንግሥት አንቀፅ 32 (1) ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በመረጠው የሀገሪቱ አካባቢ የመዘዋወር መብት እንዳለው በግልጽ ያስቀመጠ ቢሆንም፤ ዜጎች ለሥራ፣ ለትምህርት፣ ለንግድና ለተለያዩ ጉዳዮች ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብታቸው ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ ተገድቧል። ከመስከረም 11 እስከ መስከረም 14 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ ባሉት ቀናት መነሻቸውን ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች አድርገው ወደ አዲስ አበባ ከተማ ሲጓዙ የነበሩ የሕዝብ ማመላለሻ አውቶብሶች ሰበታ፣ ሱሉልታ፣ ጫንጮ እና ገብረ ጉራቻ ከተሞች ላይ ሲደርሱ በኦሮሚያ ክልል ፖሊስ እና ጸጥታ ኃይሎች ታግደው ወደ አዲስ አበባ እንዳይገቡ መደረጋቸውን ኢሰመጉ በየአካባቢዎቹ ከሚገኙ ከመረጃ ምንጮቹ ለመረዳት ችሏል። በእነዚህ ቀናት በነበረው እንቅስቃሴ ወደ አዲስ አበባ ሲጓዙ ከነበሩ የሕዝብ ማመላለሻ አውቶብሶች መካከል አብዛኛዎቹ በአቅራቢያ ወዳሉ ከተሞች ተመልሰው ለማደር በመገደዳቸው፤ ዜጎች ለከፍተኛ እንግልትና ወጪዎች መዳረጋቸውን ኢሰመጉ ለማረጋገጥ ችሏል።

    ይህን መሰሉ ድርጊት፥ ከአሁን ቀደምም ተከስቶ ጥቅምት 01 ቀን 2012 ዓ.ም መነሻቸውን ከተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች ያደረጉ ከ80 በላይ የሆኑ የሕዝብ ማመላለሻ አውቶቡሶች ‹‹ወደ አዲስ አበባ መግባት አትችሉም›› በማለት ወደ ደጀንና ባህር ዳር ከተሞች እንዲመለሱ መደረጋቸው ይታወሳል። ይህን አስመለክቶም፥ ኢሰመጉ በወቅቱ ጥቅምት 07 ቀን 2012 ዓ.ም ዜጎች ለከፍተኛ እንግልት እንየተዳረጉና ከቦታ ቦታ በነጻነት የመንቀሳቀስ መብታቸው አላግባብ እየተጣሰ መሆኑን የሚገልጽ አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ አውጥቶ ነበር። ስለሆነም፤ ከዚህ በኋላ ተመሳሳይ ዓይነት የመብት ጥሰቶች እንዳይከሰቱ፤ ተጨባጭ የጸጥታ እና ደህንነት ጉዳዮች በሚኖሩ ጊዜ አስቀድሞ ለማኅበረሰቡ በግልጽ በማሳወቅ አስፈላጊና ሕጋዊ የሆኑ እርምጃዎችን ከሕብረተሰቡ ጋር በትብብር በመሥራት ሊፈቱ እንደሚገባ ኢሰመጉ ያምናል።

    ከዚህም በተጨማሪ፥ በተለያዩ የሀገሪቱ አከባቢዎች በልዩ ልዩ ምክንያቶች የዜጎችን ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት አላግባብ የሚገድቡ የመንገድ መዝጋት እንቅስቃሴዎችን እና እርምጃዎችን በየደረጃው ያሉ የመንግሥት አካላት በትኩረት ተመልክተው ሕጋዊ እርምጃዎችን እንዲወስዱ ኢሰመጉ ይጠይቃል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ – ኢሰመጉ
    መስከረም 18 ቀን 2013 ዓ.ም

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) በአፍሪካ የሕዝቦችና የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የታዛቢነት ቦታ አለው፤ የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ፌዴሬሽን (FIDH) አባል፣ የዓለም አቀፍ ጸረ-ሥቃይ ድርጅት (OMCT) አባል፣ የምሥራቅና የአፍሪካ ቀንድ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥበቃ ኅብረት (Defend Defenders) መሥራች አባል ነው።

    የሰዎች በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደህነነትና ነጻነት የመጠበቅና ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት ይጠበቅ

    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ የ2020 አለም አቀፍ (P3) ተጽዕኖ ፈጣሪ ሽልማት አሸናፊ ሆነ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – አሜሪካ፥ ሻርሎትስቪል ከተማ በሚገኘው ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቨርጂንያ ዳርደን የቢዝነስ ኢንስቲትዩት (the University of Virginia, Darden School of Business) ዓለም አቀፍ አጋር ድርጅቶች ጽሕፈት ቤት ኮንኮርዲያ (ኒው ዮርክ) በሚያዘጋጀው ዓለምአቀፍ የተጽዕኖ ፈጣሪዎች ዓመታዊ ጉባዔ ላይ (Concordia Summit) የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ የ2020 “የሕዝብና የግል ተቋማት አጋርነት የተጽዕኖ ፈጣሪዎች” (P3 Impact Award) አሸናፊ በመሆን ተመርጧል።

    የኢትዮጵያ ዓይን ባንክ አሸናፊ የሆነው ከቀረቡት አምስት ዕጩዎች መካከል የተሻለ ተጽዕኖ ፈጣሪ ሆኖ በመገኘቱ መሆኑ ተገልጿል።

    የውድድሩ አሸናፊ የሆነው የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን በዓይን ብሌን ጠባሳ እና ተያያዥ ምክንያት የሚከሰተውን ዓይነ-ስውርነት ለማጥፋት እያደረገ ባለው ከፍተኛ ጥረት እና ለማኅበረሰቡ እያበረከተ ባለው ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንደሆነ ተነግሯል።

    የኢትዮጵያ ዓይን ባንክ “የሕዝብና የግል ተቋማት አጋርነት የተጽዕኖ ፈጣሪዎች” ሽልማት (public-private partnership (P3) Impact Award) ተብሎ የሚጠራውን ሽልማት በማሸነፍ ሰባተኛው ተቋምም ሆኗል።

    በዓለም ዙሪያ ከ 12 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በዓይን ብሌን ጠባሳ ዓይነ-ስውርነት ምክንያት በጨለማ የሚሰቃዩ ሲሆን፥ ከእነዚህ ውስጥ ከ300,000 የሚልቁት ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውንም በመግለጫው ተነስቷል።

    “የሕዝብና የግል ተቋማት አጋርነት የተጽዕኖ ፈጣሪዎች” ሽልማት (P3 Impact Award) ተብሎ የሚጠራውንና በአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዓለም አቀፍ ጥምረት ቢሮ፣ ኮንኮርዲያ በተባለ ተቀማጭነቱን ኒው ዮርክ ከተማ ውስጥ ባደረገ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት እና በዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቨርጂንያ ዳርደን የቢዝነስ ኢንስቲትዩት አማካኝነት የሚሰጠው ይህ ሽልማት የሕብረተሰቡን ችግሮች ለሚፈቱና እና ማኅበረሰባዊ አገልግት ለሚሰጡ የመንግሥት፣ የግል፣ ለትርፍ ያልተቋቋሙ ወይም መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን በማወዳደር የሚሰጥ ሽልማት ነው።

    የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ ከሰሃራ በታች ካሉ ሃገራት ውስጥ በብቸኝነት በሀገር ውስጥ የዓይን ብሌን በመሰብሰብ ለንቅለ-ተከላ ማዕከላት በማሰራጨት ለዓይን ብሌን ንቅለ-ተከላ ድጋፍ እያደረገ ይገኛል።

    ዓይን ባንኩ እስከ ፈረንጆቹ 2019 መጨረሻ ለ2,400 (ሁለት ሺህ አራት መቶ) ወገኖች ንቅለ-ተከላ ተደርጎላቸው ብርሃናቸው እንዲመለስ አድርጓል።

    የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ የብሌን ጠባሳ ዓይነ ስውርነት ለማስወገድ ከአጋር ድርጅቶቹ የኢትዮጵያ ጤና ሚኒስቴር፣ ሳይትላይፍ (SightLife) እና ከሂማሊያ ካታራክት ፕሮጀክት (Himalayan Cataract Project) ጋር በመሆን በአፍሪካ የልህቀት ማዕከል ሆኖ ለመሥራት አልሞ የሚሠራ የማኅበረሰብ ተቋም ነው።

    የዚህን ዜና ዋነኛ ምንጭ (በእንግሊዝኛ) ለማንበብ እዚህ ጋር ይጫኑ

    Eye Bank of Ethiopia የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ

    Anonymous
    Inactive

    ግልፅ ደብዳቤ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት ለክብርት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ
    ነጋችንን እንዳንፈራ ሕግ ተርጓሚው ይፈራ!

    ክብርት ፕሬዝደንት፥ እንደሚያውቁት የኢትዮጵያውያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) ባለፉት 20 ዓመታት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ በጭፍን ከመደገፍ እና ከመቃወም ወጥቶ በምክንያት መቃወም እና መደገፍ የፖለቲካ ባህል፣ አስተሳሰብ እንዲገነባ የራሱን ሚና ሲጫወት የቆየ ፓርቲ ነው። ይሄ ስልጡን የፖለቲካ ባህል እንደምንፈልገው ፍሬ ባያፈራም ቀላል የማይባል የፖለቲካ ባህል ለውጥ ጭላንጭል አይተናል ብለን እናስባለን። ይህን አዲስ ባህል የፈጠረ ፓርቲ ግን ለሱ የሚመጥነውን ያህል ክብር ሊሰጠው ቀርቶ በየዘመኑ የመጡ ገዥዎች አና ጽንፈኛ ፖለቲከኞች በሴራ አላላውስ ብለውታል።

    ኢዴፓ ከለውጡ በፊት ባሉት ሁለት ዓመታት እና ከለውጡ ማግስት ባሉ ሁለት ዓመታት የተቀነባበረ በሚመስል ደረጃ ፓርቲያችንን የማዳከም እና ከፖለቲካው መድረክ እንዲገለል የማድረግ ከፍተኛ ደባ እየተሠራበት ይገኛል። ይህን በፓርቲው ህልውና ላይ የተቃጣውን መሠረተ ሰፊ የማፍረስ እርምጃ በተለያዩ መድረኮች እያሸነፍን እዚህ ብንደርስም፥ አሁንም ድረስ በግፍ የተነጠቅነውን የፓርቲውን ቢሮዎች፣ ንብረቶች ገንዘቦች እና ሰነዶች ለማስመለስ በፍትህ አደባባይ እየታገልን ነው። አሁንም በቢሮክራሲ ውጣ ውረድ እየተንገላታን ነው፤ ባለፉት አራት ዓመታት በፓርቲያችን ህልውና ላይ እየደረሰ ያለውን ፈተና እየታገልን ባለንበት ሁኔታ ይባስ ብሎ የአርቲስት ሃጫሉን ሞት ተከትሎ ሌላ የፖለቲካ ጫና እየደረሰብን ይገኛል። ይኸውም የፓርቲያችን ብሔራዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ልደቱ አያሌው ያለጥፋታቸው የፖለቲካ ጥቃት ሰለባ እንዲሆኑ ተፈርዶባቸዋልል። አቶ ልደቱ በወንጀል ድርጊት ውስጥ መሳተፋቸው በተጨባጭ ማስረጃ እስከተረጋገጠባቸው ድረስ አይያዙ አንልም፤ ለሕግ የበላይነት ሲታገል የኖረ ፓርቲ በዚህ ረገድ ምንም ብዥታ የለበትም። ነገም ከነገ ወዲያም ማንም በፖለቲካ ፓርቲ አመራርነትና አባልነት ስም ከሕግ ማምለጥ አለበት ብለን አናምንም፤ ነገር ግን ፖሊስ እርቸውን አስሮ ማስረጃ ሲፈልግ ሲታይ፣ ማስረጃ ማቅረብ ተስኖት ፍርድ ቤት ልቀቅ ብሎ ሲወስን እምቢኝ ካለ የታሰረው ወንጀል ሠርቶ ሳይሆን ለምን የተለየ አሰብክ ተብሎ እንደሆነ ድርጊቱ ያሳብቃል። ከዚህ በተጨማሪ አቶ ልደቱ መንግሥት ላይ የሰላ ትችት በማቅረባቸውና በመቃወማቸው ብቻ እንደታሰሩ በፍትህ ሂደቱ ላይ የታዩትን ህጸጾች ስለታዘብኩ ነው ለእርስዎ አቤት ማለቴ። አቶ ልደቱ የሃጫሉን ሞት ተከትሎ ሁከት በተቀሰቀሰበት ሰዓት የፌዴራል ፖሊስ ለህይወትህ ያሰጋሃል ብሎ አጅቦ ከቢሾፍቱ ወደ አዲስ አበባ አምጥቷቸዋል። ይሄ ሆኖ ሳለ በፖሊስ የተከሰሱበት እና የተጠረጠሩበት ወንጀል የቢሾፍቱ ከተማ ወጣቶችን አደራጅተሃል፣ በገንዘብ ረድተሃል እና አስተባብረሃል ቢሆንም ተጨባጭ ማስረጃ ፖሊስ ለፍርድ ቤት ሊያቀርብ አልቻለም። በኋላም የተሰጠውን የምርመራ ግዜ በመጨረሱና አቃቢ ሕግም ተጨማሪ የምርመራ ግዜ ባለመጠየቁ ፍርድ ቤቱ በነፃ አሰናብቷቸዋል። ነገር ግን ይህንን የፍርድ ቤት ውሳኔ ሰምቶ ፖሊስ መልቀቅ ሲገባው፥ ከ17ቀናት በላይ በሕገ-ወጥ መንገድ አስሮ ሲያሰቃያቸው ቆይቷል። እኛም በፍትህ ሂደቱ ተስፋ ቆርጠን፣ አቶ ልደቱም ጠበቆቻቸውን አሰናብተው ፌደራል ላይ አካልን ነፃ የማውጣት ክስ ልንመሠርት ስንዘጋጅ ደግሞ ሌላ ክስ አዳማ ላይ ተከፈተባቸው።

    ይሄ ክስ በመጀመሪያው የቢሾፍቱ ከተማ የክስ መዝገብ ላይ ሕገ-ወጥ ሽጉጥ ተገኝቶባቸዋል ተብሎ ማስረጃ ቀርቦበት ውድቅ የተደረገ የክስ ጭብጥ ነው። የሆነው ሆኖ በሕገ-ወጥ መሣሪያ በመያዝ በሚል ምሥራቅ ሸዋ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቢከሰሱም ፍርድ ቤቱ የአቃቢ ሕግንና የጠበቆቻችንን የሕግ ክርከር መርምሮ አቶ ልደቱን በ100,000 (አንድ መቶ ሺህ) ብር ዋስትና ውጭ ሆነው እንዲከራከሩ ወሰነ። እኛም 100,000 (አንድ መቶ ሺህ) ብር አስይዘን ማስፈቻ ትዕዛዝ ለፖሊስ ብንወስድም አሁንም ፖሊስ ትዕዛዙን አልፈፅምም አለ። እኛም ትዕዛዙን ለሰጠው ፍርድ ቤት አቤት ብለን መልስ ሊነገረን ለበነጋታው ቀጠሮ ይዘን መጣን። ነገር ግን ማታ የአቶ ልደቱ ዋስትና እንደታገደ በመገናኛ ብዙኃን ሰማን። በዚህ ሁኔታ አቶ ልደቱ ከልብ ህመም ጋር ተያይዞ የልብ ቀዶ ጥገና ባደረጉበት አሜሪካ ቀጠሮአቸው እንዲያልፍ ተደርጎ፥ ከዚህ በተጨማሪ ካለባቸው የአስም ህመም የተነሳ ለኮሮና ተጋላጭ መሆናቸው በሐኪሞችም በፍርድ ቤቶቹም ታምኖበት ጭምር ውጭ ሆነው እንዲከራከሩ የተደረገው ጥረት በፖሊስ እምቢተኝነት ህይወታቸው አደጋ ውስጥ እንዲወድቅ ተደርጓል። በሂደቱ ሁሉ አቶ ልደቱ እያቀረቡት ያለው ቅሬታ ሁሉ ተቀባይነት እያጣ፣ የፍርድ ቤት ውሳኔ እየተሻረ የፖለቲካ ውሳኔ አሸናፊ እየሆነ ይገኛል። አሁንም እንደቀጠለ ነው። እና በፍትህ አደባባይ አቶ ልደቱ ደግመው ደጋግመው ነፃ ቢሆኑም ፖሊስ አለቅም ማለቱን ሳይ ነው የአቶ ልደቱ እስር ሕግ ጥሰው ሳይሆን በፖለቲካ እስር ነው ብዬ በእርግጠኝነት መናገሬ፤ እንጂማ ሁለቴ ያሸነፈ አይደለም አንድ ግዜም ያሸነፈ ቤቱ እስር ቤት አይሆንም ነበር። ይሄ የሚያሳየው የፍትህ ሥርዓቱ ላይ የበዛ የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት መኖሩን ነው።

    ክብርት ፕሬዝደንት፥ የፍትህ ተቋሙ በእርስዎ መመራት ሲጀምር በፍትህ መጓደል ላለፉት 27 ዓመታት ፍዳውን ሲያይ የነበረው ዜጋ እፎይ ይላል ብዬ በግሌ ተስፋ አድርጌ ነበር፤ ሕግ ተርጓሚው ከሕግ አስፈፃሚው ተፅዕኖ ወጥቶ የሚገባውን ክብር እና የሚወስነውም ውሳኔ በአስፈጻሚው አካል ሳይሸራረፍ ተፈፃሚ ይሆናል ብዬም ነበር። ፍትህ እና ርትዕ በእርስዎ አመራር ይሰፍናል ብዬ በእርስዎ የቀደመ ልምድ ፍፁም ተማምኜ የነበረ ቢሆንም እየሆነ ያለው የተገላቢጦሽ ነው። ፍትህ ከቀደመው ጊዜ በባሰ ችግር ውስጥ መውደቁን እኔ በግሌ በዚች ሁለት ወር በተግባር ባየሁት ነገር አረጋግጫለሁ። እርስዎ የተሰጠዎትን ኃላፊነት ያለምንም ፍርሃት እና ይሉኝታ ለመወጣት ከሞከሩ የፍትህ ሥርዓቱ ወደ መስመር ውስጥ መግባቱ አይቀርም፤ ግን ክብርት ፕሬዝደንት ለተቋማዊ ለውጥና ከታሪክ ተጠያቂነት ለመዳንም የበኩልዎን ይወጡ።

    ክብርት ፕሬዝደንት፥ ዜጋ በፍትህ ሥርዓቱ ተስፋ ሲቆርጥ ለሥርዓት አልበኝነት መንገድ ይከፈታል፤ የሞራል ልዕልና ቦታ አጥቶ ፍትህ በየአደባባዩ ትረገጣለች፤ ዜጋ በራሱ መንገድ ፍትህን ይፈልጋል፤ ፍትህን በራሱ ህሊና ተመርቶ ለመስጠት ይገደዳል። ያኔ እንደ ሀገር ዜጋው ወጥቶ የመግባት፣ ሠርቶ ሀብት ንብረት የማፍራት መብቱ አደጋ ውስጥ ይወድቃል። ስለዚህ እርስዎ የሚመሩት ተቋም ክብርና ሞገሱን ካጣ የሀገር ክብር እና ሞገስ ጠፍቶ እንደ ሀገር የመኖር ህልውናችንም አደጋ ውስጥ ይወድቃል። የመንግሥት መኖር ምልክት የሆነው ሕግና ሥርዓት ጠፍቶ ባለፈው እንዳየነው በየአካባቢው የደቦ ፍርድ ይነግሳል። አቶ ልደቱስ በፖለቲካው ባላቸው ተደማጭነት እና ተሰሚነት ድምፅ የሚሆናቸው ብዙ ነው። በዚህ ሁኔታ ተራው ዜጋ ምን ያህል በፍትህ ሥርዓቱ ፍዳውን ሊያይ እንደሚችል ተገንዝበውታል? ለእርስዎ ተቋም ክብር የሚመጥን የፍትህ ሥርዓት አለ ብለው ያምናሉ? አይመስለኝም ፍትህ እና ርትዕ እንዲሰፍን፣ እንዳይጓደል የበለጠ ሥራ በመሥራት የዳኞችን ክብር ያስመልሱ። ዳኞች የሚፈርዱት ፍርድ በአስፈፃሚው አካል ሲደፈጠጥ ማየት ያሳፍራል፣ ያሸማቅቃል ነገን እንድፈራ ያደርጋል። ነጋችንን እንዳንፈራ ሕግ ተርጓሚው ይፈራ! ስለዚህ ክብርት ፕሬዝደንት፥ ጉዳዩ የአቶ ልደቱን ጉዳይ የፍትህ መጓደል ብቻ አድርገው አይቁጠሩት። በህይወት የመኖር እና ያለመኖር የመብት ጥያቄ ነው እያቀረበ ያለው። በፍርድ ቤት ውሳኔ ሳይሆን በአስፈፃሚው ጡንቻ በህይወቱ ላይ አንድ ነገር ቢደርስስ ማን ነው ተጠያቂው? በተለይ የሃጫሉን ሞት ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል የታዘብኩት ዜጎች ወደ ፍትህ ሳይቀርቡ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ እየተጉላሉ መሆኑን ነው። በየማጎሪያው እየተሰቃዩ ነው፤ የፍትህ ያለ እያሉ ነው። አሁንም እደግመዋለሁ ወንጀል የፈፀመ አይታሰር አልልም፤ ግን ከሕገ-መንግሥቱ ድንጋጌ ውጭ ዜጎች መጉላላት የለባቸውም፤ የተፋጠነ ፍትህ ይሰጣቸው፤ ሰብዓዊ መብታቸው ይጠበቅላቸው። ይህን በሁለት ወር ውስጥ የታዘብኩት ነው። ይህ የሚያሳየው የፍትህ መጓደል በሌሎች ክልሎች ላይም ቀላል በማይባል ደረጃ ችግሩ መኖሩን ነው። በቢሾፍቱና አዳማ ዋስትና ተፈቅዶላቸው ከወር በላይ ፖሊስ አለቅም በማለቱ በእስር የሚማቅቁ ብዙ ዜጎች እንዳሉ ያገኘኋቸው የሕግ ባለሙያዎች አጫውተውኛል። ፍትህ ተጠምተው በየእስር ቤቱ የሚሰቃዩ ብዙዎች ናቸው። ለፍትህ መከበር ሁሉም ሊጮህ ይገባል። ፍትህ በጉልበተኞች ጫማ ሲደፈጠጥ ሥርዓት አልበኝነት ይነግሳልና!

    ክብርት ፕሬዝደንት መዓዛ፥ ይህችን ግልፅ አቤቱታዬን ሰምተው በፍትህ ሥርዓቱ ላይ ነፍስ ይዘሩበታል፤ በየማጎሪያ ካምፑ ያሉ የብዙ ዜጎችን እንባ ያብሳሉ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። አመሰግናለሁ።

    ከከበረ ሰላምታ ጋር!
    አዳነ ታደሰ
    የኢዴፓ ፕሬዝደንት

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የጠቅላይ ፍርድ ቤት ክብርት ፕሬዝደንት መዓዛ አሸናፊ

    Anonymous
    Inactive

    ወለጋ ዩኒቨርሲቲ ለ15 ኛ ዙር 3,608 ተማሪዎችን አስመረቀ
    ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ በትምህርታቸው የላቁ ተማሪዎችን የሚያስተምርበት ትምህርት ቤት ተረከበ

    ወለጋ ዩኒቨርሲቲ በመደበኛ፣ በተከታታይና በርቀት መርሀግብር በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች ያሰለጠናቸውን 3,608 ተማሪዎች መስከረም 14 ቀን 2013 ዓ.ም አስመረቀ።

    በዕለቱ የተመረቁት 3608 ተማሪዎች የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በሀገራችን ከመከሰቱ በፊት ትምህርታቸውን የጨረሱና በበየነ መረብ ትምህርታቸውን በመከታተል ያጠናቀቁ ናቸው። ከእነዚህ ተማሪዎች መካከል 1,139 ተማሪዎች በአካል ተገኝተው ምርቃታቸው ላይ የተካፈሉ ሲሆን፥ ቀሪዎቹ ተመራቂዎች ቤታቸው ሆነው በበየነ-መረብ እና በኦሮሚያ ቴሌቪዥን ኔትወርክ (ኦ.ቢ.ኤን) በቀጥታ ሰርጭት ምርቃታቸውን ተከታትለዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሀሰን ዩሱፍ በምረቃ ሥነ-ሥርዓት ላይ እንደገለጹት፥ ተማሪዎቹ በንድፈ ሀሳብና በተግባር የተሰጣቸውን ስልጠና በአግባቡ በማጠናቀቃቸው ለምረቃ መብቃታቸውን ተናግረዋል። ከተመራቂ ተማሪዎች መካከል ስምንቱ በሦስተኛ፣ 1,153ቱ በሁለተኛና ቀሪዎቹ በመጀመሪያ ዲግሪ የተሰጣቸውን ትምህርት ያጠናቀቁ ናቸው።

    ክቡር ዶ/ር ሀሰን_ዩሱፍ በምረቃው መርሀግብር ላይ ባደረጉት ንግግር ተመራቂዎችን እንኳን ደስ ያላችሁ ካሉ በኋላ፥ ብዙ ውጣ ውረዶችንና ፈተናዎችን በማለፍ ተመራቂዎች ለዚህ በመብቃታቸው እጅግ የሚያኮራ እና የሚያስደስት ነው ብለዋል። ተመራቂዎች በሰለጠኑበት የትምህርት መስክ ማኅበረሰቡን በታሞኝንት፣ በቅንንትና፣ በጥሩ ሥነ ምግባር እና ሀቀኝነት እንዲያገለግሉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

    ክቡር ዶ/ር አበራ ዴሬሳ፥ የወለጋ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ አባልና የዕለቱ የክብር እንግዳ፥ በምርቃት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ንግግር አድርገዋል። ተመራቂዎችን እንኳን ደስ ያላችሁ፤ እንኳን ለዚህ ታሪካዊ ቀን አበቃችሁ ብለዋል። በተለይ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ተጽዕኖ በመቋቋምና በኢንተርኔት ትምህርታችሁን በመከታተል ለዚህ በመብቃታችሁ ጥንካሬያችሁን ያሳያል ሲሉ ተናግረዋል። በትምህርታችሁ ሂደት ያሳያችሁትን ጥንካሬ በተግባር ሥራው አለምም እንድትደግሙና ማኅበረሰቡን በተሰማራችሁበት የሥራ መስክ ሁሉ በቅንነትና በታማኝንት እንድታገለግሉ ሲሉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

    ወለጋ ዩኒቨርሲቲ ባለፉት 14 አመታት ከ44 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በማስመረቅ ለሀገሪቱ እድገት ሁነኛ አስተዋጽዖ ያበረከተ ሲሆን፥ በአሁኑ ወቅትም ክ30 ሺህ በላይ ተማሪዎች በመጀመሪያ፣ በሁለተኛ እና በሦስተኛ ድግሪ መርሀግብር በ159 የትምህርት መስኮች ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ይገኛሉ።

    በሌላ ዜና፥ ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ በኦሮሚያ ሰሜን ሸዋ ዞን በደብረ ሊባኖስ ወረዳ በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት የሚያስመዘግቡ ተማሪዎችን የሚያስተምርበት ትምህርት ቤት መስከረም 13 ቀን 2013 ዓ.ም ተረከበ። ትምህርት ቤቱን ለዩኒቨርሲቲው ያሰረከቡት የዞኑ ትምህርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፀጋዬ ኃይሉ ናቸው።

    አቶ ፀጋዬ በወቅቱ እንዳሉት ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ በወረዳው ሸረሮ ከተማ የተረከበው ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ቀደም ሲል በመሰናዶ ትምህርት ቤትነት ሲያገለግል የነበረ ነው። ትምህርት ቤቱ 420 ተማሪዎችን በአዳሪና ተመላላሽ በመደበኛነት ለማስተማር የሚያስችለውን ቁሳቁስና በጀት በማሟላት ዘንድሮ ሥራ እንደሚጀምር ተመልክቷል።

    የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ምክትል ኘሬዚዳንት ዶ/ር ፀጋዬ ደዮ በተረከቡት ትምህርት ቤት ከስምንተኛ ወደ ዘጠነኛ ክፍል በከፍተኛ ውጤት የሚያልፉ ተማሪዎችን ከዞኑ 13 ወረዳዎች ተቀብለው እንደሚያስተምር ገልጸዋል።

    በትምህርት ቤቱ በቂ ቤተ-መፃሕፍት፣ ቤተ-ሙከራና ሌሎች ለመማር ማስተማር የሚያግዙ ሥራዎችን በማከናወን ለሌሎች ትምህርት ቤቶች አርአያ ተደርጎ እንደሚመቻች ተናግረዋል።

    ዩኒቨርሲቲው በተጨማሪም ተማሪዎች የኮሮና ቫይረስን በመከላከል በትምህርታቸውም ውጤታማ እንዲሆኑ 3,200,000 ብር ግምት ያለው የማመሳከሪያ መፃሕፍትና የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁስ ለዞኑ አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በቅርቡ መስጠቱንም አስታውሰዋል። የሚደረገው ድጋፍ የትምህርት ጥራትን በመጠበቅ በሥነ-ምግባር የታነፀ ሥራ ወዳድ ትውልድ ለማፍራት መሆኑንም ጠቁመዋል።

    ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ በዞኑ ይህን መሰል ትምህርት ቤት ከፍቶ አገልግሎት መስጠቱ ለዞኑ ደግሞ ጎበዝ ተማሪዎች ትልቅ ዕድል መሆኑን የገለፁት የዞኑ ወላጅ መምህራን ሕብረት አባል ወ/ሮ ሌሊሴ ባልቻ ናቸው። ተማሪዎች በተፈጠረላቸው ምቹ ዕድል ለመጠቀም በርትተው ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ የሚያነሳሳ መሆኑንም ተናግረዋል።

    ሌላው አስተያየት የሰጠው የሸረሮ ከተማ የስድስተኛ ክፍል ተማሪ መገርሣ ሁንዴ፥ ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ የተረከበው ትምህርት ቤት በተሻለ አቅምና ቁሳቁስ ተደራጅቶ የተሻለ እውቀት እንዲያገኙ እንደሚያግዛቸው ገልጿል።

    ሰላሌ ዩኒቨርስቱ በማኅበረሰብ አገልግሎት ለአካባቢው ነዋሪዎችና ተማሪዎች የሚጠቅሙ ኘሮጀክቶች ነድፎ ዘንድሮ ተግባራዊ እንደሚያደርግ ከዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ምክትል ኘሬዚዳንት ገለጻ ለመረዳት ተችሏል።

    ምንጮች፦ ወለጋ ዩኒቨርሲቲ እና የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ወለጋ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች ምርቃት እና ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ የተረከበው ትምህርት ቤት

    Semonegna
    Keymaster

    የተባበረችና የተከበረች ኢትዮጵያን ለመገንባት ወደፊት!
    ከባልደራስ – መኢአድ ቅንጅት የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    ኢትዮጵያ ሀገራችን ከገባችበት ምስቅልቅል ፓለቲካዊ ችገሮች ለማውጣት በቅንጅት መሥራት አስፈላጊነቱን የተረዱት የመላው ኢትዮጽያ አንድነት ድርጅት /መኢአድ/ እና ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ /ባልደራስ/ የካቲት 29 ቀን 2012 ዓ.ም በመኢአድ ጽሕፈት ቤት ባደረጉት ስብሰባ ሁለቱ ፓርቲዎች በቅንጅት ለመሥራት ያደረጉትን ስምምነት ለሕዝብ ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል።

    የባልደራስ – መኢአድ ቅንጅት ተመሥርቶ ለሕዝብ ይፋ በተደረገ በቀናት ውስጥ ዓለም-አቀፍ ወረርሽኝ የሆነው የኮሮና ቫይረስ /COVID-19/ ወደ ሀገራችን መግባቱን ተከትሎ የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከ4 ሰው በላይ መሰብሰብ በመከልከሉ 20 አባላት ያሉት የቅንጅቱ ምክር ቤት ስብሰባዎችን ለማድረግ ተቸግሮ ቆይቷል::

    የሁለቱ ፓርቲዎቸ ቅንጅት አላማ በሀገራችን ኢትዮጵያ ያለውን ሰፊ የፖለቲካና የልሂቃን ክፍፍል በማጥበብ፥ ብሎም በሚመጣው ምርጫ ላይ ተቀናጅቶ በመወዳደር አብላጫውን የሕዝብ ድምጽ ይዞ መንግሥት በመመሥረት ሀገራችን ኢትዮጵያ አንድነቷና ሕብረቷ ተጠብቆ እንዲኖር ለማድረግ ብሎም ከፍተኛ የሆኑ ሀገራዊና መዋቅራዊ ችግሮችን በመፍታት ኢትዮጵያችን በሰላምና በልማት ጎዳና ላይ ከፍ ብላ እንድትራመድ ለማድረግ ነው።

    የባልደራስ – መኢአድ የጋራው ምክር ቤት መስከረም 9 ቀን 2013 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ የቅንጅቱን ፕሬዝደንት፣ ምክትል ፕሬዝደንት እና ሥራ አስፈፃሚውን በሙሉ ድምፅ መርጧል።

    በሀገራችን ኢትዮጵያ ለሦስት አስርት ዓመታት በተደረገው መራራ ትግል ውስጥ አቶ እስክንድር ነጋ አድልዎንና ኢፍትሃዊነትን በብዕራቸው በመታገል የሚታወቁት ናቸው። ነገር ግን ዛሬም እንደገና ለእስር የተዳረጉ ሲሆን ይህ ውንጀላና እስር በፖለቲካ አመለካከታቸው ብቻ እንደሆነ የሚያምነው የባልደራስ – መኢአድ ከፍተኛው ምክር ቤት ጥልቅ ውይይት ካካሄደ በኋላ ክቡር አቶ እስክንድር ነጋ በእስር ቤት ሆነውም ቢሆን የባልደራስ – መኢአድ ፕሬዚዳንት እንዲሆኑ በሙሉ ድምጽ ወስኗል። እኚህን የሕዝብ ልጅና መሪ መንግሥት በፍጥነት ከእስር እንዲለቅም ምክር ቤቱ በጽኑ አሳስቧል።

    በሌላ በኩል ምክር ቤቱ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ከ1984 ዓ.ም ጀምሮ ሰፊ ተሳትፎ የነበራቸውና በተደጋጋሚ ለእስር የተዳርጉትን የነፃነት ታጋዩን አቶ ማሙሸት አማረን በምክትል ፕሬዚዳንትነት የመረጠ ሲሆን፥ አቶ ማሙሸት አማረ ለሕግ የበላይነት ለዴሞከራሲ ሥርዓት ግንባታ የከፈሉትን ወደር የሌለው መስዋዕትነትና ቁርጠኝነት የቅንጅቱ ምክር ቤት ያደነቀ ሲሆን፥ በቀጣይነት ትግሉን በመምራት ቅንጅቱ በአሸናፊነት እንዲወጣ ያላሰለሰ ጥረት እንደሚያደርጉ ምክር ቤቱ እምነቱን ገልጿል።

    ምክር ቤቱ ለሌሎች ፓርቲዎችም ጥሪ ያቀረበ ሲሆን፥ ከባልደራስ – መኢአድ ጋር አብሮ ለመሥራት የጠየቁትን ፓርቲዎች በቅርቡ አብሮ ለመሥራት የሚያስችሉ ሥራዎችን እንደሚጀምር የገለጸ ሲሆን፥ ሌሎች ከቅንጅቱ ጋር ለመሥራት ፍላጎት ያላቸውን ፓርቲዎች የሀገራችንን ተጨባጭ ሁኔታ ከግምት በማስገባት ቅንጅቱን እንድትቀላቅሉ ሲል ጥሪውን አቅርቡዋል። መላው የኢትዮጵያ ሕዝብም ከቅንጅቱ ጎን በመሆን ያልተቆጠበ ድጋፉን እንዲሰጥ በታላቅ ትህትና ጥሪውን አቅርቧል።

    ምክር ቤቱ በመጨረሻም በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የመከረ ሲሆን፥ በቅርቡ በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል በንጹሃን አርሶ አደር ወገኖቻችን ላይ ማንነትን መሠረት ባደረገው ጭፍጨፋ ሕይወታቸውን ላጡ ወገኖቻችን የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን እየገለጸ፥ የቅርብ ቤተሰቦቻቸውን ላጡ እና ለመላው ሕዝባችን አምላክ መጽናናትን እንዲሰጥልን እንመኛለን ሲል ተጎጅዎችን ያጽናናል። ምክር ቤቱ ይህንን ማንነትን መሠረት ያደረገ ጭፍጨፋ እያወገዝ፥ መንግሥት ሙሉ ኃላፊንቱን ይወስዳል ሲል አሳስቧል። በወልጋ፣ በሚዛን ቴፒ፣ በሐረር፣ በደራና በሌሎችም አካባቢዎች በተደራጁ ቡድኖች አማካኝነት በዜጎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰ ሲሆን፥ በቀጣይም አስከፊ ጉዳት ከመድረሱ በፊት የመከላከል እርምጃዎች እንዲወሰዱ ምክር ቤቱ ያሳስባል።

    በሌላ በኩል በጎርፍ መጥለቅለቅ በአዋሽ ተፋሰስ አካባቢዎች በተለይም በመተሃራ፣ አፋር፣ ጋምቤላ እንዲሁም በጣና ዙሪያ ባሉ ጉማራና ርብ ወንዞች መሙላት በተከሰተው የጎርፍ መጥለቅለቅ ህይወታቸውንና ንብረታቸው ላጡ ወገኖቻችንም ከልብ ማዘናችንን እየገለጽን፥ መላው ሕዝባችን ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖች በአኩሪ ኢትዮጵያዊ የመደጋገፍ ባህላችን በመደገፍ ኃላፊነታችንን እንድንወጣ ምክር ቤቱ ጥሪውን ያቀርባል።

    ዓለም-አቀፍ የሆነውን የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ /COVID-19/ ወደ ሀገራች መግባቱን ተከትሎ የበሽታውን ወረርሽኝ ለመግታት መላው ሕዝባችን ሳይዘናጋ ራሱን ከወረርሽኙ እንዲጠብቅ ምክር ቤቱ ጥሪውን አቅርቧል።

    በመጨረሻም የሀገራችንን ኢትዮጵያ መፃዒ ዕጣ-ፈንታ የተሻለ ለማድረግ በምናደርገው ወሳኝ ትግል ውስጥ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገር የምትኖሩ የቅንጅቱ ደጋፊዎች የሚጠበቅባችሁን ትግል እንድታደርጉልን ጥሪያችንን እናቀርባለን።

    ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!
    መስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም
    የባልደራስ – መኢአድ ቅንጅት

    ባልደራስ – መኢአድ ቅንጅት

    Semonegna
    Keymaster

    በጉራጌ ዞን የመስቀል በዓል በተለያዩ ዝግጅቶች መከበር ተጀመረ
    (የመስቀል በዓል በጉራጌ ማኅበረሰብ)

    በሀገራችን በድምቀት ከሚከበሩ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ክብረ በዓላት መካከል የመስቀል በዓል አንዱ ነው። የመስቀል በዓል በጉራጌ ማኅበረሰብ ዘንድ ልዩ ቦታ የሚሰጠው እንደመሆኑ፥ በየዓመቱ በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ይከበራል። የዘንድሮውን የዋዜማ ዝግጅት በዞኑ ቸሃ ወረዳ የጠናቃ ቀበሌ ለኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በማያጋልጥ መልኩ የፌዴራል እና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በሀገር ሽማግሌዎች ምርቃት ከመስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ በድምቀት መከበር ተጀምሯል።

    በመክፈቻ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሐመድ ጀማል ታዳሚዎችን እንኳን አደረሳችሁ በማለት “የመስቀል በዓል የኛነታችን መገለጫ ነው፤ የመስቀል በዓል ትውፊታዊም መንፈሳዊም ነው። በመስቀል በዓል የእርስ በእርስ የመተሳሰብ፣ የአብሮነት፣ የፍቅር፣ የሰላም እንዲሆን የመልካም ምኞት ማብሰሪያ አበባ የሚሰጣጡበት ጊዜ ነው። እንዲሁም በሥራም ሆነ በሌላ አጋጣሚ ተራርቆ የቆየ ሰው የሚገናኝበት፣ ዘመድ ከዘመዱ የሚጠያየቅበት፣ የሚረዳዳበት እንዲሁም አዲስ ጎጆ የሚቀለስበት ጊዜ መሆኑ ማኅበረሰባችን ልዩ ቦታ ይሰጠዋል። አያይዘውም በበዓሉ ባህላዊ እሴቶቻችንን በደንብ አልምተን እንደ አንድ የቱሪዝም ገቢ ምንጭ በማድረግ ለሀገራዊ ብልጽግናችን መሠረት የምንጥልበት ነው ብለዋል።

    የመስቀል በዓል ከሀይማኖታዊ ክዋኔ ባሻገር ባህላዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያለው ሲሆን በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት የሚከበር ቢሆንም መስቀል በጉራጌ በተለየ የአከባበር ሁኔታ ይከበራል ብለዋል – አቶ መሐመድ።

    እንደ አቶ መሐመድ ገለፃ እንደ መስቀል ያሉ ቱባ ባህሎቻችን ታሪካቸው ሳይሸራረፍ ለትውልድ በማስተላለፍ ዘረኝነት፣ ጥላቻና ቂም በቀል በማስወገድ የሀገራችን ብልፅግና ለማረጋገጥ  ሁሉም ዜጋ የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ብለዋል።

    መርሀ-ግብሩን በጋራ ያዘጋጁት የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ፤ የጉራጌ ዞን አስተዳደር እና የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር በመተባበር ሲሆን፥ የዚህ ክብረ በዓል አከዋወን በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና ባህል ድርጅት /UNESCO/ ከማይዳሰሱ የሰው ልጅ ወካይ ባህላዊ እሴቶች (“intangible heritages of Ethiopia”) ተርታ መመዝገቡን በማስመልከት ሲሆን፥ በአከባበሩ ሥርዓት ውስጥ ያሉት ትውፊቶች በትውልድ ቅብብሎሹ ውስጥ ተጠብቀው ያለ ምንም ተፅዕኖ ክዋኔዎቹ እየቀጠሉ እንዲሄዱ የማስተማር ዓላማ ያለው እንደሆነ ተነግሯል።

    በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የባህል እሴቶች ልማት ዳይሬክተር ወ/ሮ እስከዳር ግሩም በበኩላቸው፥ ሀገራችን ኢትዮጵያ የበርካታ ባህላዊና ታሪካዊ ሀብት ባለቤት ብትሆንም በተገቢው ማልማትና ማስተዋወቅ ባለመቻላችን ከዘርፉ የምናገኘው ገቢ እንዳላደገ ገልጸዋል።

    አንድነታችን አጠናክረን ሀብቶቻችን ማልማት፣ መጠበቅና መንከባከብ አለብን። ይህ ደግሞ የቱሪዝም ዘርፍ እንዲነቃቃ ያደርገዋል። በተጨማሪም ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር ይቻላል ብለዋል።

    የቸሀ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ፈለቀ የመስቀል በዓል በጉራጌ ሁሉም በድምቀት ከማክበር ባለፈ የጉራጌ እሴት የሚገለፅበት በመሆኑ የረጅም ጊዜ ቅድመ ዝግጅት እንደሚደረግበት በማስታወስ፤ በዓሉንም በድምቀት ለማክበር ሁሉም የቤተሰብ አባል የድርሻውን ኃላፊነት እየተወጣ እንደሚከበር ገልጸዋል።

    ለበዓሉ ማብሰሪያ የጉራጌ ዞን የባህል ቡድንም ያሰናዳቸውን ሙዚቃዊ ክዋኔዎች እንደነ “ጊቻዌ፣ ጊቻዌ”፣ “አዳብና” የመሳሰሉት ተውኔታዊ ክዋኔዎች በሴቶችና ወንዶች የታየበት፣ የሥራ ባህልን፣ ሠርቶ ማደግን የሚያወድሱ፣ የሚያስተምሩ ማሳያዎች፣ ኢትዮጵያዊነትን የሚያቀነቅኑ በአንድነት በአብሮነት ባህላዊ እሴቶች የሚጎለብቱበት ተውኔታዊ ትዕይንቶች የተንፀባረቁበት ነበር።

    የመስቀል በዓል በጉራጌ ማኅበረሰብ

    Anonymous
    Inactive

    ወልቂጤ ከተማ ውስጥ ከ50 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተገነባው ባሮክ ሆቴል ተመርቆ ሥራ ጀመረ
    የዞኑ ኢንቨስትመንት ለማሳደግ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን የጉራጌ ዞን አስተዳዳር አስታውቋል።

    ወልቂጤ (ሰሞነኛ) – በወልቂጤ ከተማ ከ50 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተደረገበት ባሮክ ሆቴል ተመርቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን የጉራጌ ዞን መንግሥት ኮሚኒኬሽን መምሪያ ዘግቧል። ባሮክ ሆቴል ባዘጋጀው የምረቃ ሥነ ሥርዓት ላይ የተለያዩ ተጋባዥ እንግዶች ተገኘተዋል።

    በሆቴሉ ምረቃዉ ላይ የተገኙት የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሀመድ ጀማል ለአንድ ከተማ እድገትና ለዉጥ በኢንቨስትመንት ዘርፍ የሚሰማሩ ባለሀብቶች ሚና የጎላ መሆኑን በማስገንዘብ እንደተናገሩት፥ የዞኑ ኢንቨስትመንት ለማሳደግ ከመቼዉም ጊዜ በተሻለ ሁኔታ አጽንኦት ተሰጥቶ እየተሠራ ነዉ።

    በተለይም ከዚህ ቀደም ይስተዋሉ የነበሩ የኢንቨስትመንት ልማት ሥራዎችን ለማሳደግ እንደ ክፍተት የሚስተዋሉትን የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ በተደረገዉ እንቅስቃሴ አሁን ላይ ባለሀብቶች በዞኑ ኢንቨስት እያደረጉ ይገኛል።

    ይህንንም አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚያስችሉ ሂደቶችም መኖራቸዉንም አቶ መሀመድ ጠቁመዉ፥ በቀጣይ በዘላቂነት የዞኑ ኢንቨስትመንት ለማሳደግ ከባለሀብቶች ጋር እየተሠራ ያለዉን ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም በመግለጽ፤ ባለሀብቶች በዞኑ ባሉ የልማት አማራጮች እንዲሰማሩ አስፈላጊዉን ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።

    የወልቂጤ ከተማ ከንቲባ አቶ እንዳለ ገብረመስቀል፥ በበኩላቸዉ ከዚህ ቀደም በከተማዉ ኢንቨስት ለማድረግ ይስተዋሉ የነበሩ ችግሮችን ለመቅረፍ ባለሀብቶች በማበረታታት ኢንቨስት እንዲያደርጉ እየተሠራ ነዉ ብለዋል።

    ከተማዉን ለማልማት የሚመጡ ባለሀብቶች አስፈላጊዉን ድጋፍ በማድረግ ከዞኑ መንግሥት ጋር በመሆን እየተሠራ መሆኑም በመጠቆም፤ በአሁኑ ሰዓት በሆቴል ዘርፍ የተሰማራዉን ባርክ ሆቴል አገልግሎት መስጠት በመጀመሩ ለሌሎች ባለሀብቶች የሚያበረታታ መሆኑም አቶ እንዳለ ጠቅሰዋል።

    ሌሎች በተለያዩ ዘርፎች ኢንቨስትመንት ለሚሰማሩ ባለሀብቶች የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር በተገቢው መንገድ ተቀብሎ እንደሚያስተናግዳቸው በመግለጽ፥ “ኑ! ተደጋግፈን አብረን እንልማ” የሚል ጥሪ አሰተላልፈዋል።

    የባሮክ ሆቴል ባለቤት አቶ አሰፋ በቀለ በበኩላቸው ሆቴሉ ተጠናቆ አገልግሎት መሰጠት በመጀመሩ ደሰተኛ መሆናቸዉም አስረድተዋል። ሆቴሉ ሙሉ ለሙሉ ሲጠናቀቅ 50 ሚሊየን ብር እንደሚፈጅም ተናግረዉ በሆቴሉም ከ50 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጠርም አስረድተዋል ።

    ባሮክ ሆቴል 39 አልጋዎችና አንድ የስብሰባ አዳራሽ ያካተተ መሆኑን የገለጹት የሆቴሉ ባለቤት አቶ አሰፋ፥ በአካባቢያቸዉ በማልማታቸዉ ደስተኛ መሆናቸዉ እንዲሁም ለተደረገላቸዉ ድጋፍ የከተማ አስተዳደሩና የዞኑ መንግሥት አመስግነዋል።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን መንግሥት ኮሚኒኬሽን መምሪያ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ባሮክ ሆቴል Baroc Hotel Wolkite

    Anonymous
    Inactive

    በወቅታዊ ጉዳዮች ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ መስከረም 9 እና 10 ቀን 2013 ዓ.ም ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ ሕዝባችንን ባጋጠሙት ወቅታዊ ሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎች ላይ ተወያይቶ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፏል።

    1] በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በሕዝባችን ላይ የተፈፀመውን የዘር ጥቃት በተመለከተ፦

    አብን በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በመተከል ዞን ቡለን ወረዳ ከጳጉሜን 1 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት ማንነትን መሠረት አድርገው የተፈፀሙ ጥቃቶችን በተመለከተ ተጨባጭ መረጃዎችን ሲያሰባስብ ቆይቷል። በዚህም ከ160 በላይ ወገኖቻችን በአሰቃቂ ሁኔታ እንደተጨፈጨፉ ተገንዝቧል።

    የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአማራው ሕዝብ ጥንተ ርስቱን ተነጥቆ፣ ሰብዓዊና ዜግነታዊ መብቱ ተገፎ ለሦስት አስርት ዓመታት ለዝርፊያ፣ ለመፈናቀል እና ለተደጋጋሚ የዘር ፍጅት የተጋለጠበት ነው። በተለይም “ለውጥ” እየተባለ በሚጠራው ባለፉት ሁለት ዓመታት ጊዜ ውስጥ በክልሉ ውስጥ ባለው የአማራ ሕዝብ ላይ የሚደረገው የዘር ማጽዳትና ሰብዓዊ ጥቃት ከመቼውም ጊዜ በላይ ተባብሶ ቀጥሏል።

    ንቅናቄያችን ልክ ከሰኔ 22 እስከ 24 ቀን  2012 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በአማራው ሕዝብ ላይ  የደረሰውን ጥቃት አስመልክቶ እንደገለገፀው ሁሉ በቤንሻንጉል ክልል የተፈፀመው ጥቃት ተራ የማኅበረሰቦች ግጭት ወይም የሽፍቶች ድርጊት ውጤት ሳይሆን በአማራ-ጠል ትርክት ላይ የተመሠረተ፣ ስልታዊ የሆነ እና በመንግሥታዊ መዋቅር ጭምር የተደገፈ የሽብርና የዘር ማጥፋት ድርጊት መሆኑን ያምናል።

    በዚህ አሰቃቂ ጥቃት የትህነግ ተቀጥላ የሆኑ በተለያዩ ደረጃዎች የሚገኙ የቤንሻንጉል ክልል መንግሥት ኃላፊዎችን ጨምሮ የአማራ ሕዝብንና የሀገሪቱን ሰላም ለማሳጣት የሚታትሩ ባዕዳንና ውስጣዊ ኃይሎች ያሰማሯቸው የሽብር ቡድኖች እጃቸው እንዳለበት አብን ያምናል።

    የጥቃቱ ፈፃሚዎች ለተከታታይ ቀናት ሕዝባችንን (አማራ/አገው) በማንነታቸው እየመረጡ በአካባቢው ባሉ ትምህርት ቤቶች ውስጥ በኃይል አሰባስበው ለጅምላ ጭፍጨፋ ሲያዘጋጁ የክልሉ መንግሥት መረጃ እና ጥሪ እየቀረበለት ባለመድረሱ፤ የፌዴራል መንግሥቱም ባለው የደኅንነት መረጃ ተመርኩዞ ጥቃቱን ለመከላከል ፈጥኖ እርምጃ ባለመውሰዱ ተጠያቂ መሆን እንዳለባቸው አብን በጥብቅ ያምናል።

    አብን በሕዝባችን ላይ ከእንግዲህ ማናቸውንም ዓይነት ማንነቱን መሠረት አድርገው የሚፈፀሙ ጥቃቶች ሊታገስ የማይችልበት ደረጃ መድረሱን እየገለፀ፤ ለችግሩ አስቸኳይ መፍትሄ ካልተበጀለት ጉዳዩ  ከአማራው አልፎ ታላቅ ብሔራዊ ቀውስ ሊያስከትል እንደሚችል በመገንዘብ፦

    (ሀ) መሣሪያ የታጠቁ ገዳዮችን በመደገፍና እንዳላዩ በማለፍ ለጥቃቱ መዋቅራዊ ከለላ የሰጡና በቀጥታም ሆነ በእጅ አዙር የዘር ማጥፋቱ ተባባሪ የሆኑ የክልሉ ባለሥልጣናት በአስቸኳይ በሕግ ተጠያቂ እንዲሆኑ፤

    (ለ) በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ለሚኖረው ሕዝባችን አስተማማኝ የደህንነት ዋስትና እንዲሰጥ፣ በየአካባቢያቸው የፖሊስና የደኅንነት መዋቅሮች ውስጥ የመሳተፍ መብታቸው እንዲከበር፣ በማኅበረሰብም ደረጃ ደህንነታቸውን የሚያስጠብቁበት አስቸኳይ መፍትኄ እንዲፈለግ፤

    (ሐ) የፌደራል መንግሥቱና ገዥው ብልፅግና ፓርቲ በአማራው ሕዝብ ላይ በሚፈፀሙ የዘር ጥቃቶች ላይ የያዘውን ዳተኝነት እንዲያቆምና ችግሩን ለመከላከልና ከመሠረቱ ለመቅረፍ ተጨባጭ እርምጃ እንዲወስድ፤

    (መ) የአማራ ብልጽግና ፓርቲና የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በአማራ ሕዝብ ላይ በሦስት ወራት ውስጥ ብቻ ሁለት እጅግ አሰቃቂ የዘር ማጥፋት ድርጊቶች ሲፈፀሙ ወንጀሉን በስሙ ከመጥራት ጀምሮ ለችግሩ ዘላቂ መፍትኄ በመፈለግ ረገድ ያሳየው አቅም እና ፍላጎት ከደረጃ በታች መሆኑና ከእንግዲህም ለችግሩ ዘላቂ መፍትሄ ከዚህ አካል ሊመጣ እንደማይችል ሕዝባችን በግልፅ እንዲገነዘበው፤

    (ሠ) ሕዝባችን በተከታታይ ለዘር ማጥፋት እና ዘር ማጽዳት ጥቃቶች የተጋለጠበት የቤንሻንጉል ክልል አማራው ፍጹም ሥነ-ሕዝባዊ አብላጫ እያለው ፖለቲካዊ ውክልና በማጣቱ የተነሳ በመሆኑ ችግሩን በዘላቂነት ለማስወገድ የክልሉ መዋቅር የነዋሪዎቹን መብቶች በሚያረጋግጥ ሁኔታ እንዲከለስ ድርጅታችን አብን ያሳስባል።

    2] በአማራ ክልል የደረሰውን በጎርፍ የመጥለቅለቅ አደጋ በተመለከተ፦

    በአማራ ክልል በዘንድሮ ክረምት ዝናብ ምክንያት በተፈጠሩ የመሬት መንሸራተትና የጎርፍ አደጋዎች በአጠቃላይ በ6 ዞኖች በሚገኙ 36 ወረዳዎች ውስጥ ባሉ 164 ቀበሌዎች በተለያዩ ደረጃዎች የሚገለፁ ጉዳቶች እንዳደረሱ ይታወቃል።

    በተለይ ደግሞ በማዕከላዊ ጎንደር በምሥራቅ ደምቢያ ወረዳ፣ እንዲሁም በደቡብ ጎንደር በሊቦከምከም፣ ደራና ፎገራ ወረዳዎች በከፍተኛ የጎርፍ መጥለቅለቅ በመጠቃታቸው በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወገኖች ከመኖሪያ ቤታቸው ተፈናቅለው በጊዜያዊ መጠለያዎች ይገኛሉ።

    አብን እነዚህ በጎርፍና በመጥለቅለቅ የተፈናቀሉ ወገኖች በአስቸኳይ የእለት እርዳታ እንዲያገኙ የበኩሉን አስተዋፅኦ እንደሚያደርግ እየገለፀ፤ በመላው ዓለም የሚገኙ የድርጅታችን አባላትና ደጋፊዎች፣ መላው የአማራ ሕዝብና ኢትዮጵያውያን ወገኖች ለድጋፍ እጃቸውን እንዲዘረጉ ይጠይቃል።

    በጎርፉ ጉዳት በደረሰባቸው አካባቢዎች ሊነሱ በሚችሉ የወባ እና ሌሎች ውሃ-ወለድ በሽታዎች ሕዝቡ እንዳይጋለጥ ጥንቃቄ እንዲደረግ ይጠይቃል።

    ተጎጂዎች ሰብሎቻቸው እና ንብረቶቻቸው የወደሙባቸው በመሆኑ አፋጣኝ ድጋፍ እና የመልሶ ማቋቋም ተግባራት እንዲከናወኑ፣ ለመጪው ዘመንም የሚያስፈልጋቸውን ሁለገብ እርዳታ የማዘጋጀት ሥራ እንዲሁም ለዘለቄታው በየዓመቱ የክረምት ወቅት ሊከሰቱ ከሚችሉ ተመሳሳይ አደጋዎች ለመጠበቅ ዘላቂ መፍትኄ እንዲፈለግ ይጠይቃል።

    በመጨረሻም በአማራ ሕዝብ ታላቅ መስዋዕትነት የተገኘው ለውጥ አቅጣጫውን በመሳቱ በሕዝባችን ላይ ሥርዓት እና መዋቅር ሠራሽ ጥቃቶቹ ስጋት ደቅነውበት እንደቀጠሉ አብን ይገነዘባል።

    እጅግ ራስ-ወዳድ በሆነው ሰፊ የፖለቲካ ውቅር ውስጥ ጨካኞች እና ያልተገሩ ስብስቦች በአማራው ላይ ጥቃታቸውን ባስቀጠሉበት አግባብ፣ ለኩርፊያቸው እና ለደም ጥማታቸው አማራ ቋሚ ግብር ወይም ማስያዥያ የሚሆንበት የፖለቲካ ድባብ በትግላችን መገፈፍ ይኖርበታል።

    በተፈፀመው የዘር ማጥፋት ወንጀል ውስጥ ያሉ ተዋንያንንና በቸልተኝነትና በሴራ ተባባሪ የሆኑ አካላትን ጭምር ለማጋለጥ እና በኃላፊነት እንዲጠየቁ ለማድረግ አብን እንደሚሠራ በአፅንዖት ለማስገንዘብ ይወዳል።

    በመጨረሻም አብን በቤንሻንጉል ጉሙዝና በኦሮሚያ ክልሎች በአሰቃቂ ሁኔታ የዘር ጭፍጨፋ ወንጀል ሰለባ ለሆኑ ወገኖቻችን የተሰማንን ጥልቅ ሐዘን ለመግለፅ ለመላው የአማራ ሕዝብና ለሕዝባችን ወዳጆች ከነገ ሰኞ መስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም  ጀምሮ እስከ ማክሰኞ መስከረም 12 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ ለሁለት ቀናት በምናደርገው ጥቁር የመልበስ እና ተያያዥ የሐዘን መግለጫ ሥርዓቶች እንዲካፈሉ አብን የአክብሮት ጥሪውን ያቀርባል።

    አንድ አማራ ለሁሉም አማራ ፥ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ!
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) /NaMA/
    መስከረም 9 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ ፣ ሸዋ ፣ ኢትዮጵያ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)

    Anonymous
    Inactive

    በ2013 ዓ.ም የጉራጊኛ የፊደል ገበታ በተመረጡ ትምህርት ቤቶች ለሚያስተምሩ መምህራን በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ስልጠና ተሰጠ

    ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ከጉራጌ ዞን አስተዳደር በጋራ በመሆን የጉራጊኛ የፊደል ገበታ የቅድመ መደበኛ ተማሪዎች ለማስተማር በዞኑ ከተለያዩ ወረዳዎች ለተዉጣጡ መምህራን ስልጠና የሰጠ ሲሆን፤ በቀጣይ የጉራጊኛ ቋንቋ የትምህርት፣ የሚዲያና የሥራ ቋንቋ ለማድረግ የፊደል ገበታዉ ለቅድመ መደበኛ ተማሪዎች መስጠት አጋዥ መሆኑ ተገልጿል።

    በስልጠናዉ ተገኝተዉ ንግግር ያደረጉት የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ፋሪስ ደሊል የሱፍ እንዳሉት፥ የሀገራችን ሕገ-መንግሥት የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች በቋንቋቸዉ የመናገር፣ የመፅሀፍ፣ ቋንቋቸዉን የማሳደግ መብት እንዳላቸዉ አስፍሯል። የቤተ-ጉራጌ ህጻናትም በአፍ መፍቻ ቋንቋቸዉ እንዲማሩ ለማድረግ ይሁንታ ያገኘዉን የጉራጊኛ የፊደል ገበታ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ ለማድረግ እየተሄደበት ያለዉን መንገድ አበረታች ተግባር እንደሆነም አስታዉቀዋል። የጉራጊኛ የፊደል ገበታ የትምህርቱን መስክ መሣሪያ በማድረግና ወደ መሬት ለማውረድ የሰልጣኝ መምህራን ሚና የጎላ እንደሆነም አስረድተዋል።

    ለህጻናት በአፍ መፍቻ ቋንቋ ትምህርት መስጠት አስፈላጊዉን የቤተሰብ ድጋፍ በቀላሉ ለማግኘት የሚያስችላቸዉን ዕድል ለማስፋትና ሳይንሱን ይበልጥ ለመረዳት፥ እንዲሁም አዳዲስ ነገሮችን ለመፍጠር የሚያስችላቸዉ ተመራጭ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴ እንደሆነም አስታዉቀዋል።

    በስልጠናዉ ተገኝተዉ ንግግር ያደረጉት የጉራጌ ዞን ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ መሠረት አመርጋ እንዳሉት፥ የጉራጊኛ ቋንቋ የትምህርት፣ የሚዲያ እና የሥራ ቋንቋ እንዲሆን ለማድረግ የምሁራን ሚና የጎላ ነዉ። ቋንቋ የአንድ ማኅበረሰብ የማንነት መገለጫ እንደመሆኑ መጠን ዜጎች የራሳቸዉ ቋንቋ እንዲማሩ ሕገ-መንግሥቱ ላይ ተደንግጓል ብለዋል።

    ህጻናት በአፍ መፍቻ ቋንቋቸዉ መማር እንዲችሉ ለማድረግና የጉራጊኛ ቋንቋ በማልማት የትምህርትና የሚዲያ ቋንቋ ለማድረግ የተሄደበት ርቀት ከቁጭት ባሻገር ወደ ተግባር አለመገባቱም አስታዉሰዉ፥ የተለያዩ ምሁራን መጽሐፍ በማዘጋጀት በጥናትና ምርምር ሁሉም የበኩሉን ቢያበረክትም ዉጤታማ እንዳልሆነም አንስተዋል።

    ቋንቋዉን ለማልማት የኮምፒዩተር ቀመር (ሶፍትዌር) በመቅረጽ፣ ጥናትና ምርምር በማድረግ እና የተለያዩ ዕቅዶችን በማቀድ የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲና ምሁራን እያደረጉት ያለዉን ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም አስረድተዋል።

    በስልጠናዉ የተሳተፉ አንዳንድ መምህራን በሰጡት አስተያየት፥ የጉራጊኛ ቋንቋ የትምህርትና የሚዲያ ቋንቋ እንዲሆን የበኩላቸዉን ሚና እንደሚወጡም አስረድተዋል።

    በስልጠናዉ ያገኙት እዉቀት በመጠቀም የጉራጊኛ የፊደል ገበታዉ የቅድመ መደበኛ ተማሪዎች ከማስተማር በተጨማሪ በሁሉም የትምህርት ደረጃ እንደ አንድ የትምህርት ዓይነት ቢሰጥ መልካም ነዉ ብለዋል።

    በመጨረሻም ከሁሉም ወረዳዎች ከሚገኙ ሁለት ሞዴል ትምህርት ቤቶች አራት አራት መምህራን ስልጠና ተሰጥቷል ሲል የዘገበዉ የጉራጌ ዞን መንግሥት ኮሚኒኬሽን መምሪያ ነዉ።

    የጉራጊኛ የፊደል ገበታ

    Anonymous
    Inactive

    የገዳዮች ወንድማማችነት

    የገዳዮች ወንድማማችነት
    አገኘሁ አዳነ ድልነሳሁ

    ሰዎች በተለያየ ርዕሰ ነገር ወይም ዓላማ ይወዳጃሉ። የወዳጅነቱ ዓይነት የትየለሌ በመሆኑ ቆጥሬ አልዘልቀውም። በጥቅሉ ግን ማኅበራዊ ፋይዳው መልካም የሆነ ሕብረት ሲሆን ያ ጓድ የለውጥ ሠራዊት/ሐዋርያት “pioneers of change” የሚል ታሪካዊ ቅጽል ያገኛል። እንደሰንደቅ የሚውለበለብ ድል ባያቀዳጅም ዘወትራዊ ሕይወትን በድል የሚያሻግር መደበኛ ወንድማማችነትም ክብር ይገባዋል። ዓላማው በጉልህ የማይታየው የፈንጠዝያ ውድጅትንም ቢሆን የሚለካው አግኝቶ “ቢሰፍሩት” ዋጋው ከፍ ሳይል አይቀርም። ዝንጋኤ እስካላስከተለ ድረስ አብሮነት ደግ ነው።

    እኔን ግርም የሚለኝ የነፍሰ-ገዳዮች “ወንድማማችነት” (Fraternity of Assassins) ነው። ይህ ውድጅት በተለያየ ምክንያት ይመሠረታል። አንዳንዱ እጅግ እውቀታዊ፣ ርዕዮተ ዓለማዊ እና ፍልስፍናዊ መሠረት ያለው ይመስላል። ይሁንና የዚህን ሕብረት መሠረት ቢያናጉት ከሆድ ወይም ከግላዊ ጥቅም የዘለለ ጉዳይ አታገኙበትም። ይህ ቡድን ለስሙ መጠርያ ተጨናቂ፣ ለቀለሙ ማማር ተብረቅራቂ፣ የሆዱን ጩኸት “በሕዝብ አለኝታነት” ደባቂ ነው። ይህን መልከ ቀናነት ለመቀዳጀት የታቀደ “እውነት”የሚመስል ቅደም ተከተላዊና ፈር ያለው ስልት ያዘወትራል። ይህ ውድጅት በነገረ ፆታ፣ በነገረ ወሲብ፣ በሃይማኖት፣ በብሔር፣ በፖለቲካ አቋም፣ በሙያ… በመሳሰለው ታላላቅ ሰብዓዊ ጉዳይ ሁሉ ልታይ፣ ልታይ ይላል፤ ሀገር ያውካል። ይህ ዓይነቱ ውድጅት ይሉኝታ ሲያልፍም አይነካው። እንደደጎች ሁሉ የዚህን ቡድን ደቀ-መዛሙርት በፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ።

    1. የጋራ የሆነችውን ሀገራችንን ጠፍጥፈው ዛሬ የሠሯት ይመስል፥ እኔ ብቻ አውቅልሻለሁ ይሏታል። መሽቶ እስኪነጋ “አያምኗትም”፤ ከቆሙበት ስፍራ በቀር ተጨማሪ ወይም የትየለሌ ግላዊም ቡድናዊም አንጻር፣ ምልከታ፣ አቋም፣ ወዘተ… እንዳለ አይረዱም። ቢረዱም ሌላው ሁሉ የማይረባና የተዋረደ ነው። በጉልህ የሚታያቸው “ከሀገር የሚሰፋው ሆዳቸው” ነው። ሀገር አፍ አውጥተሽ ተናገሪ ቢሏት ስለነዚህ ሰዎች ቃላት የሚያጥሯት ይመስለኛል።

    በሌላ ወገን እነዚህ ሰዎች በሰይፉ መታፈርያ ፍሬው አንዲት የግጥም አንጓ እንዲህ ይታዩኛል:-

    ይህ ዓለም ይህ ዓለም” ይላሉ፥
    ይህን ዓለም ሞልተው እንደኖሩ ሁሉ።

    ሀገሩ የማናየው፣ የማናውቀው፣ የማንሰፍረው፣ የማንለካው፣ የማንገምተው ጭምር ብዙ ጉዳይ አለው፤ ዓለም ሰፊ ነው። ይህን ሲያውቅ ሰው ትህትና ትዘልቀው ይመስለኛል።

    1. ጩኸት መቀማት ዓይነተኛ ጠባያቸው/ፍሬያቸው ነው። በዚህ ጠባያቸው “ራሳቸው ገርፈው ራሳቸው አልቃሽ” በመሆን ከፊት ተሰላፊ ናቸው።
    2. ስለመቃወም መቃወም የሚያስገኘውን ትርፍ ያሰላሉ። ጀብድ እንጂ ጀግንነት አያውቃችውም።
    3. ተቆርቋሪ ከሚመስለው የፊት ገፃቸው ባሻገር ድብቁ ህልማቸው ሆድ መሙላት ወይም ጥቅም ማሳደድ በመሆኑ ያቀዱት ሲከሽፍ ካሸናፊው ጎን ለመሰለፍ እፍረት አታውቃቸውም። የጠበቁት ጥቅም ካልተገኘ ጠላት ለመሆን እንዲሁ አይሰንፉም፤ ይቸኩላሉ።
    4. በእነሱ ዘንድ ወዳጅ ማለት ከጠባብ ሆዳቸው የመንጨ ደካማ ህልማቸውን የሚያገለግል እና ለሙት ህልማቸው ሕይወት መዝራት “ለምን? “ ሳይል የሚሰለፍ agent/object ነው።

    እነዚህ ሰዎች ውድጅት የሚያስፈልጋቸው የሰው ልጅ ለብቻው የማይገፋቸው በርካታ ሕይዎታዊ ጉዳዮች ስላሉት ነው። ወዳጅነት ለብቻ የማይገፋውን ለመግፋት የሚመሠርቱት ስላታዊ ኮንትራት ወይም ‘strategic alliances’ ነው። እንደተራራ የከበዳቸውን ሸክም ካራገፉ በኋላ ግን “ሆዳቸው አምላካቸው” ሆኖ ያርፈዋል።

    በተለምዶ “ባንዳነት” ለፍርፋሪ ተገዝቶ ከውጭ ጠላት ጋር በግልፅ በመወገን ሀገርን መጉዳት/መክዳት ብቻ የሚመስለው ብዙ የዋህ አለ። ነገር ግን ባንዳነት መጠነ ዙሪያው እጅግ ሰፊ ነው። የሀገርን ህልም ለግል ሆድ መሸቀጫ ማድረግ መጠኑም ልኩም ካቅም በላይ ነው።

    የገዳይ ወንድማማቾቹን መስፋፋት በማኅበራዊ ድረ-ገፆች፣ በቴሌቪዥን መስኮቶች፣ በሬዲዮና በመሰለው ሁሉ አዋጅ ነጋሪ ሆነው ማየት አዲስ አልሆን አለ፤ ተለመደ። የምናዋጣት ማንኛዋም “ቅንጣት” ነገ ለሚፈጠረው ሀገራዊ ግዙፍ ምስል አስተዋፅኦ ስላለው እየተስተዋለ ለማለት የተፃፈ። ምክሩ መካሪውን እንዲጨምር ይሁን አሜን!

    አገኘሁ አዳነ ድልነሳሁ

    አቶ አገኘሁ አዳነ ድልነሳሁ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፥ ቲያትርና ጥበባት ኮሌጅ ውስጥ በሚገኘው አለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ትምህርት ቤት ዳይሬክተርና መምህር ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የገዳዮች ወንድማማችነት

    Anonymous
    Inactive

    በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል የተከሰተውን ግድያ እና መፈናቀል አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የተሰጠ ይፋዊ መግለጫ

    አሶሳ (ኢሰመኮ) – የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን /ኢሰመኮ/ (ኮሚሽኑ) በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል በአንዳንድ አካባቢዎች እየታዩ ያሉ የፀጥታ መደፍረሶችን ተከትሎ ያጋጠሙ ክስተቶች እጅግ አሳስበውታል።

    ኮሚሽኑ ከክልሉ ከመተከል ዞን፣ ቡለን ወረዳ አጳር ቀበሌ እንዲሁም ከወንበራ ወረዳ መልካን ቀበሌ እጅግ አሳሳቢ መረጃዎች እየደረሱት ነው። ኮሚሽኑ በጳጉሜ 1 ቀን 2012 ዓ.ም. እንዲሁም ከጳጉሜ 2 አስከ መስከረም 3 ቀን 2013 ዓ.ም. መካከል ቢያንስ ሁለት ጥቃቶች ማጋጠማቸውን ከክልሉ መንግሥት ለማረጋጥ ችሏል።

    በቦታው ላይ ከሚገኝ አንድ መንግሥታዊ ምንጭ መረዳት እንደተቻለው፥ ቢያንስ በሁለት ዙር በደረሱ ጥቃቶች ባልታጠቁ ሲቪሎች ላይ ግድያዎች መፈፀማቸውን፤ እንዲሁም በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መፈናቀላቸውን ኮሚሽኑ ማረጋገጥ ችሏል።

    የክልሉ መንግሥት እንደጠቆመው ከተፈናቃዮቹ መካከል 300 ያህል የሚሆኑት ወደ ቀያቸው የተመለሱ ሲሆን፤ የሀገር መከላከያ ሠራዊት እና የፌደራል ፖሊስ ከክልሉ የፀጥታ ኃይሎች ጋር በመተባበር አካባቢውን ለማረጋጋት እየሠሩ ነው።

    ስለሆነም ኮሚሽኑ፡-

    • በክልሉ ባልታጠቁ ሲቪሎች ላይ የደረሱትን ጥቃቶች፣ ግድያዎች እና መፈናቀሎችን ሙሉ በሙሉ ያወግዛል፤
    • በክልሉ ሰላምና መረጋጋት እንዲኖር በመከላከያ ሠራዊት፣ በፌዴራል ፖሊስ እና በክልል የጸጥታ ኃይሎች ሰላምን ለማስጠበቅ እየተደረገ ያለውን ጥረት ያበረታታል፤
    • በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ሕገ-መንግሥትና እንዲሁም ኢትዮጵያ ተቀብላ ባጸደቀቻቸው የቃል ኪዳን ሰነዶች ማለትም፡ በአፍሪካ የሰብዓዊና ሕዝቦች መብቶች ቻርተር፣ በዓለምአቀፍ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች ቃል ኪዳን (ICCPR) እና በሌሎች አግባብነት ባላቸው የሰብዓዊ መብቶች ሰነዶች የተደነገጉትን በህይወት የመኖር መብቶች እንዲከበሩ ይጠይቃል፤
    • በክልሉ ከዚህ ቀደምም ተመሳሳይ ጥቃቶች በተደጋጋሚ ማጋጠማቸውን ከግምት ውስጥ በማስገባት፥ ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው አካላት ገለልተኛ፣ ፈጣን እና ውጤታማ ምርመራዎችን በማካሄድ ግድያው በተከሰተባቸው ሁኔታዎች ላይ የጥፋተኞችን ተጠያቂነት እንዲያረጋግጡ ያሳስባል፤
    • የሚመለከታቸው የክልሉ መንግሥት አካላት ተጎጂዎች እና ቤተሰቦቻቸው ወደ ቀደመ ህይወታቸው የሚመለሱበትን መንገድ እንዲያመቻቹ ጥሪ ያቀርባል፤
    • ኮሚሽኑ በተለይም መሰረታዊ የሆነው በህይወት የመኖር መብት ይረጋገጥ ዘንድ የሚመለከታቸው የክልሉ የመንግሥት አካላት እንዲሠሩ ያሳስባል።

    በአጠቃላይ ኮሚሽኑ ሁሉም የፖለቲካ ቡድኖች እና ባለድርሻ አካላት ገንቢ ውይይት እንዲያደርጉ እና ከማንኛውም ዓይነት የሁከት ድርጊቶች እንዲታቀቡ ጥሪውን ያቀርባል፤ እንዲሁም በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ሕገ-መንግሥት እና ኢትዮጵያ ፈርማ የተቀበለቻቸውን ሌሎች አግባብነት ያላቸውን የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች ውስጥ የተቀመጡ መብቶችን እና ግዴታዎችን እንዲያከብሩ ኮሚሽኑ እየጠየቀ፥ በቀጣይም ጉዳዩን በንቃት እንደሚከታተለው ይገልፃል።

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን /ኢሰመኮ/

    የሰብዓዊ መብቶች እና ተያያዥ ጉዳዮች ― ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን

    Anonymous
    Inactive

    የሀገር ሰላምና መረጋጋት፣ የዜጎች ሰብዓዊ-መብትና ክብር ከሁሉም ይቀድማል፤ ብሔራዊ መግባባት እና ውይይት በአስቸኳይ!
    ከአብሮነት ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት (አብሮነት) የተሰጠ መግለጫ

    በቅድሚያ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ እንኳን ለ2013 ዓ.ም አዲስ ዓመት በሰላም አደረሳችሁ በማለት መልካም ምኞቱን ይገልፃል። አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የጤና፣ የፍቅር፣ የመተሳሰብ፣ የመከባበር፣ የመግባባት፣ የሀገራችንን ዘርፈ ብዙ ችግሮች በመወያየት፣ በመነጋገርና በእርቅ የምንፈታበት ዘመን እንዲሆንልን ይመኛል።

    አብሮነት ላለፉት 27 ዓመታት በሀገራችን ተንሰራፍቶ የነበረው የህወሓት/ኢህአዴግ አፋኝ አገዛዝ ሥርዓት “የለውጥ ኃይል” በሚባለው የብልጽግና የሪፎርም አካሄድ ከተተካ ባለፍነው ሁለት ዓመት ከግማሽ ያህል ጊዜ የሀገራችንን አጠቃላይ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ሁኔታዎች፥ በአጠቃላይ ወቅታዊ ጉዳዮችን በተለይ በአዲሱ ዓመት መባቻ ገምግሟል።

    በአጠቃላይ የሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ግምገማው አብሮነት የሀገራችን ሕዝብ በሪፎርሙ ጅማሬ የተገባውን ቃል እና የፈነጠቀውን የፖለቲካ ምህዳር መሻሻል ተከትሎ የቋጠረው ተስፋ፣ ያሳደረው እምነት በጊዜ ውስጥ እየሟሸሸ፣ በሀገሪቱ የሚታየው ሁኔታ ከቁጥጥር ውጪ እየሆነ “የሽግግሩ መንግሥት” የሀገሪቱ ፍኖተ-ካርታ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በበዓለ ሲመታቸው ያደረጉት ንግግር ነው ከተባለው ጋር በከፋ ተቃርኖ ውስጥ ገብቷል። የሕግ የበላይነትን አክብሮ ስለማስከበር፣ የዜጎች ሀሳብን በነፃ መግለጽና መቀበል መብት፣ “አሸባሪዎች እኛ ነን” በማለት ይቅርታ ጠይቀው የሽብር ሕጉን ያወገዙበትና በዚህ ሕግ የታሰሩ ፍርደኞች የተፈቱበት፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት የፖለቲካ ፓርቲዎችን ተሳትፎ ያበረታቱበት፣ የሰብዓዊ መብት መከበር ለጥያቄ የሚቀርብ አይሆንም የተባለበት… ሌሎች አዎንታዊ ቃል-ኪዳኖች በፈጣን ሁኔታ ተቀልብሰው [ቀድሞ] ወደ ነበርንበት፣ ሲያልፍም ከድጡ ወደ ማጡ ሊያስብል በሚችል ወደ ከፋ ደረጃ መድረሳችንን ተረድቷል።

    በሀገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ የሚታየው ሁለንተናዊ ምስቅልቅል፣ ያጋጠሙን ፈተናዎች ከውስጥም ከውጪም እየገዘፉ፣ እየሰፉና እየተወሳሰቡ መጥተው ከመንግሥት የቁጥጥር አቅም በላይ በመሆናቸው ችግሮቹን የብልጽግና መንግሥት በተናጠል ሊሸከማቸውም ሆነ ሊያስተካክላቸው ከሚቻለው በላይ ሆነዋል፤ መፍትሄውም አብሮነት ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ሲያቀነቅነው የነበረው “በሁሉን-አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ሕገ-መንግሥታዊና መዋቅራዊ ለውጥ የሚመጣበትን ሥርዓት የመዘርጋት ፖለቲካ መፍትሄ እንጂ በምርጫም ሆነ ሌላ ከብልጽግና ብቻ በሚቀርብ መፍትሄ አያገኝም። ከአማራጭ መፍትሄዎች አንዱ የሽግግርና እርቅ መንግሥት ነው” የሚለው አቋሙ ትክክልና ዛሬ የበለጠ ግልጽ መሆኑን አረጋግጧል።

    በመሆኑም አብሮነት ሰላማዊ ትግሉን አጠናክሮ የመቀጠል ዓላማና ተልዕኮውን አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትና ለዚህም ግንኙነቱን በማጽናት፣ ማጠናከርና በማስፋት ለመሥራት ቃልኪዳኑን አድሷል። ወደ ወቅታዊ ሁኔታዎች ስንገባ አብሮነት የፖለቲካ ፓርቲዎችን እንቅስቃሴና የፖለቲካ እስረኞችን፣ የሀገራችን ቀጣይ ምርጫና የትግራይ ምርጫ፣ በአዲስ አበባ የሚፈጸመውን ዘርፈ ብዙ ሕገ-ወጥ ተግባራት፣ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ እና በሀገራችን በጎርፍና በዜጎች ላይ በሚፈጸም ጥቃት እየደረሰ ያለውን አደጋ፣ የሚመለከቱ ጉዳዮችን ገምግመናል።

    የፖለቲካ ፓርቲዎችን እንቅስቃሴ በሚመለከት፥ ከጅምሩ ታይቶ የነበረው የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሕጋዊና ሰላማዊ መንገድ ተደራጅተው እንዲንቀሳቀሱ የማበረታታት አካሄድ ተቀልብሶ ፓርቲዎች በሕጋዊ መንገድ በነፃነት ተንቀሳቅሰው ብቃት ያላቸው ተፎካካሪ ሆነው ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የሚያደርጉት አስተዋጽኦ በሕግ ማስከበር ስም በገዢው ፓርቲ እንዲገደብ ተደርጓል።

    ለዚህም እንደቅድመ 2010 ከገዢው ፓርቲ በሀሳብ የሚለዩትን፣ የሚተቹና የሚቃወሙትን፣ በገዢ ፓርቲውና መንግሥት ባለሥልጣናት በተጨባጭ የሚፈጸሙ ሕገ-ወጥ ተግባራት እንዲቆሙ፣ እንዲስተካከሉና አጥፊዎች በሕግ እንዲጠየቁ የሚጠይቁትን፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችንና አባላት በፈጠራ ውንጀላ ማሰርና ማሰቃየት፣ ትናንት ከተወገዘው ባልተናነሰ፥ እንዲያውም በከፋ ሁኔታ እየተፈጸሙ ነው። በዚህም ከሰላማዊ ታጋይነታቸው ውጪ የማይታሙት የአብሮነት ከፍተኛ አመራሮች በፈጠራ ውንጀላ ለእሥራትና ሥቃይ ተዳርገዋል።

    በፖለቲካ ሀሳብ ጥራታቸውና ነገሮችን አስቀድመው አርቀው በማስተዋላቸው የሚታወቁት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ያለምንም ማስረጃ ተሰቃይተው በነፃ ተለቀዋል፤ ትናንት የብልጽግና ፓርቲ አባል እንዲሆኑ ተጠይቀው ያልተቀበሉት የሰላማዊ አማራጭ መፍትሄ ሀሳብ አፍላቂ እውቁ ፖለቲከኛ አቶ ልደቱ አያሌው በተጠረጠሩበት ወንጀል ፖሊስ ማስረጃ ሊያቀርብ ባለመቻሉ ነፃ መሆናቸው በፍርድ ቤት ቢረጋገጥም ለህይወታቸው አስጊ የልብ ህመምተኛ በመሆናቸው የቅርብ የሐኪም ክትትል እንደሚያስፈልጋቸው ማስረጃ አቅርበውም የፍትህ ሥርዓቱን ግምት ላይ በጣለ፣ ሰብዓዊነትን በረገጠ አሳፋሪ ሁኔታ ዛሬም በከፍተኛ ስቃይ ውስጥ ይገኛሉ። አዲስ አበባ ውስጥ በማስረጃ አስደግፎ እንዲያቆም ችግሩን አደባባይ ያወጣው፣ በቀዳሚነት የታገለው የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ሊቀ-መንበሩን ጨምሮ ከፍተኛ አመራሮችም የዚሁ ፈጠራ ወንጀል ሰለባ ከመሆን አልፈው በተወገዘው “የፀረ-ሽብር ሕግ” እንዲከሰሱ ተበይኖባቸዋል። በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ከፖለቲካ አመለካከታቸውና አቋማቸው ጋር በተያያዘ ጉዳይ ክስ ሳይመሠረትባቸው፣ በትምህርት ቤቶች ጭምር ታስረው ይገኛሉ የሚሉ መረጃዎች በስፋት ይቀርባሉ።

    አብሮነት ኮሮና ቫይረስ /ኮቪድ-19 ወረርሽኝ ከመከሰቱ አስቀድሞም “የሀገራችን ነባራዊና ወቅታዊ ሁኔታ በሀገራችን ነፃ፣ ዲሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ምርጫ ማካሄድ አያስችልም፤ ምርጫ ቢደረግ የሀገሪቱን ችግሮች ከሚያባብስ በቀር መፍትሄ አይሆንም፤ ያሳለፍናቸው ተደጋጋሚ ምርጫዎች ለውስብስብ ችግራችን መፍትሄ አላመጡም፤ በቀጣይም ምርጫ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ቢደረግ ለውጥ አያመጣም፤ ለሀገራችን ዘላቂና አስተማማኝ መፍትሄው ሕገ-መንግሥታዊና መዋቅራዊ ለውጥ ነው፤ ይህ ፖለቲካዊ መፍትሄ ማለት ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ነው” የሚል ግልጽ አቋም መውሰዱ ይታወቃል። ይህንን አቋም የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መከሰት አግዞት ሀገራዊ ምርጫው እንዲራዘም ተደርጓል። ይሁን እንጂ ብዙ ፓርቲዎች የእኛን የብሔራዊ መግባባት ውይይት መፍትሄ ሀሳብ ቢቀበሉትም ገዢው የብልጽግና ፓርቲ/መንግሥት ባለመቀበላቸው መንግሥት ዕድሜውን በሕገ- መንግሥት ትርጉም ስም ላልተወሰነ ጊዜ ሲያራዝም፣ ህወሓት ደግሞ ሕገ-መንግሥትን ማክበር በሚል የብሔራዊ ምርጫ ቦርድየፌደሬሽን ምክር ቤትም ሆነ አስፈጻሚው እንዳይደረግ ቢወስኑም፣ ቢያሳስቡም፤ እምቢኝ በማለት ምርጫ በክልሉ አካሂዷል። ለዚህ ችግር ምላሽ ይሆናል፣ የውጥረቱን ጊዜ ያሳጥራል በሚል ይመስላል መንግሥት ከሰሞኑ ምርጫው በዚህ ዓመት ይደረጋል ሲል እየሰማን ነው፤ አንዳንድ እንቅስቃሴዎችም እየታዘብን ነው።

    አብሮነት መንግሥት በሕገ- መንግሥት ሥም ዕድሜውን ያለገደብ ማራዘሙም ሆነ ህወሓት /የትግራይ ክልል መንግሥት ያቀረብነውን የብሔራዊ መግባባት ውይይት ቢቀበልም፥ ተግባራዊ ለማድረግ ከመታገል ይልቅ የተናጠል ምርጫ ማድረጉ ትክክል አይደለም፤ የሁለቱም – ብልጽግና እና ህወሓት – የእልህ አካሄድ የሀገሪቱን ፖለቲካ ወደ ከፋ ውጥረት ከማሸጋገር ያለፈ ሰላማዊና ዘላቂ አስተማማኝ መፍትሄ ሊያመጡ አይችሉም ብሎ ያምናል።

    የሀገራችንና የአፍሪካ ዋና ከተማ በሆነችው አዲስ አበባ የሚፈጸሙት ዘርፈ-ብዙ ሕገ-ወጥ ተግባራት ካለፈው ጥፋት በቀጠለ ስህተት እና በዕውቀትና የፖለቲካ ዓላማ መሠረት አድርጎ በተነደፈ ስልት በስፋት እየተካሄደ ነው። በተለይ የመሬት ወረራና የኮንድሚኒየም ቤቶች ዝርፊያ ጎልተው ከወጡና አደባባይ ከዋሉ በርካታ ወራት ተቆጥረዋል። ዛሬ አቤቱታ አቅራቢዎች ቢበራከቱም የመጀመሪያው በማስረጃ የተደገፈ አቤቱታ አቅራቢዎች – የባልደራስ አመራሮች – ዛሬ ወህኒ ተጥለዋል። ችግሩ መፍትሄ አላገኘም፤ ጥያቄዎች አልተመለሱም፤ በቀረቡት ማስረጃዎች መሠረት የከንቲባ ሹም ሽር ከመደረግ ያለፈ አጥፊዎች ለሕግ አልቀረቡም፤ በቀጣይም ይህን ለማስተካከል ቁርጠኝነት ስለመኖሩ አመላካች እርምጃዎች አልታዩም፤ ይልቁንም በነበረው መሠረት ለማስቀጠልና “‹በከተማዋ የባለቤትነት ጥያቄ” ላይ የሚደረገው ሽኩቻ ሲባባስ እንጂ ለማስቆም የሚደረግ ጥረት አልተስተዋለም። በመሆኑም ችግሩ ወደ ከፋ ደረጃ እንዳያድግና በፍጥነት እንዳይስፋፋ፥ ብሎም ጥፋትና ስርቆቱን እንዳያባብስ አብሮነት ሥጋት ገብቶታል። አፋጣኝ ሕጋዊ የእርምት እርምጃ በመውሰድ የሕግ የበላይነት ማስከበር፣ ከተማይቱንም በግልጽ የአስተዳደራዊ ባለቤት ለሆኑት ነዋሪዎቿ ማስረከብ እንደሚያስፈልግ በጽናት ያምናል።

    የኮቪድ-19/ኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በሚመለከት በተለይ ከወረርሽኙ መከሰትጋርተያይዞ ተጥሎ የነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መነሳትን ተከትሎ በሕብረተሰቡ ላይ እየታየ ያለው መዘናጋት አብሮነትን አሳስቦታል። መንግሥት በአዋጁ መነሳት ሕብረተሰቡ እንዳይዘናጋ በቂ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን መሥራት ባለመቻሉ ሕብረተሰቡ ወረርሽኙ የለም የተባለ ይመስል ከፍተኛ መዘናጋት ውስጥ ገብቷል። ሕብረተሰቡ የበሽታው መከላከያ የሆኑትን እርምጃዎች ሁሉ በመተው እራሱን ለበሽታው በሚያጋልጡ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በማስገባቱ በሽታው የበለጠ እንዳይስፋፋ አብሮነትን አስግቶታል። በመሆኑም መንግሥትም ሆነ ሕብረተሰቡ የወረርሽኙን አደገኛነት በመገንዘብ ለበሽታው የሚመጥን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ በአንክሮ ያሳስባል።

    በሀገራችን በጎርፍ እየደረሰ ያለውን አደጋ፣ በተለያዩ የሀገራችን ክልሎች/አካባቢዎች ከመጠን በላይ በጣለው ዝናብ የአዋሽ ወንዝ፣ የኦሞ ወንዝ፣ የባሮ ወንዝ፣ የአባይ ገባር ወንዞች ከመሙላታቸው በተጨማሪ ከግድቦች በተለቀቀ ውሃ ከ580,000 በላይ ዜጎች ለጉዳት ተዳርገዋል፤ ከዚህ ውስጥ ግማሽ ያህሉ ተፈናቅለዋል። በሌላ በኩል በተለያዩ አካባቢዎች (ኦሮሚያ ክልል፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፣ ደቡብ ክልል/ኮንሶ…) በዜጎች ላይ ጥቃት እየተፈጸመ ነው፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በአሰቃቂ መንገድ እየተገደሉና በሺዎች ህይወታቸውን ለማትረፍ ከቀዬአቸው እየተፈናቀሉ ነው። በመንግሥት በኩል ለመከላከል በቂ ዝግጅት፣ አደጋው ከደረሰም በኋላ በቂ ክትትልና ድጋፍ ያለመደረጉን፣ እንዲሁም በቀጣይ ሊደርሱ ለሚችሉ አደጋዎች በቂ የመከላከል ዝግጅት እየተደረገ ያለመሆኑን፣ ከአካባቢው የሚደርሱን መረጃዎች ያመለክታሉ። በሌላ በኩል የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በዚህ ልክ በሀገራችን በደረሰው አደጋና ጉዳት ምንም ሳይሉ በጎረቤት ሀገር ሱዳን በደረሰው ሀዘናቸውን ገልጸዋል፣ እንዳይቀጥልም ከጎናቸው እንደሚቆሙ ቃል ገብተዋል። ዜጎች በማያውቁት በተፈጸመባቸው ጥቃት ለሞት ተዳርገዋል፤ እየተዳረጉም ነው። በተረፉት ዜጎቻችን የደረሰው አደጋን ተከትሎ የሚመጣው የጤናና ምግብ ችግር፣ እንዲሁም ሊደርስ የሚችለው አደጋ በአንድ በኩል፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ዝምታና “የራሷ እያረረባት፣ የሰው ታማስላለች” አካሄድ በሌላው፣ በእጅጉ ያሳስበናል። ስለዚህ መንግሥት በራሱ እና ሕዝቡንና ዓለምአቀፍ ማኅበረሰቡን በማስተባበር በአፋጣኝ እንዲደርስላቸው ያስፈልጋል።

    በመጨረሻ ገዢው ፓርቲ /መንግሥት በአፈናና የሸፍጥ ፖለቲካ በተመሳሳይ መንገድ እየተጓዘ በፕሮፖጋንዳና ባዶ የተስፋ ቃላት ጋጋታ ፣ የተለየ ውጤትም ሆነ ችግሮቻችን መፍታት እንደማይችል በተደጋጋሚ ተመልክተናል። ስለዚህ አብሮነት ችግሮቻችንን በአስተማማኝና ዘላቂ መንገድ ለመፍታት፣ ሃቀኛ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ለነገ የማይባል ተግባር እንደሆነ ያምናል፤ ገዢው ፓርቲ ለዚህ ያለውን ከፍተኛ ኃላፊነት እንዲወጣ በአጽንኦት ጥሪ ያደርጋል።

    ለዚህ እንዲረዳም፡-

    1ኛ/ በፖለቲካ አመለካከታቸው ከገዢው ፓርቲ በመለየታቸውና በሀገሪቱ ለሚታዩት ችግሮችና በሕዝብና ሀገር ሀብት ላይ እየደረሰ ያለውን በደል በማስረጃ አስደግፈው ተቃውሞ በማሰማታቸውና ጥያቄ በማቅረባቸው ብቻ የታሰሩ የፖለቲካና የኅሊና እስረኞች በአስቸኳይ እንዲፈቱ፤

    2ኛ/ ለ27 ዓመታት አንድ ሆነው ሕዝባችን ሲያሰቃዩ የነበሩትና ዛሬ በሥልጣን ጥያቄና ያለፈውን በማስቀጠል ስልት ላይ ባለመስማማታቸው በተለያዩት በህወሓት እና በብልጽግና ፓርቲዎች መካካል ትናንትም ሆነ ዛሬ በሚደፈጥጡት ሕገ-መንግሥትና አምስት ጊዜ ባጭበረበሩት ምርጫ ሥም የሚታየው መካረርና ፍጥጫ በአስቸኳይ ተገትቶ፥ ለብሔራዊ መግባባት ውይይት ችግሮቻቸው እንዲፈታ የፖለቲካ ቁርጠኝነታቸውን እንዲያረጋግጡ፤

    3ኛ/ የሀገራችን ችግሮች ምንጭ ምርጫ ባለመሆኑ፥ በምርጫም የሚፈቱ ያለመሆናቸው ባለፉት አምስት ምርጫዎች በመረጋገጡ፥ ለሕገ-መንግሥታዊና መዋቅራዊ የፖለቲካ መፍትሄ ምርጫ ለማድረግ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችም ሆነ እንዲደረግ የሚደረጉ ግፊቶች በአስቸኳይ ቆመው ሁሉንም ወገኖች የሚያሳትፍ የውይይት መድረክ እንዲመቻች ለዚህም ሁሉም ዜጋ አስፈላጊውን ተፅዕኖ በመንግሥት ላይ እንዲያሳርፍ፤

    4ኛ/ መንግሥትም ሆነ ሕብረተሰቡ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን በመከላከል ረገድ እያሳዩ ያሉትን ቸልተኝነት በማቆም አስፈላጊውን የመከላከል ጥንቃቄና የመለየት ምርመራ እንዲያደርጉ፣ ለተጠቂዎች አገልግሎት ማቅረቡንና የግንዛቤ ማሳደግ ተግባራት በስፋት እንዲያከናውኑ፤

    5ኛ/ በሀገራችን በተፈጥሮና ሰው-ሠራሽ ምክንያት ጎርፍ እያደረሰ ላለው ከፍተኛ አደጋ መንግሥት “የራሷ እያረረባት የሰው ታማስላለች” ከሚያስብል አካሄድ ወጥቶ በዜጎች ህይወት፣ ሥቃይ፣ የንብረት ውድመትና ቀጣይ ህይወት ላይ ትኩረት እንዲያደርግ፤

    6ኛ/ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች እንደየቱም ክልል ነዋሪ የከተማቸው አስተዳዳራዊ ባለቤት መሆናቸው እንዲረጋገጥ፣ በከተማዋ የባለቤትነት መብት የሚደረገው በብልጽግና ውስጥ ጭምር የሚደረገው ሽኩቻ እንዲቆም፣ የተበዘበዘውና የተዘረፈው የከተማዋ ሀብት በሕግ ተመልሶ ለከተማዋ ልማት እንዲውል፣ አጥፊዎች ለሕግ እንዲቀርቡ፣ እንዲደረግ፤

    7ኛ/ በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች በዜጎች ላይ የደረሰው ጥቃት በገለልተኛ ወገን በአስቸኳይ እንዲጣራና ተገቢው ካሳ እንዲደረግላቸው፥ እንዲሁም አጥቂዎችና ተባባሪዎቻቸው በሕግ እንዲጠየቁ እንዲደረግ፣ ለጥቃቱ ሰለባዎች አስፈላጊው የዕለት ደራሽ ዕርዳታና የማቋቋሚያ ድጋፍ በአስቸኳይ እንዲደርሳቸው፤ ለዚህ ተፈጻሚነትም የፖለቲካ ፓርቲዎች ጅምሩ የብሔራዊ መግባባት ውይይት እንዳይነጠቅና በገዢው ፓርቲ እጅ እንዳይወድቅ፣ ከላይ ያቀረብናቸው እንዲፈጸሙ በልዩነታችን ውስጥ በሀገራዊ ጉዳዮች በቅድሚያ በሕግ የበላይነትን በማክበርና ማስከበር ለሰላምና መረጋጋት፣ ለሰብዓዊ መብት መከበር ተባብረን እንድንቆም ጥሪያችንን እናቀርባለን፤ ለተግባራዊነቱ ያለንን ቁርጠኝነት እናረጋግጣለን።

    ከአሳታፊ ሁሉን አቀፍ ሃቀኛ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ውጪ የቱም አንድ ፓርቲና ከብሔራዊ መግባባት ውይይት በፊት የሚደረግ የይስሙላ ምርጫ ለሀገራችን ችግሮች ዘላቂና አስተማማኝ መፍትሄ አያመጣም።

    ከሁሉም በፊት መንግሥት የሕግ የበላይነት በማክበርና በማስከበር በሃቀኛ ሕዝባዊ ተሳትፎ የሀገራችን ሰላምና መረጋጋት፣ የዜጎችን የመኖር ሰብዓዊ መብት የማረጋገጥ ኃላፊነቱን ይወጣ፤ ከሥልጣኑ ይልቅ ለሀገርና ሕዝብ ጉዳይ ቅድሚያ ይስጥ።

    አብሮነት ለኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት (አብሮነት)
    መስከረም 07 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ

    ብሔራዊ መግባባት እና ውይይት

    Anonymous
    Inactive

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ሆይ! እባክዎ፥ የሕዝብዎን የማመዛዘን አቅም አይናቁብን፤ የሚነግሩን አይመጥነንም
    አቶ ግርማ በቀለ – የኅብር ኢትዮጵያ ሊቀመንበርና የአብሮነት አመራር አባል

    አምና በተከልነው ችግኝ ሐረማያ ሐይቅ ዳግም ነፍስ ዘራ፤ አቢያታ ሐይቅ አንሰራራ፤…

    ሕዝብ የመንግሥትን ጥሪ (አምስት ቢሊዮን ችግኝ ተከላ፣ ሕዳሴ ግድብ፣ ማዕድ ማጋራት፣…) ሁሉ ተቀብሎ ከጎናችን በመቆሙ ያሰብነው ሁሉ ካቀድነው በላይ ተሳካ።…

    በዚህ ደረጃ ድጋፍ ያገኘ የአፍሪካም ሆነ የኢትዮጵያ መንግሥት አላውቅም።…

    የትግራይ ምርጫ የጨረቃ ምርጫ ነው፤ ከጨረቃ ቤት ጋር ይመሳሰላል፤ ሁለቱም ተኝተው አያድሩም።…

    እኔ ግን ከፖለቲካውም፣ ከማሳመኛ ፕሮፖጋንዳውም ከዚያ ሁሉ ንግግር የገረመኝን፥ በትምህርትም በተግባርም ጠንቅቄ የማውቀውን አንስቼ ትዝብቴን ላቅርብ። ስለ ሐረማያ ሐይቅ እንደገና ውሃመያዝ፣ የሞተው መዳን።

    የደረቀ ሐይቅን አምና በተተከለ ችግኝ ማዳን መቻሉን እናቆይና፥ በቅድሚያ መሠረታዊ ጥያቄዎችን እናንሳ። እውነት አምስት ቢሊዮን ችግኝ በአንድ ዓመት ማዘጋጀት ይቻላል? በስንት የችግኝ ማፊያ ጣቢያ? የዛፍ ችግኝ ወይስ የሽንኩርት፣ የቲማቲም፣ የቀይሥር፣… ችግኝ? አምስት ቢሊዮን የዛፍ ችግኝ ለማዘጋጀት ምን ያህል ጊዜ (የችግኙ ዘር ከተዘራበት ወደ መደበኛ ማሳ እስከሚዛወርበት)፣ ጉልበት (በችግኝ ማፊያ ጣቢያ ከተሰማራው በተጨማሪ፥ አምስት ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል የተሰማራው 25 ሚሊየን ሕዝብ ከሆነ እያንዳንዳችን 20 ችግኝ ተክለናል ማለት ነው)፣ ቁሳቁስ (ቦታ፣ ዘር፣ ፍግ/ኮምፖስት/፣ ፕላስቲክ፣…) ያስፈልጋል? እንደገና ይህን ሁሉ እንለፈውና፥ ሲጀመር ኢትዮጵያዊያን ዛፍ የተከልነው “ለእርሳቸው ያለንን ድጋፍ ለመግለጽ” መሆኑን መግለጽስ ለቀጣዩ ምን መልዕክት ያስተላልፋል? እኔ በግቢዬም፣ በአደባባይም የተከልኩት የፕሮግራሙን ዘላቂ ጥቅም በማመን እንጂ፥ እርስዎን ስለደገፍኩኝ አለመሆኑን ግልጽ ማድረግ እወዳለሁ።

    ጥያቄዬ አምና የተተከለ ችግኝ በዓመቱ የመሬትን የውሃ የመያዝ አቅም አሻሽሎ፣ የዛፍን ውሃ ትነት ምጣኔን ለውጦ፣ ጎርፍን አስቀርቶ፣ የአፈር ርጥበትን ጨምሮ፣… ውሃ አጠራቅሞ የደረቀን ሐይቅ ተመልሶ ነፍስ እንዲዘራ የማስቻል አቅም ያጎለብታል ወይስ እራሱን ከችግኝ ማፊያ ጣቢያው ከሚለየው አፈርና አየር ንብረት ጋር አዋዶና አዛምዶ፣ የቀረበትን እንክብካቤ አካክሶ ችግኙ መጽደቁ የሚመዘንበት ጊዜ ነው? የሚለው ነው። መልሱ በአጭሩ ችግኝ በተተከለ በዓመቱ ሐይቅ ሲያድን በዓለም ላይ ታይቶም ተሰምቶም አይታወቅም። መነሻዬንና እውነታውን ትንሽ ላብራራ።

    “ዛፍ በመትከላችን ሐረማያ ሐይቅ ዳግም ህይወት ዘራ፣ አቢያታ ሐይቅ አንሰራራ” ማለትዎ ሥልጣን የጉልበትም የዕውቀትም ምንጭ ነውና ዝም ብላችሁ ስሙ፤ ጸጥ ረጭ ብላችሁ አድምጡ፤ አትጠይቁ ካልተባለ በቀር፥ ለእንደ’ኔ ዓይነቱ የመጀመሪያ ዲግሪውን ሐረማያ ሐይቅ ዳር በግብርና /ዕጽዋት ሳይንስ ላገኘ (ፎረስትሪ /forestry/፣ አግሮፎረስትሪ /agroforestry/፣ ሲሊቪካልቸር /silviculture/፣ የዕጽዋትን ሥርዓተ-ህይወት በአጠቃላይ፣ የዛፍ ተክሎች ከችግኝነት አስከ ዛፍነት ያላቸውን ፍላጎትና ባህሪይ በተለይ፣…) ኮርሶች እንደተማረ፣ ከዚያም ከ12 ዓመታት በላይ በሀገሪቱ የግብርና ልማት ፕሮጀክት መሥሪያ ቤት በሰብል ምርት የፕሮጀክት ኤክስፐርትነት (የአፈርና ውሃ ጥበቃን እና የፕሮጀክት በአካባቢ/environment/ ላይ ያለውን ተጽዕኖ ትንተና ጨምሮ) ላገለገለ ሰው፣ የጣና በለስ ሰፈራ ፕሮግራም ላይ የአግሮ ኢንዱስትሪ (የዘር ማዘጋጃ ፕላንት /ፋብሪካና የዘር ስርጭት አመራርና ከዛፍ ችግኝ ማፊያና የመስኖ ግብርና ምርምር ጋር በቅርበት የሠራሁትን ጨምሮ) ክፍል እንደመራ፣ በፕሮጀክትና ልማት አመራር በርካታ ሀገራዊና ዓለምአቀፍ ሥልጠናዎች (የአካባቢ ተጽዕኖ ትንተና ጨምሮ) እንደተሳተፈና የተመሰከረለት የልማት አመራር አማካሪ ሆኖ 15 ዓመታት እንዳገለገለ፣ ይህን መቀበል እጅግ አስቸጋሪ ብቻ ሳይሆን ጠቅላይ ሚኒስትራችንን በእጅጉ እንድታዘብ አድርጎኛል። ይህን የሰማ ዓለም ምን ይለን ይሆን? ብዬ ሳስብ ስለእርስዎ በጣም፣ እጅግ በጣም አፍሬኣለሁ። ገበሬውማ ከልጅነት እስከ ዕውቀት፣ ከጥንት እስከዛሬ የህይወቱ መሠረት ነውና የሚኖረውን ትዝብት አልነግርዎትም።

    ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር፥ እባክዎ! የሕዝብዎን የማመዛዘን አቅም አይናቁብን፤ የሚነግሩን አይመጥነንም። በማይጨበጥና በማይመጥነን ፕሮፖጋንዳ ተስፋችንን አያድርቁብን። ስለሀገራችን መጻኢ ዕድልና የገጠማትን የህልውና አደጋ መክተንና ቀልብሰን መጪውን ጊዜ በመተማመንና በመከባበር፣ ደንቃራዎችን ወደ መልካም ዕድል ለውጠን ተያይዘን ለመሻገር የሰነቅነውን ተስፋና የምናደርገውን ጥረት አያምክኑት። እባክዎ፥ ፈጣሪ በማያልቀው ይቅርባይነቱ በቸርነቱ የዘረጋልንን የምኅረት እጅ የርስዎ ድጋፍ ውጤት አድርገው “በቃችሁ” ብሎ ያዞረልንን ፊት እንዲያዞርብን አይትጉ፤ ቆም ብለው፣ ደግመው ያስቡ። አበቃሁ።

    አቶ ግርማ በቀለ /Girma Bekele/

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    አቶ ግርማ በቀለ ― ጠ/ሚ ዐቢይ ሆይ! እባክዎ፥ የሕዝብዎን የማመዛዘን አቅም አይናቁብን

Viewing 15 results - 151 through 165 (of 730 total)